Telegram Web Link
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ
               አሜን

📌 ስንክሳር ዘወርኀ ታኅሣሥ ፲፫

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ታኅሣሥ ዐሥራ ሦስት በዚች ቀን አባ በጽንፍርዮስ በሰማዕትነት አረፈ።
ይህም የከበረ መነኰስ በምስር አገር በወንዝ ዳር በአለች በሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መንኵሶ ታላቅ ተጋድሎን ሲጋደል ኖረ ስለቀናች ሃይማኖትም ከእስላሞች መሳፍንት ጋር ተከራከረ የጌታችን ክርስቶስንም መለኮቱን ገለጠላቸው አምላክነቱንም አስረዳቸው ስለዚህም እስላሞች በአፈሩ ጊዜ ተቆጡ ጽኑዕ ሥቃይንም አሠቃዩት ራሱንም በሰይፍ ቆረጡ የሰማዕትነት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።



📌 በዚችም ቀን ከላይኛው ግብጽ ቅዱስ አባት አብራኮስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ዕድሜው ሃያ ዓመት ሲሆን መንኵሶ መልካም የሆነ ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለ።

ሰይጣንም ከእርሱ ጋር በመጣላት በተሸነፈና በደከመ ጊዜ በእርሱም ላይ ምንም ምን ማድረግ ባልተቻለው ጊዜ ፊት ለፊት ተገልጦ መጥቶ እነሆ ከዚህ ዕድሜህ ሌላ ኀምሳ ዓመት ቀረህ አለው። በዚህም ወደ ስንፍና ሊጥለው ወዶ ነው ሽማግሌውም እንዲህ ብሎ መለሰለት አሳዘንከኝ እኔ ሌላ መቶ ዓመት እኖር ዘንድ ስለ አሰብኩ ቸል ብያለሁ አንተ እንዳልከውም ከሆነ ከቀድሞው እጅግ አብዝቼ እጋደል ዘንድ ይገባኛል። ከዚህም በኋላ ተጋድሎውንና በገድል መጸመዱን አበዛ ሰባ ዓመታትም ከተጋደለ በኋላ በዚያች ዓመት አረፈ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
    
   


📌 በዚችም ቀን በደብረ ቀልሞን የሚኖር የገዳማዊ የአባ ሚካኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር አሜን።

📌 በዚችም ቀን ቆቅ ሲመገብ የነበረ የአባ መቃርስ መታሰቢያው ነው፤ ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ ሕያው እግዚአብሔርን መከተል ፈለገ የቤተ ክርስቲያንንም ትምህርት መጻሕፍትንም ተማረ የዚህንም ዓለም ኃላፊነቱን ለጻድቃንም በጎ ዋጋ ለኃጥአን ቅጣት እንዳለም አስተዋለ ስለዚህም ዓለምን ትቶ በአንድ ገዳም ውስጥ መነኰሰ ከዚያም ወጥቶ የዐሥር ቀን ጐዳና ተጓዘና በውስጡ ኵዕንትና ቆቆች ውኃም ካለበት ተራራ ደረሰ።
❖ አስቦም እንዲህ አለ ኵዕንትን ወደመልቀም ብሰማራ የስግደቴና የጸሎቴ ሥራ ይቋረጣል ሰብሰቦ የሚያስገባልኝ ረዳት የለኝ ብቸኛ ነኝና ሥጋ አትብላ ያለውስ የባልንጀራችንን ሥጋ በሐሜት የምንበላውን አይደለምን ሌላ ምግብ እንደሌለኝ ፈጣሪዬ ያውቃል ብሎ ከዚያችም ዕለት ወዲህ ቆቆችን የሚያጠምድ ሆኖ በየቀኑ አንድ አንድ የሚያዙለት ሆኑ፡፡
❖ እርሳቸውንም እየተመገበ ከዚያ ውኃም እየጠጣ በማመስገን ኖረ በቀንና በሌሊትም በጸሎትና በስግደት በመትጋት ወደ እግዚአብሔርም እየለመነ ብዙ ዘመናት ኖረ የሰውንም ድምጽ አይሰማም የሰውንም ፊት አያይም ሐሜትንም ሆነ ስድብን በማንም ላይ አብሮ አይነጋገርም ከሰው ጋር ካልሆነ በቀር ሰይጣን አይመጣም ይባላልና።

❖ ከዚህም በኋላ ከቁስጥንጥኒያ ከተማ አንድ መነኲሴ ዋሻ እየፈለገ አባ መቃርስ ካለበት ደርሶ ቆቅን ሲያጠምድ አየው ያንጊዜ አልታገሠም ግን ወንድሙን በሐሜት እስከሚገድለው ቸኮለ ወደ ቁስጥንጥንያ ከተማ ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ተመልሶ እንዲህ ብሎ ነገረው እኔ ዋሻ እየፈለግሁ ወደ በረሀ ሔድሁ በዚያም ሥጋ ሊበላ ቆቅን ሲያጠምድ መነኲሴውን አየሁት የሚሰራውን ሲያዩ በአሕዛብ ዘንድ ሊያስነቅፈን ነው አለው፡፡
❖ ሊቀጳጳሳቱም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ነገሩ እውነት እንደሆን ያውቅ ይረዳ ዘንድ ከዚያ ከነገረው መነኲሴ ጋር ሌላ መነኲሴ ላከ እነርሱም በጕዞ ላይ በጐዳና ሳሉ ገና ሳይደውሱ አባ መቃርስ እንደልማዱ ወደ ወጥመዱ ሔደ በአንዲት ወጥመድ የተያዙ ሦስት ቆቆችን አገኘ እንዲህም ብሎ አሰበ ጌታዬ እሊህን የሰጠኝ እኔን ሊፈትነኝ ነውን ወይስ ከዚች ዕለት በፊት ሆዴ ያልጠገበች ኑራለችን ወይም ለሌላ ነው እንዳልል በዚህ በረሀ ውስጥ ከሰው ወገን ያየሁት የለም፡፡
❖ እንዲህም እያሰበ ሳለ ከሊቀ ጳጳሳቱ የተላኩት እሊያ መነኰሳት ደረሱ በአያቸውም ጊዜ ደስ አለው ችግረኛነቴን አውቀህ ለአገልጋዮችህ ቅዱሳን ምግባቸውን የሰጠኸኝ አቤቱ አመሰግንሃለሁ ብሎ ሰገደ። እነርሱ ግን ማዕድ ሠርቶ አዘጋጅቶ እስከአቀረበላቸው ድረስ ይጠቃቀሱበት ነበር ከዚህም በኋላ አቅርቦላቸው ንሱ አባቶቼ ባርኩና ተመገቡ አላቸው እርሱም የራሱን ድርሻ ይዞ እስከሚጨርስ ያለ መነጋገር በጸጥታ ተመገበ።

❖ ከዚህም በኋላ ዓይኖቹን ቀና ቢያደርግ እንዳልበሉ አየ አባቶቼ እንዴት አልበላችሁም አላቸው እኛ መንኰሳት ስለሆን ሥጋ አንበላም ትኅርምትም አለን አሉት እርሱም ተዋቸው አላስገደዳቸውም እነዚያን ያበሰላቸውን ቆቆች አንሥቶ ሦስት ጊዜ እፍ አለባቸው ያን ጊዜም ድነው በረሩ ወደ ቦታቸውም ሔዱ እነዚያ መነኰሳትም ይህን ተአምር አይተው ደነገጡ የእግዚአብሔር ቅዱስ ሆይ በደላችንን ይቅር በለን ብለው ሰገዱለት እርሱም የሁላችንንም በደል እግዚአብሔር ይቅር ይበለን አላቸው።

❖ ከዚህም በኋላ ወደ ሀገራቸው ተመልሰው ያዩትን ይህን ድንቅ ተአምር ለሊቀ ጳጳሳቱ ነገሩት እርሱም ሰምቶ አደነቀ ወደ ንጉሥም እንዲህ ብሎ ላከ በዘመናችን ጻድቅ ሰው መነኰስ ተገኝቷልና አንተም ና ሒደን በረከቱን እንድንቀበል አለው።

❖ ወዲያውኑ ንጉሡ ከሠራዊቱ ጋር ተነሣ ሊቀ ጳጳሳቱም ከካህናቱ ጋር አባ መቃርስ ወዳለበት እነዚያ መነኰሳት እየመሩአቸው ሔዱ ወደርሱም ሲቀርቡ ወደ ብሔረ ሕያዋን ያደርሰው ዘንድ መልእክ አንሥቶ በክንፎቹ ተሸከመው ሲያርግም በአዩት ጊዜ የእግዚአብሔር ቅዱስ ሆይ ባርከን የምንድንበትን አንዲት ቃል ንገረን ብለው ጮኹ፣ እርሱም ከሐሜትና ከነገር ሥራ አንደበታችሁ ይከልከል።
❖ ካህን ብዙ ባይማር ትዕቢትና መታጀር ባልመጣበት ነበር መነኵሴም ትኅርምት ባያበዛ ባልተመካም ነበር እርስበርሳችሁ ተፋቀሩ እግዚአብሔርም አድሮባችሁ ይኑር አላቸው ይህንንም ብሎ ዐረገ ከዐይናቸውም ተሠወረ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ጻድቅ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

? ታኅሣሥ 13 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.አቡነ ዘርዓ ቡሩክ ጻድቅ
2.ቅዱስ መቃርስ ገዳማዊ
3.አባ አብራኮስ ገዳማዊ
4.ብጽዕት ሐና (የእመቤታችን እናት)
5.አባ በጽንፍርዮስ ሰማዕት
6.አባ ሚካኤል ዘቀልሞን

📌 ወርኀዊ በዓላት
1.እግዚአብሔር አብ
2.ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላዕክት
3.ቅዱስ አርሳንዮስ ጠቢብ ገዳማዊ
4.አእላፍ (99ኙ) ነገደ መላእክት
5.ቅዱስ አስከናፍር ሮማዊ
6."13ቱ" ግኁሳን አበው
አቡነ ዘርዓ ቡሩክ

✥•••••●◉ ✞ ◉●•••••✥


❖ ሃገራችን ኢትዮዽያ ብሉይ ከሐዲስ ያልጐደለባት በክርስቶስና በድንግል እናቱ ኪደተ እግር የተቀደሰች የቅዱሳን መጠጊያ እና ብዙ ቅዱሳንን ከእቅፏ ያፈራች ስለ ሆነች የተባረከች ሃገር ትባላለች፤ ሁሉም የሃገራችን ክፍሎች ቅዱሳንን አፍርተዋል::
❖ በምሥራቅም፣ በምዕራብም፣ በሰሜንምና በደቡብም ያሉ አካባቢዎች ሁሉ የቅዱሳን ቤቶች ናቸው፤ ቅዱሳንን በብዛት ካፈሩ አካባቢዎች አንዱ ደግሞ ምድረ ጐጃም ነው፤ በጐጃም አካባቢ ከተነሱ ቅዱሳን ደግሞ አንዱና ስመ ጥሩ ጻድቅ አቡነ ዘርዓ ቡሩክ ናቸው፤ አቡነ ዘርዓ ቡሩክ በብዙ ጐዳና የተለዩ አባት ናቸው፤ ለመጥቀስ ያህል እንኩዋ
1⃣ በታሪክ ዓለምን ከበው የያዙ 2ቱ ግሩማን አራዊት (ብሔሞትና ሌዋታንን) ጥርስ ቆጥረው ብዙ ምሥጢራትንም ተመልክተው ተመልሰዋል፤ (በነገራችሁ ላይ ይህ ጉዳይ ዛሬም ድረስ ሳይንሱ በብዙ ድካም ያልደረሰበት ነው)
2⃣ ጻድቁ በልደታቸው ጊዜ ዓይነ ስውራንን አብርተዋል፤ ለራሳቸው ግን ይህን የግፍ ዓለም ላለማየት ጸልየው ዓይናቸው እንዲጠፋ አድርገዋል::
❖ ጻድቁ የተወለዱት በ16ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እዚያው ጐጃም ውስጥ ሲሆን አባታቸው ደመ ክርስቶስ እናታቸው ደግሞ ማርያም ሞገሳ ይባላሉ፤ ወላጆች በልጅ እጦት ተማረው ይህን የተቀደሰ ፍሬ አገኙ፤ "ጸጋ ኢየሱስ" ብለውታል፤ በኢየሱስ ክርስቶስ ተሰጥቷቸዋልና::
❖ ቀጥሎ የወለዱትንም "ተስፋ ኢየሱስ" ብለውታል፤ ይህም የጻድቁ ታናሽ ወንድም ነው፤ በሒደት ግን የጸጋ ኢየሱስ ስም በፈቃደ እግዚአብሔር ወደ ዘርዓ ቡሩክነት ተቀይሯል::
❖ ጻድቁን ስመ ጥር ካደረጉዋቸው ሥራዎቻቸው መካከል በአፄ ሱስንዮስ ዘመን የሠሩት ቅድሚያውን ይወስዳል፤ ነገሩ እንዲህ ነው፤ በ1598 ዓ.ም በኢትዮዽያ ላይ የነገሡት አፄ ሱስንዮስ ዼጥሮስ (ፔድሮ) ፓኤዝ ከሚባል ፈረንጅ መናፍቅ ጋር በፈጠሩት ወዳጅነት ሃይማኖታቸውን ለወጡ::
❖ ካቶሊክ (ሮማዊም) ሆኑ፤ በሁዋላም አልፎንሱ ሜንዴዝ የሚሉት እሾህ መጥቶ ሁሉም የኢትዮዽያ ሕዝብ መናፍቅ እንዲሆን ከንጉሡ ጋር መከረ፤ ለጊዜው በቤተ መንግስቱ አካባቢ የነበሩ መሣፍንት ተቀላቀሉ፤ እየቆየ ግን ዜናው በመላ ሃገሪቱ ተሰማ፤ በተለይ በ1611 በተዋሕዶ አማኞችና በመናፍቁ ንጉሥ መካከል ነገሩ ተካሮ ዻዻሱ አቡነ ስምዖን ጠዳ ላይ መገደላቸው ተሰማ::
❖ በዚህ ጊዜ ገበሬው ከእርሻው ሴቷ ከማዕድ ቤት ካህኑ ከመቅደሱ ነጋዴው ከገበያው እየወጡ ስለ ቀናችው ሃይማኖት ደማቸውን አፈሰሱ፤ በበዓት የተወሰኑ በሺህ የሚቆጠሩ ቅዱሳንም ወጥተው ተሰየፉ::
❖ በዚህ ጊዜም የግሺው አቡነ ዘርዓ ቡሩክ ዳዊታቸውን አንግበው ለሰማዕትነት ሔዱ፤ ዓባይ ወንዝ ላይ ሲደርሱ ዳዊታቸውን ወደ ወንዙ ውስጥ ጣሉት፤ ተሻግረውም ከንጉሡ አደባባይ ደንቀዝ ደረሱ፤ በጊዜውም ልክ እንደነ ፍቅርተ ክርስቶስና ወለተ ዼጥሮስ እርሳቸውም መከራ ደረሰባቸው::
❖ ንጉሡም ሳይገደሉ እንዲታሠሩ አደረገ፤ በጨለማ እስር ቤትም 5 ዓመታትን ሲያሳልፉ ትኩስ ምግብን ያመጡላቸው ነበር፤ እርሳቸው ግን ምግባቸው ሰማያዊ ነበርና አልነኩትም፤ ከ5 ዓመት በሁዋላም ያ ሁሉ ምግብ በተአምራት በትኩስነቱ እየጨሰ ተገኝቷል፤ ዘርዓ ቡሩክም ከእሥር ተፈትተዋል::
❖ እግዚአብሔርም በከሐዲው ንጉሥ ላይ ፈርዶ ፋሲል ነግሷል፤ ሃይማኖት ተመልሷል፤ ጻድቁም በዓባይ ወንዝ ላይ የጣሉት ዳዊታቸውን ሳይርስ አግኝተውታል፤ ጐጃም ሲደርሱም ሰይጣን እርሳቸውን መስሎ ሲያስት ስላገኙት ወደ ጥልቁ አስጥመውታል፤ በተረፈ ዘመናቸው አቡነ ዘርዓ ቡሩክ ብዙ ተጋድለው ጥር 13 ቀን ዐርፈዋል፤ ድንቅ ሠሪ አባት ናቸውና ዛሬም በግሺ ብዙ ተአምራት ይደረጋሉ።
ረድኤታቸው በረከታቸው ይደርብን፤ በጸሎታቸው ይማረን፤ ሀገራችን ሰላም ፍቅር ያድርግልን 
"አሁን እየጾምክ ነው? እስቲ ጾምህን በተግባር አሳየኝ? የቱን ሰራህ? ድሃውን ባየህ ጊዜ ምህረትን አሳየው። ጠላትህን ስታየው ታረቀው። ስኬታማ የሆነ ወንድምህን ስታየው አትቅናበት በመንገድ የምትሔድ ሴትን ስታይ ዝም በለህ እለፋት። በአጠቃላይ አፍህ ብቻ አይጹም ነገር ግን ዓይንህ፣ እግርህ፣ እጅህ ሁሉም አካልህ ይጹም። እጅህ ከመስረቅና ከስስት ይጹም፣ እግሮችህ ወደ ኃጢአት ከመጓዝ ይከልከሉ፣ አይኖችህም በሌሎች ሰዎች ውበት ላይ ተተክለው ከመዋል ይጹሙ።

አሁን ስጋ እየበላህ አይደለም አይደል? በዓይንህም መጥፎ ነገር አትመልከት፤ መስማትንም ጹም። የፈውስ ጾም ክፉን አለመስማት የሌሎችንም ስም አለማጥፋት ነው። አንደበትም ከክፉና ከአጸያፊ ንግግር ይጹም። የዶሮና የአሳ ስጋ ከመብላት እንከለከላለን ነገር ግን የወንድማችንን ስጋ ስናኝክና ስንበላ እንውላለን። የወንድሙን ስጋ የሚበላ ደግሞ የተረገመና አሳች ነው። ቅዱስ ጳውሎስ “ነገር ግን እርስ በርሳችሁ ብትነካከሱና ብትበላሉ እርስ በርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ” እንዳለን። ገላ.5:15

ሆዳችንን ከምግብ ብቻ ባዶ ማድረግ አይደለም። ነገር ግን ሁለንተና ሕይወታችንን ራሳችንንም የምንቆጣጠር እኛ ወደ መንፈሳዊ ነገሮች የምንመራ መሆን አለብን።"

የቅዱስ ዮሐንስ በረከቱ ይደርብን ውርስ ትርጉም #መምህር_ንዋይ_ካሳሁን
Daniel:
††† እንኳን ለዕለተ ብርሃን: ለታላቁ ሰማዕት ቅዱስ መርምሕናም እና ቅድስት ነሣሒት ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ዕለተ ብርሃን †††

††† ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱስንና የቅዱስ ያሬድን አስተምሕሮ መሠረት አድርጋ ይህንን ዕለት (ታኅሳስ 14ን) "ዕለተ-ብርሃን" : ሳምንቱን (ከታኅሳስ 14-20 ያለውን) ደግሞ "ሰሙነ-ብርሃን" ስትል ታስባለች::

"ብርሃን" በቁሙ የእግዚአብሔር ስሙ: አንድም የባሕርይ ገንዘቡ ነው:: "እግዚአብሔር ብርሃን ነውና:: ጨለማም በእርሱ ዘንድ የለችምና::" (ዮሐ. 1:4)
~በዚህ ዕለት "ብርሃን" በሚል መነሻ ቤተ ክርስቲያን እነዚህን ታስተምሠራለች:-
1.እግዚአብሔር ብርሃን መሆኑን:: (ዮሐ. 1:5)

2.አምላካችን በመጀመሪያው የፍጥረት ቀን (በዕለተ እሑድ) ዲያብሎስ ቅዱሳን መላእክትን ሲረብሽ "ለይኩን ብርሃን" ብሎ ብርሃንን መፍጠሩን:: (ዘፍ. 1:2, አክሲማሮስ)

3.ነቢያት አበው በጨለማው ዓለም ሆነው መከራ ሲበዛባቸው "ፈኑ ብርሃነከ - ብርሃንህን ላክልን" እያሉ መጮሃቸውን:: (መዝ. 42:3)

4.ጩኸታቸውን የሰማ ከሦስቱ አካላት አንዱ ወልድ (እውነተኛው ብርሃን) ወደዚህ ዓለም መምጣቱን:: (ሉቃ. 1:26)

5."እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ" ሲል የባሕርይ ብርሃንነቱን እንደ ነገረን:: (ዮሐ. 9:5)

6.ብርሃነ መለኮቱን በገሃድ መግለጡን:: (ማቴ. 17:1)

7.ብርሃን የሆነችውን ሕግ: ወንጌልን እንደ ሠራልን:: (1ዮሐ. 2:9)

8.ድንግል እመቤታችን ብርሃን : የብርሃንም እናቱ መሆኗን:: (ሉቃ. 1:26, ራዕ. 12:1)

9.ቅዱሳኑ ብርሃን መባላቸውን:: (ማቴ. 5:14)

10.እኛ በሰው ፊት ሁሉ እንድናበራ መታዘዛችን:: (ማቴ. 5:16) ሁሉ ይታሰባል::

እርሱ ፈጣሪያችን ክርስቶስ ጨለማውን በምሕረቱ አርቆልናልና ዳግመኛ ወደ ጨለማ እንዳንሄድ እየለመንን እናመስግነው::
"ክርስቶስ ብርሃን ዘአሰሰልከ ጽልመተ::
ላዕለ ኪሩቤል ነቢረከ ዘትሬኢ ቀላያተ::
ስቡሕኒ ወልዑል አንተ::" (መልክአ ኢየሱስ)

††† ቅዱስ መርምሕናም ሰማዕት †††

††† ሰማዕቱ በቤተ ክርስቲያን ትልቅ ቦታ ከሚሰጣቸው ዐበይት ቅዱሳን አንዱ ነው:: በየአብያተ ክርስቲያናቱ ከሚሳሉ ቅዱሳንም አንዱ ነው:: ሃገሩ አቶር (በፋርስ አካባቢ) ሲሆን አባቱ ሰናክሬም የሚባል ንጉሠ ነገሥት ነው::

እናቱ ምንም ክርስቲያን ብትሆንም ስለ ፈራች 2ቱን ልጆቿን (መርምሕናምና ሣራን) ክርስትናን አላስተማረቻቸውም:: 2ቱም ወጣት በሆኑ ጊዜም ከንጉሥ አባታቸው ጋር ይወጡ ይገቡ ነበርና እናታቸው በሐዘን ጸለየች:: ወዲያውም ወጣቷ ሣራ በለምጽ ተመታች::

የሚፈውሳት ጠፋ:: መርምሕናም ግን ጐበዝ ወጣት ነውና 40 የጦር አለቆችን ይመራ ነበር:: በዚያው በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ቅዱስ መርምሕናም 40 ተከታዮቹን ይዞ ለአደን ወደ ዱር ሲወጣ ከአባ ማቴዎስ ገዳማዊ ጋር ተገናኘ::

ጻድቁ ለብዙ ዓመታት በበርሃ የኖሩ አባት ናቸው:: አካላቸው በጸጉር ስለ ተሸፈነ ደንግጦ ሲሸሽ "ልጄ አትፍራ! እኔም እንዳንተ የክርስቶስ ፍጡር የሆንኩ ሰው ነኝ" አሉት::

እርሱ ግን "ደግሞ ክርስቶስ ማነው?" ሲል ጠየቃቸው:: አባ ማቴዎስም ምሥጢረ ክርስትናን ከመሠረቱ አስተምረው የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት ነገሩት::

ቅዱስ መርምሕናም ግን "ክርስቶስ አምላክ እንደ ሆነ አምን ዘንድ እህቴን አድንልኝ" አላቸው:: "አምጣት" ብለውት አመጣት:: ጻድቁ ጸሎት አድርሰው መሬትን ቢረግጧት ውሃን አፈለቀች:: "በእምነት: በስመ ሥላሴ ተጠመቁ" አሏቸው::

ቅዱሱ: እህቱ ሣራና 40 የጦር አለቆች ተጠምቀው ሲወጡ ሣራ ከለምጿ ነጻች:: ፈጽሞም ደስ አላቸው:: ወደ ቤተ መንግስት ተመልሰውም ቅዱስ መርምሕናም ከእናቱ: ከእህቱና ከ40 ተከታዮቹ ጋር ክርስቶስን ሊያመልኩ ጀመሩ::

ንጉሡ ሰናክሬም ግን ነገሩን ሲሰማ ተቆጣ:: እነርሱም ወደ ተራራ ሸሹ:: ንጉሡ "ልጆቼ! መንግስቴን ውረሱ" ብሎ ቢልካቸውም "እንቢ" አሉ:: ስለ ተበሳጨም ቅዱስ መርምሕናምን: ቅድስት ሣራንና 40ውን ቅዱሳን በሰይፍ አስመታቸው::

ሥጋቸውን በእሳት ሊያቃጥሉ ሲሉ ግን መነዋወጥ ሆኖ ብዙ አረማውያን ሞቱ:: ንጉሡም አብዶ አውሬ (እሪያ) ሆነ:: ያን ጊዜ አባ ማቴዎስ ከበርሃ ወጥተው ንጉሡን ሰናክሬምን ፈወሱት::

እርሱም አምኖ የልጆቹና የ40ውን ሥጋ በክብር አኖረ:: በሃገሩ አቶርም የእመ ብርሃን ማርያምን ቤተ መቅደስ አነጸ:: በክርስትና ኑሮም ዐረፈ:: እርሱ ከተቀበረ በሁዋላ ግን የከለዳውያን ንጉሥ መጥቶ አቶርን ወረራት::

ንግሥቲቱን (የቅዱሳኑን እናት) ከሕጻኑ ልጇ ጋርም ገደለ:: በሁዋላም "ለጣዖት ስገዱ" ማለቱን የሰሙት የቅዱስ መርምሕናም ወታደሮች ደርሰው በምስክርነት ተሰየፉ:: ቁጥራቸውም 170,000 ሆነ::

††† ቅድስት ነሣሒት ቡርክት †††

††† በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ከነበሩና አስደናቂ ታሪካቸው ከተጻፈላቸው ቅዱሳት እናቶቻችን አንዷ ነሣሒት ናት:: የእርሷን ገድል (ዜና ሕይወት) የጻፈው አባ ያዕቆብ የአውሲም ኤዺስ ቆዾስ ነው:: እርሱ እንዲህ ይላል:-
"አንድ ቀን በገዳም ሳለሁ: አመሻሽ ላይ የገዳሙ በር ሲጸፋ (ሲንኩዋኩዋ) ሰማሁ:: ማን እንደ ሆነ አውቅና እከፍት ዘንድ ተጠጋሁ" ይላል ቅዱሱ አባት::

በሩን ከፍቶ ሲመለከት ፊቱን የተሸፋፈነ አንድ መነኮስ ራሱን አዘንብሎ ቁሟል:: "ማነህ? ከወዴትስ መጣህ?" ሲል ጠየቀው:: መነኮሱም "እኔ ከገዳመ ቅዱስ መቃርስ የመጣሁ መንገደኛ ነኝ:: በዚህች ሌሊት በእናንተ ዘንድ ላድር: ሥጋውን ደሙንም እቀበል ዘንድም እፈልጋለሁ" አለው::

አባ ያዕቆብ ግን ለገዳሙ ደህንነት ሲል "መጐናፀፊያህን ግለጥና ፊትህን አሳየኝ" ቢለው መነኮሱ "አባቴ! በኃጢአቴ ብዛት ፊቴ ጠቁሯልና ኃጢአቴን አትመራመረኝ" ሲል መለሰለት::

አባ ያዕቆብ "አላስገባህም" ብሎ ትቶት ሔደ:: "ግን ምናልባት የራበው ሰው ቢሆን ፈጣሪየ ሊያዝንብኝ አይደል!" ብሎ ከፍቶ አስገባው:: አበው ራት ሲበሉ እንግዳው አልበላም ነበር:: እነርሱ ሲተኙ እንግዳው መነኮስ ይጸልይ ጀመር::

ከድምጹ ግርማ የተነሳም መነኮሳቱ ሁሉ ደንግጠው ተነሱ:: የዳዊትን መዝሙር ሲዘምር ነጐድጉዋድ ድምጹ እንደ መልአክ ድምጽ ነበርና ምድር ራደች:: አባ ያዕቆብም ተደነቀ:: እንዲህ አድረው ዕለተ ሰንበት ነበርና በነግህ ቅዳሴ ገቡ::

ስለ ክብሩም በቅዳሴ ሰዓት መልእክታቱንና ወንጌሉን እንግዳው አነበበ:: ቅዱስ መጽሐፍን ሊያነብ መጐናጸፊያው ሲገለጥ ግን ከመልኩ ግርማና ከፊቱ ብርሃን የተነሳ ሊመለከቱት አልቻሉም::

ሥጋውን ደሙን ከተቀበለ በሁዋላ እነ አባ ያዕቆብ በረከቱን ይነሱ ዘንድ ቢሔዱም ተሰወረባቸው:: እነርሱም አዘኑ::

እስካሁን ድረስ ያነበባችሁት ዜና የአንድ ወንድ መነኮስ ታሪክ ሳይሆን ወንድ መስላ ራሷን ሰውራ የኖረችውን የቅድስት ነሳሒትን ታሪክ ነው::

ቅድስቲቱ ከሮም ነገሥታት የአንዱ ልጅ ብትሆንም ስለ ጌታ ፍቅር በ12 ዓመቷ ከቤተ መንግስት ጠፍታ በርሃ ገብታለች:: ነገር ግን የአባቷ ሠራዊትና መነኮሳት ስለሚፈልጉዋት ወንድ መስላና ራሷን ሠውራ በደብረ አባ መቃርስ ኑራለች::

ከዚያም ከአንዱ ገዳም ወደ ሌላኛው ስትዘዋወር ኑራ ጸጋ እግዚአብሔር ቢበዛላት ድምጿም መልኩዋም ልዩ ሆነ:: እግዚአብሔር በቅዱሳኑ ላይ ድንቅ ነውና:: ቅድስት ነሣሒት በዚህች ዕለት በበርሃ ስታርፍ መንገደኛ አበው ቀብረዋታል::
††† አምላከ ቅዱሳን ብርሃን ፍቅሩን ይላክልን:: ከወዳጆቹ ክብርም ያሳትፈን::

††† ታሕሳስ 14 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ዕለተ ብርሃን
2.ቅዱስ መርምሕናምና እህቱ ሣራ
3."40" ሰማዕታት (የቅዱሱ ተከታዮች)
4."170,000" ሰማዕታት (የቅዱሱ ሠራዊት)
5.ቅድስት ነሣሒት ቡርክት
6.ቅዱስ ስምዖን ሰማዕት
7.ቅዱስ አሞንዮስ ሰማዕት
8.አባ ገብረ ክርስቶስ ሊቀ ዻዻሳት

††† ወርሐዊ በዓላት
1.አቡነ አረጋዊ (ዘሚካኤል)
2.አባ ስምዖን ገዳማዊ
3.አባ ዮሐንስ ጻድቅ
4.ቅዱስ ፊልዾስ ሐዋርያ (ከ72ቱ አርድእት)
5.ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ መርዓዊ
6.ቅዱስ ሙሴ መርዓዊ

††† "ብርሃን ወደ ዓለም መጥቷልና:: ሰውም ሥራው ክፉ ስለ ሆነ ከብርሃን ይልቅ ጨለማን መርጧልና:: ሥራው ክፉ የሆነ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና:: ክፉም ስለ ሆነ: ሥራው እንዳይገለጥበት ወደ ብርሃን አይመጣም:: እውነትን የሚሠራ ግን ሥራው ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል:: ስለ እግዚአብሔር ብሎ ይሠራልና::" †††
(ዮሐ. 3:19)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
Audio
ገድለ አቡነ አረጋዊ ዘወርሃ ታህሣሥ
https://www.tg-me.com/SinkisarZekidusan2
Encoderbot file id99420 64k
ስንክሳር ዘወርሃ ታህሣሥ አሥራ አራት(፲፬)
https://www.tg-me.com/SinkisarZekidusan2
õ  a e( ­-5v5 ­ Õ+M  •õ `¨
ASR by NLL APPS
ገድለ አቡነ ገብረ ክርስቶስ ከምዕራፍ ፩ በከፊል
@SinkisarZeKidusan2
Daniel:
<<< ታሕሳስ 15 >>>

=>+"+ እንኩዋን ለአበው ቅዱሳን "ጐርጐርዮስ ዘአርማንያ" እና "አቡነ ኤዎስጣቴዎስ" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ +"+

+*" ቅዱስ ጐርጐርዮስ ዘአርማንያ "*+

=>ይህ ቅዱስ አባት ከሰማዕታት: ከጻድቃን: ከሊቃውንትና ከዻዻሳት ዝርዝር ውስጥ ይገኛል:: በቤተ ክርስቲያንም ዓበይት ከሚባሉ አበው አንዱ ነው:: ቅዱስ ጐርጐርዮስ ሮማዊ ሲሆን ከክርስቲያን ወላጆቹ የተወለደው በዘመነ ሰማዕታት (በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን) ነው::

+አበው በትውፊት እንደ ነገሩን ከሆነ ቅዱሱ የታላቁዋ ሰማዕት ቅድስት አርሴማ ትልቅ ወንድም ነው:: በዜና ሰማዕታት ተጽፎ እንደሚገኘው በዚያ የመከራ ዘመን ቅዱስ ጐርጐርዮስ ሦስት ኃላፊነቶች ነበሩበት:-

1.ቅድስት አርሴማን ጨምሮ ደናግሉን ማጽናት:
2.ትምሕርተ ቤተ ክርስቲያንን በሚገባ ማጥናት:
3.የሚመጣውን መከራ ለመቀበል ራሱን ማዘጋጀት::

+ቅዱሱ 3ቱንም ኃላፊነቶች በሚገባ በመወጣቱ ከራሱ አልፎ ለሌሎቹ አርአያ መሆን ቻለ:: ያቺን ንጽሕት አርበኛ ቅድስት አርሴማንም አጽንቶ የደናግሉ መሪ አደረጋት:: መከራው በጣም ገፍቶ እስከ መጣበት ጊዜ ድረስ በአንድ የደናግል ገዳም ውስጥ ሆነው ይጸልዩ: ይጾሙ: ገዳማዊ ሥራንም ይሠሩ ነበር::

+ለዚህም ነው ቅድስት አርሴማና ቅዱስ ጐርጐርዮስ ጻድቃን የምንላቸው:: በሁዋላ ግን ማሕደረ ሰይጣን ዲዮቅልጢያኖስ በመልኩዋ ተማርኮ ቅድስት አርሴማን ካላገባሁ በማለቱ ቅዱስ ጐርጐርዮስ ድንግሏን አርሴማን ጨምሮ ክርስቲያኖችን ይዞ ወደ አርማንያ ተሰደደ::

+በአርማንያም በአንድ ገዳም ውስጥ ተደብቀው በጾምና በጸሎት ለጥቂት ጊዜ ቆዩ: ነገር ግን ረሃብ ፈጃቸው:: የሚላስ የሚቀመስ ነገር በአካባቢው ባለ መኖሩ ቅዱስ ጐርጐርዮስ ወደ ከተማ ለመውጣት ተገደደ::

+በዚያም በድርጣድስ ቤተ መንግስት ውስጥ ባርነት ተቀጠረ:: በሚያገኛት ገንዘብም ወገኖቹን ይረዳ ነበር:: መከራው ግን አለቀቃቸውም:: ርጉም ዲዮቅልጢያኖስ ቅዱሳኑ ወደ አርማንያ መሔዳቸውን ስለ ሰማ ይዞ እንዲልክለት ድርጣድስን ላከው::

+ድርጣድስ ግን ቅድስት አርሴማን ባያት ጊዜ ከውበቷ የተነሳ መታገስ ባለመቻሉ "ካላገባሁሽ" አላት:: ድንግሊቱ ግን "እኔ የክርስቶስ ሙሽራ ነኝ: አይሆንም" አለችው:: ሊያስፈራራት ሞከረ:: ዐይኗ እያየ ደናግሉን ጨፈጨፋቸው::

+አልሳካልህ ቢለው በአደባባይ በግድ ሊያገባት ቢሞክር እጁን ጠምዝዛ በሰው ሁሉ ፊት መሬት ላይ ጣለችው:: እጅግ ስላፈረ አስገረፋት: አሰቃያት: ዐይኗንም አወጣ:: በመጨረሻም አንገቷን አስቆርጦ ከሰማዕታቱ ጋር ተራራ ላይ ጣላት::

+ወዲያው ደግሞ የቅዱስ ጐርጐርዮስ ማንነቱ በመታወቁ ይዘው አካሉ እስኪያልቅ ገረፉት:: በእሳትም አቃጠሉት:: በብዙ ስቃይም አሰቃዩት::

+በመጨረሻ ግን ከነ ሕይወቱ እንዲቀበር ተወሰነበት:: ወደ መጸዳጃ ቤት ወስደውም ከነ ሕይወቱ ቀበሩት:: ነገር ግን የእግዚአብሔር መልአክ ወርዶ መተንፈሻ ቀዳዳን ሠራለት:: አንዲት ሽማግሌ ክርስቲያንም በዚያች ቀዳዳ ቂጣ እየጣለችለት ለ15 ዓመታት ተቀብሮ ኖረ::

+አካሉና አፈሩ ተጣበቀ:: እርሱ ግን ፈጣሪውን እያመሰገነ ቆየ:: ከነገር ሁሉ በሁዋላ ድርጣድስና ባለሟሎቹ ለአደን በሔዱበት ርኩስ መንፈስ ወደ አውሬነት (እሪያነት) ቀየራቸው::

+የንጉሡ እንስሳ (አውሬ) መሆን በአርማንያ ታላቅ ድንጋጤን ፈጠረ:: የንጉሡ እህት ስታለቅስ በራዕይ "ለእመ ኢያዕረግምዎ ለጐርጐርዮስ አልብክሙ ድኂን-ጐርጐርዮስን ከተቀበረበት ካላወጣችሁት አትድኑም" አላቸው:: ወዲያውም በዚያች ሽማግሌ መሪነት ቆፍረው አወጡት::

+አካሉንም እግዚአብሔር መለሰለት:: ቅዱሱ እንደ ወጣ ዕረፍትን አልፈለገም:: ለ15 ዓመታት ቀባሪ አጥቶ የተበተነውን የቅድስት አርሴማንና የሰማዕታቱን አጽም ሰብስቦ በክብር አኖረው:: ድርጣድስና ባለሟሎቹንም ወደ በርሃ ሒዶ ፈወሳቸው::

+ወደ ሰውነትም መልሶ መላ አርማንያን ወደ ክርስትና መለሰ:: የንጉሡን እግር ግን የአውሬ አድርጐት ቀርቷል:: በመጨረሻም ቅዱስ ጐርጐርዮስ የአርማንያ ሊቀ ዻዻሳት ሆኖ ተሹሞ ብዙ መጻሕፍትን ደረሰ:: ከ318ቱ ሊቃውንትም አንዱ ሆኖ ተቆጠረ:: ዛሬ ታሕሳስ 15 ቀን ዕረፍቱ ነው::

+*" አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ረባን "*+

=>ሐዋርያዊው ጻድቅ ኢትዮዽያዊ (ኤርትራዊ) ሲሆኑ በዓለም ደረጃ የሚታወቅ አገልግሎት ያላቸው አባት ናቸው:: በመካከለኛው ዘመን የኢትዮዽያ ታሪክ የኤወስጣቴዎስንና የተክለ ሃይማኖትን ያህል ስሙ የጐላ ጻድቅ አይገኝም::

+ጻድቁ በ1265 ዓ/ም አካባቢ እንደ ተወለዱ ሲታመን ወላጆቻቸው ክርስቶስ ሞዐና ስነ ሕይወት ይባላሉ:: የጻድቁ የመጀመሪያ ስም "ማዕቀበ እግዚእ" (ለጌታ የተጠበቀ) ነው:: ኤዎስጣቴዎስ የተባሉ በሁዋላ ነው::

+ገና ከልጅነታቸው መንፈሰ እግዚአብሔር አድሮባቸዋልና ለዚህ ዓለም ግድ አልነበራቸውም:: ከመምሕር ዘንድ ገብተው: ቅዱሳት መጻሕፍትን ተምረው: ዲቁናን ተቀብለው ያገለግሉ ገቡ:: በዲቁና አገልግሎታቸው ስሉጥ (ፈጣን) በመሆናቸውም የዘመኑ አበው "ዳግማዊ እስጢፋኖስ" እያሉ ይጠሯቸው ነበር::

+ከዚያ በወጣትነት እድሜአቸው ምናኔን መርጠው: ጾምና ጸሎትን ከስግደት ጋር አዘወተሩ:: እንዲህ ባለ ሕይወት ሳሉ አንድ ቀን ለስም አጠራሩ ጌትነት ይሁንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ዘንድ መጣ::

+በዘባነ ኪሩብ: በግርማው ቢያዩት ደነገጡ:: ጌታ ግን "ወዳጄ ኤዎስጣቴዎስ! ገና ከእናትህ ማሕጸን መርጬሃለሁ:: ከኢትዮዽያ እስከ አርማንያም ሐዋርያ ትሆን ዘንድ ሹሜሃለሁ:: "ዘኪያከ ሰምዐ: ኪያየ ሰምዐ . . . አንተን የሰማ እኔን ሰማ:: አንተን እንቢ ያለ እኔን እንቢ አለ::" ብሏቸው: ባርኩዋቸው ዐረገ::

+ጻድቁ ፈጣሪያቸውን ስለ ስጦታው እያመሰገኑ ቅስናን ተቀብለው ስብከትን ጀመሩ:: ስም አጠራራቸውም ፈጥኖ በሃገሪቱ ተሰማ:: በየቦታው እየዞሩ ያላመነውን አሳምነው እያጠመቁ: ያመነውን በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እያጸኑ: ሕይወተ ገዳምን እያስፋፉ ኖሩ::

+አሁን ኤርትራ ውስጥ የሚገኘውንና እርሳቸው የመሠረቱትን ገዳም ጨምሮ ለገዳማዊ ሕይወት መስፋፋት አስተዋጽኦ አድርገዋል:: በገዳማቸውም አባ አብሳዲን ጨምሮ በርካታ አርድእትን አስተምረዋል: አፍርተዋል::

+አቡነ ኤዎስጣቴዎስ በተለይ የሚታወቁት ቀዳሚት ሰንበት እንዳትናቅ (እንድትከበር) ባደረጉት ጥረት ነው:: ደግሞም ተሳክቶላቸዋል:: ቅርብ ጊዜ ከምናየው የድፍረት ሥራ በቀር በሃገራችን 2ቱም ሰንበቶች ክቡር ናቸው::

+አቡነ ኤዎስጣቴዎስ 2 ጊዜ ወደ ኢየሩሳሌም በእግራቸው ተጉዘዋል:: መሔዳቸው ግን ለመሳለም ብቻ አይደለም:: ይልቁኑ የወንጌል ዘርን እየዘሩ: ፍሬውንም እየለቀሙ እንጂ:: እርሳቸው መቼም ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን ቸል አይሉምና::

+በመጨረሻ ሕይወታቸውም በገዳማቸው ላይ ደቀ መዝሙራቸውን አባ አብሳዲን ሹመው ለአዲስ ጉዞ ተነሱ:: እኩሎች ልጆቻቸውን በገዳማቸው ትተው እኩሎችን አስከትለው ጉዞ ወደ አርማንያ ተደረገ::

+በመንገድም ወደ ባሕረ ኢያሪኮ ሲደርሱ የሚሻገሩበት መርከብ አጡ:: ድንቅ አባት ናቸውና በእምነት አጽፋቸውን (ኩታቸውን) አውልቀው ባሕሩ ላይ ጣሉት:: በላዩ ላይም በትእምርተ መስቀል አማትበው ተቀመጡበት::

+ደቀ መዛሙርቶቻቸውም ባሕሩ ላይ በተነጠፈው ኩታ ላይ ከበው ተቀመጡ:: ከሰማይም ጌታችን ወርዶ በመካከላቸው ቆመ:: ሚካኤል በቀኝ ገብርኤልም በግራ ቆሙ:: ጻድቁ ደግሞ ልጆቻቸውን ያስተምሯቸው: ይተረጉሙላቸው ገቡ::
+በመካከል ግን አንዱ (የማነ ብርሃን ይሉታል በቅኔ ቤት) በመጠራጠሩ እርሱ የተቀመጠባት ብቻ ተቀዳ ሰጠመ:: በሁዋላ ግን ጻድቁ ተመልሰው አውጥተው: ከሞት አስነስተውታል:: በዚህም ምክንያት 'ዘአደወ ባሕረ-ማዕበልን የተሻገረ' ይባላሉ::

+አቡነ ኤዎስጣቴዎስ በአርማንያ ለዘመናት ሰብከው: ሕይወተ ገዳምን አስፋፍተው: ብዙ ተአምራትን ሠርተው: በተወለዱ በ80 ዓመታቸው: በ1345 ዓ/ም ዐርፈዋል:: በብዙ ዝማሬ በመቅደሰ መርምሕናም ተቀብረዋል:: በኢትዮዽያ: ኤርትራ: ግብጽና አርማንያ ይከብራሉ:: ዛሬ ጻድቁ ማዕበሉን የተሻገሩበት መታሰቢያ ቀን ነው::

=>አምላከ ቅዱሳን ስለ አባቶቻችን ሲል በምሕረቱ ይጐብኘን:: ከበረከታቸውም ያሳትፈን::

=>ታሕሳስ 15 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ጐርጐርዮስ ሊቅ (ዘአርማንያ)
2.አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ረባን
3.ቅዱስ ሉቃስ ዘዓምድ
4.አባ ይምላህ

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ (አፈ በረከት)
2.ቅድስት እንባ መሪና
3.ቅድስት ክርስጢና
4.ቅዱስ ሚናስ ሰማዕት
5.ቅዱስ ቂርቆስ ሰማዕት
4.ብጽዕት ኢየሉጣ ሰማዕት

=>+"+ ጻድቃን ጮሁ:: እግዚአብሔርም ሰማቸው::
ከመከራቸውም ሁሉ አዳናቸው::
እግዚአብሔር ልባቸው ለተሰበረ ቅርብ ነው::
መንፈሳቸው የተሰበረውንም ያድናቸዋል::
የጻድቃን መከራቸው ብዙ ነው::
እግዚአብሔርም ከሁሉ ያድናቸዋል::
እግዚአብሔር አጥንቶቻቸውን ሁሉ ይጠብቃል:: +"+ (መዝ. 33:17)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
2024/09/30 22:23:03
Back to Top
HTML Embed Code: