Telegram Web Link
ድሮ አስረኛ ክፍል ተማሪ ሳለን ነፍሰ ቀጭኑ ኬሚስትሪ መምህራችን እንዲህ ሲሉ ጠየቁን ።
ውሀ ከምን እና ከምን ንጥረ ነገሮች ነው የተፈጠረው ?🙂
ብዙ ተማሪዎች ይህችን ቀላል ጥያቄ ለመመለስ ተቅለበለብን ። መምህሩ ግን ከሁሉም ተማሪ ይልቅ ትኩረታቸውን ስንሻው ላይ አድርገው እንዲመልስ አስገደዱት ።
ስንሻው ከእንቅልፉ የተነሳ ይመስል አይኑን አሻሽቶ ትንሽ ቆየና መምህሩ ጥያቄውን እንዲደግሙለት ጠየቃቸው። /በነገራችን ላይ የስንሻው አባት ልጃቸው ትምህርት እንዳይገባው ተደግሞበታል ብለው ስለሚያስቡ እሱን ይዘው ያልተንከራተቱበት ፀበል አልነበረም ። ኋላ ላይ ቢታክታቸው ጊዜ እርግፍ አድርገው ተውት ! እርሱም ትምህርት አይንህን ላፈር ብሎ ማንበብ እና ማጥናቱን እርግፍ አድርጎ ተወው /
"እኛ የምን ጠጣው ውሀ ከምንና ከምን ውህደት ተፈጠረ ? " ብለው ጥያቄውን ደገሙለት ።
ውሀ ልማት እና ቀበሌ ተዋህደው በገጠሙት የቧንቧ መስመር ነው የተፈጠረው ! ብሎ ሲመልስ ያልደነገጠ ተማሪ አልነበረም ። ሁላችንም እያሾፈ ነው ብለን በትኩረት አየነው ።
እሱ እቴ !
ልቡ ደጭ እንኳ አላለም !
“ስ ! ውይ ይቅርታ” አለን መልሶ .... በቃ ኦክሲጂንና ሀይድሮጂን ታውሰውት ነው ማለት ነው ብለን ማስተካከያውን በጉጉት መጠባበቅ ያዝን !
“ውሀ ልማት እና ሰሜን ሸዋ ዞን በመተባበር ነው “ ብሎ እርፍ አለው ።
ነፍሰ ቀጭኑ መምህራችን በንዴት ተነፋፍተው ነብር አከሉ ! አለ አይደል የቤት ውስጥ ድመት ስትቆጣ እንዴት ነው ኩፍ የምትለው ?
መምህራችን ኩፍ አሉ ።
በስመአብ !
አስተማሪ ሲናደድ ለካ እንደዚህ ያስፈራል ?
ከአስተማሪም ሁሉ ደግሞ ኬሚስትሪ አስተማሪ ሲናደድ በጣም ያስፈራል ። የሆነ ሰልፈሪክ አሲድ ከላብራቶሪ አንስተው ፊቱ ላይ የሚከለብሱበት ሁሉ መሰለን ።
“ተነስ !”
ስንሻው ተነሳ ።
“እነ ሚካኤል ፣ እነ እዮብ እነ አቤል ኢንጅነር ወይ ዶክተር ሲሆኑ ሻንጣ ተሸካሚያቸው እንደምትሆን አልጠራጠርም “ ብለው ሞራሉ ላይ ቀዝቃዛ ውሀቸውን ከለበሱበት ።
እንደፈራነው ከወራት በኋላ ስንሻው ማትሪክን ወደቀ ። እኛ ፈተናውን በጥሰን አለፍን ።
እኛ አስራ ሁለተኛ ክፍል አልፈን ለዩንቨርሲቲ ስንዘጋጅ ስንሻው የሆነ ትምህርት እንደከረሜላ አሽጎ የሚሸጥ ኮሌጅ ዲፕሎማ መማር እንደጀመረ ሰማን ።
ግቢ ሁለተኛ ዓመት ተማሪ ስንሆን ስንሻው ቀበሌ ስራ አጊንቶ መግባቱ ተነገረን ። ያኔ በሱ ሙድ ያልያዘ አልነበረም ።
እንደውም አንድ ቀን በድሉ የሚባል ቸካይ የነበረ ተማሪ ወደኔ ጠጋ ብሎ "ስንሻው በዚህ ድድብናው ቀበሌ ስራ ማግኘቱም ተመስገን ነው ብሎ ገለፈጠ ። "ስንሻው እኮ ቀን ስራ እንኳ ይበዛበታል ። እንደ ህንዶች ሰባቴ ቢፈጠር ሰባት ጊዜም ትምህርት አይገባውም" አለኝ ቀጥሎ ።
ስንመረቅ ግን የነፍሰ ቀጭኑ ሰውዬ እርግማን ለስንሻው ምርቃት ሆኖ እርፍ አለው ።
የከተማችን አስተዳደር ተመራቂ ተማሪዎች ተደራጅታችሁ ኮብልስቶን አንጥፉ ምናምን ብሎ በስብሰባ ሰበብ ሲጀናጀነን ስንሻው ተከብሮ የከተማችን ከንቲባ ሆኖ ነበር ።
ጭራሽ እዛ አመዳችን ቡን ባለ ተመራቂ ተማሪዎች ፊት ቀርቦ ስለ ስራ ፈጠራ ሰፊ ማብራሪያ ሰጠን ። ኢንጅነር ነን ዶክተር ነን ብላችሁ አትኮፈሱ የጀበና ቡና ብታፈሉ ትችላላችሁ ። ለምሳሌ ሚካኤል እዮብ አቤል በኢንጅነሪንግ እና ዶክትሬት ተመርቃችሁ ሰፈር ለሰፈር ከምታውደለድሉ የጀበና ቡና ብታፈሉ ምን ችግር አለው ? ብሎ በምሳሌነት ጠቀሰን ። እኔ እንዳስተማረን ሳይሆን እንደ ሰደበን ቆጥሬው እሳት እንደነካው ላስቲክ ተኮራመትሁኝ ።
ከስብሰባው በሁላ ስንሻውን ለማናገር ከተቀመጥሁበት ተነስቼ ተራመድኩኝ ። የልጅነት ጓደኛዬ ስለሆነ ሰላምታ ልሰጠው አስቤ ነው የቀረብሁት ። በሰዓቱ ከየት መጣ ያልተባለ ጠባቂው በመዳፉ ጭብጦ አሽቀነጠረኝ ።
ቀና ብዬ አየሁት !
“ምን አጠፋሁ አለቃ?”
ፈርጣማው ጠባቂ በቁጣ ቱግ ብሎ እንዲህ አለኝ
“አንተ ምን አይነት ደፋር ነህ ባክህ ? ክቡር ከንቲባችንን ለመቅረብ አይደለም ሻንጣቸውን ለመሸከም ብትመጣ እንኳ ማስፈቀድ ነበረብህ “ 🙂

@wegoch
@wegoch
@paappii

#ሚካኤል አስጨናቂ
ወግ ( የቀን ማህደር )

ከሶላ


<< አለወትሮዬ ... >>

፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨ ገፅ ፩ ፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨


አለወትሮዬ ነበር በጠዋት የነቃሁት ... አለወትሮዬ ስነቃ አለወትሮዬ ያለምኩት ህልም ትዝ አለኝ ... አለወትሮዬ በህልሜ ሊያውም በተመረኩበት ስራ ሳገኝ ይታየኝና ስነቃ የፍርድ ቤት ዳኛ ያስመሰለኝ የምርቃት ፎቶዬ ትኩር ብሎ ሲያየኝ አገኘዋለሁ ... ( መንቃቴ ህልም ቢሆን ምን ነበር ) የፎቶው ፍሬም ወይም ጋወኑ ተሰቅሎ ከመቆየቱ ብዛት አቧራ ለብሷል ... በፎቶው ላይ መመረቄን ከሚያውቁ ሰዎች ውጭ የሚያመሳክር ኮፍያም ይሁን ሪቫን የለውም ... እንዴት ? ... ከምርቃቴ 5 ቀን በፊት ሙሉ ጋወኔን ወሰጄ እቤት አስቀመጥኩ ፤ የምታስርበት ስታጣ እናቴ < ለራሱ አይደል እንዴ > ብላ በሪቫኑ የጠመቀችውን ጠላ ሸብ አረገችበት ... በርግጥ ጠላው ለምርቃቴ ለተጠሩት እንግዶች ነው ትበል እንጂ በክፍያ ነበር ስትሸጥላቸው የነበረው ... እርሱም ቢጎል ምን ችግር ብዬ ሳለ በሞንታርቦው በኩል << እንኳን ደስ አላችሁ እንኳን ደስ አላችሁ እንኳን ደስ አላችሁ >> የሚለው ዘፈን ሲንቆረቆር የጠዋቱ ድባብ ታውሶኝ ኮፍያዬን ከአናቴ አንስቼ ወደ ላይ ለመልቀቅ ወደ ጎን ስወረውር ከግቢው ውጭ አረፈች ... ሰው እንዳልፈነከትኩ ተስፋ እያረኩ ከግቢው ስወጣ እንኳን ሌባ ልትጠብቅ ትቅርና በረሮ ገና ስታይ የምትገባበት የሚጠፋት << ክፉን ችላ >> የምትባለው ውሻ በጥርሷ ዘነጣጥለው ስጨርስ ደረስኩ ... ከመቅጠኗ እና ከመናደዴ የተነሳ ልበላት ወስኜ ነበር ፤ እርጉዝ ስለሆነች ተውኳት እንጂ ... ጥቂት ከተጨፈረ በኋላ ፎቶግራፈሩ መጣ ... እናቴ በነፃ እንድትሰጠው ያረኩትን ጠላ እና < ብፌው ከሱ ነው እንዴ የሚነሳው > እስኪባል ድረስ ተራራ አሳህሎ ካነሳው ማዕድ ጋር እያጣጣመ ያጋጠመኝን አወራውት ...

<< ብሮ ዛሬ ምርቃቴ ነው ታውቃለህ አ ? >>

<< አውቃለሁ >> ( አጎራረሱን ለአንባቢዎቼ ስል ውጬዋለሁ. )

<< ግን ኮፍያው እና ሪቫኑ የለኝም ብሮ ... >>



<< አደለም እርሱ COC ስ መች አለሽ >> ( በጉርሻው መሀል የተብላላ ድምፅ ነው )

<< ምን አልሽኝ ብሮ ? >>

<< ጣጣ የለውም በ Photoshop ይመጣል >> አለኝ

በበሳምንቱ...

<< ብሮ ሰራሽው እንዴ ? >>

<< አይ አልሰራውትም >> ( ሲያገሳ የድግሱን ወጥ ይሸታል )

<< እንዴ ለምን ? >>

<< ንሰሀ ስለገባሁ ልሰራልህ አልችልም ... ባይሆን >>

<< ባይሆን ምን ... >>

<< ባይሆን ንሰሀውን ስጨርስ >> ሲለኝ ተናድጄ

<< እንደውም Soft copyውን ስጠኝ >> ብዬ ከተቀበልኩ በኋላ << ከቻልክ ንሰሀውን ስጨርስ ንሰሀ ግባ >> ብዬው ሄድኩ


፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨ ገፅ ፪ ፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨፨

በአንድ ቀን መምህሩ 3+1=4 ነው ብሎ ሲያስተምር < አንተ ውሽንታም ትናንትና 2+2=4 ነው አላልክም > ብሎ ትምህርት በአፍንጫዬ ያለው ጓደኛዬ ...

<< ታውቃለህ ? >>

<< ምኑን ነው ማውቀው ... >>

<< የምርቃትህ ፎቶ አሁን ሶስተኛውን ምርጫ ሊያይ ነው >>

ዝም ...

ለጠቀና

<< አንዳንዴም እጠበው >>

<< ደሞ አሁን ምኑን ነው? >>

<< የተመረክበትን ጋወን ነዋ >> ብሎኝ ወደስራ ይሄዳል ... ( አሽሙር መሆኑ እኮ ነው ) ... አለወትሮዬ ፎቶውን ደጋግሜ አየሁት ... ስራ አግኝቼ ፤ ፍቅረኛ ይዤ ፤ ልጆች ወልጄ ፤ የልጆቼን ምርቃት ሳይሆን ስራ ማግኘት አይቼ ፤ ከደሞዛቻቸው ስበላ እያየሁ .... ለወትሮ እንኳን አልሜ የማላውቀውን አለወትሮዬ በሀሳብ እኖራለሁ ... ከምናበ አሳቤ እንደመጣው ያኔ ስንመረቅ መልስ ለመመለስ አውጥቶ የሚፈልገው ተማሪ እስኪያወጣ ድረስ ባላየ እንደሚሆን መምህር እጆቻችንን አስነስተው ያስገቡን ቃል ትዝ አለኝ ... በወቅቱ የመድረኩ መሪ የነበረው ወጣት << በተማራችሁት ስራ አምናችሁ ህዝባችሁን በታማኝነት እያገለገላችሁ ልትፈውሱት ይገባል ስለዚህም ቃል ግቡ >> ( አሁን ፓስተር ሳይሆን አይቀርም ) እያለ ሲያጨናንቀን ነገረኛው ተመራቂው አይምሮዬ << እኛ ቃሉ መች አስጨነቀን ስራ ማግኘቱ እንጂ >> ያለው መልስ በጊዜው ቢያስቀኝም ነገሩ ትንቢት መሆኑ የገባኝ አሁን አለወትሮዬ ሳስታውሰው ነው ... ከጥቂት አለወትሮ የመጣ ዝምታ በኋላ የግቢው በር ተንኳኳ ... እመቤቴ ማርያም ሆይ ብቻ < እቴዬ ወይዘሮ > ባልሆኑ ብዬ ዝም አልኩ ... በድጋሚ ኳ .. ኳ .. ኳ .. አለ ፤ በሩን እስከክፍተው ድረስ አይምሮዬን ስራኝ ቀጥሬው እትዬ ወይዘሮ ባለፈው ያሉኝን ማስታወስ ጀመርኩ.

<< ደህና ዋልህ ልጄ ? >>

<< እግዚአብሔር ይመስገን ደህና ዋሉ ? >>

<< ይመስገነው... እኔ ምለው እናትህ አለች ? >>

<< አይ የለችም ስራ ሄዳለች >> ( አድጌም እየሰራች የምታኖረኝ እናቴ ነች ውዷ እናቴ )

<< አይ የኔ ነገር ረስቼው እኮ ነው ... አንተስ ስራ አለህ እንዴ ? >>

<< ለጊዜው የለኝም >>

<< እሱንስ ተወው ...ለጊዜው እያልክ ይሄው 3 የምርጫ ዘመን አየህ እኮ >> ( በነገራችን ላይ ከላይ ለነገርኳችሁ ጓደኛዬ እናቱ ናቸው ) ለጥቀውም ...

<< እንግዲህ ስራም የለኝም ካልክ ና ቡና አጣጣኝ >>

በሩን ከፈትኩ ... የ< እገሌ > ፓርቲ ቀስቃሾች ነበሩ ... ወጣት እና ፈርጣማ ከመሆናቸው የተነሳ እየደበደቡ በፍቅር ምረጥ የሚሉ ይመስሉ ነበር ... እንዳልገባው ሆኜ...

<< ምን ነበር >>

<< ከእገሌ ፓርቲ ነው የመጣነው የይምረጡን ቅስቀሳ እያደረግን ነበር >> ( እውነት በሉ እስኪ... ይልቅ የምናውቀን ትታችሁ የማናውቀውን ብትነግሩንስ አላልኩም )

<< እሺ ቀጥሉ >> ( እኔ ሂዱ ማለቴ ነበር )

ከብዙ ቀደዳዎች በኋላ << ፓርቲያችን ከፍተኛ የስራ ዕድልን ይሰጣል >>

<< ጥሩ ነው ግን ልጠይቃችሁና በዚህ ፓርቲ ስንት አመት ሰርታችኋል ? >>( ወጣትነታቸውን ታሳቢ አድርጌ )

ተያዩና << እኛ እንኳን አሁን በተጠባባቂነት ነው ያለነው ያው ግን ወደፊት... >>

.
.
.

እነሆ ከዚህም በኋላ ጥሁፌም በጥሁፌ ውስጥም ያለው የግቢዬ በር ተከርችሞ አለ !

@wegoch
@wegoch
@paappii

#በሶላ
የታናሽ ወንድሜ ክፍል ገባሁ ።
እንደ አጋጣሚ ሱቅ ተልኮ ስለወጣ እንጂ የቤተሰቡን አባል ቤቱ ውስጥ የማስገባት ፍላጎት አልነበረውም።
እማዬ ብዙ ጊዜ በሩን ስትቆረቁር እሳት ለብሶ እሳት ጎርሶ ያንባርቃል።
"ይሄ የድመት ሙጭሊት የመሰለ ልጅ ቤቱ ውስጥ ፎርጂድ ዶክመንት ይሰራል እንዴ? " ይላል አባዬ አንዳንዴ ሲበሳጭ ።
እኔም ምክንያቱ የገባኝ ዛሬ ገና ነው :)
የቤቱ ግድግዳ ላይ ተሰቅለው የሚታዩት ፖስተሮች ከ አምስተኛ ክፍል ተማሪ የሚጠበቅ አይደለም። ጭራሽ በቀኝ በኩል በፒኪኒ ሙታንታ የተበለቃቀተች የፈረንጅ ሴት ፎቶ አየሁ ።
እግዚኦ!
አሁን ይሄ ልጅ እንብርትና የሴት ልጅ ብልትን እንኳ በቅጡ የሚለይበት እድሜ ላይ ነው ወይ ?
ፍራሹን ከፍ ሳደርገው የባህል መድሀኒት የሚሰራ ደብተራ ይመስል የደረቁ ቅጠሎች ተበታትነዋል።
ሀሽሽ ????
አቤት ይህቺ ምድር የተሸከመችው ጉድ !!
አሀ !
ከዚ ቀደም ለካ ከክፍሉ ሲወጣ እንባ የምታክል ውሀ መሬት ላይ አይቶ እንደ ሚዳቆ ዘሎ የተሻገራት ለዚህ ነዋ !
ብዙ ጊዜ ... የሬጌ ሙዚቃ እንደሚሰማ አውቃለሁ። ግን...ግን እንዲህ እንደ ትልቅ ወጣት ሀሽሽ ያጨሳል ብዬ እንዴት ልመን?
ጌታ ሆይ ወዴት ነህ? ! መምጫህስ መቼ ነው?
በጣም ደንፍቼ ስልኩ ላይ ስደውል ስልኩ ጠረጴዛ ላይ አቃጨለች። ይዟት አልወጣም ማለት ነው !
አንስቼ መጎርጎር ጀመርኩ ። እጄን ምን እንደመራኝ ባላውቅም ቴሌግራሙ ውስጥ ገባሁ ።
Mal love u! ብሏል ፀዲ ጭሷ ለምትባል ህፃን ወጠጤ።
የታችኛው መልዕክት ውስጥ ዘው አልኩኝ።
ማማዬ ዛሬ ያደረግነው Sex አቅሌን አሳተኝ ይላል mal Lila ***×+~ ምናምን የሚል ስም ላላት ሌላ ህፃን ሴት !
እስክስ ማተራመስ !
ሶስተኛው መልዕክት ሄድኩኝ የድብቅ ወሲብ አገናኝ የሚል ግሩፕ ውስጥ ቀንደኛ ተሳታፊ ወንድም ነው ያለኝ።
አበስኩ ገበርኩ !
ወደ ኋላ ልወድቅ ተንገዳገድኩ ። አራተኛው መልዕክት ውስጥ ገባሁ ።
አንዲት የሚመጠጠውን ከረሜላ እግር የምታክል ልጅ የእርቃን ፎቶ ልካለታለች ።
አሁን ይህቺ እቃቃ ተጫውታ ያልጠገበች ልጅ የእርቃን ፎቶ ለመላክ ምን አነሳሳት ?
ወንድ ልጅ ፀጉሩን በአጭሩ ከመቆረጥ ሌላ ምን አይነት ባህሪ እንዳለው ከምኔው ለየች ?
ደግሞ እኮ ነጥብ የምታክል ትንሽዬ ጡት አላት ።
Mal ያበደ ገላ ነው ብሎ መልሶላታል ወንድሜ ።
እኔ በሱ መልዕክት አበድኩ !
ወድያው Sami ላላ የሚባል ልጅ ፎቶ ሰደደለት ። ክለብ ተቀምጦ ሺሻ የሚያጨስ ህፃን ልጅ! ... እኔ በሱ እድሜ ትምህርት ቤት ውስጥ የስነ ፅሁፍ ክለብ ምናምን ነበር የምሳተፈው ።
እሺ ክለብ መግባቱንስ ይግባ!
እዚህ ውድ ክለብ ገንዘብ ከየት አምጥቶ ገባ ?
እሺ መግባቱንስ ይግባ የክለቡ ተጠቃሚዎች እንዴት ኮርኩመው አላበረሩትም ?
ስምንተኛው ሺህ ነው ወይስ አስራ ስምንተኛው ሺህ ላይ ነው ያለነው ጎበዝ? :)
....
ከዚህ በላይ የመቀጠል አቅሙ አልነበረኝም።
በንዴት ጨስኩ !
በብስጭት በገንኩ !
ይሄ ልጅ ይምጣ እንጂ እንደ ቴኒስ ኳስ ነው የማነጥረው ስል ዛትኩኝ።
....ብቻዬን ቁጭ ብዬ ተብሰለሰልኩ ...
አላስችል ብሎኝ ላፕቶፑ ላይ ደግሞ ማሰስ ጀመርኩ። የወሲብ ቪድዮ መዓት! የሬጌና ራፕ ሙዚቃ መዓት !
ገና መቀመጫውን በቅጡ ያልጠረገ ፈላ ይሄ ሁሉ የዝሙት ፊልም ምን ያደርግለታል ?
ትዝ የሚለኝ እኮ ከቤተሰብ ጋር ተሰብስበን ህንድ ፊልም ስናይ እማዬ ይሄ ለልጅ የሚሆን ፊልም አይደለም ብላ አባራዋለች።
እማዬ ጉድሽን ባወቅሽ ?
ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ህፃኑ ጋኔን መጣ።
ተንደርድሬ አንገቱ ላይ ተሳፈርኩ ። መቀጥቀጥ ብቻ ሳይሆን ሚጥሚጣ ባጥነውም አልጠላም። አንድ ሁለቴ ሳቀምሰው እንደ ሚግ ተወንጭፎ እናታችን ጋር ደረሰ። የእማዬን ቀሚስ ይዞ ከጀርባዋ ተሸሸገ !
"ልቀቂኝ እገለዋለሁ!"...አንባረኩኝ።
"አንተ ምን ያርግህ ይሄ ህፃን ልጅ! " እናቴም በተራዋ ጮኸችብኝ።
"ምን አልሽ ?"
"ይሄ ህፃን ምን ያርግህ ?" እማዬ ደገመችው።
ምፅ!
ህፃን ልጅ አሳድጋ ሞታለች።
ተንደርድሬ ወደ ጓዳ ገባሁ ። የሚጥሚጣውን መያዣ ክዳን ስከፍት አንድ ድምፅ ከውጭ ሰማሁ።
"ምን አርገኸው ነው ወንድምህን አንተ ?"
"ምንም እማዬ! ... ከፍቅረኛው ጋር ተያይዞ ቤርጎ ሲገባ ስላየሁት እሱን እንዳልናገርበት ነው የሚደነፋው " ብሎ ፈላው መለሰ።
ጭራሽ እንደ ሀገራችን ፖለቲከኞች ሴራም ተምሮልኛልና !
እማዬ ፊቷን ኮስኩሳ ወደኔ ተንደረደረች :) ....

ሚካኤል አስጨናቂ

@wegoch
@wegoch
@paappi

ለተጨማሪ https://www.tg-me.com/MichaelAschenakipoems
ክትባት እንዴት እንዳመለጠኝ

(በእውቀቱ ስዩም)

አበሻ ገራሚ ህብረተሰብ ነው! ማስክ ገድግደህ ሲያይህ” ይሄን ያህል ትንቦቀቦቃለህ እንዴ” እያለ ያሸማቅቅሀል ፤ ከዚያ አጅሬው አስተኝቶ ለሳምንታት ያክል አበራይቶ ትቶት ይሄዳል፤ ከዚያ እንዴት ነህ? ስትለው” በዝሆን እግሩ ረግጦ አድቅቆ ለቀቀኝ በማለት ፈንታ” ይዞ ለቀቀኝ “ በማለት አቃሎ ይነግርሃል፤ ከህመሙ በረከት እንዲደርስህ ወጥሮ ያበረታታሀል፤ ስለክትባት ስታነሳበት “ ቺፕስ ሊያስገቡብን” ነው ይልሀል፤ ባለፈው አንዱ “ ፈረንጆች ቺፕስ ክንዴ ላይ ቀረቀሩብኝ “ እያለ የዝግባ ፍልጥ የመሰለ ክንዱን ለታዳሚው ሲያስጎበኝ በሆነ ዩቲውብ ቻናል ላይ አየሁት ፤ ዙም አድርጌ ስሾፈው ክንዱ ላይ ያለው ኮረሪማ እሚያክል ኪንታሮት ነው፤

እኔ ያለሁበት ከተማ ውስጥ የክትባት እደላ ቢጀመርም ምዝገባውና ወረፋው አይቀመስም ፤ አንድ ቀን ግን ዝም ብየ በድንኩዋን ሰበራ ጎራ አልሁ፤
“ ምን ፈልገህ ነው?” ሲሉኝ

“ የማትፈልጉት ክትባት ይኖራችሁዋል? ” አልኩ ራሴን እያከክሁ’

“ እድሜህ ስንት ነው?” አለቺኝ ነርሲቱ

“ ኦፊሻል እድሜየ አርባ ይገመታል ፤”

“ አዝናለሁ! አሁን እየከተብን ያለነው ካምሳ አመት በላይ የሆኑትን ነው “ አለችኝ::

“ የሰባ አመት አዛውንት አተነፋፈስ ነው ያለኝ ፤ እንደምንም አጠጋግተሽ አስገቢኝ ”ብየ ተማፀንኩዋት፤

“ ኦኬ፤ ተመዝግቦ የቀረ ሰው ካለ፤ በምትኩ ትከተባለህ”

“ እጅሽን ከቁርጥማት ይሰውርልኝ” በማለት መርቂያት ቁጭ አልኩ
ጥበቃው እንዳይታክተኝ አጠገቤ ከተቀመጠው ሰውየ ጋ ላውጋ ብየ ዞር አልሁ፤ በሁለት ከዘራ መሀል ጎብጦ የሚንቀጠቀጥ አዛዛዛዛውንት አይቼ
“ስንት አመትዎ ነው?’ በማለት ጠየኩት፤
“ ምን አልከኝ ? ” አለኝ፤
ከኪሴ ማይክ አውጥቼ
“ ቼክ ማይክ! ዋን ፥ቱ ፥ ትሪ ! ስንት አመት ሆነዎት? “

“ ባለፈው ሳምንት መቶ አመት ሞላኝ “

“ እና ርስዎም ክትባቱን ይፈልጉታል?”

“ አይ ለኔ አይደለም! አባቴን ላስከትብ መጥቼ ነው”

በመጨረሻ ተጠራሁ፤

ነርሲቱ ፥ ክንዴን አፈፍ አድርጋ ይዛ እንደ ጥጥ ስታባዝተው ከቆየች በሁዋላ፤
“የደም ስርህ ላገኘው አልቻልኩም” አለቺኝ ፤

“ የደምስሬ wireless ነው፤ በቀላሉ አይገኝም “ አልኩዋት

“ አትቀልድ ፤ በዚህ ሁኔታ መርፌ ለመጠቀም ያስቸግረኛል”

“ እንደ ልጅነት ልምሻ ክትባት ለምን አፌ ላይ ጠብ አታረጊልኝም?”

“ ብዙ ጊዜ የምትመገበው ምግብ ምንድነው ?” ስትል ጠየቀችኝ፤

“ ሩዝ ! ይገርምሻል ሩዝ አብዝቼ ከመውደዴ የተነሳ ወዳጆቼ ' ሩዝቤልት' የሚል ቅፅል ስም አውጥተውልኛል”

“ በል አሁን ወደ ቤትህ ተመልሰህ፤ ገንቢ ምግብ ብላ፤ ዳምፔል አንሳ! ፑሽ አፕ ስራ ፤ ከዚያ ከሁለት ወር በሁዋላ ተመለስ”

ይህን ስትለኝ ይሄን ልላት ብየ ተውኩት፤
“ ሴት!Yo! ልትከትቢኝ ነው ወይስ ቦዲጋርድ ልትቀጥሪኝ ነው የምትፈልጊኝ ? ”

በዕውቀቱ ሥዩም

@wegoch
@wegoch
@beckyalexander
ሽልማቱ

(በእውቀቱ ስዩም)

በቀደም ሰይፉ ላይ የሰማሁት ዜና እንዲህ ይላል” የናይጀርያ ዜግነት ያላቸው ሌቦች አዲሳባ ገብተዋል” 🙂ከኢትዮጵያ አቻዎቻቸው ጋራ ልምድ ልውውጥ ለማድረግ መሆን አለበት!

ሌብነት ሲነሳ የሚከተሉት አስተካዥ ገጠመኞች ትዝ ይሉኛል፤
ሰውየው የበግ ነጋዴ ናቸው፤ ወደ ገበያ ሲሄዱ ከፍተኛ ጥንቃቄ ያደርጋሉ፤ እንደተለመደው አንድ ማለዳ ገንዘባቸውን ከፍየል የቆለጥ ማቀፍያ ቆዳ የተሰራች ትንሽየ ቦርሳ ውስጥ ጠቀጠቁት፤ ከዚያ ቦርሳውን እንደ ቡዳ መዳኒት አንገታቸው ላይ አንጠለጠሉት ፤ በላዩ ላይ ግድንግድ የድሮ ቢትልስ ለበሱበት፤ በዚያ ላይ ካሽሚር ጃኬት በጃኬቱ ላይ ጋቢ፥ በጋቢው ላይ ደግሞ መለስተኛ ቤተሰብ ማስጠለል እሚችል ካፖርት ደረቡበት፤ ከዚህ ሁሉ ጥንቃቄ በሁዋላ ገበያ ውለው ሲወጡ እጃቸውን ወደ አንገታቸው ሲሰዱ ቦርሳው አምልጡዋል ፤

ቤታቸው ገብተው የደንቡን ያክል አልቅሰው ሲያበቁ ወደ ሚስታቸው ዞረው
“ ጉድ እኮ ነው! ይሄን ሁሉ አለባብሼው፥ ሌባው እንዴት አርጎ ወሰደው?” አሉዋቸው’?’

ሚስትዮም እንዲህ መለሱ ፥

“ አንተ ደሞ! ላት ያላት በግ አትሰረርም ያለህ ማነው?”

2

ሸገር ውስጥ "የሌባ ሰፈር " ነው እየተባለ የሚታማ ሰፈር አለ! እስከ ሰባ አመት ፥በዚህ አለም መቆየት ስለምፈልግ ስሙን አልጠቅሰውም! አንድ ጋዜጠኛ ወዳጄ በሬድዮ ፕሮግራሙ ላይ ስለዚህ ሰፈር ለየት ያለ ቆንጆ ፕሮግራም ሰራ፤ የሰፈሩ ልጆች ሰምተው ፈነጠዙ! “ በስርቆት ብቻ ሲነሳ የነበረ ሰፈራችንን ገፅታ ስለገነባህልን የምስጋና ድግስ አዘጋጅተንልሀል ፤ ሽልማትም ተሰናድቶልሀል” ብለው ጋበዙት፤ እሱም ልቡ በጣም ተነክቶ በዝግጅታቸው ላይ ታደመ፤ መኪናውን ዝግጅቱ ከሚዘጋጅበት አዳራሽ ጀርባ አቆመና ወደ ውስጥ ዘለቀ፤ ድብልቅልቅ ባለ ጭብጨባ ተቀበሉት::

የተለያየ የኪነጥበብ ድግስ ተከታትሎ መቅረብ ጀመረ፤ አንድ ወጣት “ ካልተሳፈሩበት ቶሎ ተሽቀዳድሞ
ጊዜ ታክሲ አይደለም አይጠብቅም ቆሞ” የሚል ግጥም አነበበና በቅርቡ ከሚታተመው መድብሌ የተወሰደ ነው ብሎ ከመድረክ ወረደ::

የስነፅሁፍ ዝግጅቱ ሲጠናቀቅ ምሳ አበሉት፤ ምን ምሳ ብቻ፤ በሹርቤ ብርሌ ጠጅ አቀረቡለት፤ ብርሌውን ሾፍ ሲያደርገው “ ብሄራዊ ሙዝየም “ የሚል ማህተም ተለጥፎበታል፤ በመጨረሻወደ መኪናው ሄደ፤ ባየው ነገር ክው ብሎ ቀረ፤ የመኪናው ሁለት ስፖኪዮ በቦታው የለም፤

የደረሰበትን የነገረኝ ቀን በምን ቃል እንዳፅናናሁት አልረሳም

” ጎማውን ስለማሩልህ እንደ ሽልማት ቁጠረው”

@wegoch
@wegoch
@beckyalexander
ኢትዮዽያ መኪና ነድቼ አላውቅማ ... ራሴ ነዳለሁ ብዬ መኪናውን ልከራይ የቀጠርኩት ሰውዬ ...

"አይከብድሽም? እርግጠኛ ነሽ? ረዥም አመት እንኳን ውጪ የነዱትኮ እዚህ ይፈራሉ .... (ሲያስፈራራኝ ከቆየ በኃላ ) ለማንኛውም እስኪ አብረን ሆነን ልይሽ" ብሎ ከኃላ ተቀምጦ ስንዳ ... ሲኖትራክ ሲንቀለቀል መጣ ...

"ውይይ ይለፍ ቆይ ያስፈራል" አልኩት ...

"ገና እሩቅ ነውኮ .."

"አይ ቢሆንም አመጣጡን እየው ያስፈራል::" እለዋለሁ:: ምን ቢለኝ ጥሩ ነው?

"በዚህ አያያዝሽ ሹፌሩ ወርዶ ሁላ እለፊ ቢልሽ...'በማርያም ሞተሩንም አጥፋውና ነው የማልፈው' ትያለሽ::" 😊

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ፍተላ ነች አበበና አቤል፣ ሁለቱ ጓደኛሞች በረሃ አቋርጠው ሲጓዙ በጣም ራባቸው። በዚሁ ከቀጠሉ በረሃብ እና በውሀ ጥም ሊሞቱ እንደሆነ እየተነጋገሩ ጥቂት እንዳዘገሙ አንድ መስጊድ አዩ። አበበም "ስማችንን ቀይረን እዚህ መስጊድ እንግባ ምግብ ይሰጡናል - እኔ አህመድ ሆናለሁ" አለ።

አቤል "እኔ ስሜን አልቀይርም" አለና ወሰነ። ተያይዘው ወደ መስጊዱ ገቡ።
የመስጊዱ ኢማምም "አሰላሙአለይኩም፤ ሀጂ አሊ እባላለሁ" ሲሉ መንገደኞቹን በሰላምታ ተቀበሏቸው። አበበ "አህመድ እባላለሁ" ብሎ ራሱን አስተዋወቀ። አቤልም "አቤል እባላለሁ" አለና ስሙን ተናገረ። ሀጂም እንግዶቻቸውን ካስቀመጡ በኋላ "ልጆች፡ ለአቤል ምግብ እና የሚጠጣው ነገር አምጡለት። አህመድ ያው ጾም ነው . . . ረመዳን ከሪም!"

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Gemechu merara fana
ብ.ል.ግ.ና ፓርቲ

" ጣፋጯን ሲጋራ እናጭስ በጋራ"

በጠዋት ከተነሳው ዛሬ አምስት አመቴ ሆነኝ ማለት ነው፡፡ በዚ ለሊት 'ምሄድበት አለኝ አደራ እንዳላረፍድ ቀስቅሱኝ' ያላቸው ሰው ያለ ይመስል በሁለት ትላልቅ ማደንቆሪያ ሬድዮ ከመቀስቀስ አልፎ ልትፈርስ አንድ ሀሙስ የቀራትን ጎጆአችንን ሊያፈርሱት ሲሞክሩ አንዲት አዛውንት አሮጊት ቀድሞውኑም የተከፈተ በራቸውን ከፍተው ወጡ፡፡

"ኧረ ስለፈጠራቹ ፤ ኧረ በጉልበታችሁ አምላክ ፤ ቆይ እስኪ ንገሩኝ እኛ ምርጫ በመጣ ቁጥር ጭቃ ማዘጋጀት አለብን እንዴ?" ወገባቸውን ይዘው ሹፌሩን ይገላምጡት ጀመር፡፡

" እንዴ ማዘርዬ የምርጫ ካርዶን ነው እንጂ የምን ጭቃ ነው ሚያዘጋጁት?" ሹፌሩ መለሰ፡፡

" እናንተ የቦረቦራቹትን ጆሮዬንም ግርግዳዬንም ልደፍንበት ነዋ" አሉት የንዴት ፊት እያሳዩት፡፡

ሹፌሩም ምንም ሳይመስለው ፈገግ ብሎ የሬድዮኑን ድምፅ ከፍ አደረገው፡፡

"ሰላም ሰላም ሰላም ፤ ስዶች ነን ብ.ል.ግ.ናን ይምረጡ ፤ ፓርቲአችን በብዙዎች ዘንድ የሚወደደውን 'ሲጋራን' ምልክት አድርጓል፡፡
ብ.ል.ግ.ናን ቢመርጡ ሲጋራን የማናደርስበት ክልል አይኖርም፡፡ ምን እሱን ብቻ ከሲጋራ ጋር እጅና ጓንት የሆኑትን አሽሽ ፤ ጋንጃና ጫትን እንደ እድሜአችሁ ተደራሽ እናደርጋለን፡፡ አሮጊቶች ያለከልካይ ሰው እንዲዘለዝሉ ወይንም እንዲያሙ ተግተን እንደምንሰራ
በ ስድ ስም ቃል እንገባለን፡፡ እኛን አምነው ስልጣን ላይ ቢሾሙን ከበፊቱ በተሻለ መልኩ አምስት አመት ሙሉ ያለስራ ተኝቶ የሚቅም ትውልድ እናፈራለን፡፡
አላማችን ሳንባ የሌለው ትውልድ ማፍራት ነው ፡፡
ብ.ል.ግ.ናዎች ነን !! "

በሂወቴ እንደዛሬ ምርጫ እንደ ነፃነት የናፈቀኝ ጊዜ የለም፡፡ እኔም የዜግነት ግዴታዬን ለወጣ ብዬ አሰብኩና ከሱቅ ሲጋራ ገዛውና ወደ ሹፌሩ ጠጋ ብዬ "ተመርጣችሁ በነፃ አብረን እስከምንጨስና እስከምናጨስ
አሁን እኔ የገዛውልህን አጭስ" ብዬው መርሀቸውን ጮክ ብዬ እየተናገርኩ ወደ ቤቴ ገባሁ፡፡

#Beki

@wegoch
@wegoch
@MahletZerihun
"ጣፋጯን ሲጋራ እናጭስ በጋራ"

ቤካ ስም አይጠቅስም😜
"መዳፍና ዓይን"
(ያሬድ ሹመቴ)
ለፊልም ስራ አባይ ማዶ ተሻግሬ በነበረበት ጊዜ እንዲህም ሆነ! ፊልሙ - የገጠር ያውም የሽፍታ ታሪክ ነበረና "አብራራው" የተባለው የድሮ ጠመንጃ አስፈለገ። "አብራራው" ስሙን ያገኘው ለማቀባበል ከሚወስደው ጊዜ ተነስቶ ይመስላል። አንድ ሰው ነገር ስያረዝም "አብራራው" እንደሚባለው ማለት ነው።... የምንሰራው ፊልም ርዕሱ "ገዳይ ሲያረፋፍድ" ይሰኛል። እኔ በፕሮዲዩሰርነት እና በኤዲተርነት ተሳትፌበታለሁ። ዝግጅቱ የናኦድ ለማ ነው። የቀረጻ ቦታውም የጣና ሐይቅ ደቡብ ምዕራባዊ አቅጣጫ ላይ የምትገኘው ቆራጣ ላይ ነው።....ይህን ጠመንጃ ፈልጎ ማግኘት ቀላል ቢሆንም ፈቃጅ ማግኘቱ ግን እጅጉን ያለፋል። ምክንያቱም የጦር መሣሪያ ነዋ። ከፖሊስ ሊገኙ የሚችሉት መሣሪያዎች ዘመናዊ በመሆናቸው አንዱን የየአካባቢው ሰው ማሳመን ግድ ሆነ። "አብራራው"ን አስፈቅደን ቀረጻ ላይ ለማዋል "አብራራው" ከሆኑ [አቶ አዝመራው ከተባሉ] የአካባቢው ነዋሪ ጋር ስንለማመጥ ስንነታረክ አረፈድን። በኋላ በቀን 50 ብር ክፍያ ተስማምተን ያለ ጥይት አብራራውን ተከራየነው።
"አብራራው" ፀሐይ ስትወጣ ስራ ይጀምርና ፀሀይ ስትጠልቅ "በሞክሼው" (የጠመንጃው ባለቤት) ወደ ቤቱ ይወሰዳል። እንዲህ እንዲህ
እያለ ጥይት አልባው ጠመንጃ የፊልም ባለሙያ ሆነ። ብዙውን ጊዜ በቀረጻ ወቅት ደጋግሞ ማቀባበልና ቃታ መሳብ የተለመደ ስለሆነ ከዚህ ቀደም ሰርቶ የማያውቀውን ከባድ እንቅስቃሴ ለመደ። ለካንስ ይህ አሮጌ መሳሪያ ዕለት በዕለት በሚገጥመው ከባድ ስራ የቃታው ማስፈንጠሪያ እየላሸቀ ሄዷል። ከተቀባበለ በኋለ ቃታውን ለመሳብ በማሰብ ብቻ ተወንጭፎ መርፌውን
ይመታል። ጠመንጃ በባህሪው ልክ እንደ ውሀ እያሳሳቀ ነው የሚወስደው። "ወይ ወደ መሬት፥ አልያም ወደ ሰማይ ተደርጎ ነው የሚነጣጠረውም፥ የሚተኮሰውም።"
የሚለውን መርህ ለመሻር ጥይት አልባውን አብራራው ለሁለት ቀናት ብቻ
ሲያቀባብሉ እና ቃታ ሲስቡ መዋል በቂ ነው። ከዛ በኋላ ማቀባበሉም ሆነ መተኮሱ በወዳጅ ላይ ልክ እንደ ቀልድ ነው የሚቆጠረው። ጥይት የጎረሰለት
መጉረሱ ይዘነጋና የዕለት ቀልድ ሊቀጥል ይችላል። አንድ ቀን ታዲያ ጠመንጃው ጥይት ሲጎርስ መቀረጽ ስለነበረበት ባለ ንብረቱ ጥይቶች ይዞልን መጣ። ጥይቱን ተከትሎ ዝናብ መጣ። ቀረጻው ተስተጓጎለ። ጠበቅን ጠበቅን አያባራም። "ለበጎ ነው" የሚለውን ጥቅስ ያስታወሰ ማንም አልነበረም። ተበሳጭተን ተስፋ ቆርጠን እቃችንን ጠቅለን የገጠሩን መንደር ለቀን ወደ ባህር ዳር ተመለስን።
የአብራራው ባለቤት እዛችው መንደር ባለች "አንጓች አረቄ ቤት" ውስጥ የላሸቀውን ጠመንጃ ጥይቱን አጉርሶ፥ እንደነገሩ ነቅነቅ ሲያደርገው ተፈትልኮ መርፌና እርሳስ ተገናኝተው ባረቀ። በተአምር ማለት ይቻላል አንድም ሰው
ሳይጎዳ አካባቢውን አሸብሮ የአንጓችን የተደረደሩ 6 ትላልቅ ጋኖችን በታትኖ
ቤቱን በጠላ ጎርፍ ሞላው። የተፈጠረውን ድንጋጤና ረብሻ ለመረዳት ቦታው ላይ መድረስ አላስፈለገንም ወሬው 42 ኪ.ሜትሮችን አቆራርጦ ባህርዳር ሳለን ሰማን። የነበረን ምርጫ
ከቦታው መሰወር ብቻ እስኪመስለን ድረስ ተደናገጥን። እየመነታን እያማተብን በማግስቱ ማልደን ቆራጣ ገባን። የአብራራው ባለቤት አቶ አዝመራው ግን "የምወዳትን ጠመንጃዬን አሰሩልኝ እንጂ እግዚአብሔር ባዘዘው ገብቼ እናንተን አልወቅስም" አለ። ያስጠነቀቀው ግን ታዲያ "ጠመንጃዬ ያልተሰራች እንደው ይቅርታም አላደርግ" ብሎ ነው። በአካባቢው አሉ የተባሉ የመሳሪያ አዋቂዎች ዘንድ ተንከራተትን።
የመሳሪያው አሮጌነትና በአይን ለማየት አስቸጋሪ የሆነውን የውስጡን ክፍል ለይቶ ማን ይወቀው። እንግዲህ ፀባችን እርግጥ ሆነ ስንልም ሁላችንም ሰጋን።
በዚህ ግዜ ነበር አንድ ወዳጄ ባህር ዳር ሆስፒታል አካባቢ አንድ ባለሙያ መኖራቸውን የጠቆመኝ። ወደተባሉት ሰው የመጨረሻ እድል ለመሞከር ሄድኩ። አሮጌ ጠመንጃ ታጥቄ ባህርዳር ከተማ ውስጥ መታየት ችግር እና ትኩረት መሳብ ሊፈጥርብኝ ይችላል ብዬ ስላሰብኩ ጋቢ ጣል አድርጌ አብራራውን
ታጠቅኩት። መኪና መግባት እስከሚችልበት ቦታ ድረስ በመኪና ሔጄ ጠመንጃውን አንግቼ ከመኪና በመውረድ እየተንጎራደድኩ የባለሙያውን ቤት ፍለጋ የሰፈሩን ሰዎች
ማጠያየቅ ጀመርኩ። አንድም አተኩሮ ያየኝ ሰው የለም። ቤቱን ጠቆሙኝ። እኚህ ሰው ጋሽ ጥላሁን ይባላሉ። በአካባቢው ስመጥር ናቸው። ግን ሸምግለዋል። ሽማግሌ መሆናቸውን ስሰማ አይሳካም ስልም አመነታው። ነገር
ግን "ለካስ የባሰም አለ" አልኩ ቤታቸው ደርሼ ሳያቸው። በእርጅና ምክንያትም
አንደኛው ዓይናቸው ከናካቴው ሲጠፋ ሁለተኛው ደግሞ ከጥላ ውጪ ማየት
አይችልም ነበር። "አሰላሳይ አገናዛቢ" ነኝ ብሎ ለሚታበይ ሰው በሙሉ የሚመጣለት፥ "ጊዜ መግደል ጥሩ አይደለም" የሚል ሀሳብ ነው። እኔም ቢሆን እንዲያ ማለቴ አልቀረም።
ነገር ግን ሰውየው። አብራራውን ተቀበሉኝና ከመቅፅበት በእጃቸው ዳብሰው በስሙ ጠሩት። "አብራራው" አሉ። ትንሽም ቢሆን ላምናቸው ሞከርኩ። እሳቸው ለዘመናት የሚያውቁትን መሳሪያ እኔ ያን ሰሞን ስላወኩት የምበልጣቸው መስሎኝ ነበር። የስህተቴ ብዛት። እኚህ ሰው ፊታቸውን ወደ ጣራው መልሰው ጥቂት ዳብሰውት "ሰው አገኘባችሁ ታዲያ?" አሉ። "ሰምተው ነበር እንዴ?" አልኳቸው። "ኣረ የለ! ምላጭ ማስወንጨፊያው ከጥቅም ውጪ መሆኑን እያየሁት?" አሉኝ ቆጣ ብለው። ዋጋ ነግረውኝ በኋላ ተመለስ ብለው ቀጠሩኝ። ከቀጠሩኝ ሰዓት ትንሽ ረፈድ አድርጌ ደረስኩ። ጊዜ ልስጣቸው ብዬ ነበር። ቤታቸው ደርሼ ወደ ውስጥ ገባሁ። ከድምፄ ቀድመው በጥላዬ አውቀውኛል። ተቆጡኝ። "ምነ ቆየህ? አንተን ጥበቃ በር በር ልይ እንዴ? ሽማግሌ እኮ ማረፍ አለበት" አሉኝ። ማስረዳት ስላቃተኝ ይቅርታ ጠየቅኳቸው። ልቅም አድርገው
ስራቸውን አጠናቀው ነገረኛውን አብራራው ጤነኛ አድርገው ጠበቁኝ ነበር። በጣም ገረመኝ። ለሙከራም አንገላታሁት። ወይ ፍንክች። እንደ ጠላት የታየንበት መንደር በኩራት ተመልሰን የፊልማችንም ቀረጻ ቀጠለ። አብራራውም አደብ ገዛ (ከነ ሞክሼው) ጤነኛውን ጠመንጃም ለባለንብረቱ አቶ
አዝመራው ሳስረክበው አንድ ጥያቄ ደጋግሞ ጠየቀኝ። "ማነው የሰራው?" የሰውየውን ማንነት "አብራራሁለት"። ዐይናቸው እንደማያይላቸው ስነግረው
ትልቅ ቁም ተናገረ፦ "እጃቸው ላይ ሸምግለው ነዋ" አለኝ። በአንድ ሙያ ውስጥ ማርጀት፥ አይን እንኳ ጠፍቶ ጠቢብነትን አይነጥቅም" ወደ ፊልም ሙያ አንድ አፍታ ልመለስ። በሆሊውድ እና በሌሎቹም ግዙፍ የፊልም ኢንዱስትሪዎች ውስጥ ታዋቂና ስኬታማ የተባሉት የፊልም ዳይሬክተሮች በሙሉ (99%) ሽማግሌዎች ናቸው። ምክንያቱም በፊልም ሙያ ውስጥ የተራቀቀ ጥበበ የሚወለደው በሙያው ሲያረጁበት ነውና። በየሙያቸው፣ ሙያቸው ላይ ያረጁ ሰዎችን እናክብር!! እውቀት ከዚያ አለች!! አመሰግናለሁ።

@wegoch
@wegoch
@paappii
"ወዜን አልሸጥም"
(ያሬድ ሹመቴ)
ከአመታት በፊት በካን ፊልም ፌስቲቫል ላይ ይፋዊ የዕይታ ተሳትፎ በማድረግ የመጀመሪያ ኢትዮጵያዊ ፊልም ሆኖ የተመረጠው እኔ በረዳት ዳይሬክተርነት የተሳተፍኩበት፤ የያሬድ ዘለቀ ዳንግሌ (Lumb) ተንቀሳቃሽ ምሥል ላይ የነበረኝን የሥራ ቆይታ አስታውሼ፣ ከቀረፃው በፊት ስለነበረው የአልባሳት ግዢ ቆይታ ላጫውታችሁ። ህሊና ደሳለኝ የፊልም ሥራ ውስጥ በአልባሳት ዲዛይነርነት እየታወቀች የመጣች ወጣት ባለሙያ ነች። አሁን በቃና ቲቪ ውስጥ በዳይሬክተርነት ትሰራለች። በዚህ ፊልም ደግሞ የዋናዋ ፈረንሣዊት ዲዛይነር የሳንድራ በርቢ ረዳት ናት። ከእሷ ረዳት መስከረም ወንድማገኝ (ነፍስ ሔር!) ጋር ሆነን ሦስታችንም በመኪና አዲስ አበባን ለቀን በክረምቱ ወራት ጉዞ ወደ ጎጃም
አደረግን። ለፊልሙ የሚያስፈልጉ አልባሳትን ንድፍና ናሙናቸውን በፎቶ የተደገፈ ማብራሪያ ስለያዝን ፣ የሚቀራረብ ልብስ ባየን ቁጥር በየመንገዱ እየቆምን ለመግዛት
ጥረት ማድረግ ጀመርን። ልብሶቹ ከተሰበሰቡ በኋላ በዲዛይነሮቹ አማካኝነት ወደ'ሚፈለገው የልብስ አይነት ስለሚቀየሩ በአብዛኛው በዲዛይነሯ የተነደፉ አልባሳት ጋር ተቀራራቢነት ያላቸው የተለበሱ፣ ያገለገሉ የገጠር አልባሳት ላይ ትኩረት እናደርግ ነበር። በዚህ ጊዜ ነበር "ወዜን አልሸጥም" የሚል ፈተና የገጠመን።
ወዝ መሸጥ ምንድነው? ወዝ ማለት - ላብ ያረፈበት ልብስ ልክ እንደ አንድ የአካል ክፍል የሚቆጠር ማለት ነው - ቆይቶ እንደገባኝ። እኛ የምንፈልገው የተለበሰ፣ በመጠኑ ያረጀ ወይም ደግሞ ለእድሳት የተለጣጠፉ የአዘቦት የሥራና የክት የገጠር አልባሳትን ነው። በአጭሩ ወዝ የተነከሩ። ብዙ ተለብሰው መነሻ ባህሪያቸውን የቀየሩ። የገጠሩን ነዋሪ ኑሮውን ሚመለከት የሚመስሉት። ከአፈር ጋር ያላቸውን ትግል የሚያሳዩ ማለት ይቻላል። "አንዱ 'አዋቂ' ቤት ሄዶ ለባልንጀራው ክፉ ሲመኝ ‘ወዙን አምጣልኝና እሠራልሀለው' ተብሎ የልብሱን ቁራጭ አዋቂው ጋር ወስዶ አፍዞ አደንዝዞ አስቀረው። እና በምን አምኛችሁ ነው ወዜን የምሸጥላችሁ?" ሲል አንዱ ቆፍጣና ገበሬ አወጋኝ። ጉድ እኮ ነው። አንዱ ምስኪን የለበሰውን ያለ ቅያሪ አውልቆ ግዙኝ ያለበት መንደር ደግሞ፣ በካህን አስወግዘው ሰው ያለ ጨርቅ የሚያስቀሩ ጉዶች መጡ ተብለናል። በጢስ ዓባይ መንደር ልጆች ዕርዳታ ቅዳሜ ገበያ አሮጌ ልብስ ለብሶ የመጣውን ገበሬ በአዲስ ልብስ እየቀየርነው የተወሰነ ግዢ አደረግን። ትንሽ ቆይቶ ተጨማሪ ገንዘብ መጠየቅና ለአሮጌ ጉርድ ቁምጣ ሙሉ ጋቢ በድርቡ መጠየቅ መጣ። ከጢስ ዓባይ ደግሞ ተሰደድን። እንዲህ እንዲህ እያልን ፈተናውን እያጣጣምን እግረ መንገዳችንንም እየተገረምን ፍለጋችንን ቀጠልን። ከዚህ ቀደም "ገዳይ ሲያረፋፍድ" የተሰኘውን ፊልም ፕሮዲዩስ ለማድረግ ሄጄ የተዋወቅኳቸው ሰዎች ያሉባትና ከባህር ዳር 45 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ወደምትገኘው የአለቃ ገብረ ሐና የትውልድ መንደር "ቆራጣ" በመባል
የምትታወቀው ቀዬ ትልቅ ተስፋ ይዘን አመራን። የፊልም ሥራን ባህሪ የተረዱ
ነዋሪዎች ያሉበት ቦታ በመሆኑ ብዙ ልብሶች ገዛን። "ወዜን አልሸጥም" የሚል ቃል ያልሰማንበት ብቸኛውን መንደር እያደናነቅን፣ በማግሥቱ ስለሚኖሩን በርካታ ግዢዎች ዕቅድ እያወጣን ወደ ባህር ዳር ዘለቅን። በማግሥቱ ጠዋት የገዛናቸውን ልብሶች ባህር ዳር ላገኘናት አመለ ሸጋ ልብስ አጣቢ፣ አሮጌዎቹ ልብሶች በመጠኑ ብቻ እንዲፀዱ አስረድተናት ወደ ቆራጣ
አመራን። ቆራጣ ስንደርስ የመንደሩ ሰው ግልብጥ ብሎ ወጥቶ ልብሱንም አዘጋጅቶ ጠበቀን። በደስታ እየመረጥን ዋጋም እየተስማማን ከሰዓት በኋላውን በሙሉ ስንገበያይ ዋልን። ወዙን አምኖ የሰጠንን የመንደሩ ነዋሪ ከፈቃደኝነቱ
በላይ ግፊያው መከራ ቢሆንም፣ የምንፈልገውን ያህል ገዝተን በደስታ፣
በጥቋቁር ረጃጅም ላስቲኮች ሰባት ከረጢት ሙሉ "ወዞችን" የራሳችን አደረግን። ዲዛይነር ህሊና ደሳለኝ አንድ ቀለሙ ለየት ያለ "ጎጃም አዘነ" (ፎጣ) ከርቀት አየች። በጣም ተመኘችው። መኪናችንን አስነስተን ሰውየው ወደሄደበት አቅጣጫ እንደተጠጋን ጠመንጃ የያዘ ሰው አፈ ሙዙን ደግኖ "ቁሙ!" ብሎ አስቆመን። ሰውየው የመንደሩ አዲስ ሹም ነው። የተፈጠረው ግርግር በምን ምክንያት እንደሆነ ጠየቀን። አስረዳነው። ሊገባው አልቻለም። ከዚህ ቀደም እዚህ መንደር ፊልም እንደሠራሁ በትህትና ነገርኩት "አይመለከተኝም" አለ። መንገዱን
ዘግቶብን ከመኪናው ፊት እንደቆመ ስልኩን አውጥቶ ለወረዳው ኃላፊ እያጋነነ ሪፖርት ማድረግ ጀመረ። ከውስጥ የሚያወራው ሰው ድምፅ አይሰማኝም። ሰውየው ግን "እሺ ጌታዬ"፣ "እሺ ጌታዬ" ይላል። ስልኩን እንደዘጋው ይቅርታ ጠይቆን መንገዱን ለቀቀልን። እኔ ስደሰት ህሊና ግን ተናዳለች። ዐይታ የወደደችው "ጎጃም አዘነ" የለበሰው ገበሬ ተሰውሯል።
ወደ ቆራጣ መንደር የሚያሳጥፈው ብቸኛውን የፒስታ መንገድ እየተውን
አስፋልቱን ለማግኘት ወደ ሐሙሲት አቅጣጫ ልንወጣ አስፋልቱ ዳር ስንደርስ
ሰባት ታጣቂ ፖሊሶችና ሁለት ሚሊሻዎች መሣሪያቸውን እንደታጠቁ መንገዱን
ዘግተው አስቆሙን። ልብሱም እኛም በቁጥጥር ሥር ዋልን። ሁሉም መኪናው
ላይ ተጣበው ተጭነው ወደ ሐሙሲት ከተማ አመራን። የወረዳው ምክትል አስተዳዳሪ በሌሎች ታጣቂዎች ታጅበው ጠበቁን። አስረዱ ተባልን ትንታኔ ሰጠሁ። ምክትል አስተዳዳሪው "የአካባቢው ሕዝብ አስተዳደርና የፀጥታ አካላት እንዲህ ዓይነቱን የወረዳችንን ‘ኢሜጅ’ የሚያጠፋ ድርጊት በቀላሉ አንመለከተውም?" በማለት ፖለቲካዊ አንድምታ ሰጡት። ቀጠል አድርገውም፣ "መጪው ዓመት የምርጫ በመሆኑ ‘ሕዝቡ ኑሮው አልተቀየረም' የሚል መልዕክት የማስተላለፍ አዝማሚያ ያለው ድርጊት በመሆኑ፣ ጉዳዩን ላይ ድረስ የምናጣራው ይሆናል። ልብሶቹን በሙሉ አስረክቡ፤" አሉ። "ወዜን አላስረክብም" ዓይነት ወኔ መጣብኝ። በስንትና ስንት ልፋት እና ውድ ዋጋ የተገኙ ልብሶች ዕጣ ፈንታ መቃጠል እንደሆነ አንዱ አጃቢያቸው "ከነተባዩ እሳት መልቀቅ ነው" በማለት ሲናገር ሰምቼ ተረዳሁ። "ከነልብሱ እዚህ እቆያለሁ እንጂ ብቻውን አልሰጣችሁም፤" አልኳቸው። ምክትል አስተዳዳሪው ቀጭን ትዕዛዝ ሰጥተው ሄዱ፡፡ ‘‘ቀበቶህን ፍታ’’ ተባልኩ። ሲመሻሽ ከሰባቱ ላስቲክ ልብሶች ጋር
ወደ ወህኒ ወረድኩ። በሕይወቴ የመጀመሪያዬ የሆነውን የእስር ጊዜ ከ11 ታሳሪዎች ጋር ለማሳለፍ ወደ እስር ቤቱ ስገባ በእጅጉ ተገረምኩ። አሥራ አንዱም እስረኞች ያለፍራሽ ወለሉ ላይ የተነጠፈው ላስቲክ ላይ ተኝተዋል። ሰባቱን ላስቲኮቼን ግጥም አድርጌ አስሬ ደርድሬ ምቹ ፍራሽ አደረግኳቸው። የላስቲኩን ድምፅ የሰሙት እስረኞች በየተራ እየነቁ ከኔ ጋር ማውራት ጀመሩ።
የታሰርኩበትን ምክንያት ስነግራቸው መሳቅ ጀመሩ። አብዛኛዎቹ ታሳሪዎች
የገጠር ሰዎች ስለነበሩ "የኔን ወዝ የማትገዛኝ" እያሉ አሳሳቁኝ። አንዳንዶቹም ልሽጥልህ እያሉ ሲያስጎመጁኝ አደሩ። በሕይወቴ የማውቀው ረጅሙ ሌሊት በእስረኞቹ አጫዋችነት በመጠኑም ቢሆን አጥሮልኛል። ሊነጋ ሲል ሸለብ
አደረገኝ። ጠዋት በሩ ተከፍቶ የሚጣፍጥ አምባሻ በሻይ መጣልን። እስር ቤቱ በራፍ ላይ ካለው ፍርግርግ አጥር ውስጥ ፀሐይ ለመሞቅ ስንወጣ ስልክ ተፈቅዶልኝ መደወል ጀመርኩ።
በወቅቱ የባህልና ቱሪዝም ሚንስቴር ሚንስትር ዲኤታ የነበሩት አቶ ሙሉጌታ ሰኢድን አናገርኳቸው። ሊረዱኝ የሚችሉ ሌላ ባህርዳር ከተማ የሚገኙ ኃላፊ ጋር
ደውለው ጉዳዬን እንደራሳቸው ጉዳይ ነገረው በአስቸኳይ እንድፈታ ትብብር
ጠየቁልኝ። ኃላፊዎች ተባብረውኝ፣ ስለሥራችን አስረድተውና ደብዳቤ ጽፈው እኔም ልብሶቹም ከእስር ነፃ ወጣን

የወረዳው አስተዳደር ወዙ ደርቆ "ወዜን" አሳልፌ አልሰጥም ቢልም በስንት ውጣ
ውረድ ከቃጠሎ የተረፉ ልብሶችን አስለቅቀን ወደ መንደሩ ላለመመለስ ወስነን ወጣን። አዲስ አበባ ለመመለስ ጉዞ ጀምረን ጥቂት እንደተጓዝን የህሊና ዓይኖች ብርሃን ለበሱ። ቆራጣ የወደደችውና ያመለጣትን "ጎጃም አዘነ" ተመሳሳይ ልብስ አንድ የቆሎ ተማሪ ለብሶ አየች። መኪናውን አስቁመን መንደር ውስጥ ተሯሩጠን ደረስንበት። የእግዜር ሰላምታ ተለዋውጠን የሮጥንበትን ምክንያት አስረዳነው። የቆሎ ተማሪው በጥያቄ ሲያጣድፈን ቆይቶ "ወዜን አልሸጥም" ብሎን እብስ አለ።
ወዝ ያለው!!

@wegoch
@wegoch
@paappii
ስልክ አውርቶ ካበቃ በኋላ ጓደኛዬ ላሎ ፊቱ ጨው ሆኖ ከሰመ።
"ምን ሆንክ ላሎ ?"
"ተወኝ እስቲ !" ወገቡን ይዞ ተንጎራደደ ።
ወድያው እጁን ከወገቡ ላይ አንስቶ ጠረጴዛውን ደቃው ።
"እንዴት አባቷ እንደዚህ ታደርጋለች? :) ...እኔ ላይ ? ቤቴ ላይ ? አይደረግም !"
"ማናት ምን ሆንክ ?"
በረዥሙ ተነፈሰ። እሳት ከአፉ ውስጥ ተፋ ብል ይቀለኛል። ላሎ ቫምፓየር ሆነ ...
"ማናት ?" ጥያቄውን ደገምኩለት !
"ሚስት ተብየዋ ናታ !"
ጠረጴዛውን መነረቱን ለቀቅ አድርጎ ወደኔ አቅጣጫ ተመለሰ። መሀል ወለሉ ላይ ያገኘውን የወረቀት መያዣ ካርቶን ጠለዘው።
ባዶው ካርቶን ግንባሬን ቀምሶ ተንሸራቶ ወደቀ።
"ይቅርታ ሚኪ !"
"አይ ምንም አይደለም። "
"አትፍረድብኝ የሆነውን ነገር ብታውቅ ሽጉጥ ባርቆብኝ ብመታህም አትፈርድብኝም።" ለደቂቃዎች ዝም አለ።
"ደግሞ እኮ አልጋችን ላይ። ሌላ ቦታ አጣች ይህቺ አለሌ !" ...የድምፁ ንዝረት እየጎላ መጥቶ መንግስቱ ሀይለማርያምን የሆነ መሰለኝ።
በቃ ሚስቱ ቺት አድርጋበት ይሆናል አልኩኝ ካርቶኑ የቀመሰኝን ግንባሬን እያሻሸሁ።
"ተኗኗርናታ! ...ተዛለቅናታ !" ... ላሎ ለይቶለት ወፈፈ።
ሚስቱ ከሱ ሰርቃ ሌላ ወንድ ጋር ሄዳ ከሆነ ይሄም ሲያንሰው ነው። ... ምሽት ቤቱ ሲገባ ካገኛት እንደ ማስቲካ ያላምጣታል...እንደ ቲማቲም ይከትፋታል ...እንደ እንቁላል ይጠብሳታል።
ዛሬ ያቺ ሴት ያከትምላታል በቃ !
ቀጣዩ የተዘጋው ዶሴ ታሪክ የነ ላሎ ታሪክ ነው።
ተራኪው ፖሊስ ተጠርጣሪው ግለሰብ ከቢሮ ወጥቶ ቤቱ በደረሰ ወቅት መጥረቢያ ይዞ ገባ። ... በያዘው መጥረቢያ የባለቤቱን አናት ፈርክሶ እዛው ልጆቻቸው ፊት ገደላት ። ምናምን እያለ ድምፁን እየጎተተ ሲናገር አስቤ አንፃረ ገፄን ሶስት ጊዜ አማተብኩኝ።
"ማንነቴን ታየዋለች!
ላሎ ማን እንደሆነ ታየዋለች ይህቺ ዋልጌ !"
ድምፁ ከመጮህ ወደ መንቀጥቀጥ ወረደ።
ሰው ሲናደድ ለካ ድምፁ የጎዣምን እንቅጥቅጥ ይደክራል። ሰማኸኝ በለው በሌለበት የላሎ ድምፅ እንደ ዝናብ ወረደ። ጉሮሮው ... አንደበቱ አብዮት ጨፋሪውን ሆነ። እንዝርት ሆኖ ሾረ።
ይሄ ሚስቱ ቺት ያደረገችበት ወዳጄን ምን ብዬ ላፅናናውና ላረጋጋው እችላለሁ ብዬ ተብሰለሰልኩ።
"እገድላታለሁ! " አለኝ ፈርጠም ብሎ።
"ተረጋጋ ላሎ! "
"አልረጋጋም " አንባረቀ። ጩኸቱ የደረሰች ሴት ማህፀን ከፍቶ ፅንስ ያስወርዳል።
እየፈራሁ እየተቸርኩ...
"ባለቤትህ ምን አደረገች ?" አልኩት።
"እሷ? "
"አዎ እሷ"
"እሷማ ከዚህ በላይ ምን ታደርግ? ...ኑሮ የሚያቃጥለኝና ቤቴን ሙሉ የማደርገው አንሶ ጭራሽ አልጋችን ላይ ?"
ዝም አልኩ።
መልሼ የጅል ጥያቄዬን ወረወርኩ።
"አልጋችሁ ላይ ምን? "
ላሎ ሲያስብ ቆየነ አንደበቱን ከፈተ...
"ትናንት የገዛሁላትን አምስት ሊትር ዘይት ስትደናበር አልጋችን ላይ ደፋችው "😃

ሚካኤል አስጨናቂ

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰላም እንዴት ሰነበታቹ ፥ በሸክላ ስራ ሙያ ላይ (የሚሸጡ አይደለም) እና በመምህርነት ሙያ ላይ የተሰማራችኹ ወይንም በዚኹ ሙያ ላይ ያለ የምታዉቁት ሰው ካለ በዚህ ሊንክ @Mykeyliyew አናግሩን።

@Wegoch
@Wegoch
@Wegoch
የኃይል መገኛው የት ነው? - አንገብጋቤ ጥያቄ
ቫረስና ቴሪየን አለቃና ምንዝር ናቸው፡፡ ቲሪየን ከመሳፍንቱ ወገን ሲሆን ቫረስ የነገስታቱ አማካሪ ነው፡፡ የወይን ብርጭቋቸውን እያጋጩ ስለ ዙፋንና ስለ ኃይል አሰላለፍ ሞቅ ያለ ጨዋታ ይዘዋል፡፡ በመሐል ይሄንን ወሳኝ ጉዳይ አነሱ፡፡
.
“እንቆቅልሽ ትወዳለህ ጌታዬ?” አለ ቫረስ፤ ከወንበሩ ሳብ ብሎ ወደ ቲሪየን አንገቱን እያቀረበ።
“ለምን ጠየከኝ? ከእንቆቅልሾቹ አንዱን ልትነግረኝ መሆኑ ነው?” ብሎ በወይን የተሞላ ብርጭቆውን እንደጨበጠ ቫረስን ለመስማት ወንበሩ ላይ ተስተካከለ።
“…ሦስት ኃያላን ሰዎች በአንድ ቤት ውስጥ ተቀምጠዋል” አለ ቫረስ ንግግሩን ሲጀምር “አንዱ ንጉሥ ነው፤ ሁለተኛው ደ'ሞ ጳጳስ፤ ሦስተኛው የናጠጠ ሀብታም። በመካከላቸው ጎራዴ የታጠቀ ወታደር ቆሟል። ወታደር ስልህ ይኼ በየጦር ሜዳው ጀብዱ እየፈጸመ ወይዛዝርቱና እረኞች የእሱን ስም እየጠሩ የሚዘፍኑለት ዓይነት አይደለም። ተራ ወታደር ነው፤ ቅጥረ ነብሰ ገዳይ የሚሉት ዓይነት ወታደር። እውቀትም የለው፤ ፊደል ቆጥሮ የማያውቅ መኻይም ወታደር። ታዲያ ሦስቱ ኃያላን ሰዎች አንድ በአንድ ጮኸው ለወታደሩ ትዕዛዝ ይሰጡታል፤ ‘እነዚህን ሁለት ሰዎች ግደላቸው!’ ይሉታል።
በመጀመሪያ ንጉሡ “እኔ ሕጋዊ ገዥህ ነኝ! ትዕዛዜን ፈጽም!!” አለው።
ቀጠለ ጳጳሱም “በአማልዕክቶች ስም ይዤሃለሁ! የምልህን አድርግ!!” ሲል አዘዘው።
ባለጸጋውው“ትዕዛዜን ከፈጸምክ ይኼ ሁሉ ወርቅ ያንተ ይሆናል!” አለው…
...አሁን ጥያቄው ከሦስቱ ማን ይድናል? ማንስ ይሞታል?” አለ ቫረስ እንቆቅልሹን እንዲፈታለት ቲሪየንን አተኩሮ እየተመለከተ።
ቲሪየን ጥቂት አሰብ አደረገና፣
“እንደ ባለጎራዴው ሰውዬ ማንነትና ፍላጎት ይወሰናላ...” ሲል መለሰ።
“እንደዚያ ይሆናል ብለህ ነው ጌታዬ?” አለ ቫረስ የነገሩን ውስብስብነት ለማስረዳት በአእምሮው ቃላት እየመረጠ። "ሰውዬው ተራ ሰው ነው፤ ብዙም የወርቅ ፍላጎት የለውም። ደ'ሞም ከራሱ ውጭ የሚንከባከበው ወይም የሚያስተዳድረው ሚስት የለው ድስት! እምነትም ላይ እስከዚህም ነው - አልተቀባም፤ አማልዕክት ስለሚባሉት ነገሮች ብዙም ቦታ አይሰጥም። በሌላ በኩል የነገሥታትም ደም የለው - ሊነግስ አይችልም። ያለው ብቸኛ ነገር ቢኖር ያ ስለታም ቆርቆሮው ነው" (ጎራዴውን ማለቱ ነው)
“ታዲያ እኮ የያዘው ስለታም ቆርቆሮ ሕይወትንና ሞትን፣ መኖርና አለመኖርን ይወስናል! ጎራዴ እስካለው ድረስ ኃይል አለው ማለት ነው፤ የፈለገውን መወሰን ይችላል...”
“እርግጥ ነው ጎራዴው መግደልና አለመግደል ይችላል፤ እሱ ላይ አልተሳሳትክም። ዳሩ ግን የኃይል ምንጭ ‘ጎራዴ ነው’ ካልን ወታደሮች እያሉ ሰዎች ሁሉ ለንጉሥ መገዛታቸው እንግዳ ነገር አይሆንብህም? ሌላው ቀርቶ እጅግ ፈርጣማዎቹ ወታደሮች እንኳን ለጩጬ አልጋ ወራሽ ይገዛሉ፤ ለምን?... ዋናው ጥያቄ ‘ለምን ይገዛሉ?’ የሚለው ነው” አለ ቫረስ ፈገግ እያለ።
“ምክንያቱም ንጉሡም ሆነ ጩጬው አልጋ ወራሽ ሌሎች ወታደሮችን መጥራት ስለሚችሉ ነዋ!!” ቲሪየን እንደመበሳጨትም፣ እንደመቆጣትም እያለ ፈጥኖ መለሰለት።
“ስለዚህ እውነተኛ ኃይል ያለው ‘ሌሎች’ የተባሉት ወታደሮች ጋር ነው ማለት ነው? ግን ለምን እነሱስ ሳያመነቱ ይታዘዙታል? ጎራዴ ታጥቀው ሳለ በቀላሉ ለሚያሸንፉት ሰው መታዘዛቸው ምክንያቱ ምንድን ነው?”
ቲሪየን መልስ ሳይሰጥ ዝም አለ።
“አንዳንዶች ‘እውቀት ኃይል ነው’ ይላሉ። ሌሎች ደግሞ ‘ኃይል ከእግዚአብሔር ነው’ ሲሉ ይደመጣሉ። ጥቂት የማይባሉ ሰዎችም ‘ኃይል ከሕግ ይመነጫል’ ሲሉ ይመሰክራሉ። ችግሩ ግን አንዳንድ ጊዜ በሕግ ሥልጣን የተሰጠውም፣ በእግዚአብሔር የተቀባውም፣ ምሁር የተባለውም እንደ አንድ ተራ ሰው ምንም ማድረግ የማይችሉ አቅመ ቢሶች ሆነው ይገኛሉ” ብሎ ቫረስ ቲሪየንን ተመለከተው። ታዲያ አለ የተባለው ኃይል የታለ? በሚል አኳኋን ዐይኑን ከቲሪየን ላይ ሳይነቅል ዝም ብሎ ሲቆይ...
“ድሮም እንቆቅልሽ የሚሉት ነገር እንደማይጥመኝ ቀድሜ አውቀዋለሁ” አለና አቀርቅሮ ጭንቅላቱን ካሻሸ በኋላ ቀና አለ። ምን ብሎ እንደሚመልስለት ስለጨነቀው ራሱ ቫረስ መልሱን እንዲነግረው በዝምታ ይጠብቅ ጀመር።
ቫረስ ፈገግ ብሎ፣
"ጌታዬ፣ ኃይል መገኛው ሰዎች አለ ብለው የሚያምኑበት ቦታ ነው። ነገሩን ሲያስቡት ትንሽ ፈገግ ያስብላል። ግን ደግሞ እውነት ነው፤ ኃይል የሚኖረው ሰዎች አለ ብለው የሚያስቡበት ቦታ ነው። ልክ እንደ ጥላ ነው - ግድግዳ ላይ እንደሚታይ የሰው ጥላ፤ እጅግ በጣም ኮስማና የሆነ ሰው እንኳን እጅግ ግዙፍ የሆነ ጥላ ሊፈጥር ይችላል” አለና የወይን ብርጭቆውን አንስቶ ወደ ጉሮሮው አንቆረቆረ...
*
በተለይ የፊልሙ ወዳጆች ይሄንን አንብባችሁ በትዝታ መለስ እንደምትሉ አልጠራጠርም!!
ማስታወሻ፡- ፊልሙን ላልተመለከታችሁ አንባቢዎች… ቫረስ እና ቲሪየን ‘Game of Thrones’ በተሰኘ ተወዳጅ የእንግሊዘኛ ተከታታይ ፊልም ላይ የሚተውኑ ገጸ-ባሕርያት ናቸው። የሚነጋገሩት ሐሳብም ከዚያው ከፊልሙ ላይ ተቀነጭቦ ለትረካ እንዲስማማ ተደርጎ የተተረጎመ ነው።) ሚያዚያ 3፣ 2011 ዓ.ም 💙

መሳፍንት ተፈራ

@wegoch
@wegoch
@paappii
እስኪ አንድ ጊዜ ሰዎች attention

እስኪ እናስበው🙄 እናስታውሰው ,እናውሳው😭 የዛሬ 3 አመት ገደማ ነበር ይህ የምነግራቹ ነገር እድሜያቸው ከ17 በታች ለሆኑ አይመከርም💀

እንዳልኩት የዛሬ 3 ዓመት ገደማ ሁለተኛው ክ/ጊዜ አልቆ በሶስት ስፖርት እንደ ሆኑ በማወቅ በደስታ ትጥቃቸውን ቀይረው hpe teachern ይጠባበቁት ጀመር የዛኔው g-9A(meselegn🙄)ያሁኖቹ g-12 this year ተፈታኞች😭,,teacher g/egzier(hpe) ተናገረ :ውጡ ተውሎ ቧሉ😂 ተማሪዎቹም እነሆ ወጡ ለካ ዛሬ ሚማሩት መከረባበት ነው ያቺ ጥቁር ፍራሽም ያው ፀሀይ ላይ ግላላች

ተጀመረ 😱አባቴ ተጀመረ ሀብቶም😂😂ብድግ 😱ለጥ,ዮሀንስ እንጣጥ እንደ መከርበት ነገር,ያው የሴቶቹ ግልፅ ነው ኩስትርትር ብላ ትሄድና ሮጥ ሮጥ ብላ እጇን እንደሚሰጣ ፎጣ ወደ ኋላ ከዛ
1.ወይ በጭንቅላቷ ስንቅር ልክ እንደ ደመራ ቋሚ ከዛ teacher ደንገጦ ጠጋ ይልና ባላየ ገፋ
2.ወይ እንደተለመደው የተጣመመ ሮል(ከፍራሹ ውጭ ሌላ ታሪክ😭)
3.አለበለዚያ ደሞ የሚገርም action (like አንዷ ሳትጨርስ አንዷ እንደመዝነብ)ነበር

አሉ ደሞ እኔ ስም አልጠራም አንከረበትም ብለው ጥጋቸውን ይዘው በሌሎች የሚስቁ

እእእ ግማሹ :እንዲ አርገህ እኮ እንዲ ስታረግ ቀላል ነዉ
አንደኛው:ቀስ ብዬ ቶሎ ልበል(😂በጣም ድንጋጤ)

💀💀😱😱በዚህ ሁሉ መሀል ነበር አሰቃቂው አደጋ ምስኪኑ የ15 አመት ከሩብ የሆነው ግቢዉ ዉስጥ famousu mr.hpe የሚወደው (😘ነገር ናቸው),mr.ግርማም የሚመቻቸው

እስኪ guess ማን ይመስለሰችኋል አው ልክ ናቹ(👀) ሱጥዎታ😭

አው ሟች ስጦታው አህመድ ወደ ተደገሰለት የሞት ድግስ እየሮጠ ነበር የገባው ነገርየው dive roll ምስኪኑ ልጅ ደሞ dive ጦር ይመስል ነበር የተሰካው እስኪ ያሳያቹ ላጥ ላጥ ብሎ ሮጠና ብድግ dive ፍራሹ ውስጥ ሽንቁር(ቋ ሲል የሰሙም አሉ)ሁሉም ፀጥ ረጭ ብሎ ነበር😭😱ሟችም ተንጋሎ ወቀ።😭😭😭😭

ግማሹ በስመአብ ወወልድ : ግማሹ ያረቢ ቢስሚላ : ግማሹ በየሱስ ስም : ግማሹ ብዛየው ድረስልኝ(የሰፈራ famous አዋቂ(ያው ጠንቋይ)): ግማሹ የ odin ልጅ thor አውጣኝ እያሉ የየራሳቸውን እምነት አመለከቱ

ገሚሱ:ባካቹ የምግብ እጥረት ነው አሁን ይነቃል
ገሚሱ:እየተንሾካሾከ ቡዳ በልቶታል አላልኩሽም
ገሚሱ:ባካቹ ቀልዱን ነው (ያብስራ ቢኖር እሱ ነበር ያለው)
ገሚሱ: ብር ፈልጎ ነው መሰለኝ(ባክ ተነስ ባነናለል)
ገሚሱ:ፀሀዩ ነው ቢሉ ምስኪኑ ልጅ ንቅንቅ ሊል አልቻል

mr .g/egzier 😱ክው ብላ እኔ ክው ልበል ሱጥወታ ሱጥወታ ሱጥ ስጥዎ ሱሱ ልጁ አይንን ጨፍኖ ሌላ ታሪክ ውስጥ teacher university እያለ የተማረው ትዝ አለው 😱ለካ ከ100 ሰዎች አንዱ ላይ የሚፈጠረው "the tounge the eat"የሚባለው ልክ ሰዎች እርቧቸው በፀሀይ ከዘለሉ:ከተንከባለሉ የራሳቸውን ምላስ ዋጥ 😱አርገው ይበሉና በዛው ከጠገቡ ይሞታሉ

teacher መፍትሄው ምን እንደሆነ ስለሚያውቅ ከድንጋጤው ባነነ ከዛም ሰልቤን ሱቅ ላካት
እስኪ ገምቱ ምን ይዞ የመጣ ይመስላችኋል የምላስ መጎተቻ:ፀበል:mr.bio ካላቹ ተሳስታችኋል መድሀኒቷ ሚስጥር ነበረች እንዳይረክስ ነው መሰለኝ ደብቆ አመጣና በዝግታ ልጁ ፌንት ከነቀለበት ፍራሽ ከፍ አርገውት አፉ ውስጥ መድሀኒቷን ሲከታት ደነገጡ እንዴ ምንድነው ሚሰራው እንዴት ይሆናል ለልጁ የሰጡት የዛኔዋ የሀለት ብር ከሀምሳ ኮክቴል የፆም ብስኩት ነበር,ነገር ግን ከሀሉም አጀብ ያስባለው የሱጦታ አይን ቀለስለስ ብላ ግልጥ ማለት አፎቹም ቀስ ብለው ማላመጥ መጀመር ነበር ልጁ ቁልጭ ቁልጭ ብሎ ምን ቢል ጥሩ ነው teacher እኔ እኮ አልፆምም የፍስኩን አትገዛልኝም ብላ ቁልጭ ፍጥጥ ጨምሩ

ተማሪዎችም በመደንገጥ በመደመም በመደሰትም ከላይ በጠቀስኩላችው እምነታቸው ማመስገን ጀመሩ ከሰዐታት በኋላ ፍራሹን ፈቀቅ ሲያረጉት ቴራዞ ተሰንጥቋል ያ ቦታ እስከ ዛሬ ስጦታው ኮክቴል እየተባለች ነው ምትጠራው ታድያ አሁን ውሀ ፈልቆ ህዝቡን በልማት ተጠቃሚ ከማድረግ ባሻገር ለዜጎች የስራ እድል ፈጥሯል በዚህ መቆፈርያ ጭንቅላቱ አሁን social science እየተከታተለ ይገኛል(ክብር ለተሸላሚ መቆፈርያ ራስ አርሶ አደሮች)


የምር ግን ተዐምር ነው መትረፉ ተብሏል(እንኳን ተረፍክልን)😭😱

የኮክቴሏ ተዐምር ወይስ የልጁ ረሀብ እሱ ይዳኝ ለማንኛዉም መልካም የህማማት ጊዜ,,funfact do u know if u laugh its sin is on me meselegn ,,,,bye


Info----teacher hpe
Writer-ab
Best boy -👀👀
Writting time-from 1:00-infinite

👴peace

@wegoch
@wegoch
@Mahletzerihun

#abenaw
...
ወላንሳ አመለ ምቹ ህፃን ሆኜ ላባ በጣም እወድ ነበር። ነጭ ላባ። ከዶሮ ተነቅሎ የቀረ። ምናልባትም ከሞተ ዶሮ። ልስላሴዉ እስካሁን ላባዉን በአንሸራሸርኩበት የአንገቴና የፊቴ ክፍል ይሰማኛል። አይኔን እከድንና አንገቴን በላባ አባብል ነበር። ይለሰልሳል። የሚጣፍጥ መለስለስ። አይዞሽ! አይዞሽ! የሚል መለስለስ። ማንም ሲያደርግ አይቼ አይደለም። ያ በጣም ለስላሳ ነገር ላባ እንደሚባል ያወኩት ሳድግ ነዉ። አንዳንድ ነገር ግን ሲገርም።ነገሮችን መቼ ነክተን ፤ ቀምሰን ፤ አሽትተን ጣእማቸዉን ፤ ባህሪያቸዉን እንዳወቅን አናዉቅም። ግን ደሞ እናዉቃለን። ማንም ሳይነግረን እንኖረዋለን። የላባን ልስላሴ ማን ነገረኝ? ደመነፍሴ? እንጃ!! ከዛ በኋላ ለልቤ የሚለሰልሱ ነገሮች ሁሉ ያንን ላባ ያስታዉሱኛል። ልክ እንደ አንተ!!
...
መንገድ ስወጣ እጄ መሃል ምራቄን አድርጌ አካሄድና መንገዴን በምራቄ አቅጣጫ የምወስን አይደለሁም። ዉይ ያን ያህል ወግ ከየት አመጣለሁ? ከርታታ ተጓዥ ነኝ። ወደ አምላክ ጥላ ለመቅረብ ፤ ወደ ሰዉ ልብ ለመድረስ ፤ ለነፍሴ ጩኸት ፋታ ለመስጠት እግሬን የማወናክር ድኩም ነኝ። በንፋስ አቅጣጫ ጥላዬን የምዘረጋ መንገደኛ ነኝ። ከፊት ከሚቀድመኝ የቀን ጥላዬ ከኋላ ከሚከተለኝ የምሽት ጥላዬ ፉክክር የምገጥም አላዋቂ ነኝ። ለአረማመዴ ወግ የለኝም። ምን ትሰራለህ ከስሬ? ጩኸቴ አይረብሽህም? አርያም የሚደርስ ሳቄ ከጥሞናህ አያናጥብህም? ጥያቄዎቼ ከአቅምህ በታች አይሆኑብህም? ፍለጋዬ ዉል አልባ ሆኖ አያበሳጭህም? እንደ እኔ ነህ ወይስ እኔን ሆነሀል? ከመንገዴ ፈቀቅ ብልልህ አብረኸኝ ትጓዛለህ? ወይስ በአካሄዴ ለመሳለቅ ጊዜ ትጠብቅልኛለህ? አትተወኝም ወደመንገድህ ልምጣ? ወይስ ወደ እኔ መጥተህ እዚሁ እንቅር? ብዙ ጥያቄ አለኝ! ካላሰለቸዉህ።
...
ደስ ትለኛለህ። ስትስቅ ፤ ስታወራ ፤ ስትዘምር እና ሁሌም ደስ ትለኛለህ።
በቀዳዳዉ ማንነቴ አጮልቄ ሳይህ ዉብ ነህ። አልነገርኩህም አይደል? በጣም
ዉብ ነህ። እንደ ጨረቃ!! ለስላሳ እንደ ላባ!! ... እጄን ስትይዘኝ አዋጅ የለህም።
ዝም ብለህ ያዝ። ስትወድ እወቁልኝ አትደግስም። ዝም ብለህ ዉድድድ።
የሚወደድ ነገር ሁሉ ነህ። እንቅፋት የበዛበት እድሌ ላንተ ልብ እንዳይተርፍ
የቤቴን አድባር እለማመናለሁ። ቂጣ ከቆሎ እጥላለሁ። እንደወደድከኝ ልወድህ... እንደያዝከኝ ጥብቅቅቅቅ ላደርግህ። ከሚዛኔ እንዳልጎል ፥ ከአይኖቼ ስር እንዳላጣህ እለማመናለሁ። ልቤን እለምናለሁ። እቅፍህ መሃል እንዲያደርሰኝ፥ ብተወዉም እንዳይረሳኝ ለፈጣሪን ጧፍ እጣን እሳላለሁ። ያልገባሁት ሱባኤ
ያሳስበኛል። ያልፆምኩትን ፆም የሻርኩ ይመስለኛል። ልቤ ይደነግጥብኛል። ግን
ምንድነዉ?

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Ruth habte mariyam
መብራት ሲጠፋ አልወድም። የምሰራው ኖሮኝ ሳይሆን አይምሮዬ
እንዳይሰራ ብዬ። ያዳፈንኩትን ትዝታ እንዳያጠነጥንብኝ! ስለጨለመ
የማየውን እንዳያስቀር ሳይሆን ከራሴ ጋር እንዳያስተያየኝ። መብራት ካለ
መፅሃፍ ከማንበብ ወደ ስልክ፤ ከስልክ ወደ ቴሌቪዥን። ብቻ ብዙ
ግርግር። የስልኬ ባትሪና የተለኮሰው ሻማ ወደማለቁ ነው። ያስታወስኩህ
ዛሬ ባይሆንም ትዝ ባልከኝ ቁጥር ነፍሴ ራሷን የሆነ ነገር ውስጥ ለመደበቅ
ትጣደፋለች። ሁሌ አይሞላላት ሆኖ ለትላንቴ ያጋለጠችኝ ጊዜ ፀፀት
ያናውዘኛል። አየህ ዛሬ ሊመሽብኝ ሲቃረብ ነቅቻለሁ። የሚቆጨኝ ላንተ
የደከምክልኝን ያህል አለመሆኔ ነው። ልብ ስገዛ፤ እሳቴ ሲበርድልኝ፣
የልጅነት አመሌ ሲሟጠጥ የለፋህባት ሰው ውጤቷን ሳታይ እህል ውሃችን
አለቀ። ያላወራረድኩት ሂሳብ ሃሳብ ሆኖብኝ ቁጭት ያንገበግበኛል።
ምነው እንደአሁኗ አይነት ሴት ሆኜ ጥለኸኝ በሄድክና ከኔ ስህተት
ባልተገኘ... ምነው ገፊ ሆኜ ግፍ ባላስቆጠርኩ... ምነው ያን ሁሉ መንገድ
ችዬህ መጥቼ ቁልቁለቱ ላይ አቅም ከዳኝ?! ምነው?.
የራስህ የሆነ ከየትኛውም ጥንዶች ያልተኮረጀ አወዳደድህን እወደዋለሁ።
ህይወትን የምትረዳበትን አቅም እሸነፍለታለሁ። ልጅን በከረሜላና በሚታይ
ነገር መሸወዱን ነው ያልቻልክበት። አለመቻልህ ካንተ አርቆኝ የኑሮ አዙረኝ
አታዙረኝን በሜዳ ተሽከርክሬ እነአይሆኑ ላይ ወድቄ ተነሳሁ። ከአንዴም
አራቴ። እርግጥ ዛሬ ዓለም ስቃልኛለች። እኔ ግን ሳቋን በሳቅ መመለስ
ከበደኝ። ቅጣቴን አለመቀበሌን ተቀብሎ መኖር አቃተኝ። ያጎደልክብኝ
ካጎደልኩብህ ተጣፍቶ ሳለ ለምን እኔ ደልቶኝ አንተ አልተካስክም?! እግዜር
ለምን ያንተን ልብ አክሞ አልያ የጉዳትህን እጣ ለእኔ ሰጥቶ ፍትሃዊ
አይሆንም?!
እነዛ አመታት ታሪኮቻችን ተሰነደባቸው። ገና ከ ሀ ስንጀምር አይኔን
የገለጥኩት ባንተ ነው። ከቤት እንደወጣሁ ከከተማውና ከሰው ሳልቀላቀል
አንተን አወቅሁ። አምስት ቦታ ወደኋላ ተሾርቤ፤ የሴትነት ቅርፅ እና መልኬን
ለመሸሸግ ሰፊ የወንድ ጅንስ ሱሪና ትልቅ ጃኬት ለብሼ። የልብሴን እጀታ
በጥርሶቼ እያኘኩ ዓይኖቼን ከወንድ ዓይኖች በማሸሽበት ጊዜ። እንደዛሬ
ጭኖቼ በአጭር ቀሚስ ሳይጋለጡ፤ ሴትነቴ ሳይጎመራ... በዛ ማንንም
በማልስብበት እድሜዬ የወደድከኝ አንተ! ጡቶቼን ለመጀመሪያ ጊዜ
ያሳየሁህ አንተ! አይን አውጥቼ ስጎረምስ የአፍላነት እብደቴን የታገስክልኝ
አንተ! በታሪክህ ውስጥ ብዙ ታሪክ ያለኝ እኔ! ቁጣህን በፈገግታ የምረታ፤
በሀይልህ ውስጥ ፍቅርህን አጮልቄ የማይ እኔ!
አዎ እንዲህ ነበርን። በህይወት አብዝቼ የሚፈልገውን ነፃነት ያገኘሁት
ካንተ ነው። በፍቅር፣ በባህል፣ በሃይማኖት ስም በሚደረጉ ማሰሪያዎች
ሳትሸብብ መንፈሴን ነፃ ዓለም አሳይተሃታል። የማልቆጥርልህ ውለታ፥
የማላስታውሰው ኑረት የለም። ስምህን በክፉ ማንሳት አይሆንልኝም።
ስሄድ ብዙ ሳልርቅ የምትጠራኝ መስሎኝ ነበር። የማልመለስበት እስክደርስ
ለምን ጠበቅከኝ? ለምን እንድጨክንብህ ህመም እያሰቃየ ሲያሳድረኝ ዝም
አልክ? ብቻ ሁሉም መሆን ስለነበረበት ሆኗል። የምፈልገው ከፍቶህ
እንዳላይህ ብቻ ነው።
በምትወደው ጠይምነቴ፤ በምወደው ቀና ልብህ
እለምንሃለሁ...
ለተጫነብህ ሙጫ ትዝታ... ስላጎደልኩት የመኖር ትርጉም...
ስላጣመምኩት የህይወት መንገድ...
ይቅርታህን!!!!!!!
.
የመብራቱ ብርሃንና የቴፑ ድምፅ ሳይቀዳደሙ እኩል ደረሱ።
"ሙሉውን ሰውዬ ስቀናንስህ፣
ሆኜ ተገኘሁ ላንተ የማንስህ!"
ኩኩ ሰብስቤ ነበረች።

@wegoch
@wegoch
@Mahletzerihun

#Enqopawit enqopa 🖤
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት፣አውሮፓ ውስጥ ነው። ሁለት ወጣት መነኩሲቶች በማታ አብረው እየሄዱ ሳለ ሁለት ጋጠወጥ ወታደሮች ይይዟቸውና አስገድደው ይደፍሯቸው ጀመር። መሀል ላይ.... አንደኛዋ መነኩሲት ወደ ሰማይ እየተመለከቱ «አምላኬ ሆይ፤ የሚያደርጉትን
አያውቁምና ይቅር በላቸው!» በማለት ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ፀሎታቸውን
አሰሙ። ሁለተኛዋ መነኩሲት አንዴ ወደ ደፋሪአቸው አንዴ ደግሞ ወደ ሰማይ
እየተመለከቱ በተቆራረጠ ድምፅ «ይሄኛው. . . የሚሰራውን . . .ያውቃል!» አሉ
አሉ።
-
የምንሰራውን የምናውቅ ሰዎች የዚህ ሳምንት ንሰሀ ትዝ ብሎኝ ነው! 🙂

@wegoch
@wegoch
@paappii
#Gemechu Merera Fana
#እውነት_እውነቱ_ከተወራማ_ጉጉት_ይደበዝዛል_ጃን!
~
~
ፈሪ ነኝ? አዎ ግጥም አድርጌ... በቀን ሀያ ሰባት ሰአት ከእሩብ ሰኮንድ እንቦቀቦቃለሁ፡፡ የፍርሀቴ ትልቁ ፍርሀት ግን ፈሪ መሆኔ መታወቁ ስለሆነ ከምንም ፊት ደፍሬ እቆማለሁ፡፡ ደፋር የሚያስብሉኝ ታሪኮቼ በሙሉ ተጋድመው ሆድእቃቸው ቢመረመር ፍርሀት ይፍለቀለቃል፡፡ የደፈረኝ ሰው እኔን ፈሪ አድርጎ ማየቱ ነው የድፍረቴ እና ምላሽ የመስጠቴ ምንጭ፡፡
የሆነ ግዜ እንዴት ሆነ...ስምንተኛ ክፍል መሰለኝ... ትላንቶቼ ይደበዝዙብኛልኮ አንዳንዴ የማስታውሳቸው በፍቅርተ ነው፡፡ ስምንተኛ ክፍል... ፍቅርተ እግሯን ምን መቷት እንደሆነ እንጃ ስታነክስ... አዎ የዛኔ ነው... ስምንተኛ ክፍል፡፡
ደፋሮች ነን የሚሉ ሁሉ ይሰባሰባሉ፡፡ ምናልባት አንዱ ከአንዱ ተነካክሶ ብዙ ያለመጎዳት ፍርሀት ነው የጓደኝነታቸው ስሩ፡፡ ካልተሰበሰቡ ለብቻቸው ሰው አይደሉም... ጎዶሎ ናቸው፡፡ እና እኚህ ስብስብ ፍጡራን ሰብሰብ ሲሉ ድፍረታቸው ብቻ ሳይሆን ንቀታቸው ይጨምራል... ፈሳም ተሰብስቦ... ይጨመቅና አንድ ቦርጫም ጉልበተኛ ያበጃሉ፡፡ አንድ አካል ሲሆኑ አንዱ እጅ (ወፈር ያለ ሆዳም) አንዱ እግር (አሯሩጦ የሚጠልፍ ነገር) አንድ አይን (ንቀትኛ የሚያጉረጠርጥ) አንድ ፀጉር (ስራ ፈት ፂማም) እኚህ ተሰባስበው አንድ ፍጡር ይሰሩና ያስፈራራሉ፡፡ ከዚያ መሀል ደግሞ አንድ ቀዥቃዣ አይጠፋም... የጠብ ቅመማ ጥበብ የተካነ... አጫጫር የሚችልበት... ድምፅ ብቻ የሆነ፡፡ አይጠፋም አንድ... ኤልያስ ነበር እሱ፡፡
በድሉ ሱቅ ጋር ተቀምጫለሁ፡፡ ከእቤት ለመውጣት ለሰነፉ ሰዎች ሲጋራ ኮካ ምናምን አመላልስና የሰጡኝን ይሰጡኛል፡፡ ትዕዛዝ እየጠበኩ ተቀምጫለሁ፡፡ እነ ኤልያስ ተሰብስበው እያለፉ ነበር፡፡ ጠብ አደን ስምሪት ላይ ያሉ ይመስላሉ... ስድስት ይሆናሉ...
<<ይሄ ልጅ ያፈጣል!>> ኤልያስ ነበር...እንዲህ እስኪላቸው ድረስ እኔም ራሱ ማፍጠጤን አላስተዋልኩም፡፡
<<ምን ታፈጣለህ?>> ተጠጋኝ... እድሜ ልኬን ሲያቀኝ ሳፈጥ ነበር፡፡ የኖረ ልምድ ለአዲስ ፀብ ጠፍጥፎ ሲያመቻች እንጂ
<<መብቴ ነው>> ብቻውን ላነጥረው እያሰብኩ
ነው፡፡
<<ይዋጣልን እንዴ?>>
<<አልፈልግም>> ሳቁ ሌሎቹ...ላነጥረው እያሰላሁ ነው አሁንም
<<ከዚህ በኀላ ስታፈጥ እንዳላይህ...>> ከቲቸር የኮረጀው ነው? <ወላጅ ሳትይዝ እዚህ እንዳላይህ> ብለውኝ ያውቃሉ ቲቸር ኬሚስትሪ፡፡
<<ለምን ዝም ብለህ አታልፍም?>> አልኩት...በድሉ ብቅ አለ፡፡
<<አይንህን አጠ...>> ቃሉን አልጨረሰም አፍንጫውን መታሁት፡፡ ወደቀ፡፡ ሌሎቹ ከበው ይደበድቡኛል... (<ኸረ ገደሉት> ትላለች የሆነች ሴትዮ... ድምፅዋ ረበሸኝ?) ኤልየያስ ሳልመታው በፊት ምን ሊለኝ ነበር? አይንህን አጠፋለሁ? አጠፋሪስ? አጠናግረው እስቲ? አጠንክር? ቢጨርስ ምናለ?
እየደበደቡኝ ነው... የሻሞ ቡጢ ይደርሰኛል፡፡ ኩርኩም ራሱ አለው... ቀሽሞች፡፡ በድሉ ብቅ ብሎ እያየ ነው? የሚገዛው ቢመጣ ጨው አይሸጥም? ይሄ ስግብግብ ወረኛ...
የሆነ መንገደኛ ጎትቶ አላቀቀኝ፡፡ ደክሞኝ ነበር... ፊቴ ረጥቧል... አቧራ ልሷል... ከከንፈሬ ላይ ስቀምሰው ምንም ምነንም አለኝ፡፡ የሆነ ነገር ሆኛለሁ፡፡ ወደ ቤት ሄድኩ!
ደፋር አይደለሁም! ግን በማግስቱ ፈልጌያቸው ሄድኩ... የከንፈሬ ልሙጥ ለስላሴ ሳይጠግግ...
ደበደቡኝ (<ኸረ ገደሉት> ትላለች አንድ ሴትዮ)
በነጋታውም ሄድኩ... በስልችት ደበደቡኝ (<ኸረ ገደሉት> ትላለች ሌላዋ... የተጠና አይመስልም? <አፍንጫውን ሲሉት በቀጭን ድምፅ ጩሁ> ተብለው የሰለጠኑ አይነት?)
በማግስቱም ሄድኩ (ስንዱ ፈራች... ልጄን ይገድሉታል ብላ... የ<ኸረ ገደሉት> ውጤቱ መሰለኝ...)
ተመላልሼ እስኪሰለቻቸው ደበደቡኝ... ነገም መምጣቴ እንደማይቀር ሲገባቸው ለመኑኝ <<ተው እንጂ ሲራክ ትጎዳለህ... ጥርስህን አወልቀዋለሁ>> አለኝ የልመና አይነት... እላይ ሰፈር ያለ ሆዳም ዘጠዘጥ ነው፡፡
መጨረሻ ላይ ፈሩኝ፡፡ ልክ አለም አይደለም... ተደብዳቢን ድፍረት ላይ ይሾማል?
ቁስሌ ሲድን <ደፋር> ተባልኩ... ደፋር ሲሉኝ አንድ ደረጃ አደግሁ... ጉልበተኛ ሆንኳ! ጉልበተኝነት የመጫጫር ፈቃደኝነት ነው፡፡ <ነህ> <ነህ> ብለው እፍ እፍ ይሉህና ነህ ላሉህ አለመሆንህ ያኖሩሀል፡፡ ነህ ላሉህ ጉዳይ ልትሞላ ትጋጋጣለህ፡፡
~
~
ፍቅርተን እጠብቃት ነበር... ፍርሀቷን ከፊቷ ላነብ... አንገት መድፋቷ ላይ የተሳለ በውስጧ ያለኝን ስዕል ላየው... አዲስ ነበር ሁሌ፡፡ ከቀይነት ወዟ የሚፈልቅ ደግሞ ሌላ አይነት አፈራር...
የምታየኝ ሩቅ ሆና እንደሆነ አውቃለሁ... እያየችኝ ትመጣለች... የ<እያየችኝ ነው?> ጥርጣሬ ውስጥ እንድወድቅ አስባለች፡፡ እየቀረበች ስትመጣ... ስትደርስ... ገዝታ ስትሄድ ደግሞ እንደሌለው... እንደማልታይ አይነት ነው ነገሯ፡፡ አታወራም! (ድምፄ ሲያምርህ ይቀራል መሆኑ ነው?) አታየኝም (ማን ነህና ትታያለህ? ትለኛለች?)
የወደዱትን መጠበቅ የተለማመድኩት ከሰማሁት ካየሁት ነው... ሬድዮ ሰምቼ ምናልባት፡፡ ያፈቀረ ሰው ካልጠበቀ ምኑን አፈቀረ? መጠበቅ ባይፈልግ እንኳን የስምምነት ግዴታ ነውና እየሰለቸ ይጠብቃል፡፡ ከከዋክብት ሽራፊ ያነፃፅራታል፡፡ አሁን ፍቅርተ መልኳ ግሩም ነው... ቅላቷ ምኗ... እግዜር ከሰኞ እስከ ቅዳሜ ሰርቶ እሁድ አረፈ... እሁድ ቁጭ ብሎ ጣቶቹን ሲያንቋቋ ሀሳብ መጣለት... ወይ ወደ ሀሳቡ ሄደ... የብርሀን ጨርቅ ከመጎናፀፊያው ላይ ቀደደና በሰው ቅርፅ አቦካው... እፍፍ አለው! ፍቅርተ ያቻት! እንዲህ አይነት ማካበድ ይጠይቃል ማፍቀር መሰለኝ፡፡ ስታፈቅር እንከን ትክዳለህ... አሁን ፍቅርተ ቆንጆ ትሁን እንጂ ሰውነት የሌላት ሰላላ... ሰባራ... አጥንታም... ቋቋታም... ሲጥ ሲጥ... ቆሮቆንዳ ናት፡፡ ያፈቀረ እንደዚህ አይልም ነውር ነው... እስኪንቅ ድረስ የሚክብ ውሸታም ነው የማፍቀርን ልኬት ያረቀቀው! ውሸት እኮ ጉልበተኛ ስር ትሽሎከሎካለች... አቅመኛ ስር ታለከልካለች... እንደ ፍጥሯ ይፈጥራታል... ያቦካታል... በፈለገው መንገድ ሲያጣምማት ተመልከት...
~
አንዳንዴ ግንፍልፍል ስል የማልለው የለኝም፡፡ መኖሬን ማጣጣል ጀምራለሁ...
<አላማ> ምናምን ቅብርጥሱ ተውና ትላንቴን ከነገዬ ለዩልኝ፡፡ ቅንጣት ይለያያሉ? በርቶ የመጥፋት ሂደት ምኑ ያጓጓኛል?
ይቺን ድብርታም ኑሮ ስሳደብ <የበላበትን ወጭት ሰባሪ በሉኝ> አቅሙ ኖሮኝ ምናለ መስበር ብችል? ባንከሻክሻት... አልችልምና ወጭቱን እቧጭራለሁ... ቢሳካልኝ ውብ ቀለሟን እልጣለሁ፡፡
ይቺን ኑሮ ብቁለጨለጫት አይኔ ይጥፋ! ለምኗም አልቀላውጥም! እንዲህ ስል ነው ፍቅርተ ትዝ የምትለኝ፡፡
ይቺ ሰቀቀናም ኑሮ... ትሰስታለች እንጂኮ ታስነካሀለች... ታሳይሀለች... ትዳስሳለህ... ምኑም ግን ያንተ አይደለም፡፡ መሰሰት ማለትኮ ጭራሹኑ አለመስጠት አይደለም... እጅግ አጉድሎ መስጠት ነው፡፡ ይቺም ሰቀቀናም እንደዛው ነች፡፡ አትሰጥህምም አትቀማትምም! ሰው ብትሆን ማሪያም ጣቷን በጥርሴ ቦጭቅና በስቃይዋ እምባ አፌን አባብስ ነበር፡፡
(ከጥቁርና ነጭ ማስታወሻ ላይ የተወሰደ)
(በረከት ታደሰ)

@wegoch
@wegoch
@wegoch
2024/09/23 20:19:51
Back to Top
HTML Embed Code: