Telegram Web Link
«በሕጋዊ መንገድ ሰው መግደያ ዘዴ» - ሥጦታ?!

* * * *
ከጥቂት ቀናት በፊት ጓደኛዬ ቤት ሄጄ በካርቶን የታሸገ ኩኪስ ውሰድ አለኝ።
«ለምንድነው የምትሰጠኝ?» አልኩት። ተግባብተናል፣ በነጋታው ለሳምንት ከከተማ ይወጣል። «ስለማልኖር ይበላሻል» አለና ሐቋን ተናገረ። ሰማንያ ምናምኑም ብሔሮች በየቋንቋቸው "የሥጦታ ፈረስ ጥርሱ አይታይም" እያሉ ነግረው ነው ያሳደጉን። ለምን? እንዴት? ምናምን አንልም፣ መቀበል አለብን ነው መሠለኝ 路♂ ባለፈው አንድ ሀኪም ወዳጄ ነፃ ምርመራ ላርግልህ ሲለኝ ያወራነው ነገር ነው ይሄንን ያስታወሰኝ። እምቢ አልኩ። ለምን? እኔንጃ፣ "አለብህ" የሚለኝን ነገር እያሰብኩ መሰለኝ። ናሲም ታለብ የተባለው ፀሀፊ "በሕጋዊ መንገድ ሰው መግደያ ዘዴ አለ!" ይላል። ይሄን ዘዴው ሲያብራራው እንዲህ ይላል፣ በግርድፉ . . . የሆነን ሰው ሞት ማፋጠን ከፈለግክ የግል ዶክተር ስጠው። መጥፎ ዶክተር ስጠው እያልኩህ አይደለም፣ እሱ የፈለገውን ዶክተር ይምረጥ፤ አንተ ገንዘቡን ክፈልለት። የትኛውም ዶክተር ይሆናል። ምናልባት የቱንም ሕግ ሳትጥስ ግድያ መፈፀም የምትችለው በዚህ መልኩ ነው። ስለጤናህ ዳታ/መረጃ ሲኖርህ ሕክምና ትጨምራለህ፣ መታከም አለብኝ ትላለህ። እንደ neurotic ሰው ያደርግሀል። የግል ዶክተርህም ምንም ሳይሰራ ደሞዝ እንደተቀበለ እንዲሰማው አይፈልግም። ስለዚህ የሚያይብህን ጥቃቅንና tolerable ሕመሞች ሁሉ ይነግርሀል። አንተም የሆነ ህመም እንዳለብህ እያወቅክ ዝም አትልም። መድሀኒት ትፈልጋለህ። (የማይክል ጃክሰን ዶክተር በተመሳሳይ ጥፋት መከሰሱን ይጠቅሳል) በጣም የተራቀቀ ሕክምና ማግኘት የሚችሉ ሀብታሞችና የሀገር መሪዎች ለምን እንደተራው ሰው በቀላሉ እንደሚሞቱ አስበህ ታውቃለህ? ከሁኔታቸው እንደምናየው ከበዛ የሕክምና ድጋፍና ከበዛ የመድሀኒት አጠቃቀም ነው የሚሆነው።' የተራቀቀ የዳታ መሰብሰቢያ ክፍል ያላቸው ፖሊሲ አርቃቂዎቻችንም ተመሳሳይ ችግር ይፈጥራሉ ይላል ታለብ፤ የሚሰሟትን ድምፅ እንደ መረጃ እየቆጠሩ ያልተገባ ምላሽ በመስጠት ቀውስ ውስጥ ይከቱናል። የዳታ ዘመን ነው፣ በብዛት ይገኛል። ነገር ግን ዳታ ሲበዛ መርዛማ መሆኑ አይወራም። ዳታ ላይ ያለን አተያይ ወሳኝ ነው ይለናል። ዳታዎችን በየቀኑ ስናይ የሚያስደነግጠን፣ ለምላሽና ለውሳኔ የሚያስነሳን ነገር ብዙ ነው። ይሄንን ተመሳሳይ ዳታ ተጠራቅሞ በዓመት አንዴ ብናይ ግን ተመሳሳይ ኹኔታ ውስጥ አንገኝም። የፌስቡክ አጀንዳ፣ የመንግሥት አማካሪዎች፣ የመንግሥት ውሳኔዎች ወዘተ በጩኸት ላይ የተመሰረቱ ናቸው። ዛሬ የሆነ ነገር ተፈፀመ ይባላል። ያቺን የዕለት ዜና ወይም ዳታ ይዘን እርምጃ እንዲወሰድ፣ የሆነ ነገር እንዲደረግ እንጮሀለን። ነገ ሌላ ነገር እንሰማለን፣ የዚያኔ ደግሞ ሌላ እርምጃ እንዲወሰድ እንጮሃለን። ጩኸት በጩኸት ነው። ቆም ብለን ባለፈው ዓመት ወይ ሁለት ዓመት የጮህንባቸውን አንድ ሺህ አጀንዳዎች ስናስብ ግን አብዛኞቹን ረስተናቸዋል። ወጥ በሆነ መልኩ አድጓል፣ አሽቆልቁሏል፣ እስካሁን አለ ወዘተ ብለን ልንናገርላቸው የምንችላቸው ነገሮች በጣም ጥቂት ናቸው። ነገር ግን ሺሆቹንም ጩኸቶች ሰምቶ በረባ ባልረባው የፖሊሲ ሀሳብ ያቀረበ አማካሪና ውሳኔ ሰጪም እንዳለ ከተፈጠሩትና ከሆኑት ነገሮች መረዳት እንችላለን። ይህ ኹኔታ ከሥነ-ሕይወታዊ (ባዮሎጂካል) እኛነታችን ጋር ማያያዝ እንችላለን። ብዙ መረጃ ብዙ ጭንቀት ውስጥ ይከታል። የቅርብ ጊዜ የሕክምና ጥናቶች የፆምን የጤና ጥቅም በሰፊው ሲገልፁ አይተናል። ሆርሞኖች በብዛት የሚመነጩት ምግብ ሲወሰድ ነው። ሆርሞኖች ወደተለያዩ የሰውነታችን ሥርዓቶች መረጃ ያደርሳሉ፣ ሲበዙ ሰውነታችንን ግራ ያጋቡታል። ብዙ ዜና እኛን ግራ እንደሚያጋባን ነው ብዙ ሆርሞንም ሰውነታችንን ግራ የማጋባት ሥራ ይሰራል። ሚዲያውም ያበደ ነው። የጠራና የነጠረ ጠቃሚ መረጃ ሳይሆን በየቀኑ ሰዓታቸውን እና ገፃቸውን የሚሞላ ጩኸት ነው የሚለቁብን። በየቀኑ በሀገራችን 1000 ሰዎች ተገቢውን ቀላል ሕክምና ማግኘት ባለመቻላቸው፣ ወይም በረሃብ፣ ወይም ደግሞ በሌላ መንግሥትና ሕዝቡ ትንሽ ጥረት አድርገው ሊያስቀሯቸው በሚችሏቸው ተራ ምክንያቶች ይሞታሉ እንበል። ሚዲያዎቻችን የሚነግሩን ግን ስለ አንድ ሺሁ ሞት ሳይሆን ስለ ሁለት ለየት ባለ ሁኔታ ስለሞቱ ወይም ስለተገደሉ ሰዎች ነው። የየዕለት ጩኸት ነው የሚሰጡን። የሚያስደነግጡንና በቀላሉ ኡኡ የሚያስብሉንን ሁለት አሰቃቂ ግድያዎች ወይም ኹነቶች ነው የሚተርኩልን።
* * * *

አንድ የሕግ ድራማ/ፊልም ላይ ያየሁት ታሪክ ጭብጥ ከዚሁ ይያያዛል፣ ትልልቆቹን የመድኃኒት አምራች ኩባንያዎች "ሕመም ሻጮች" ናቸው ይላቸዋል። የገፀባህሪውን አገላለፅ ወደፌስቡክ ከሞላ ጎደል ወደፌስቡክ እንዲህ ላውርደው . . .
«እረፍት አልባ የእግር ልክፍት» ሲባል ሰምታችሁ ታውቃላችሁ? ቁጭ ብላችሁ
ወይም ተኝታችሁ በእንቅልፍ ልባችሁ እግራችሁን የሚያስነቀንቅ ልክፍት ነው። ከእንቅልፍ አያነቃም ወይም አያደክምም፣ ጉዳትም የለውም። እንደችግር አይታችሁትም አታውቁ ይሆናል። ነገር ግን የመድሃኒት አምራች ኩባንያዎች በጣም ከባድ ህመም እንደሆነ ይነግሯችኋል። መድኃኒት ሰርተውለታል። ችግሩ ካለባችሁ እሱን መውሰድ አለባችሁ። ስለዚህ ልክፍት ሰምታችሁ የማታውቁ ከሆነ ምናልባት «የትኩረት ማጣት ቀውስ» ችግር ሰለባ ሆናችኋል። የትኩረት ማጣት ቀውስ አሳሳቢ ችግር ቢሆንም ለሱም መድኃኒት ሰርተውለታል። መውሰድ አለባችሁ። «feeling depressed» ብላችሁ ትለጥፋላችሁ። ምናልባት በዚህ ሌሊት ይሄንን ረዘም ያለ ጽሁፍ እያነበባችሁ ነው። የእንቅልፍ ማጣት ችግር አለባችሁ
ማለት ነው። ምናልባት ያልተኛችሁት ቀን የበላችሁት ምግብ ሆዳችሁን አሳምሟችሁ ይሆናል። የሆድ ቁርጠት መድሃኒት አለላችሁ። እዚህ ፌስቡክ ላይ የተለያየ ደፋርና ገራሚ ጽሁፎች ፖስት ታደርጋላችሁ፣ ነገር ግን ከሰው ስትቀላቀሉ የሚያስደነግጥ፣ የሚያስሸሽ የsocial anxiety ችግር አለባችሁ። መድሀኒት አለው። በአጠቃላይ ሁላችሁም የማታውቁት ብዙ ዓይነት ሕመም አለባችሁ! አያሳስብም
እንደዕድል ሆኖ ለሁሉም ሕመሞች መድሐኒት አለ!! መውሰድ አለባችሁ!!
* * * *
ሁላችንም የምናውቀውና የማናውቀው በሽታ አለብን። ፌስቡክ የሚባል ነፃ ሕክምና ስናገኝ ለሁሉም ሕመማችን መፍትሔ ለማግኘት የተለያዩ ነገሮች
እናደርጋለን። ያደረግናቸው ነገሮች፣ የወሰድናቸው መድኃኒቶች ደግሞ ብዙ ነገር አሳጥተውናል። ጭንቀት፣ ጥል፣ መከፋት፣ ማፈር፣ ጓደኛ ማጣት፣ መጥላት/ መጠላት፣ ወዘተ አትርፎልናል።
ደግሞ . . . ለሁሉም በሽታዎቻችን መድኃኒት አለ። ፖለቲከኞችና አክቲቪስቶች መድኃኒቱን ይሸጡልናል። ችግሮቻችንን ይነግሩናል። ነገር ግን ለሚነግሩን ችግራችን «መፍትሔ ነው» ብለው ያሰቡትና ያዘጋጁት መድሃኒት መኖሩን ሲያውቁ ብቻ ነው ችግሮቻችንን የሚነግሩን። እስከዚያው ድረስ ትክክለኛ
ችግራችንን ቢያዩም አይነግሩንም። መፍትሔ ብለው የሚሸጡልንን መድሀኒት
አላዘጋጁማ። እሱ ደግሞ አያዋጣም።
ዘፋኙ እንዲህ ይላል .

«ላንቺም ለእኔም ከቶ ማይበጁ ጥጥ ሸምነው ጋቢ እየቋጩ
ያሞጋገሱሽ ምን እንኳን ቢመስልም ነጠላቸው ብርድ አያስጥልም።
እንኳንስ ለኛ ላገሩ ሊያውቁ
ለራሳቸው ከቶ የት አወቁ
ባንቺ ዝምታ ጎን እየታከኩ
ጎጇችንን ስሩን ነካኩ
እናትዬ ጥንስሱን እይው እታለሜ ድግሱን ለይው..
-
የተሰጣችሁን ሁሉ ያለጥያቄ የማትቀበሉ፣ ድግሱን የምትለዩ ያድርጋችሁ!

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Gemechu merara fana
ተ/ፕሮፌሰር ተስፋዬ ገሠሠ እንዴት እንዳዋረደኝ......

እነሆ ዩኒቨርስቲ ለመግባት ወደ አዲስ አበባ የመሄዴ ነገር እውነት ሆነ፡፡
(በጎርኪ ስታይል በመምጣቴ ይቅርታ) በመጨረሻው ምሽት ዘመድ
አዝማድ ተሰብስቦ ምን መማር
እንዳለብኝ ሃሳብ ያዋጡ ጀመር፡፡
ሸምገል ያሉት ዘመዳችን ዝንብ መከላከያ ጭራቸውን
በኮንዳክተር ሙድ ግራ ቀኝ ካወናጨፉ በኋላ እንዲህ አሉ፡፡
“… እንግዲህ አገር ቆርጠህ መጓዝህ ካልቀረ ደህና ነገር ተምረህ ነው
መምጣት!! ሲሆን ሲሆን ህክምና ብትገባ ደግ ነው፡፡ ወባ እንኳ ካቅሟ
ሰው ሆና ስንቱን ስትረፈርፍ ታያት
የለም? ይህ ሁሉ አኪም በመጥፋቱ ነው፡፡ ትምርቱን ስትጨርስ የት
እቀጠራለሁ ብለህ ከቶም እንዳትሰጋ! አንተ ተማር እንጂ ሃገሬውን
አስተባብረን መተዳደሪያህን አንድ ጋሻ ጥቅጥቅ ያለ ለም መሬት፣
እየተፈራረቁ የሚያርሱ ቀንጃዎች፣ የመጀመሪያ እህል ዘር ከሚስትና ከጎጆ
ጋር እናሰጥሃለን..” ሲሉ ቀሰቀሱ፡፡
አብዛኛው ሰው በጭብጨባ ደስታውን
ገለጠ፡፡
ሌላው የቅርብ ዘመዳችን እጁን መዘዘና አደግድጎ ሃሳብ ሰጠ፡፡
“… እህህህ እንግዲህ ምክክርም አይደል የያዝነው? ምንም እንኳ አሁን
አባታችን በሰጡት አሳብ ላይ ሌላ መደመር ከድፍረት የሚቆጠር ቢሆንም
ዘመድ ተብለን መሰየማችን ቅሉ አስተያየት እንድንሰጥ ያስገድደናል፡፡
እሳቸው እንዳሉት እክምና ብትገባ በጎ ነው፡፡ እሱ አልሆን ታለ ግን
እንደምንም ብለህ መንዲስ ብቶን ይሻላል ባይ ነኝ፡፡ እንግዲህ መንዲስ
ሲኮን መንገድ ትቀይሳለህ፣ እስባልት ትዘረጋለህ፣ሌላው ቢቀር እህች
ጎረቤታችን ያለችው ቡካይ ጅረት እንኳ ልብ በቅቷት ስንቱን እንደ ግንድ
እያየን እያንከባለለች ወሰደችው? ልብ በል እንግዲህ በበጋኮ ዘለን
የምንሻገራት ቦይ ናት ክረምት ሲመጣ ወንዝ ነኝ ብላ ሰውን ያህል ነገር
እያንዘፋዘፈች የምትወስድ፡፡ ይሄ ሁሉ ለምን ሆነ ታልክ ዛዲያ ድልድይ
ስላልተሰራላት ነው፡፡ አቻምና እንኳ እኛ ና ባሻገር ያሉ መንደሬዎች
ተረባርበን ወደል የሚያህል ግንድ እየቆረጥን ድልድይ አጋድመን ነበር፡፡
ውሃ በላውና በስብሶ የአያ ደባልቄን ልጅ እሻገራለሁ ሲል ተጠርምሶ አብሮ
ወሰደው፡፡ እና እንግዲህ ላሳጥረውና መንዲስ ኮነህ
ከመጣህ እኔ በበኩሌ ተመሬቴ የማርሰውን የእኩል ሰጥሃለሁ፡፡..” አለና
ተቀመጠ፡፡
ደማቅ ጭብጨባ ተከተለው፡፡ በስተመጨረሻ ተነሳችና
“… እኔ እንኳ ጠበቃ ቢሆን እመርጣለሁ፡፡ ወገን እሰቡ እንጂ! አዳሜ
ድንበራችንን እየገፋ የሚያርሰው፣ ምሎ ተገዝቶ በታቦት ሸምጋይ ገንዘብ
ተተበደረን በኋላ ሽምጥጥ
የሚያደርገን፣ ወረዳ ሹመኞች ሳይቀሩ ግብር እያሉ አጠፌታ የሚያስከፍሉነ
ለምን ነው? የመንግስትን ደንብ አያውቁም ብለው አይደለም? እኔ
በበኩሌ የተበላሁ ገንዘብ አስር ልጅ
አሞናሙኖ ያስድረኝ ነበር፡፡ አሁንም የሆነ እንደ ሆነ ነገረ ፈጅ ሁኖ ሲሆን
እስከዛሬ የተቦጠቦጥነውን እንዲያስመልስልን ያም ባይሆን ለወደፊቱ
እንዲከላከልልን ነው፡፡..” ብላ
ቦታዋ ተመለሰች፡፡
የሚገርመው ግን አንድም ቦተ ስለኔ አሳብ የጠየቀኝ ሰው የለም፡፡ ግራ
ቀኙን እንደ ፍርድ ቤት ሰምቼ ገባሁና ተኛሁ፡፡
በጥቂት ቀን አዲሳባ ገባሁና ትያትር መማር ጀመርኩ፡፡ ይህንን ከ4 ዐመት
ህጻን ወንድሜ በቀር ለማንም አልተናገርኩም፡፡ ለሱም ልነግረው የቻልኩት
ገመና ድራማ በሚተላለፍበት ግዝ ሹገር ዳዲ ሆነው ሚተውኑት ጋሽ
ተስፋየን ስለወደዳቸው መምህሬ ናቸው ብየ ስለ
ነገርኩት ነው፡፡ በተረፈ ሶስት አመት ሙሉ በጓጉንቸር ቁልፍ እንደከረቸሙት
የከርቸሌ በር ተጠርቅሜ ኖርኩ፡፡
በየአጋጣሚው ምን እንደምማር ሲጠይቁኝ በስልት እያፈገፈግኩ
አመልጣቸዋለሁ፡፡ ከኔ አልመጠ ቢላቸው ዘመዶቼ ራሳቸው መላ ይመቱ
ጀመር፡፡ ህክምና የተመኙልኝ አዛውንት
“..ይህ ልጅ እክምናውን ነው የመረጠ፡፡ ማስረጃውም….” አሉና
ከብብታቸው አንድ ፎቶ መጅርጠው አወጡ ፎቶው እኔ ነጭ ጋውን ለብሼ
የተነሳሁት ነበር፡፡ እንዴት እሳቸው እጅ
ሊገባ እንደቻለ ደነቀኝ እንጂ ፎቶው ለአንድ ኮርስ ማሟያ የሞሌርን “
የፌዝ ዶክተር” የተሰኘ ተውኔት ስተውን የተነሳሁት ነበር፡፡ እንዲህ እንዲህ
እያልኩኝ መመረቂያዬ ተደገሰ፡፡
በአጋጣሚ ዘመድ ሁሉ ተሰብስቦ ምርቃቴን ሲያከብር ተስፋየ ገሰሰ በቲቪ
ብቅ አሉ “…የጓዴ መምህር!!” አለና ህጻኑ ወንድሜ ጮኸ! ግራ ቀኝ
ሲያፋጥጡኝ ትያትር መማሬን ነገርኳቸው፡፡ አባቴ ክፉኛ አዘነ፡፡
“… ምነው ልጄ አዲሳባ እሚያህል አገር ድረስ ሄደህ ቅሌት ተምረህ
ትመጣ?! አይይይ አለዛሬም አላዋረድከኝ! ምሰህ ቀበርከኝ እንጂ! እኔ
ደግሞ እንደ ሰዎቹ ሞያ ተምረህ
መጣህ መስሎኝ 10000 ብሬን ሆጭ አድርጌ መደገሴ!! አሄሄ ምን
አደርጋለሁ! ራስን አይገርፉ!..”
እያለ አቅማማብኝ፡፡
ህክምና የተመኙልኝ አዛውንት እንዲህ ብለው ለአዝማሪ ግጥም ሰጡ
አኪም ይሁን ብየ ዳር አገር ሰድጄ፣
ቀሎ ወርዶ መጣ ደጀን ያልሁት ልጄ።

©ጥላሁን ሀገሬ

@MahletZerihun
@Wegoch
@Wegoch
እንኳን ለ 125ናው የአድዋ በዓል አደረሳችሁ
ሥዕል #ለይኩን_ግርማ
.
@seiloch
@getem
@wegoch
አነስተኛ የሰው ቁጥር ከምታስተናግድ ካፌ ቁጭ ብለው እያወጉ ሳለ…በረጅም ደቂቃዎች የተሰላ ምስጠት በሚመስል የትካዜ ፊት ዝምታ ውስጥ ቆየ።በቅርብ እርቀት የተቀመጠው ጓደኛው ሻዩን ጎንጨት አረገና ጉሮሮውን ሲጠራርግ ከትካዜው መለሰውና "እኔ ምለው" ብሎ ጀመረ… የምስጠቱን ውጤት ሊያቀርብ ይመስል …


"እኔ ምለው…ምንም ይሁን ምን ዛሬም በጥያቄ ጎዳና ላይ ነኝ፡፡ ጥያቄ በዘመን ርዝመት መልስ ያገኛል ብለውኝ ነበር።መልስ ካላገኘ ግን በጊዜ ሂደት ጥያቄ ራሱ መልስ የማይፈልግ የሕይወት ክፍል ይሆናል።? …ጥያቄ ጠይቄ በአራት ነጥብ እንዳልዘጋው ጥያቄ ነው፤የሰዋሰው ህግን ያናጋው ይመስለኝና ጠያቂነቴን ለመቀጠል እጠይቃለው።እሺ ቆይ ስለጥያቄዎቼ ብጠይቅ በጠያቂነቴ እጠየቅ ይሆን?አለ።

ከሁለቱም በስተቀኝ የተቀመጠው አጠር ያለው ጓደኛቸው ቀደም አለና "ወዳጄ ልምከርህ… ምክር አይጠየቅም።እኔ ለመናገር መጠየቅ አለብኝ ብዬ አላስብም።ጠይቄም ባገኘውት መልስ ተጠያቂነትን ስለማልፈልግ ድምፄን አቅበዋለው።
አለመጠየቅ ከአዋቂነት እንደ ሰበሰበኝ ለሚያስቡም እኔ ማውቀው አለማወቄን ነው እያልኩ ማፅናኛን ለራሴ ስችር ሰምተውኛል።ዛሬ ተቀባይ ነኝ።አልጠይቅም…በሂደቱ ላይ ቅሬታ ቢኖረኝ እንኳ በዝምታ ማለፍን አምኛለው።
ወይም አላውቅምን ዋጋ እሰጠዋለው።በመልሶች ውስጥ ሌላ ጥያቄ አይጠፋምና አላውቅም የሚል ቃል ሀብት ነው"።
የቀረበውን የብርጭቆ ውሀ በአንድ ትፋሽ ጨልጦ ሲያበቃ በረጅሙ ተንፈስ አለና ቀጥሎ "ወይ እስቲ እግዜርን ጠይቀው" አለው። ባለ ትካዜው "እግዜርማ ብዙ ጠያቂ አለው "ብሎ አለፈው።

ባለ ሻዩም በመሀል " ገባና ሲመስለኝ «ለምን?» ወይም «እንዴት?» የሚሉ ጥያቄዎች ህብር ፈጥረው ያመጡት
ሐብት አለ።
ውስጡን የጥያቄዎች ማዕበል
የማይንጠው ሰው ለህይወት የሚያበረክተው አዲስ ነገር ቅንጣት አይኖረውም ብዬ አስባለው።ጥያቄ ጅማሬ ነው።መጠየቅ ቢያመሳስለንም አቻ መልስ መፈለግ ያለያየናል… ክብደቱ መልስ ፍለጋው ላይ ያይላልና።
እናም ጠይቅ!
አሁን ከአንድ ስኬታማ ወንድ በስተጀርባ በለው ጎን ማን አለ ብለህ ብጠይቅ አንድ ጠንካራ ሴት ብለው የመጀመሪያውን መልስ ይሰጡሀል።ሀብታም ዘመድም የሚል አይጠፋም።ግና ከእያንዳንዱ ስኬት ከራቀው ወንድ ጀርባ አንድ ሰነፍ ሴት ልትኖር እንደምትችል ማንስ ነገረን… ካልጠየቅን " አለው።ተሳሳቁ።ሳቃቸው ሲረግብ

አልጠያቂው አልጠይቅ መፈክሩ የሆነው አጭሩ ጓደኛቸው በተራው ጣልቃ ገባና " እና እንደው እንደ ብዙሀኑ ለጥያቄው ከቀረቡት መልሶች ውስጥ መልሱ አልተሰጠምን አክበህ ማለፍ አቅቶህ ነው?መልስ ያጣስ ጥያቄ እንዳለ ዘንግተህ ነው ?ብሎ ሳያስበው ጠያቂ ሆኖ ጨረሰ።

ቀን ፪፬/፬/፪፼፩፫

@wegoch
@wegoch
@wegoch

#Heaቨን
(Maggie)

"እንደናንተ ዘመን ተሻጋሪ ...ባለ ብዙ ፍሬ ...ከንፁህ ልብ የተቀዳ ... በማስመሰል በውድድር እና በይሉኝታ ያልተፈተለ ..... ገንዘብ ውበት ዝና ና ክብር ሚባሉ ኮተቶችን ያልደረተ.... ድንገት ብልጭ ብሎ ደግሞ ድርግም የማይል....... የደረቀ ነፍስን የሚያለመልም.. አመድማ ገፅን የሚያወዛ.... ከእውነተኛ ማንነት የተጨለፈ መዋደድ.... መገኛው ወዴት ነው?" ብዬ ጠየቅኳቸው.. .....ገጠር ሄጄ የነበረ ግዜ.. ....... ከአያቴ የመጨረሻ ልጅ ከእታፈሱ ጋር ምንጭ ውሀ ልንቀዳ የሄድን ግዜ እንደሳቸው እድሜ ጠገብ ዛፍ ስር ቁጭ ብለው ያገኘዋቸውን የቀዬው ነዋሪ አዛውንትን
...
....
የህይወት ትልቁ ክፍል ላይ ተስፋ ቆርጫለው... ፍቅር ላይ!

.. ፍቅር ሸቀጥ ከሆነብኝ ከራረመ... በወንድ ኪስ ውስጥ እና በሴት ልጅ ውበት ስር የቀብር ስነስርዐቱን የፈፀመ ርካሽ ሸቀጥ!....(በተለይ በዚ ዘመን)

ዝግመተለውጡን የጀመረው ከራስ ነው!.... በነፈላስፎቹ ዘመን ፍቅር በጭንቅላት ይለካ ነበር.
ለጥቆ ወደ ልብ ወረደ! እራሱ ፍቅር(ክርስቶስ) መጥቶ ፍቅርን አነገሰው. ሰልሶ... ወደብልት ወረደ! የኛ ዘመን ላይ!.....የፍቅር ቀን በሚል የገበያ ስምኮ ሚደረገውን ብናገር ለቀባሪው ማርዳት ነው ሚሆንብኝ... እስቲ ተውት!......
አራትኛ ወደጉልበት አምርቷል... ይኸው ለጉድ የጎለተኝ መድሀኒያለም ክብሩ ይስፋና.... የኔ አልሆነችምና ፊቷ መበላሸት አለበት ብሎ አሲድ ሲደፋባት አይቻለው.....

:::::;;;;;;;:::::::::::::

ወደቀድሞው ልመለስማ

ሽማግሌው ....እድሜን ስክነትን ጥበብን ትዕግስትን እና ጥልቅ ማስተዋልን... መሬት ላይ ወድቆ አቧራን ቃም እንዳደረገ እርጥብ ልብስ ቅመውት....ፍፁም በተረጋጋ መንፍስ እንዲህ አሉኝ
.
.
"ልጄ.... ባሁኑ ዘመን ሁሉም ሰው ፍቅርን አድናቂ ብቻ ስለሆነ ነው! ዳር ቆሞ ብቻ ማድነቅ! የሰው ድግስ ላይ ከዳር እንደቆመ የበይ ተመልካች በምኞትና በህልም አለም እንደሚደሰት... መናኛ ሰው!.... ፍቅርኮ እጃችን ላይ ነው!
የተሳካላቸው ሰዎችን ስታይ ምነው እነሱን ባደረገኝ! ምነው ፈጣሪዬ መልካሙን ልክ የነሱ ያለውን የሞቀ ፍቅር በሰጠኸኝ.....ታድለው.. ትላለህ እንጅ... "እኔም አንድ ቀን..." ብለህ እጅህ ላይ ያለውን ፍቅር ለመዘርዘር አታልምም!
...... ታካች ትውልድ! .... እንኳን ሰውን ውሻን ለማልመድ መስዋዕት ትከፍላለህኮ! .... ምስያህን ለማልመድ ግን እንደው እንሰናከላለን.

በዛላይ.... እናንት ያሁን ዘመን ልጆች... በሳይንሱ በቀለሙ በጥበቡ... በሁሉም ላይ እንደተሳለ ሰይፍ ናቹ.... ግን... ፍቅር ላይ ይቀራዋል! ምድር ራሱ የቆመችው ፍቅር ሚባል መቋሚያ ተደግፋ ነው.
..... ፍቅርን "ባለቤት መሆን" ወይ በላባቹ እንዳደረጃቹት ቤት ንብረት"የእኔ ብቻ ሀብት! የኔ ንብረት" በሚል ስም ሸብልላቹ ያፈቀራቹት ወገን ድንገት ተቅፋቹ ገሸሽ ያለ እንደሆነ በፍቅር ላይ ተስፋ ትቆርጣላቹ!..... "ተከዳው!" "አወይ ሰው ማመኔ" ትላላቹ.....

ቀድሞ ነገር የጀመራቹት መች ፍቅር ሆነና?! ....ግብይት ይ?"

የጥጥ ማሳ የመሰለ ራሳቸውን ዳበስ አድርገው.... ቀጠሉ

"ወፊቱን በወጥመድህ ይዘህ ቤትህ ጎጆ ሰርተህ ጥሬ ወሀ እና መሰል ነገሮችን እየሰጠህ በድሎት ብታሳድጋትም እሷ ግን ከዛ ጎጆ መውጣትህ ሁሌ ትናፍቃለች

.. በተመሳሳይ... ይችኑ ወፍ ለቀህ እሯሷው የሯሷን ጎጆ ሰርታ ብትኖር ግን እጎጆዋ ለመመለስ እጅጉን ትናፍቃለች.... አየህ...
የሙጥኝ ብለህ ፍቅርን ስትይዝ እንደባህር ዳር ድንጊያ ያሟልጭሀል.... ነፃነቱን ስተሰጠው ግን... ቅንጭብ እንዳዋደደው ወረኧት የሙጥኝ ይልብሀል"

ሰው እጅግ የተወሳሰበ ፍጥረት ነው... መልአካዊ አመልና እንስሳዊ አመል አለው......... በመልአካዊው ያፈቅርበታል በእንስሳዊው ይበቀልበታል.........
ለዛኮ ነው ወንጌል ስሙ ቁርዐን ቅሩ መጣፍቅዱስ አንብቡ የሚባል.....
የምትወድዳት ሴት ውስጥ ያለውን እንስሳ ለመግደል መጀመርያ አንተውስጥ ያለውን አውሬ መግደል አለብህ!
ያኔ ማንንም የሚያ ስ ቀና እጡብ ድንቅ ፍቅር ትመሰርታለህ..."

ቀጭን ኩታቸውን ወደ ትከሻቸው እያጣፉና ሱፍ እንደተዘራበት ጥቁር መሬት በነጭ ጢም የተወረረ ፊታቸውን ዳስሰው

"እየውልህ.... ልጄ.... ... ክርስቶስ ፍቅሩን የገለጠው ቆስሎ ነው... አንተም ቁሰል ድማ አካልህን እጣ ወይ ደግሞ እንዲያ እንደክርስቶስ ያለውን አይነት ስ ቃይ ተሰቃይ አይደለም ያልኩት.... ትግስትን ገንዘብ አድርግ..... ማስተዋልን አስከትል.... ፍቅር ስሜት ብቻ አንዴ ቦግ አንዴ እል ም እንደሚል ተራ የሚሆነው.... ለሰጠኸው ፍቅር ምላሽ ስተጠብቅ ግዜ ነው. አፍቅር.... አንተውስጥ ያለው ፍቅር አገር ያህላል.... ትጎዳለህ እሱ እርግጥ ነው... ግን ጉዳትስ ቀን ጠብቆ ይክስሀል..... ፍስሀን በሰውነትህ ኮለል ያደርግልሀል...... ብቻ ታገስ .... "ቦ ጊዜ ለኩሉ!" አይደል ያለው ጠቢቡ!......... ስጥ ስጥ ስጥ..... ተስጠኸው አጥፎ ደርቦ የሰጥሀል.....ታድያ የሚሰትበትን ግዜ አታስላ.... እሱው በፈቀደው ቀን ይስጥህ."

ተመስጬ ነበር.....ካሉት ውስጥ አንድ ሀሰት የለበትም.

አንድ ነገር ተረዳው......... ግብዞች እንደሆንን... ወድደን ለካ በዛ ፋንታ መወደድን እንጠብቃለን??......

እታፈሱ እንስራውን ሞልታ ጨርሳ እንዳሻክማት ጠራችኝ...... ሽማግሌውን እጅ ነስቼ ሄድኩ

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Magi 🖤
"የመነኩሴውን ታሪክ ታውቂዋለሽ አይደል "…

"አላውቀውም ንገሪኝ" አልኳት

" እ…አንድ ሰው ሚስት ለማግባት ፈለገና ምክር ፍለጋ አንድ የሚያውቃቸው መነኩሴ ጋር ሄደ።መነኩሴውም የመጣበትን ምክንያት ጠየቁትና ሰዉየውም 'ቆንጆ፣ምርጥ ዘር ያላት፣የተማረች፣ፀባየሸጋ ሁሉን ያሟላች ሴት ፈልጋለው' ቢላቸው እሳቸውም 'ልጄ ለምን መነኩሳለው ...ህሄን ሁሉ የምታሟላ ብትገኝማ እኔም አገባት ነበር' አሉ አሉ።"

ፈገግ አልኩ…

በንዴት ቀጠለች

"አጋዥ፣ትሁት፣ለጋስ፣ታማኝ፣አፍቃሪ፣ይቅር ባይ፣አስተዋይ፣በተጨማሪም በሱ ቁንጅና መስፈርት ቆንጆ በአንድ ጊዜ  እንድሆን ይፈልጋል … ይሄስ እሺ ግን መድከምን ፣ መሳሳትን(ጠብቆ) ይከለክለኛል።ግርም የሚለኝ  እሱ በጊዜ ቀነጫጭቦ የሚኖራቸውን ከኔ በድምር መፈለጉ ነው።ለራሱ አያውቅ ነዳይ ለመነ ለአዋይ አሉ

"ምነው" አልኳት ብሷቷን ላረግብ እያሰብኩ።

"የሆንኩትን አይደለም… ያልሆንኩትን ነው።ያልሆነውን ግን መሆን የሚፈልገውን እንድሆን ይለፋል።እሱ መሆኑ አይቀድምም?

ስቆሽሽ ካላፀዳኝ?ወይም የምፀዳበትን ካላቀበለኝስ? ...የስህተት ልጆች አይደለን…የተሳሳተች ሄዋን ውስጥ ፍፁም እኔን ለመቅረፅ ይዳክራል።

Love cleanses አይደል የምትሉት ምነው ለሱ ከሸፈበት?ሰነፍ ነው?የራሱ ሰው ላይ ስህተት ሲያገኝ ይጨንቀዋል?

ንፁህ ያለመቆሸሽ ዋስትና የለው… ንፁህ ማለት ቆሽሾ የጨረሰ ነው?ከዚያ ወድያ የማያድፍ ፍፁም?ጥጉስ እስከመጨረሻው ባለማደፍ መዝለቅ ነው?"
ብሷቷን በጥያቄዋች ደረደረችልኝ።

አፅናናለው ብዬ ሀሳብ አዋቅሬ "እንከን የለሽ ሴት ፍለጋ ስትወጣ አይደክምህም አትባክንም?" ብዬ ምነው በጠየኩት

searching for the perfect person while we are messes… ፐ what an easy way to get disappointed ... ብቻዬን አውርቼ አፌን አጣመምኩ።ማፅናናት ብቀጥልም ከኔ ዘንድ የቀረ ትምህርቴ ይህ ነበር።

ያልተደረሰበት ትልቅ የሚባል ስኬት፣የቁጥር መጨረሻ የለካው ገንዘብ፣ከሁሉ የላቀ ግዙፍ እምነት፣ የማይረታ የሚባል አንድነት ፣ በመጨረሻም ፍፁም የሚባል ፍቅር እና ሰው ከሰው ልጅ መንደር ያሉ አይመስለኝም፤ሁሉም አንፃራዊ ነው። ለተቀማጭ ሰማይ…) አሉ ብዞዋቻችን ተቀምጠን የተራመደውን ወልጋዳነት ለመናገር ስንቸኩል እኛው ተደናቀፍን እኮ

anyway be what you seek, what you seek is seeking you ብሏል Rumi …ያኔ ምርጫችን ቢቀናጣም ቢጤውን አያጣም።

just one last golden rule
"None of us can vow to be perfect. In the end all we can do is promise to love each other with everything we got.Because love is the best thing we do.
Said Ted(A fictional character who said it all )

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Heaቨን
#አሉላ_አባነጋ 🔥👑


ምን ተብሎ ነው ሚጀመረው? ማን ነው ነው የሚባለው? ምንድነው ነው
የምንለው? በምን ማዕረግ ነው የሚጠራው? ራስ'ስ ለአሉላ ምኑ ነው?
ጀነራልነት የአሉላን የሩብ ግማሽ ይገልፀዋል? በታሪክ የነበሩት ጀግኖች
ሁሉ ተደምረው አኪሊስ ጋኒከስ ስፓርታከስ ሊዎኒዳስ ዳዊት ጎልያድ ጌድዮን
ዮፍታሔ ሊጣመሩ ማይችሉት ሁሉ ተጣምረው አንድ ባትል ፊልድ ላይ
አሉላን ባዶ እጁን ቢገጥሙት መሪያቸውን በንቀት እያየ "I knew you
would lead these men to their death eventually, is this the
day you would do it?" ብሎ ኢሬቻቸውን ሚያበላቸው ይመስለኛል።
ከልጅነቱም aggressiveness ደሙ ውስጥ ነው። ገብረሚካኤል የነበረው
የክርስትና ስሙን አባቱ እንግዳ ቁቢ ንስሐአባቱ ወልደጊዮርጊስ ጋር ሄደው
"ቀይሩልኝ" ይሏቸዋል። ምነው ቢባሉ "ወልደ ገብርኤል አርጉለት ልጄ
እንደሚካኤል የዋህና ገራገር ሳይሆን እንደ ገብርኤል ቁጡና ቀልጣፋ
እንዲሆንልኝ ነው ምፈልገው" ብለው ነበር። ወንዳታ አሉላ። ወንዳታ
ገብርኤል።
ካሳ ምርጫ ለንግስና ሻፍዶ ከላስታው ዋግሹም ጎበዜ(ተክለጊዮርጊስ)
ጋር ሲፈሳፈስ አሉላ ማርኮ እንደ በግ እየጎተተ አመጣው። ከዛ ትግሬዎቹ
ምን በለው ፎከሩ
"ንጉስ ማራኪ ከነዘውዱ
የበዝብዝ አሽከር አሉላ ወንዱ"
አሉላ ግብፅን መሐዲስቶችን ጣልያንን በተለያየ የጦር አውድማ
ረምርሟቸዋል። አሁን በየንግግርህ መሃል ዶግ-አመድ እያልክ ወሬ
ምታሳምርበት figure of speech የመጣው ዶጋሊ ላይ 500 የጣልያን
ጭባ ወታደሮችን አመድ ካደረጋቸው በሁዋላ ነው። ያኔ ነበር አፄ ዮሐንስ
ቀኝ እጁን ነው ምቆርጠው ይምጣ ብቻ ሲሉት አሉላ ጀግናዬ የቀኝ
እጃቸውን ቀኝ እጅ ለመቁረጥ ከሆነላቸው ምን ቸገረኝ ብሎ ሲከንፍ መቀለ
የሄደለት። ከዛስ? ከስልጣን ገሸሽ አረገው። የጦር ስትራቴጂስቱን አሉላን
ምክር መስጠት አትችልም ብሎ። መሐዲስት የጎንደር አብያተ
ክርስትያናትን ማቃጠል ሲጀምር ጆ ጎጄውን ራስ አዳል ተሰማን(ንጉስ
ተክለሓይማኖትን) ላከው። ቀምሶ ተመለሰ። ምኒልክና ሌሎቹን አስተባብሮ
መሐዲስትን ሊፈጅ ወደ መተማ ተመመ። ሚላ ቢጠበቅ ቢጠበቅ ዝር
ሳይል ቀረ ላሽ አለው። ትግሬዎቹ በዚ አኮረፉት። ዮሐንስን ሱዳኖች
ቀልበውት አንገቱን ይዘው ሄዱ። አሉላ ምኒልክ ላይ ጥርሱን እንደነከሰ
የዮሐንስን ልጅ መንገሻን ሊያነግስ ደፋ ቀና አለ። ምን ምክሩን አልሰማ
ብሎ በፈጣጣው ተዋግቶ ቢሰዋም ጌታዬ ነበር የሚለው። ታማኝነቱ ሌላ
ታሪክ ነው። አሉላና ክህደት በአንድ ዋንጫ ጠጥተው አያውቁም።
ምኒልክ በኃይል በልጦ ራሱን ሹሞ ጠበቃቸው። ትግሬዎቹ ራስ አሉላ በዘር
ሐረግ የባላባት ልጅ ሆኖ ሳይሆን በላቡ በውጊያ ችሎታው በmerit የራስ
ወርቅ ያሰረ ብትፈልግ በመውዜር ቢያሻህ በቡጢ የሚከነትር ጀግና መሆኑን
ያውቃሉና አቄሙበት። ተናቆሩት። ርስ በርስ እባብ ለእባብ ሆኑ። ሸዋ
ሊያስታርቅ ቀጠራቸው። አሉላ 'ከሃዲው' ምኒልክ ጋር ሄደ። ወደደው።
ሊገድሉት ከሚያሴሩበት ዘመዶቹ አዳነው። ታዲያ ከሸዋ አልመለስም አለ።
ድፍን ሸዋ በምኒልክ አዝማችነት ለአሉላ ወንድነት ጀግንነት ገበረ። የዚህኔ
ነበር አሉላን የገበሬ ልጅ፤ ከሃዲ ብለው እነ ራስ መንገሻ label ያረጉት።
አሉላ ምን ቢሉት መስሚያው ድፍን ሆነ።
"ያደራ ልጄ ከተቀናቃኞቹ ጋር ተመሳጥሮ ሊያጠፋኝ ሲል ነፍሴን የታደግካት
ምኒልክ በሩቁ ስጠላህ በሩቁ ስንቅህ ኖሬያለሁ። በሩቁ ሆነህ ነፍሴን
አተረፍካት። ከእንግዲህ ከግቢህ አልወጣም" አሉ። ከትግራይ ራሶች አንዱ
የሆነውን ራስ ሐጎስንም
"ሐገሬ እንኳን በናንተ እጅ አልወደቀች። እንኳን ትክክለኛውን ጌታ አገኘች"
ብሎት ነበር ይሄን ነው royalty recognizes royalty የምንለው።
አደዋን አንስተህ አሉላን መግደፍ ድንግል ሰገጥ መሆን ነው። ዘመቻው
በጎራዴ በመድፍ እና በነፍጥ ተጀምሮ ያለቀ ከመሰለህ ሌጣ መሃይም
ነህ። አሉላ ባሻይ ዓውዓሎምን ለስለላ የጣልያን ሰፈር ልኮ fake news
አሰራጭቶ ጣልያኖችን ሌላ ታሪክ ውስጥ የከተተበት መንገድ ከሁሉም
የቀደመው ነው። የነጣይቱ የውሃ ጉድጓድ ከበባም ቀላል የሚሊተሪ
ስትራቴጂ አልነበረም።
አየህ ጌታዬ አሉላ አንድ ሰውና አንድ ማዕረግ የሚበቃው ፍጥረት
አይደለም። ብቻውን ጀምዓ ነው። ጀግና ያደንቃል። ዮሐንስን ጌታዬ
ብያለሁና ምኒልክን አልልም የሚል ሽልም ደደብ አይደለም። "ሳውቅህ
ገባኝ ምኒልክ ጭስ ነህ አገሬ አንተን በማግኘቷ ዕድለኛ ናት ይመችህ"
ነው ያለው።
ሌላው ፕላኔታችን የአሉላን የሩብ ግማሽ ጀግና አፍርታ አታውቅም።
ምድርን ወክሎ ከaliens ጋር መዋጋት ይችላል። I can take all of you
motherfucker all at once የሚል፤ ፍርሃት ሲያልፍም የማይነካካው
ጀግና ነው። አንዴ ይሄን ብዬ ነበር
"ቀን የጣለው ጀግና ሄዶ ቀን የቀናው ቢመጣ
አባቴ ይሙት ስልህ
በአሉላ ስም ብዬ ነው ዛሬም የፍርሃት ዛር የማስወጣ"
ስሙ ጠበል ነው ዘምዘም ነው የኢዩ ጩፋ ካራቴ ነው በፈለከው መንገድ
address ያደርግሃል። አገሪቱ ኃይማኖት ብትሆን አሉላ ገብርኤሏ ነው
ለዚች አገር ፊትም ያላለፈ ሁዋላም የማይገኝ መልዐከ ዑቃቤዋ፤ የሌሊት
ጠባቂዋ ግብር የማይበላ ዛሯ ነው።
አሉላ
ምኒልክ
አሉላ
ምኒልክ
አሉላ
ምኒልክ

©ክቡር ሰይጣን 🖤🖤🖤

@MahletZerihun
@wegoch
@wegoch
እንደ ሀገር፣ እንደ ህዝብ ነፃ ለሆንበት ቀን እንኳን አደረሰን የቆየችልንን ሀገር ጠባቂ ትውልድ እንሁን ከተከፈለላት ዋጋ በታች አናድርጋት፤ ተሰብረው ያቀኑንን፣ ተገብረው ያቆዩንን፣ ባፈሰሱት ደም ነፃነትን ላጠመቁን አባቶች የሚገባውን ዘልአለማዊ ክብር ሰርተን እንችራቸው። በብዙ መስዋዕት የቆመን ማንነት ታግለን ልናፈርሰው አንችልም

"አድዋ ዛሬ ናት አድዋ ትላንት
መቼ ተነሱና የወዳደቁት"

የካቲት 2፫ ፲፱፹፰
አድዋ የጥቁር ህዝብ አኩሪ ታሪክ
እኔ ጥቁር ሰው ነኝ!!!

በእምኒ የጨረቃ

@wegoch
@wegoch
@wegoch
እኔ ነኝ ጤነኛ እነሱ?

ሬሳ በቀብር ፈንታ ሲቃጠል አይታችሁ ታውቃላችሁ ወይ?

እኔ ግን አይቻለሁ:: አጅቤ ወስጄ አስቃጥዬ ... አመዱን አጅቤ ... ምን አቻኮላችሁ ልነግራችሁ አይደል?

እኔ ሁለት ቀን ነው ያየሁት ... እቤታችን መጥቶ ... ለበዓል ... ተጫዋች .. ወጣት ነው! እነሱ
ቤተሰቦቹ ናቸው...

"ጆናስ እኮ ሞተ" ብሎ የሚነግረኝ አባቱ ራሱ ነው:: እኔን ነው ማየት ... ነጠላዬን አቀብሉኝ አልኩ:: እሱ እቴ ... ውስኪዬን አቀብሉኝ ብሎ በላይ በላዩ ይጨልጠዋል::

"ምን ሆነሽ ነው ኸረ ተረጋጊ!" አባትየው ነው በድጋሚ ..... የልጁን ሞት የረሱት መስለው ከወንድሙጋ ሌላ ወሬ ያወራሉ....

ልጁ
ይሄ ከተራራ ላይ ገመድ ወገባቸው ላይ አስረው የሚሽቀነጠሩትን ነገር ታውቁት የለ? እንደሱ ሲምዘገዘግ ነው ተፈጥፍጦ ...ትንሽ ቀን ሀኪም ቤት ተኝቶ የሞተው...

(እኔ ሀበሻ ነኝ! ምንም ሆኖ ይሙት ... ሰው ሞተ ከተባለ 'ወየው ልጄን... ወንድሜን ... አጎቴን ..." ነው! እነሱ 'እረፍ ስንለው አልሰማ ብሎ' ይላሉ:: 'ኸረ ሙት አይወቀስም ተው' እላለሁ በሆዴ ... (በነሱ ቆንቃ ማለት ስለማልችል ነው)

የቀብሩ ቀን ... (የመቃጠሉ ቀን ) ሬሳው በስነስርዓት በሳጥን ተደርጎ ጥቁር ሱፋችንን ግጥም አድርገን ቤተ ክርስቲያን ሄድን!! ... እንደማንኛውም ሬሳ የፀሎት ስነስርዓት ተደረገለት... ወላ ሀሌሉያ የሚለውን እንግሊዝኛ መዝሙር ዘመርኩላቸው ... (ሚስማር ሊያዘንቡብኝ ሆ! የመዝሙሩ ግጥምኮ ከእግዜር ጋር ፀብ አለው! )

የሆነው ሆኖ ሬሳው መቃጠያ ስፍራ ከመሄዱ በፊት ተሰናበቱት ሲባል ... የልጁ አያት አበባ ሊያስቀምጡ በሄዱበት ከእናቱጋ ተደጋግፈው ማልቀስ ጀመሩ.... ድምፄን እንዴት ልዋጠው? ህቅቅ ብዬ መነፋረቅ...

እናት የምመስለው እኔ ነኝ!! ሰው 'ምኑ ናት? ' እየተባባለ የሆነ ፊልም ይመስል ያፈጡብኛል:: ... ስንት ነገር አለ? ህእ ... ሀበሻኮ በአንድ ለቅሶ ለአንድ ሞት ብቻ አያለቅስም ... እነሱ ይሄን ያውቃሉ? አያውቁም!! ... የዛሬ 20 ዓመት የሞተ ወንድሜ... የዛሬ 14 ዓመት የሞተ አያቴ .... የዛሬ 6 ዓመት የሞተ ጏደኛዬ ... በእዛ እንባ ውስጥ ይሄ ሁሉ ሀዘን መኖሩን ያውቃሉ? አያውቁም....

ስንወጣ ሰው እናትና አባቱን ትከሻቸውን ጨበጥ እያደረገ ካለፈ በኃላ እኔጋ ሲደርሱ አበክረው ያፅናኑኛል::

የሚቃጠልበት ቦታ ሄደን ተቃጥሎ እስኪበቃና እስኪቀዘቅዝ ጊዜ ስለሚፈጅ ተመልሳችሁ ኑ ተብለን ሲለኮስ አይተን ሄድን!!

(በነገራችሁ ላይ ... ሬሳዬ እንዳይቀበር ይቃጠል ያለው ራሱ ሟች ነው:: እናትና አባቱ እንቢ ብለው ነበር ... እህቱ ቃሉ መከበር አለበት:: ብላ በዛ ላይ 18 ዓመት ስላለፈው መብቱ ነው ተብሎ ነው::)

ልናርፍ በሄድንበት እህትየው የባሰውን አመጣችው!!

"አመዴን ከወደቅኩበት ተራራ ላይ ወስዳችሁ በትኑት ብሏል:: እዛው ወስደን ነው የምንበትነው!"

አባትየው ምርር ብሎት

"በህይወት እያለም እረፍት ሰጥቶኝ አያውቅም! ይኸው ሞቶም ያንከራትተኛል! ምን አይነት የተረገመ ልጅ ነው?" (ልጁ ራሱ ግፉ)

እኔ አይኔን በልጥጬ ደንግጬ አያቸዋለሁ!! እነሱ ያፅናኑታል

"አይዞህ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ነው!! ቃሉን እናድርግለት"

አመዱን በሚያምር እቃ አስቀምጠው ሰጡን!! አመድ አጅቤ ትንሽ መንገድ ከሄድኩ በኃላ እኔ ወደቤቴ ተመለስኩ.... እነሱ አመድ ብተና ወደተራራው ተጏዙ....

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ልንጋባ ሁለት ሳምንት ሲቀረን እጮኛዬ ጤነኛ እንዳልሆነ አወቅኩ!! (ርዕስ ነው)

"አታውቂም ነበር እንዴ?" ብለው የሚያዩኝ አስተያየት ራሱን ሊያጠፋ የነበረው ልጃቸው ሳይሆን እኔ የሆንኩ በሚያስመስል ሀዘኔታ አይን ነው።

"ምኑን? ምኑን ነው የማውቀው?"

"bipolar እንደሆነ አልነገረሽም?"

"ባይፖላር ምንድነው?"

እናቱና ወንድሙ 'ውይ ምስኪን አታውቅም!' የሚል አስተያየት ተያዩ። ያሉት ነገር ትርጉሙ ሳይገባኝ ግን ፍቅረኛዬ እንደ እርጅና የሚያስፈራ ነገር(ለእኔ ከእርጅና በላይ አስፈሪ ነገር የለኝም) እንደደበቀኝ ገባኝ።

ፍቅረኛዬ ነው! አብረን መኖር ከጀመርን ሶስት ወራችን! ማታ ከእንቅልፌ ስነቃ ከአጠገቤ አልነበረም። ለደቂቃዎች ጠበቅኩት። አልተመለሰም። አንዳንዴ እንቅልፍ ሲያስቸግረው እንደሚያደርገው ሳሎን ከሆነ ብዬ ሄድኩ። አልነበረም! የሳሎኑ ወደ ጓሮ የሚያስወጣ በር ክፍት ነው። እግሬ በደመነፍስ ተራመደ።

ቤታችን (ቤቱ) ውሃ ዳር ነው። የሳሎኑ ወደጓሮ የሚያስወጣ በር ወደ ውሃው ነው የሚመራው። ጨረቃዋ ፏ ብላ ምሽቱ የእኩለቀን ድምቀት ደምቋል። ዙሪያ ገባውን ቃኘሁ። በስሱ ከሚያፏጨው ንፋስ በቀር ምንም ተንቀሳቃሽ ነገር የለም። ዓይኔን ወደውሃው ላኩት። ውሃው ውስጥ የሚንቀሳቀስ ነገር ያየሁ መስሎኝ አተኮርኩ። ማመን አልፈለግኩም ወይም ባይሆን ተመኘሁ እንጂ ያየሁት የሰው ጭንቅላት ነበር። ከደቂቃዎች በኃላ ራሱ መሆኑን አረጋገጥኩ። ፍቅረኛዬ ነው!! ውሃው ውስጥ እየተራመደ ነገር ........ ውሃው አንገቱጋ ደርሷል::

እኔ ምን ነበር ያደረግኩት? ቆምኩ! ደነዘዝኩ! ተጣራሁ
"ፔር! ሀኒ..."

ውሃው ውስጥ ልገባም ጀመርኩ:: ከነየቤት ጫማዬ ..... የውሃው ቅዝቃዜ እርሱጋ ሳልደርስ የሚገድለኝ አይነት ነው:: እየገባሁ ደጋግሜ ተጣራሁ።

"ፔር ! ፔር! " እንደሀበሻነቴም 'እሪሪሪሪ ..... ኸረ ወየው ኡኡኡኡኡኡ.... የሰው ያለህ' ማለትም ያምረኛል።

የጎረቤታችንን ስም እየጮህኩ ተጣራሁ አንዴ የፍቅረኛዬን ..... አንዴ የጎረቤታቸንን ስም ... እጮሃለሁ! የምይዘው ግራ ገባኝ .... የእሳት አላርማቸው ራሱ እንደእኔ መጮሁን እንጃ ጎረቤት መብራት ሲበራ እሪታዬን ከበፊቱ አብልጬ አቀለጥኩት። መጥተው እሱን ሲያወጡት እኔ ግማሽ ውሃ ውስጥ እንደገባሁ ደንዝዤ ቆሚያለሁ። እግሬ መንቀሳቀስ አቃተው። ድንጋጤው ...... ከዜሮ በታች የሆነው የውሃው ቅዝቃዜ ....... ጭንቅላቴ ውስጥ አሁንም አሁንም የሚያቃጭለው ሀሳብ 'ራሱን ሊያጠፋ ነበር?' አማተብኩ። መጥተው እጄን ይዘውኝ ከውሃው ወጣሁ!!

ሀኪም ቤት ከደረስን በኋላ ተደውሎላቸው የመጡት ቤተሰቦቹ 'እንዴት አታውቂም?' ብለው ይገረሙብኛል።

የፍቅረኛዬ ህመም ምን እንደሆነ ሊያስረዱኝ ሳይንሳዊ ማብራርያ ይነግሩኛል። በግልብ ሀበሽኛ ቋንቋ ፍቅረኛዬ መለስተኛ እብድ ነው። ይኸው ነው!! የአዕምሮ አለመረጋጋት!

"በሆነ መንገድ ትሪትመንት ይኖረዋልኣ? የሚድን ነገር ነው?" አልኩት ዶክተሩን። እሱም እንደቤተሰቦቹ እንዴት አታውቂም በሚል ሀዘኔታ እያየኝ(መሰለኝ)

"በሚያሳዝን ሁኔታ አይደለም! ... እ እ ከስንት አንዴ በራሱ የመጥፋት ነገር አለው። ጨርሶ ባይድንም በመድሃኒትና በትሪትመንት ግን ኖርማል ቀን ይኖራቸዋል።" ብሎኝ ምን ማድረግ እንደሚገባኝ ይነግረኛል። ማድረግ አለብሽ ብሎ የሚነግረኝን ነገር ማድረግ መፈለጌን እንኳን ሳያውቅ

ልንጋባ ቀን ቀጥረናልኮ!

ምንድነው የማደርገው?

ክፉ ሴት ነኝ? ፍቅረኛዬ ራሱን ሊያጠፋ ከመሞከሩ ከሰዓታት በኋላ ያሳሰበኝ ቪዛዬ ነው! ካላገባሁት ወደሀገሬ ልመለስ ነው።

በለሊት ተነስቶ ራሱን ለማጥፋት የሚሞክር እብድ ከመሆኑ ውጪኮ ጥሩ ሰው ነበር።

አንዳንዴ ልክ እንደጦዘ ሰው እየተቅለበለበ አንዱን ቃል ከአንዱ እየደረበ ከማውራቱ ውጪኮ ደህና ሰው ነበር።

አንዳንዴ በጣም ከመደበሩ የተነሳ እቤት ውስጥ ሲንቀሳቀስ ሰው ሰራሽ ሮቦት እንጂ ስጋና ደም ያለው ሰው አይመስልም ነበር እንጂ ደህና ሰው ነበርኮ

ለሊት ለሊት ብዙ መተኛት ስለማይችል ግማሽ ለሊቶችን ብቻዬን ተኛለሁ እንጂ ደህና ሰው ነበርኮ!

አንድ ቀን የጦፈ ልፋት ላይ ሆነን ድንገት የሆነ ራዕይ እንደተገለጠለት ነገር አክሱሙን ነቅሎ እንደተንጋለልኩ ጥሎኝ እርቃኑን ከመኝታ ቤት ወጥቶ ሲሄድ ምን ሆኖ ነው ብዬ ብከተለው ምንም እንዳላቋረጠ መጠጥ ቀድቶ ሳሎን ቢቀመጥም ..... ደህና ሰው ነበርኮ

ይሄ ሁሉ የህመሙ ምልክት መሆኑን የማውቀው ዛሬ ነው። ሀበሻ ነኛ .... የአእምሮ መታወክ ... አለመረጋጋት ... እያለ ከማያለዝብ ማህበረሰብ ነው የመጣሁት!! ... እብደት እብደት ነው የማውቀው!! በደረጃና በምልክት ተከፋፍሎ አንድ ሀገር ስም እንዳለው አላውቅም!! ከአዕምሮ ጋር የተያያዘ ምንም ነገር ከተፈጠረ ... ፀሎት ... ፀበል ... ጠንቋይ ቤት ... ባስ ካለ እና ትንሽ ከዘመኑ ሀኪም ቤት .... ትንሽ ትንሽ ያለመረጋጋቱን 'እገሌ እኮ ወሰድ ያደርገዋል' እየተባለ በሳቅ የሚታለፍ ነው!

የተወሰኑ ቀናት ሆስፒታል ከቆየን በኋላ ወደ ቤት ተመለስን! ፈራሁት! በተራዬ የማልተኛው እኔ ሆንኩ! እሱን ጥበቃ ገባሁ!
እንደፈራሁት ገብቶታል።

"You are free to leave me" አለኝ የሆነ ቀን!

ምን ማለት ነው? ማንን ነው የሚያስኮንነው? ደሞስ ቪዛዬስ? ቀድሞስ የያዘ ይዞኝ እንጂ አካሄዱ መች ጠፋኝ? ሰበር ሰካ እያልኩ እፈተለከው!

ግን ከዛስ?

አልጨረስንም ............

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
#Hiking_trip to Mount Mogle

Mount Mogle or the Mogle hills are located 19kms West of Addis Ababa. The hills contain a spectacularly diverse landscape. With the elevation of around 3210 meters above sea level, it is the highest peak in the West side of the capital.

The beautiful group of mountains, various types of trees and birds make the place an ultimate destination for hikers.

Hiking Date :- March 14, 2021 (megabit 5, 2013)

#Hiking_Cost 500 ETB only and for foreign 25 dollar

Departure Spot-piyasa (Tayitu Hotel)🍁
Departure Time - 12:30 Am LT 🍂🌴🍁

🎉🎊Package includes🎋🎊

🚍 Transportation
🌲 Bottled water
🌺 entrance with Guide
🍂 photography 📷
💐 Breakfast and lunch
🌷 Family Chilling & Talent performance ( if any)🙊🙊

🧗‍♂️ Trip grade: Medium
👉 Score Level: 8/25
👉 elevation: 3210 meter
👉 walking hour: 5-6 hour (8 km of walking)

suitable for:
- beginner
- walking of average fitness
- basic skill required

NB.
🚫 Sanitizer & facemask mandatory!

Brought to you by
💥#Sunset_Hiking_Group

for more join the
🔸channel @sunsethiking🍁
🔹the group @sunsethike🍁
🔻📷 @sunsetphotography🍁

🎫 tickets available at
@Paappii (0922303747)
ልንጋባ ሁለት ሳምንት ሲቀረን እጮኛዬ ጤነኛ እንዳልሆነ አወቅኩ (ክፍል ሁለት)

"ተሻለህ? እንዴት ነው የሚያደርግህ?"ይባላል?

"እንደ እብድ እንደእብድ ነው የሚያደርገኝ!" እንዲለኝ ነው?

እንደእውነቱ ከሆነ የሚያደርገውስ እኔ እነደማውቃቸው እብዶች አይደለም። የሚያደርገው ብቸኛ ነገር ጉልበቱን አቅፎ መተኛት ነው።

በግድ ይጎርሳል ..... ተፈጥሯዊ ግዴታ ስለሆነ እግሩን እየጎተተ ሽንት ቤት ይሄዳል። በቀን ውስጥ ከጥቂት ቃል ያለፈ ከአፉ አይወጣም።

ከሱ እንዲህ መሆን በላይ ልፋት ማቆማችን አሳሳቢ ነገር ሆኖ ባይሆንም እስከመቼ እንደምፆም ማወቁም አይከፋምኮ🤪 አብሯት ብዙ አልባሌ ነገር እንዳደረገ ሰው ሳይሆን ዛሬ እቤቱ እንደመጣች እንግዳ ነው የሚያየኝ። ቀኑ መርዘሙ ለሊቱ ደግሞ መባሱ ከአጠገቤ ዞር ሲል ካለማመኔ ሽንቱን ሁሉ ቆሜ ላሸናው ምንም አይቀረኝም።

የዛን ያህል ክፉ ሴት አታድርጉኝ! ፍቅረኛዬ ባይሆን ..... አብሬው ባልተኛ ......ወደፊቴን አብሬው ባላስብ ..... በአንድ ጣራ አብሬው ባልኖር ...... ይሄ ሁሉ ባይሆን እናንተ ስታነቡት እንዳዘናችሁለት እኔም አዝኛለሁ። ቤተሰቦቹ ; ጎረቤቱቹ ; ጓደኞቹ መጥተው 'እንዴት ነው?' ብለው ጠይቀውት እንደሚሄዱት፣ ስልክ እንደሚደውሉት እንደሱኮ እኔም የዛን ያህል ሀዘኔታና ፍቅር አለኝኮ

ግን ቀሪውን ዘመኔን ልሰጠው? በትዳር ስም ራሴንም ምንም የማያውቅ ልጄንም የየእለት ሰቀቀን ውስጥ ለመክተት የሚያስደፍር ቸርነትም ፍቅርም የለኝም። የዛን ደረጃ ፍቅር ማፍቀር የሚችለው ማፍቀሪያዬ ቆይቷል ከጥቅም ውጪ ከሆነ ......

ኸረ እንደእውነቱ ከሆነ በየትኛውም መጠን የሚሆን ፍቅር የለኝም!

አዎ ላገባው ነው። አዎ አብሬው እየኖርኩ ነው። አብረን ከመኖራችን በፊትም ለአንድ አመት የኔ ፍቅር የኔ ህይወት ተባብለናል። አላፈቅረውም ማለት እጠላዋለሁ ማለት አይደለም? 🤷🏽 መሃል ላይ የሆነ ስሜት አለ አይደል? ደስ ይለኛል! ከዛ ባለፈ ግን መሽለኩያዬ ነው። ማምለጫዬ ነው! ማለቴ ነበር!

እሱ ዛሬ ብድግ ብሎ ሰርጉን ሰርዤዋለሁ ቢል አንደኛ አይገርምም ያመዋላ!

ሁለተኛ ኖርዌጅያን ነው። እንኳን ሰርጉን ራሱንም በፈቃዱ ከመኖር ቢሰርዝ ከአንድ ቀን ቀብር ያለፈ ግርግር የለውም።

እኔስ?
እኔ እሱን ሳገባ ለእርሱ የሁለት ሰው ጥምረት እንደሆነው አይደለም ለኔ።

እሱ ቤት ስገባ የልጄን የወደፊት ህይወት ... የቤተሰቤን ድህነት ..... ያቺ የምወዳት ጎረቤቴን የበዓል ወጪ ሳይቀር በትከሻዬ አዝዬ ከነብዙ ጓዜ ነው የማገባው!

እሺ እኔስ በቃ ሰርጉን ሰርዝኩት አልኩኝ 'ልጄ ቀስ ብላ ትከፍላለች' ብሎ በብድር መሬት የገዛ አባቴን ምንድነው የምለው?

'ልጄን ሰው ካደረግክልኝ ሙክት አስገባለሁ!' ብላ ለመድሀንያለም የተሳለች እናቴን ምንድነው የምላት?

ለሚያውቃቸው እኩዮቹ ሁሉ 'እናቴ ውጪ ሄደች መጥታ ፈረንጆቹጋ ትወስደኛለች!' ብሎ የተቀደደ ልጄን ምንድነው የምለው?

'አይዞሽ እህታለም እኔ አለሁልሽ የግል ትምህርት ቤት አስገባሻለሁ' ያልኳትን ታናሽ እህቴን ምንድነው የምላት?

ለእነሱ መክፈል ያለብኝ መስዋዕትነት ከእብድ ጋር መኖር ከሆነ የምገባበትን ማጥ በወጉ ማወቅ ስላለብኝ ስለህመሙ ጎግል ማድረግ ጀመርኩ። ሳልዋሻችሁ መጀመሪያ የጎለጎልኩት ካገባሁት በኋላ እንደለመደው ራሱን ሊያጠፋ ቢሞክርና ቢሳካለት የኔ እጣ ፋንታ ምን እንደሚሆን ነው። ቋሚ የመኖርያ ፈቃድ ለማግኘት 3 ዓመት አብሬው የመኖር ግዴታ አለብኝ።

እንደክፉ ሴት አትዩኝ። እሺ በቃ ትንሽ ትንሽ ክፉ ነኝ። ከሞተ ወረቀቴን ይሰጡኛል። ለሆነ ሰከንድ ቢሞት ሁሉ ምንም እንደማይመስለኝ አሰብኩ። አምኛለሁ እሺ በደንብ ክፉ ነኝ!

በአለም ላይ 45 ሚሊየን ህዝብ የባይፖላር ህመም ተጠቂ መሆኑን ሳነብ በተመሳሳይ ምልክቶች የማውቃቸውን ሰዎች ሁላ እጠረጥር ጀመር። ራሴን ሁላ ስሜቶቹ ተሰምተውኝ ከሆነ ፈተሽኩ 'እብድ እኮ ለራሱ አይታወቀውም'ብዬ ተውኩት

በአለማችን ታዋቂ የሆኑ በዚህ ህመም ተጠቂ የነበሩና የሆኑ ሰዎችን ስም ዝርዝር ሳነብ የእብዶች ዓለም ነውሳ ዓለማችን?

በጣም ጥቂቶቹን ላስቆጥራችሁ ከመሪዎች የአሜሪካውን አብርሃም ሊንከን Abraham Lincoln የእንግሊዙን ዊንስተን ቸርችል (Winston Churchill)

ከሙዚቀኞች በፍቅር የምወዳት ኒና ስሞንን ጨምሮ Nina Simone, Selena Gomez,,Mariah Carey , Amy Winehouse, Demi Lovato ዘፋኞቹ ላይ ይበረታል ልበል? ብዙ ናቸው

በቁጠኝነቱ የሚታወቀው ታዋቂው ቦክሰኛ mike tayson

ታዋቂው የፊልም ፀሃፊ ዳይሬክተርና ተዋናይ Mel Gibson የዘመኔ ወንድ ልጆች እንደሱ ለመሆን ካራቴ የሚማሩለት አክተር ቫንዳም Claude Van Damme

እሺ ማነው ጤነኛ? የእብዶች ዓለምማ ነው!

ዶክተሩጋ ደውዬ ላገኘው እንደምፈልግ ነግሬው አገኘሁት። ይሄ ደግሞ ክፋቴን ሲያበዛው

"አንቺ ወደህይወቱ ከመጣሽ በኃላ ደስተኛ እንደሆነው ደስተኛ ሆኖ አያውቅም። ለ20 ዓመት ህክምናውን የምከታተለው እኔ ነኝ። አንቺን ካገኘ በኋላ ድኛለሁ ብሎ ለራሱ ስላመነ መድሃኒቱን አቋርጦ ነው" ይለኛል!!

ምን ውስጥ ነው ራሴን የዘፈቅኩት?

አሁንም አልጨረስንም ......

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ልንጋባ ሁለት ሳምንት ሲቀረን እጮኛዬ ጤነኛ እንዳልሆነ አወቅኩ (ክፍል ሶስት)

(ተፋፍረን እንጂኮ ሁላችንም አብደናል)

እንዴ የፈረንጅ አማች ሲከፋ ከሀበሻ ይብስ የለ እንዴ?

"በሱ ፋንታ ምናለ አንቺን ቢያቆራምድልኝ!" አንሾካሽካለሁ

"Pardon?" ትላለች ወደ አፌ ጆሮዋን አሹላ

"እዚሁ ነው እናቴ እዚሁ ነው!"

"Excuse me?"

ኡፈይ እቺ ደግሞ አላስተነፍስ ልትለኝ ነው እንዴ? እህቱኮ ናት! ወንድሟን አለሁልህ ልትለው ለተወሰነ ቀን መጥታ ልትደፋኝ በነገር። ቀድሞውኑም እንደማላፈቅረው ገብቷታል። 'እሰይ የታባሽ !' አይነት ሙድ ታሸሙራለች። የኔ መጨናነቅ ደስ ያላት ነው የምትመስለው።
'በላሁ ብለሽ ተቆረጠምሽ!' አይነት የነገር ዳርዳርታ
ጨዋታ ትጫወታለች::

"ስለሰርጉ ተነጋገራችሁ?"

"አልተነጋገርንም ምናልባት ቀኑን መቀየር ሊኖርብን ይችላል" አልኳት

"ሀሳብሽን የምትቀይሪ መስሎኝ ነበር።" እና ይህቺ የሀበሻ አማች አይደለችም?

"ለምን ብዬ?"

"አይ ያለበት ሁኔታ ከከበደሽ ብዬ ነው።" (ከባዱን ይስጥሽ እላታለሁ በልቤ)

የሰርጉን ቀን ላልተወሰነ ቀን አራዘምነው። እሱም መድሀኒቱን መቃም ቀጠለ። ከቀን ወደ ቀን ድባቴው ለቀቅ እያለለት መጣ።

የሆነኛው ቀን ከእህቱ ጋር እቤት ትቼው ወጣሁ እና አንዲት የምግባባት ታይላንዳዊት ጋር ሄድኩኝ። የማሳጅ ቤት አላት። የተፈጠረውን ነገር አንድ በአንድ ነገርኳት። እኔን ክፉ ናት አላችሁ? በሷ ሂሳብ እኔ ለመላዕክትነት እቀርባለሁ።

"ምን ትሰሪያለሽ ታዲያ? መድሀኒቱ ህመሙ የሚነሳበትን የጊዜ ጋፕ ያረዝምልሻል እንጂ ዘላለምሽን ወይም ሶስት ዓመት ከእብድ ጋር ነው የምትኖሪው ይልቅ በቀረሽ ጊዜ ዞር ዞር ብለሽ የሚያገባሽ ፈልጊ!" አለችኝ። ባል ከምስር ውስጥ የሚለቀም ጠጠር ነው ወይ ፈለግ ፈለግ ተደርጎ የሚገኘው? በዛ ላይ አብዛኛው ኖርዌጅያን አግባ ከሚባል ሲኦል ግባ ቢባል ኪሱ ውስጥ እጁን ከቶ እያፏጨ ይገባል።

"ከየት ነው የምፈልገው?"

"ቲንደር አካውንት ክፈቺ (የታወቀ የዴቲንግ ሳይት ነው) ወንዱ እዛ አፉን ከፍቶ አይደል እንዴ የሚውለው? ከፈለግሽ ደግሞ ማሳጅ ቤት እየመጣሽ እኔጋ ዋዪ ሀብታሞቹ ይመጣሉ::"

"ከዛስ? በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ አግባኝ ብለው ማን ይሰማኛል?"

"አንቺ (እንዴት ያለሽው እንከፍ ነሽ አይነት አስተያየት ከፀጉሬ እስከጥፍሬ እያየችኝ) ይሄን የመሰለ ሰውነት ይዘሽ .... ቆንጆ ነሽ ... በዛ ላይ ስማርት ነሽ ...ጨዋታውን ተጫወቺ (አባባሏ ስድድድ ያለ ስድነት አለው ) አጊንቶ ነው። ካላገባኸኝ ቪዛዬ ሊያልቅ ስለሆነ ልሄድብህ ነው ትዪዋለሽ አለቀ!"

"እሺ ባይለኝስ? ከሁለት ያጣ ሆንኩ ማለት አይደል?"

"አንቺ (አሁንም አጠራርዋ እንዴት ያለሽው ገንገበት ነሽ አይነት ነው) አንድ አምስቱን አጫውቺ ከአምስቱ አንዱ ይፈርምልሻል!"

"መድሀንያለምዬ አምስቱን እያጫወትኩ ተመልሼ ፍቅረኛዬ ቤት ነው የምገባው?"

"ምን? ከቤት ስትወጪ ምልክት ያደርግበታል? ወይስ ይለካዋል?"

"እኔ ለሱ አይደለም ለራሴ? ጭንቅላቴ አይቀበለውም!"

"እንግዲህ ምርጫው ያንቺ ነው!"

እቤት ስገባ እሱ ከእህቱ ጋር ሳሎን ቁጭ ብለዋል።

"እንኳን ወጣሽ ከኔ የባሰ ድብርት ውስጥ ገባሽ!" አለኝ። ዛሬ ደግሞ በደንብ ነቃ ያለ ይመስላል።

"እ ለለውጥ አሪፍ ነው!" አልኩት።

ዶክተሩ እንዳስረዳኝ ይሄን የድባቴ ጊዜ ካለፈ መድሀኒቱን በስርዓት ከወሰደ ደህና ይሆናል። ላልታወቀ ያህል ጊዜ..... ደግሞ ድጋሚ እስኪነሳበት ....

ህመሙ ከገነት ሲኦል አይነት የስሜት ለውጥ ነው። እጅግ ከፍተኛ የሆነ የፈንጠዝያ ስሜት ከብዙ ተያያዥ ስሜቶችና ቅዠቶች ጋር ለቀናት ወይም ለሳምንታት ይቆይና ከዛ ደግሞ ከፍተኛ የሆነ የድብርት ስሜት ራስን እስከማጥፋት የሚያስደርስ ራስን መጥላትና አለመፈለግ ስሜት ለቀናት ለሳምንታት ይከተላል

"ይቅርታ! " አለኝ እህቱ ስትሄድ ጠብቆ "ስላልነገርኩሽ ይቅርታ"

"እሺ ለምንድነው ግን ያልነገርከኝ?"

"አንቺ ዓይኖች ውስጥ ብቻ ነው ጤንነቴን የማየው። አንቺ ስታዪኝ ብቻ ነው ሙሉነት ... እንደማንኛውም ሰው ጤንነት ይሰማኝ የነበረው። ሌሎች በዙሪያዬ ያሉ ሰዎች ሲያዩኝ አይናቸው ውስጥ አቅም አልባነቴን አየዋለሁ። ተስፋ ቢስነቴን አየዋለሁ። አንድ ምንም እንዳልጎደለሽ አድርጎ የሚያይሽ ያውም የምታፈቅሪው ሰው በህይወትሽ ሲኖር ደስ ይላል። ለመኖር ፈለግኩ .... ዓይንሽ ተስፋ ሰጠኝ .... ለመኖር ጓጓሁ .... አለመናገር መረጥኩ!" አለኝ። አይኑ ሳያነባ ድምፁ እያለቀሰ።

ግራ ገባኝ .... የምር ግራ ገባኝ። ልጄ አልቅሶ ሲያበቃ እንቅልፍ ሲወስደው በእንቅልፍ ልቡ ህህቅ ብሎ ሲቃ ሲያሰማ አንጀቴ እንደሚላወሰው አንጀቴ ተላወሰብኝ። አጠገቡ ሄጄ አቀፍኩት ትከሻው ላይ አገጬን አድርጌ ግራ የገባው ሀሳብ ሳስብ ከቆየሁ በኃላ

"መቼ ነው ለመጀመሪያ ጊዜ ያወቅከው?" እንዴት ብዬ እንደምጠይቀው ግራ ገባኝ ብቻ ገብቶታል። አይኑን ቡዝዝ አድርጎ

"ከአባቴ ሞት በኋላ አባቴን እንደገደልኩት ሳስብ ለሳምንታት ዲፕረስድ ሆንኩ::" እያለኝ እህቱ መጣች

ምንድነው ያለው? አባቴን ገድዬው ነው ያለው? ገድዬው ሲጥ ገድዬው?

አሁንም በድጋሚ አልጨረስንም

@wegoch
@wegoch
@paappii
ልንጋባ ሁለት ሳምንት ሲቀረን እጮኛዬ ጤነኛ እንዳልሆነ አወቅኩ (ክፍል አራት)

"አባትህን እንዴት አድርገህ ነው የገደልከው?" እንዲህ ተብሎ አይጠየቅም! "ቅድም አባቴን ገደልኩት ነው ያልከኝ?" ይሄም ያው ነውኮ! "ቅድምኮ እንዴት መጀመሪያ እንዳወቅክ እየነገርከኝ ...." ኤጭ ምንድነው የምቀባጥረው?

ወደ መኝታ ከመሄዴ በፊት ሽንት ቤት ሆኜ ጥርሴን እየፋቅኩ ነው ፊልም ላይ እንደሚያወሩት ብቻዬን የማወራው። የራሱ ጉዳይ በቃ "አባትህ ምን ሆነው ነው የሞቱት?" እለዋለሁ። እሱ አፉን ሞልቶ አባቴን ገድዬ ሲል ያልተሳቀቀ እኔ ምን ያሳቅቀኛል? ውይ እሱ ወሰድ ያደርገዋል ለካ!

"ስለአባታችን እባክሽ እንዳታነሺበት!" ትለኛለች ይህቺ ደግሞ ከሽንት ቤቱ ስወጣ ጠብቃ

"ለምን?" ያልኳት እንደመጣልኝ ነው

"ለእሱ እጅግ በጣም መጥፎ ትዝታው ነው። ሰላም እደሪ!" ብላኝ እብስ ልትል .... አባቴን ገድዬ ካለኝ ሰውዬ ጋር ደግሞ እንዳታነሺበት ብላኝ ደህና እደሪ ? ቀልድ ነው?

"እሺ አንቺ ንገሪኛ? አባቴን እንደገደልኩት ሳስብ እኮ ነው ያለኝ!"

"ኦ ኖ ኖ እንደሱ አይደለም! (ዘገነናት) ፔር ማንም ላይ እጁን የሚያነሳ ሰው አይደለም! ኦህ ማይ ጋድ ጭራሽ አታውቂውም አይደል? (ቆይ እዚህ ቤት ታዲያ ምን ትሰሪያለሽ? በውል እንኳን የማታውቂውን ሰው ነው አገባዋለሁ ብለሽ ቀን የቀጠርሽው? የሚል ለዛ ነው ድምፅዋ ያለው።) በጥቂቱ አፈርኩ። የምርም አላውቀውም!

"ስለዛ ቀን ለማንም አውርቶ አያውቅም በትክክል በቦታው የተፈጠረውን ከግምት ውጪ ማናችንም አናውቅም። ፔር በ20 ዓመቱ የዩንቨርስቲ ተማሪ እያለ ነበር። አባታችን ከጓደኞቹጋ አሳ ሊያጠምዱ ሲወጡ አብሬ ካልሄድኩ ብሎ ወጣ ስምንት ሆነው ነው የሄዱት። መጥፎ ወጀብ ነበር። መርከባቸው ከዓለት ጋር ተጋጭታ ተሰባበረች። እኛ የምናውቀው የእርዳታ ሰጪ ሰራተኞቹ ሌሎቹን ማትረፍ ሲችሉ አባቴን ማትረፍ አለመቻላቸውን ነው። 'ላድነው እችል ነበር ገደልኩት' እያለ ይቃዥ ነበር። ከዛ ውጪ ለማንም ቃል ተንፍሶ አያውቅም።" አለችኝ

ዝም አልኩ። መተንፈሴን የሚያስጠረጥር ዝምታ ዝም አልኩ። የሆነ ነገር የተጫነብኝ ቁመቴ ሁሉ ያጠረ መሰለኝ።

"እንደማታፈቅሪው አውቃለሁ። እውነት ለማውራት እኔም አልወድሽም! ግን እባክሽ ወንድሜ በቂ ስቃይ በህይወቱ የተሰቃየ ሰው ነው። አትጨምሪበት! ደህና እደሪ!!" ብላኝ በቆምኩበት ጥላኝ ወደ ክፍሏ ሄደች። እግሬን እየጎተትኩ መኝታ ቤታችን ገባሁ። በጎኑ ተኝቶ ኩርምት ብሏል። ቶሎ አልጋው ላይ አልወጣሁም።

"እባክሽ እንደሱ አትዪኝ" አለኝ በዛ እንባ ሳይወጣው ለቅሶ ባለው ድምፁ

"እንዴት አድርጌ አየሁህ?" አልኩት ቅስስ እያልኩ አንሶላውን ገልጬ እየገባሁ

"ልክ ጊዜውን ጠብቆ እንደሚፈነዳ ፈንጂ .... ከጥፋት ውጪ ምንም ፍፃሜ እንደሌለው።"

"እንደሱ አልነበረም ያየሁህ!" አልኩት ልክ እንደሱ በጎኔ ፊቴን ወደሱ አዙሬ እየተጋደምኩ።

"እኔ እስከማውቀው ከራስህ አልፈህ ለሀገርህ የምትተርፍ ጂኒየስ ነህ! አንተ በሰራሃቸው ሶፍትዌሮች ምክንያት ብዙ ስርአጥ ስራ አጊንቷል። ብዙ ድርጅት አትርፏል። የብዙ ሰዎችን ህይወት አቅልለሃል አንተን ከጥፋት ውጪ ሌላ ፍፃሜ እንደሌለው ሰው ማየት እንዴት ይቻላል?"

(በሙያው IT ኢንጂነር ነው። የምሬን ነው ያልኩት ከIT ቴክኖሎጂጋ ተያይዞ ያለው እውቀትና ፈጠራ የምርም ለሀገር የተረፈ ነው።)

"ውሃው ቀዝቃዛ ነበር። ጨለማ ነበር። ሁላችንም የእርዳታ ሰራተኞቹ እስኪደርሱልን ነፍሳችንን ለማትረፍ እየታገልን ነበር። እንደምንም በህይወት ለመቆየት ጭንቅላቴን ከውሃው በላይ አድርጌ እየዋኘሁ ነበር። እሱም ነፍስ ይዞት ለመትረፍ ሲፍጨረጨር እግሬን ይዞኝ ለመትረፍ መታገል ጀመረ። እግሬን በጎተተኝ ቁጥር እኔም እየዘቀጥኩ ለመሞት መሽቀዳደም ሆነ። እግሬን አስለቅቄው ነፍሴን ለማዳን መዋኘት ጀመርኩ። በሰዓቱ ራሴን ከማዳን ውጪ ስላለው ነገር አላሰብኩም። በኋላ ላይ እግሬን ያስለቀቅኩት አባቴ መሆኑን አወቅኩ።"

ይሄን እያወራኝ ይበልጥ ኩምትር አለ። እንባው ትራሱ ላይ ተከታተለ። አቀፍኩት። ድምፅ ሳያሰማ ህቅ ሳይል ሰው ይሄ ሁሉ እንባ እንዴት ይወጣዋል? አብሬው አለቀስኩ።.... ለምን እንዳለቀስኩ እንኳን ሳይገባኝ ፍቅፍቅ ብዬ አቅፌው አለቀስኩ .....

አሁንም በድግምጋሚ አልጨረስንም

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ልናጋባ ሁለት ሳምንት ሲቀረን እጮኛዬ ጤነኛ እንዳልሆነ አውቅኩ (ክፍል አምስት)

አንድ ህቅታ ሳያሰማ እቅፌ ውስጥ ሆኖ ትኩስ እንባው ክንዴን ያርሰኛል። ለምን እንዲህ ሆድ እንደባሰኝ አላውቅም። የሚያስለቅሰኝ የሱ ለቅሶ ይሁን የራሴ ውጥንቅጥ ሁላ አላውቅም። ግን መቼ እንዳለቀስኩ የማላስታውሰውን ለቅሶ ከሱ የባሰ ተንፈቀፈቅኩ።

ምን አለ ሀላፊነት ባይኖርብኝ? ምናለ ጠዋት ተነስቼ ጨርቄን ማቄን ሳልል መጥፋት ብችል? ምናለ ድሀ ባልሆን? ምንለ የሆንኩትን ሁላ ባልሆን? ምናለ ከነጭራሹኑ እኔን ባልሆን?

“የቱ ይብሳል? " አልኩት ሁለታችንም ከለቅሷችን ጋብ እንዳልን

"ከምኑና ከምኑ?"

"ከሜኒያው እና ከዲፕረሽኑ?" (የበሽታው ሁለቱ የስሜት ፅንፍ ኢፒሶዶች ናቸው)

"ሁለቱም ያው ናቸው። አንደኛው አይንሽን የሚያጠፋ ብርሃን ሌላኛው የሚያደናብር ድቅድቅ ጨለማ ናቸው። ሁለቱንም ጊዜ ራሴን አይደለሁም። የማታዢበት ጭንቅላትና ሰውነት መያዝ ምን ያህል ዋጋ ቢስነት ነው?" አለኝ ከእቅፌ ሸሽቶ በጀርባው እየተኛ ፊቱን ወደኔ መልሶ አይን አይኔን እያየ።

ለደቂቃዎች ዝም አልኩ። እንባውን ለመዋጥ ሲታገል የሚንቀጠቀጥ ከንፈሩን ልስመው ፈለግኩ ግን ደግሞ የባሰ የሚታዘንለት ፍጥረት እንደሆነ እንዲሰማው አልፈለግኩም።

"ግንኮ በብርሃንህ ወቅት ብዙ ነገር ትሰራለህ። እራሱን እንደማይቆጣጠር ሰው አይደለህም።" አልኩት ከልቤ

"አ..ዎ...ን (ዝቅ ባለ አቅመ ቢስ በሆነ ስሜት አይኑን ቡዝዝ አድርጎ) ችግሩ የቱጋና መቼ ከልክ በላይ እንደሚሆን አታውቂውም። የሆነኛው ቀንና ቦታ ላይ የልኩን መስመር አልፋለሁ።" አለኝ

በማንባት ያበጡ አይኖቹን ተራ በተራ ሳምኩለት። ከንፈሩን ልስመው ከንፈሬን ሳንቀሳቅስ የእንባው ጨው ጨው የሚል ጣዕም ምላሴ ላይ ደረሰ። እንባውን ነው የቀመስኩት .....ሀዘኑን ነው በምላሴ ያጣጣምኩት ..... የዘመናት ሰቀቀኑን ነው ከምራቄ አዋህጄ ምላሴ ላይ ያጣጣምኩት .... .....እናም የዋጥኩት .... እናም የተዋሃድኩት ....... ሆዴ እርብትብት አለብኝ።

ከንፈሩን በስሱ ስሜው ደረቱ ላይ ጋደም አልኩ። የቀመስኩት ሀዘን ..... የዋጥኩት ሰቀቀን ..... ያጣጣምኩት እንባ ....... ድጋሚ ያነፋርቀኝ ጀመር። በተራው እሱ ደግሞ ደረቱ ላይ በሁለቱም እጆቹ አቅፎኝ ለኔ ይሁን ለራሱ እንባውን አብሮኝ አፈሰሰው። ደክሞን እንቅልፍ በዛው ይዞን ሄደ።

እንዲህ እንደሚሆን ባውቅ ላገባው እወስን ነበር? እንዲህ እንደሚሆን ባውቅ ወደ ኖርዌይ እመጣ ነበር? እንዲህ እንደሚሆን ባውቅ የግብዣ ወረቀቱን ልላክልሽ ሲለኝ እሺ እለው ነበር? እንዲህ እንደሚሆን ባውቅ ኢትዮጵያ ለሁለተኛ ጊዜ ሊያየኝ ሲመጣ ቤተሰቤን አስተዋውቀው ነበር? ልጄን አሳየው ነበር? እንዲህ እንደሚሆን ባውቅ ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ሊያየኝ ሲመጣ ለጓደኞቼ አስተዋውቀዋለሁ? ኸረ ቀድሞውኑ እንዲህ እንደሚሆን ባውቅ ስልኬን እሰጠው ነበር?

ዱባይ ነው የተዋወቅነው። እሱ ከሆነ ሶፍትዌር ካምፓኒ ጋር የስራ ውል ኖሮት። እኔስ? እቁብ ጥዬ ተጣጥዬ በአንዲት ጓደኛዬ ምክር እና ምሪት ከዱባይ እቃ አምጥቶ ለመሸጥ ተከትያት ሄጄ!

ስንሸማምት ውለን የሆነኛው ቦታ ቡና ልንጠጣ ባረፍንበት። ቡናውን ከምትቀዳው ሴትዮ ተቀብዬ በቁሜ ስኳር ስጨምር

"ኦውውው .." የሚል ድምፅ ሰምቼ ዘወር አልኩ።

"ይሄ ሁሉ ስኳር ለአንድ ብርጭቆ ቡና ገርሞኝ ነው ይቅርታ" አለኝ። ፈገግ ብዬ ዝም አልኩት።

በሚቀጥለው ቀን አንደኛው ሞል ውስጥ ከጓደኛዬ ጋር ክልው ክልው ስል ድጋሚ ተገናኘኝ።

"Ohh hey Sugar lady" አለኝ

አለ አይደል ጓደኛህን አጊንተህ "አንተ ከንቱ አለህ በናትህ ?" ምናምን እንደምትለው አይነት ምን የሚሉት አጠራር ነው አሁን ይሄ

"ሄይ" አልኩት ቆም ብዬ ... በእጄ አንድ ሀገር እቃ ተሸክሚያለሁ። 'ላግዛችሁ?' ብሎ የተወሰነ እቃ ተቀበለን። ማታ እራት ሊጋብዘኝ ሲጠይቀኝ እንደሀበሻ ሴት መግደርደር አልነበረብኝም? ቢያንስ ላስብበት አይባልም?

አይባልም! የፈረንጅ ቆንጆ ነው .... በዛ ላይ ሰውነቱ.... በዛ ላይ ..... ምንም ምክንያት አያስፈልገውም። በቃ አብሬው እራት መብላቱን ፈልጌዋለሁ!!

እራት ስንበላ ስለብዙ ነገር አወራን። ስለስራው .... ስለሀገሩ .... ሀገሩ ስለሚያመርተው brown cheese ሳይቀር አወራልኝ። (የትኛውም ኖርወጅያን ይሄን ካልጠቀሰላችሁ የተወጋ ኖርዌጅያን ነው)።

ጨዋነቱ ደስ ሲል ..... በረራው የዛኑ እለት እኩለ ለሊት ነበር።

"እንዴት ላግኝሽ?" ሲለኝ ስልኬንም ... ሜሴንጀሬንም ... ዋትስአፔንም .... የሰይጣን ነገር አይታወቅም እሱም ባይሰራ የቤት ስልክ ... ድንገት ሰይጣን እጅግ ሲከፋና ይሄም ካልሰራ ፖስታ ሳጥን ቁጥሬም ሳይቀር ሰጠሁት።

ለወራት በርቀት ስናወራ ፎቶ ስንለዋወጥ ከቆየን በኋላ ሊያየኝ መጣ።

የአዲስ አበባ አስፓልቶች ላይ ተመናቀርኩ። ድህነት ላይ ዘበጥኩበት። ብቸኝነት ላይ ተቁላላሁበት ::

አስቡት ፈረንጅ ሆኖ ቆንጆ .... ቆንጆ ሆኖ ሀብታም ... ሀብታም ሆኖ ውጪ የሚወስድ ያውም ከነ ልጅሽ ልንከባከብሽ የሚል ..... ዋናው ነጥብ የአልጋው ልፋት ላይ ሌላ የማያስመኝ ለፊ ... በምንም የማይገኝ ስብጥርኮ ነው።

ህም .......

ስብጥሩ እብደት እንደሚቀላቀልበት ባውቅ ኖሮ ይሄን ሁሉ እርቀትስ እሄድ ነበር?

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ልንጋባ ሁለት ሳምንት ሲቀረን እጮኛዬ ጤነኛ እንዳልሆነ አወቅኩ (ክፍል ስድስት)

"በፍፁም እኔ አይኔ እያየ የሀብትህ ተካፋይ አታደርጋትም!" ብላ ያዙኝ ልቀቁኝ አለች እህትየው።

"ለምን?" አላት ኮስተር ብሎ

"ይሄን እንዴት ማየት ያቅትሃል? አትወድህም!" ብላ ተንጨረጨረች። ቀና ብሎ ትርጉሙ ያልገባኝ አስተያየት አይቶኝ

"ንብረቱ የኔ አይደል? እኔ ልወስንበት! አይሻልም እህቴ? " ብሏት

ምንም የሚቆረፍድ ነገር እንዳልተወራ እኔም እንዳልሰማሁ አስመስሎ የበረዶ ሸርተቴ ልንጫወት እኔና እሱ ልብሳችንን ደራርበን እቃዎቹን መጫን ጀመርን።

ልንጋባ ቀን ቀጥረን ነው። የጋብቻ ውህደቱ ላይ እኔን ከማግባቱ በፊት ያፈራው ንብረት ተካፋይ እንዳልሆን እህትየው ወጥራ የምትሟገተው።

እውነት ለማውራት ይሄን ጉዳይ አላሰብኩትም ነበር። ከሀገሬ ስመጣም የመኖሪያ ፈቃድ ማግኘት ከዛ ልጄን ማምጣት ከዛም ለዓመታት ስቋምጥ የነበረውን ትምህርት መማር ከዛ ቤተሰቤን መርዳት በእርሱ ሀብት ከእርሱና ከልጄ ጋር በድሎት ስለመኖር እንጂ ብፋታው ወይ እሱ የሆነ ነገር ቢሆን ስለሚለው አስቤ አላውቅም። ቢሞትስ ብዬም ያሰብኩ ጊዜ ስለ መኖሪያ ፈቃዴ እንጂ ስለሀብቱ ሽውም አላለኝ:: ሳልዋሽ ግን የእህትየው መንገብገብ እልህ አስያዘኝ።

"እህትህ አትወደኝም!" አልኩት የበረዶ መናሸራተቻውን ጫማው ላይ እየሰካን። መናሸራተቱን ከዚህ በፊት ሁለቴ ሞክሬው ሁለቴም ወድቄ እግሬን ተጎድቻለሁ። ዛሬ ለኔ ብዬ ሳይሆን እርሱን ደስ እንዲለው ነው አብሬው የወጣሁት። ሰሞኑን ብዙ ነገር ለእርሱ ብዬ እያደረግኩ ነበር:: አላውቅም:: ብቻ ደህና እንዲሆን እፈልጋለሁ::

"አንቺን ስለማትወድሽ አይደለም እኔን ካንቺ በላይ ስለምትወደኝ የተጠነቀቀችልኝ መስሏት ነው!" አለኝና አወሳሰበብኝ።

"እኔ ስለንብረትህ አስቤ አላውቅም ታምነኛለህ? እሷ እንዳለችው ብታደርግም ቅር አይለኝም" አልኩት።

"አምንሻለሁ። እውነቱን ሳወራሽ እሷ ጉዳዩን እስካነሳችበት ሰዓት ድረስ እኔም ብንለያይ ወይም ብሞት የሚለውን አስቤው አላውቅም!" አለኝ

መንሻራተቱን ጀምረነው ስለነበር መደነቃቀፌን ጀመርኩ። ቁልቁላቱ ላይ ልንደርስ ስንቃረብ ከነመንሸራተቻዬ አዝሎኝ ቁልቁለቱን ተምዘገዘገ። እጮሃለሁ .....ይስቃል ...... እስቃለሁ ደግሞ እጮሃለሁ። የሚያየን ሰው ፈገግ እያለ .... የሚያውቁት ደግሞ ሰላም እያሉት እንተላለፋለን። ቁልቁለቱን ስንጨርስ ተያይዘን በረዶው ላይ ወደቅን።

ከብዙ ቀናት በኋላ ጥርሱ እየታየ ሳቀ:: ክፉ ደግ እንደማያውቅ ህፃን ፍልቅልቅ ብሎ ሳቀ!! ኩርምት ብሎ አራት ሳምንት ጉልበቱን አቅፎ እንዳልተኛ ሰው ሳቀ ........ ከአራት ሳምንት በፊት ራሱን ሊያጠፋ እንዳልነበረ ሰው ሳቀ .........

ድንገት ሳቁን አቁሞ ደንግጦ እያየኝ "ምነው ምንሆነሻል?" ሲለኝ ነው ሳቁን እያየሁ እንባዬ ሳያስፈቅደኝ ጉንጬ ላይ እየተንከባለለ እንደሆነ ያወቅኩት

"ምንም አልሆንኩም ደስ ብሎኝ ነው። የደስታ እንባ ነው አልኩት::" እንባዬን እየጠረግኩ።

ገብቶታል። ፈገግ እያለ እጄን ተቀብሎኝ ውስጥ እጄን ሳመልኝ።

"አፈቅርሻለሁ!" አለኝ እጄን ደጋግሞ እየሳመ። ዝም አልኩት። ከዚህ በፊትም እንዲህ ሲለኝ ምንም መልሼለት አላውቅም። እንድመልስለትም ጠብቆ አያውቅም። ዛሬ ታዲያ ለምን ጨነቀኝ? ለምን የበደለኝነት ስሜት ይሰማኛል? ልቤ ላይ አየር ያጠረኝ አይነት የማፈን ስሜት .... ልነግረው ነበር .... ምን እንደሚሰማኝ አላውቅም ልለው ..... እህትህ ያለችው እውነቷን ነው ልለው ..... አላፈቅርህም ነበር አሁን ግን ላፍቅርህ አላፍቅርህ አላውቅም ልለው ነበር ....... አፌን ስከፍት ቶሎ ብሎ በሌባ ጣቱ ከንፈሬን ከደነው

"ተይ እንዳትይኝ!" አለኝ ዝም አልኩትና ከንፈሬ ላይ የጫነውን ጣቱን ስሜው

"እሺ እንነሳ!" አልኩት። ተመልሰን መኪናችንጋ እስክንደርስ ምንም ሳናወራ እሱ በመንሸራተቻው እኔ በጫማዬ ተጓዝን። እቤት ደርሰን ሻወር ሊወስድ ሲገባ እህቱ ሳሎን ተቀምጣ መፅሃፍ እያነበበች ነበር። አጠገቧ ተቀመጥኩ። ምን እንደምላት አስቀድሜ ያሰብኩት ነገር አልነበረም።

"ቃል እገባልሻለሁ እሱን የሚጎዳ ምንም ነገር አላደርግም!" አልኳት። የሆነ ከአፌ እስኪወጣ እየጠበቀችው ያለ ነገር ይመስል ስግብግብ ብላ ተጠመጠመችብኝ።

"አመሰግናለሁ። አመሰግናለሁ ። አመሰግናለሁ" ብዙ ጊዜ አለችኝ ጭምቅ አድርጋ ይዛኝ።

ቤተክርስቲያን ፀሎት አድርሶ አንደሚመለስ ሰው ያለ ስሜት ...... ለካህን ሀጢያቱን ተናዞ እንደሚመለስ ሰው ያለ ስሜት ..... ተቀበለኝ። ወደ መኝታ ቤት እየሄድኩ ለእሷ ያልኳትን ለራሴ ደጋግሜ እያልኩ ነበር

"ምንም ቢሆን የሚጎዳው ነገር አላደርግም!!" ከኋላዬ ገብቶ የመኝታ ቤቱን በር ሲዘጋው ወደርሱ ዞርኩ። ፎጣውን ወገቡ ላይ አሸርጦ የረጠበ ፀጉሩን ወደ ኋላ እየላገ በስድ አይን እያየኝ ነበር። እንዲህ ካየኝ መቼ ነበር? ወር? ስድስት ሳምንት? እኔንጃ ..... ዘልዬ እጄን አንገቱ ላይ ጠምጥሜ በእግሬ ወገቡን ዞርኩት። "

ምንም ቢሆን የሚጎዳህ ነገር አላደርግም እሺ!" እያልኩት አንገቱን .... ትከሻውን .... ጸጉሩን ... ጆሮውን ያገኘሁትን ቦታ እስመዋለሁ! ያልኩበት ስሜት ገብቶት ይሁን አላውቅም እየደጋገመ

"አውቃለሁ! አውቃለሁኮ" ይለኛል። መልሼ ነግረዋለሁ መልሶ "አውቃለሁ" ይለኛል።
ያሸረጠው ፎጣ ተፈታ (አይበቃችሁም እንዴ ምንድነው?) ለፍተን በጀርባችን እንደተጋደምን።

"ፔሬድሽ መምጣት አልነበረበትም?" አለኝ:: ቆጠርኩ .....ከተጋደምኩበት ብንን እንዳለ ሰው ተስፈንጥሬ ተነሳሁ

"ኦህ ኖ !" አልኩኝ። ተስፈንጥሮ ተነሳ

"በፍፁም! በፍፁም አይሆንም! በፍፁም እንደእኔ አይነት ልጅ እንዲወለድ አልፈልግም።" እንዲህ ጮሆብኝ አያውቅም። ሁኔታው አስደነገጠኝ!!

ህመሙ በዘር እንደሚተላለፍ ያነበብኩት ትዝ አለኝ።

እህእ አልጨረስንማ ታዲያ

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ታክሲዋ ከታክሲነት ወደ ክለብነት ተቀየረች ።
በጃቦኒ ሆኖ መሪውን የሚዘውረው ሹፌር ድራፍት ማዘዝ እስኪቀረው ድረስ ቧረቀ።
ጭራሽ አንድ ሞቅ ያለው ተሳፋሪ ተነስቶ እንደመደነስ ሁሉ ቃጣው ።
ይህን ጊዜ አንድ እድሜያቸው የቆጠረ.. .በጉልምስና እና እርጅና መሀል የተጣዱ አባት ... "ሹፌር ኸረ ሙዚቃውን ቀንስልን በመድሀኒያለም " አሉት ጮክ ብለው።
ሹፌሩ እቴ!
እንኳን ሰው የጮኸበት ዝንብ ያረፈበት እንኳ ሳይመስለው ሸመጠጠ። ባልሰማ ላሽ አላቸው /ሰምቶዋቸውም ሊሆን ይችላል :) /
ሽማግሌው "ሹፌር ሰማኸኝ? " አሉ ቀጥለው ።
ዝም!
በዚህ ቅፅበት ታድያ አንዲት እናት ቱግ ብለው "ደግሞ ደህና ብብት እንዳለው ሰው በካኒቴራ ይዝናናል " ብለው አንጓጠጡ ።
እውነትም የሹፌሩ ብብት ያሳቅቃል ። ወደ ቡኒ መልክ ያጋደሉ ጠጉሮች ብብቱን ሞልተውታል ።
"ሰውዬ የእንጦጦ ጫካን በብብትህ ይዘህ ነው እንዴ የምትዞረው? ... ፓርኩ ግን አይታየኝም " አለች አንዲት ዘመናይ ሴት ለጥቃ ።
ለሽማሌና አሮጊቷ ሀፍረት ይሁን ንቀት አድሮበት ዝም ብሎ የነበረው ወያላ ...
"ዝም በይ አንቺ ፔሬድ የላሰች ውሻ " ብሎ ሞሸለቃት ።
እግዚኦ ሀበሻ ይሄ ሁሉ የስድብ ማህደር ተሸክሞ ነው የሚዞረው ? እስክል ድረስ ታክሲዋ ወደ 7ተኛ ሰፈር ተቀየረች።
የቡና ቤት ሴቶች ራሱ ይሄን ያህል ሲሰዳደቡ አይቼ አላውስም።
በመሀል ሽማግሌው.. .የመኪናዋን መስኮት ከፈት አድርገው
"ፎሊስ ይሄ ዋልጌ ሹፌር አስቸገረን" ብለው አንባረቁ። ሹፌሩ ወታደር ፖሊሱን ባላየ ሸልቅቆ ሊያልፍ ሲል አስቆመው ።
"ችግርህ ምንድነው? " ብሎ ሹፌሩን ተቆጣው።
"አብርሮ ሊደፋን ነው ልጄ! ይሄ ሰው ፓይለት ነው ወይስ የታክሲ ሾፌር ?" ብለው ጠየቁ አሮጊቷ።
"ምን ይሄ ብቻ ይሄ የጁንታ ርዝራዥ የሆነ የቀን ጅብ አልደመርም ብሎ ሲፎክርና ሲያሽላላ ነበር " ብሎ ቀጠለ አንዱ ስጋው በላዩ ላይ አልቆ የሞገገ ነፍሰ ቀጭን ሰውዬ :)
የሌዘር ጃኬቱ ላዩ ላይ ነትቦ በኗል።ይሄን ጭማሪ ወሬ ከየት አምጥቶ እንደሰካው እንጃ!
ይህን ጊዜ ወታደር ፖሊሱ ሹፌርና ረዳቱን እንደኳስ አንጠባጠባቸው ።
"ፎሊስ!" ብለው የተጣሩት ሽማግሌ የወታደሩ ርግጫ ጠንከር ማለቱን ሲረዱ ...
"አይ ፎሊሱም አበዛው ቆለጣቸውን ሊያበረው ነው እንዴ? " አሉ በለሆሳስ ።
"ሰውዬ ዝም በሉ ...አለበለዚያ ዱላው ወደ እርሶም ይዞራል " ሲላቸው ቀጭኑ ሰውዬ ሁላችንም ኩምሽሽ ብለን ተኮማተርን።
ወታደሩ ረግጦ ካስገባቸው በኋላ...
"ችግር ካለ ቁጥሬን ያዙ " ብሎ ሳናገር አቃጣሪው ሰውዬ ስልኩን አውጥቶ መጠቅጠቅ ጀመረ ።
በራፕ ሙዚቃ ሲያደናቁረን የነበረው ሹፌር ከባምቢስ እስከ ሜክሲኮ ድረስ በበዛወርቅ ትዝታ ሙዚቃ አጅቦን ደረሰ።
እኔ በመሀል ወታደሩን ሰውዬ የት እንደማውቀው ስብሰለሰል ቆይቼ የልጅነት ጓዴ ቦቄ ስለሆነ ሰላምታ ሳልሰጠው ማለፌ ቆጨኝ።
ቦቄ ከመዋዕለ ህፃናት ጀምሮ እስከ ስምንተኛ ክፍል ድረስ አብሮኝ የተማረ ልጅ ነበር ።
ሜክሲኮ እስክንደርስ ድረስ ሹፌሩ ባጉረመረመ ቁጥር ቀጭኑ ሰውዬ ስልኩን እያወጣ ሲያስፈራራውም ነበር።
መዳረሻ ቦታችን ደርሰን ሁሉም ተሳፋሪ ከወረደ በኋላ ሹፌሩ ጮክ ብሎ.. .
"አንተ አቃጣሪ ያደረከው ቆዳ ሌዘር አንተ ላይ የቆየውን ያህል በሬው ላይ አልቆየም። ሾክሿካ " ብሎ ተሳደበና አቅጣጫውን አዙሮ ተፈተለከ ።
እኔ ቀጭኑን ሰውዬ ተከተልኩት ። ልክ ከስሩ ስደርስ.. .
"ወንድም " ብዬ ተጣራሁ.. .
"አቤት "
"እባክህን የቅድሙን ወታደር ስልክ ቁጥር ስጠኝ። የልጅነት ጓደኛዬ ነበር " አልኩት ...
ነፍሰ ቀጭኑ ሰውዬ ለረዥም ደቂቃዎች ከትከት ብሎ ሲስቅ ከቆየ በኋላ.. .
"ሹፌሩን ላስፈራራ እንጅ ስልክ ቁጥር መመዝገብ አልችልም " ብሎ ኩም አደረገኝ :)

...ሚካኤል አስጨናቂ ....

@wegoch
@wegoch
@paappii
ልንጋባ ሁለት ሳምንት ሲቀረን እጮኛዬ ጤነኛ እንዳልሆነ አውቅኩ
(የመጨረሻ ክፍል)

ልጄን ወይ እወልደዋለሁ ወይ አስወርደዋለሁ። ምርጫ ነው። ህይወት ራሱ የምርጫችን ውጤት አይደል? ልክ እሱን ማግባት አለማግባት ራሱ ምርጫዬ እንደሚሆነው?

"ተገላገልሽ!" ትለኛለች ያቺ ታይላንዳዊቱ ወዳጄ ጠርታኝ። ሁለታችንም የምናውቀው አንድ ምግብ ቤት ባለቤት የሆነ ሰውዬ ያለሁበትን ሁኔታ ነግራው ሊያገባኝ እና ሊረዳኝ እንደሚፈልግ እየነገረችኝ።

"ለምን ሊረዳኝ ፈለገ?"

"ምክንያቱ ምን ያደርግልሻል? የመኖርያ ፈቃድሽን አይደል የምትፈልጊው? ደሞ አሪፍ እድል ነው። ካልፈለገች አብራኝ አለመኖር ትችላለች ብሏል። ቅረቢውና ከወደድሽው አብረሽ ትሆኛለሽ። ካለበለዚያ በቃ ለመኖርያ ፈቃድሽ ሲባል የውሸት ጋብቻ ይሆናል ማለት ነው።"

(እዩት እድሌን ግን ... ይሄ እድል ስፈልገው የት ነበር? ዛሬ ስለፔር ማሰብ ስጀምር .... ራሴን የማልመልሰው ርቀት ያህል ከሄድኩ በኃላ ነው የሚረዳኝ ሰው የሚገኘው? የት ነበር? )

"አልፈልግም" አልኳት ሳስብ ቆይቼ

"እና ከእብድ እጮኛሽ ጋር መጋባቱ ይሻልሻል?"

"ሁለተኛ እብድ እንዳትዪው!" ብዬ ዘልዬ ተነሳሁ

"ኦ ማይ ጋድ ፍቅር ይዞሻል" አለችኝ በጣም የተገረመች መስላ

አልመለስኩላትም። ትቻት እየሄድኩ የወሰንኩት ውሳኔ ይቆጨኝ እንደሆነ አስባለሁ። ህይወት ራሱ የምርጫችን ውጤት አይደል? እሱን መረጥኩ። ምርጫዬ የሚያፈራው ፍሬ መራራም ይሁን ጣፋጭ ..... እሱን መረጥኩ::

"ማውራት አለብን!" አልኩት እቤት እንደገባን

"እሺ" አለኝ።

"ልጃችን የባይፖላር ተጠቂ ላይሆን የሚችልበት እድልምኮ አለው" አልኩት::

"ሊሆን የሚችልበት እድልም ሰፊ ነው።"

"እሺ ባይሆንስ?"

"ዜሮ ምናምን ነጥብ ቢሆን እንኳን የመሆን እድሉ በፍፁም በፍፁም ልጄን እኔ የማልፈውን ስቃይ እንዲያልፍ አልፈቅድም።"

"እሺ እኔ ልጄን ማስወረድ ባልፈልግስ?"

"እባክሽ እዚህ አጣብቂኝ ውስጥ አትክተቺኝ። እባክሽ?" አለኝ

ዝም አልኩ። ወሬውን ከዛ በላይ መቀጠል አልፈለግኩም። ተጨማሪ ጥያቄ ብጠይቀው የሚመልሰውን መልስ ፈራሁት። ወይ ልጄን ወይ እሱን መምረጥ አለብኝ:: ልጄን መውለድ እፈልጋለሁ ብለው መጋባቱ ይቅርብኝ እንደሚል እንኳን ልቤ እያወቀው .... እሱ የምርጫው አጣብቂኝ ውስጥ ላለመግባት እኔን እንድመርጥ እያስገደደኝ እንደሆነ እንኳን እያወቅኩ እሱን መረጥኩ!! .... ደግሞም ልጄስ እሱ እንደፈራው አባቱ የሚያልፈውን ሰቀቀን የሚደግም ቢሆንብኝስ? ከአንድ ልጄ ውጪ ሌላ ልጅ መውለድ ብፈልግም አልወልድም።

እሱን ማግባት የሚያስከፍለኝን በሙሉ አሰብኩት። አለማግባቱም የሚያስከፍለኝን አሰላሁት። ከእርሱ ጋር መሆን ብዙ ያስከፍለኛል። እንደዛም ሆኖ ማድረግ የምፈልገው ከእርሱ ጋር መሆኑን ነው።

"እሺ!" አልኩት በመጨረሻ

"እሺ ምን?" አለኝ ከአፌ የሚወጣውን ለመስማት እየጓጓ

"እሺ ልጅ አይኖረንም ግን አንድ ነገር ቃል እንድትገባልኝ እፈልጋለሁ!"

"ምንም ይሁን ምንም!.... ምንም ነገር!!" አለኝ በደስታ እያቀፈኝ

"መድሃኒትህን መቼም ቢሆን ሳታቋርጥ እንደምትወስድ ቃል ግባልኝ።"

"ቃሌ ነው።"

ሰርጋችን በቤተክርስቲያን እንዲሆን የመረጥኩት እኔ ነኝ። ቄሱ ፊት ቆሜ አይን አይኑን እያየሁት

"በህመሙም በጤናውም በድህነቱም በሃብቱም ........" ብዬ እየማልኩ እህቱን አያታለሁ ለሚያያት ሰው ግድ ሳይላት እንባዋን ትነዳዋለች።

ጨርሰናል!!!!!

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
መሳቅ ሽቼያለሁ። መንከትከት ፈልጌያለሁ። ነገር ግን ለሐሴት፣ ለተድላ፣
ለፍስሓ፣ ለፈገግታ ምክንያት አጥቼያለሁ። ከንፈሬን መግለጥ ከብዶኛል።
ሰውነቴ በጭንቀት፤ አእምሮዬ በሐሳብ እንደበገና አውታር ተወጥሯል።
ከብፌ ላይ በተርታ እንደሚወድቁ የሸክላ ሳህኖች ከወለል ላይ ልጋጭ
ተዘጋጅቼያለሁ። እንዲህ ማን እንዳስቀመጠኝ አላወቅሁም።
ደግሞ





ት ነው።
ደግሞ

ት ሊለኝ ነው።
ደግሞ እንደ ቅል




ጥ ነው።
ደግሞ እንደ ገል




ር ነው።
ደግሞ ሕመም እንዳዘለ፤ በቤት ውስጥ እንግዳ ሲመጣ ውኃ
እንደሚጠጣበት ያማረ ብርጭቆ ከእጅ ወድቄ


ቅ ልል ነው።
ከክርስቶስና ከገብርኤል ጋር በዕንባ ተራመድሁ። ሰው ነኝና የመለኮት ቋንቋ
አይገባኝም። ልሳናቸው ሐምራዊ ቀለም ይዞ እንደዥረት ይፈስሳል።
“ምናለበት የሚያወሩት ቢገባኝ?!” እላለሁ። ደጋግሜ የማልደርስበት ቦታ
ላይ ስለበላኝ ቁስል እነግራቸዋለሁ። “ክርስቶስ ሆይ በላኝ እኮ!”
“ገብርኤልዬ አሳከከኝ እኮ!” በዕንባ እንደጨርቅ የራሱ ዓይኖቼ
ይንከላወሳሉ። ሸንበቆ አንገቴ ሊሰበር ደርሷል። ሕፃን ነኝና የትልቅ ሰው
ጨዋታ አይያዝልኝም። የሚሰሙኝም የማይሰሙኝም ይመስለኛል። ጮክ
ልበል ይሆን? ልንጠራራ ይሆን? ዓይኔ እስኪጠፋ ላልቅስ ይሆን? ወይስ
እምነት ማን ያበድረኛል? የቱ ደገኛ ነው የሚጨምርልኝ? አለማመኔንስ
የሚረዳው?
የፈሰሰን ውኃ በጸሎት ማፈስ ይቻላል? ወደ ሕዋ አንጋጥጬ የማጣትንና
የማግኘትን በር አየሁ። አንዱ ጥርቅም ተደርጎ ተዘግቶ፤ አንዱ ወለል ብሎ
ተከፍቷል። እየበረርኩ “አንኳኩ ይከፈትላችኋል…” እንደተባለ እንዲሁ በሩን
ዘበዘብሁ። ለእኔ ጸሎት ሄጄ የሰው ለቅሶ አየሁ። ሰዉ ያለቅስ የለ እንዴ? …
አለቃቀስ አይቼ የዚህ ሰውስ በእምነት የሚደረግ ታላቅ ልመና ነው
አልኩኝ። በቀትር የቤተክርስቲያን ደጅ ላይ ተንበርክኮ በዓይኖቹ ክረምትን
የሚያውጅ ሰው ምንጭ ዕንባዬን አሳፈራት። ሰው ከለቀስተኛ ጋር ያለፈቃዱ
ተነክቶ እንዲያለቅስ እንዲሁ ከጸሎተኛ ሰው ጋር ዳር ይዤ አለቀስሁ።
መጠለያ ፈለግኩ። የስቃዬ ቀን ረዘመ። መቅኔው እንደተመጠጠለት
አጥንት ባዶ ሆንኩኝ። በዋጋ ቀለልሁኝ፤ በሕመም ከበድኩኝ። ሰው ፈልጌ
ሰው አጣሁ። ማን ጋር ልደውል? ከማን አንደበት አጽናኝ ቃል ልስማ?
በምሄድበት መንገድ ዕንባዬ ከቁጥጥሬ ውጪ ፈሰሰ። ረዥም መንገድ
ለብቻዬ ሄድኩኝ። በጣም ረዥምምም ጎዳና በሌጣ እግሬ ተጓዝሁ። ቤት
ስደርስ ደክሞኝ ብተኛ… ፎጣ ብሆን ብዬ። መንገዱ አጥሮ ዕለቱ ረዘመ።
እንደሰከረ ሰው ተንገዳገድሁኝ። በደረቅ ሌሊት እንደ ልጅ ባነንሁኝ። ወደ
ግድግዳዬ ዞሬ እስከሚነጋ በደካማ ቃላት ልመናዬን ያዝኩኝ። እየጸለይኩ
እንቅልፍ ወሰደኝ። ማለዳ በሕመም ተቀበለኝ። አዲስ ልብስ ገዛሁኝ።
ገላዬን ታጥቤ አንድ በአንድ ለበስኩኝ። መስታወት ፊት ቆምኩኝ።
እንዳማረብኝ ግን እንደከፋኝ አየሁ። መንገደኛ ይላል “ዛሬ አምሮብሃል” ።
ሁሉም ሰው ከውጪዬ እንጂ ከውስጤ አይደለም። እና ሌላውስ ሰው
እንዴት አድሮ ይሆን? ጎዳና ላይ ሽር ብትን ከሚለው፤ ቂቅ ብሎ ከለበሰው
መሃል ስንቱን ሰው ከፍቶታል?
መንገዱን ተሻግሮ ነጭ ግርማው የሚያስፈራ መልአክ የሚመስል የቀትር
ሠይጣን ይደንሳል። ከሁኔታው ያለለት፤ አንዳችን ነገር የሰመረለት
ይመስላል። ጠጋ ብዬ እጠይቃለሁ።
“ምን አግኝተህ ነው?”
“ሕልምህን ታውቃለህ!” ይለኛል።
“ደስ ከሚላቸው ጋር ደስ ይበላችሁ እንዲል እንኳን ደስ አለህ!” እለዋለሁ።
ደስ እንደማይለኝ እያወቀ፤ ለይስሙላ ያልኩትን ይዞ “እንኳን አብሮ ደስ
አለን!” ይለኛል።
“ብቻ ግን…”
ዳንሱን አቁሞ “ ብቻ ግን ምን??? ” ሲል ይጠይቃል።
“ብቻ ግን ደስታህ እንደሚቀጥል ርግጠኛ ሁን!” ብዬው አልፋለሁ።
ይስቃል። ሠይጣንስ ማን አለው? ሥራው ምንድነው? ማነው የቀጠረው?
ምናገባኝ!
የጭንቅ ወዳጆቼ “ተሥዬልሃለሁ! ” “እጸልይልሃለሁ እና ደግሞ ቅዳሜና
እሁድ አገኝሃለሁ” “በታመምኩበት ወቅት ስለሆነ የጸለይኩልህ የምሰማ
ይመስለኛል” “እጸልይልሃለሁ ... እና ደግሞ ሁሉም ያልፋል። በምድር
እንዳያልፍ ሆኖ የተፈጠረ ኅዘንና ችግር የለም።” ይሉኛል።
ከራሴ ጋር እነጋገራለሁ።
“እስኪያልፍ እንዴት እሆናለሁ?”
“ሕፃን ነህ እንዴ? እደግ እንጂ! ”
የምር መሳቅቅቅቅ በጣም ፈልጌያለሁ። ግን አልቻልኩም። እንዴት ብዬ?
የጠፋብኝን ፍለጋ ብዙ በር ያለማቋረጥ አንኳኳሁ። ደበደብሁ። እና
ያጠያይቃል። ማለት ጠፋብን ያልነው ነገር ባንኳኳነው የበር ብዛትና
የድምፅ ኃያልነት በኩል ምን ያህል እንደፈለግነው ይረዳል? ወይስ እርሱን
ፍለጋ ባንኳኳነው የበር ብዛትና ድምፅ ይረበሻል? እና እያንኳኳሁ እጄ ዝሎ፤
ድምፄ ሰልሎ፤ እንዲያው መሳቅ እንዳማረኝ እ'ደጁ ላይ ተኛሁ።
በእንተ ኅዙናን ወትኩዛን ናስተበቁዕ ከመ እግዚአብሔር ይናዝዞሙ ፍጹመ።
(እግዚአብሔር ፈጽሞ ያረጋጋቸው ዘንድ ስላዘኑና ስለተከዙ ሰዎች
እንማልዳለን።)


©እሱባለው አበራ

@wegoch
@wegoch
@Mahletzerihun
"ጳውሎስ ሆስፒታል እንሂድ" አልኩ፡፡ ስልኩ ከመዘጋቱ በፊት የሀኪም ቤቱን ስም ከርቀት ሰምቼው ነበር፡፡ " ግን እኮ አለርት ሆስፒታል ይቀረበናል" አለኝ አንድ ጎረቤታችን " ወንድሜ እዛ ነው ያለው እዛ ውሰዱን" አስካሁን እንባዬ ማቆሚያ አላገኘም፡፡ ' እንዴት ግን ወንድሜ እንደሆነ አሰብኩ? አባቴም ቢሆን ሹፌር ነው፡፡ እንዴ! ሌላ ዘመድስ ቢሆን?' የማይፈታ እነቆቅልሽ ለራሴ እየጠየኩ ሆስፒታሉ በር ላይ ደረስን፡፡ 'የድንገተኛ አደጋ ' ወደሚለው ክፍል ገሰገስኩ፡፡ እናቴን የት እንደወሰዷት አላውቅም፡፡የክፍሉን በር ልከፍትስታገል አንዲት ነርስ የተራመደች ወደኔ መጣች፡፡
"የልጁ ቤተሰብ ነህ ?" አለችኝ፡፡ መልስ አልሰጠዋትም፡፡ "በቃ እሱ ነው ፤ወንድሜ ፤ አንድ ቀን እንኳን ወጉ ደርሶኝ ወንድሜ ብዬ ያልጠራሁት ምስኪኑ ወንድሜ " ብቻዬን እንደ እብድ ማውራት ጀመርኩ፡፡ ነርሷ በየደቂቃው እየመጣች " ተረጋጋ የኔ ወንድም" ትለኛለች፡፡ ተረጋጋ ባለችኝ ቁጥር ህመሜ እንደሚብስ አልገባትም፡፡ ፊቴን ወደግድግዳው እንዳዞርኩ የክልሉ በር ሲከፈት ተሰማኝ፡፡ ፊቴን መለስ አደረኩ ዶክተሩ ጓንቱን እያወላለቀ ወደኔ መጣ፡፡ "ዶክተር የልጁ ቤተሰብ ነው" አለች ነርሷ ወደኔ እያየች ፡፡እኔ ለሰከንዶች ዶክተሩን እንደ እግዜር ቆጥሬ መልካም ነገር እንዲነግረኝ ተመኘው፡፡ "አንተ ምኑ ነህ የኔ ወንድም?" አለኝ፡፡ የሀዘን ስሜት ፊቱ ላይ ይነበባል፡፡
" ወንድሙ " አልኩ ባጭሩ፡፡
" ይኸዉልህ .....ምን መሰለህ...... ወንድምህ በደረሰበት አደገኛና አሰቃቂ አደጋ ........ሂወቱ አልፋለች፡፡ ይቅርታ በጣም አዝናለው" የቺን ቃል እንደቀላል ተናግሮ ወንድሜ ወዳለበት ክፍል እንድገባ ጋበዘኝ ፡፡ የእግሬ ኮቴ ከተኛበት እንዳይቀሰቅሰው ይመስል ቀስ ብዬ ገባሁ፡፡ ነጩን ጨርቅ ከፊቱ ላይ አነሳውት፡፡

ኬት መቶ ነው 32 አመት ያልታየኝ ቁንጅና ዛሬ የታየኝ፡፡ "የኔ ውድ ወንድም ቆንጅዬ ኮ ነህ" እንባዬ ፊቱ ላይ ይንጠባጠባል ፤ ፀጉሩን አሻሻለው "አይ አንተ አሁን እስኪ ምን አስቸኮለህ ፤ እኔ የማልጠቅመው ፤ ለአንድ ወንድሜ የማልሆን ከንቱ ሰው እያለሁ አንተ ምን አስቸኮለህ " የህመምን መጨረሻ በዚያች ቅፅበት ታመምኩ "ወንድሜ ግን ታውቃለህ ? በጣም ነውኮ ምወድህ ፤ ማርያምን በጣም ነው ምወድህ "
የ'ናቴ ድምፅ ከሩቅ ይሰማኛል
" የታል ልጄ ? ልጄ የታል ? ልጄን አምጡልኝ እህህህህህህ"
ልጇ ወዳለበት ይዘዋት ገቡ
" እሜ ልጅሽ እኮ ..........." ትንፋሼ የቆራረጣል " እሜ ልጅሽ እኮ ሸወደን ፤ ስራ ነው ምሄደው ብሎ ሸወደን ፤ ማርያምን ሸወደን እሜ " እናቴ ደም ታነባለች፡፡ አሷስ ቀን በቀን ቁርሱን አብልታ ፤ ምሳውን ቋጥራ ፤ ግንባሩን ስማ ለምትሸኘው ለጇ ደም አለቀሰች፡፡ እኔ ግን አንድ ቀን እንኳን ሰላም ዋል ሳልለው ላመለጠኝ ወንድሜ ምን ላልቅስ? ምን ላንባ? ፡፡

ዛሬ ሁለተኛ ቀኑ ነው የኔ ውድ ወንድም ከተሰናበተን፡፡ እናቴ 'እኔ አፈር ሳለብስ የኔ ልጅ አፈር አይለብስም' ብላ አላስቀብርም ብላ ነበር፡፡ ዛሬ እንደመንም ሽማግሌዎች መክረዋት እሺ አለች፡፡
የቀብር ሰአት ሲደርስ ልብሴን ለመቀየር ወደ ክፍሌ ገባው፡፡ ክፍሌ ገብቼ ከዛሬ ስምንት አመት በፊት ገና ስራ እንደያዘ በመጀመሪያው ደሞዙ በሌለው ገንዘብ የገዛልኝን ጅንስ አወጣውት፡፡

አይገርምም ደሞዙ 400 ብር ነበር፡፡ 'የመጀመሪያ ደሞዜ ነው ለራሴ አንድ ነገር ላድርግበት' ሳይል 200 ብር ተበድሮ ለኔ ሰማያዊ ጅንስ ገዛልኝ፡፡ ከዚህ በፊት የልብስ ቀለም አማርጬ አላውቅም፡፡
ያን ቀን ግን ለዘላለም የማይጠገን ስብራት ወንድሜን ሰበርኩት፡፡

ከስራ ደክሞት ነበር የመጣው፡፡ ወደቤት ሲገባ ግን ሙሉ ፈገግታን ተላብሷል፡፡ ብረት ሲያቀልጥና ሲቀጠቅጥ የዋለ አይመስልም ነበር፡፡ ፊቱ ግን እሳት የለበለበው
ለብቻው ቅርፅ ይዞ ያስታውቃል፡፡
እናቴ ፤ አባቴና እኔ ክብ ሰርተን ተቀምጠናል፡፡ ወንድሜ ነጫጭ ጥርሶቹን እያሳየ ገባ፡፡
"ሰላም አመሻችሁ" ፈገግታው አልተለየውም ነበር፡፡
"እግዚሀር ይመስገን እንዴት አመሸኽ" አባቴም እናቴም እኩል መለሱለት እኔ ግን ፊቱን እንኳን ቀና ብዬ አላየውትም፡፡
" እሜ......... ዛሬ የመጀመሪያ ደሞዜን ተቀበልኩ ፤ በመጀመሪያ ደሞዜ ደሞ......... ከሚቀጥለው ወር ደሞዜ ላይ 200 ብር ተበድሬ ለወንድሜ ጅንስ ሱሪ ገዛውለት" አላት የደስታ እንባ እየተነናነቀው፡፡
ሱሪውን ከፌስታሉ እስኪያወጣው ቸኩሎ ነበር፡፡ እናቴ የምርቃት ናዳ ታወርድበታለች፡፡ እኔ ግን አሁንም አልዞርኩም፡፡ ፌስታሉ አልፈታም ሲለው ቀዶ አወጣው፡፡ የሱሪውን ወገብና ወገብ ይዞ "ወንድሜ እየውማ አያምረም? ብታይ እኮ 600 ብር አልሸጥም ብሎኝ ጉልበቱ ላይ መውደቅ ነው የቀረኝ
ላለቅስ ሁላ ነበር" አሁንም አይኑ እንባ አቅርሯል፡፡ "ሰማያዊ ጅንስ ከመቼ ጀምሮ ነው ሳደርግ አይተኸኝ ምታቀው?" መለስኩ፡፡
ፊቱ ከብርሀን በቅፅበት ወደ ጨለማነት ተቀየረ፡፡ ማንም ሰው ምንም አልተናገረም፡፡ በቆመበት ጥዬው ወደ ክፍሌ ገባሁ፡፡
ታዲያ በምድር እንደኔ አረመኔ ሰው ይገኛል? በፍፁም አይገኝም፡፡
የትኛው ወንድም ነው ወንደሙ ላይ የዚን ያህል የሚጨክን? ፤ የትኛው ወንድም ነው ወንድሙ እጁ እስኪላጥ ብረት ቀጥቅጦ ያመጣለትን ስጦታ የሚንቅ? ኸረ እኔ ሰው አደለውም፡፡ ሰው ብሎ ሚጠራኝም ካለ ሰውነት ምን እንደሆነ አልገባውም ማለት ነው፡፡

ጥቁሩን አውለቄ ሰማዊውን ጅንስ መልበሴ ሰውን ሁሉ አስገርሞታል፡
የመጣው ሰው ሁሉ "አሁን ይሄ ወንድም ነው? እንዴት በቀብር ቀን ሰመያዊ ይለብሳል?" እያሉ በሹክሹክታ ያሙኛል፡፡ በማንም ግን አለፈረድኩም ምክንያቱም የምፈርድበት አንደበት የለኝማ፡፡

የወንድሜ እሬሳ በሰው ለቅሶ ታጅቦ ፤ በእናቴ የደም እንባ እየተመራ ቤተ ክርስቲያን ደረሰ፡፡ ስርአቱ ከተፈፀመ ቡኃላ ወንድሜ አፈር ለበሰ፡፡እኔም አረመኔው ወንድሜን በእንባ ሸኘውት፡፡

ይሄ ሁሉ ከሆነ እንሆ ስምንት አመት ሆነ፡፡ ከዛ ሁሉ ህመም ቡኃላ በወንድሜ ሱፍ ተመርቄ በምርቃቴ ቀን በወንድሜ ሱፍ አገባሁ፡፡ እናም ከስምንት አመት በፊት የጣልኩትን ጥቅስ በድጋሚ በፍሬም አሰርቼ ከግርግዳችን መሀል ለመሀል ሰቀልኩት፡፡

""""""""""'""""
""""""!! ሁሉም ያልፋል!!""""''''"
""'''"''"""""""""

፡ የጌትነት ልጅ ፃፈ

@wegoch
@wegoch
@paappii
2024/09/23 18:28:10
Back to Top
HTML Embed Code: