Telegram Web Link
† እንኳን ለቅዱስ ጢሞቴዎስ ሐዋርያ: እና ጻድቅ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቅዱስ ጢሞቴዎስ ሐዋርያ †††

††† ይህ ቅዱስ ሐዋርያ አንድ የቤተ ክርስቲያናችን መብራት ነው:: ወደ ክርስትና የመጣው በ40ዎቹ ዓ/ም አካባቢ ሲሆን አሳምኖ ለቅድስና ያበቃው ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ዻውሎስ ነው::

በጊዜውም በነበረው ትጋትና ተጋድሎ ፍሬ አፍርቷል:: ሆዱንም እጅግ ያመው ነበር:: ቅዱስ ዻውሎስ ሲጠራው "የምወድህ ልጄ" እያለ ነበር:: በኤፌሶንም ዽዽስናን ሹሞ 2 መልዕክታትን ልኮለታል:: ቅዱስ ጢሞቴዎስ ቤተ ክርስቲያንን ለብዙ ዘመናት አገልግሎ በሰማዕትነት ዐርፏል::

ከሐዋርያው ቅዱስ ጢሞቴዎስ በረከትን እንሳተፍ ዘንድ ጊዜ ካለን ቅዱስ ዻውሎስ ለልጁ ጢሞቴዎስ ከላካቸው መልዕክቶች ጥቂት እናንብብ::

††† ቴዎዶስዮስ †††

††† በዚህ ስም የሚጠሩ ብዙ አበው አሉ:: ሰማዕታትም: ጻድቃንም: ሊቃውንትም: ነገሥታትም ተጠርተውበታልና:: ዛሬ የምናከብረውም ቴዎዶስዮስ ዘየዓቢ (ታላቁ) የሚባል ሲሆን ይህን የምንለው ከትንሹ ቴዎዶስዮስ (የልጅ ልጁ ነው) ለመለየት ነው::

ታላቁ ቴዎዶስዮስ በሮም የነገሠው በ370 ዓ/ም አካባቢ ሲሆን ከነ ቤተሰቡ ክርስቲያን ነበር:: እነዚህ ነገሮቹ ደግሞ በቤተ ክርስቲያን እንዲታሰብ አድርጐታል:-
1.በዓለም ታሪክ ክርስትና በሮም ግዛት ሁሉ ብሔራዊ ሃይማኖት እንዲሆን አውጇል::
2.የቤተክርስቲያንን ትልቁን 2ኛ ጉባኤ ቁስጥንጥንያን በ381 (373) ዓ/ም አሰናድቷል::
3.ከበጐነቱ የተነሳ የተቀደሱ ልጆችን አፍርቷል:: ሙሽራው ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ: ቅዱስ አኖሬዎስ: ቅዱስ አርቃዴዎስ እና ቅድሰት ታኦድራ ልጆቹ ሲሆኑ አቡነ ኪሮስ ትንሽ ወንድሙ ናቸው::

ጻድቁ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ በ390 ዓ/ም አካባቢ ዐርፏል::

††† አምላከ ቅዱሳን ስለ አባቶቻችን ሲል ይማረን:: ከበረከታቸውም ይክፈለን::

††† ጥር 23 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ጢሞቴዎስ (ሐዋርያና ሰማዕት-የቅዱስ ዻውሎስ ደቀ መዝሙር)
2.ቅዱስ ጌርሎስ ሰማዕት
3.ቅዱስ አትናቴዎስ ሰማዕት
4.ጻድቅ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ (ዘቁስጥንጥንያ)

††† ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ዳዊት ልበ አምላክ
2.ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት
3.ቅዱስ ሰሎሞን ንጉሠ እሥራኤል
4.አባ ጢሞቴዎስ ገዳማዊ
5.አባ ሳሙኤል
6.አባ ስምዖን
7.አባ ገብርኤል

††† "መድኃኒታችን እግዚአብሔር: ተስፋችንም ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳዘዘው ትእዛዝ የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የሆነ ዻውሎስ: በእምነት እውነተኛ ልጄ ለሆነ ለጢሞቴዎስ::
ከእግዚአብሔር ከአባታችን: ከክርስቶስ ኢየሱስም ከጌታችን: ጸጋና ምሕረት: ሰላምም ይሁን . . ." †††
(1ጢሞ. 1:1)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
† እንኳን ለቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ሐዋርያዊ †††

††† ልደት †††

††† መልካም ዛፍ መልካም ፍሬን ያፈራልና ተክለ ሃይማኖትን
የወለዱት ደጋጉ: ጸጋ ዘአብ ካህኑና እግዚእ ኃረያ ናቸው::
እርሱ በክህነቱ: እርሷ በደግነቷ: በምጽዋቷ ጸንተው ቢኖሩ
እግዚአብሔር ጣፋጭ ፍሬን ሰጥቷቸዋል::

በዳሞቱ ገዢ በሞተለሚ አደጋ ቢደርስባቸው ቅዱስ
ሚካኤል: ጸጋ ዘአብን ከሞት: እግዚእ ኃረያን ከትድምርተ
አረሚ (ከአረማዊ ጋብቻ) አድኗቸዋል:: በኋላም የቅዱሱን
መወለድ አብስሯቸዋል::

ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የተጸነሱት መጋቢት 24 ቀን
በ1206 ዓ/ም ሲሆን የተወለዱት ደግሞ ታኅሣሥ 24 ቀን
በ1207 ዓ/ም ነው:: በተወለዱበት ቀንም ብዙ ተአምራት
ተገልጸዋል:: ቤታቸውም በበረከት ሞልቷል::

††† ዕድገት †††

የጻድቁ የመጀመሪያ ስማቸው "ፍሥሃ ጽዮን" ይሰኛል::
ይሕንን ስም ይዘው: አባታቸው ጸጋ ዘአብን ተከትለው
አድገዋል:: በተለይ ቅዱሳት መጻሕፍትን (ብሉያት:
ሐዲሳትን) ተምረዋል:: በሥጋዊው ጐዳናም ብርቱ አዳኝ
እንደ ነበሩ ይነገራል:: ዲቁናም ከወቅቱ ጳጳስ አባ ጌርሎስ
ተቀብለዋል::

††† መጠራት †††

አንድ ቀን ፍሥሃ ጽዮን ለአደን ወጥቶ ሲያነጣጥር ድንገት
ከሰማይ አስደንጋጭ ድምጽ ተሰማ:: የክብር ባለቤት
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አእላፍ መላእክት እያመሰገኑት
በሚካኤል ክንፍ ተቀምጦ ወረደ::

የወጣቱን አዳኝ ፍርሃቱን አርቆ ጌታችን ተናገረ:: "ከዛሬ
ጀምሮ ስምህ ተክለ ሃይማኖት (ተክለ ሥላሴ) ይሁን::
ከዚህ በኋላ አራዊትን ሳይሆን ነፍሳትን ታድናለህ:: ዘወትር
ካንተ ጋር ነኝ" ብሎ በግርማ ዐረገ:: ቅዱስ ተክለ
ሃይማኖት ከዚህ ጊዜ በኋላ ሰዓትን አላጠፉም::
ንብረታቸውን ለነዳያን በትነው በትር ብቻ ይዘው ቤታቸው
እንደ ተከፈተ ወደ ምናኔ ወጡ::

††† አገልግሎት †††

ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ከጳጳሱ ቅስና ተቀብለው የወንጌል
አገልግሎትን ጀመሩ:: በመጀመሪያ ስብከታቸው እዚያው
ሽዋ (ጽላልሽ) አካባቢ ብቻ በ10ሺ የሚቆጠሩ ሰዎችን
አሳምነው አጠመቁ:: ያን ጊዜ ኢትዮጵያ 2 መልክ ነበራት::

1ኛ. ዮዲት (ጉዲት) በፈጠረችው ጣጣና በእስላሞች
ተጽዕኖ ወደ ደቡብ አካባቢ ያለው ነዋሪ አንድም ሃይማኖቱን
ክዷል: ወይም በባዕድ አምልኮ ተጠምዷል::
2ኛው ደግሞ በዛግዌ ነገሥታት ጥረት ክርስትናና ምናኔ
ተነቃቅቶ ነበር::

ግማሹ ሃገር በጨለመበት ወቅት የደረሱት ሐዲስ ሐዋርያ
አባ ተክለ ሃይማኖት በወጣት ጉልበታቸውና በኃይለ
መንፈስ ቅዱስ ብዙ ቦታዎችን አደረሱ:: ሕዝቡን:
መሣፍንቱን ወደ ሃይማኖት መልሰው: ማርያኖችን
(ጠንቋዮችን) አጥፍተዋል::

††† ገዳማዊ ሕይወት †††

††† ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት በወንጌል ብርሃን ኢትዮጵያን
ከማብራታቸው ባለፈ ገዳማዊ ሕይወትንም አስፋፍተዋል::
እርሳቸው ከሁሉ የተሻሉ ሳሉም በ3 ገዳማት በረድዕነት
አገልግለዋል::

እነዚህም በአቡነ በጸሎተ ሚካኤል ገዳም ለ12 ዓመታት:
በአቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ ገዳም ለ7 ዓመታት: በደብረ
ዳሞ ከአቡነ ዮሐኒ ጋር ለ7 ዓመታት: በአጠቃላይ ለ26
ዓመታት አገልግለዋል::

በአቡነ ኢየሱስ ሞዐ ከመነኮሱ በኋላም ወደ ምድረ ሽዋ
(ዞረሬ) ተመልሰው በአንዲት በዓት ውስጥ ለ22 ዓመታት
ቆመው ጸልየዋል:: በተሰበረ እግራቸውም 6 ጦሮችን
በግራና በቀኝ ተክለው ለ7 ዓመታት ጸልየዋል::

††† ስድስት ክንፍ †††

ኢትዮጵያዊው ጻድቅና ሐዋርያ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት
ከኢትዮጵያ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዘው ከቅዱሳት መካናት
ተባርከዋል:: ጻድቁ ምድረ እሥራኤል የገቡት በየመንገዱ
መንፈሳዊ ዘርን እየዘሩ: እያስተማሩና እያሳመኑ ነበር::

ከወቅቱ ሊቀ ጳጳሳት አባ ሚካኤል ጋርም ተገናኝተው
ቡራኬን ተሰጣጥተዋል:: ዋናው ጉዳይ ግን ከዚህ በኋላ
ነው:: ጻድቁ እመቤታችንና ጌታችን ከጽንሰታቸው እስከ
ዕርገታቸው የረገጧቸውን ቦታዎች ሲመለከቱ በፍጹም
ተደሞ እንባቸው ይፈስ ነበር::

ምክንያቱም እግዚአብሔር ስላበቃቸው ተክለ ሃይማኖት
የሚያዩት ቦታውን አልነበረም:: በገሃድ:-
*በቤተ መቅደስ ብስራቱን
*በቤተ ልሔም ልደቱን
*በቤተ ዮሴፍ ግዝረቱን
*በፈለገ ዮርዳኖስ ጥምቀቱን
*በቤተ አልዓዛር ተአምራቱን ይመለከቱ ነበር::

የጉብኝታቸው የመጨረሻ ክፍል ወደ ሆነው ቀራንዮ
ደርሰው ጌታቸውን እንደ ተሰቀለ ሆኖ ቢመለከቱት
ከዓይናቸው ይፈስ የነበረው ቁጡ እንባ መልኩን ቀየረና
ዓይናቸው ጠፋ::

በዚያች ቅጽበት ስም አጠራሯ የከበረ እመቤታችን ድንግል
ማርያም ፈጥና ደርሳ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ወደ ሰማይ
አሳረገቻቸው::

††† በዚያም:-
*የብርሃን ዐይን ተቀብለው
*6 ክንፍ አብቅለው
*የወርቅ ካባ ላንቃ ለብሰው
*ማዕጠንተ ወርቁን ይዘው
*ከ24ቱ ካህናተ ሰማይም ተደምረው
*ሥላሴን በአንድነቱና ሦስትነቱ ተመልክተው
*"ስብሐት ወክብር ለሥሉስ ቅዱስ ይደሉ" ብለው መንበረ
ጸባኦትን አጥነው ወደ መሬት ተመልሰዋል::

††† ተአምራት †††

የቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ተአምራት እንደ ሰማይ ከዋክብት
የበዛ ነው::
*ሙት አንስተዋል
*ድውያንን ፈውሰዋል
*አጋንንትን አሳደዋል
*እሳትን ጨብጠዋል
*በክንፍ በረዋል
*ደመናን ዙፋን አድርገዋል::

ብዙ ደቀ መዛሙርትን አፍርተው ደብረ ሊባኖስን
መሥርተዋል:: በዚያም ሴትና ወንድ መነኮሳት እንደ
ሕጻናት አብረው ኑረዋል:: በዘመናቸው ሰይጣን
ታሥሯልና::

††† ዕረፍት †††

††† ጻድቅ: ሰማዕትና ሐዋርያ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ብርሃን
ሆነው: መከራን በብዙ ተቀብለው: እልፍ አእላፍ ፍሬን
አፍርተው: በተወለዱ በ99 ዓመት: ከ8 ወር: ከ1 ቀናቸው
ነሐሴ 24 ቀን በ1306 ዓ/ም ዐርፈዋል:: ጌታ: ድንግል
ማርያምና ቅዱሳን ከሰማይ ወርደው ተቀብለዋቸዋል:: 10
ትውልድ የሚያስምር ቃል ኪዳንም ተቀብለዋል::

††† በዚህ ዕለት አባታችን ተክለ ሃይማኖት ለ22 ዓመታት
የቆሙበት ቀኝ እግራቸው መሠበሩንና በአንድ እግራቸው
ለ7 ዓመታት ቆመው መጸለያቸውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን
ታስባለች::

††† ጥር 24 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1አቡነ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት
2.ቅድስት ማርያ ግብጻዊት
3.ታላቁ አባ ቢፋ
4.አባ አብሳዲ ቀሲስ
5.ቅዱሳን ጻድቃነ ሐውዚን

††† ወርኀዊ በዓላት
1.አቡነ ዘዮሐንስ (ዘክብራን ገብርኤል-ጣና)
2.ቅድስት እናታችን ክርስቶስ ሠምራ
3.ቅዱስ ቶማስ ዘመርዓስ
4.ቅዱስ ሙሴ ጸሊም
5.ቅዱስ አጋቢጦስ
6.ሃያ አራቱ ካህናተ ሠማይ

††† "በድካም : አብዝቼ በመገረፍ : አብዝቼ በመታሠር :
አትርፌ በመሞት ብዙ ጊዜ ሆንሁ:: በድካምና በጥረት :
ብዙ ጊዜም እንቅልፍ በማጣት : በራብና በጥም : ብዙ
ጊዜም በመጦም : በብርድና በራቁትነት ነበርሁ . . .
የቀረውን ነገር ሳልቆጥር ዕለት ዕለት የሚከብድብኝ
የአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ አሳብ ነው::" †††
(፪ቆሮ ፲፩፥፳፫)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
† እንኳን ለቅዱሳን አርባ ዘጠኝ አረጋውያን ሰማዕታት ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †

††† አረጋውያን ሰማዕታት †††

††† ሰማዕትነት በክርስትና ለሃይማኖት የሚከፈል የመጨረሻው ዋጋ (መስዋዕትነት) ነው:: ሰው ለፈጣሪው ሰውነቱን ሊያስገዛ: ሃብት ንብረቱን ሊሰጥ ይችላል:: ከስጦታ በላይ ታላቅ ስጦታ ግን ራስን አሳልፎ መስጠት ነው::

ራስን መስጠት በትዳርም ሆነ በምናኔ ውስጥ ይቻላል:: የመጨረሻ ደረጃው ግን ሰማዕትነት ነው:: "አማን መነኑ ሰማዕት ጣዕማ ለዝ ዓለም: ወተዓገሡ ሞተ መሪረ በእንተ መንግስተ ሰማያት" እንዳለው ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ ሰማዕትነት ማለት መራራውን ሞት ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር ሲሉ መታገስ ነው::

እርሱ ቅሉ መድኃኒታችን ክርስቶስ የሰማይና የምድር ጌታ ሲሆን ኃፍረተ መስቀልን ታግሦ ሙቶልን የለ! በዓለም ያሉ ብዙ እምነቶች ስለ መግደል በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ያስተምራሉ:: ክርስትና ግን መሞትን እንጂ መግደልን የሚመለከት ሕግ የለውም::

እርሱ ባለቤቱ "ጠላቶቻችሁን ውደዱ: የሚረግሟችሁን መርቁ: ስለሚያሳድዷችሁ ጸልዩ" ብሎናልና:: (ማቴ. 5:44) ነገር ግን
ዕለት ዕለት ራሳችንን በሃይማኖትና በምግባር ካልኮተኮትነው ክርስትና በአንድ ጀምበር ፍጹም የሚኮንበት እምነት አይደለምና በፈተና መውደቅ ይመጣል::

በተለይ የዘመኑ ክርስቲያን ወጣቶች ልናስተውል ይገባናል:: የቀደሙ ሰማዕታት ዜና የሚነገረን እንድንጸና ነውና::

የእነዚህ ሰማዕታት ቁጥራቸው 49 ሲሆን አባ ቢስዱራ የሚባል ጻድቅ ሰው 50ኛ ሁኖ ይመራቸው ነበር:: መኖሪያቸው ገዳመ አስቄጥስ (ግብጽ) ሆኖ ዘመኑ 5ኛው መቶ ክ/ዘ ነበር::

ሃምሳውም ሙሉ ዘመናቸውን በምናኔና በቅድስና ፈጽመው በስተእርጅና ደግሞ ሰማዕትነት መጣላቸው:: በ430ዎቹ አካባቢ
የዚያን ጊዜ በርበር ይባሉ የነበሩት አረማውያኑ (የዛሬዎቹ አሕዛብ አባቶች) "ሃይማኖት ካዱ" እያሉ ሰይፍን መዘዙባቸው::

በጊዜው አባ ቢስዱራ በማረፉ ሃላፊነቱን የወሰዱት አባ ዮሐንስ ከአርባ ስምንቱ ባልንጀሮቻቸው ጋር ተስማምተው በበርበር እጅ ሰማዕትነትን ተቀብለዋል:: ከንጉስ ቴዎዶስዮስ (ትንሹ) ተልኮ የነበረ አንድ ክርስቲያንም በፍቅረ ክርስቶስ ተስቦ ከወጣት ልጁ ጋር ተሰይፏል:: የብርሃን አክሊልም ለሃምሳ አንዱም ወርዷል::

††† አምላከ ቅዱሳን ከተከፈተ ገነት : ከተነጠፈ ዕረፍት በቸርነቱ ያድርሰን::

††† ጥር 26 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.አርባ ዘጠኝ አረጋውያን ሰማዕታት (ግብጽ ገዳመ አስቄጥስ ውስጥ)
2.ቅድስት አንስጣስያ (በ5ኛው መቶ ክ/ዘ ከቁስጥንጥንያ ወደ ግብጽ ወርዳ ፡ ንግሥናን ንቃ በበርሃ ስትጋደል የኖረች ቅድስት
እናት ናት::)
3.ቅዱስ ዮሴፍ (መፍቀሬ ነዳያን)
4.አባ ጽሕማ (ከተስዓቱ ቅዱሳን)

††† ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ
2.አቡነ ሐብተ ማርያም ኢትዮጵያዊ
3.አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ
4.አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን

††† "ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ: ወይስ
ጭንቀት: ወይስ ስደት: ወይስ ራብ: ወይስ ራቁትነት: ወይስ ፍርሃት: ወይስ ሰይፍ ነውን? 'ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን:: እንደሚታረዱ በጐች ተቈጠርን' ተብሎ እንደ ተጻፈ ነው:: በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን::" †††
(ሮሜ. ፰፥፴፭-፴፰)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
2024/09/30 21:34:03
Back to Top
HTML Embed Code: