Telegram Web Link
#ራስን_መግዛት (ክፍል-፫)

#መብላትና_መጠጣትን_መግዛት

ብዙ ሰዎች «ዳይት» በሚለው አካሄድ ምግብን ከወትሮው በመቀነስ ራሳቸውን ተቆጣጥረው ክብደታቸውን ይቀንሳሉ፡፡ ይህን የሚደርጉትም ለስኳር በሽታ፣ ለልብ ሕመም፣ ለደም ብዛትና ስብ (ውፍረት) ለመቀነስ ሲሉ ነው:: መንፈሳዊው ስው ግን ምግቡንና መጠጡን የሚቆጣጠረው ለመንፈሳዊ ምክንያቶች ነው፡፡ ይህም ጾምንና መከልከልን ያካትታል፡፡ እርሱ እዚህ ላይ ራሱን የሚገዛው ሥጋውን አድክሞ ለመንፈሱ የትጋት ጊዜ ለመስጠት ነው::

ምግብን አስመልክተን ስንናገር እናታችን ሔዋን ራስዋን መግዛት እንዳልቻለች እናስታውሳለን። እርሷ ራስዋን መግዛት ስላልቻለች የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በመተላለፍ እንዳትበላ ከተከለከለችው ዛፍ ፍሬዋን ቆርጣ በልታለች:: አባታችን አዳምም እንዲሁ ተቀብሎ በልቷል:: በዚህም የመጀመሪያው ኃጢአት ወደ ዓለም ገባ፡፡

እዚህ ላይ ከውድቀት በፊት ቀድሞ የመጣው ስሜትን ለመቆጣጠር አለመቻል ነው:: በመሆኑም የመጀመሪያው ኃጢአት የተፈጸመው ሔዋን እባቡን በመስማቷ ወይም ደግሞ «ዛፉ ለመብላት ያማረ እንደ ሆነና ለዓይንም እንደሚያስጎመጅ ለጥበብም መልካም እንደ ሆነ . . » አይታ ስለጎመጀች ነው:: ዘፍ. 3፥5:: በእርግጥም አንዱ ኃጢአት ወደ ሌላኛው ኃጢአት ስለሚመራ በመጀመሪያ ከስሜት ወደ አሳብ፤ ቀጥሎም ወደ ልብ፤ ከዚያም ወደ ድርጊት ያሸጋግራል፡፡

#ቁጣን_በተመለከተ ...

ይኼኛውን «ነርቭን መግዛት» ልንለው እንችላለን፡፡ እንደ መጽሐፍ ቅዱስ ቃል መንፈሳዊው ሰው ዘወትር ከቁጣ ለመራቅ ይሞክራል:: «...የሰው ቁጣ የእግዚአብሔርን ጽድቅ አይሠራምና።» ያዕ. 1፥20:: እርሱ ንዴት በልቡ ውስጥ መንቀሳቀስ መጀመሩን ሲያውቅ ምላሱንና ነርሹን እንዲቆጣጠሩበት አይተዋቸውም:: ስለሆነም በቁጣ ጊዜ ቃላቱን በሚገባ ለመቆጣጠር እንዲችል ወይ ዝም ማለትን ይመርጣል አሊያም ንግግሩ እንዲዋጥ ያደርጋል፡፡

ከሁሉ በላይ ደግሞ ቁጣን ከልቡ ውስጥ ያባርራል:: በዚህም በሚችለው ሁሉ በቁጣ እንዳይቀጣጠልና ድምፁ ከፍ ብሎ እንዳይወጣ ያደርጋል። በተጨማሪም ገጹን አያጨፈግግም:: በዚህ ጊዜ አኳኋኑ ሁሉ የሐዋርያውን ቃል የተከተለ ይሆናል፡፡ «ሰው ሁሉ ለመስማት የፈጠነ ለመናገርም የዘገየ ይሁን . . » ያዕ. 1፥19:: ለቁጣ የፈጠነ ሰው በጥድፊያ ስለሚወድቅ ብዙ ኃጢአት ይፈጽማል: በተረጋጋ ጊዜ በወሰደው የተሳሳተ እርምጃው አብዝቶ ይጸጸታል። በመጨረሻም መስኮታዊውን መልክ ስለሚያጣ ለብዙዎች የማሰናከያ በቁጣው ውስጥ ድንጋይ ይሆናል።

መንፈሳዊው ሰው በቁጣ ውስጥ እያለ ደብዳቤ አይጽፍም:: ብስጭት ውስጥ እያለም ውሳኔ አይወስንም:: ምናልባት ግን በቁጣ ውስጥ እያለ ደብዳቤ ከጻፈ ተጣድፎ ወደ ፖስታ ቤት አይልከውም ለአንድ ለሁለት ቀን እንዳለ ያስቀምጠዋል:: ከዚህ በኋላ በድጋሚ ያነበውና ወይ ቀዶ ይጥለዋል አለበለዚያም ሌላ ይጽፋል:: ይህን በማድረጉም ይህ ነገር በእርሱ ላይ የኃጢአት መረጃ እንዳይሆንበትና ውጤቱም የማያስደስት ሆና እንዳይቀር ያደርጋል:: በተናደደ ጊዜ ውሳኔዎቹን የሚወስደውም ባለማስተዋል ነው:: እንደነዚህ ዓይነቶቹ ውሳኔዎች «ስሜታዊ ውሳኔዎች» ተብለው ይጠራሉ:: ብዙዎቹ የተሳሳቱና ተገቢ ያልሆኑ ውሳኔዎች ናቸው:: ከዚህ ጋር በተያያዘ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል:: «በነፍስህ ለቁጣ ችኩል አትሁን፤ ቁጣ በሰነፍ ብብት ያድራልና: መክ. 7፥9::

ይቀጥላል....

(#በብፁዕ_አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ
#መንፈሳዊ_ሰው_መጽሐፍ ገጽ 122-128
#በአያሌው_ዘኢየሱስ_የተተረጎመ)
የቤተክርስቲያናችን የሕግ ባለሙያዎች ኮሚቴ አባል
ጠበቃ እና የሕግ አማካሪ አያሌው ቢታኔ ታሠሩ ።
********
ታኅሳስ ፱ ቀን ፳፻ ፲ወ፮ ዓ.ም
"""""""""""""""""""""""""""
አዲስአበባ -ኢትዮጵያ

ጠበቃ እና የህግ አማካሪ አያሌው ቢታኔ የዕለት ችሎት ተከራርክሮ ከፍርድ ቤት ወጥቶ ከባለቤቱ እና ከእህቱ ጋር ሜክሲኮ በሚገኘው ነዳጅ ማደያ ለመኪናው ነዳጅ በመቅዳት ላይ ሳለ ሲከታተሉት በነበሩ በመንግስት የጸጥታ አካላት ተወስዶ የታሠረ መሆኑ ታወቀ።

ጠበቃ አያሌው ቢታኔ በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት በተቋቋመው የሕግ ባለሙያዎች ኮሚቴን በመምራት ሙያዊ ግዴታቸውን በመወጣት ቤተክርስቲያንን ወክለው የሕግ አገልግሎት ሲያበረክቱ ቆይተዋል። በተለይም በቤተክርስቲያናችን ተከስቶ በነበረው ሕገ ወጥ ሢመተ ኤጲስ ቆጶሳት ተከትሎ ሃይማኖታዊ ግዴታቸውን በመፈጸማቸው በተለያዩ ምክንያቶች ከሥራቸው ለተፈናቀሉ ምእመናን በነጻ የሕግ ማማከርና ጥብቅና አገልግሎት በመሥጠት ከፍተኛ አገልግሎት አበርክተዋል።

በተጨማሪም በቅዱስ ሲኖዶስ በሚወጡ ሕጎችና መመሪያዎችን በማርቀቅ ሰፊ አገልግሎት አበርክተዋል።
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ

አሜን

✍️"ችግር ለራሳችን እንድንጸልይ ያነቃቃናል፤ ፍቅር ደግሞ ለሌሎች ሰዎች እንድንጸልይ ያስገድደናል"
📚ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

ቀናችንን በጸሎት እንጀምር

📌 ስንክሳር ዘወርኀ ታኅሣሥ ፱



አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ታኅሣሥ ፱ በዚች ቀን ያለ ደም መፍሰስ ታማኝ የሆነ ቅዱስ አባት አባ በአሚን በሰማዕትነት አረፈ።


❖ እርሱም በደቡብ ግብጽ በእስሙናይን አውራጃ ለሀገረ ቴርሳ አቅራቢያ ከሆኑ ከሐፂብ ተወላጆች ወገን ነው ለአንድ ባለጸጋም በጅሮንድ ሆኖ ሳለ ስለ ንጽሕናውና ስለ ቅድስናው በሁሉ ዘንድ ተወዳጅ ሆነ የባለ ጸጋውም ሚስት አባ በአሚንን እጅግ የምትወደውና የምትተማመንበት ሆነች።

❖ እርሱ ግን የዚህን ዓለም ፍጻሜ አሰበ የባለጸጋውንም አገልግሎት ትቶ ወደ ገዳም ሒዶ መነኰሰ ባለጸጋውም መሔዱን በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ ሚስቱንም ይዞ አባ በአሚን ወዳለበት በአንድነት ሔዱ ወደ እርሳቸው እንዲመለስም ለመኑት እንዲህም አሉት ከአንተ እንለይ ዘንድ ከቶ አንችልም ስለዚህ አንተውህም አሉት።

❖ አባ በአሚንም እኔ ራሴን ብፅዓት አድርጌ ለእግዚአብሔር ሰጥቻለሁ እኮን አላቸው ይህንንም ሲሰሙ ከእርሱ በመለየታቸው እያዘኑ ተትውት ተመለሱ።

❖ ከዚህም በኋላ በአማረ ተጋድሎ ሁሉ ታላቅ ተጋድሎን በመጋደል ብዙ ዘመናት እግዚአብሔርን አገለገለው።

❖ ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ሁኖ ደሙን ሊአፈስ ወዶ ወደ እንዴናው ከተማ ሒደ ብዙዎች ምእመናንም ሲአሠቃዩአቸው አገኛቸው እርሱም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ ጽኑ ሥቃይንም አሠቃዩት ሥጋውን በእሳት ለበለቡ ሕዋሳቱንም ሠነጣጥቀው ከመንኰራኲር ውስጥ ጨመሩት ዳግመኛም በአጋሏቸው የብረት ዘንጎች አቃጠሉት በዚህም ሁሉ ጸና ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ያለ ጉዳት በጤና ያስነሣው ነበር።

❖ እንዲህም እየተሠቃየ ሳለ ጣዖት የሚመለክበት ወራት አለፈና ጻድቅ ቈስጠንጢኖስ ነገሠ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ዲዮቅልጥያኖስ ያሠራቸውን እሥረኞች ሁሉ እንዲፈቷቸው አዘዘ ጌታችንም ለአባ በአሚን ተገለጠና ከሰማዕታት ጋር እንደቆጠረው አስረዳው።

❖ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስም ከእሳቸው ቡራኬ ሊቀበል ሽቶ ከውስጣቸው ሰባ ሁለት እሥረኞችን ወደርሱ ያመጡ ዘንድ አዘዘ አባ ኖብ ከእርሳቸው ጋር በዚያ ነበረ ከእርሳቸውም አንዱ ይህ አባ በአሚን ነው።

❖ ከዚህም በኋላ ከእሥሙናይነረ ውጭ በሆነች ገዳም የሚኖር ሆነ ጌታችንም ታላቅ ጸጋን ሰጥቶት በሽተኞችን ሁሉ የሚፈውሳቸው ሆነ ዜናውም በቦታው ሁሉ ተሰማ።

❖ በዚያም ወራት የሮም ንጉሥ ሚስት የሆነች አንዲት ንግሥት ነበረች እርሷም ከእርሷ ጋር ስለሚኖር የወንጌላዊውን ዮሐንስ የራእዩን መጽሐፍ ሁልጊዜ የሚፈራ ስለ አንድ ዲያቆን እጅግ የታመመች ናት ከንጉሥ ሹሞች አንዱ በቀናበት ጊዜ ወደ ንጉሡ ሒዶ ጌታዬ ንጉሥ ሆይ ዕወቅ ይህ ዲያቆን ዮሐንስ ሁልጊዜ የዮሐንስ የራእዩን መጽሐፍ በማንበብ እያመካኘ ከእመቤቴ ንግሥት ጋር ይተኛል አለው።

❖ ንጉሡም ይህን በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ በዚያንም ጊዜ ተነሥቶ ንግሥቲቱ ወዳለችበት ቤተ መንግሥት ገባ ያንንም ዲያቆን በፊቷ ቁሞ የዮሐንስን የራእዩ መጽሐፍ ሲያነብ አገኘውና ከነመጽሐፉ ወስደው ዲያቆኑን ከባሕር እንዲአሠጥሙት አዘዘ ሁለት ሰዎችም በታናሽ ጀልባ ጭነው ወስደው ከባሕር መካከል ወረወሩት ወዲያውኑ ብርሃንን የለበሰ ሰው ከሰማይ ወርዶ ያንን ዲያቆን ከመጽሐፉ ጋር ነጥቆ ወስዶ ከአንዲት ደሴት ላይ አኖረው እንዚያ ሁለት ሰዎች ሲያዩ ነበር እጅግም እያደነቁ ተመለሱ ያዩትንም ለንጉሡ አልነገሩትም።

❖ ንግሥቲቱም በዲያቆኑ ላይ የተደረገውን በአየች ጊዜ እጅግ አዘነች በእርሷም ደዌ ጸናባት ሆድዋም ቁስሎ ዐሥራ አምስት ዓመት ኖረች ወደርሷም ብዙ ጥበበኞች ባለመድኃኒቶች መጥተው ነበር ግን ሊፈውሷት አልቻሉም አንድ አዋቂ ሰውም እንዲህ ብሎ መከራት በግብጽ አገር ወደሚኖሩ ቅድሳን ብትሔጂ ከደዌሽ በተፈወስሽ ነበር።

❖ በዚያን ጊዜ ተነሣች ከእርሷም ጋር ብዙ ሠራዊት አለ ወደግብጽ አገርም ደርሳ ገዳማቱንና አብያተ ክርስቲያንንም ሁሉ ዞረች ግን አልዳነችም።

❖ ወደ እንዴናው ከተማም በደረሰች ጊዜ ስለ መምጣቷ የአገሩ መኳንንት አደነቁ እርሷም ችግርዋን ሁሉ ነገረቻቸው እነሱም ወደ ቅዱስ አባ በአሚን እንድትሔድ መከሩዋት በመርከብም ተሳፍራ ወዲያውኑ ቅዱስ አባ በአሚን ወዳለበት ገዳም ደረሰች እነሆ ንግሥት ወዳንተ መጥታለች ከአንተም ልትባረክ ትሻለች ብለው ነገሩት እርሱም ከምድር ንግሥት ጋር ምን አለኝ ብሎ መውጣትን እምቢ አለ መነኰሳትም ወደርሷ እንዲመጣ አጽንተው ለመኑትና ወጣ በአየችውም ጊዜ ከእግሩ በታች ወድቃ ሰገደችለት እርሱም በዘይት ላይ ጸልዩ ቀባት በዚያንም ጊዜ ዳነች።


❖ ቅዱስ አባ በአሚንም ንጉሥ ከባሕር በአሠጠመው በዚያ ዲያቆን ምክንያት ይህ ሁሉ እንደደረሰብሽ ዕወቂ እርሱ ግን በአንዲት ደሴት ውስጥ በሕይወት ይኖራል የአቡቀለምሲስ ዮሐንስ የራእይ መጽሐፍም ከእርሱ ጋር አለ አላት።

❖ ንግሥቲቱም ሰምታ እጅግ አደነቀች ደስ አላትም ስለዚያ ዲያቆን በሕይወት መኖርና እርሷም ፈውስ ስለማግኘቷ ለቅዱስ አባ በአሚንም እጅ መንሻ ብዙ ገንዘብ አቀረበችለት ከንዋየ ቅዱሳት በቀር ምንም ምን ገንዘብ አልተቀበለም።


❖ ከዚህም በኋላ እግዚአብሔርን እያመሰገነች ወደ ሮሜ አገር ተመለሰች በእርሷ ላይ የሆነውን ሁሉ ወደ ባሕር ስለ አሠጠሙት ስለዚያ ዲያቆንም እርሱም እስከ ዛሬ በአንዲት ደሴት ውስጥ በሕይወት እንዳለ ለንጉሡ ነገረችው።

❖ ንጉሡም ይህን ነገር ሰምቶ እጅግ አደነቀ ይፈልጉትም ዘንድ መልክተኞችን ላከ በደሴትም ውስጥ በሕይወት አገኙት መጽሐፉም ከርሱ ጋር አለ ተመልሰውም ለንጉሡ ነገሩት ሁለተኛም ወደርሱ እንዲመጣ እየማለደ ላከ ከመልክተኞችም ጋር ወደ ንጉሡ መጣ ንጉሡም በአየው ጊዜ ታላቅ ደስታ አደረገ ከእግሩ በታችም ወድቆ በአንተ ላይ ስለአደረግሁት በደል ይቅር በለኝ አለው እርሱም በአንድነት እግዚአብሔር ይቅር ይበለን አለ።

❖ ከዚህም በኋላ ያ ዲያቆን በሮሜ ሀገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ ያንንም የዮሐንስ አቡቀለምሲስ ራእይ ተረጐመው፤ ቅዱስ አባ በአሚንም በቀንና በሌሊት ያለማቋረጥ የሚጋደል ሆነ።


❖ በአቅራቢያውም አንድ ደግ ኤጲስቆጶስ አለ በአንዲት የሰማዕታት ገዳም ከምእመናን ጋር በዓልን ሲያደርግ አርዮሳውያንም ለራሳቸው ሐሰተኛ ኤጲስቆጶስ ይዘው ሕዝብን የሚያስቱ ሆኑ የሀገሩም ኤጲስቆጶስ ወደ አባ በአሚን መጥቶ ስለ እሊህ ከሀድያን የደረሰበትን ኃዘኑን ሁሉ ነገረው።

❖ የሰማዕታትም በዓል በሆነ ጊዜ የእሊህን ከሀድያን ምክር እግዚአብሔር ይበትን ዘንድ ቅዱስ አባ በአሚን ከሕዝብ ጋር በመለመንና በመስገድ ጸለየ ከዚህም በኋላ የሽመል በትር ያዘ ሕዝቡም ሁሉ እየአንዳዱ በትሮችን ይዘው ወደእነዚያ ከሀድያን ሔዱ ከሀድያንም በአዩ ጊዜ ተበተኑ ወደዚያ ዳግመኛ አልተመለሱም እግዚአብሔር ምክራቸውን በትኖባቸዋልና።
❖ ቅዱስ አባ በአሚንም ፈጽሞ በአረጀ ጊዜ የሞት ደዌን ታመመ መነኰሳቱንም ሁሉ ሰብስቦ ዕድሜው እንደ ቀረበ ነገራቸውና አጽናናቸው እነርሱም ከእርሱ ስለመለየታቸው አዘኑ ከዚህም በኋላ በፈጣሪው እግዚአብሔር እጅ ነፍሱን ሰጠ። መነኰሳቱም እንደሚገባ እያመሰገኑና እየዘመሩ መልካም አገናነዝን ገነዙት ሥጋው በእምነት ወደርሱ ለሚመጣ ሁሉ መጠጊያ ሆነ ወይም በቀናች ሃይማኖት ጸንቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሒዶ በስሙ ለሚለምን ሁሉ የለመነው ይሆንለታል።


ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ጻድቅ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።


✍️ በዚችም ቀን የበድላም የአርምያና የዘካርያስ የዕረፍታቸው መታሰቢያ ነው በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።



📌 ታኅሣሥ 9 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ አባ በአሚን (ጻድቅና ሰማዕት)

2.ቅድስት አርምያ

3.ቅዱስ ዘካርያስ



📌 ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱሳን 318ቱ ሊቃውንት

2.አባ በርሱማ ሶርያዊ (ለሶርያ መነኮሳት ኁሉ አባት)

3.አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ

4.የብሔረ ብፁዐን ጻድቃን

5.አባ መልከ ጼዴቅ ዘሚዳ

6.ቅዱስ ዞሲማስ ጻድቅ
#ራስን_መግዛት (ክፍል - ፬)

#ዶግማና_ትምህርት

መንፈሳዊው ሰው በዶግማና በትምህርት ላይ ራሱን ይገዛል፡፡ እርሱ አዘውትሮ ስለሚያነብ ወደ አእምሮው የገባውን ማንኛውንም ዓይነት አሳብ ለማስፋፋት አይጣደፍም:: ለምሳሌ፦ ቀስ ብሎ ሊያስተምረው ወይም አሳጥሮ ሊጽፈው ወይም ደግሞ መጽሐፍ አድርጎ ሊያሳትመው ይችላል፡፡ አንድ ሰው አንድን አሳብ ከመስጠቱም ሆነ ከመቀበሉ በፊት ወይም ጉዳዩን ለሌሎች ሕሊና ከማስተዋወቁ በፊት ለረዥም ጊዜ ሊያብላላውና ከገዛ ራሱ ሕሊና ጋር ሊወያይበት ይገባል፡፡

በልብህ ውስጥ ያለው አሳብ በአንተ ቁጥጥር ሥር ነው፡፡ ካወጣኸው ወይም ካስፋፋኸው ግን በሌሎች ሰዎች ቁጥጥር ሥር ነው:: ታላቁ አባት ቅዱስ መቃርስ «ወንድሜ ሆይ! ሰዎች በአንተ ላይ ከመፍረዳቸው በፊት በራስህ ላይ ፍረድ!›› ብሎ መናገሩ ምንኛ ትክክል ነው! ምናልባት ይህንን አባባሉን ያገኘው ከሐዋርያው ከቅዱስ ጳውሎስ ሊሆን ይችላል፡፡ «ራሳችንን ብንመረምር ባልተፈረደብንም ነበር . . » 1ኛ ቆሮ. 11፥31። ይህም ማለት መንፈሳዊው ሰው በሌሎች ቁጥጥር ሥር ከመውደቅ ይልቅ ራሱን መቆጣጠር ይመርጣል ማለት ነው፡፡

#ታዛዥነትና_ቃል_መግባት

ራሱ ቃል በመግባት፣ በታዛዥነትና በተሸናፊነት ውስጥ ራሱን ይገዛል፡፡ ምክንያቱም ዛሬ አንዳንድ ሰዎች በነፃነት፣በግል ክብርና በራስ መተማመን ስም ስለ ሥነ ሥርዓት፣ ስለ ወግና ስለ ሕግ ሳይጨነቁ የወደዱትን ስለሚያደርጉ ነው፡፡ በዲሞክራሲ ብናምንም የምናምነው በገደብ ውስጥ ባለ ዲሞክራሲ ነው:: ለዚህ አባባል ወንዝ ጥሩ ምሳሌ ሊሆነን ይችላል፡፡ ወንዝ ከግራና ከቀኙ ባሉት ሁለት ከፍ ያሉ የምድር አካላት ተገድቦ ይፈሳል፡፡ ሰዎች ወንዙን ከሚፈስበት አቅጣጫ በማስቆም ነጻነቱን ሊነፍጉት ባይችሉም አፍሳሹ ወጥቶ የጎርፍ አደጋ እንዳያስከትልና አካባቢውን ረግረግ እንዳያደርግ ግን ሊቆጣጠሩት ይችላሉ፡፡

መንፈሳዊው ሰው ቃሉን ይጠብቃል፤ ግብረገብነትን ያከብራል! ሕግጋትን ያጤናል፡፡ ሌሎች ሰዎችንም እንዲሁ ያከብራል፡፡ ሐዋርያው የተናገረውን ቃል ሳያንገራግር ይቀበላል:: «ለሁሉ የሚገባውን አስረክቡ፤ግብር ለሚገባው ግብርን፣ቀረጥ ለሚገባው ቀረጥን፣ መፈራት ለሚገባው መፈራትን፣ክብር ለሚገባው ክብርን ስጡ።» ሮሜ 13፥7: የራሱን ምኞትና አስተሳሰብ የሚከተለውና ለሥነ ሥርዓት፣ ለበላዩና ለማንም የማይገዛው ሰው ግን መንፈሳዊ ሰው አይደለም፡፡ እርሱ መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረውን ስለማይቀበል ምንም ዓይነት ነገር አይቀበልም።

ታዛዥነትን አስመልክቶ መንፈሳዊው ሰው ራሱን ይገዛል፡፡ እርሱ ለወላጆቹ፣ ለንሥሐ አባቱ፤ ለሥነ ሥርዓት ከመታዘዙም በላይ ለእግዚአብሔርም ፍጹም ታዛዥ ነው:: መታዘዝ ክብሩን እንደማይቀንሰው ይረዳል:: መታዘዝ የትሕትና ምልክት ሲሆን ትሕትና ደግሞ መልካም ባሕርይ ነው፡፡ ለማንም የማይታዘዝ ሰው ሙሉ ለሙሉ የሚታዘዘው ለትዕቢቱና ለአሳቡ መሆኑ እርግጥ ነው፡፡

ይቀጥላል......

(#በብፁዕ_አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ
#መንፈሳዊ_ሰው_መጽሐፍ ገጽ 122-128
#በአያሌው_ዘኢየሱስ_የተተረጎመ)

@beteafework    @beteafework
@beteafework    @beteafework
ስለትሕትና የሚነገሩ ቃላት ሁሉ ምን ያህል የተደነቁ ናቸው!
ትሕትና ሰይጣን እንዲገዛ ('ገ' ጠብቆ ይነበብ) ያደርገዋል። ይህ በታላቁ አባት አባ መቃርዮስ ሕይወት ግልፅ ሆኖ እናገኘዋለን። ሰይጣን ተገልጾ አባ መቃርዮስን እንዲህ አለው " ከአንተ መራቅ እፈልጋለሁ። መቃርዮስ እኛ ማድረግ የምንችለው ነገር ግን አንተ የማታደርገው ምንድን ነው? አንተ ትጾማለህ እኔም እንደ እንተ አልበላም፤ ነቅተህ ትጠብቃለህ እኔም አልተኛም፤ አነተ በበርሃ ብቻህን ትኖራለህ እኔም እንደ አንተ አደርጋለሁ ነገር ግን በእንድ ነገር አሸነፍከኝ" አለው። አባ መቃርዮስም በምን እንዳሸነፈው እንዲነግረው ሰይጣንን ጠየቀው። ሰይጣንም '' በትሕትና አሸነፍከኝ '' አለው። ይህ ግልፅ ነው ሰይጣን ትሑት መሆን አይችልም። ሁልጊዜም ለራሱ ክብር ይሰጣል። ለዚህም ነው ትሕትና ሰይጣንን የሚያሸንፈው። ሰይጣን ገንዘቡ ማድረግ የማይችለውን ትሕትና ቅዱሳን ገንዘባቸው አድርገዋል።

የሚየምኑትን ከማያምኑ ወገኖች፤ የእግዚአብሔር የሆኑ ወገኖችን የእግዚአብሔር ካልሆኑት የሚለያቸው ጥበብ ይሄ ነው። ሰይጣን ገንዘቡን ወዳጅ ነው፤ ማንም ወገን ገንዘቡን ከያዘበት ከእርሱ አይርቅም ስለዚህ የእግዚአብሔር ወገን መሆን ከፈለግህ የሰይጣንን ገንዘቡን መልስለትና የእግዚአብሔር ልጆች የያዙትን ገንዘብ ገንዘብህ አድርግ። የሰይጣን ገንዘቡ ትዕቢት፣ ራስን ማግነን፣ ከንቱ መታበይ ሲሆኑ የእግዚአብሔር ልጆች ገንዘብ ትህትና ነው።

#ብጽእ_አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ
#የሕይወት_መዓዛ ከተባለው መጽሐፍ የተወሰደ
"በወንድሙ ዉድቀት የሚደሰት ሰዉ ተመሳሳይ ዉድቀት ይጠብቀዋል"

ቅዱስ ኤፍሬም
0
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ

አሜን

✍️"ችግር ለራሳችን እንድንጸልይ ያነቃቃናል፤ ፍቅር ደግሞ ለሌሎች ሰዎች እንድንጸልይ ያስገድደናል"
📚ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ

ቀናችንን በጸሎት እንጀምር


📌 ስንክሳር ዘወርኀ ታኅሣሥ ፲፩


አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ታኅሣሥ ዐሥራ አንድ በዚች ቀን የግብጽ ደቡብ ከሆነ ከመጺል አውራጃ ከሬስ ከተማ ሰዎች ወገን የሆነ ቅዱስ አባት አባ በኪሞስ አረፈ።

እርሱም የአባቱን በጎች የሚጠብቅ ነበር ዕድሜውም ዐሥራ ሁለት ዓመት ሲሆነው ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ በጐልማሳ አምሳል ተገለጠለትና በአንድነት ሒደን እንመነኵስ ዘንድ ትሻለህ አለው እርሱም አዎን አለ ሁለቱም ተስማምተው ወደ አስቄጥስ ገዳም በአንድነት ተጓዙ ሦስት አረጋውያን መነኰሳትንም አገኙ አባ በኪሞስም ከእነርሱ ጋር ሃያ አራት ዓመታትን ኖረ።

❖ ከዚህም በኋላ አባ በኪሞስ ከዚያ ተነሥቶ የሦስት ቀን ጐዳና ያህል ተጓዘና ሩቅ ወደ ሆነ በረሀ ውስጥ ገባ ሰይጣናትም በእሪያዎችና በዘንዶዎች አምሳል ሁነው መጡበት ሊነክሱትም አፋቸውን ከፍተው ከበቡት እርሱ ግን የአጋንንትን ሐሳብ አወቀ በእግዚአብሔርም ኃይል እፍ አለባቸው በዚያንም ጊዜ ተበተኑ።

❖ እርሱም ወንዝ አገኘ ሰባት ሰባት ቀን እየጾመ በዚያ ሦስት ዓመት ኖረ በሱባዔውም መጨረሻ በመሀል እጁ ተምር መልቶ ያንን ይመገባል ውኃም በጥቂቱ ይጠጣል ሁለት ሽህ አራት መቶ ጊዜ በሌሊት እንዲሁም በቀን ሁለት ሽህ አራት መቶ ጊዜ አቡነ ዘበሰማያትን ይጸልያል።

❖ ከዚህም በኋላ አርባ አርባ ቀን እየጾመ ሃያ አራት ዓመታት ያህል ኖረ አርባውም ቀን ሲፈጸም አንድ ጊዜ ይበላል ከዚህም በኋላ አንድ ጊዜ ቆዳው ከዐጥንቶቹ ጋር እስቲጣበቅ ሰማንያ ቀን ጾመ በዚያንም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ይበላና ይጠጣ ዘንድ እንጀራና ውኃን አመጣለት ያም ውኃና እንጀራ ሳያልቅ እስከ አረፈ ድረስ ብዙ ዓመታትን ኖረ።


ፈጣሪ እግዚአብሔርም በሌሊት ራእይ ተገልጦ ወደ አገሩ እንዲመለስ አዘዘው በዚያንም ጊዜ ተነሥቶ ሔደ ወደ አገሩም ደርሶ በዚያ ታናሽ ማደሪያ ጎጆ ሠርቶ በውስጡ ብቻውን የሚኖር ሆነ ወደርሱም ለሚመጣ ሁሉ መጠጊያና ወደብ በጎ አለኝታም ሆነ ሰዎችም ሁሉ በትምህርቱ እየተጽናኑ ኖሩ ንጹሕ በሆነ አምልኮቱ በትሩፋቱና በተጋድሎው መንፈሳዊ ቅናትን ይቀኑበት ነበር።


❖ በአንዲት ዕለትም ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ተሸክሞ ወደ ኤፍራጥስ ምድር አደረሰው የዚያ አገር ሰዎች በመተላለፍ ከእውነተኛ ሃይማኖት ወጥተው ነበርና ሁሉንም ወደ ቀናች ሃይማኖትና ወደ በጎ ምግባር መለሳቸው ከዚያም ወደ ቦታው ተመለሰ።


❖ አንድ ጊዜም ሽጦ ምግቡን ያገኝ ዘንድ አገልግሎችን ተሸክሞ ወደ ከተማ ሲሔድ በጎዳና ላይ ደክሞት አገልግሎቹን አስቀምጦ ጥቂት ያርፍ ዘንድ ተቀመጠ በዚያንም ጊዜ ከአገልግሎቹ ጋር የእግዚአብሔር ኃይል ተሸክሞ ወደሚሻው ቦታ አደረሰው።



❖ በዚያንም ወቅት አባ ሲኖዳ ከፍተኛ የዕንቈ ባሕርይ ምሰሶ በራእይ አየና ይህ ታላቅ ምሰሶ ምንድን ነው ብሎ ደነገጠ የእግዚአብሔርም መልአክ ተገልጦ ይህ አባ በኪሞስ ነው አለው።

❖ አባ ሲኖዳም ወዲያውኑ ተነሥቶ ወደ አባ በኪሞስ አገር እስቲደርስ በእግሩ ተጓዘ ከዚያችም ቀን በፊት ከቶ አላየውም ነበር በተገናኙም ጊዜ እርስበርሳቸው ሰላምታ ተሰጣጡ።


❖ አባ በኪሞስም ወጥ ሊአበስል ወደደ አባ ሲኖዳንም ይቺን እንስራ ያዛትና ሔደህ ውኃ ቀድተህ መልተህ አምጣልኝ አለው በዚያንም ጊዜ አባ ሲኖዳ ተነሣና ያቺን እንስራ ተሸከማት ውኃውንም ቀድቶ መልቶ አመጣለት ወጡንም ፈልቶና በስሎ አገኘው በዚያንም ጊዜ አባ በኪሞስ መሆኑን አወቀ ከእርሱም ጋር ሰላምታን ደገመ እጅ በመነሣሣትም ሰላምታ ተለዋወጡ፤ ከዚህም በኋላ አባ ሲኖዳ ስለርሱ ያየውን ራእይ ነገረው በእርሱም ዘንድ ጥቂት ቀኖች ኖረ።



❖ ዳግመኛም በአንዲት ቀን በአንድነት ሲጓዝ የሞተ ሰው ራስ አገኙ አባ ሲኖዳም በበትሩ ነቅነቅ አደረገውና ምውት ሆይ ያየኸውን ትነግረንና ታስረዳን ዘንድ ተነሣ አለው በዚያን ጊዜ ነፍሱ ወደ ዐፅሙ ተመልሳ ሥጋ ለብሶ ተነሣና ሰገደላቸው በሲኦል የሚሠራውንም ሁሉ በየወገናቸውም በውስጧ የሚሠቃዩትን እርሱም አረማዊ እንደሆነ ነገራቸው።

❖ እንዲህም አለ ክብር ይግባውና በጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ያመኑ ትእዛዙን ግን ያልጠበቁ በአሕዛብ ሥራና በአረማውያን ርኵስት የኖሩ ከእኛ በታች የሚኖሩ ክርስቲያኖች አሉ አለ ቅዱሳንም ተመልሰህ ተኛ አሉት ወዲያውኑ እንደ ቀድሞው ሆነ።



❖ ከዚህም በኋላ አባ ሲኖዳ ቅዱስ በኪሞስን ተሰናብቶ ወደ ቦታው ተመለሰ። ዕረፍቱም በቀረበ ጊዜ ቅዱስ አባ በኪሞስ አገልጋዩን ጠርቶ በኖረበት ቦታ ሥጋውን እንዲቀብር አዘዘው።

❖ ከዚህም በኋላ በሆድ ዝማ ሕመም ጥቂት ታመመ፤ ቅዱሳንን በአንድነት ወደርሱ ሲመጡ አያቸው በዚያንም ጊዜ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ፤ መላእክትም ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት እስከአደረሷት እያመሰገኑና እየዘመሩ አሳረጓት፤ መላ ዕድሜውም ሰባ ዓመት ሆነ ዐሥራ ሁለት ዓመት በዓለም ውስጥ ሃምሳ ስምንት ዓመት በምንኵስና ሥራ ኖረ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ አባት ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።



📌 በዚችም ቀን የኤጲስቆጶሱ በርተሎሜዎስና የሰማዕቱ በጥላን መታሰቢያቸው ነው በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።


📌 ታሕሳስ 11 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ታላቁ አባ በኪሞስ

2.ቅዱስ በርተሎሜዎስ

3.ቅዱስ ቴዎድሮስ

4.ቅዱስ በጥላን



📌 ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ያሬድ ካህን

2.ማር ገላውዴዎስ ሰማዕት

3.ቅዱስ ፋሲለደስ ሰማዕት

4.አቡነ ሐራ ድንግል ጻድቅ

5.ቅድስት ሐና ቡርክት
Daniel:
✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ አምላክ፡፡ አሜን፡፡ ✞✞✞

=>+"+ እንኩዋን ለታላቁ "ጻድቅና ገዳማዊ አባ በኪሞስ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ +"+

+*" ታላቁ አባ በኪሞስ "*+

=>በቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ "ታላቁ : ዓቢይ : (THE GREAT)" የሚል ስም የሚሰጣቸው አባቶች የተለዩ ናቸው:: አንድም እጅግ ብዙ ትሩፋቶችን የሠሩ ናቸው:: በሌላ በኩል ደግሞ በተመሳሳይ ስም ከሚጠሩ ሌሎች ቅዱሳን እንለይበታለን::

+ገዳማዊ ሕይወት ጥንቱ ብሉይ ኪዳን ነው:: በቀዳሚነትም በደብር ቅዱስ አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ደቂቀ ሴት እንደ ጀመሩት ይታመናል:: ሕይወቱ በጐላ: በተረዳ መንገድ የታየው ግን በታላቁ ጻድቅ ሄኖክ: ከዚያም በቅዱሱ ካህን መልከ ጼዴቅ አማካኝነት ነው::

+ቀጥሎም እነ ቅዱስ ኤልያስ ነቢይ : እነ ኤልሳዕ ደቀ መዝሙሩ ኑረውበታል:: በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ሙሉ ሕይወቱን በገዳም (በበርሃ) ያሳለፈው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቅድሚያውን ይይዛል::

+ለስም አጠራሩ ስግደት ይሁንና መድኃኒታችን ክርስቶስ በገዳመ ቆረንቶስ ለ40 ቀናት በትሕርምት ኑሮ ገዳማዊ ሕይወትን ቀድሷል:: አስተምሯል:: በዘመነ ስብከቱም ያድርባት የነበረችው የደብረ ዘይቷ በዓቱ (ኤሌዎን ዋሻ) በራሷ ለዚህ ሕይወት ትልቅ ማሳያ ናት::

+ከጌታ ዕርገት በሁዋላም ክርስቲያኖቹ የዓለም ሁካታ ሲሰለቻቸው: አንድም በንጹሕና በተሸከፈ ልቡና ለፈጣሪያቸው መገዛትን ሲሹ ከከተማ ወጣ እያሉ ይኖሩ እንደ ነበር የታሪክ መዛግብት ያሳያሉ:: አኗኗራቸውም በቡድንም: በነጠላም ሊሆን ይችላል::

+ዋናው ነገር ግን በጾምና በጸሎት መትጋታቸው ነው:: ይሕም ሲያያዝ እስከ 3ኛው መቶ ክ/ዘመን ደረሰ:: በዚህ ዘመን ግን አባ ዻውሊ የሚባል አንድ ንጹሕ ክርስቲያን ይሕንን ሕይወት ወደ ሌላ ደረጃ ከፍ አደረገው:: ለ80 (90) ዓመታት ሰው ሳያይ ተጋድሎ "የባሕታውያን አባት" ተባለ:: ደንብ ያለው ተባሕትዎም ጀመረ::

+ይህ ከሆነ ከ20 ዓመታት በሁዋላ ደግሞ አባ እንጦንስ የሚባሉ ደግ ክርስቲያን ይህንን ገዳማዊ ሕይወት በሌላ መንገድ አጣፈጡት:: በቅዱስ ሚካኤል አመንኩዋሽነት ገዳማዊ ሕይወት በምንኩስና ተቃኘ:: ስለዚህም አባ እንጦንስ "የመነኮሳት አባት" ተባሉ::

+እርሳቸውም ሕይወቱን ለማስፋፋት ከተለያዩ አሕጉር ደቀ መዛሙርትን እየተቀበሉ አመንኩሰዋል:: ቅዱሳን የአባ እንጦንስ ልጆችም ወደየ ሃገራቸው ተመልሰው: ሕይወቱን በተግባር አሳይተው ገዳማዊነትን አስፋፍተዋል::

=>አባ በኪሞስ ስም አጠራሩ እጅግ የከበረ: ሽምግልናው ያማረ ባሕታዊ: መነኮስና ሐዋርያዊ አባት ነው:: የነበረው በዘመነ ጻድቃን (በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን) ሲሆን ትውልዱ እንደ ብዙዎቹ የወቅቱ ቅዱሳን በላይኛው (በደቡብ) ግብጽ ነው::

+አባ በኪሞስ ከክርስቲያን ወላጆቹ ተወልዶ: በልጅነቱ ክርስትናን አጥንቶ በእረኝነት ተሰማራ:: በጐቹን ሲጠብቅም የእግዚአብሔር ጥሪ ወደ እርሱ መጣ:: ያኔም እድሜው ገና 12 ዓመት ነበር::

+አጠራሩም እንዲህ ነው:: በእረኝነት ሳለ መልአከ እግዚአብሔር ሰው መስሎ መጥቶ ተገናኘው:: ቁጭ ብሎም ስለ መናንያን ክብር ሲያጫውተው ከዋለ በሁዋላ "ለምን እኔና አንተ ለዚህ ክብር እንድንበቃ አንመንንም?" ሲል ጠየቀው::

+ሕጻኑ በኪሞስም ደስ ብሎት "እሺ!" አለው:: ወዲያውም መንጋውን ለወላጆቹ መልሶ ከመልአኩ ጋር ወደ ገዳም ሔዱ:: ቅዱሱ መልአክም በመንገድ ሳሉ ብዙ ምሥጢራትን ነገረው:: አጸናው:: ረድኤተ እግዚአብሔርንም አሳደረበት::

+ልክ ወደ አንድ ገዳም ሲደርሱ ግን ተሰወረበት:: ቅዱስ በኪሞስም ወደ ገዳሙ ገብቶ ይምናኔ ሕይወትን ጀመረ:: በዚያም እንደ ልጅነቱ አበውን እያገለገለ: ሥርዓተ ገዳምን: ትሕርምትን: አርምሞንና ተጋድሎን በደንብ አጠና::

+በዚያው ገዳም ሳለም ምንኩስናን ተቀበለ:: ለ24 ዓመታት አገልግሎ 36 ዓመት በሞላው ጊዜም ተባሕትዎን ተመኘ:: ከአባቶች ዘንድ ተባርኮም ጭው ወዳለው በርሐ እየዘመረ ተጉዋዘ::

+አንዲት ቦታ ላይም የቀኑን ሐሩር: የሌሊቱን ቁር ሳይሰቀቅ ለ3 ዓመታት ጸለየ:: እድሜው 39 ዓመት ሲሆን እንደ ገና ጭራሽ ፍጥረት ወደ ማይደርስበት በርሃ ተጉዞ ደረሰ::

+የደረሰበት አካባቢ ፀሐይ እንደ እሳት የምታቃጥልበት: ምድር እንደ ብረት ምጣድ የጋለችበት ነው:: ቸር እግዚአብሔር ግን ለዚህ ታላቅ ሰው አንዲት የተምር ዛፍ አበቀለለት:: ትንሽ ምንጭንም አፈለቀለት::

+አባ በኪሞስም ዋናውን ተጋድሎ በዚህ ሥፍራ ጀመረ:: ጾምን : ጸሎትን : ስግደትን ያዘወትር ነበር:: ጾሙ በመጀመሪያ 3 ቀን: ቀጥሎ 7 ቀን: በመጨረሻ ግን በ40 ቀን አንዴ ብቻ ማዕድ የሚቀምስ ሆነ::

+ለዛውም ምግቡ አንዲት እፍኝ ይቆረጥማል:: አንዲት ጉንጭ ውሃን ይጐነጫል:: ከዚህ በላይ ለሥጋው ምክንያትና ምቾትን ሊሰጣት አልፈለገም:: በዚህም ምክንያት አካሉ ደርቆ ከሰውነት ተራ ወጣ:: ግን ብርቱና ደስተኛ: የማይደክምም ተዋጊ ነበር::

+የሚገርመው ደግሞ ጸሎቱ ነው:: ሌሎች ጸሎቶቹ ሳይቆጠሩ በመዓልት (በቀን) 2,400 ጊዜ አቡነ ዘበሰማያትን በልዩ ተመስጦ ያደርሰው ነበር:: በሌሊትም በተመሳሳይ ቁጥር ይደግመዋል:: በድምሩ በየዕለቱ 4,800 ጊዜ አቡነ ዘበሰማያት ይል ነበር::

+ስግደቱንማ ማን ቆጥሮት! ታላቁ አባ በኪሞስ እንዲህ ባለ ገድል ለ24 ዓመታት ቆየ:: እድሜውም 63 ደረሰ:: አንድ ጊዜ ግን ሕማማተ ክርስቶስን እያሰበ ያለ ምግብ ለ80 ቀናት ቆየ:: ፈጽሞ በተራበ ጊዜም ቅዱስ መልአክ ከሰማይ ሕብስተ በረከቱን: ጽዋዐ አኮቴቱን ይዞለት ወረደ::

+ከሕብስቱ መግቦት: ከጽዋው አጠጥቶት ወደ ሰማይ ዐረገ:: ሲያርግ ግን ሕብስቱን ትቶለት ነበር:: "ዘወትርም ከዚህ ተመገብ" ብሎታል:: አባ በኪሞስም ከዚያች ቀን ጀምሮ እስከ ዕረፍቱ ድረስ የተመገበው ከዚያ ሕብስት ነው:: ግን አላለቀም ነበር::

+በታላቁ አባ በኪሞስ ዘመን እነ አቡነ ኪሮስና ታላቁ ሲኖዳን የመሰሉ አበው ነበሩ:: በተለይ የባሕታውያን ሁሉ አለቃ አባ ሲኖዳና አባ በኪሞስን መንፈስ ቅዱስ እንዲህ አስተዋውቁዋቸዋል::

+አንድ ቀን አባ ሲኖዳ የእንቁ ምሰሶ ከምድር እስከ ሰማይ ተዘርግቶ ያይና "ጌታየ! ምሥጢሩ ምንድን ነው?" ቢል "ይህ ምሰሶ አባ በኪሞስ ነውና ሒድ ተገናኘው" የሚል ቃልን ሰማ:: አባ ሲኖዳም በእግሩ ተጉዞ አባ በኪሞስን አገኘው::

+ሰላምታን ከተለዋወጡ በሁዋላ አባ በኪሞስ ታላቁ ሲኖዳን "እኔ ወጥ ልሥራ: አንተ ውሃ ቅዳ" አለው:: ቅዱስ ሲኖዳ ከበር ብቅ ብሎ ማሰሮውን በተአምራት ውሃ ሞልቶት ሲመለስ አባ በኪሞስ ደግሞ ያለ እሳት ወጡን አብስሎት ቆየው::

+2ቱም ተገርመው ፈገግታን ተለዋወጡ:: ማንነታቸውንም ተዋወቁ:: ለመናፈስ ወደ በርሃ ወጥተው ሳለም ደክሟቸው ቁጭ አሉ:: ከፊታቸው አንድ የሰው ራስ ቅል ነበርና በበትራቸው መታ : መታ አድርገው "አንተ! ተነስ አጫውተን" አሉት::

+ያ አጽምም ሥጋ ነስቶ: ተነስቶ ሰገደላቸው:: "ከወዴት መጣህ?" ቢሉት "ከሲዖል" አላቸው:: አረማዊ እንደ ነበርና የሲዖልን የመከራ ብዛት ነገራቸው:: አክሎም "ክርስቲያን ነን እያሉ በክርስትናቸው የሚቀልዱ ከእኛ በታች በብዛት አሉ:: መከራቸው ተነግሮ አያልቅም" አላቸው::+ድጋሚ በበትራቸው ነክተው ወደ ነበረበት መለሱ:: ከዚያም ቅዱሳኑ ወደየ በዓታቸው ተሰነባበቱ:: ታላቁ አባ በኪሞስ ከዚህ በሁዋላ ለ7 ዓመታት ያህል መልአክ በክንፉ እየወሰደው ወንጌልን ሰብኩዋል:: ብዙዎችንም ወደ ሃይማኖትና
ንስሃ

አምጥቷል::

+ሁሌም እንቅቦችን እየሰፋ ይሸጥ: በዋጋውም ለነዳያን ይራራ ነበር:: መልአኩም ወደ ፈለገበት ቦታ ተሸክሞ ይወስደው ነበር:: ታላቁ ቅዱስ አባ በኪሞስ በርሃ በገባ በ58 ዓመቱ : በተወለደ በ70 ዓመቱ በዚህች ቀን ዐርፏል:: የክብር ክብርንም ወርሷል::

=>አምላከ አባ በኪሞስ ጸጋውን: ክብሩን አይንሳን:: ከበረከቱም ይክፈለን::

=>ታሕሳስ 11 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ታላቁ አባ በኪሞስ
2.ቅዱስ በርተሎሜዎስ
3.ቅዱስ ቴዎድሮስ
4.ቅዱስ በጥላን

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ያሬድ ካህን
2.ማር ገላውዴዎስ ሰማዕት
3.ቅዱስ ፋሲለደስ ሰማዕት
4.አቡነ ሐራ ድንግል ጻድቅ
5.ቅድስት ሐና ቡርክት

=>+"+ በእሸቅድምድም ሥፍራ የሚሮጡት ሁሉ እንዲሮጡ: ነገር ግን አንዱ ብቻ ዋጋውን እንዲቀበል አታውቁምን? እንዲሁም ታገኙ ዘንድ ሩጡ:: የሚታገልም ሁሉ በነገር ሁሉ ሰውነቱን ይገዛል:: እነዚያም የሚጠፋውን አክሊል ሊያገኙ ነው:: እኛ ግን የማይጠፋውን:: +"+ (1ቆሮ. 9:24)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
ታኅሣሥ 12 

እንኩዋን ለታላቁ ጻድቅ "አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ" እና ለሰማዕታት "አንቂጦስ ወፎጢኖስ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" አባ ሳሙኤል ዘዋሊ "*+

=>ሃገራችን እልፍ አእላፍ ቅዱሳንን አፍርታለች:: እንኩዋን በተባረከው በቀደመው ዘመን ይቅርና ዛሬም ከሃገር ተርፈው ለዓለም የሚጸልዩ : በየበርሃውና በየፈርኩታው የወደቁ ብዙ አባቶችና እናቶች አሉን::

+በኢትዮዽያ ውስጥ ከተነሱ ቅዱሳን "ሳሙኤሎች" ልዩ ቦታ አላቸው:: በ20 ዓመታት ልዩነት ብቻ 6ቱ ሳሙኤሎች ተነስተው ከቅድስና ሕይወት እስከ ስብከተ ወንጌል : ከገዳማዊ ሕይወት እስከ ምናኔ በጐውን ጐዳና አሳይተዋል::

+እነዚህም:-
1.ሳሙኤል ዘዋልድባ
2.ሳሙኤል ዘጣሬጣ
3.ሳሙኤል ዘቆየጻ
4.ሳሙኤል ዘግሺ
5.ሳሙኤል ዘሃሌ ሉያ እና
6.ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ ናቸው::

+በተመሳሳይም በግብጽ የደብረ ቀልሞኑን ኮከብ ጨምሮ (መልአኩን ቀውስጦስን ከጌታ ያማለዱት) ብዙ ሳሙኤሎች ተነስተዋል:: የድሮ እናቶቻችን በእውነት ስም መሰየሙን ይችሉበታል:: "ሳሙኤል" ማለት "ሰምዓኒ እግዚአብሔር ስዕለትየ - እግዚአብሔር ልመናየን ሰማኝ" ማለት ነውና::

+ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና ታላቁ ኢትዮዽያዊ ጻድቅ አቡነ ሳሙኤል ዘዋሊ የተወለዱት በ13ኛው መቶ ክ/ዘመን (በ1295) በምድረ አክሱም ነው:: ወላጆቻቸውም እስጢፋኖስና ዓመተ ማርያም ይባላሉ::

+የዘር ሐረጋቸው ከካህናት ወገን ነውና ጻድቁ ገና በልጅነት ምሥጢራተ ሃይማኖትን ጠጥተዋል:: ለዚህም ይመስላል ገና ሕጻን ሳሉ ምናኔን የተመኙት::

+ከልጅነታቸው ጀምረው ወላጆቻቸውን ያገለገሉት ሳሙኤል ትምሕርታቸውን ሲፈጽሙ የተጉዋዙት ወደ ደብረ በንኮል ነበር::
በጊዜውም የጻድቁ ወላጆች ዐርፈው እንደ ነበር ይነገራል:: ደብረ በንኮል ማለት የታላቁ ኮከብና አበ መነኮሳት አቡነ መድኃኒነ እግዚእ ገዳም ነው::

+መድኃኒነ እግዚእ ለሃገር ብርሃን የሆኑ ቅዱሳንን ያፈሩ ዘንድ ሲተጉ እግዚአብሔር 7ቱን ከዋክብት ሰጣቸው:: ክእነዚህ መካከልም ቀዳሚው አቡነ ሳሙኤል ናቸው:: ቀሪዎቹ ደግሞ እነ አቡነ ያሳይ ዘመንዳባ : ሳሙኤል ዘጣሬጣ : ሳሙኤል ዘቆየጻና ያፍቅረነ እግዚእ ዘጉጉቤን የመሰሉ ናቸው::

+አቡነ ሳሙኤል ከ6ቱ ባልንጀሮቻቸው ጋር ሆነው በደብረ በንኮል ተጋድሎን አሐዱ አሉ:: እንጨት ይሰብራሉ:: ውሃ ይቀዳሉ:: እህል ይፈጫሉ:: በፍጹም ልባቸውም ይታዘዛሉ:: ጐን ለጐን ደግሞ ከቅዱሱ አበ ምኔት መድኃኒነ እግዚእ ጽንዓትን : ትሕትናን : ትሕርምትን ይማሩ : ሥርዓተ ገዳምንም ያጠኑ ነበር::

+ከአገልግሎታቸው ማማር የተነሳ ሁሉን ደስ ማሰኘት ቻሉ:: በዚህ ጊዜም ጻድቁ አበ ምኔት አቡነ ሳሙኤል ዘዋሊንና 6ቱን አበው ጠርተው ለምንኩስና አቀረቧቸው:: "ይገባቹሃል!" ሲሉም ከአሞክሮ ወደ ምንኩስና አሸጋገሯቸው::

+በዚያች ቀን 7ቱ ሲመነኩሱ ከሰማይ ብርሃን ወርዶ በመታየቱ ቅዱሳኑ "ከዋክብት ብሩሃን" ተባሉ:: ለተወሰነ ጊዜም በዚያው በገዳሙ አገለገሉ:: የአቡነ ሳሙኤል ዘመዶች ግን እየመጡ ጻድቁን ስላስቸገሩ 7ቱም ቅዱሳን ተመካክረው : ከአባታቸው መድኃኒነ እግዚእ ተባርከው ከደብረ በንኮል ወጡ::

+ሁሉም መንፈስ ቅዱስ ወደ መራቸው ሲሔዱ 3ቱ (ማለትም ሳሙኤል ዘዋሊ : ያሳይ ዘመንዳባና ያፍቅረነ እግዚእ ዘጉጉቤ) ወደ ጣና ሔዱ:: በዚያም ለጥቂት ጊዜ አብረው ከቆዩ በሁዋላ ለአገልግሎት ተለያዩ:: አቡነ ያሳይ "መንዳባን" : አቡነ ያፍቅረነ እግዚእ "ጉጉቤን" ይዘው እዛው ጣና አካባቢ ሲቀሩ አባ ሳሙኤል ወደ ዋልድባ ሔዱ::

+ዋልድባ በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን በጌታ ፈቃድ የተመሠረተ ሲሆን 860ው መሥራች ቅዱሳን በመሠወራቸው እንደ ጠፍ ይቆጠር ነበርና አቡነ ሳሙኤል እንደ ገና አቀኑት::

+ጻድቁ በዋልድባ የመጨረሻውን ትሕርምት ከመያዛቸው በፊት በጊዜው ከፍተኛ የሆነ የወንጌል አገልግሎት ሰጥተዋል:: ቀጥለውም ኑሯቸውን ከግሩማን አራዊት ጋር አድርገዋል:: በስዕለ አድኅኖው እንደምናየው ለዘመናት በአንበሳ ጀርባ ላይ ተጭነዋል::

+ጧት ማታም ብዙ ግሩማን አራዊትን እያስከተሉ ለአገልግሎት ደክመዋል:: ጻድቁ ከትሕርምት ብዛት እህል ትተው የሻገተ ጐመንና መልኩን የለወጠ ውሃን ለቁመተ ሥጋ ይጠቀሙ ነበር::

+አንድ ቀንም መድኃኒታችን ክርስቶስ ወደ እርሳቸው መጥቶ ባረካቸው:: አካላቸውንም በቅዱስ ምራቁ አትቦ ቀባቸው:: በዚህ ጊዜም ኃይለ መንፈስ ቅዱስን ተመሉ:: የክርስቶስን ሕማማት እያሰቡም እልፍ ጊዜ ይሰግዱ: ጀርባቸውን ይገርፉም ነበር::

+እግራቸውን በሰንሰለት አሥረው ይጋደሉም ነበር:: በዚህ ግብራቸው አጋንንትን አሳፍረው: ፈጣሪያቸውን ደስ አሰኙ:: ከቆይታ በሁዋላም ዋልድባ በመነኮሳት ተሞላ:: ደቀ መዛሙርት በዙ:: ቀዳሚው ግን አባ ዘሩፋኤል ጻድቅ ነው::

+አቡነ ሳሙኤል ከድንግል እመቤታችን ጋር ልዩ ፍቅር ነበራቸው:: ዘወትር ውዳሴዋንና ቅዳሴዋን በተመስጦ ያደርሱላት: ፈጽመውም ያመሰግኗት ነበር:: ይህንን ሲያደርጉ ከመሬት ክንድ ከፍ ብለው ይንሳፈፉ ነበር::

+ተከታዮቻቸው ሲርባቸውም ውሃውን በቅዳሴ ማርያም ነጭ ሕብስት ያደርጉት ነበር::

"ሶበ አተቦ ለማይ በቅዳሴኪ እንዘ ይጼሊ::
ረሰዮ ሕብስተ ሳሙኤል ጽጌ ሃይማኖት ዘሐቅለ ዋሊ::
ምሕረተ ወፍትሐ ለተአምርኪ እኅሊ::
ስረዪ ኃጢአትየ ወዕጸብየ አቅልሊ::
እስመ ኩሎ ገቢረ ማርያም ትክሊ::" እንዳለ ሊቁ:: (ማኅሌተ ጽጌ)

+እመ ብርሃንም ስለ ፍቅር ነጭ እንቁ ሰጠቻቸው:: ሰማያዊ ሕብስትን መገበቻቸው:: ንጹሕ ዕጣንንም አበረከተችላቸው:: ለ12 ዓመታትም ከሰማይ ካህናት ጋር አጠኑ:: ድንግል ማርያም "እንዳንተ ውዳሴየንና ቅዳሴየን በፍቅር የሚደግምልኝን አማልደዋለሁ" ስትላቸው:-

+ጌታ ደግሞ ገዳማቸውን ዋልድባን ቀድሷታል:: ቀድሞም በስደቱ ባርኩዋት ነበር:: የጻድቁ ዜና ፈጽሞ ብዙ ነውና ለዛሬ በዚህ ይብቃን:: የዋልድባው ኮከብ አቡነ ሳሙኤል ያረፉት ታሕሳስ 12 ቀን በ1395 ሲሆን ዕድሜአቸውም 100 ዓመት ነበር::

<< ለጻድቁ ክብር ይገባል !! >>

+"+ ቅዱሳን አንቂጦስ ወፎጢኖስ +"+

=>እነዚህ ቅዱሳን በሥጋ ወንድማማቾች ሲሆኑ የዘመነ ሰማዕታት ፍሬዎች ናቸው:: ዜና ሕይወታቸውን ሳስበው ይገርመኛል:: በእሳት የወጣትነት ዘመናቸው በሃይማኖት ጸንተው: ፍቅረ ክርስቶስ እንደ እሳት በላያቸው ላይ ይነድ ነበር::

+በእውነት ክርስቶስን በከንፈር ያይደለ በፍጹም ልቡና መውደድ እንዴት ያለ መታደል ነው! ክርስቶስን የወደደ የድንግል እናቱና የቅዱሳን ወዳጆቹ ፍቅር ይበዛለታል እንጂ አይቀንስበትም::

+ቅዱሳኑ አንቂጦስና ፎጢኖስ ወጣትነት: የዓለም ኑሮ ሳያታልላቸው ለሰማዕትነት ራሳቸውን አዘጋጁ:: እንኩዋን ሰውን አራዊትን የሚያስበረግግ የስቃይ ዓይነት ተሰልፎ ሳለ በፍጹም አልደነገጡም::

+መጀመሪያ አንቂጦስን አቀረቡት:: ገረፉት: ምንም አልሆነም:: በእሳት አቃጠሉት: ምንም አልነካውም:: ለአንበሳ ሰጡት: እነርሱ ግን ሰገዱለት:: ከዳር ሆኖ ይህንን ሁሉ ሲመለከት የነበረው ወንድሙ ፎጢኖስ ዘሎ ወደ መከራ አደባባይ ገባ::

+"ወንድሜ የክርስቶስ ነውና መቼም አታሸንፈውም" ሲል ጮኸ:: በዚህ ጊዜም በሥፍራው የነበሩ ብዙ አሕዛብ "የእነዚህ ወጣቶች አምላክ አምላካችን ነው" አሉ::
መኮንኑም 2ቱን ቅዱሳን ከብዙ ሕዝብ ጋር አሰይፏቸዋል::
+እንደ እኔ ያለ ኃጢአተኛም በስማቸው እንዲህ ሊጸልይ ይገባል:-"ሰላም ዕብል ለአንቂጦስ ማሕበሮ::
እለ በእሳት ፈጸሙ ረዊጸ ወተባድሮ::
ያብጽሑኒእሉ ምስለ መላእክት ድርገተ ዘምሮ::
ህየ አኀሉ ወሬዛ ነዳየ ኩሉ አዕምሮ::
ኀበ ይዘብጣ ደናግል ከበሮ::" (አርኬ)

=>አምላከ ሳሙኤል በምጃቸው ሃገራችን ከጦርነት: ሕዝቦቿን ከስደት ይሰውርልን:: ሞልቶ ከተረፈ በረከታቸውም አይንሳን::

=>ታሕሳስ 12 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ
2.ቅዱሳን አንቂጦስ ወፎጢኖስ (ሰማዕታት)
3.አባ ነድራ
4.ቅዱስ ዮሐንስ ተአማኒ
5.ጉቡዓን ኤዺስ ቆዾሳት

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት
2.ቅዱስ ላሊበላ ጻድቅ (ንጉሠ ኢትዮዽያ)
3.ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ
4.ቅዱስ ቴዎድሮስ ምሥራቃዊ (ሰማዕት)
5.ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ
6.ቅዱስ ማቴዎስ ሐዋርያ
7.ቅዱስ ድሜጥሮስ ሊቅ

=>+"+ የሚያሳድዷችሁን መርቁ . . . ደስ ከሚላቸው ጋር ደስ ይበላችሁ:: ከሚያለቅሱም ጋር አልቅሱ:: እርስ በርሳችሁ በአንድ አሳብ ተስማሙ:: የትዕቢትን ነገር አታስቡ:: ነገር ግን የትሕትናን ነገር ለመሥራት ትጉ:: +"+ (ሮሜ. 12:14-16)

    <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
2024/09/30 20:17:29
Back to Top
HTML Embed Code: