Telegram Web Link
ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የደቡብ እና የደቡብ ምሥራቅ ትግራይ፣የቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ና የማኅበራት ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ አላማጣ ከተማ ሲገቡ ደማቅ አቀባበል ተደረገላቸው።

ጥር ፬ ቀን ፳፻ ፲ወ፮ ዓ.ም

ከሦስት ዓመታት በፊት የቋሚ ሲኖዶስ ተረኛ መሆናቸውን ተከትለው ወደ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የመጡት ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ በሰሜኑ የአገራችን ክፍል በተቀሰቀሰው ጦርነት ምክንያት በአዲስ አበባ ለመቆየት በመገደዳቸው ወደ ሀገረ ስብከታቸው ሳይሔዱ መቆየታቸው ይታወሳል።

የሰላም ስምምነቱ ከተፈረመም በኋላ በአካባቢው ያለው ችግር በመሰረቱ ባለመፈታቱ ምክንያት በራያና አካባቢው የሚገኙ ኦርቶዶክሳዊያን ምዕመናን የሚባርካቸው፣ የሚያስተምራቸውና የሚያጽናናቸው አባት ማጣታቸውን ተከትሎ ለቅዱስ ሲኖዶስ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ እንዲመጡላቸው ያቀረቡትን ጥያቄ መነሻ በማድረግ በጊዜያዊነት የራያና አካባቢው  ስድስቱ ወረዳዎች ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ተቋቁሞ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ እንዲመሩት የሰጠውን ውሳኔ ተከትሎ ጽሕፈት ቤቱ ተቋቁሞ ሥራ መጀመሩና በ42ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ሪፖርት ማቅረቡም ይታወቃል።

ይህን ተከትሎ ጽሕፈት ቤቱን በማቋቋም፣ በማደራጀትና ሰራተኞችን በመመደብ በርካታ ሥራዎችን ሲያከናውኑ የቆዩት ብፁዕነታቸው ጥር 3 ቀን 2016 ዓ.ም የጥምቀት በዓልን ለማክበር በጦርነትና በድርቅ የተጎዳውን ሕዝበ ክርስቲያን ለማጽናናት  አላማጣ ከተማ ገብተዋል።

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ  አላማጣ ከተማ ከመግባታቸው በፊት በምትገኘው ቆቦ ከተማ በብዙ መቶ ሺህ የሚቆጠሩ ካሄናት፣የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፣ምዕመናንና ምዕመናት በአይሱዙ መኪናዎች፣በቤት መከናዎች፣በባጃጃጅና በኝግር በማጀብ ደማቅ፣ናፍቆት የተሞላበትና በእጅጉ ፍቅር የታየበት በዓይነቱ ልዩና ደማቅ አቀባበል። አድርገውላቸዋል።
በአላማጣ ከተማ በሚገኘው ጥንታዊው፣ታሪካዊው አላማጣ ደብረ መድኃኒት መድኀኔዓለም ካቴድራል በተደረገላቸው ደማቅ አቀባበል ሥነሥርዓት ላይ በአላማጣና አካባቢው ነስድስቱ ወረዳ ቤተክህነት አስተባባሪ ጽሕፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ሥዩማን ሀብቱ አየነው የእንኳን ደህና መጡ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በአቀባበል ሥነሥርዓቱ ላይ ለተገኙ በብዙ መቶ ሺህ ለሚቆጠሩ ካህናት፣የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ፣ምዕመናንና ምዕመናት"እስራኤልን የሚጠብቅ አይተኛም አያንቀላፋም።" በሚል ርዕስ  ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት ልዑል እግዚአብሔር እንኳን በሰላምና በጤና አገናኘን ካሉ በኋላ ከሦስት አመታት በፊት ለቋሚ ሲኖዶስ አገልግሎት ወደ ጠቅላይ ቤተክህነት በተጓዝኩበት ወቅት በሰሜኑ የአገራችን ክፍል በተቀሰቀሰው ጦርነት ምክንያት መንገድ በመዘጋቱ አገልግሎቴን አጠናቅቄ ወደ አገሬ መመለስ ባለመቻሌ በዚያው ለመቆየት ተገድጃለሁ ብለዋል።ልጆቼ ስትራቡ፣ስትጠሙ፣ስትታረዙ፣ስትሰቃዩና ስትሰደዱአብሬአችሁ ባለመሆኔ እጅጉን ሳዝን፣ሳለቅስና ወደ ፈጣሪሬ ሳለቅስ ከርሜአለሁ።ያለፉትን ሦስት ዓመታትም በጾም፣በጸሎትና በናፍቆት በመቆየት ዳግም የምንገናኝበትን ጊዜ ስናፍቅ ከርሜአለሁ ብለዋል።

በአላማጣና አካባቢው በአጠቃላይም በሰሜኑ የአገራችን ክፍል በተቀሰቀሰው ጦርነት ምክንያት በሞተ ሥጋ የተለዩንን አባቶች፣ካህናት፣ዲያቆናት፣ወንድሞችና እህቶችን ልዑል እግዚአብሔር ነፍሳቸውን ከደጋጎቹ አባቶቻችን ጎን ያኑርልን ካሉ በኋላ ላደረጋችሁልኝ ታሪካዊና ደማቅ አቀባበል ልባዊ ምስጋናዬን እያቀረብኩ ለወደፊቱ በእምነታችሁ ጸንታችሁ፣አንድነታችሁን አጽንታችሁ እኔድትኖሩ አባታዊ መልዕክቴን አስተላልፋለሁ በማለት ቃለ ምዕዳንና ቡራክፌ ሰጥተው የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል።

በብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የአቀባበል ሥነሥርዓት ዙሪያ ዝርዝር መረጃዎችን ለማድረስ በአካባቢው ኢንተርኔት ባለመኖሩ ምክንያት በፎቶግራፍ የተደገፈ መረጃ ለማድረስ ባንችልም ለወደፊቱ የተጠናከረ መረጃ ስናገኝ መረጃውን የምናደርስ መሆኑን ከወዲሁ እንገልጻለን።

ምንጭ፦ የኢኦቲቤ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ
#ጥምቀት

" በተለያዩ ማኅበራዊ ሚዲያዎች እየተላለፈ ያለውን የበዓል አከባበር ክልከላን የሚገልጹ የሐሰት ዜናዎች ቤተክርስቲያንን አይወክሉም " - ብፁዕ አቡነ አብርሃም

በዓለ ጥምቀትን አስመልክቶ የሚተላለፉ መልእክቶች የቤተክርስቲያንን አስተምህሮ ላይ ብቻ ያተኮሩ እንዲሆኑ ብፁዕ አቡነ አብርሃም የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የባህር ዳርና የሰሜን ጎጃም አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ መመሪያ አስተላልፈዋል።

ብፁዕነታቸው በተለያዩ ቋንቋዎች ለተለያዩ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ቃለ መጠይቅና ምላሽ እንዲሰጡ ለተመረጡ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን በሰጡት አባታዊ መመሪያ የቅድስት ቤተክርስቲያን መልእክት የሚተላለፈው በማእከል በመሆኑ የማእከሉን መልእክት ብቻ እንዲያስተላልፉ መመሪያ የሰጡ ሲሆን ከግል አስተያየት መቆጠብ እንደሚገባም አበክረው አሳስበዋል።

ቤተክርስቲያኗ የሰላም ሰባኪ እንደመሆኗ መጠን የቤተክርስቲያን መልእክት ሲተላለፍ ሰላም ላይ ማተኮርና በዓል ለማክበር የሚወጡ ምእመናን በዓሉ በሰላም አክብረው እንዲመለሱ መልእክት ማስተላለፍ እንደሚገባ ግልጽ መመሪያ ሰጥተዋል።

ሀገራችን ኢትዮጵያዊ ሁሉም ሃይማኖቶች ተከባብረው የሚኖሩባት ሀገር መሆኗ ከሚገለጽባቸው መንገዶች አንዱ ይህ በዓል የሚከበርባቸውን ቦታዎች ለማጽዳትና ሥርዓት ለማስከበር ጥረት እያደረጉ ያሉ የሌሎች ሃይማኖት አባላትን በአባትነት ያመሰገኑት ብፁዕነታቸው ታቦታቱ በሚያልፉባቸው መንገዶች የሚገኙ የሌሎች ቤተ እምነቶችን ማክበር እንደሚገባ ለሁሉም ካህናትና ምእመናን አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።

በተለያዩ ማኅበራዊ ሚዲያዎች እየተላለፈ ያለውን የበዓል አከባበር ክልከላን የሚገልጹ የሐሰት ዜናዎች ቤተክርስቲያንን የማይወክሉና ቤተክርስቲያናችን በዓሉን በሰላም ለማክበር ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር እያደረገች ያለውን ጥረት ከግንዛቤ ያላስገባ መሆኑን ብፁዕነታቸው አሳውቀዋል።

#EOTCTV

@tikvahethiopia
ብፁዕ አቡነ ሄኖክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በዓለ ጥምቀትን አስመልክቶ በሀገረ ስብከታቸው ጽ/ቤት መግለጫ ሰጥተዋል !

ጥር 8 ቀን 2016 ዓ.ም (ተ.ሚ.ማ/አዲስ አበባ)

+++

ብፁዕ አቡነ ሄኖክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በዓለ ጥምቀትን አስመልክቶ በሀገረ ስብከታቸው ጽ/ቤት መግለጫ ሰጥተዋል !

የብፁዕነታቸው ሙሉ መግለጫ ከዚህ እንደሚከተለው ቀርቧል።

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

“ ወኪያነኒ ይእዜ ያድኅነነ በአርኣያሁ በጥምቀት ።” ጥምቀት ምሳሌ ሆኖ አሁን ያድነናል ። 1ኛ ጴጥ 3፥ 21

በመላው ዓለም የምትገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልጆች ምእመናንና ምእመናት
የሰላም አለቃ ፣ የዘለዓለም አባት ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን በሰላም ጠብቆ ለ2016 ዓ.ም በዓለ ጥምቀት በጤና አደረሰን አደረሳችሁ።

የጥምቀት በዓል ነጻነታችን የታወጀበት ፣ የዕዳ ደብዳቤያችን የተፋቀበት የባርነት ቀንበር የተሰበረበት ፣ የሚናፈቀው የእግዚአብሔር ድምፅ የተሰማበት ፣ ምሥጢረ ሥላሴ የተገለጠበት ፣ ልጅነትን የምንቀበልበት ጸጋ የተመሠረተበት ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከዘጠኙ ዐበይት በዓላት መካከል አንዱ በመሆኑ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በልዩ ድምቀት ይከበራል።

ይኸውም በመዲናችን አዲስ አበባ ከተማ የቅዱስ ሲኖዶስ ርዕሰ መንበር እና ታላቁ አባታችን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በተገኙበት በጃን ሜዳ ባሕረ ጥምቀት የሚከበረው በዓል እንደተጠበቀ ሆኖ በጠቅላላ በከተማዋ ውስጥ ከ78 ያላነሱ የጥምቀት በዓል ማክበሪያ ሥፍራዎች ይገኛሉ። በዚህም መሠረት በዓሉ በተቀናጀ መልኩ ለማስኬድ ሲባል በእያንዳንዱ ክ/ከተማ ላይ ግብረ ኃይል በማደራጀት እና ተጠሪነታቸውንም ለሃገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ በማድረግ በሰፊው ዝግጅት ተደርጓል በየባሕረ ጥምቀቱም በብዙህ ሺህ የሚቆጠሩ ምእመናን ይሳተፉበታል።

ሀገረ ስብከቱም በዓሉ በሰላም እንዲከበር ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን ያካሄደውን ሰፊ ዝግጅት አጠናቅቋል።

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን
ምእመናንና ምእመናት

ሰላም የጌታ ድንቅ ስጦታ እንደሆነና ደግሞም ማንም እንዳይወስድብን አጽንተን ልንይዘው የሚያስፈልገን የሁሉም መሠረት ነው ፣ ሰላም ከሌለ በዓላትን ማክበር ይቅርና ወጥቶ መግባት ፣ ሠርቶ መብላት የማይቻልበት ሁኔታ ሊፈጠር እንደሚችል መገመት ብቻ ሳይሆን ከጥቂት ዓመታት በፊት በተግባር ያየነው መሆኑ ሊዘነጋ አይገባም።

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ሰላምን በማስጠበቅ ረገድ እና ለሰላም ዘብ በመቆም ቀዳሚ መሆኗ ይታወቃል።

ከላይ እንደተገለጸው በሰላም አምላክ የተመሰረተን እና የተሰጠን ጸጋ ማስጠበቅ የእያንዳንዱ አማኝ ግዴታ ነው። እንዲሁም የጥምቀት በዓል የአደባባይ በዓል እንደመሆኑ መጠን ሰላምን የመጠበቅ እና የማስጠበቅ ድርሻ በእያንዳንዳችን ላይ እንዳለ በመገንዘብ ሐዋርያዊት ፣ ብሔራዊት እና ዓለምአቀፋዊት ለሆነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሚመጥን መልኩ በዓሉን ማክበር ያስፈልጋል።

ስለሆነም ይህንን በዓል በምናከብርበት ወቅት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወልንን ሰላም በመንከባከብ እና በመተግበር ፍፁም ክርስቲያናዊ በሆነ ሥነ ምግባር እና አካሄድ በዓላችንን ልናከብር ይገባናል።

ይህ በእንዲህ እያለ
1. መንፈሳዊ ሰልፋችን ከነአለባበሳችን የጉዞውን ቅደም ተከተል በጠበቀ መልኩ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ማዕከል ያደረገ እና ለበዓሉ ድምቀት የሚሰጥ እንዲሆን

2. ወደ ባሕረ ጥምቀቱ የሚደረገው ጉዞ የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ፤ ከልዕልና ወደ ትህትና መውረዱን የሚያሳይ መንፈሳዊ እሴት ያለበት እንደሆነ የታወቀ በመሆኑ በጉዞው ላይ የሚደረግ እያንዳንዱ ክንውን አስተማሪ ሊሆን ይገባል። ሰልፉም ውበትና መስመር እንዲኖረው ይጠበቃል። በመሆኑም የአምልኮ መርሐግብር እያከናወኑ ዋዛ ፈዛዛ በመከወን የሚደረግ ጉዞ ከቤተ ክርስቲያናችን ቀኖና ጋር ፈጽሞ የሚጣረስ በመሆኑ በተለይ ወጣቶች በዚህ ረገድ ከካህናት አባቶች የሚሰጡ መመሪያዎችን በመቀበል የበዓሉን አከባበር በደመቀ መልኩ ማከናወን እንዲቻል እንዲደረግ።

3. ሰዓትን በተመለከተ ጥር 10 ቀን 2016 ዓ.ም ታቦታተ ምሥዋዕ ከመንበረ ክብር ስለሚነሱበት ሰዓት በወጣው መርሐ ግብር መሠረት ከጠዋቱ 4:00 ሰዓት ዋዜማ ስብሐተ እግዚአብሔር ይቆማል። በማስቀጠል 7 ሰዓት ሲሆን በመላዋ አዲስ አበባ አብያተ ክርስቲያናት ለ10 ደቂቃ የደወል ድምፅ ይሰማና መነሻ ሰዓት ይሆናል።

- የጥር 11 የጥምቀት በዓልና የጥር 12 የቃና ዘገሊላ በዓልን በተመለከተም መነሻ ከጠዋቱ 3:00 ሰዓት እንዲሆንና መድረሻውም ከ 7 - 10 ሰዓት ባለው ጊዜ እንዲሆን እያሳሰብን በዓሉ የትህትና እና የፍቅር እንደመሆኑ መጠን ከእኛ የሚጠበቁ ክንውኖችን በመፈፀም ለበዓሉ በድምቀት መከበር አስተዋጽኦ ልናደርግ ይገባል።

4. አገልግሎታችን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የተከተለ መሆን ስለሚገባው አስፈላጊውን ግብዓት ከማቅረብ በቀር ከአበው ካህናት ውጭ በየትኛውም መልኩ በሌሎች አካላት የሚደረግ ማዕጠንት ተገቢነት የሌለው እና ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጭ በመሆኑ እንዳይፈፀም የሚመለከታቸው አካላትም ተገቢውን ክትትል እንዲያደርጉ እንዲሁም በማዕጠንት አገልግሎቱ በካህናት አባቶች በሰፊው እንዲሰጥ ይሁን።

5. በረከተ ጥምቀቱን የማድረስ እና የመርጨት ክንውን የሚፈጸመው በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መሠረት በካህናት ብቻ መሆኑ ይታወቃል በዚሁ መሠረት ቀኖና ቤተ ክርስቲያን ባለማወቅ ምክንያት ሥርዓቱ እንዳይፈርስ ወጣት ልጆቻችንም ይህን አውቃችሁ ሥርዓቱን እንድትጠብቁና አገልጋዮች ካህናትም ድርሻችሁን እንድትወጡና ሕዝቡን እንድታገለግሉ እናሳስባለን ።

6. ከልክ ያለፉ እና በተደጋጋሚ የተስተዋሉ ከሥርዓት ውጭ በሆነ መልክ ለታቦታቱ ክብር በማይመጥኑ ሥፍራዎች ላይ እንዲቆሙ የሚደረገው ልምድ እንዲታረምና ሁሉም በሕግና በሥርዓት እንዲመራ።

7. ምእመናን እንደተለመደው ራሳችሁን ከሁከትና አላስፈላጊ ነገሮች በማራቅ በትዕግሥት እና በሆደ ሰፊነት በዓሉን እንድናከብር እያሳሰብን ችግሮች ቢፈጠሩ እንኳን ከሚመለከታቸው የጸጥታ አካላት ጋር በመቀናጀት በተናበበ መልኩ እልባት እንዲሰጣቸው ሊደረግ ይገባል።

በመጨረሻም ፦

በዓለ ጥምቀትን ስናከብር በፍፁም ወንድማዊ ፍቅር የተራቡትን በማብላት ፣ የተጠሙትን በማጠጣት ፣ የታረዙትን በማልበስ በተለያዩ ምክንያቶች ከቀያቸው የተፈናቀሉ ወገኖችን በመርዳትና በመደገፍ ፤ የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ትህትና አብነት በማድረግ በመተሳሰብና በመደጋገፍ እንዲሆን እናሳስባለን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይባርክ አሜን

ብፁዕ አቡነ ሄኖክ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

ጥር 8 ቀን 2016 ዓ.ም አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ
#AddisAbaba

ዝግ የሚሆኑ መንገዶች ይፋ ተደርገዋል።

የከተራና የጥምቀት በዓልን ተከትሎ የትራፊክ መጨናነቅ እንዳይኖር ለትራፊክ ዝግ የሚደረጉ መንገዶችን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታውቋል።

በጥምቀት በዓል በርካታ ህዝብ ታቦታትን አጅቦ ከተለያዩ ቤተ-ክርስቲያናት ወደ ጥምቀተ ባህር የሚንቀሳቀስ በመሆኑ በትራፊክ ፍሰቱ ላይ መጨናነቅ እንዳይፈጠር ታቦታቱ በሚጓዙባቸው መንገዶች ተሽከርካሪዎችን ለአጭርም ሆነ ለረጅም ሰዓታት አቁሞ መሄድ የተከለከለ ሲሆን በተለይም በርካታ ህዝብ በሚታደምበት በጃን ሜዳ ከጥር 10 ቀን 2016 ዓ/ም ጀምሮ ታቦታት ወደ መንበረ ክብራቸው እስኪመለሱ መንገዶቹ ለተሸከርካሪዎች ዝግ እንደሚደረጉ የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታውቋል፡፡

በዚህም መሰረት ፡-

- ከ6ኪሎ አደባባይ እስከ 3ተኛ ሻለቃ ፈረንሳይ ለጋሲዬን መንገድ

- ከ3ኛ ሻለቃ አደባባይ በምንሊክ ሆስፒታል እስከ ቀበና አደባባይ

- ከምንሊክ ሆስፒታል እስከ 6 ኪሎ ታክሲ ተራ

- ከቅድስተ ማርያም ቤ/ክርስቲያን እስከ 6 ኪሎ፣

- ከ6ኪሎ እስከ መነን፣

- ከሀምሌ 19 እስከ ግብፅ ኢምባሲ፣

- ከቅድስተ ማሪያም መነጸር ተራ እስከ ጃንሜዳ፣

- ከግንፍሌ ድልድይ ምንሊክ ሆስፒታል ውስጥ ለውስጥ፣

- ከግንፍሌ መገንጠያ ምንሊክ ሆስፒታል ፊት ለፊት፣

- ከምንሊክ ሆስፒታል የኋላ በር እስከ ቤላ መገንጠያ ድረስ፣ መንገዶቹ ለተሽከርካሪ ዝግ ይሆናሉ።

በዓሉ እስከሚጠናቀቅ ድረስ በጃን ሜዳና በዙሪያው ተሽከርካሪ አቆሞ መሄድ ፍፁም የተከለከለ መሆኑን ፖሊስ እየገለፀ አሽከርካሪዎች የትራፊክ ፖሊስ አባላትን ትእዛዝ በመቀበል የድርሻቸውን እንዲወጡ ጥሪ ቀርቧል።

#AddisAbabaPolice
የ2016 ዓ.ም የከተራ በዓል በደመቀ መልኩ በመከበር ላይ ይገኛል
2024/09/30 02:17:08
Back to Top
HTML Embed Code: