Telegram Web Link
((Maggie))

(ቆንጅዬ ምስቅልቅል)


አው ዝምተኛ ነኝ! ማውራት አልወድም ጋግርት የሚባል በሽታ ምናልባት አጥቅቶኝ ይሆናል......ግን አስተውላለው! የራሴን ነጥብ ይዛለው! እመዝናለው ....እገረማለው የራሴ ምለውን ልምድም ቀስማለው.... ከሞራል እና ከሀይማኖት አንፃር እያስተያየው እገመግማለው.... ቅሉ ግን .....አልናገርም!
መናገር አንድ ውድ ነገር አሳጥቶኛልና!


ብናገርስ ..ምን ዋጋ አለው!....ሸክላ አፈር ላይ እንደተርከፈከፈ እድለቢስ ውሀ ...ወደ ውስጥ ሳይሰርግ ይቀራላ! ወይ ደግሞ ጭስ በሚወጣባት የቆርቆሮ ቀዳዳ በምታክል ቅንጣት ሽንቁር .......... (ሁሉን በፍቅር ወደሚመረምረው) ልብ ሳይሆን.......... (በስሌት ና ብዜት ወደ ሚመረምረው አዕምሮ) ዘልቆ ገብቶ የተናገርኩትን ሰው ...........ካልኩት ነገር ላይ ሸካራና ሚዋጋ ነገር እየፈለገ መልሶ በንግግሬ ያስገዘግዘኛል....ከዛ ልምከር ልዝከር ባልኩት አፌ መልሶ 'ምነው አፌን በቆረጠው!' ያስብለኛል.

ከተወሰነ ግዜ ወዲህ(በተለይ አንተን ካጣው ወዲህ).........ተናግሬ ካተረፍኩት እፍኝ ነገር ይልቅ ዝምታዬን ተከናንቤ ያተፍኩት ጋን ሙሉ ነገር በልጦ አጊንቼዋለው. መሆን ግን የለበትም ነበር ....

አምላክ ለሁላችንም አንድአንድ አዕምሮና አፍ ያደለን ለብቻችን አስበን ከዛ በአፋችን ተነጋግረን ደግሞ በጋራ እንድናስብ ነበር. ዳሩ ግን ምን ዋጋ አለው........ ምንጣፉን ለአቧራው ብለህ ብትመታው .... ነገሩን ጠምዝዞ ባለ10 አቋም መጥፎ ነገር እየደረደረ ሲወቅስህ ታገኘዋለህ!

በርግጥ ሰው ከሰው ጋር ብቻ አያወራም! ከራሱ ጋር ..ከመፃህፍት ገፀባህርያት ጋር...ከተፈጥሮ ጋር... ከአምላክ ጋር... ከጥበብ ጋር ....ካሀሳቡ ጋ...ከብዙ ነገር ጋር ያወራል... ግን ደግሞ ይህ ነገር ሲበዛ ከተፈጥሮ ህግ ውጭ የመሆን እድሉ ይሰፋል.....
...
...
ለምትወደው ሰው ስህተቱን እንደመሸፈን ያለ መጥፎ ስጦታ የለም. እውነቱን ስትነግረው ትገነባዋለህ.... ታንፀዋለህ... ተመልሶ እንዳይደፈርስ ታጠራዋለህ.... ከእብቅ ማንነቱ ትለየዋለህ.. ... እንደተሳሳተ እያወክ ዝም ያልክ እንደሆነ ግን እየቀበርከው ነው...

ሰው አድጎና ተምሮ አላለቀም....እስኪሞት ድረስ ያድጋልም ይማራልም!.......

ከስተትህ ጋር ስላልተባበርኩ ብትጠላኝ ግድ የለኝም! ለምን እንደሆነ ታውቃለህ?? ከህሊናዬ ጋር ሰላም ፈጥሬያለውና. ብየንስ እዳ የለብኝም....... ሞራህ ተገፍፎልህ....." ልክ አልነበርኩምኮ!" ብለህ ስትፀፀት ያኔ እኔን አትወቅስም........ ድርሻዬን ተወጥቻለዋ!

ፍቅር እውነትን ትከተላለች
............................

እራስህን አጥርተህ ብስብስ ቦታ ብትቆም መልሰህ መበስበስህ አይቀርም........... እኔም ስህተትህን ባልነግርህ ኖሮ ትክክል ነኝ በሚል ትምክህት ዛሬንም ትቀጥል ነበር... እና ብዙ ነፍሶችን ትቀጣና ትበድል ነበር........

በዚ ምክንያት መቼም የማልረሳውን ነገር ተናግረህ ይኸው ዝምታን እንድማርጥ አድርፈኸኛል.....

"መቼም አፍቅረሺኝ አታውቂም!"

የእስከዛሬ መሰበሮቼ ቢሰሉ ይህንን አያክሉም!........ምላስ በሁለቱም በኩል እንደተሳለች ሰይፍ ነች! ትሰብራለችም ትጠግናለችም! .... እኔንም ሰብራኛለች.. .....
ለዛውም ካንተ ከማፈቅርህ ሰው አፍ የወጣ ሲሆን ደግሞ ስብራቱ ባስር ይባዛል...........

ነገር ግን ለምላስህ መርዝ ማርከሻ ልቤ ውስጥ ዘመን ማይሽረው ፍቅር ትተህ ሄደሀል....

አየህ እንዲ ፍቅርህ እያመመኝ እንኳ....... ከቃላት በላይ የሆነው ፍቅር ከልቤ እንዳይነቀል እየፀለይኩ ነው.

ከዚ ሁሉ ነገር ግን
አንድ ነገር አስተምረኸኛል....
ዝምታን!....

ሲያርር ሲከስል ሲጨማለቅ እውነት ከግርጌ ውሸት ከራስጌ ስትሆን... ውጥንቅጡ ሲወጣ.... ዝምምምምምምን ማለትን!

የዘመመውን ለማቃናት አፌን ልከፍት ስል...... ልቤ ውስጥ እንዳይጠፋ የምሳሳለት ፍቅርህ ይይዘኛል.

እናም......... ዝምተኛ ነኝ ... ጋግርታም!.....ባንተ ምክንያት ዝምምምምምምም እላለው! ..........

የዝምታን ትልቅነት ህይወት ምትባል ቅጧ የጠፋት መምህርት አንተን ሰጥታ በመንሳት በደንብ አስተምርኛለች!

እናም አዎ ዝምተኛ ነኝ!

@wegoch
@wegoch
@paappii
ከዕለታት በአንዱ ናፍቆትህ በፀናብኝ ቀን እንዲህ ሳስብ ዋልኩኝ። ፀሐዬ ዮሐንስ "ጊዜው ይርዘም እንጂ ማየት አይሻለሁ ሞት ካለየኝ በቀር በህይዎት እያለሁ" እያለ ያዜማል ሙዚቃውን ለምን ያህል ጊዜ እንደሆነ ባላውቅም፡ ቀኑን ሙሉ ስሰማው ዋልኩኝ። ከእኔ ባልሆነ እና በማልቆጣጠረው ስሜት እየደጋገምኩት። እንዲህ ባለ ፍቅር ውስጥ መኖር የምርም መታደል ነው። ሁሉም ይሄን ስሜት አጣጥሞ ኖሮት ለማውራት ላይበቃ ይችላል። ከልብ የመነጨ ፡ ጊዜ እና ርቀት የማይገድበውን ዕውነተኛ እና ሲወራ አፍ ላይ የሚጣፍጠውን ልብ የሚያሞቀውን ፍቅር! እደለኛነት ተስምቶኛል። በመሀል እንዲህ ሲል ደግሞ "ቀኑም አይመሽ አንቺን ሳላዎሳ በፍቅርሽ ታስሬ ቆጠርኩኝ አበሳ" በንዴት መሀል ፣ በኩርፊያ እንኳን ፣ በብስጭት ውስጥም ሆነን እናወራቸው የነበሩትን ነገሮች ፡ በቀን ውስጥ ለምናምነኛ ጊዜ በትውስታዬ ውልብ እያሉ ፈገግ ያደርጉኛል አንዳንዴም እያስገረሙኝ ፡ ብቻ አንተን ሳላስብ ፡ አንተን ሳላነሳህ አልውልም። ልቤን በሚያሞቀኝ በራሴ ፈገግታ ፈገግ እያልኩኝ ስምህን በለሆሳስ እያንቆለጳጵስኩ እጠራሃለሁ። ዓይኔ ላይ ስምህና ምስልህ የለተጠፈ ይመስል አንድም ቦታ አላጣህም እኮ ደሞ እንዲህ ብሎ ሲያዜም "ካንቺ ተለይቼ ደስ ብሎኝ አልኖርም ዓለም ካንቺ ጋር ናት አለዚያም አታምርም" በኩርፊያ እና በፀባችን ወቅት ከተማ ውስጥ አንድም ሰው ሊወደኝ የሚችል እንደሌለ እስኪሰማኝ ድረስ ይከፋኛል። ስናወራ ፣ ስንስቅ ፣ ነገኣችንን ስናወራ ትላንት የነበሩትን እያነሳን ስንስቅ እንደምትወደኝ በጆሮዬ ስሰማ ፣ እንደምወድህ ስነግርህ ፣ አይን ለአይን እየተያየን በደስታ ያወራንባቸውን ጥቂት ቀናት ሳስብ ደሞ ዓለም ላይ ደስተኛ እና ዕድለኛ ፍጡር ያለ እኔ ያለ አይመስለኝም! ልባዊ ፍቅር ፣ ከነፍስ የሆነ ፍቅር ሙዚቃው ቀጥሏል "በዓይኔም አያሳየኝ ያንቺን ክፉ ለኔ ቀድሜሽ መሞት እመርጣለሁ እኔ ምነው ተለያይተን እኔ ምጨነቀው እባክሽ ነይና መኖሬን ልወቀው " በመራራቅ ውስጥ ያለ ሀያል ፍቅር ፣ በየቀኑ መተያየት ፣ በየሳምንቱ መገናኘት በሌለበት ፡ ተስፋ የተሞላ ልባዊ ፍቅር ውስጥ ሆኜ ክፉህን እንዳያሰማኝ የምፀልይባቸው ቀናት ብዛታቸው ብታይ። ዛሬም ልክ ትላንት በነበረው መውደድ እወድሃለሁ!

መልካም ምሽት

@wegoch
@wegoch
@paappii

#ጠርሲዳ ከበደ
ልብ እና ብል

((Maggie))

አያውቅሽም አታውቂውም... አጋጣሚ አስተያያቹ እንበል..... ወደደሽ ተመሰጠብሽ..... በህሊናው,,,,,,,,,ፍቅረኛው ሆነሽ...ፈልም ላይ ሚሆኑትን ሁሉ ሆናቹ... አግብቶሽ... አሁንም ፊልም ላይ ሚሆኑትን ሁሉ ሆናቹ... ወልደሽለት... በሰላም ስትኖሩ እስክንጃጅ! ሚለውን የወንዲ ማክን ዘፈን ራሱ ለራሱ ጋብዞ የሌለ ምስጥ ብሎብሽ ,,,,,,, ራሱን ሳለው.... ፈገግታውን እንደንጀራ ፊቱ ላይ አስፍቶ ቀረበሽ..... ተለሳልሶ አንጀትሽን ለመብላት ሲሞክር... ተኮሳተርሽ.... አመናጨቅሽው... ተስፋ ሳይቆርጥ ሞከረ ደገመ ደጋገመ..... እውነት መስሎሽ... ጥርስሽን ከፈትሽለት.... ጭንሽን አንደምትከቺ ተስፋ በማድረግ ጥረቱን ቀጠለ.... ገፋበት... የሌለ ሰመጥሽ.... የሌለ ሰመጠ..... ውዴ ማሬ ካንተ ሌላ ካንቺ ሌላ ተባባላቹ.... እቅዱን ነገረሽ...አመንሺው..... ...እንደሱ አይነት ወንድ ስለሰጠሽ ቤተስኪያን ሄደሽ ሻማ አበራሽ.... ለጓደኞችሽ እንደምትወጂው ልታገቢው እንደምትፈልጊ ተናገሽ.... ተቃቅፋቹ ተሳስማቹ እየሳቃቹ የተነሳቹ ፎቶዎች ታግ እያደረግሽ ፌስቡክሽ ላይ ለጠፍሽ... አይለያቹ..ያዝልቃቹ... ስታምሩ.. ኮመንት ጎረፈ.... ወራት ነጎዱ..... በሰርፕራይዝ እና "አታምኚኝም? አትወጂኝም?" ሰበብ ከአንጀትሽ በታች ያለውን አስበላሽ... .. በጣም ስለምትወጂው ትመክሪዋለሽ መውጫ መግቢያውን ትቆጣጠርያለሽ.. ስልክሽን ሳያነሳ ሲቀር ትጨነቂያለሽ... ቴክስት ሳይመልስ ሲቀር ልትሞቺ ትደሻለሽ.... መላ አንቺነትሽን ሰጥተሽዋል... ከሀሳብሽም አይወጣም..... ትጋባላቹ... ምርጥ ግዜ ታሳልፋላቹ... ... ጫጩት ያስፈለፍልሻል.... ለቤትሽ እና ለጫጩቶችስ ራስሽን አሳልፈሽ ት አጭያለሽ......በዚ መሀል
...ሰውዬሽ ሌላ ታሪክ ውስጥ ገብቷል... ኦቨር ቁጥጥርሽ ተጨናቂነትሽ ለልጅና ቤትሽ ብለሽ አፈር መምሰልሽ... እንደድሮው አለመኳኳልሽ የወተት... የት/ት ቤት....የሽንኩርት.. አምጣ ማለትሽ ይሰለቸውና... ፈታ ያለች ፍለጋ ይመርሻል..... የድሮው ባህሪው ለምን ተለወጠ ብለሽ ትብሰከሰኪያለሽ... .. ልትጠይቂው ስትይ በንዴት ይመልስልሻል..... ግራ ይገባሻል ትናደጃለሽም ግን ምንም አታደርጊም....ጫጩት አለሻ!...... ቀስ ብለሽ የልጃገረድ ሽቶ ልብሱ ላይ ማሽተት ትጀምሪያለሽ.... ገንፍለሽ ስትጠይቂ....ትናቂያለሽ... ..... በፍቅር የሞቀው ልብሽ ወደ ብልነት ይቀየራል.... የቀረሽ ብቸኛ ፍቅር የልጅሽ ብቻ ነው......

የ"ልብ" ሆሄያት ቦታ ይለዋወጡብሽና ከግዜያት ቦሀላ

ፍቺ ፈልጋለው ትያለሽ ከሰውዬሽም ከራሱ ፍቅር ጋርም!

@wegoch
@wegoch
@paappii
ወንድ ብሆን ኖሮ!
((Maggie))

ወንድ ብሆን ኖሮ..ምን እንደማደርግ ታውቃላቹ??? የወንደላጤነትን ኑሮ በነፃነት መኮምኮም!..

ሌላሌላውን ተውትና(መረር ምትለዋን ማለቴ ነው) ያለተገደበ ነፃነት ውስጥ መዘፈቅ ነው ምፈልገው!

ለምን አላቹ? ...ጥሩ.... አንደኛ ነጠላ ነኝ..... ሁለተኛው እስካሁን ያልተነቀለልኝ መንፈስ...i am toooo lazy!
...ሰነፍ ነኝ.. እርቦኝ ለመብላት ም ሰንፍ.....
ለስካሁኑ ነጠላነቴ ይህ ስንፍናዬ ትልቅ ቦታ አለው...... .....ስልክ ተቀብሎኝ አንድ ዛግ ብሎ የፈረደበት ተባዕት... .. እናላቹ...ደወለ.... ለማንሳት ሰንፌ ይኸው የማታ እንጀራዬ ተዘጋ....ለነገሩ እንኳንም ቀረውበት..... ጨጓራው ይከዳው ነበር( ፀጉሩ ከከዳው ቦሀላ!)

ስንፍና ሚባል ዛር ከነዘመዶቹ የሰፈረባት ሴት በዛ ላይ ቦሰሮ( ሙያ የሌላት)በነፃነት መኖር ምትችልበት መንገድ ይኖር ይሆን......ብዬ
ከእንቅልፍ በተረፈኝ ግዜ ሳስብ..... የሰነፍ ነገር..... ምኞትን! ማይሆን ምኞትን! አስቤ ቁጭ...... ወንድ ብሆን ኖሮ!

ጎረቤት ቤቴ በመጣ ቁጥር የተበታተነውን የማስቲካ ልጣጭ...... የተበላበት ሰሀን.... ሶፋላይ ድብርድልብስ......ሶፍት..... ማበጠርያ..... ካልሲ.... ጡት ማስያዣ... ዶክመንት...ምናምን.... አይቶ ...ፊቱን ቁጥር አድርጎ "ምነው ምነው ምነው! ሴት አይደለሽም እንዴ??? ፀዳ ፀዳ አታደርጊውም" ከሚል አስተያየት 100ጫማ ከ2ካልሲ መራቅ!

ጠዋት ረፋዱ ላይ ከቁርባን የተረፈ መክፈልት ለበረከት ብለው ሊሰጡኝ በሬን ከሚቆረቁሩት አከራዬ ወይዘሮ ሀረጓ ... "ወይ! እንደው ምን ይሻልሻል ይይይይይይ? እንደ ሴቶቹ በጠዋት ተነስተሽ..ጉድ ጉድ አትይም!" ከሚለው ሽሙጥ ጣል ያለበት አስተያየት መዳንን ነበር ምፈልገው

በተለይ ክንዴን ሳየው!..... ወንድ የመሆን ምኞቴ ቅናትን አስከትሎ አናቴ ላይ ይወጣል.........ወንድ ስለሆነ ብቻ አብዛኛው ሰው...ሁኔታውን አይቶ "አግባ! ብታገባኮ ልክ ትገባላህ" የሚል አስተያየት ይሰነዝርለታል... እኔጋስ??????? እኔጋማ " ቆይ ስታገቢ እንዴት ልቶኚ ነው??? ሸክም?? የሴት ሰነፍስ አይጣል!! ባልሽ ግን ውይይይይ!!" ይባላል.

ቆይ ነጠላ ወንዶች ብቻ ናቸው... አልጋቸውን ለመኝታነትም ለቁም ሣጥንነትም መጠቀም ሚችሉት?.... ማነው ይህንን ህግ ያረቀቀው? እእ?....... እነሱ ብቻ ናቸው... መኮረኒ አጥበው አስጥተው አድቀው ሚቀቅሉት?? .. ... እራት በበሉበት ሰሀን ሳያጥቡ ደግመው ቁርስ መብላት ሚችሉት እነሱ ብቻ ናቸው????? ..
በላብ ብክትትት ያለን ሸሚዝ በሳምንት 7ቀን ከ5 ቀን ሚለብሱት??? ወይስ ካልሲያቸው ደርቆ ሰው እስኪፈነክት ድረስ መል በስ ሚችሉት??

ባሁኑ ዘመን affermative action ያልተወሰደበት ጉዳይ ቢኖር የነጠላ( single) ሴቶች ጉዳይ ነው. "እንደፈለጉ መኖር ይችላሉ!..... አስተያየት ሰጪዎች በሴተ ላጤዎች ኑሮ ላይ አስተያየት ስትሰጡ የአፈርማቲቭ አክሽንን ህግ ተግባራዊ ያድርጉ" ብሎ አቢቹ ማስታወቂያ መልቀቅ አለበት.

ኧረ ጎበዝ እህመነው!... መኖር አልቻልንም!...... መረረን!

በላጤ ወንዶች ስም የተከፈተ fb እድር ውስጥ (ያው በኦንላይን ማስተዛዘን ነው ብዬ ነው ኮ ግሩፕ ያላልኩት) ብገባ ይባስ እያስቀናኑ ሆዴም አባቡት... ... በሴቶች ስም ልግባ ብል.....ምናልባት አንዷ የምታቀኝ የ5 አመት ቂሟን ብትወጣብኝ ስ.... በሰው ፊት ጉድ ሆንኩ አይደል!........ ወይ እንደ አሁንስ ወንድ በሆንኩ! ኤጭ!

@wegoch
@wegoch
@paappii
የዶክተር አብይ መግለጫ!
((Maggie))

አብቹ! ተወዳጁ መሪያችን (የናንተን አላውቅም እኔ ግን ሌላው ቢቀር ጎልማሳነቱን ቀና ብሎ መራመዱንና ቀና ማሰቡን ውድድ አደረግለታለው፣፣ ያው ያለፈው ታሪካችን እንደሚሳብቅብን.. ቀና ብሎ መራመድና ቀና ማሰብ ትንሽ ሚያዳግታቸው ሙሴዎችን ነው ያሳለፍነው)

እናላቹ አቢቹ በfb እድር (የዲጂታል ወሬ ፍትፈታ ጣብያ! ማስተዛዘንንም ይጨምራል..... ማርክ ዙከምበርግ እና ጭፍሮቹ ማያመጡብን ጉድኮ የለም!.............
የርጎ ዝንብ በሆነ ዜና..........
.... የሆነ ሰሞን... የአያቴን ህልፈተ ህይወት አስመልክቶ እዝን ውስጥ ገብቼ ነበር.... ድንኳን ጥለው ...ንፍሮ ቀቅለው.. ቡና አፍልተው ጥብስን የሚያስንቁ ወሬዎች እያወሩ ያስተዛዝኑኛል ብዬ ስጠብቅ.... 'ፍቅር ፈላጊ ኳታኞችና አጋሮቻቸው' በሚለው የfb እድር( ግሩፕ!) የሀዘን መግለጫቸውን አዥጎደጎዱልኝ! ምን እላለው ታድያ ማርክን .....እእእ....ማነው ይሄ ደግሞ.. ስቲቭን ረግሜ ዝም!)

የት ነበር ያቆምኩት........

አዎ....እናላቹ አብቹ በfb እድር ስለ ሰውነቱ ማማር፣ ስለፊቱ መስታወት መምሰል ፤፤በተለይ በተለይ ስለከንፈሩ ሮዝነት ሲወራ ይሰማል. ...... ............ በተለይ አታክልት ወሀ እያጠጣ እያለ፣ አርቴፊሻል እግር ሚሰራበትን የጎበኘ ግዜ፣ መግለጫ ምናምን እየሰጠ እያለ የሚፖሰተው ፎቶ ላይ ........

"በርታ! ፣ታታሪው መሪያችን!፣
ያይናችን ብሌን ነህ!፣ ትንቢት የተነገረልህ መሪ መሆንህን እያረጋገጥን ነው!፣ የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጅ!" የሚል ኮመንት ሲጠብቅ.......

" pmዬ የዛሬው ሜካፕህ አንጀሊናን ያስንቃል! ፣ ፓ! የዛሬው አለባበስ ደግሞ እንትናን ነው ያስታወሰኝ!!፣ ምነው ማዲያትህ ፈጠጠ ?? ፓውደር አለቀብህ እንዴ!?? በዚ አድራሻ ኢሜል አርግልኝ ኦርጅናል ፓውደር ሸጥልሀለው ፣.. ዶክተርዬ የለበሻትን ቱታ የት እንደማገኛት ትጠቁሙኝ?? ......" የሚሉ ኮመንቶች ሲዥጎደጎዱ

ብልጡ መሪ ...ለምን መግለጫ አልሰጥም! በዛውም ለምርጫ ቅስቀሳ የጃጀ ወሬ ከማወራ .... የውበቴን ምስጢር ብናገር ወጣቱ ትውልድ ስለሚበዛ አሪፍ ይሆናል!" ይልና... ... ተዝኽ ለጥቆ ያለውን መግለጫው ይሰጣል


"ሰፊው የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ! ዛሬ የምሰጠው መግለጫ ስለሚስጥራዊው ውበቴ ይሆናል...... ከፍትፍቱ ፊቱ ነውና...በጠዋት ተነስቼ ነጭዱቄት በጥብጬ ፊቴን በስ ሱ ቀብቼ ለ15 ደቂቃ በእንፋሎት አጥነዋለው.. ከዛ እታጠበዋለው ቀጥሎ ባለቀው የልጄ ሹራብ አደርቀዋለው... .... .... ሚስቴ ካጠፋችው የእሳት ጥፍያ መሀል ተለቅ ያለው ክሰል መርጥና ጥርሴን ቦርሸዋለው ከዛ ቅድም ባሞቅኩት ውሀ እጉመጠሞጣለው! ንጣቱን ሰፊው ያሀገሬ ህዝብ ይገልጠው ዘንድ ትቸዋለው!

ከኩሽና ወደ ሳሎን ከሳሎን ወደ ምኝታ ቤት በመንጎራደድ ካሎሪዬን እቀንሳለው! ምድረ ዝፍዝፍ አንዳድን የሀገር ልጅ ብልሀቷ ይችው ነች ተጠቀምባት!....... በቀጣይ "አገር መሪ ስትሆን ትለብሰዋለህ" ብላ እናቴ ያስቀመጠችልኝን ልብስ አማርጬ ለብሳለው... እዚ ጋ ባለፈው የለበስኩት ቱታ የምሽቴ ስጦታ ነው!... በተረፈ ያነጋጋሪው የከንፈሬ ጉዳይ እንደሆነ ብዙሀኑ ነግሮኛል...... ይገርማችዋል.. .. በትርፍ ግዜዬ የምንከባከበው የጓሮ አትክልት አለኝ.... የሱን ውለታ በምን ቃላት መግለፅ እንደምችል አላውቀውም.... ለዚ ዝና እንድበቃ ቀይስሬ ትልቅ ሚና ተጫውቷል( ስሜታዊ ሆነው ነበር እዚጋ!) እንባቸውን ጠራርገው..... እእእ! ወደ አዘገጃጀቱ ስንገባ.... ግማሽ ቀይስር ይከተፋል በአንድ ብርጭቆ ውሀ ይቀቀላል ከቀይነት ወደ ሮዝነት እንዲያደላ ግማሽ ኩባያ ውሀ ይጨመራል.... ጣዕም እንዲያመጣ ስኳር ይጨመራል መዐዛው እንዲጣፍጥ የሚስቴን ሽቶ( ኤቭሪባዲ .....ባለህ ነው! ሉባንጃ ወይ ሰንደል አልያም ደግሞ በረሮ ማጥፊያ ፊሊትም ሊሆን ይችላል) ነስነስ አደርግበታለው...... ከዛ በቃ መቀባት........
ሰፊው የሀገሬ ህዝብ ሆይ ይህን ብልሀት ተጠቅመህ አለምን በውበትህ እንደምታስደምመው ጥርጥር የለኝም... በተጨማሪ ክሬዲቴን ምርጫ ላይ ድምጥ በመስጠት እንድትከፍለኝ በውበቴ ስም ጠይቃለው.... አበቃው!"
...

@wegoch
@wegoch
@wegoch
ሁሉንም መፅሀፎቹን አንብባለች፣ ከጥግ እስከጥግ. . .እያሰላሰለች፣ እየመረመረች. . . ከቃላቶቹ ብቻ በደንብ እንደምታውቀው ይሰማታል። እንደምታውቀው፣ እንደምታደንቀው፣ ስለግጥሞቹ ለቀናት እና ለወራት ልታወራውና ልትጠይቀው እንደምትችል አስባለች፣ ደጋግማ። የአድናቆቷን ልክ
የተረዳ ጓደኛዋ የሚያውቀውን ሰው ፈልጎ ስልኩን ሲቀበልላት ፣ የተሰማት ደስታ ልክ አልነበረውም። ስለምትቃረናቸው እይታዎቹ፣ ስለምትደግፈው እሳቤው፣ ስላስደነቃት ምልከታው ሲያወሩ ፣ ሲከራከሩ በምናቧ ትስላለች። ለመጀመሪያ ጊዜ ለመገናኘት ሲቀጣጠሩ ብቻዋን እንዳትሆን፣ አየሩም እንዲቀል ሌላ ጓደኛዋን አብራት እንድትመጣ ትጋብዛታለች። ካፌው ሲደርሱ ተቀምጦ አገኙት፣ ሰላምታ ተለዋወጡ፣ ተቀመጡ። አይኑ ወዲያውኑ ጓደኛዋ ላይ ሄደ። ለሚቀጥለው አንድ ሰአት አይኑ ተሳስቶ እንኳን እሷ ጋር አልተመለሰም። በህይወቷ ለመጀመሪያ ጊዜ የማትታይ የማትዳሰስ የሌለች አካል እንደሆነች ተሰማት። አየሩን በእሱ ድምፅ
ሞላው፣ አንዳንዴ አይኑን ከጓደኛዋ ሳይነቅል “እናንተስ?” የሚል ጥያቄ ይወረውራል፣ ምናልባት የጓደኛዋን እንጂ የእሷን መልስ ለመስማት ፍላጎት እንዳልነበረው ለማወቅ ግን የጠፈር ተመራማሪ መሆን አልነበረባትም። ትንሽነት ተሰማት። ወንዶች እሷን አልፈው ሌላ ሴትን ሲያዩ የመጀመሪያዋ አይደለም። ለምን የእሱ እንደዚህ ጎልቶ ታያት? በሀሳቧ ትልቅ አድርጋ ስለሳለችው ነው? ያደነቀችው ስለስራው ነው እንጂ ስለወንድነቱ አይደለም። ፍራንዝ ፋኖን ስለ “gaze of desire” እና ራሳችንን እንዴት በሌሎች የመፈለግ ምልከታ ውስጥ እንደምንመዝን የፃፈውን አስታወሰች። እንዲያ የጓጓችለት ቀጠሮ ረዘመባት፣ ቶሎ እንዲያልቅ ተመኘች። ጨርሰው ለመሄድ ሲነሱ እንዲፈርምላት ይዛ የመጣችውን መፅሀፍ መልሳ ቦርሳዋ ውስጥ ከተተችው። የምትወዳቸውን ፅሁፎቹን እንደድሮው በንፁህ እና ክፍት ልብ አነባቸው ይሆን? ብላ አሰበች። ባታገኘውስ ኖሮ? አሁንም የሌሎች “gaze of desire” እሷን አልፎ ሲሄድ ታያለች፣ ታጠናለች።

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Hewan Hulet Shi🖤
ቢራ ቢሮ
ደብዳቤ
.
.
.
ሁሉም ነገር ያለዉ ጭንቅላቴ ዉስጥ መሆኑን እያሰብኩ ዳግም ከራሴ ጋር እቃረናለሁ፤ ትዉስታዬ ቢሰወር እይታየ ቢደበዝዝ መገለጥህን እናፍቃለሁ። አጠገቤ ስትቆም የልቤ ምት ከገላዬ አልፎ እንዲሰማ በዜማህም እንደ ቅጠል መወዛወዜን አዉቃለሁና። ጠረንህ ማህሌት ቆሞ እንዳደረ ካህን ያዉደኛል፤ ይሄ ከብሩህነት የረቀቀ ስሜት እንደምን ያለ ተኣብ ነዉ? ነፍሴ አንተን ትሻለች፦
ባታምንም እንኳ እንዲያ አስባለሁ፣ ምንምን መዉደድ የሚቻለዉ ከነፍስ ወዲያ ምን አለ? ባዶነትህ ጥላ ያለዉ እኔም ላይ ታጠላብኝ ዘንድ የወደድሁ፣ በነፍሴና በአእምሮዬ መካከል የተፈጠረዉ ተቃርኖ ያላጠፋኝ፣ ይልቁን መፃረርን ሸሽተዉ ተደጋግፈዉ ያቆሙኝ ያህል ይሰማኛል። ምንምነትህን ወድጄ ስዉር የእግሮችህን ዳና ተከትዬ ይሄም ረቆብኝ በአንተ ዘልቄ ጥላህን መንካት ሲቻለኝ፤ ይህን የጠረን ዳና ከወዴት ነዉ የማዉቀዉ? አልኩኝ፤ የደራ ቀዬ መሀል ቆሜ ከግርግሩ እንኳ ፈቀቅ አላልኹ፤ ታዲያ በሞሳነቴ የማዉቀዉ የደብር እጣን ከወዴት አወደኝ? ይሄስ እንዴት አያስተኣጅብም? ለብዙ ቀናት ባለሁበት ቆሜያለሁ፥ ከቆምኩበት ሳልዘንፍ ክረምት አልፎ ሄዷል፣ እልፍ ተሲያቶች አዝግመዋል፣ በመንገዱ ላይ የተሻገርኩ
ሳይሆን ጊዜም ጎዳናዉም ባለሁበት አልፈዉኝ የተሻገሩ እስኪመስለኝ።
.
.
.
አይኖቼን ስገልጥ ፀሊም ነፋሴ ሆይ ብዬ ጠራዉህ። ወደ አላወቅሁት አለም ወስደህኛልና መገለጥን አስተምረኸኛልና ይህ እንዴት ድንቅ ነዉ ብያለሁ። ለዚህም የኔታዬ ነህ ኦ ረቢ!
.
.
ከሄድኩበት አለም ስመለስ አጠገቤ የነበሩት አበቦች አንገታቸዉን ደፍተዋል ቀለማቸዉም ደብዝዟል። በከናፍሮቼ እንዳልነካኋቸዉ በጣቶቼ መዳበስን
ነፈግኋቸዉ፣ አፋፍ ላይ ወጥቼ የፀሀይዋን መዉጣት እንዳልጠበቅሁ ሰባራ ጉቶ ላይ ተቀምጨ ግባቷን እንዳልቃኘሁ ከዉበቷ ይልቅ ደም የለበሰ አስፈሪነቷ አስበረገገኝ። እኩለ ሌ'ት መስኮቴን ከፍቼ የጨረቃዋ ፀዳል ባህሩ ላይ ሲያርፍ ባህሩም በጨረቃ መሳምን ናፍቆ ማዕበሉን ፀጥ ሲያደርግ እንዳላየሁ፦ ይህ እንዴት ያለ መፍዘዝ እንዴት ያለ ድኩም ብርሃን ነዉ ብዬ ተሳለቅሁ። ከወጣሁበት ተራራ ስወርድ ምቾቴን ሸምቼ በእጆቼ የጨበጥኩትን ረገጥኩ።
.
.
ህልም አለምኩ ጥቁር ህልም ከህልሜ ስነቃም እሸሸግህ ዘንድ ሮጥኩ፡ ነፋስን
ማምለጥ እችል ይመስል፤ ቁልቁል ነፍሰህ በላዬ ስትረብ በዝምታዬ ዉስጥ
እንዲህ አንሾካሾኩ፦ ነፋስን መከተል አለመስከን፣ አለመርጋት የያዙትን መልቀቅ፣ ከደርዙ ለመቆም ትላንትን መርሳት። እናም ነፋሴ ሆይ እንዳሻህ ተመላለስ፤ ነፍሴ በመቅደስህ ሽቶ መዓዛ ትታወድ። ትርምስህም ዉስጥ ልጥፋ ሁለመናህን እንዳይ ደግሞም ምንም አልወቅህ፣ ገላዬ እንዲቀልጥ፥ ጠፍቼም እንዳልቀር ህያዉ እንድሆንም። ከእኔ ርቀህም ሂድ ወደ ጥልቁ፤ እንድታመም ባንተ መሻርን እንድናፍቅ። አይኖቼም ዙሪያየን ይቃኙ በአበቦቹም ፍካት ደስ ልሰኝ፣ ጨረቃም በእኩለ ሌ'ት የባህሩን ከንፈሮች ትዳብስ፤ ማዕበሉም ፀጥ ይበል፣ እኔም ፍቅርን ላቃስት፣ በመሄድህም አልጉደል በመምጣትህም አልሙላ ረቢ ሆይ።
*//*******
~ያንተዉ ቢራቢሮ
ታህሳስ 18 /2013
አዲስ አበባ

@wegoch
@wegoch
@paappii
Meri is back!!

★★ ስንቴ ገረዝኩት? ★★
(ሜሪ ፈለቀ)


"አንቺማ አትገርዢኝም። በስመአብ! " አለ እያማተበ ለመቀመጥም ለመነሳትም በቀረበ አኳኋን አየሩ ላይ ተንጠልጥሎ።

"አየር ላይ ነህ፣ አረፍ ትል?" አልኩት አኳኋኑ ሳቄን እያመጣው

"የታለ ዶክተሩ ከምር? " አለኝ ወንበሩ ላይ ተስተካክሎ እየተቀመጠ

"እኔ ነኝ!!" አልኩት ምን እንደሚያስብ ለመገመት እየሞከርኩ

ካርዱ ላይ የተፃፈው እድሜ 33 ይላል። ወጣት ነው፣ ማንም ሴት አይታው የምትደነግጥለት ዓይነት ቁመናና መልክ፤ በራሱ የሚተማመን የሚመስል ገፅታ ፤

"አንቺማ አትገርዢኝም። ይዤው አረጃታለሁ እንጂ………" አለኝ ለኔ ሳይሆን ለራሱ የሚያወራ በሚመስል ድምፅ

"ለምን? ሴት ስለሆንኩ?"

"አወና ፣ ሴት ብቻ አይደለሽም። ህልም የመሰልሽ ቆንጆ ሴት ነሽ። ሆ!!"

"እሱ ከስራዬ ጋር ምን አገናኘው?"

"ላንቺ ነዋ ስራ…………" ቀጥሎ ያልሰማሁትን ነገር አጉተመተመ

"ይቅርታ አቶ ሲሳይ ብዙ አገልግሎት ፈላጊዎች ውጪ ተሰልፈዋል። ስራችንን እንቀጥል?"

"እህ ስለተቆጣሽ ይሰማሽ መሰለሽ እንዴ?" አለ ወደሱሪው ዚፕ አይኑን እየላከ። መሳቅ አምሮኛል ግን መሳቅ የለብኝም።

"እንዴት ሳትገረዝ ……….?" ጥያቄዬን የምጨርስበት ቃል ስፈልግ

"አረጀህ? አይባልም ግን እሺ! ……….. ባክሽ አንጀት ነው ታሪኩ። ………… ተረት ነገር ነው የሚመስለው።"

"እየሰራሁ ታወራኛለሃ!!"

ብድግ ብሎ ገላውን አራቆተው።
"እንዴ እዚህ አይደለም የምሰራው።።።" አልኩት

"ቆይ ግን ትልቅ ወንድ ገርዘሽ ታውቂያለሽ?" አለኝ ምንም የተጋለጠ ሳይመስለው ተረጋግቶ ልብሱን ወደሰውነቱ እየመለሰ።

" አዎ። አውቃለሁ። "

"እኔን የሚያህል?"

" ካንተም የሚበልጡ"

"ይሄን ነገር መቼም እንዲህ እንደቆመ አትገዘግዢውም አይደል?" እፍረት አይታይበትም። ስለቆመው አክሱም እንጂ ስለቆመው ንብረቱ ያወራ አይመስልም። በድጋሚ መሳቅ አምሮኛል። ፊቴን አዙሬ ፈገግታዬን ደበቅኩበት። ጭንቅላቴ ውስጥ ብቅ ያለው ሀሳብ ግን ቆሞ ነበር እንዴ? የሚለው ነበር። በየሱስ ስም!

"ማደንዘዣ እሰጥሃለሁ።"

"እህ! አይደለም ማደንዘዣ ፀሀይ የመሰልሽ ሴት ነክተሽው ሞቼ እንኳን ቢሆን አይቆምም?"

አሁን አለመሳቅ አልችልም ነበር። መጥሪያዬን ተጭኜ እጄን ከማንሳቴ ሲስተር ገባች።

“ኸረ ፍጥነት? በሩ ላይ ነበረች እንዴ? ” በማያገባው የሚገባ ሰው በቸልታ ማለፍ አልችልም እኮ ግን እንዳልሰማ ወደ ሲስተር ዞርኩ

”OR 2 ይዘጋጅልኝ። ማረፊያውን ታሳይሃለች እዛ ቆየኝ።” ካርዱን ለሲስተር አቀበልኳት። እሷ ያልኳትን ሰምታ ወጥታለች። እሱ እንደተቀመጠ በትዝብት ያየኛል።

“ምንድነው?”

“ይሄን ፊትሽን ግን ስሞትልሽ ፀብ ሲኖረኝ ሲኖረኝ እዋስሻለሁ። እንቢ እንዳትዪኝ! ኸረ በኪዳነምህረት!! “

“አቶ ሲሳይ የሚመለከተን ነገር ላይ ትኩረት እናድርግ?“

“you see እያናደድኩሽ እንኳን ፈገግ ብለሽ ነው የምትቆጪኝ። ምክንያቱም ደሞዝሽን የምከፍልሽ እኔ ነኛ! ባትመቺኝ ሌላ አማራጭ እንደምጠቀም ታውቂያለሽ። ስለዚህ ምን ያህል ስድ የሆነ costumer እንኳን ቢገጥምሽ በትህትና ታስተናግጃለሽ። ረዳቶችሽ ወደውሽ እንጂ ደመወዝ ስለምትከፍያቸው ፈርተውሽ እንዲታዘዙሽ አታድርጊ! እንደዛ ሲሆን አብረውሽ ያሉት ምርጫ እስካጡ ድረስ ብቻ ነው ማለት ነው።”

ልለው ያሰብኩት ብዙ ነበረ። ዋጋ ያለው ስላልመሰለኝ ተውኩትና እንዲወጣልኝ ብቻ በሩን አሳየሁት። ተነስቶ እየወጣ በሩን ተደግፎ ቆም አለና

«ያንቺን ስራ ደመወዝ ከፍለሽ እንደምታሰሪያቸው ሳይሆን እነርሱም የስራው አካል እንደሆኑ እንዲሰማቸው አድርጊ ያኔ ላንቺ ወይ ለደሞዝ ብለው ሳይሆን የራሳቸው ስራ መሆኑን ስለሚያስቡ ማንም ስራው እንዲበላሽበት አይፈልግም።»

«አቶ ሲሳይ ስድስት አመት ይሄን ሆስፒታል ቀጥ አድርጌ አስተዳርያለሁ። ሰራተኞቼን እንዴት መያዝ እንዳለብኝ አንተ አትነግረኝም!!» እንዴት ያለው ነው? እያናደደኝኮ ነው። ፈገግ ብሎ ከወጣ በኋላ መለስ ብሎ

«አይባልም ግን እሺ! ቤት ውስጥ የተቀጠረ ሰው እንኳን አሁን ቀርቷል ሰራተኛ አይባልም። ሆስተስ፣ አቀናባሪ ምናምን ነው የሚባለው። በሙያቸው የሚረዱሽን ሰዎች ሰራተኞቼ? ኸረ አይባልም!» ብሎኝ በሩን ዘጋው!! ኡፍፍፍፍፍፍፍፍ ምን አይነቱን ነው ዛሬ ደግሞ የጣለብኝ?

★ ★ ★

በሶስት ቀናት ውስጥ የተኛሁባቸው ሰዓታት 7 መሙላታቸውን እንጃ። እቤቴ ሄጄ አላውቅም። ተረኛ ታካሚ እስኪገባ ስጠብቅ እያወራ ወደ ውስጥ ዘለቀ።

"ስንቴ ነው የምትገርዢኝ?"

"ማለት?"

"ቁስሉ ተቦትርፎልሻል። ጨርሺኝ ብዬ ነው አንቺውጋ የመጣሁት።"

"አልገባኝም። እስኪ እዛጋ ሁንልኝ። ምን ሆኖ ነው?" አልኩት

"እኔ አንቺን ማሰብ ማቆም አቃተኝ። እሱም አለመቆም አቃተው። ተነፋፋሁ ሲል ቁስሉ ጣጣጣ…………" የሚያሾፍ ይመስላል። ቁስሉ ግን እንዳለው ቆስሎ ነበር።

"ስነስርዓት ባለው መንገድ እንደአዋቂዎች እናውራ?" አልኩት።ማንም ደንበኛ በዚህ መጠን ነፃነት እንዳወራኝ አላስታውስም።

"እኔ የምለው ማሂ?" አለ ኮስተር እንዳለ

" ዶክተር ማህደር" መለስኩለት

"ኡፍ! ከክብርና ከፍቅር የቱ ይበልጥ ይመስልሻል?"

"ሁለቱም ዋጋ ያላቸው የማይነፃፀሩ ነገሮች ናቸው።"

" ዶክተር ብልሽ ያከበርኩሽ ሊመስል ይችላል። ማሂ ስልሽ ግን ውዴታዬን እየነገርኩሽ ነው። ከክብር ሁሌም ፍቅር ይበልጣል። በክብር ውስጥ ፍቅር ላይኖር ይችላል። በፍቅር ውስጥ ግን ሁሌም ክብር አለ" የሆነ ነገሬን ያወቀ ስለመሰለኝ ተናደድኩ። ለተናገረው ትኩረት የሰጠሁ ባለመምሰል

"ጨርሻለሁ። ተጨማሪ አንድ መድሀኒት አዝልሃለሁ። በትክክል መድሀኒቱን ከወሰድክ በድጋሚ እዚህ መመላለስ አያስፈልግህም።" አልኩት

" OK አልጋ ልትሰጪኝ ማለት ነው? እሱ ጥሩ ሀሳብ ነው። "

"አቶ ሲሳይ ለጨዋታ ጊዜ የለኝም።"

" ሊኖርሽ ግን ይገባል ማሂ!። " መልስ ሳይጠብቅ የፃፍኩለትን ወረቀት ተቀብሎኝ ወጣ።

…………አልጨረስንም…………………

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
★★ ስንቴ ገረዝኩት #2 ★★
(ሜሪ ፈለቀ)

"ዶክተር? ያው ሰውዬ ነው የላከልሽ………" ሲስተር ቀለም በፈገግታ በደመቀ ፊት ጠረጴዛዬ ላይ በፎይል የተጠቀለለውን ምሳ አስቀምጣው ወደ በሩ ተመለሰች

"ሲስተር ከዛሬ በኋላ የሚያመጣውን ምሳ እንዳትቀበሉት።" አልኳት

ለሁለተኛ ጊዜ ታክሞ ከሄደ ጀምሮ ሶስት ቀኑ ነው። የምሳ ሰዓት እየጠበቀ ምሳ ይልካል። ጠዋት ፅዳቶቹ አፅድተው ሲጨርሱ አበባ ይልካል።

"አበባውንም ነው ዶክተር?"

"አዎን። ምንም ነገር!!"

"እሺ!!" ብላኝ ወጣች

ሲስተር ለምንድነው የምትሽቆጠቆጥልኝ? ስለምታከብረኝ? ደሞዝዋን ስለምከፍላት? አለቃዋ ስለሆንኩ? እንጂ አትወደኝም…………… ትጠላኝም ይሆናል። ይሄ የተረገመ ሰው ምን እንዳስብ እያደረገኝ ነው?


★ ★ ★

ሆዴ ምግብ አስፈልጎታል። ሆስፒታሉ አቅራቢያ ያለ ሬስቶራንት እራቴን ለመብላት አዝዤ ተቀምጫለሁ። ከየት መጣ ሳልል ከፊቴ ያለውን ወንበር ስቦ ተቀመጠ።

"ማሂ……ዬ……… ?" አለ በተሟዘዘ አጠራር

"አንተ ሰው ለምን አትተወኝም?"

"አቶ ሲሳይ ታፈሰ። ማዕረግ ያለኝ ሰው ነኝ እሺ።"

"Whatever አቶ ሲሳይ ምን እያሰብክ እንደሆነ አልገባኝም። እኔና አንተ ግን ምንም መሆን የምንችል ሰዎች አይደለንም።"

"ምክንያት? በእድሜ ስለምትበልጪኝ?"

"አቤት? "

"በ18 ዓመትሽ ዩንቨርስቲ ብትገቢ፣ 7 ዓመት ዶክተር ለመባል ብትማሪ……"

"ዶክተር ለመሆን " አቋረጥኩት

"ስፔሻሊስት ለመባል የሆነ ዓመት… …… ይሄን ሆስፒታል ከከፈትሽ 6 ዓመት… …… በስሱ 37 የግልሽ ነው። "

እንዲያውቅብኝ ባልፈልግም ተናድጃለሁ። ለምን ተናደድኩ? ትክክለኛ እድሜዬን ስለነገረኝ። እና ምን አናደደኝ? ምክንያት እንኳን የለኝም።

"ቁስልህ ዳነልህ?" ወሬውን መቀየር ነው ፍላጎቴ

"እየደረቀ ነው። ላሳይሽ?" ከመቀመጫው ብድግ አለ

"ኸረ አንተ ሰው?" ለመቀመጥም ለመነሳትም በቀረበ አኳኋን አየሩ ላይ ተንሳፈፍኩ

"አየር ላይ ነሽ! አረፍ ትዪ……" ብሎኝ ተመልሶ ተቀመጠ

ያዘዝኩት ምግብ መጣ። ተነስቶ እጁን ታጥቦ እስኪመጣ ጠብቂኝ ባይለኝም ጠበቅኩት። የጠቀለለውን ሊያጎርሰኝ ዘረጋ
"ጉርሻ አልወድም።" አልኩት

"እንዴ? በሞቴ? በፍቅራችን?" ሆነ ብሎ ሬስቶራንት ውስጥ ያለው ሰው እንዲሰማ ጮክ ብሎ ነው የሚናገረው። ሰዎች እየዞሩ ያዩናል። ግማሾቹም ፈገግ እንደማለት ይላሉ። ጎረስኩለት።

"ማሂዬ ለክብርሽ ይሄን ያህል አትጨነቂ። ……" አለ የተናገረው ተራ ነገር እንደሆነ ሁሉ ለሌላ ጉርሻ እየተሰናዳ። ተበሳጭቻለሁ። ይበልጥ ያበሳጨኝ ደግሞ ያለው እውነት መሆኑ ነው።

"ክብር አንጃ ግራንጃህን ተወኝ። ባለትዳር ነኝ ለባለቤቴ …………"

ሳቁ አቋረጠኝ። አስቂኝ ተረት እንደነገሩት ህፃን ተንፈቀፈቀ::

"ምን ያስቅሃል?"

"ባለቤትሽ ነዋ ያሳቀኝ ሃሃሃሃ "

"ምን ለማለት ፈልገህ ነው?"

" እንዳንቺ አይነት ሴቶች ወይ አላገቡም፣ ወይ አግብተው ፈተዋል፣ ወይ ከባላቸው ጋር ሰላም አይደሉም።"

"እኔ ምን ዓይነት ሴት ነኝ?"

"ካልኳቸው ምድብ ውስጥ ከሌለሽ ልቀጣ? እ?" መልሴን ጠበቀ

መልስ አልነበረኝም። ተነስቼ ጥዬው መሄድ ነበር ፍላጎቴ እግሮቼን ማዘዝ አቃተኝ። ሽንፈቴን መቀበልም መሰለኝ። ልከራከረውም አቅሙ አልነበረኝም።

"እኔ ምን አይነት ሴት ነኝ? " ድምፄ የቅድሙ ጥንካሬ የለው

"እውቀትና ደረጃዋን ድክመትና ሽንፈቷን ለመሸፈን የምትጠቀም ዓይነት ሴት"

ከዚህ በላይ መስማት የሚያሳምመኝ መሰለኝ። ተነስቼ ስወጣ ድምፁ ተከትሎኛል።

"አየሽ አንቺ ይህቺ ነሽ። ትፈረጥጫለሽ።"

እኔ ምን አይነት ሴት ነኝ? የትኛውን ሽንፈቴን ነው በደረጃዬ የሸፈንኩት?
★ ★ ★

ወትሮም ለእንቅልፍ እምብዛም የሆነው ዓይኔ ጭራሽ አልከደን አለ። እቤቴን ጠላሁት። ልብሴን ለመቀየር ካልሆነ በቀር አዳሬም ሆስፒታል ከሆነ ሰነባበትኩ። ምግቤንም የምመገበው እዛው እያስመጣሁ ሆነ። ከዛ ቀን በኋላ ሲሳይን አላገኘሁትም። ከዛ ቀን በኋላ ግን ስላወራናቸው ነገሮች አለማሰብ አቃተኝ። ሁኔታዬን ይብስ ያባባሰው ደግሞ ከቀናት በፊት የገጠመኝ ነገር ነው። ዶክተር ሰይፈ!!! በግምት የ12 አመት ልጅ የምትሆን ህፃን በዊልቸር እየገፋ ሲያልፍ ነበር ያየሁት። ደሜ ሰውነቴ ውስጥ ሲቀዘቅዝ ታውቆኝ ነበር።

«ሲስተር? ዶክተር ሰይፈ ልጅ አለው እንዴ? » ቢሮ እንደገባሁ ጠየቅኳት። ጥያቄዬ ይሁን ሰይፈ የትኛው መሆኑ ግራ ያጋባት አልገባኝም። « ዶክተር ሰይፈ የህፃናት...............»

«እኮ ገብቶኛል። መጠየቅሽ ገርሞኝ ነው። አዎን ሁለት ሴት ልጆች አሉት። አንዷ ልጁ የመኪና አደጋ ደርሶባት she is totally paralyzed እሱ ነው የሚንከባከባት። አይኗም የማየት አቅሙ እየተዳከመ ነው።» አነጋገሯ ውስጥ ያለው ድምፀት ያሳምማል። አንቺ ምን ግድ አለሽ አይነት ነው።

« ሚስቱስ?»

«ህምምም....... ሚስቱ እኮ ሞታለች ዶክተር!»

« ለምን አልነገራችሁኝም? እንዴት አንድ ሰው አይነግረኝም?» ፀፀቴን ማራገፊያ አጥቼ እንጂ እሷ ላይ የምጮህበት ምክንያትም መብትም የለኝም።

« ምን ብለን? ዶክተር አንቺ ልብ ስለማትዪ እንጂ እኮ ለህክምና እዚህ ትመላለሳለች።» ብላኝ በመገረም እያየችኝ ወጣች።

ኡፍፍፍፍፍፍፍ በየሱስ ስም ምንድነው የሰራሁት? ዶክተር ሰይፈ በሙያው ማንም እንከን የማያወጣለት ጎበዝ ነው። በተደጋጋሚ እያረፈደ እና እየቀረ ስላስቸገረ ቦርዱን ሰብስቤ ከስራው እንዲባረር ያደረግኩት ቀን ያሳየኝን ፊት ትርጉም የምረዳው አሁን ነው። ምክንያቱን እንኳን ሊነግረኝ የደከመው ነበር የሚመስለው። እሺ ብቻ ነበር ያለኝ። ከቦርድ አባላቱ አንዱ ምክንያቱን እንድሰማው ጠይቆኝ ነበር።

«ተውት ምክንያቴን ለእናንተ እያስረዳሁ ህመሜን አላበዛም። ለእስከዛሬው ቆይታችን አመሰግናለሁ!» ያለው በሰአቱ ምን ያለ መስሎኝ ነው ከምንም ያልቆጠርኩት? እንዴት ግን አንዳቸው እንኳን ልጁን እያስታመመ ነው አይሉኝም? ይሄን ያህል ድንጋይ ልብ ያለኝ ነው የምመስላቸው? ይጠሉኛል ማለት ነው አይደል?

ማሰብ ይደክማል እንዴ? ማሰብ ደከመኝ:: ስልኬ መልዕክት መቀበሉን ነገረኝ። ከፈትኩት። የማላውቀው ቁጥር ነው።
"ሁሉም ሰው የራሱ የሆነ አይነኬ የህይወት ክፍል አለው። ያን ሽሽት የሆነ ነገር ውስጥ ይደበቃል። ሌት ተቀን ህሙማንን ማገልገልሽ ለብዙዎች ታታሪነትሽን ይነግራቸዋል። ስራሽ መደበቂያሽ መሆኑን ግን አሳምረሽ ታውቂዋለሽ።"
ከሱ ውጪ ማንም አይሆንም። ቁጥሩን ደወልኩበት። ይሄ ደግሞ ሊያሳብደኝ ነው እንዴ ሀሳቡ?
"ምንድነው ከኔ የምትፈልገው? ምንድነው ግን ችግርህ?"

"ደህና እግዜአብሄር ይመስገን!! ምሳ እንኳን አይመቸኝም። እራት ቢሆንልኝ እመርጣለሁ።" አለኝ ዘና ብሎ።

ምን ልለው ነበር የደወልኩት? ቁጣዬን ምላሴ ላይ ምን ያልከሰክሰዋል?
"እራት ልጋብዝሽ?" አለኝ ዝምታዬን ተከትሎ። ምን እንደምመልስለት ግራ ገባኝ።

"ማሂ ፕሊስ?……… እኔ ደስ ብቻ ነው የሚለኝ። ዶክተር ማህደር እራት ተጋበዘችልኝ ብዬ ቀላል ሴት የሆንሽ አይመስለኝም።" የማስበውን እኔ ከስቤ ሳልጨርሰው ከሱ አፍ እሰማዋለሁ።
"የባለፈው ሬስቶራንት 12 ሰዓት ላይ ላግኝሽ! ውብ ቀን ዋዩ!!" ብሎኝ እንቢም እሺም ሳልለው ስልኩን ዘጋው።

## አሁንም አልጨረስንም##

@wegoch
@wegoch
@paappii
ዝምምምም.........


"ህመሙን የሸሸገ መዳህኒት አይገኝለትም" ትለኛለች አንድ እንደኔ ያልደረሰባትና ያልታመመች እህቴ። አንዳንዴ ይገርመኛል እንዴት ነው በሽታውን ላሸከመኝ ሰው በሽታዬን የምነግረው። በእርግጥ መዳኒቱን ከሷ ውጪ አላገኘው ይሆናል ነገር ግን ይሁን ብዬ ብናገር ደግማ ሌላ በሽታ እንደማትጨምርብኝ ምን ማረጋገጫ አለኝ። እንደው ይህን ሁሉ ትቼ አንኳ ልንገራት ብል ድፍረት ከየት አባቱ ሊመጣ ነው።
ነገር ግን ደሞ ሌላ አማራጭ ያለኝ አይመስለኝም። እውነቱን ተናግሮ የመሸበት ማደር አይደል ሚባለው እኔ ግን እውነቱን ተናግሬ መልሱ ጥሩ ካልሆነ ቀድሞውኑም አይመሽም ከመሸም የማድርበት ያለኝ አይመስለኝም ፤ ልቤ ግን ለመናገር ወስኗል።
ችግሩ እንዴት ተብሎ በየትስ ተሂዶ እንደምነግራት ነው የጨነቀኝ። ሀሳብ ሀሳቤን እያሸነፈ አንድ መሬት የማዮድቅ ሀሳብ መጣልኝ።

"ደብዳቤ"
ደስ አለኝ ምክንያቱም ፊቷ ፊቴን አይገርፈውም፤ ፊት ለፊቴ ጥላኝ ስትሄድም አላይም፤ ሌላው ቢቀር መስማት የማልፈልገውን ምላሽ አጠገቧ ሆኜ እንደማልሰማ ሳስብ ልቤ እርፍ ይላል። ወዲያው ግን ምላሿ ምን ይሆን በሚል አስቀያሚ ጥዬቄ እጨናነቃለው።

ደብዳቤውን ለመፃፍ ስጀምር አጠገቤ ሆና አብራኝ ትፅፍ ይመስል የምፅፈው ይጠፋብኛል። ነገር ግን እንደምንም ሀሳቤን ሰብስቤ መፃፍ ስለነበረብኝ የሞት ሞቴን ጀመርኩት።ለአንድ ደብዳቤ አንድ ሰአት ፈጀብኝ። የፃፍኩት ግን ሦስት ቃል ብቻ ነበር።

"የውብዳር ከልቤ አፈቅርሻለው"

በቃ ጨረስኩ ፤ እጄን ወደ ግንባሬ ስደድሁ፤ ላብ ጠምቆኛል። የላቤ ብዛት ሦስት ቃል ሳይሆን ሦስት መፃፍ የፃፍኩ ነበር የሚመስለው።
ወዲያው ደብዳቤዬን ፖስታ ውስጥ ከትቼ ከቤት ወጣሁ።
ማንም ሰው እንዲያገኘኝ ስላልፈለኩ እርምጃዬ አፈጠንኩት። አንድ የሰፈር ሰው ቢያየኝ ለ'ናቴ ሄዶ "እኔምልሽ ምነው ልጅሽ ሶምሶማ ውድድር መጀመሩን ብትነግሪኝ " ብለው ማውራታቸው አይቀርም ነበር።ነገር ግን ተመስገን ማንም ሳያየኝ ኪዳነምህረት በር ላይ ደረስኩ። ሦስቴ ተሳልሜ ከገባሁ ቡኃላ እሷም እኔም ወደምናውቃት ቦታ ገሰገስኩ። ቦታው ላይ ስደርስ እሷ እንዳለች ያህል ይሰማኝ ጀመር። ቁጭ ብዬ ግራ ቀኜን እማትር ጀመር። ቤ/ክኑ ጭር ብሏል ነገር ግን አንድ ቦታ ተደብቃ ምታየኝ እየመሰለኝ እጄ ድመት እንደገደለ ይንቀጠቀጥብኛል። ፊት ለፊቴ ያለውን ድንጋይ አነሳውና ደብዳቤውን ላስቀምጠው እጄን ወደኪሴ ስልክ ነገር አለሙ ጨለመብኝ።

ከሰአታት ቡኃላ ስነቃ በዘመድ ተከብቤ እራሴን ሆስፒታል አገኘውት። "የደብዳቤ ያለህ ኡኡኡኡኡ" ብዬ መጮህ አማረኝ ነገር ግን በዘመድ ፊት ፍቅር ይዞት ነው የወደቀው መባልን ፈራው።

ዝምምምም......አልሁ

የጌትነት ልጅ ፃፈ

@wegoch
@wegoch
@paappii
★★ ስንቴ ገረዝኩት #3 ★★
(ሜሪ ፈለቀ)

"እኔ ምን አይነት ሴት ነኝ? " ድምፄ የቅድሙ ጥንካሬ የለውም "እውቀትና ደረጃዋን ድክመትና ሽንፈቷን ለመሸፈን የምትጠቀም ዓይነት ሴት" ከዚህ በላይ መስማት የሚያሳምመኝ መሰለኝ። ተነስቼ ስወጣ ድምፁ ተከትሎኛል። "አየሽ አንቺ ይህቺ ነሽ። ትፈረጥጫለሽ።"

★ ★ ★
ወትሮም ለእንቅልፍ እምብዛም የሆነው ዓይኔ ጭራሽ አልከደን አለ። እቤቴን ጠላሁት። ልብሴን ለመቀየር ካልሆነ በቀር አዳሬም ሆስፒታል ከሆነ ሰነባበትኩ። ምግቤንም የምመገበው እዛው እያስመጣሁ ሆነ። ከዛ ቀን በኋላ ሲሳይን አላገኘሁትም። ከዛ ቀን በኋላ ግን ስላወራናቸው ነገሮች አለማሰብ አቃተኝ። "እኔ ምን አይነት ሴት ነኝ?"
"የትኛውን ሽንፈቴን ነው በደረጃዬ የሸፈንኩት?" ማሰብ ይደክማል እንዴ? ማሰብ ደከመኝ:: ስልኬ መልዕክት መቀበሉን ነገረኝ። ከፈትኩት። የማላውቀው ቁጥር ነው። "ሁሉም ሰው የራሱ የሆነ አይነኬ የህይወት ክፍል አለው። ያን ሽሽት የሆነ ነገር ውስጥ ይደበቃል። ሌት ተቀን ህሙማንን ማገልገልሽ ለብዙዎች ታታሪነትሽን ይነግራቸዋል። ስራሽ መደበቂያሽ መሆኑን ግን አሳምረሽ ታውቂዋለሽ።"
ከሱ ውጪ ማንም አይሆንም። ቁጥሩን ደወልኩበት። "ምንድነው ከኔ የምትፈልገው?" "ደህና እግዜአብሄር ይመስገን!! ምሳ እንኳን አይመቸኝም። እራት ቢሆንልኝ እመርጣለሁ።" አለኝ ዘና ብሎ። ምን ልለው ነበር የደወልኩት?
"እራት ልጋብዝሽ?" አለኝ ዝምታዬን ተከትሎ። ምን እንደምመልስለት ግራ ገባኝ። "ማሂ ፕሊስ?……… እኔ ደስ ብቻ ነው የሚለኝ። ዶክተር ማህደር እራት ተጋበዘችልኝ ብዬ ቀላል ሴት የሆንሽ አይመስለኝም።" የማስበውን እኔ ከስቤ ሳልጨርሰው ከሱ አፍ እሰማዋለሁ። "የባለፈው ሬስቶራንት 12 ሰዓት ላይ ላግኝሽ! ውብ ቀን ዋዩ!!" ብሎኝ እንቢም እሺም ሳልለው ስልኩን ዘጋው።

★ ★ ★
እግሬና ሀሳቤ ሳይስማሙ እግሬ ቀድሞ ሬስቶራንቱ ውስጥ ተገኘ። ሲሳይ ቀድሞኝ ተገኝቷል። ልጨብጠው የዘረጋሁትን እጄን ሳብ አድርጎ አቀፈኝ። ፀጉሬን እንደመሳም አደረገና የምቀመጥበትን ወንበር ሳበልኝ። እራትና ወይን አዘዝን።
አፉ ከማውራት እጁ ከማጉረስ ሳይቦዝን እራት ተመግበን አለቀ። "እኔ ከዚህ በላይ አልጠጣም። ስራ መመለስ አለብኝ።" ያልኩትን የሰማ አይመስልም። ቀዳልኝ። በአትኩሮት ሲመለከተኝ ከቆየ በኋላ "ሴክስ ካደረግሽ ስንት ጊዜሽ ነው? ወራት? አመታት?" አለ ቀለል አድርጎ
"አንተ? ያምሃል እንዴ? " አልኩት ደንግጬ ይሁን አፍሬ ሳይገባኝ "ምነው? አንቺ? ጭራሽ… …… እ? ነው እንዴ?" በማብሸቅ ለዛ ነው ያወራው። ደሞ አብሽቆኛልም። "አንተ እኔን ለማንጓጠጥ የሚያስችለህ ቦታ ላይ እንዳለህ ነው የሚሰማህ?" ሳልጨርስ መንፈቅፈቁን ያዘው " ማሂ ከእኔ ጋር ስታወሪ ጨዋ ቃል አትፈልጊ…… ሃሃሃሃ ‘ትናንት እጄ ላይ ሸለፈትህን ተገርዘህ፣ ልጅህን በማስገረዣ እድሜህ አንዠርግገኸው………‘
በይው " "እንደሱ ለማለት እንኳን አልነበረም።" መለስኩለት "በጨዋኛ ስለሴክስ ምን ታውቅና? እንደማለት አይደል?" "አዎን!" አልኩት "ያልተገረዘ ሴክስ አያደርግም ያለሽ ማነው?" አባባሉ ቀዝቃዛ ስሜት ስለነበረው ስሜቱን የጎዳሁት ስለመሰለኝ ወንዶች ስለማይገረዙባቸው ሀገራት፣ ገጥመውኝ ስለሚያውቁ አጋጣሚዎች ነገርኩት። "ኮንዶም የለ፣ ምን የለ… … ሸብ አድርጎ መሰማራት ነው። ሃሃሃ" ብልግና ያወራ፣ በራሱ ያላገጠ አይመስልም። ደንግጬ ፈጥጬ አየዋለሁ። "ኸረ ስቀልድሽ ነው አንቺ!!" አለ መሳቁን ሳያቆም። በህይወቱ ውስጥ የሚያስከፋው፣ የሚያፍርበት፣ ሊያወራው የማይፈልገው ነገሩ ምን ይሆን? ብዬ አሰብኩ። ሲያወራ ፍፁም ጨዋ፣ ደግሞ ፍፁም ባለጌ፣ ደግሞ ፍፁም አዋቂ፣ ደግሞ ፍፁም ህፃን………ሁሉንም ይሆናል። ሲሳይን ማወቅ ከበደኝ። ያልተገረዘው ቤተሰባቸው ወንድ ልጅ እየሞተ ሲያስቸግራቸው የሄዱበት
ጠንቋይ እንዳይገረዝ ስለነገራቸው መሆኑን እንደለመደው በራሱና በቤተሰቡ
እየቀለደ ነገረኝ። "እያደግኩ ከመጣሁ በኋላ መገረዙ አሳፈረኝ እና አረጀሁ። ""ያፈርክበት ግን አትመስልም ነበር።"
"አንቺጋ ስመጣማ ከማፈር አልፎ አስጠልቶኝ ነበር።" ሲያወራ በራስ መተማመኑ ለሰከንድ አይለየውም። ደጋግሞ ከሚያወራቸው ነገሮች በወላጆቹና በ6 እህቶቹ የተለየ ፍቅር ተሰጥቶት እንደኖረ ገባኝ። ከብዙ
ሰው ጋር መግባባቱ፣ ብዙ ጓደኞች ማፍራቱ ምናልባትም ከተማረው የሳይኮሎጂ ትምህርቱጋ ግንኙነት ይኖረው ይሆናል ስል አሰብኩ።
"ጓደኞች የሉሽም? የሆነ አብረሻቸው አንዳንዴ ዘና የምትዪበት ምናምን?"
"የሉኝም!!" "እሺ ሲደብርሽ፣ ሲከፋሽ፣ ደስ ሲልሽ ወይ የተለየ ነገር ሲገጥምሽ ለማን
ታወሪያለሽ?" አለኝ አይኖቹ የሚያነቡኝ ስለሚመስሉኝ እሸሻቸዋለሁ "ለራሴ አወራዋለሁ።" አልኩት አይኑን ሳይሰብር አየኝ። "አንተስ?" አልኩት "ያ ስሜት በተሰማኝ ሰዓት አጠገቤ ላገኘሁት ሰው። ለምሳሌ በኋላ ሸኝቼሽ ስመለስ ለሆስፒታላችሁ ዘበኛ ደስ እንዳለኝ ልነግረው እችላለሁ።" ቀለል አድርጎ
ነው የሚያወራው "እየቀለድክ ነው?"
"የምሬን ነው። ምነው?" "የምልህ ከእኩዮችህ፣ ቢያንስ ከቤተሰብህ……… ባንተ ደረጃ ካሉ ሰዎች ጋር……… " አላስጨረሰኝም።

"ደረጃ ምንድነው? ደረጃ መዳቢውስ ማነው? እኔን ከኒኛ ዘበኛ ወይ ከዚህ አስተናጋጅ በላይ ወይ በታች ደረጃ የሰጠን ማን ነው? የኔ መማር እና ቢሮ
መቀመጥ? የሳቸው የእኔን እድል አለማግኘትና ዘበኛ መሆን? ንገሪኝ እስኪ
እሳቸው የሚያውቁትን ወይ የሚችሉትን ደረጃ ብለን ባወጣንላቸው ዘበኝነት እንዴት እንመዝነዋለን?" አይቼበት የማላውቅበትን ፈገግታ ፈገግ ብሎ ቀጠለ "አፈር ምን ደረጃ አለው? ነፍስስ ብትሆን ያው ነፍስ አይደለች? በምትሰራው ስራ ካልዳኘናት በቀር? የሰው ደረጃው ‘ሰውነቱ‘ ነው።" አለኝ። ዝም አልኩት። ምንስ ልለው እችል ነበር?
"ቤተሰቦችሽ? የት ናቸው?" አለኝ ወዲያው ከዛኛው ስሜት ወጥቶ "ቤተሰቦቼ………?…… "
"ምነው? ሞተዋል? ተጣልታችኋል? ወይስ…… እንደ እህል ዘርተውሽ ነው
የበቀቀልሽው?…" ተናድጄ አቋረጥኩት ቁስሌን እያወራ እንደሆነ አልገባውም።
"ምንም ስነስርዓት አታውቅም። ባለጌ ነህ እሺ!!" አልኩት "እሺ!" አለኝ ቁጣዬን ከምንም ሳይቆጥረው እጄን እየዳበሰ።
"እሺ ግን ንገሪኝ። ማወቅ እፈልጋለሁ።
ምኑን ልንገረው? አባቴ ከእህቱ ልጅ እንደወለደኝ እና ወንድ አያቴ እንዳሳደጉኝ? ቤተሰቡ ውስጥ እንደ አንዳች መዓት ሲፀየፉኝ እንደኖርኩ? አያቴ ሲሞት ያየሁትን አስቀያሚ የህይወት ገፅታ? የቱን ልንገረው? ለማንም አውርቼው አላውቅም። እንባዬ መጣ። እያየኝ ማልቀስ አልፈለግኩም። ፈርጣጭ ይበለኝ። ተነስቼ መውጣት እንደጀመርኩ እንባዬን ማስቆም አቃተኝ።
ሬስቶራንቱን መግቢያ እንዳለፍኩ እሮጦ ደረሰብኝ። አቀፈኝ። እንደህፃን ደረቱ ላይ
አጥብቆ አቀፈኝ። አለቀስኩ። አላባበለኝም። ፀጉሬን እየደባበሰና እየሳመ ለቅሶዬን እስክተው ጠበቀኝ። ያስለቀሰኝ ምን እንደነበረም አልጠየቀኝም። እያሳቀኝ የሆስፒታሉ መግቢያ ድረስ ሸኘኝ። ሲሰናበተኝ መልሶ አቀፈኝ። እቅፉ ውስጥ ብዙ መኖር ፈለግኩ። ከሆነ ነገር የሸሸገኝ መሰለኝ። ሰላም ያለበት ዓይነት። እሱም የገባው ይመስል አቅፎኝ ለደቂቃዎች ቆየ። ግንባሬን ሳመኝ።

★ ★ ★
ፈገግ እያልኩ መሆኔ ለራሴ ይታወቀኛል። ታካሚዎቼን እየፈገግኩ እንደማዋራቸው ገብቶኛል። ማታ ከሲሳይ ጋር ከተለያየን ጀምሮ እንደዚያ እየሆንኩ ነው። ሲስተር ቀለም በተረኛ ታካሚ ፈንታ ገባች "ዶክተር ሰው ይፈልግሻል?" "ሲሳይ ነው? ትንሽ ታገሰኝ በይውና ተረኛ ታካሚ አስገቢልኝ።" "ዶክተር ……… ባለቤትሽ ነው።
" "ባለቤትሽ? ኢሳያስ?…………"

አሁንም በድጋሚ አልጨረስንም

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
((Maggie))

"ሁሌ ማስበው ስላንተ ነው.... ስላንተ ብቻ! ልክ ትኩስ አፍቃሪ ፍቅረኛውን በየሰከንዱ ስንጥርጣሪ እንደሚያስብ.... ነፍሰጡር ሴት ስለልጇ ቀኑን እያሰበች፤ ለሊቱንም እያለመች እንደምታነጋ...

ለ ሰከንድ ፍልጥላጭ ሳላስብህ ባሳልፍ " ለምን አላሰብሽውም? በሱ ዙሪያ የፀለይሽውን ፀሎት ውድቅ እንዳደርገው ይፈልጊያለሽ?" ፈጣሪ የሚለኝ እስኪመስለኝ ድረስ አንተን በሙሉ ግዜዬ ሳላሳል ስ ሳላስልፍ አስብሀለው

አይኔን ስከድን ምስልህ በድብዛዛ ቀለም ይከሰትልኛል... አይኔን ስገልጥ ያ ምስል ድምቅ ብሎ በብራው ሰማይ ላይ ይታተምብኛል.....
ከጭንቅላቴ ለሰከንድ ወጥተህ አታውቅም.... የብቻህ ግዛት አድርገኸዋል ...

አንተን ማሰቤ ሀሴት ሲፈጥርልኝ ፊቴ በጥርሴ ፀሀይ እንደጠዋት ጀምበር ሰማይላይ በ ስሱ እንደተቀባ የእግዜር ጥበብ በፈገግታ ብሩሽ በደማቁ ይቀባል... እንደገና አንተን ስለማሰቤ ሳስብ ደግሞ ሌላ ፍስሐ ይመጣና " አንች የፈገግታ ቅብ ሆይ! ይችን ጨምሪበትና ይባስ ድምቅምቅ በይበት" ብሎሻ እግዜር ብሎ የደስታ ቀለም ፊቴ ላይ ይርከፈከፋል..

ግንኮ አልነካውህም አላሸተትኩህም... በ ስ ልኬ መስታወት በኩል ብቻ ነው ምስልህን ያየውት! .. በመስታወቱ ውስጥ እንደሚጎበኝ ውድ እና ድንቅ የሙዝየም እቃ!

ከመስታወቱ ውስጥ በምትሀት ተጎትተህ ወጥተህ አጠገቤ ብትከሰት ብዬ አስባለው......... አጠገቤ ተቀምጠህ በእጄ ሳልነካህ (ቅር ሴ አይደለህ!) ብቻ ቁልጭ ቁልጭ እያልኩ ባየውህ ብዬ አልማለው...... በስልክ የሰማውት ድምፅህን በሉባንጃ ጢስ ታጅቦ ወፍራም አቦል ቡና በጀበናዋ ጉረሮ እንደሚንቆረቆረው በለስላሳ አየር ታጅቦ ያጎርናና ድምፅህ በጉረሮህ ኮለል እያለ በጆሮዬ ቢንቆረቆር ብዬ ብዙ ግዜ እግዜርን "በማርያም!" እያልኩ ለምኜዋለው...
መፅሀፍ ሳነብብ...... አፍቃሪው፣ ሸበላው ና እንዳንተ ድምፀጎርናና ገፀባህሪውን እንደ "አንተ" አመናጫቂዋ ፣ማጋጭዋ ፣እንዳንዴ እንደኔቢጤ ሳንቲም ወርወር የምትደረግ ፍቅር ብቻ የምታሳየው ገፀባህሪን ...ሰርዤ ....እኔን በቦታዋ ተካና በዛች የኔቢጤ ሳንቲም በምታክል የፍቅር ግዜያቸው ውስጥ የትዬለሌ ግዜ ዘረጋና በሰመመን የኔና ያንተን የፍቅር ገመድ ገምዳለው.....

እንዲ ባላደርግ ግን እንዴት ቀጥል ነበር? እግዜር ግን ጥበበኛ ነው! ለእንደኔ አይነት አፍቃሪዎች ይህንን ሀሳብ ህልም ምኞት ምናምንየተባሉትን ባይፈጥር ኖሮ እንዴት እንደምንሆን እንጃ!.."

@wegoch
@wegoch
@paappii
#ክፍል_አራት (የመጨረሻ ክፍል)
:
:
ደረሲ:-ሜሪ ፈለቀ
:
:
....“ባለቤትሽ? ኢሳያስ?…………”
“ቢሮዬ ድረስ እየመጣህ ለምን ትረብሸኛለህ ኢሳ?” “ናፈቅሽኝ!! ከዚህ በላይ ሳላይሽ መቆየት አልችልም። ”ከዩንቨርስቲ ጀምሮ የማውቀው ሰው ነው ኢሳያስ። ለ6 ዓመት አብሮኝ የቆየ
የትዳር አጋሬም ነው። አብረን በኖርንባቸው ጊዜያት መጀመሪያዎቹ አመታት በፍቅር ያጌጡ ነበሩ። እየሰነባበተ ግን ሳንጨቃጨቅ ያለፉ ቀናት ውስን ሆኑ። የሁለት ዓመት ልጃችን በሞት ስትለየን ሰላማችን ይብስ ደፈረሰ። ልጃችን የሞተችው በምግብ መመረዝ ነው። ታማ ስትሰቃይ ሁለታችንም ልንደርስላት አልቻልንም ነበር። ሰራተኛዋ ስትደውልልኝ ስራ ላይ ነበርኩ። ስልኬን እየሰማሁት ቆይቼ ለመደወል አስቤ ተውኩት። ግን ቆይቼም አልደወልኩም። ሌላ ስራ ያዝኩ። እናም ልጄን ሳልደርስላት ሞተች። እሱም በተመሳሳይ ምክንያት ስልክ ሳይመልስ ቀረ። ቆይቼ ስደርስ ዘግይቼ ነበር። ለዚህ በደሌ አንድ ሚሊየን ጊዜ ራሴን ብቀጣውም በቂ አይሆንም። ከኢሳያስ ጋር መወቃቀሱ አቁሳይ ስለነበር በሆነው ባልሆነው ሰበብ እየፈለጉ መነታረክ ሆነ ምሽታችን። ቤቱን ለቆ ከወጣ ሶስት ወር አለፈው።“ቁጭ ብለን እንድናወራ እፈልጋለሁ። ” አለኝ አይን አይኔን በልመና እያየ። ምንድነው ልለው የነበረው? ‘ውጣልኝ‘ ነበር ሌላ ጊዜ ቢሆን የምለው። አሁን የምትሸሸዋን ሴት አይደለሁም። ምንም ቢሆን የምትጋፈጠዋን ማህደር እየተለማመድኳት ነው። “እደውልልሃለሁ። ” ያልኩትን ያመነኝ አይመስልም። ተገርሞ እያየኝ ተሰናብቶኝ ወጣ። የገባኝ አንድ ነገር ሲሳይ በብዙ ፍጥነት ማንነቴን እያሾረው መሆኑ ነው። ወደ ቤቴ ገብቼ ሲሳይ ያለኝን አደረግኩ። «በህይወትሽ የምትሸሺው ነገር ምንድነው? መስታወት ፊት ቁሚና ለራስሽ ንገሪው። እመኚው!! መቀየር የማትችዪውን ነገር መቀበል ነው የሚፈውሰው።» ነበር ያለኝ የልጄን ፎቶዎች ከደበቅኩበት አወጣኋቸው። በመጀመሪያው ቀን ቀላል አይሆንም ነበር ያለኝ። ቀላል አልነበረም። ሁሉንም ፎቶዎች በፊት የተሰቀሉበት መለስኳቸው። መሸሽም መደበቅም መድሃኒት አይሆንም። ስሸሽ የተጠራቀመው እንባዬ ገደቡን ጥሶ አይኔን አደፈራረሰው። ስልኬ መጥራቱን እንኳን የሰማሁት ብዙ ከጠራ በኋላ ነበር። «ምን ሆነሻል? አልቅሰሽ አይደለምኣ?» ሲሳይ ነው። «ነው! አልቅሼ ነው።» እያልኩት ጭራሽ መንፈቅፈቅ ጀመርኩ። «እህህህ ምን ተፈጠረ ቆይ?» እቤቴ ደጅ ድረስ አድርሶኝ ነበር የተመለሰው። መልስ መመለስ እስኪያቅተኝ ሲቃዬ አነቀኝ። «በቃ በቃ እሺ መጣሁ። ስልኩን አትዝጊው እያወራሁሽ እደርስልሻለሁ። እኔ አጠገብሽ ሆኜ እንደፈለግሽ እንድታለቅሺ ፈቅድልሻለሁ። እስከዛ ግን ስወድሽ አታልቅሺ?» ብሎኝ ሊያስቀኝ እየሞከረ ከቤቱ ሲወጣ፤ «ብርድ እንዳይመታህ በደንብ ልበስ» ስለው «አትስጊ ካልሲ አጥልቄለታለሁ» ሲለኝ
ታክሲ ሲያናግር «የኔ እመቤት ደሞ ስስ ፒጃማ ፍለጋ ቁምሳጥኑን ዘረጋግፊው አሉሽ!» ሲለኝ ሲከፍል «ስንቴ መስታወት አየሽ?» ሲለኝ ሲደርስ እውነትም ማልቀሴን ትቼ ልቤ ተሰቅሎ እየጠበቅኩት ነበር። በሩን ከፍቼ
ተጠመጠምኩበት። ሙሽራውን በሰርጓ እለት ወደ መኝታ ቤታቸው እንደሚያስገባ ሙሽራ አቅፎኝ ወደሳሎኑ ገባ! ማልቀሴን እረሳሁት። ሳሎኑ ውስጥ የተሰቀለውን የእኔንና የኢሳያስን የሰርግ ፎቶ አይቶታል። ግን አልጠየቀኝም። ሌላ ነገር እያወራ ሲያስቀኝ ቆየ።
«ሲስ?»
«ወዬ እመቤቴ?»
«ስለእኔ ማወቅ ያለብህ ነገር አለ።»
«ምኑን ትነግሪኝ? በፎቶ አሳየሽኝኮ አስጎበኘሽኝ።» አለ ወደፎቶው እየጠቆመኝ።
«እየቀለድኩ አይደለም ሲስ! ከምሬ ነው።» «እሺ እመቤቴ ንገሪኝ! ይኸው! Am all yours!» ስለ ኢሳያስ እና ስለልጄ ነገርኩት ብቻዬን ስለፈልፍ ሲያባብለኝ እና ሲደባብሰኝ ብቻ ቆየ። ብዙ ደቂቃ እቅፉ ውስጥ ካቆየኝ በኋላ
«ባንቺ ደረጃ ካሉ ሴቶች ይልቅ አንዲት ምንም የማታውቅ የቤት እመቤት
የሰመረ ትዳር ለምን የሚኖራት ይመስልሻል?» አለኝ «ጭራሽ እንደዛ ስለመሆኑም እንጃልህ! ምን ለማለት ፈልገህ ነው?» «ይሄ ሀቅ ነው ብዙ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት በጋራ ስምምነት ባስቀመጥነው ደረጃ ብዙዎቹ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ያሉ ሴቶች በትዳራቸው ስኬታማ አይደሉም።» «ምናልባት ከትዳራቸው ሌላ ትኩረታቸውን የሚሻ ሌላ ስራ ስላላቸው?» «እኔ አይመስለኝም። እነዛ በትዳር ውስጥ ለፍቅር ወይ ለልጃቸው አልያም በሌላ ምክንያት ዝቅ ማለትን ያውቁበታል። እስኪ አንድ ጥያቄ ልጠይቅሽ? ክርስቶስ ለባል የሰጠው ትእዛዛ ሚስትህን ክርስቶስ ቤተክርስትያንን በወደደበት ፍቅር ውደድ የሚል ነው። ያ ማለት ነፍሱን እስከመስጠት። ለሚስት ያላት ግን ሚስት ለባሏ ትገዛ ነው። የቱ የሚከብድ ይመስልሻል?» ሳልመልስለት ራሱ ቀጠለ። «ባትወጂም መገዛት ትችያለሽ። ወደሽ አለመገዛት ግን በፍፁም አትችዪም።» ዝም ነበር መልሴ። ከአንዱ ስሜት ወደሌላው መሻገር ምንም አይከብደውም። መከፋቴን አስረስቶኝ አመሸን። «ያው እንደምታውቂው ድንግል ነኝ። በዛ ላይ ቁስሉ ራሱ ሰበብ አይፈልግም።» ብሎኝ እኩለ ለሊት አልፎ ወደ ቤቱ ሄደ።

★ ★ ★
በሚቀጥለው ቀን በስራ የደከመ ሰውነቴን እየጎተትኩ መኪናዬጋ ደረስኩ።
መሽቷል። እቤቴ ገብቼ ማረፍ ነው ያማረኝ። ስልኬ ጠራ። ሲሳይ ነው።
“እራት በላሽ?” “አልበላሁም። ግን ደክሞኛል በጣም።” “እማ ቆንጆ እራት ነው የሰራችው። እየጠበቀችሽ ነው።” “ትቀልዳለህ እንዴ? ማን ነኝ ብዬ ነው እናትህ ቤት እራት ልበላ የምመጣው?” “ማንም መሆን አይጠበቅብሽም። ሰው መሆን የእማን እራት ለመብላት በቂ ነው።”

★ ★ ★
አመመኝ። የቤተሰቡ ፍቅር አሳመመኝ።
“ደህና ነሽ ግን?”
“ምነው ደስ አላለሽም?”
“ምነው ልጄ ከፋሽሳ?” ይሉኛል እየተቀባበሉ ። አመመኝ። የሚታገለኝን እንባ እየዋጥኩ የደመቀ እራት
በላሁ። የቤተሰብ ፍቅር ህመሜ፣ ንጭንጬ ፣ ሽንፈቴ፣ ድክመቴ መሆኑ
አልገባቸውም። ይሄን ፍቅር በዘመኔ አይቼው አንጊንቼው እንደማላውቅ አያውቁም። የሲሳይ እናት ፊቴን እያገላበጡ፣ ፀጉሬን እየዳበሱ የሆንኩትን ሲጠይቁኝ እናት እንደማላውቅ አያውቁም። አባትየው እየደጋገሙ ‘ልጄ‘ ሲሉኝ። አይኑ ለማያይ ያአረጀ አያቴ እየተላላኩ እና ምርኩዝ ሆኜ እንዳደግኩ አልገባቸውም። እህቶቹ እግሬ ስር በርከክ እያሉ ‘ሲሳይ አስከፍቶሽ ነው? እሱ እኮ ክፍት አፍ ነው።” ሲሉኝ አያቴ ሞቶ የአክስቶቼ ልጆች እንደምናምንቴ እየቆጠሩኝ ተምሬ መጨረሴን አያውቁም። ብዙ አወሩኝ። እቤት ይዟት የመጣ ብቸኛ ሴት መሆኔን ነገሩኝ።

★ ★ ★
እንደምንም ያመቅኩትን እንባዬን መኪናዬ ውስጥ ሲሳይ እቅፍ ውስጥ ዘረገፍኩት። አላባበለኝም። እየደጋገመ እንባዬን እየጠረገ ፣ ፀጉሬን እያሻሸ ጠበቀኝ። “አውሪኝ። የተሰማሽን ሁሉ አውሪኝ።” አለኝ። ሲቃዬ አላስወራ አለኝ።
ጣቶቹን ፀጉሬ ውስጥ ሰዶ ወደራሱ አስጠጋኝ። ይበልጥ ሲቀርበኝ ከመቃወም ይልቅ ልስመው ፈለግኩ። በሌላኛው እጁ እንባዬን ከጉንጬ ላይ ጠራረገው። ከንፈሩ ከንፈሬን የሚነካበት ሰዓት ረዘመብኝ። መጠበቅ አቃተኝ። ሳምኩት። ነፍስ በሚያሳርፍ መሳሙ ለደቂቃዎች ሳመኝ። “ምንም ይሁን ንገሪኝ፣ አንድም ሳታስቀሪ የተሰማሽን ንገሪኝ፣ አንቺ ራስሽን ከምትረጂው በላይ እረዳሻለሁ። እንባሽ ከመጣ አልቅሺ ብቻ ልስማሽ!” አለኝ መረጋጋቴን ሲያይ “አሁን እኮ መሽቷል። ሌላ ቀን ላውራህ?” “ማደር ካለብኝ እየሰማሁሽ አድራለሁ።”
አውርቼ የማላውቃቸውን ብዙ ነገሮች ነገርኩት። ሳለቅስ አያባብለኝም። እጄን እየደባበሰ ይሰማኛል። ስለቤተሰቦቼ ሁሉንም ነገርኩት። አያቴ ሲሞት ከልጅነቴ ጀም ምርኩዙ ሆኜ ስላደግኩ

ያለው
ን ንብረት ሁሉ ተናዞልኝ ነበር የሞተው። በንብረቱ ሳቢያ ዘመዶቼ ሁሉ በፊት ይጠሉኝ ከነበረው በብዙ እጥፍ ጠሉኝ። የደበቅኩት የለም ሁሉንም ነገርኩት። ያልሰማኝ የለም። ያለፍትን ውሳኔዎቼን በሙሉ ቆም ብዬ እንዳይ አደረገኝ። እቤቴ ስገባ እንደሌላው ቀን ኢሳያስ የሌለበት ወና ቤት አላስጠላኝም። አልጋዬ ላይ ጋደም ብዬ ከራሴ ጋር አወራሁ። “በራስሽ መተማመን ካለብሽ ራስሽን እወቂው። ጠንካራ ጎንሽን እና ድክመትሽን ለዪ፣ ድክመትሽን በጠንካራው ነገርሽ ለመሸፈን አትሞክሪ፣ ተጋፈጪው ማሻሻል ያለብሽን አሻሽዪ፣ ያለፈ ቁስልሽን ተቀበዪው እመኚው እንጂ አትሽሺው።” ያለኝን የሲሳይ ንግግር አሰብኩት። ደስ ብሎኝ ተኛሁ።

★ ★ ★
በጠዋት ወደስራ ስገባ ሲስተር ቀለምን ቀድማኝ አገኘኋት ። ጠርቻት ለልጆቿ
የሆነ ነገር እንድታደርግ የተወሰነ ገንዘብ ሰጠኋት። እጄን እያገላበጠች ስትስም
እንባዋ ነካኝ። አቀፍኳት። እስከዛሬ ልረዳት ባለመቻሌ ራሴን ረገምኩት። እቤቷ ሄጄ ልጆቿን ላይላት ለሳምንቱ መጨረሻ ቀጥርያት ስራ ጀመርን።
በህይወቴ ከመቼውም ጊዜ በላይ ደስተኛ ነኝ። ግን ደግሞ መንታ መንገድ ላይም ነኝ። ሲሳይና ኢሳያስ!! የብዙ ዓመት አለሁሽ ባዬ ግን በራሴ ትህምክትና ፍራቻ ያልተረዳሁት ኢሳያስ ሳልነግረው የማስበው እና የሆንኩት የሚገባው ሲሳይ መወሰን ነበረብኝ። ማናቸውንም መምረጥ ህመም አለው። ፈሪ ግን አይደለሁም። አልሸሽም።
★ ★ ★
ውሳኔዬን መጀመሪያ ለሲሳይ ማሳወቅ ፈለግኩና አገኘሁት። ነገርኩት።“እርግጠኛ ነሽ?” አለኝ መጀመሪያ ግራ እየተጋባ “አዎን። መቼም እንደዛሬ እርግጠኛ የሆንኩበት ውሳኔ የለም። ” መለስኩለት “አሁን ነው የገረዝሽኝ። ያማል።” አለኝ ድምፁን ዝግ አድርጎ “አዝናለሁ። አንተ በህይወቴ ፈጣሪ የላከልኝ መልዓክ ነህ። ባልጎዳህ በወደድኩ። ”አልመለሰልኝም። ግንባሬን ሳመኝ። ለመጀመሪያ ጊዜ ሲከፋው አየሁት። ሊሄድ መንገድ ከጀመረ በኋላ መለስ ብሎ እንዲህ አለኝ “ኢሳያስን እድለኛ መሆኑን ንገሪው!!”

★ ★ ★አሁን ጨረስን።★ ★

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
#ወግ_ብቻ
.
=> አድዋ እና ሰበቡ
©በሲራክ ወንድሙ
... ክፍል ፩
....... ይህ ፅሁፍ ኅብረ ኢትዮጵያ በሚል ርዕስ በቴዎድሮስ በየነ በ2008 ዓ.ም ከታተመው የታሪክ መፅሀፍ ውስጥ የአድዋ ድል ከሚለው ምዕራፍ ላይ ለአንባቢ እንዲበጅ (እንዲገባ) በሌላ ቅንፍ በትንሹ እውቀቷን ለማስጨበጥ በሌላ ሌላ ቅንፍ ለመላው አፍሪካ የነፃነት በዓል ምክኒያት በማድረግ ከ ፌስቡክ ሆይሆይታ ና ሆያሆዬ ባሻገር ጦርነቱ ላይ በምናብ በመገኘት ለመዘካከር ነውና ሳትሰለቹ አንብቧት።

መጀመሪያ ላይ ስለአድዋ ጦርነት መንስኤ ሲነሳ የውጫሌው ውል አንቀፅ አስራ ሰባት እንደሆነ በሰፊው ሲነሳ እንሰማለን
ውሉ ችግሩ ምንድነው? መቼ ተፈራረሙ? ውጫሌ የት ነው?

....ውጫሌ በወሎ ወረኢሉ ውስጥ የምትገኝ መንደር ስትሆን ይህን ውል የኢጣልያ መንግስት እና የኢትዮጵያ መንግስት በሚያዚያ 25 ቀን 1881 ዓ.ም በውሉ አስተርጓሚ በግራዝማች ዮሴፍ ንጉሴ የተከናወነ ውል ነው።
ውሉ ጠቅላላ 20 አንቀፅ ሲኖረው ለጦርነቱ መነሻ የሆነው አንቀፅ 17 ነው።

እስኪ አንቀፁን በሁለቱም ትርጉም እንመልከተውና ለጥቀን ሌላውን እንቀጥል:-
#በአማረኛ_የተፃፈው
"የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት ከአውሮፓ ነገስታት ለሚፈልጉት ጉዳይ ሁሉ የኢጣሊያ መንግስት አጋዥነት መላላክ ይቻላቸዋል።"

.... ይላል።
#በኢጣሊያኛ_የተፃፈው_ደግሞ
"የኢትዮጵያ መንግስት ከውጭ አገር መንግስታት ጋር የሚያደርገውን ግንኙነት በኢጣሊያ መንግስት አማካኝነት ማድረግ ይገባቸዋል።"
...የሚል ነበር።

ጣሊያኖች ይህን ውል ከተዋዋሉ በኃላ ለ12 የአውሮፓ መንግስታትና ለዩናይትድስቴትስ ኦፍ አሜሪካ ጭምር October 11 ቀን 1889 ዓ.ም በተፃፈ ደብዳቤ
#ኢትዮጵያ_በኢጣሊያ_ስር_ነች እያሉ አሳወቁ።
በትምህርት ቤት መማሪያ ደብተሮችም ላይ ሁሉ ኢትዮጵያ በኢጣሊያ ጥገኝነት ስር ናት የሚል ታተመ።

ይህ ለአድዋ ጦርነት መነሳት ምክኒያት ና ዋነኛ መንስኤ የሆነው ጉዳይ ሊታወቅ የቻለው አለቃ አፅመ ጊዮርጊስ የተባሉ ቋንቋ አዋቂ አፄ ምሊኒክ በሰጧቸው ትዕዛዝ መሰረት የውሉን ሰነድ በመመርመር የውሉ 17ኛው አንቀፅ የያዘውን ትርጉም መዛባት በመግለፅ ጉዳዩ ኢትዮጵያ የምትጎዳበት ስለመሆኑ ጭምር በማስረዳት በሰጡት ቃል ነው።

............. ይህን ያህል ስለ17ኛው ውል መሳሳት አቅጣጫ ከያዝንና ካየን የትርጉሙ መጭበርበር እንዴት ከአለቃ አፅመ ጊዮርጊስ ለአፄ ምሊኒክ እንደደረሰ እንቃኝ።
አለቃ አፅመ ጊዮርጊስ ባልታተመ (ይህ የወንድማችን ቅፅ አንድ እስከወጣበት ጊዜ ድረስ) መፅሀፋቸው እንደገለፁት ለአፄ ለምሊኒክ እንዲህ ሲሉ በደብዳቤ አመለከቱ :-
<< የተፃፈው ውል ኢጣሊያ አገር የሚሄደው ማለፊያ ነው።
ብቻ 17ኛውን ክፍል ይመልከቱት።ዛሬ በሚዛን ብትመዘን የብር ተመን አትሆንም ካንድ ዓመት በኃላ ግን ከሺህ ቶን ፈረሱላ እርሳስ ይልቅ ትከብዳለች። >>

... ይህ ደብዳቤ እንደ ደረሳቸው ምኒሊክ አንቶኔን አስጠርተው እንደገና ጠየቁት።
አሁንም ግልፅ ባልሆነ አነጋገር አጭበረበራቸው። እንዲህም አለ << ታዲያ ይህ ምን ክፋት አለበት (17ኛው ክፍል) እኛ የርስዎ አሽከርዎ ፖስተኛ መሆናችን ነው እንጂ።>>... | አለቃ አፅመ ጊዮርጊስ የኦሮሞ ህዝብ ታሪክ (ያልታተመ)|

....... የውሉ ዋና ፀሀፊ ፒዬትሮ አንቶኔሊ ከአፄ ምሊኒክ ከእቴጌ ጣይቱና ከመኳንንቱ ፊት ቀርቦ ይህን የውጫሌ ውል እምቢ ካሉ ጦርነት መነሳቱን እንዲያውቁት ያስፈልጋል ብሎ ሲደነፋ እቴጌ ጣይቱ ደግሞ እጥፍ ጊዜ ቱግ ብለው ተቆጡና፤
" የዛሬ ሳምንት አድርገው። በዚህ የሚደነግጥልህ የለም ሂድ የፎከርክበትን አድርግ። እኛም የመጣውን እናነሰዋለን። እግሩን ለጠጠር ደረቱን ለጦር ሰጥቶ አገሩን የማያድን ሰው በዚህ የሌለ አይምሰልህ።
የገዛ ደሙን ገብሮ ለገዛ አገሩ መሞት ጌጥ ነው እንጂ ሞት አይባልም። አሁንም ሂድ አይምሽብህ የፎከርክበትን በፈቀደህ ጊዜ አድርገው። እኛም እዚህ እንቆይሃለን።.....
እኛ ለራሳችን እንበቃለን የሀገራችንንም ክብር እንጠብቃለን። አንፈራችሁም! በፈቀድነው ጊዜ ከመሬታችን ከሀገራችን ተራራ እንደ ድንጋይ እንፈነቅላችኃለን።" አሉት።

እርሱም ከአዳራሹ ሊወጣ ከሞከረ በኃላ እንደገና መለስ ብሎ
"የምንገጥመውኮ ጦርነት ነው፤ ወንዶቹስ በሆነላቸው እንኳን ሴቲቱ" አላቸው።
"የእኔ ሴትነትና ያንተ ወንድነት የሚለካው እዚያው ጦር ሜዳ ነውና እንዳትቀር።"ብለው መለሱለት።
እንግዲህ የአጭቤው(አጭበርባሪው)አንቶኔሊ አንቶዬ(ስምህን ቄስ ይጥራው አንተ ሰላቢ😀 ለነገሩ....😀😀)
በንቀት እና በወኔ ሙላት የተመላለሱትን ቃለ ምልልስ አይተናል።

የጣይቱን ፉከራ በጦርነቱ ውስጥ በሰራችው ገድል የምናውቀው ነው መቼስ።
ያው ዘመን እየመጣ ዘመን በሄደ ቁጥር እነእቴጌን መሰል ሴቶችን ማጣት የሀገር ህመም ነው። መቼስ ዘንድሮ እንደሆነ ፎክረውና ብልሃት ምሰው ከሚያሸንፉ ይልቅ ቁራጭ ጨርቅ በላያቸው ላይ ለጥፈው ወንዱን እያፈዘዙ አንዴ ከቆመ ዛፍና መኪና ጋር እያጋጩ አንዴ ቦይ ውስጥ እየከተቱ ሆኗል ብልሃቱ። (ቱ ደሞኮ እኛኑ ነው 😂)
እኔስ ስንቴ ነው አንገቴን እስኪያመኝ እየሾፍኩ ቆሎ በትኜ ጣቢያ ያደርኩት 😀 " መገን" አለ ወሎ።

የአንቶኔሊን ንቀት ታክል በዘመኔ ላይ መማረር ቢኖርብኝም ይሁን ይመቻቸው ብያለሁ።
የዚህችን ክፍል መዝጊያ ከመፅሀፉ ውስጥ ባገኘዋት ፈገግ በምታስብል ገጠመኝ ልዝጋና በቀጣዩ ቀን በሌላ ክፍል ልመለስ....

...... አንቶኔሊ ከስብሰባው ሲወጣ ምኒልክ ለጋሲዮን ድረስ የሚሄድበት በቅሎ ስጡት ብለው ተሰጠው። አንቶኔሊ በቅሎ ለሰጠው አሽከር አንድ መቶ ብር ሰጠ።
አሽከሩም የተሰጠውን ብር ይዞ አዳራሽ ገብቶ ለምኒልክ ነገረ።
ራስ መኮንን ነበሩና " ጉርሻ ከሆነ ይበዛል። ጃንሆይ ለሰጡት በቅሎ ከሆነም ያንሳልና ይመለስ!" አሉ። ምኒልክም ስቀው ለአሽከሩ "ጉርሻ ነውና ውሰደው" አሉት።

........... ዛሬ የአድዋን ድል መዳረሻ ቀናት አስመልክቼ በቅንጭብ ያቀረብኩት ክፍል ይህን ይመስላል በቀጣይ አንዳንድ የጦርነቱን ነጥቦች እናያለን ሀሳብ አስታየታችሁን ፃፉልኝ።
የተሳሳትኩትም ካለ አርሙኝ ያጠፋሁትም ካለ ይቅርታ እጠይቃለሁ።🙏

ለዚህ ፅሁፌ በዋነኝነት ኃብረ ኢትዮጵያ በሚል ርዕስ በ2008 ዓ.ም በቴዎድሮስ በየነ የታተመውን ቅፅ አንድን ተጠቅሜያለሁ።
ቸር ቆይታ!!!
- ለማድብን እጅጉ ( ቃሲም )
- ለበፍቃዱ አረጋ
#እና
- ለቃለአብ ሲሳይ (ናታኒም)
ምስጋናዬ ይድረስልኝ
©
#ሲራክ ወንድሙ @siraaq
@wegoch
@wegoch
#ወግ_ብቻ
.
አድዋ እና ሰበቡ
©በሲራክ ወንድሙ
ክፍል ፪
አድዋና ሰበቡ በሚል ርዕስ ለአድዋ በዓል መዳረሻ የምናወጋት ወግ እና ጥቁምታ ዛሬም ቀጥለናል። በዚህ ክፍል ስለ ታላቁ የአድዋ ጦርነት አዋጅና የጦርነቱን ሁነት አጠር መጠን አድርገን እናይ ዘንድ ወድጃለሁ።

እንደቀደመው ክፍል ይህንንም ክፍል ለማሰናዳት ህብረ ኢትዮጵያ ቅፅ ፩ በሚል ርዕስ በቴዎድሮስ በየነ በ2008 ዓ.ም የታተመውን የታሪክ መፅሀፍ አገላብጫለሁ።
የአፄ ምሊኒክ አድዋ ጦርነት የክተት አዋጅ የሚለውን መንደርደሪያ አድርገን እንሻገር።

አዋጁ እንዲህ የሚል ነበር።
" አዋጅ አዋጅ የደበሎ ቅዳጅ
የሰማህ ላልሰማ አሰማ
እግዚአብሔር በቸርነቱ እስካሁን ጠላት አጥፍቶ አገር አስፍቶ አኖረኝ።
እኔም እስካሁን በእግዚአብሔር ቸርነት ገዛሁ። እንግዲህ ብሞትም ሞት የሁሉ ነውና ስለኔ ሞት አላዝንም። ደግሞ እግዚአብሔር አሳፍሮኝ አያውቅም።
እንግዲህም ያሳፍረኛል ብዬ አልጠራጠርም።
አሁን አገር የሚያጠፋ ሃይማኖት የሚለውጥ ጠላት በእግዚአብሔር የወሰነልንን የባህር በር አልፎ መጥቷልና እኔም ያገሬን ከብት ማለቅ የሰውን መድከም አይቼ እስካሁን ዝም ብለው ደግሞ እያለፈ እንደ ፍልፈል መሬት ይቆፍር ጀምር።
አሁን ግን በእግዚአብሔር ረዳትነት አገሬን አሳልፌ አልሰጠውም። ያገሬ ሰው ፤ ካሁን ቀደም የበደልሁህ አይመስለኝም። አንተም እስካሁን አላስቀየምከኝም። ጉልበት ያለህ በጉልበትህ እርዳኝ። ጉልበት የሌለህ ለልጅ ለምሽትህ ለሀይማኖትህ ስትል በሀዘን እርዳኝ።
ወስልተህ የቀረህ
#እንደሁ ግን ትጣላኛለህ።
አልተውህም። ማሪያምን ለዚህ አማላጅ የለኝም።
ዘመቻዬ በጥቅምት እኩሌታ ነውና የሸዋ ሰው እስከ ጥቅምት እኩሌታ ድረስ ወረኢሉ ከተህ ላግኝህ።"

|መስከረም 7 ቀን 1888 ዓ.ም
#ሸዋ አዲስ አበባ|
(የአዋጁ ፅሁፍ ምንጭ ገብረ ስላሴ ወልደ አረጋይ ታሪክ ዘመን ዘዳግማዊ ምኒልክ ገፅ 225......)
እንዲህ በሚል አይረሴ የአዋጅ ጥሪ ህዝቡ አብሮ ድሉን እንዲቀዳጁ ጋበዙ።

በዚህ የአዋጅ ጥሪ ውስጥ እምዬ ምሊኒክ የመንፈስ ጥንካሬያቸው ፣ በአምላካቸው ላይ ስላላቸውና ስለነበረባቸው ጥብቅ ቁርኝትና የመንፈስ ቅርበት እንዲሁም ከሚመሩት ህዝብ ጋር ስላላቸውና ስለነበራቸው ግንኙነት እንዲሁም መተማመን ሲያወጉ ድሉ የራሳቸው እንደሆነ ግን ድሉ የሚመጣው በመተባበርና በአንድነት እንደሆነ ሲያትቱ እንሰማለን።

ከዚህም በተጨማሪ ዛሬ በኛ ዘመን የት ገዳም እንደመነነ ፣ የት መሬት እንደተቀበረ ወይም የት እንደተሰወረ የማናውቀው ኢትዮጵያዊ ጨዋነት የተላበሰ አዋጅ ነበር። ልብ ይሞላል ነብስ ከፍ ያደርጋል።

የሆነው ሆነና እንደጥቁምታ ያ የተሰወረብን ጨዋነትን ስታገኙ ለምንዱባን ሳንቲም መወርወር እንደማይወድ ስስታም ባለፀጋ አትለፉት!። ያዙ!!
ምናልባት ካለብን የስብዕና እና የብልሹ ባህሪ ችግራችን ያወጣናል።
ያው ሞኝ እየመሰለን ስለምናልፈው ነው።

ለማንኛውም ወደ ቀጣዩ ስንለጥቅ በቅንፍ ውስጥ ስናልፍ ለማለት ነው። ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ጥቅምት 2 ቀን 1888 ዓ.ም ሰራዊታቸውን አስከትለው ወደ አድዋ ለመዝመት ከአዲስ አበባ ጉዞ ጀመሩ።

ወደ አድዋ የዘመተው የኢትዮጵያ ወገን የጦር ቁጥር ጥቂት አከራካሪ ቢሆንም
#ኤጭ የሚያስብል ደረጃ አልደረሰም።
እስኪ ከግምቱ ጥቂት እንቅመስ፦
ቶኪ የተባለው ፀሀፊ የኢትዮጵያ ወታደር 70.000 - 80.000 ይደርሳል ሲል አንቶኔሊ ደግሞ ከ110.000 - 120.000 ነው ይላል። ባራቴሪ እንዳለው ደግሞ ከ75.000 - 80.000 ይደርሳል ብሏል።ኢልግ ፣ ዌልብ እና ካፒቴን ክሎሼት የተባሉ የታሪክ ፀሀፊዎችም እንዲሁ የእውቀታቸውን ግምት ወርውረዋል።

.... ጦርነቱ እንደታወቀና የክተት አዋጁ ከታወጀ በኃላ የጎጃም ፣ የጎንደር ፣ የወሎና የላስታው ከ300 - 500 ኪ.ሜ ያህል የሀረር ፣ የባሌ ፣ የአርሲ ፣ የከምባታ ፣ የሲዳማ ፣ የጅማ ፣ የከፋ ፣ የወለጋና ፣ የኢሉባቡር ጦር ከ 1000 - 1500 ኪ.ሜ ድረስ ያለውን አገር አቋርጦ ተጉዟል። (በነገራችን ላይ የተነሳው ሰራዊት ሁሉ ከጦርነቱ ቦታ አልደረሰም። ሰራዊቱ በከፊል ገና ጉዞ ላይ እንዳለ ጦርነቱ ተጠናቆ እንደነበረ ኢልግ የተባለ የታሪክ ፀሀፊ ይናገራል።)

...አጭር ሱሪና ጥብቆ ለብሶ በዚያ ላይ ነጠላውን ደርቧል።
የሚራመደው በባዶ እግሩ ከድንጋይና ከእንጨት እንቅፋት ጋር እየታገለ ውስጥ እግሩን እሾህ ...በሙቀት ጊዜ ረጫሞ እያቆሰለው ፤ ለራሱም ቆብ ስለሌለው የፀሀይ ሀሩር ...የሌሊት ቁር ይፈራረቁበት ነበር።

ቢታመም ያገር ባህል መድሃኒት ከመጠቀም በቀር ደንበኛ ህክምናም አያገኝም ነበር።
በጉዞ ላይ እያለም ራሱ የባህሉን መድሃኒት እንደልብ ማግኘት ይቸግራል እንደነበር ይነገራል።
.....ጦርነቱ የአፍሪካ የነፃነት እንቁ የጥቁር ህዝቦች የተስፋ ምድርና የጀግኖች እናት በተባለችው የእምዬ ምኒልክ ሀገር የሆነችው እምዬ ኢትዮጵያ አሸናፊነት በታላቅ ድል ተጠናቀቀ።
አንድ ቀን ብቻ የፈጀው ይህ ጦርነት የተካሄደው አድዋ (ትግራይ ውስጥ ) በእለተ እሁድ የካቲት 23 ቀን 1888 ዓ.ም ነበር።

የታላቁ የአድዋ ጦርነት ለሉአላዊነቷና ለነፃነቷ በተከፈለ የደምና የአጥንት መሰዋዕትነት በዚህ መንገድ ተጠናቀቀ።
አድዋ የእልፍ የአውሮፓ ጎልያዶችን እብሪት አፈር ዲሜ ያበላ ጠጠር ነው። ( ጠጠር ስል ተምሳሌቱን ለማጉላትና ጨዋታውን ለማድራት እንጂ ድሉን ለማሳነስ የተጠቀምኩት ቃል እንዳልሆነ ይታሰብልኝ 🙏)
መላው የአውሮፓ ጎልያዶችን አንገታቸውን የደፉበት እጃቸውን በአፋቸው ያስጫነ ታላቅ ድል ነው።

እኛ አይመስለንም እንጂ ድፍን አፍሪካን ያነቃቃ የጥሪ ደወልም ነበር።
ኑ ቤቴ ግቡ አጥንቴን ጋጡ ደሜንም ጠጡ እናንተን አንችልም ንገሱብን ባሉ ለአፍሪካ ሀገሮች ንጉሳቸው እንደሚከሰስ ሀይሉ እንደሚረታ የተረዱበት ችቦና ደመራ ነው አድዋ።

አድዋ እልፍ ነው። ነጥቡ አንድ ብቻ አይደለም።
በእርግጥ ድል አድርጎ ድሉን ለናቀው የኛን መሳይ ትውልድ አድዋ ምንም ነው።
የካቲት ሀያ ሶስትን ጠብቆ ባንዲራ ለብሶና ፎቶ ተነስቶ አድዋ አድዋ ከማለት በቀር እያንዳንዱ ሰው ለነገይቱ ኢትዮጵያ አቅሙ በፈቀደ መርዳት ፣ ማሰብና መታተር አይደለም ተስፋው።
እንደገና የካቲትን መጠበቅ ነው። እጣችን!
የአያቱን "መቃብር ቆፋሪ" እንደምትለዋ ወግ!

አድዋ ረቂቅ ነው ያኔ ሆነን ዛሬን ማየት ቢቻለን አድዋ ለኛ ባልተገባ ነበር።
እኔ በግሌ ለአድዋ የተከፈለውን መሰዋዕትነትና ሀገር ማዳን ሳስብ ዛሬ በፍቃደኝነት ራሱን ለአውሮፓ የሚያንበረክክ እና የሚያስገዛ ትውልድ እያለ ያ ሁሉ ዋጋ መክፈል ለምን እላለሁ።
ዛሬ ፊታችን ቢቆሙ መልሳችን ምንድነው?
የቀረው ቢቀር ፍቅር ይሉት መንፈስ ባጣ ዘመን የጣዲቄ ህመም ያመኛል።

የቀረው ቢቀር እምዬ ምኒልክ ከጦር ከመሪዎቻቸው መካከል ከፈረሱ ላይ ገበየሁን ባጡ ጊዜ ያለቀሱት እምባ የታመሙት ህመም ያመኛል።
የቀረው ቢቀር ቀድሞ ቀድሞ ኃላ የቀረው ትውልድ ስልጣኔ ባለው ስይጣኔ ፣ እውቀት ባለው ድድብና ሲኮራ ያመኛል።
የቀረው ቢቀር....!
.......
የቀረው ይቅርና ይህን መፅሀፍ ሳነብ እምባ ካስቀረሩኝ ፣ ቅንነት እና እዝነትን ካስጨበጡኝ ነጥቦች አንዱን ላንሳና በጥቁምታ ልሰነባበት።
@wegoch
@wegoch
@siraaq
👇👇👇
ይቀጥላል
☝️☝️
.... የቀጠለ
...በመጋቢት 23 ቀን 1888 ዓ.ም እምዬ ምኒልክ ለሙሴ ሽፍኔ የፃፉትን ደብዳቤ እንመልከት። እንዲህ ይላል። " በጥጋባቸው አድዋ ላይ ተዋግተው ድል ሆኑ። እኔ ግን በድንቁርነታቸው ብዛት የነዚያን ሁሉ ክርስቲያን ደም በከንቱ መፍሰሱን እያየሁ ድል አደረኳቸው ብዬ ደስም አይለኝም።"አሉ።
እምዬ ሰው የመሆን ጥግ ኢትዮጵያ የመሆን ውሃ ልክ ናቸው።

ምናልባት በኔ እሳቤ ኢትዮጵያ መሪ ያጣችው ከሳቸው በኃላ እንደሆነ ይሰማኛል።
በመሪ ስም እንደ እረኛ ከኃላ ሆነው ነድተው ነድተው ሀገሪቷን የት እንደከተቱ ለማስረዳት መነሳት ለቀባሪ ማርዳት ነው።

መቼስ አምላክ ተማፅኖዋን ሰምቶ እርስ በእርስ ድል አይሉት ውርደት እየደጋገምን ራሳችንን ከማቆሸሽና የድግግሞሽ ጦስ አውጥቶ የሚነዳ ሳይሆን የሚመራ መሪ ይስጣት እላለሁ።ደሞ አሜን በሉ ( ከፈለጋችሁ አትበሉ እናንተ ባትሉ እኔ እላለሁ)

..... ዛሬ አድዋና ሰበቡ ፪ በሚል ርዕስ ያዘጋጀውትን ፅሁፍ እንዲህ አየነው።
በቀጠሉት ቀናቶች ውስጥ ስለ አንዳንድ የአድዋ ጀግኖች ፣ በጥቂቱ እናነሳለን በተለይ በተለይ በግሌ በጣም ስለሚገርሙኝ አዝማሪዎች ከእዛም ከዚህም በቃረምኩት የንባብ እና የማድመጥ ቃሬሚያ በመነሳት አንዳንድ ነገር ልል እችላለሁ።
የአብዬ ፀጋዬን ግጥም ጨምሮም በተለያዩ ፀሀፊያን የተፃፉ ግጥሞችን እና ሙዚቃዎችን(የጂጂንም አድዋ) እያነበብን ፤ እያደመጥን እንዘካከራለን።

ይህን ሁሉ ብዬ ወስልታችሁ ፅሁፌን ያላነበባችሁ እንደሁ ውጊያዬ በቃል ነው።😀
በተረፈ ሀሳብ አስታየታችሁን ፃፉልኝ።
የተሳሳትኩትም ካለ አርሙኝ ያጠፋሁትም ካለ ይቅርታ እጠይቃለሁ።🙏

ለዚህ ፅሁፌ በዋነኝነት ኃብረ ኢትዮጵያ በሚል ርዕስ በ2008 ዓ.ም በቴዎድሮስ በየነ የታተመውን ቅፅ አንድን ተጠቅሜያለሁ።
ቸር ቆይታ!!!
©ሲራክ ወንድሙ
@siraaq
ለወንድሜ ማድብን እጅጉ (ቃሲም ) ምስጋናዬ ይድረስልኝ!🙏
@wegoch
@wegoch
@wegoch
EMINƎM

Had a dream i was king, i woke up still king!
ሲጨንቀኝ ተስፋ መቁረጥን ስገፋ መውደቅን ስከፋ ማልቀስን
አላስተማርከኝም።
ሳላውቅህ ሳላገኝህ አንስቶ ህልሜን አምነዋለሁ። ገና ፈላ እያለሁ ነው።
ትምህርት ቤት ውስጥ ዞር ብዬ አይቻት የማላውቅ ቢጫ ልጅ በህልሜ
መጣች አመለጠኝ አፈቀርኳት ቀልድ እንዳልያዝኩ የገባኝ እስካድግ
ሊለቀኝ አለመቻሉን ሳይ ነበር። 7ዓመት ቆይቼ ስፈራት የኖርኳትን ልጅ
ስካር አጀግኖኝ ነገርኳት። ተሳቀብኝ ሁላ። በዛ ዕድሜ ያለ ወጠጤ
ሊሰማው እንደሚችለው ተሰማኝ። እንደማልወደድ አመንኩ። ቀድሞም
"ደስ ሲል" ያለኝ አልነበረም። የገባኝ መሰለኝ ልፈቀር እንደማልችል
ተሰማኝ። ደደብኩ። ጨለማ ውስጥ መቀመጥ በሬን ዘግቼ መዋል ሰው
አለማግኘት ጀመርኩ። ስልኬን ሸሸሁት። መፃህፍትና የያዟቸውን የፍቅር
ታሪኮች እደበቃቸው ጀመር። የስብሐትን "ወጣት ነህ" መርህ እንኳ
አፈርኩበት።
ከቀናት በሁዋላ ወደቀልቤ መመለስ ስጀምር አደመጥኩህ። የሆንኩትን
ቀድመህ አውቀኸዋል። አረጋጋኸኝ። ሰቅለዋት እንጂ ወርደህ አይደለም
አልኸኝ
"They say the competition is stiff
But I get a hard dick from this shit, now stick it in"
"ትፈቀራለህ ትወደዳለህ የምናባህ Inferiority complex ነው።" "የምን
ጡቴን ተቆረጥኩ ቁላዬን ተሰለብኩ ብሎ ማለቃቀስ ነው። መጀመሪያ
መብራቱን አብራው" ስትለኝ ረጅም ጊዜ ጨለማ ውስጥ እንደሰነበትኩ
አወቅኩ። ለአባቴ ስል እንኳ ብርሐን ለማየት ያልፈቀድኩ እኔ ለራሴ ስል
አበራሁት።
"But don't let 'em say you ain't beautiful oh
They can all get fucked. Just stay true to you"
ከራሴ ፍቅር ያዘኝ። የማልወደድ እኔን አስወገድኩ። አዲስ እኔን ሰራሁ።
ያስተማርከኝ ይወዱሃልን አይደለም 'የማይወዱህ ይበዱ'ን ነው። 'አንተ
ለራስህ በቂ ነህ'ን ነው። ያኔ ነው ለመጀመሪያ ጊዜ ፍቅር እስከመቃብር
ላይ እንዳለችው ውድነሽ በጣሙ ራሴን በመስታወት አይቼ "አፈቅረኛለሁ"
ያልኩት። አባቴ ይሙት ከዚያ አንስቶ ለመኖር ብቻ እኖራለሁ እንጂ
ለመወደድ አልኖርኩም።
ራሴን አልፌ ማየት ስጀምር በወጠጤ ጉልበቴ ባልጠና ጡንቻዬ
መንግስት የሚባል የደደቦች ስብስብን ልቃወም አሰኘኝ። የምርጫ
ምልክት እየዞርኩ መገንጠል የኮሚዩኒቲ ፖሊሲንግ የምሽት ተረኞች በር
ስር ኢህአዴግ ይበዳ አታሸንፉም የሚል ወረቀት ማስቀመጥ ጀመርኩ።
ጓደኞቼ አብረውኝ ነበሩ። ከብዙ ጣጣ በሁዋላ ልንቀላቀላቸው ያሰብናቸው
ድውያን ከምጠላው መንግስት በምንም እንደማይለዩ ተረዳሁ። አቋረጥኩ።
አመለጠኝ። ጓደኛዬ አምልጦኝ ሄደ። ያዙት። አሰሩት። ሃገር ምድሩ ባንተ
ጦስ ነው አለኝ። "ደደብ ነህ ክፉ ነህ ከሃዲነህ" አሉኝ። አስራሁለት እንኳን
ያልተፈተንኩ ግልፍተኛ ብቻ ነበርኩ። ይሄ እንደሚመጣ እንኳ አላሰብኩም።
ለቅሶ በረከተብኝ። ያየሁትን አላዩም የጓደኛዬን ጀርባ እያየሁ
የምሰቃያቸውን ሌሊቶች አያውቁም። ሁሉም ወረደብኝ። በድጋሚ አመንኩ።
ጥፋተኛ ነኝ አልኩ። ከነበርኩበት ገጠር ስመለስ ከተማው በሙሉ የአስራ
ስምንት ዓመት እኔ ላይ አብሮ ጠበቀኝ። እንባዬ ለራሴ ያቃጥለኝ ነበር።
በፍፁም ፍቅር የሚወደኝ ወንድሜ የጠራኝን ልደት እሱ እንኳን እያለቀሰ
አካልበው አስወጡኝ። አሁን ደግሜ አላለቀስኩም። ዓለም ቢተወኝ
የማትተወኝ አንተ እንዳለህ አውቃለሁ። አይስቅም ይሉሃል እየሳቅክ
ተቀበልከኝ። በሬን ዘጋሁ። መብራቴን አጠፋሁ። በጆሮዬ ተጠግተህ
ትንፋሽህን ሁላ እስክሰማው በፍፁም እልህ እኒህን ሁሉ አልክልኝ።
It's a little too late to say that you're sorry now
You kicked me when I was down
But what you say just (don' hurt me)
That's right bitch
And I don't need you (no more)
Don't wanna see you
Ha, bitch you get (NO LOVE)
You showed me nothing but hate
You ran me into the ground
But what comes around goes around
I don't need you (no more)
ልክ ነህ'ኮ ግን ግን ቢሆንም ቢሆንም ብቻዬን ነኝ አልኩህ "አንተ ደደብ
ላንተ መሰለኝ የማወራው" አልኸኝ።
"I ain't never giving in again
Caution to the wind, complete freedom
Look at these rappers, how I treat them
So why the fuck would I join 'em when I beat 'em"
ቀጥሎ ምን ይባላል። "አሜን ነው" እያልኩ መኖር ጀመርኩ። ሁሌም
ለጥያቄዎቼ መልስ አንተ ጋር አለ። ለህመሜ ፈውስ አጥተህለት
አታውቅም። "ኢየሱስን ተቀበል" ለሚሉኝ ሁሉ አፌን ሞልቼ
"ይሄው የኔ ኢየሱስ ማን ነው የእስራቴን ገመድ የበጠሰው ማን ነው
ያዳነኝ Eminem አይደለም ወይ እላቸዋለሁ" ሁሌም ባንተ ብርቱ ነኝ
ጌታዬ።
የተወደዳችሁ ቅዱሳን if Eminem's songs can't help you to move
on sorry no one can
ሰብዕናዬን በጭብጨባና ጋጋታ ላይ እንዳልመሰርት ሆኜ ተሰርቼበታለሁ።
እኔ እስካለሁ የእኔ ንግስናም ሆነ አምላክነት ይቀጥላል። Eminem ይባረክ
Be king think not why be a king when you can be a god!

©ክቡር ሰይጣን 🖤🖤🖤

@Mahletzerihun
@wegoch
@wegoch
የትዳር አጋራችንን እግዜር ነው የሚሰጠን ብላችሁ የምታምኑ ሰዎች .... እስኪ አንዴ ጠጋ በሉ! የምራችሁን ነው?

እግዜር ለአዳም ሄዋንን የሰጣትኮ ሴት በምድር ስላልነበረ ነው!

ምድር በሰው ዘር ከሁለቱም ወገን ተሞልታ ራስሽን ፈልገሽ አጊንተሽ የሚስማማሽን ባል ፈልገሽ የምትመርጪበት ማሰቢያ እና ልብ ሰጥቶሽ .... አሁን ቤተሰብ እንኳን ለልጁ ሚስት ወይ ባል በማያጭበት ዘመን እግዜርን ማስቸገር አግባብ ነው?

እኔ የምሬን ነው እሺ አግብተሽ ... ተፋታሽ ... ከዛ እግዜር ሰጠ እግዜር ነሳ ልትዪ ነው ወይስ የሰይጣን ስጦታ ነበር ልትዪ?

አንተኛው ራሱ አስር ገርል ፍሬንድ ጠብሰህ እግዜርን ራሱ አምታተኸው ስታበቃ .... አስራ አንደኛዋን እግዜር ሰጠኝ ልትል ነው? (አስሮቹ ሳምፕል ናቸው?😜)

ስናገባ 'እግዜር ነው የሰጠኝ' ስንጣላ 'ይሄ የተረገመ ሰይጣን!!' (ሰይጣን ራሱ እኮ ግራ ገባው)

እስኪ እቤታችሁ ቁጭ በሉና ሄዋን አንኳክታ ትመጣ ከሆነ ጠብቁ.... ድህነት ብቻ ነው የሚያንኳኳባችሁ!!

አንቺም ወንድ በደረሰበት አትድረሺና 'ባሌ በመኪና ይምጣ' 🤪ብለሽ ፀልዪ እስኪ .... ተው እንጂ ....

ደሞ አንዳንዶች አለን እንጂ "እገሌን የእኔ ካደረግክልኝ!" ብለን የምንፀልይ ... ከዛ ደግሞ በአመቱ ሌላ እገሌ .... ፈጣሪ ራሱ ዝርዝሩ ብዝት ብሎበት .... ለፈርኦን እንዳለው 'ኸረ ህዝቤን ልቀቂ!' ነው የሚለው !!

አታፍሩምኮ ንጉስ ሰለሞንን በ700 ሚስቶች እና በ300 እቁባቶች ጌታ ነው የባረከው ትሉኝ ይሆናል😜😜😜

ከሆነ በጊዜ ንገሩኝ እስኪ ... በቀረው የእርጅና ዘመኔ አንድ አስሩን ላደራጃቸውና ተስማምተው በፍቅር እንዲያስተዳድሩኝ ፆም ፀሎት ልግባ 🤣🤣🤣🤣

እህህ የምር እረፉኣ? ስለ ሚስት ራሱ 700 ሚስትና 300 እቁባት የነበሩት ጠቢቡ ሰለሞን ያለውን ጥቅስ እየጠቀሳችሁ ..... ብልህ ሚስት ... አስተዋይ ሚስት....

ከ1000 ውስጥ የትኛዋ ነበረች አስተዋይዋ? በስማቸውስ ያውቃቸው ይሆን እንኳን በስብእናቸው?

ንግስተ ሳባ ናታ በሉ ደሞ ...

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
2024/09/23 20:16:17
Back to Top
HTML Embed Code: