Telegram Web Link
❖ ሰማዕታቱም አርማንያ አገር እንደደረሱ ጭፍሮቹ የሰማዕታቱን እግሮቻቸውንና እጆቻቸውን እንዳሠሯቸው ለንጉሥ ድርጣድስ አስረኩቧቸው፤ መኮንኑም ለንጉሡ ‹‹ጌታዬ ሆይ እነሆ አንተ የምታመልካቸውን ጣዖቶችህን የማያመልኩትን ብዙ ክርስቲያኖችን ሰቀልናቸው፣ ገደልናቸው፤ የቀሩትንም እየገረፍን ይኸው ከፊትህ አቁመናቸዋል የወደድከውን አድርግባቸው፡፡
❖ አንዲትም ውብ ሆነች ሴት ልጅ አብራቸው መከራ መቀበልን መርጣ መጥታለች የመልኳንም ማማርና ደም ግባቷን ባየን ጊዜ ደንግጠን በእርሷ ላይ አንዳች ክፉ ማድረግ አልተቻለንም›› አለው፡፡
❖ ንጉሡም ያመጧት ዘንድ ሲነግረው መኮንኑ ‹‹ነገር ግን ጌታዬ ሆይ እርሷ በመልክ የሚስተካከላት የሌለ እጅግ ውብ ብትሆንም ‹ከሕይወት ይልቅ መሞት ይሻለኛል› ይምትል ናት›› አለው፡፡
❖ ከዚህም በኋላ ሰማዕታቱን ወደ እሥር ቤት በመውሰድ ቅድስት አርሴማን ግን ይዘው ወደ ንጉሡ ዘንድ አመጧት፤ እርሷም ወደ ንጉሡ አዳራሽ እያማተበች ስትገባ ንጉሡ ባየት ጊዜ ልቡ ታወከ፡፡
❖ ሰማዕቷ ግን ‹‹ከሰማያትና ከምድር ንጉሥ ከእግዚአብሔር አምላኬ ትለየኝ ዘንድ የወደድክ ሰነፍ ንጉሥ ሆይ የሰይጣን መልአክተኛና የጥፋት ልጅ የይሁዳ ወገን ከእኔ ምን ትሻለህ? ከወደድክስ በእጅህ ሰማዕት እሆን ዘንድ እወዳለሁ›› አለችው፡፡
❖ ከዚህም በኋላ ሰማዕቷ በጸለየች ጊዜ ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል በታላቅ ግርማ ተገለጡላት ነገር ግን ቅድስት አርሴማ ‹‹ጌቶች ሆይ! ነፍሰ ገዳይ እንዳልባል በማንም ላይ ጥፋት አይድረስ›› ብላ ለመነቻቸው፤ ሊይዟት የመጡት ሰዎችም ግርማዋን አይተው ፈሩ፤ ሰውነቷንም ቀርበው እንዳይነኳት የመለኮት ኃይል ከለከላቸው፡፡
❖ እነርሱም ‹‹ይህች ሴት አስማተኛ ናት፣ ጥበብና ምትሃት አላት›› ብለው ለንጉሡ በነገሩት ጊዜ እርሱም ‹‹ዛሬ ያሸነፍሽኝ እንዳይመስልሽ ነገ ብርቱዎች በሆኑ አማልክቶቼ ኃይል ድል አደርግሻለሁ›› አላት፤ እርሷም ‹‹ዛሬም ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ይረዳኛል፣ በእኔ በኃጢአተኛይቱና በደካማይቱ ኃይል አይደለም፤ በእነዚህ ቅዱሳን ሰማዕታት የጸሎት ኃይል እንጂ›› በማለት መለሰችለት፡፡
❖ ሰማዕታቱም ከቅድስት አርሴማ ጋር በእሥር ቤት ሳሉ ‹‹የእግዚብሔርን ኃይል በአንቺ ላይ አይተናልና በጸሎትሽ አስቢን›› አሏት፤ እርሷም ‹‹በገድላችሁ ብርታት ለእኔ ጸልዩልኝ›› አለቻቸው፡፡
❖ ቅድስት አርሴማ ሌሊት ታላቅ ምሥጢርን አየች፤ እልፍ አእላፋት የብዙ ብዙ የሚሆኑ ቅዱሳን መላእክት የሥላሴን ዙፋን ከበው ‹‹የጌትነትህ ምስጋና ሰማይንና ምድርን መላ ፍጹም አሸናፊ እግዚአብሔር ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ›› እያሉ ሲጮኹ ተመለከተች፡፡
❖ ይህንንም የመላእክትን ዜማ እንደሰማችና እንዳየች ለሰማዕታቱ ነገረቻቸው፤ ‹‹ከእነዚህም መላእክት ውስጥ አንዱ ወደ እኔ ተልኮ መጣና በቀኜ ቆሞ በጥላው ሸሽጎ የሕይወትን እንጀራ መግቦኝ የድኅነትን ጽዋ አጠጣኝ፤ ያንጊዜም ሥጋዬ ወደ ምድር ወረደ፣ በላዬም ነፍሴ ተመለሰቸ፤ ከእንቅልፍ እንደሚነቃና የወይን ጠጅ ጠጥቶ ስካሩ እንደተወው ሰው ነቃሁ›› አለቻው፡፡
❖ በነጋም ጊዜ ንጉሡ በፍርዱ ዙፋን ተቀምጦ ሰማዕታቱን ከእሥር ቤቱ አውጥተው ወደ ፍርድ አደባባይ ያመጧቸው ዘንድ አዘዘ፤ በፊቱም አቁሞ ለጣዖታት አማልክቶቹ እንዲሰግዱና እንዲሠው አዘዛቸው፡፡
❖ እነርሱም ‹‹እኛስ የምናመልከው እውነተኛ አምላክ አለን ለረከሱ ጣዖታት አንገዛም›› ባሉት ጊዜ ‹‹ትእዛዜን ካልፈጸማችሁ ሰውነታችሁን በትንሽ በትንሹ እየቆራረጥኩ እጥለዋለሁ›› አላቸው፡፡
❖ ሰማዕታቱም ‹‹በሚያስፈራ ቃልህና በቅጣትህ የምንፈራና አምላካችንን ክርስቶስን የምክደው አይደለንም፡፡
❖ ስለ አምላካችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነፍሳችንን እንሰጥ ዘንድ ወደ አንተ መጥተናል›› አሉት፤ ያን ጊዜም ንጉሡ ድርጣድስ እጅግ ተቆጥቶ ‹‹ይህችን ሴት በማስቀደም ጽኑ ቅጣት ቅጧቸው የምታስተምራቸው እርሷ ናትና›› ብሎ አዘዘ፡፡
❖ ጭፍሮቹም ‹‹የሴት ልቧ ደካማ ነውና ቅድሚያ ወንዶችን አሠቃይተን ብንገድል ሴቶቹ ለጣዖቶችህ ይገዛሉ›› በማለት ወንዶቹን ለብቻ ወስደው ለተራቡ አንበሶችና ሌሎች አውሬዎች ሰጧቸው፡፡
❖ ቅድስት አርሴማም አጽናናቻቸውና ተሰነባብተው ወደ ሰማዕትነት ገቡ፤ ነገር ግን የተራቡት አንበሶችና ሌሎችም አውሬዎች ወደ ሰማዕታቱ መቅረብ አልተቻላቸውም ይልቁንም በሰማዕታቱ ፊት ሰገዱላቸው፤ በጅራታቸውም እየዳሰሷቸው አጫወቷቸው፡፡
❖ የቅድስት አርሴማንም የእግሯን ትቢያ ላሱ፤ እርሷም በእጆቿ ዳሰሰቻቸው፤ አውሬዎቹም ብረቱን እየበጠሱ ንጉሡ ከመንግሥቱ ዙፋን እስኪወድቅ ድረስ አባረሩት፤ ወታደሮቹንም ሲያባርሯቸው ከእነርሱ ውስጥ 300 ጭፍሮች ሞቱ፤ የተረፉትም ይህንን ተአምር ሲያዩ እጅግ እያደነቁ ሰማዕታቱ ምትሃተኞች መሆናቸውን ተናገሩ፤ ይልቁንም ቅድስት አርሴማን ‹‹እርሷ መመኪያቸውና መሪያቸው ናትና አስቀድመን እንግደላት›› አሉ፡፡
❖ ከዚህም በኋላ ጥልቅ ጉድጓድ ቆፍረው በውስጡ እሳትን አንድደው ሰማዕታቱን ከዚያ ይጨምሯቸው ዘንድ ሲመክሩ ንጉሡ በዚህ ምክራቸው ደስ ተሰኘ፤ እንደምክራቸውም ጥልቅ ጉድጓድ ቆፍረው በውስጡ እሳት አንድደው የተለያዩ ሰውነትን ቆራርጠው የሚጥሉ እንደ ዲን፣ ሙጫ፣ ቅንጭብ ጨምረው የእሳቱ ነጎድጓድ እስኪሰማ ድረስ አንድደው ሰማዕታቱን ከዚያ እንዲጨምሯቸው ንጉሡ አዘዘ፡፡
❖ ቅድስት አርሴማንም ‹‹አሁን ከዚህ ማን እንሚያድንሽ አያለሁ›› አላት፤ እርሷም ‹‹እኛንስ አምላካችን እንደሚያድነን አሁን ታያለህ አንተ ግን ከዚህ ክፋትህ ካልተመልስክና ጣዖት ማምለክህን ትተው እውነተኛውን አምላክ ካላመለክህ በኋላ ከዘላለማዊው እሳት ወዴት ትሸሻለህ በማስ ትማጸናለህ በዕንጨት ነውን ወይስ በድንጋይ …. ›› በማለት ስለ ዕለተ ምጽዓት ሌላም ብዙ ነገር አስተማረችው፡፡
❖ በዚህም ጊዜ ከወታደሮቹ አንዱ ተነሥቶ በኃይል ሲመታት ከአፍንጫዎቿ ደም እንደ ውኃ ፈሰሰ፤ ንጉሡም ‹‹በዚህ የምተውሽ አይደለሽም ሥጋሽን በእሳት አቃጥለዋሁ›› በማለት ተናገራት፡፡
❖ ያንጊዜም ምድር አፏን ከፍታ ያንን የመታትን ወታደር ዋጠችው፤ ይህንንም ያዩ ሁሉ በማድነቅ እጅግ ፈሩ፤ ንጉሡም ፈርቶ ከዙፋኑ ላይ ፈጥኖ ተነሣ፡፡
❖ ቅድስት አርሴማም ፈገግ ብላ በእርሱ ይመጣ ዘንድ ያለውን ነገር ትንቢት ነገረችው ‹‹እግዚአብሔር ስለ እኛ ይበቀልሃል፣ የአጋንንትም ማደሪያ ያደርግሃል፣ እንደ ጅብ በራስህ ሥጋህን እስከምትበላ ድረስ ያሳብድሃል፡፡
❖ መልክህና ምሳሌህ ይለወጣል፣ እንደ በረሃ እሪያም ትሆናለህ፣ የምትናገረውን አታውቅም፣ የእርኩሳን አጋንንት የእግራቸው መረገጫ ትሆናለህ፤ ያንጊዜም የሙታንን ትንሣኤ ተስፋ ትታመን ዘንድ አለህ ይህ እንደሚሆንብህ በእውነት እነግርሃለሁ›› አለችው፡፡
❖ ንጉሡም ይህን ጊዜ ‹‹እናተን በክፉ ቅጣት አሠቃይቼ ከገደልኩ በኋላ ይህን አሁን ያልሽውን ብሆን አይሳዝነኝም›› አላት፤ ይህንንም ሲነጋገሩ ወታደሮቹ መጥተው የእሳቱ ነበልባል ከሩቅ እስኪታይ ድረስ እንደነደደ ነገሩት፤ እርሱም ሰማዕታቱን ከእሥር ቤት አውጥተው በማምጣት ከቅድስት አርሴማ ጋር በእቶኑ እሳት ውስጥ ይጥሏቸው ዘንደ አዘዘ፡፡
❖ ቅድስት አርሴማም ሰማዕታቱን ካጽናናቻቸውና ከመከረቻቸው በኋላ በመስቀል ምልክት አማትባ ማንም ገፍቶ ሳይጨምራት ራሷን ወደ እሳቱ ውስጥ ወረወረች፤ ቀጥሎም ዲያቆን ጤሜልዮስ ወደ እሳቱ ተወርውሮ ገባ፡፡
❖ ታላቃቸው ጌርሎስም እንዲሁ ራሱን ወርውሮ ወደ እሳቱ ውስጥ ገባ፤ ሁሉም እንዲሁ በየተራ ራሳቸውን እየወረወሩ ገቡ፤ በጎች ወደ ወንዝ ውኃ እየሮጡ እንደሚገቡ ሁሉም ሰማዕታት ራሳቸውን እየወረወሩ ወደ እቶኑ እሳት ገቡ፡፡
❖ ይህንንም ሲያደርጉ ያዩአቸው ወታደሮች ሁሉ በሀዘኔታ አለቀሱላቸው፤ ነገር ግን ወዲያው ሰማዕታቱ ከእሳቱ ውስጥ ሆነው እግዚአብሔርን በሰላም ሲያመሰግኑ አዩአቸውና እጅግ ተደነቁ፤ ቅድስት አርሴማም በዚያ ላሉት ሁሉ ወደፊት በንጉሡ ላይ የሚሆነውን ነገር በትንቢት ነገረቻቸው፡፡
❖ ከዚህም በኋላ ንጉሥ ድርጣድስ ቅድስት አርሴማን እንደበቀሉለትና እንዲያጠፉለት ወደ አማላከቶቹ ቤት ይወስዷት ዘንድ የሠራዊቱን አለቆች አዘዛቸው፤ ወደ አማልክቶቹም ቤት በወሰዷት ጊዜ በዚያ ሆና ስትጸልይ በወንዶች አምሳል የተሠሩ 77 እና በሴቶች አምሳል የተሠሩ 33 ጣዖታት ሁሉ ተሰባበሩ፡፡
❖ ከአንገታቸው የተሰበሩ አሉ፣ እግሮቻቸውና እጆቻቸው የተሰበሩ አሉ፣ ወገባቸው የደቀቁ አሉ፣ እንደትቢያም የተነተኑ አሉ፤ በምድርም ታላቅ ንውጽውጽታ ሆነ፡፡
❖ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም እንደመብረቅ ባለ ድምጽ መጥቶ ምድሪቱን መላትና በዚያ ያሉ ጣዖታት በሙሉ እንደትቢያ ጠፉ፡፡
❖ ቅድስት አርሴማም ይህንን ባየች ጊዜ ደስ ተሰኝታ የሆነውን መጥቶ ያይ ዘንድ ወደ ንጉሡ ላከችበት፡፡
❖ ንጉሡም በመጣ ጊዜ ‹‹አምላኬ መልአኩን ልኮ አዳነኝ፣ ጣዖታቶችህንም እንዳልነበሩ አደረጋቸው እህግዲህስ እፈር›› አለችው፡፡
❖ ንጉሡም ‹‹በምትሃትሽ ይህንን እንዳደረግሽ አውቀለሁ›› አላትና ወደ እስር ቤት ወስዶ ከሰማዕታቱ ጋር ጨመራት፤ ሰማዕታቱም በእስር ቤት ሆነው እህልና ውኃ ከቀመሱ ሰባት ቀን ሆኗቸዋልና ርሀቡና ጥሙ እጅግ ጠናባቸው፡፡
❖ ያንጊዜም ቅድስት አርሴማ ተነሡ እንጸልይ አለቻቸውና ቢጸልዩ ብርናኤልና አቅናኤል በሚባሉ ሁለት ቅዱሳን መላእክት እጅ ሰማያዊ ኅብሥትባ የገነት ውኃ መጣላቸው፤ ከመካከላቸውም ካህኑ ኢያሴኖስ ባርኮ ለሌሎቹ ሰማዕታት ሰጣቸውና ተመግበው ፈጣሪያቸውን አመሰገኑ፡፡
❖ የተረፋቸውም ኅብሥት በመላአክቱ እጅ ወደ ሰማይ ወጣ፤ በማግሥቱም ንጉሡ ወደ ፍርድ አደባባይ ባወጣቸው ጊዜ ሰማዕታቱ ፊታቸው እንደፀሐይ ያበራ ነበር፡፡
❖ የእሥር ቤት ጠባቂውንም ጠርቶ ‹‹እህል ያበላሃቸውና የነገሥታትን ልብስ ያለበስካቸው ለምንድነው› ብሎ ተቆጣው፤ ጠባቂውም ‹‹ጌታዬ ሆይ እነርሱስ ሳይበሉ ሳይጠጡ ይረካሉ እንጂ የሰጠኃቸው ምንም ነገር የለም›› አለው፤ ቃሉንም በመሐላ ካጸናለት በኋላ ‹‹ነገር ግን ንጉሥ ሆይ በሌሊት እሥር ቤት በብርሃን ተጥለቅልቆ አይቼዋለሁ፡፡
❖ ዳግመኛም ሃያ ሰባት የብርሃን አክሎችም ሲወርዱ አየሁ›› አለው፤ ቀጥሎም ይህ ጠባቂ ‹‹ንጉሥ ሆይ እኔም በእነዚህ ሰማዕታት አምኛለሁ›› አለው፡፡ ወደ ቅድስት አርሴማም ዞሮ ‹‹እመቤቴ ሆይ በጸሎትሽ አስቢኝ›› በማለት ሌሎቹንም ሰማዕታት ተመጸናቸው፡፡
❖ ቅዱሳን የሆኑ ሰማዕታቱም ይህን አደነቁ ሰማዕትነትን በመፈጸም ቀድሟቸዋልና፤ በድኑንም በምድረ በዳ ጣሉት ነገር ግን አውሬዎችና አሞራዎች አልበሉትም ቅዱሳን መላእክት ይጠብቁታልና፡፡
❖ ንጉሡም ሰማዕታን በጽኑ ዱላዎች ካስደበደባቸውና ለእያንዳንዳቸው ሌላ ሦስት ሦስት መቶ ግርፋት ካስገረቸው በኋላ ወደ እሥር ቤት መለሳቸው፤ በመግስቱም ቅድስት አርሴማን አስመጥቶ ከእርሱ ጋር ትሴስን ዘንድ አባበላት፡፡
‹‹ንግሥት አድርጌሽ በወርቅ ዙፋኔ ላይ ትቀመጫለሽ፣ በአርማንያ ካሉ ሴቶች ሁሉ በላይ አደርግሻለሁ…›› እያለ አባበላት፡፡
❖ ቅድስት አርሴማ ግን ‹‹ልብህ የደነደነ ሰነፍ ሆይ ኃጢአትህን ሁሉ ይቅር ይልህ ዘንድ ወደ አምላክህ እግዚአብሔር ትመለስ ዘንድ በተሻለህ ነበር …›› እያለች አስተማረችው፡፡
❖ ስለ ጌታችንም መንገሥት ካስተማረችው በኋላ ‹‹እኛ ሰማዕታቱ ስለ አንተ እንጸልይልሃለን›› አለችው፡፡
❖ ንጉሡ በዚህ ጊዜ ‹‹ማመኔን ብትወጂ ግን ከእኔ ጋር ተስማምተሽ እንጋባለን ለአምላክሽም እገዛለሁ›› ሲላት ወዲያው እርኩስ መንፈስ ፊቱን መታውና ‹‹ከእናትህ መኅፀን ጀምሮ ያሳደኩህና በሥራህ ሁሉ ልብ፣ አፍና ብርታት ሆኜ በኃይሌም ብርታት የክርስቲያን ልጆችን እንድታስጨንቃቸውና እንትገድላቸው ያደረኩህን እኔን ለምን ተውከኝ፤ ስለዚህች ሴት ብለህ እግዚአብሔር አምላክን ታመልክ ዘንድ ወደድክን...›› እያለ በቁጣ ሆኖ አፉን አጣመመውና ምድር ላይ ጣለው፡፡
❖ ከዚህም በኋላ ለጣዖታቱ ይሰግዱ ዘንድ ሰማዕታቱን በቁጣ አዘዛቸው፤ ነገር ግን የጣዖታቱ ካህናት መጥተው ጣዖታቱን ቅድስት አርሴማ እንዳጠፋቻቸው ነገሩት፤ ዳግመኛም ‹‹እርሷን ካልገደልካት አገራችን ትጠፋለች፣ መንግሥትህ ተሻራላች›› አሉት፡፡
❖ ከዚህም በኃላ ከቅድስት አርሴማ ጋር ያሉትን 27ቱን ሰማዕታት ስሙ ጋብጋቦ ወደሚባል ወንዝ ወስደዋቸው አንገታቸውን በሰይፍ ቆረጧቸውና የሰማዕትነት ፍጻሜአቸው ሆነ፤ ከእነርሱም አንደኛውን በቅድሚያ አንገቱን ሲቆርጡት ሥጋው ወደ ምድር ወደቀ፤ ራሱ ግን ለብቻ ለአንድ ሰዓት ያህል ቆመች፡፡
❖ ቡርክት ቅድስት አርሴማም ሮጣ ሄዳ የሰማዕቱን በርቲኖስን ራስ ያዘቻትና ወደ አንገቱ መለሰቻት፤ እርሱም "ሰማዕት ለመሆን እኔን ስላስቀደመ አምላኬ እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ" እያለ ሦሰት ጊዜ ተነፈሰ፡፡
❖ ለቅድስት አርሴማም "እመቤቴ ሆይ መምጣትን እንዲያፋጥኑ ከፀሐይ ይልቅ የምታበራ አገርን እንዲያዩ ለወንድሞቻችን ለእኅቶቻችን ነገሪያቸው" አላት፤ እርሷም ወደ ሰማዕታቱ ዞራ "ወንድማችን በገነት ያየውን ይነግረንና ያሳየን ዘንድ በሕይወት ኖሯል እንጂ አልሞተም" አለቻቸው፡፡
❖ ከዚህም በኃላ ሰማዕታቱ እግዚአብሔርን አመስግነው "እኔ አስቀድሙ እኔ አስቀድሙ..." እያሉ ወታደሮቹን ለመኗቸው፤ እየተሻሙ በየተራ እየተሰየፉ ሰማዕትነታቸውን ፈጽመው የክብር አክሊልን ተቀዳጁ።

❖ ቅድስት አርሴማም የሰማዕታቱን ራሶቻቸውን ትሰበስብ ነበር፤ ወደ ሥጋቸውም ታጋጥመው ነበር በዚያም ጊዜ እንደመጀመሪያው ይሆናል፤ እንዳልተቆረጠም ይሆናል፤ ልብሶቻቸውንም ታለብሳቸዋለች፡፡
❖ ይህንንም ታላቅ ተአምር ያዩ 92 የንጉሡ ወታደሮች ወደ ንጉሡ ሄደው "እኛም በአምላካቸው አምነን ክርስቲያን ሆነናል" በማለት መሰከሩ፡፡
❖ ንጉሡም በፈረስ ገመድ ላይ አስሮ ሥጋቸው ተቆራርሶ እስኪወድቅ ድረስ ካሠቃያቸው በኃላ አንገታቸውን ሰየፋቸውና የክብር አክሊልን ተቀዳጁ፡፡
❖ ዳግመኛም በእነርሱ ምክንያት ሌሎችም አመኑ፤ ከዚህም በኃላ ንጉሡ ቅድስት አርሴማን ውበቷን እያሰበ ልቡናውን ሳተ፤ ድንግልናዋንም ሊያረክስ ሽቶ እናቷን አጋታን እንድታባብልለት አዘዛት፡፡
❖ እናቷም ሄዳ "ልጄ ሆይ ስሚ ይህ አረማዊ እንዳያረክስሽ ተጠንቀቂ" አለቻት፤ ንጉሡም ቅድስት አርሴማን "መንግሥቴንና ግዛቴን ሁሉ አወርስሻለሁ" እያለ በመሀላ ቢለምናትም እሺ እንደማትለው ሲያውቅ ይዞ በግድ ወደ እልፍኙ ሊያስገበት ሲል ቅድስት አርሴማ ይዛ መሬት ላይ ጣለችው፤ በእርሷ ላይ ያደረ የመንፈስ ቅዱስ ኃይል ሞገስ ሆኗታልና፡፡
❖ እርሱ ግን በጦርነት እጅግ የበረታ ኃይለኛ ስለነበረ አሁን በታናሽ ሴት ብላቴና ስለተሸነፈ አፈረ፤ በዚህም እጅግ ተናዶ ለሥጋዊ ፈቃዱም እንደተመኛት ሊያገኛት ስላልቻለ ተስፋ ቆርጦ በንዴት አንገቷን ይቆርጧት ዘንድ አዘዘ፡፡
❖ የቅድስት አርሴማንም ራሷን ቆረጧትና የሰማትነት ፍጻሜዋ ሆነ፤ ከአንገቷም ደም፣ ውኃ፣ ወተትና ማር ወደ አራቱም አቅጣጫ ፈሰሰ፡፡
❖ እርሷና ሌሎቹም 72 ሰማዕታት ከተሰየፉ በኃላ ሥጋቸው ቀምድር ላይ ተጥሎ ቀረ፤ ንጉሡም ጋኔን ተጭኖበት መልኩ ተለውጦ እንደ እሪያ ሆነ፡፡
❖ ከዚያ በፊት የአርማንያውን ሊቀ ጳጳሳት አቡነ ጎርጎርዮስን ንጉሡ ድርጣድስ ዕጣን ሊያሳርግ ወደ ጣዖት ቤቱ ሲገባ አቡነ ጎርጎርዮስን ጠርቶ ለአማልክት ዕጣን አሳርጉ ቢላቸው እሳቸውም ትእዛዙን አልፈጽምም ባሉት ጊዜ እጅግ ጽኑ በሆኑ በተለያዩ ሥቃዮች ካሠቃያቸው በኃላ ጥልቅ ጉድጓድ አስቆፍሮ በዚያ ውስጥ ጣላቸው፡፡
❖ አባታችንም በዚያ ጥልቅ ጉድጓድ እንደተጣሉ ለ15 ዓመታት ኖሩ፤ ስለምግባቸውም እግዚአብሔር አንዲት እናትን አዘዘላቸው፤ በንጉሡ አዳራሽ አቅራቢያም የምትኖረው ይህች ሴት በእግዚአብሔር ታዝዛ እንጀራን እየጋገረች ወደ ጉድጓዱ ትጥልላቸው ነበር፡፡
❖ ከእርሷም በቀር አባታችን በሕይወት መኖራቸውን የሚያውቅ ሰው የለም፤ እንዲህም እያደረገች 15 ዓመት ኖራለች፡፡
❖ ንጉሡ ድርጣድስም ቅድስት አርሴማን ማግባት ፈልጎ ሳለ ፈጽሞ እምቢ ብትለው በእርሷ ምክንያት ብዙ ደናግል ሴቶችን ገደለ፡፡
❖ ሰይጣን በልቡ ያደረበት ይህ ንጉሥ ድርጣድስም ደናግሎቹን እና ቅድስት አርሴማን በብዙ ሥቃይ ከገደላቸው በኋላ ሥጋቸውን በተራራ ላይ ጥሎት ነበር፤ ነገር ግን ምንም ሳይሆን በጌታችን ጥበቃ ኖረ፡፡
❖ የቅድስት አርሴማንም ውበቷን እያሰበ ስላስገደላት የሚጸጸት ሆነ፤ ወገኖቹም ‹‹ከሀዘንህ ታርፍ ዘንድ ወደ ጫካ ሄደን አውሬ አድን›› አሉት፡፡
❖ ንጉሡም በፈረሱ ተቀምጦ ወደ ጫካ ወጣ፤ ነገር ግን ሰይጣን ተዋሃደውና በእነ ቅድስት አርሴማና በአቡነ ጎርጎርዮስ ላይ በሠራው ግፍ እግዚአብሔር የተፈጥሮ መልኩን ቀይሮት እንደ እሪያ አደረገው፡፡
❖ ንጉሥ ናቡከደነጾር ከእግዚአብሔር ቁጣ የተነሣ አእምሮው ስቶ ልቡ ተሰውሮ ወደ እንስሳነት እንደተለወጠ ሁሉ።
❖ ንጉሥ ድርጣድስም እንዲሁ ከእግዚአብሔር ቁጣ የተነሣ ወደ እሪያነት ተለወጠ፤ ንጉሡ ድርጣድስ ወደ እሪያነት ከተለወጠ በኋላ ያገኘውን ሁሉ የሚናከስ ሆነ፤ በቤተ መንግሥቱም ባሉ ሰዎች ላይ ሰይጣን አደረባቸውና ታላቅ ጭንቅ ሆነ፡፡
❖ የንጉሡም እኅት በሌሊት ‹‹ጎርጎርዮስን ከጉድጓድ ካላወጣችሁት በቀር አትድኑም›› የሚል ራእይ አየችና ለወገኖቿ ነግረቻቸው፤ የሞተ መስሏቸው ስለነበር ይህን ሲሰሙ እጅግ ደነገጡና ሄደው ቅዱስ ጎርጎርዮስን 15 ዓመት ተጥሎ ከኖረበት ጉድጓድ ውስጥ በገመድ ጎትተው አወጡትና አክብረው ወሰዱት፡፡
❖ እርሱም የእነ ቅድስት አርሴማን ሥጋ ወዴት እንዳደረሱት ሲጠይቅ በተራራው ላይ እንዳለ ነግረውት ሄዶ ሲያየው ምንም ሳይነካው በደህና አገኘው፤ አንሥቶም ባማሩ ቦታዎች አኖራቸው፡፡
❖ ሰይጣን ያደረባቸውን የቤተ መንግሥቱንም ሰዎች ፈወሳቸው፤ ስለ ንጉሡም ወደ አውሬነት መለወጥ ነግረውት እንዲፈውሰው ለመኑት፡፡
❖ አቡነ ጎርጎርዮስም ወደ ንጉሡ ሄደው በእሪያነቱ ሳለ ‹‹ብፈውስህና ባድንህ ከክፉ ሥራህ ትመለሳለህ በእውነተኛው አምላክ በኢየሱስ ክርስቶስ ታምናለህ›› አሉት፡፡
❖ እሪያ የነበረው ንጉሥም ‹‹አዎ›› ቢላቸው ጸሎት አድርገው ፈውሱት፤ አእምሮውና የቀድሞው መልኩም ተመለሰለት፤ ነገር ግን አቡነ ጎርጎርዮስ ንጉሡ ዳግመኛ እንዳይታበይ በማለት ከእግሩ ላይ የእሪያ ጥፍር አስቀሩለት፡፡
❖ የቤተ መንግሥንም ሰዎች ሁሉ ከፈወሳቸው በኋላ 8 ቀን እንዲጾሙ አዘዛቸው፤ ሃይማኖትንም አስተምሮ ሥርዓት ሠራላቸው፡፡
❖ እርሱም ክህነት አልነበረውምና ወደ ሮሜው ንጉሥ ወደ አኖሬዎስና ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ መልአክት ላኩና ጳጳስ ይላኩላችሁ አላቸው፡፡
❖ የሮሙ ሊቀ ጳጳሳትም ጎርጎርዮስን ሾሞ ላከላቸው፡፡ ንጉሡ አኖሬዎስም በዚህ ተደሰተ፤ ጎርጎርዮስም ተሹሞ ከመጣ በኋላ ሁሉንም አጠመቃቸው፡፡
❖ አርማንያም በቅዱስ ጎርጎርዮስ ትምህርት በክርስትና የምትታወቅ አገር ሆነች፤ እርሱም በእመቤታችን ስም ቤተክርስቲያን ሠራላቸው፤ ምእመናንያንም የሰማዕታቱን ሥጋ ሰብስበው በመልካም ቦታ ካስቀመጡት በኃላ የመከራው ዘመን ሲያልፍ የተዋበች ቤተ ክርስቲያን ሠርተው የቅዱሳኑን በዚያ አኖሩ፤ ከሥጋቸውም ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራት ተፈጽመው ታዩ።
❖ የቅድስት አርሴማ ዕረፍቷ መስከረም 29 ነው፤ የቤተክርስቲያኗም ቅዳሴ በአርማንያ አገር፣ በኪልቂያ፣ በሶርያ፣ በአንጾኪያና በግብፅ አውራጃዎች ሁሉ በታኅሣሥ ወር በ6ኛው ቀን ሆነ፡፡
ጌታችን ከገባላት ብዙ ቃልኪዳን ውስጥ አንደኛው "... ልጁን በአንቺ ስም የጠራውን በመንግሥተ ሰማያት የበለጠና የከበረ ስምን እኔ እሰጠዋለሁ" የሚል ነው፡፡
የቅድስት አርሴማና የሰማዕታቱ ረድኤታቸው በረከታቸው ይደርብን፤ ሀገራችን ሰላም ፍቅር ታድርግልን
ዝክረ ቅዱሳን ማኅበረ ቅዱስ ዳዊት - ዘብሔረ ጎንደር (ዲ/ዮርዳኖስ አበበ):
✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞✞✞

✞✞✞ ታኅሣሥ 6 ✞✞✞

✞✞✞ እንኩዋን "ለድንግልና ሰማዕት ቅድስት አርሴማ" : "አባ አብርሃም" እና "ቅዱስ ስምዖን ጫማ ሰፊው" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞✞✞

+*" ቅድስት አርሴማ ድንግል "*+

=>እናታችን ቅድስት አርሴማን በምን እንመስላታለን? እርሷ በአድማስ ላይ ተቀምጦ እንደሚያበራ እንቁ ናትና ክብሯ ብዙ ነው:: መድኃኒታችን ክርስቶስ በወንጌል እንዳለው "በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሠወር አይቻላትምና" (ማቴ. 5:11) የሰማዕቷ ሕይወት በፊታችን እንደ ብርሃን ተገልጦ ይታያል::

*ቅድስት አርሴማ እንደ ልጅ ወላጆቿን በመታዘዝ ደስ ያሰኘች ቡርክት ናት::
*ቅድስት አርሴማ ይሕ ቀረሽ የማይሏት ውብ ናት::
*ቅድስት አርሴማ ድንግል ናት::
*ቅድስት አርሴማ ባሕታዊት ጻድቅ ናት::
*ቅድስት አርሴማ ኃያል ሰማዕት ናት::

¤ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ:

+አበው በትውፊት እንደ ነገሩን ከሆነ ቅዱሱ ጐርጐርዮስ የታላቁዋ ሰማዕት ቅድስት አርሴማ ትልቅ ወንድም ነው:: በዜና ሰማዕታት ተጽፎ እንደሚገኘው በዚያ የመከራ ዘመን ቅዱስ ጐርጐርዮስ ሦስት ኃላፊነቶች ነበሩበት:-

1.ቅድስት አርሴማን ጨምሮ ደናግሉን ማጽናት
2.ትምሕርተ ቤተ ክርስቲያንን በሚገባ ማጥናት
3.የሚመጣውን መከራ ለመቀበል ራሱን ማዘጋጀት::

+ቅዱሱ 3ቱንም ኃላፊነቶች በሚገባ በመወጣቱ ከራሱ አልፎ ለሌሎቹ አርአያ መሆን ቻለ:: ያቺን ንጽሕት አርበኛ ቅድስት አርሴማንም አጽንቶ የደናግሉ መሪ አደረጋት:: መከራው ገፍቶ እስከ መጣበት ጊዜ በአንድ የደናግል ገዳም ውስጥ ሆነው ይጸልዩ: ይጾሙ: ገዳማዊ ሥራንም ይሠሩ ነበር::

+ለዚህም ነው ቅድስት አርሴማና ቅዱስ ጐርጐርዮስ ጻድቃን የምንላቸው:: በሁዋላ ግን ማሕደረ ሰይጣን ዲዮቅልጢያኖስ በመልኩዋ ተማርኮ ቅድስት አርሴማን ካላገባሁ በማለቱ ቅዱስ ጐርጐርዮስ ድንግሏን አርሴማን ጨምሮ ክርስቲያኖችን ይዞ ወደ አርማንያ ተሰደደ::

+በአርማንያም በአንድ ገዳም ውስጥ ተደብቀው በጾምና በጸሎት ለጥቂት ጊዜ ቆዩ:: ነገር ግን ረሃብ ፈጃቸው:: የሚላስ የሚቀመስ ነገር በአካባቢው ባለ መኖሩ ቅዱስ ጐርጐርዮስ ወደ ከተማ ለመውጣት ተገደደ::

+በዚያም በድርጣድስ ቤተ መንግስት ውስጥ ባርነት ተቀጠረ:: በሚያገኛት ገንዘብም ወገኖቹን ይረዳ ነበር:: መከራው ግን አለቀቃቸውም:: ርጉም ዲዮቅልጢያኖስ ቅዱሳኑ ወደ አርማንያ መሔዳቸውን ስለ ሰማ ይዞ እንዲልክለት ድርጣድስን ላከው::

+ድርጣድስ ግን ቅድስት አርሴማን ባያት ጊዜ ከውበቷ የተነሳ መታገስ ባለመቻሉ "ካላገባሁሽ" አላት:: ድንግሊቱ ግን "እኔ የክርስቶስ ሙሽራ ነኝ: አይሆንም" አለችው:: ሊያስፈራራት ሞከረ:: ዐይኗ እያየ ደናግሉን ጨፈጨፋቸው::

+አልሳካልህ ቢለው በአደባባይ በግድ ሊያገባት ቢሞክር እጁን ጠምዝዛ በሰው ሁሉ ፊት መሬት ላይ ጣለችው:: እጅግ ስላፈረ አስገረፋት: አሰቃያት: ዐይኗንም አወጣ:: በመጨረሻም አንገቷን አስቆርጦ ከሰማዕታቱ ጋር ተራራ ላይ ጣላት::

+ከነገር ሁሉ በሁዋላ ድርጣድስና ባለሟሎቹ ለአደን በሔዱበት ርኩስ መንፈስ ወደ አውሬነት (እሪያነት) ቀየራቸው::

+የንጉሡ እንስሳ (አውሬ) መሆን በአርማንያ ታላቅ ድንጋጤን ፈጠረ:: የንጉሡ እህት ስታለቅስ በራዕይ "ለእመ ኢያዕረግምዎ ለጐርጐርዮስ አልብክሙ ድኂን-ጐርጐርዮስን ከተቀበረበት ካላወጣችሁት አትድኑም" አላቸው:: ወዲያውም ቆፍረው አወጡት::

+ቅዱሱ እንደ ወጣ ዕረፍትን አልፈለገም:: ለ15 ዓመታት ቀባሪ አጥቶ የተበተነውን የቅድስት አርሴማንና የሰማዕታቱን አጽም ሰብስቦ በክብር አኖረው::
ድርጣድስና ባለሟሎቹንም ወደ በርሃ ሒዶ ፈወሳቸው::

+የሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ አጽም በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን ከሌሎች ሰማዕታት አጽም ጋር ኢትዮዽያ እንደ መጣ አባቶቻችን በትውፊት ነግረውናል:: ለዚህም ይመስላል ቡርክቷ እናታችን ከሌሎች ሃገራት ለይታ ለኢትዮዽያውያን ልዩ ፍቅር ያላት:: በዋናው ገዳሟ (ወሎ /ኩላማሶ/ : ስባ : ውስጥ የሚገኝ ነው) ጨምሮ ስሟ በተራበት ሁሉ ኃይልን ታደርጋለችና::

+ነገር ግን ወንድሞቼና እሕቶቼ በቅድስቷ እናታችን ስም የሚነግዱ ሥጋውያን ሰዎች በዝተዋልና እንጠንቀቅ:: የሰማዕቷ ክብር ብዙ ነውና በሕልም ላይ ብቻ አንታመን:: አባ እንጦንስ እንዳሉት "በሕልሙ የሚታመን ሰው ከንቱ ነውና::" (መዝ. 75:5)

+በዚህ ዕለት ከሰማዕቷ ጋር የመንፈስ እናቷን ቅድስት አጋታን ልናስባት ይገባናል:: ይህች እናት እመ-ምኔት ስትሆን ቅድስት አርሴማን ታስተምራት: ታጸናት: ከጐኗም ትቆምላት ነበር:: ረሃቧን: ጥሟን: ስደቷን: መከራዋንም ሁሉ አብራት ተሳትፋለች:: በፍጻሜውም አብራት ተሰይፋለች::

+ይህች ዕለት ለቅድስት አርሴማና ለተከታዮቿ ሰማዕታት የፍሰትና የቅዳሴ ቤት መታሰቢያ ናት::

+"+ አባ አብርሃምና ቅዱስ ስምዖን ጫማ ሰፊው +"+

=>እነዚህ 2 ኮከቦች በ11ኛው መቶ ክ/ዘመን አካባቢ በምድረ ግብጽ ተነስተው ለቤተ ክርስቲያን ድንቅ ተአምርን የሠሩ አበው ናቸው:: እመ ብርሃን ማርያም ለሥራ እስክታገናኛቸው ድረስም እርስ በርስ አይተዋወቁም ነበር::

+"+ አባ አብርሃም +"+

=>ይህ ቅዱስ ትውልዱ ከሶርያ ሲሆን እጅግ የታወቀ ነጋዴ ነበር:: ከሶርያ ግብጽ እየተመላለሰ ሲነግድ ባለ ጸጋ ሆኖም ነበር:: ነገር ግን ክርስትናን አጥብቆ የተማረ: ነዳያንን የማይዘነጋ: ጾምና ጸሎትን የማይገፋና እኔን ብቻ ይድላኝ የሚል ሰው ስላልነበረ እግዚአብሔር ለታላቅ ሥራ ጠራው::

+የግብጽ 61ኛ ፓትርያርክ አባ ፊላታዎስ ባረፈ ጊዜ አበው ተተኪ ፍለጋ ሱባኤ ቢገቡ "ሶርያዊ አብርሃምን ሹሙ" አላቸው:: እርሱ "እንቢ" ቢልም አለቀቁትም:: እርሱም ከሆነስ ብሎ ሃብቱን እኩሉን ለነዳያን: እኩሉን ለገዳማት ሰጥቶ ባዶ እጁን ወደ መንበረ ዽዽስናው ወጥቷል:: በዘመነ ሲመቱም ልማደ ኃጢአትን ያርቅ ዘንድ ብዙ ተግቷል::

+"+ ቅዱስ ስምዖን ሰፋዪ +"+

=>በዚያው ዘመን በምስር (በአሁኗ CAIRO) አካባቢ ራሱን ደብቆ: ጫማ እየጠገነ: ነዳያንን እየመገበ: ድኩማንን እየረዳ: በፍጹም ትሕትና: በጾምና በጸሎት የኖረ አባት ነው:: አንዲት ወጣት ልታስተው ብትመጣም ስለ ክርስቶስ ትዕዛዝ አንድ ዐይኑን በመሳፈቻ አውጥቶ ጥሏል::

+"+ በእምነት ተራራ ሲነቀል +"+

=>በወቅቱ የነበረው የግብጽ ከሊፋ ፍልስፍና ወዳጅ በመሆኑ ምሁራንን ያከራክር ነበር:: አንድ አይሁዳዊ "ምሑር" ነኝ ባይም ከክርስቲያኖች ጋር መከራከር ፈልጐ ጠየቀ:: አባ አብርሃምና አባ ሳዊሮስ መጥተው ድል ነስተው: አሳፍረውት ሔዱ::

+እርሱም በቂም በማቴ. 17:20 ላይ ያለችውን ቃል ይዞ ሒዶ በከሊፋው ፊት አቀረበ:: ቃሉም:- "የሰናፍጭ ቅንጣት ታሕል እምነት ቢኖራችሁ ይህንን ተራራ ተነቀል . . . ብትሉት ይቻላቹሃል" ይላል::

+ከሊፋውም አባ አብርሃምን ጠርቶ "መጽሐፍ ቅዱሳችሁ እንደዚህ ይላል?" አለው:: "አዎ!" ሲል መለሰለት:: "አድርገህ አሳየኝ" ቢለው 3 ቀናትን ለምኖት ወጣ:: ሁሉም ክርስቲያኖች የ3 ቀን ምሕላ ሲይዙ አባ አብርሃም በእመቤታችን መቅደስ ለ3 ቀናት ያለ ምግብና እንቅልፍ አለቀሰ::
+እመ ብርሃን በሞገስ መጥታ "ጫማ ሰፊው ስምዖን ይህንን ያደርግልሃል" አለችው:: በምልክት ሒዶ: በፊቱ አዘንብሎ "አቤቱ ለገኖችህ ክርስቲያኖች ራራላቸው?" አለው::+ቅዱሱ ደንግጦ እንቢ እንዳይለው የድንግል ማርያምን ስም ጠራበት:: ቅዱስ ስምዖንም ለአባ አብርሃም "ሰው እንዳያውቀኝ አደራ!" ብሎት ወደ አንድ ግዙፍ ተራራ ሔዱ::

+ሕዝቡ ባንድ ወገን: ከሊፋውና ሠራዊቱ በሌላ ወገን ቆሙ:: ቅዱሳኑ ከምዕመናን ጋር "41 ኪርያላይሶን" አድርሰው: ሰግደው ቀና ሲሉ ተራራው ተነቅሎ በዓየር ላይ ተንሳፈፈ:: ለማጽናትም 3 ጊዜ ተነቅሎ ተተከለ::

+በሁዋላም ወደ ሌላ ቦታ አልፎ ተቀመጠ:: በዚህች ዕለትም በድንግል ምልጃ: በቅዱሳኑ ጸሎት ታላቅ ሞገስ ሆነ:: ወዲያው ግን ቅዱስ ስምዖን ተሰወረ:: ውዳሴ ከንቱን ይጠላልና:: አባ አብርሃምም በቀሪ ዘመኑ ተግቶ ዐርፏል:: ዛሬ የ2ቱም መታሰቢያ ነው::

+ሊቃውንትም ቅዱስ ስምዖንን ሲያደንቁ:-
"ሰላም ለስምዖን በአፈ ማርያም ዘተአምረ::
እንበይነ ትዕዛዙ ለወልዳ ከመ ዐይኖ አዖረ::
ኢይሌብውዎ ሎቱ ወኢይጸግውዎ ክብረ::
ሶበ ጸለየ ቀዊሞ ለሊቀ ዻዻሳት ድኅረ::
ነቀለ ደብረ ወተከለ ደብረ" ብለዋል:: (አርኬ)

=>አምላከ ቅዱሳን ተራራ ያፈለሱበትን እምነታቸውን አይንሳን:: ከበረከታቸውም ይክፈለን::

=>ታሕሳስ 6 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅድስት አርሴማ ድንግል
2."119" ሰማዕታት (ማሕበሯ)
3.ቅዱስ ስምዖን ጻድቅ (ጫማ ሠፊው)
4.አባ አብርሃም ሶርያዊ
5.ቅዱስ እንጣልዮስ ሰማዕት

ወርኀዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅድስት ደብረ ቁስቁዋም
2.አባታችን አዳምና እናታችን ሔዋን
3.አባታችን ኖኅና እናታችን ሐይከል
4.ቅዱስ ኤልያስ ነቢይ
5.ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ
6.ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ
7.ቅድስት ሰሎሜ
8.አባ አርከ ሥሉስ
9.አባ ጽጌ ድንግል



=>+"+ እውነት እላቹሃለሁ:: የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል እምነት ቢኖራችሁ ይህን ተራራ ከዚህ ወደዚያ እለፍ ብትሉት ያልፋል:: የሚሳናችሁም ነገር የለም:: +"+ (ማቴ. 17:20)

✞✞✞ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ✞✞✞
5•­3- ØÈ- s #% 5õ5u--- 16k
ASR by NLL APPS
ስንክሳር ዘወርሃ ታህሣሥ ስድስት(፮)
https://www.tg-me.com/SinkisarZekidusan2
††† እንኳን ለስብከተ ነቢያት እና ለአበው ጻድቃን አባ ዳንኤል ወአባ ማቴዎስ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

<<< ❇️ስብከት ❇️>>>

ይህች ዕለት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት "ስብከት" ትባላለች:: ስብከት ማለት በቁሙ "የምስራች: አዲስ ዜና መንገርን" የሚመለከት ሲሆን ዋናው ምሥጢር ግን ከነገረ ድኅነት (ከመዳን ትምሕርት) ጋር የተገናኘ ነው::

በዚህ ዕለት (ሳምንት) ሁሉም ነቢያት ከነ ትንቢታቸው ይታሰባሉ:: ዘመነ ስብከትም ከታሕሳስ 7 እስከ 13 ያለውን ይይዛል:: ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-

እግዚአብሔር አዳምን በ7 ሃብታት አክብሮ በገነት ቢያኖረው "አትብላ" የተባለውን ዕፀ በለስ በላ:: በዚህም ከፈጣሪው ተጣልቶ: በሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ: በርደተ መቃብር ርደተ ገሃነም ተፈረደበት:: በሁዋላ ግን ንስሃ ስለ ገባ "ከ5 ቀን ተኩል (5,500 ዘመን) በሁዋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ" የሚል ቃል ኪዳንን ሰጠው::

ከዚህ በሁዋላ ለ5,500 ዘመናት ጊዜ ወደ ታች ይቆጠር ጀመር:: ስለ እግዚአብሔር ሰው መሆንና ዓለምን ማዳንም ትንቢት ይነገር: ሱባኤ ይቆጠር: ምሳሌም ይመሰል ገባ::
ከአዳም እስከ ሙሴ (ዘመነ አበው) ምሳሌያት ይበዛሉ:: ከሙሴ እስከ ዳዊት (ዘመነ መሣፍንት) ምሳሌያቱ እየጐሉ መጥተዋል:: ከልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት እስከ ቅዱስ ሚልክያስ ድረስ (በዘመነ ነቢያት/ነገሥት) ግን ትንቢቶች ስለ ክርስቶስና ስለ ማደሪያ እናቱ እንደ ጐርፍ ፈሰዋል::

ነቢያትም የመሲህን መምጣት እየጠበቁ በጾም: በጸሎትና በትሕርምት ኑረዋል:: እንባቸውንም አፍሰው ቅድመ እግዚአብሔር ደርሶላቸዋል:: መድኅን ክርስቶስም ተወልዶ አድኗቸዋል::

ነቢይ ማለት በቁሙ ኃላፍያትን (አልፎ የተሠወረውን ምሥጢር): መጻዕያትን (ለወደ ፊት የሚሆነውን) የሚያውቅ ሰው ማለት ነው:: ሃብተ ትንቢት የእግዚአብሔር የባሕርይ ገንዘቡ ሲሆን እርሱ ለወደደው በጸጋ ይሰጠዋል:: እነዚህም ከጌታ ሃብተ ትንቢት የተሰጣቸው አባቶችና እናቶች "ቅዱሳን ነቢያት" በመባል ይታወቃሉ::

ዘመነ ነቢያት ተብሎ የሚታወቀው ብሉይ ኪዳን ቢሆንም እስከ ምጽዓት ድረስ ጸጋውን እግዚአብሔር ለፈቀደላቸው አይነሳቸውም:: በሐዋርያት መካከልም ቅዱስ አጋቦስን የመሰሉ ነቢያት ነበሩ:: (ሐዋ. 11:27) ቅዱሳን ነቢያት ከእግዚአብሔር እየተላኩ ሰውን ከፈጣሪው እንዲታረቅ ይመክራሉ: ይገስጻሉ::

ከበጐ ሃይማኖታቸውና ንጽሕናቸው የተነሳም እግዚአብሔርን በተለያየ አርአያና አምሳል አይተውታል::
"እስመ በአንጽሖ መንፈስ ርዕይዎ ነቢያት ለእግዚአብሔር: ወተናጸሩ ገጸ በገጽ" እንዳለ አባ ሕርያቆስ:: (ቅዳሴ ማርያም)

የብዙ ነቢያት ፍጻሜአቸው መከራን መቀበል ነው:: እውነትን ስለ ተናገሩ: አንዳንዶቹም በእሳት: አንዳንዶቹም በሰይፍ: አንዳንዶቹም በመጋዝ ተፈትነዋል:: ሌሎቹ ለአናብስት ሲጣሉ ቀሪዎቹ ደግሞ በድንጋይ ተወግረዋል::

ስለዚህም መከራቸው ለቤተ ክርስቲያን መሠረት ተብለዋል:: ጌታም ለደቀ መዛሙርቱ "ሌሎች ደከሙ: እናንተ በድካማቸው ገባችሁ" ብሎ የነቢያቱን መከራ ተናግሯል:: (ዮሐ. 4:36)

ነቢያት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እና ድንግል እናቱን ለማየት ብዙ ጥረዋል: ሽተዋልም:: "ብዙ ነቢያትና ጻድቃን እናንተ የምታዩትን ሊያዩ ሹ" እንዳለ ጌታ በወንጌል:: (ማቴ. 13:16, 1ዼጥ. 1:10) ዛሬ ግን በሰማያት ጸጋ በዝቶላቸው: ክብር ተሰጥቷቸው ሐሴትን ያደርጋሉ::

ቅዱሳን ነቢያት በዋነኝነት 15ቱ አበው ነቢያት: 4ቱ ዐበይት ነቢያት: 12ቱ ደቂቀ ነቢያትና ካልአን ነቢያት ተብለው በ4 ይከፈላሉ::

"15ቱ አበው ነቢያት" ማለት:-

*ቅዱስ አዳም አባታችን
*ሴት
*ሔኖስ
*ቃይናን
*መላልኤል
*ያሬድ
*ኄኖክ
*ማቱሳላ
*ላሜሕ
*ኖኅ
*አብርሃም
*ይስሐቅ
*ያዕቆብ
*ሙሴና
*ሳሙኤል ናቸው::

"4ቱ ዐበይት ነቢያት"
*ቅዱስ ኢሳይያስ ልዑለ ቃል
*ቅዱስ ኤርምያስ
*ቅዱስ ሕዝቅኤልና
*ቅዱስ ዳንኤል ናቸው::

"12ቱ ደቂቀ ነቢያት"
*ቅዱስ ሆሴዕ
*አሞጽ
*ሚክያስ
*ዮናስ
*ናሆም
*አብድዩ
*ሶፎንያስ
*ሐጌ
*ኢዩኤል
*ዕንባቆም
*ዘካርያስና
*ሚልክያስ ናቸው::

"ካልአን ነቢያት" ደግሞ:-
*ኢያሱ
*ሶምሶን
*ዮፍታሔ
*ጌዴዎን
*ዳዊት
*ሰሎሞን
*ኤልያስና
*ኤልሳዕ ሌሎችም ናቸው::

ነቢያት በከተማም ይከፈላሉ::
*የይሁዳ (ኢየሩሳሌም):
*የሰማርያ (እሥራኤል)ና
*የባቢሎን (በምርኮ ጊዜ) ተብለው ይጠራሉ::

በዘመን አከፋፈል ደግሞ:-
*ከአዳም እስከ ዮሴፍ (የዘመነ አበው ነቢያት):
*ከሊቀ ነቢያት ሙሴ እስከ ነቢዩ ሳሙኤል (የዘመነ መሳፍንት ነቢያት)
*ከቅዱስ ዳዊት እስከ ዘሩባቤል ያሉት (የዘመነ ነገሥት ነቢያት):
*ከዘሩባቤል ዕረፍት እስከ መጥምቁ ዮሐንስ ያሉት ደግሞ (የዘመነ ካህናት ነቢያት) ይባላሉ::

<< ታላቁ አባ ዳንኤል >>

ይህ ቅዱስ አባት ስም አጠራሩ ክቡር ነው:: በሁሉ ነገሩ የተቀደሰ የገዳማውያን መብራትም ነው:: ከተረፈ ንጹሕ ሕይወቱ ጣዕመ መንግስተ ሰማያትን አይቷልና:: አባ ዳንኤል በትውልድ ግብጻዊ ሲሆን ዓለምን ንቆ (መንኖ) ገዳም የገባው ገና በወጣትነቱ ነው::
ጊዜውም ዘመነ ጻድቃን (በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን) ነበር:: በገዳመ አስቄጥስና በደብረ ሲሐት ይታወቃል:: ታላቁዋ መካነ ቅዱሳን ገዳመ ሲሐት ዛሬም ድረስ በስሙ የምትጠራ ሲሆን ለዚህም ምክንያቱ እጅግ ለብዙ ዘመናት በውስጧ ተጋድሎ ፍሬ ስላፈራባት: ደቀ መዛሙርትን በቅድስና ስለ ወለደባት ነው::

ስለዚህም ዛሬም ድረስ "አባ ዳንኤል ዘደብረ ሲሐት" ተብሎ ሲጠራ ይኖራል:: ሌላኛው ስሙ ደግሞ "ዘገዳመ አስቄጥስ" ይሰኛል:: ገዳመ አስቄጥስ የታላቁ ቅዱስ መቃርስ ርስት ሲሆን በዓለም በስፋትም: ብዙ ቅዱሳንን በማፍራትም አንደኛ የሆነ ገዳም ነው::
በዚህ ገዳም ላይ አበ ምኔት ሁነው የሚሾሙ አበው ሁሌም የብቃት መዓርግ ላይ የደረሱ ሲሆኑ ክብራቸው ከፓትርያርክ በላይ ነው:: አባ ዳንኤልም ከብዙ የቅድስና ዓመታት በሁዋላ በአስቄጥስ ገዳም አበ ምኔት ሆኖ ተሹሞ እልፍ አእላፍ መነኮሳትን በጽድቅ መንገድ መርቷል::

ቅዱሱ ከትጋቱ የተነሳ ለምግብና ለእንቅልፍ ጊዜ አልነበረውም:: ቀን ቀን መነኮሳቱን ሲናዝዝ: ድውያንን ሲፈውስ: ሥርዓተ ገዳምን ሲቆጣጠር ይውላል:: ልክ ሲመሽ ጭው ወዳለውና ስውራን ወደ ሚገኙበት በርሃ ይወጣል::

በዚያም ሙሉውን ሌሊት የተሰወሩ አባቶችን ሲፈልግ ያድር ነበር:: በዚህም ምክንያት የብዙ ስውራንን ገድል የጻፈ ሲሆን ባረፉ ጊዜም ገንዞ በመቅበር በረከታቸውን ተሳትፏል:: ታላቅ ሙያንም ፈጽሟል::

እርሱ ገንዞ ቀብሮ: ዜናቸውን ከጻፈላቸው ሥውራን ቅዱሳንም እንደ አብነት እሥራኤላዊቷን ቅድስት ዓመተ ክርስቶስን (ለ38 ዓመት ራቁቷን በሥውር የኖረች) እና ቅድስት በጥሪቃ ንግሥትን (መንግስቷን ትታ በሥውር የኖረች ናት) መጥቀስ እንችላለን::
ከዚህ ባለፈም አባ ዳንኤል በሰው ዘንድ የተናቁትንም ማክበርን ያውቅበታል:: ለምሳሌ በሴቶች ገዳም "እብድ" ናት ተብላ በበር የተጣለችውን ቅድስት አናሲማን: በእስክንድርያ ከተማ ሊቀ ዻዻሳቱ ሳይቀር "እብድ" ነው ብለው የናቁትን ቅዱስ ምሕርካን: እብድ ሳይሆኑ ራሳቸውን የሠወሩ ቅዱሳን መሆናቸውን ገልጧል::አባ ዳንኤል ሐዋርያዊም ነበር:: በጊዜው ጦማረ ልዮን የሚባል የኑፋቄ ደብዳቤ ይላክ ነበርና ለዚህ ኬልቄዶናዊ ኑፋቄ በትጋት ምላሽ ይሰጥ ነበር:: አንድ ቀንም በንጉሥ ትዕዛዝ ኑፋቄው በእርሱ ገዳም ሊነበብ ሲል ቅዱሱ ከወታደሩ ቀምቶ ስለ ቀደደው ለሞት እስኪደርስ ደብድበውታል::

ጻድቁ አባ ዳንኤል አንዴ አውሎጊስ የሚባል ደሃ ድንጋይ ጠርቦ እንግዳ ሲቀበል ተመልክቶ "ጌታ ሆይ! ይህንን ደግ ሰው ለምን ደሃ አደረከው?" ሲል በፈጣሪ ሥራ ገባ::
ጌታም እንደ ወትሮው በገሃድ ተገልጦ "በነፍስህ ትዋሰዋለህ?" አለው:: "አዎ ጌታየ" ስላለው ጌታችን ለአውሎጊስ ሃብትን ሰጠው:: ግን ወዲያው የጦር አለቃና ጨካኝ ሰው ሆነ::
ጻድቁ ወሬውን ሰምቶ ሊጠይቅ ቢሔድ የአውሎጊስ ወታደሮች ደበደቡት:: ጌታችንም አባ ዳንኤልን ወደ ፍርድ ዙፋኑ አቅርቦ "ወዳጄን መልስልኝ" አለው:: እመ ብርሃን ግን ቀርባ የልጇን እግር ሳመች::

"ልጄ ሆይ ማር!" አለችው:: ጌታም "እሺ" ብሎ ጻድቁን ወደ በአቱ: አውሎጊስን ወደ ቀደመ ግብሩ መለሳቸው:: የአባ ዳንኤል ድንቁ ብዙ ነው::

ሌላው ቢቀር ሽፍታ አባ ዳንኤልን መስሎ ወደ ደናግል ገዳም: ሊዘርፍ: በማታለል ገባ:: ደናግሉም ጻድቁ መስሏቸው እግሩን አጥበው ዐይነ ስውሯን ቢቀቧት ዐይኗ በርቷል:: ሽፍታውም ደንግጦ ንስሃ ገብቷል:: አባ ዳንኤል ግን ተጋድሎውን ፈጽሞ በዚህች ቀን ዐርፏል::

<< አባ ማቴዎስ ገዳማዊ  >>

ጻድቁ ከታላቁ ቅዱስ ዻኩሚስ የመንፈስ ልጆች አንዱ ሲሆን የበርሃ ኮከቦች ከሚባሉት አንዱ ነው:: ብዙ ደቀ መዛሙርትን ያፈራ: ከግሩማን አራዊት ጋር የኖረ: ብዙ ተአምራትን የሠራ: ናዛዜ ሕዙናን የሆነ አባት ነው:: ዛሬ ዕረፍቱ ነው::
የአባቶቻችን በረከት ይደርብን::

=>ታሕሳስ 7 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ስብከተ ነቢያት
2.አባ ዳንኤል ገዳማዊ
3.አባ ማቴዎስ ገዳማዊ
4.ብጽዕት ዲዮጥርስ

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ሥሉስ ቅዱስ (አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ)
2.አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ
3.አባ ሲኖዳ (የባሕታውያን አለቃ)
4.አባ ባውላ ገዳማዊ
5.ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ
6.ቅዱስ አግናጥዮስ (ለአንበሳ የተሰጠ)

"ይህን በመጀመሪያ እወቁ:: በመጽሐፍ ያለውን ትንቢት ሁሉ ማንም ለገዛ ራሱ ሊተረጉም አልተፈቀደም:: ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና:: ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ::"
(2ዼጥ. 1:20)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>



"ፍቅር ያጌብረኒ ከመ እንግር ዜናሆሙ ለቅዱሳን"::አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ /መጽሐፈ ምሥጢር/
5•­3- ØÈ- s #% 0cu--- 16k
ASR by NLL APPS
ስንክሳር ዘወርሃ ታህሣሥ ሰባት(፯)
https://www.tg-me.com/SinkisarZekidusan2
ራስን መግዛት (ክፍል -፩)

መንፈሳዊው ሰው ካሉት ብቃቶች መካከል አንዱና ዋነኛው ራስን መግዛት ነው፡፡ እርሱ ራሱን ለሥጋ ምኞትና ለፍላጎቶቹ አሳልፎ አይሰጥም፡፡ ሕሊናው የኃጢአትን ምኞት ሲናፍቅ ይህን አሳቡን በመቃወም መንፈሱ እንድትመራው በማድረግ ራሱን አጥብቆ ይገዛል:: መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል:- «በመንፈሱ ላይ የሚገዛ (መንፈሱን የሚገዛ) ከተማ ከሚወስድ ይበልጣል፡፡» ምሳ. 16፥32

እንደ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት ራሱን የሚገዛ ወይም የሚመራ ማለት ሥጋው የጠየቀውን ሁሉ የማይሰጥ ይልቁኑ የሚቃወም ማለት ነው:: «ነፍሱን የሚወድ ያጠፋታል፤ነፍሱን በዚህ ዓለም የሚጠላ ለዘላለም ሕይወት ይጠብቃታል፡፡» ዮሐ. 12፥25።

ራስን መግዛት በውስጡ የተለያዩ ክፍሎች እንዳሉት እርግጥ ነው፡፡ እነርሱም፤-

1. #ምላስን_መግዛት፡፡
2. #አሳብን_መግዛት::
3. #ልብን_መግዛት፡፡ (ፍላጎትንና ምኞትን በመግዛት)
4. #ስሜትን_መግዛት::
5. #ሆድን_መግዛት (ምግብን በተመለከተ) ናቸው፡፡

ራሱን የሚመራ ሰው እርሱነቱን ለእሴትና ለዓላማ እንዲሁም ለሕግና ደንብ ያስገዛል፡፡ ራሱን መምራት የማይችል ሰው ግን በእርግጥ እርሱነቱን ለጥፋት ይጋብዛል፡፡ ራሱን የሚገዛ ሰው ነፍሱን በእውነተኛ ፍቅር ይወዳታል:: ራሱን የሚያቀናጣ ግን ነፍሱን ከማጣቱም በላይ ሌሎችም ከእርሱ ጋር አብረው እንዲጠፉ ያደርጋል፡፡ ራሱን አጥብቆ የሚጠብቀው በትጋቱ ነፍሱን ስለሚጠብቃትና በመልካም ሁኔታ ስለሚይዛት ያድናታል፡፡ አልፎ ተርፎም ሌሎችን ለማዳን ምክንያት ይሆናል፡፡ የራሱን አመለካከትና ግንኙነት በቅደም ተከተል ያደራጃል፡፡ በመጀመሪያ እግዚአብሔርን ያስቀድማል፤ በመቀጠል ሰዎችን ያስከትላል፤ በመጨረሻም ራሱን።

#ምላስን_መግዛት፡፡

መንፈሳዊው ሰው ቃላት ወይም አሳቦች ያቀበሉትን ወደ አእምሮው የመጡትን ሁሉ በአንደበቱ አይናገራቸውም፡፡ እያንዳንዱን ቃል ከአንደበቱ ከማውጣቱ በፊት ይመዝናል:: የእርሱ ሚዛን የሚለካው የቃሉን ፍሬ ነገር ብቻ ሳይሆን ትክክል መሆኑንና አለመሆኑንም ጭምር ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የእርሱ ዋና ዓላማው ቃሉ በሌሎች ሰዎች ላይ የሚያመጣውን ተጽዕኖ፣አፀፋና ውጤቱን ጭምር ነው::

የምላስ ወይም የአንደበት ስህተት ውጤት ሥጋን ማሳደፉንና የፍጥረትንም ሩጫ ማቃጠሉን የሚያውቅ ሰው ከመናገሩ በፊት ከፍተኛ ጥንቃቄ ያደርጋል:: ያዕ. 3፥5-6:: ከነቢዩ ከዳዊት ጋር ሆኖም:- «አቤቱ ለአፌ ጠባቂ አኑር፤ የከንፈሮቼንም መዝጊያ ጠብቅ፡፡» ይላል፡፡ እርሱ አንዴ ከአፉ የወጣው ቃል ተመልሶ ሊገባ እንደማይችል ያውቃል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ከአፉ የወጣው ቃል አድማጮቹ ጆሮ ከደረሰ በኋላ የተናገረውን መልሶ ሊውጠው፣ ወይም ይቅርታ ሊያገኝበት እንደማይችል አስቀድሞ ያውቃል:: ከዚህ በኋላ ስህተቱን ለማስተካከል ቢጥርም ጥፋቱ በእርሱ ላይ ዕዳ ሆኖ እንደሚቆጠር አጥብቆ ይረዳል፡፡ ከሁሉ በላይ ደግሞ ጌታ እንደተናገረው እንደሚኮነንበት ያውቃል፡ . . . ከቃልህ የተነሣ ትጸድቃለህና፤ ከቃልህም የተነሣ ትኮነናለህ፡፡» ማቴ. 12፥37::

#ይቀጥላል...

(#በብፁዕ_አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ
#መንፈሳዊ_ሰው_መጽሐፍ ገጽ 122-128
#በአያሌው_ዘኢየሱስ_የተተረጎመ)
#ራስን_መግዛት - ክፍል ፪

#አሳብን_መግዛት

መንፈሳዊው ሰው አንደበቱን መግታት እንደ ቻለ ሁሉ አሳቡንም መግዛት ይችላል፡፡ እርሱ የጀመረውን መንፈሳዊ መንገድ በሆነ አሳብ ምክንያት ስቶ እንዳይወጣ አሳቡን ይገታል፡፡ ወደ አሳቡ የሚመጣውን የኃጢአት አሳብ ሁሉ አይቀበልም፡፡ ፈጠን ብሎ ስለሚያስወጣው በእርሱ ላይ ለዘብተኝነት አያሳይም፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በመጀመሪያ ቀላል መስሎ የሚታየውንና ቀስ በቀስ ተቀባይነት ወደሌለው ነገር የሚመራውን አሳብ ገና ከጅምሩ አይቀበለውም፡፡ እንደዚህ ዓይነቱን ውስጡ ተኩላ ሆኖ ከላይ ግን የበግ ለምድ ለብሶ የሚመጣውን አሳብ ስለማይቀበለው ስለ ሰይጣን ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረውን «በሰይጣን እንዳንታለል የእርሱን አሳብ አንስተውምና።» (2ኛ ቆሮ. 2፥11) የሚለውን ቃል ለውስጡ አበክሮ ይነግረዋል።

እርሱ በኃጢአት አሳብ ከተሳሳተም ስህተቱን ፈልጎ በማግኘት ጥፋቱን ብዙ ሳይቆይ ያቆመዋል:: ምክንያቱም ከኃጢአት አሳብ ጋር አብሮ መጓዝ ጌታን እንደመካድ ስለሚቆጠር ብቻ ሳይሆን ይህ ክፉ አሳብ አንድ ጊዜ ከሕሊና ጋር ክፉኛ ከተጣበቀ ስለማይለቅ ነው፡፡ ከዚህ በመቀጠል እያደገና እየጎለመሰ ከንቱ ከሄደ በኋላ ልብን ከማጥቃቱም በላይ ወደ ምኞት ይቀየራል፡፡ በእርግጥም እንደዚህ ዓይነቱን አሳብ ገና ከውጥኑ ማጥፋት አማራጭ የሌለው መፍትሔ ነው::

መንፈሳዊው ሰው ጊዜውን ሙሉ ለሙሉ ክፉ አሳቦችን በመቆጣጠርና ኃጢአት በመከላከል አይጨርስም:: ይልቁኑ ሕሊናውንና ልቦናውን በንጹሕና በመንፈሳዊ አሳብ አብዝቶ ይሞላል፡፡ በመሆኑም ዲያብሎስ በክፉ አሳብ ሊዋጋው ሲመጣ ሕሊናውን በመንፈሳዊ ተመስጦ ተሞልቶ ያገኘዋል፡፡ በሕሊናው ውስጥ ያለው መንፈሳዊ ከባቢ አየር ማንኛ ውም ዓይነት የኃጢአት አሳብ ወደ እርሱ እንዳይቀርብ በማድረግ ልክ እንደ ጠንካራ ምሽግ ይመክተዋል።

#ስሜትን_መግዛት

ስሜት የአሳብ ሁሉ መዝጊያ ነው:: ስለሆነም መንፈሳዊ ሰው አሳቡን ለመቆጣጠር ሲፈልግ ስሜቱን ይቀጣጠራል፡፡ ዓይኖቹንና ጆሮዎቹን ይቆጣጠራል:: ስለሆነም ማንኛውም ወደ አሳብ የሚመራ ነገር ካለ ወደ ስሜቱ ስለሚደርስ ፈጥኖ ያስወግደዋል:: እዚህ ላይ አንዱን በሌላው መተካት በሚለው መርሆው መሠረት በአንዱ አሳቡ ቦታ ሌላ አሳብ ይተካል፡፡

ዮሐንስ ሐጺር የተባለው ቅዱስ ሰው ማዳመጥን በመከልከል ዙሪያ አስገራሚ ነገሮች ይሠራ ነበር ... አባ ኦር የተባለው ቅዱስም ለደቀ መዝሙሩ:- «ልጄ ሆይ! ወደዚህች ወደ በአታችን ምንም ዓይነት እንግዳ ቃል እንደማይገባ ተመለከትህን!?» ብሎት ነበር።

ይቀጥላል....

(#በብፁዕ_አቡነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ
#መንፈሳዊ_ሰው_መጽሐፍ ገጽ 122-128
#በአያሌው_ዘኢየሱስ_የተተረጎመ)

@beteafework
''' እንኩዋን ለቅዱሳን *አቡነ ኪሮስ *ዮሐንስ ዘደማስቆ *ሳሙኤል ዘቀልሞን *ተክለ አልፋ *ኤሲ *በርባራ *እንባ መሪና እና *ገብረ ማርያም ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ! '''

=>ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዚሁ ቀን የምታከብራቸው ብዙ ቅዱሳን አሏት:: ሁሉን ለመዘርዘር ይከብዳል:: ግን የጥቂቱን ዜና ለበረከት እንካፈል ዘንድ የጌታ ፈቃዱ ይሁንና ስለ እያንዳንዱ በጥቂቱ እናንሳ::

+*" አቡነ ኪሮስ ጻድቅ "*+

=>የጻድቁን ስም የሚጠራ አፍ ንዑድ ነው: ክቡር ነው:: በእውነት የቅዱሱን አባት ክብር ለማግኘት መፋጠን ይበጃል:: አቡነ ኪሮስ የተወለዱት በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ሲሆን ወላጆቻቸው ነገሥታት ናቸው::

+ተወልደው ባደጉባት ሃገር ቁስጥንጥንያ ገና በልጅነት ምቾት ሳያሳሳቸው መጻሕፍትንና ትሕርምትን ተምረዋል:: ወንድማቸው (ታላቁ ቴዎዶስዮስ) በነገሠባቸው የመጀመሪያ ዓመታት በቤተ መንግስቱ ዙሪያ ግፍ በዝቶ ነበርና አቡነ ኪሮስ ከኃጢአት ለመራቅና ለጌታ ለመገዛት ከከተማው ጠፍተው: አሕጉር አቁዋርጠው ወደ ግብፅ (ገዳመ አስቄጥስ) መጡ::

+እርሳቸውን ለመፈለግ የተደረገው ሙከራ አልተሳካም:: ይባስ ብሎ የንጉሡ ልጅ ገብረ ክርስቶስ ሙሽርነቱን ጥሎ ወደ ሌላ ሃገር መነነ:: "የቅኖች ትውልድ ይባረካል" እንዳለ ቅዱስ ዳዊት አቡነ ኪሮስ ለሙሽራው ገብረ ክርስቶስ አጎቱ ናቸው:: አቡነ ኪሮስ በገዳም ውስጥ የታላቁ አቡነ በብኑዳ ደቀ መዝሙር ሆነው ለዘመናት ቆይተዋል::

+ቅዱስ በብኑዳን አንበሳ በበላው ጊዜ በጣም አዝነው "ለምን ጌታ ሆይ?" በሚል መሬት ላይ ወድቀው አለቀሱ:: "ምክንያቱ ካልተነገረኝ አልነሳም" ብለው ከወደቁበት መሬት ላይ ሳይነሱ ለ40 ዓመታት አልቅሰዋል:: በዚህ ምክንያት ግማሹ አካላቸው አፈር ሆኖ ሣር በቅሎበታል::
ጌታችን ተገልጦ ምክንያቱን ነግሯቸዋል:: አካላቸውንም እንደነበረ መልሶላቸዋል::

+አንድ ቀን ጻድቁ ለቅዱስ በብኑዳ ሞት ምክንያት የሆነው መነኮስ ታንቆ መሞቱን ሰምተው በጣም አዘኑ:: ሱባዔ ገብተው: ፍጹም አልቅሰው: ከጌታም አማልደው: የዛን ኃጥእ ነፍስ ከሲዖል አውጥተዋል:: በሌላ ጊዜ ደግሞ ኃጥአን የሞሉበት አንድ ገዳም በግብጽ ነበርና መቅሰፍት ወርዶ ሁሉንም ባንድ ቀን ሲያጠፋቸው አዩ::

+ጻድቁ በዚህም ምክንያት ለ30 ዓመታት አልቅሰው: ሙታኑን አስነስተው: ንስሃ ሰጥተው: ገዳሙን የጻድቃን: ሕይወታቸውንም የፍቅር አድርገውታል:: ጻድቁ እመቤታችንን ከመውደዳቸው የተነሳ በስዕሏ ፊት አብዝተው ይሰግዱና ያለቅሱ ነበር:: እመ አምላክም ተገልጣ ትባርካቸው ነበር::

+ከዚህ በሁዋላ ወደ ምዕራብ አቅጣጫ ሒደው ለ57 ዓመታት ማንንም ሳያዩ ተጋደሉ:: ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ (ለስም አጠራሩ ስግደት ይሁንና) በየቀኑ ይጐበኛቸው: ቁጭ ብሎም ያወራቸው ነበር::

+በመጨረሻም ጌታ አእላፍ መላእክትን: ጻድቃን ሰማዕታትን: ድንግል እመቤታችንና ቅዱስ ዳዊትን አስከትሎ ወረደ::

+ቅዱስ ዳዊት ቀርቦ እያጫወታቸው: በበገናው እየደረደረላቸው: ከዝማሬው ጣዕም የተነሳ ነፍሳቸው ከሥጋቸው በፍቅር ተለየች:: ጌታችንም ታቅፎ: ስሞ ይዟቸው አረገ::

+ሥጋቸውን አባ ባውማ ቀበሩት:: የአቡነ ኪሮስ ቁመታቸው ቀጥ ያለ: ጽሕማቸውም የተንዠረገገ ነበር:: እድሜአቸውን ግን መገመት የሚቻል አይመስለኝም:: (ጻድቁ የተወለዱት በዚሁ ቀን ነው)

+*" አባ ሳሙኤል ዘቀልሞን "*+

=>በ5ኛው መቶ ክ/ዘመን በግብጽ ደብረ ቀልሞን የነበሩ:
*ከዓበይት ጻድቃን የሚቆጠሩ:
*ቀውስጦስ የሚባለውን መልአክ አማልደው ክንፈ ረድኤቱ እንዲመለስ ያደረጉ::
*መልአክን እንኩዋ ማማለድ የቻሉ::

*የታላቁ አባ አጋቶን ደቀ መዝሙር የሆኑ:
*ስለ ቀናች ሃይማኖት የተደበደቡ:
*መናፍቃን አንድ ዐይናቸውን ያጠፉባቸው:
*በፍጹም ትሕርምት የኖሩ:
*እልፍ ደቀ መዛሙርትን ያፈሩ::

*ተአምራትን የሠሩ:
*ደብረ ቀልሞን ገዳምን የመሠረቱና
*እመቤታችንን በፍጹም ልባቸው የወደዱ ቅዱስ አባት ናቸው:: (ዛሬ ዕረፍታቸው ነው)

+*" ቅዱስ ዮሐንስ ዘደማስቆ "*+

=>በ6ኛው መቶ ክ/ዘመን በሶርያ ደማስቆ የተነሳ:
*ፍልስፍናንም: ትምሕርተ ቤተ ክርስቲያንንም ያጠና:
*ስለ ስዕለ አድኅኖ ክብር ከነገሥታቱ ዘንድ የተዋጋ:
*በጦማር (በደብዳቤ) ለዓለም የሰበከ:
*ስለ እመቤታችን ተናገርክ ብለው ቀኝ እጁን የቆረጡት::

*እመ ብርሃን ግን እንደ ገና የቀጠለችለት:
*በበርሃ ውስጥ ለዘመናት በገድልና በጽሙና የኖረ:
*ከ10ሺ በላይ ድርሳናትን የደረሰ:
*ከዐበይት ሊቃውንት የሚቆጠር ቅዱስ አባት ነው:: (ዛሬ ዕረፍቱ ነው)

+*" ቅድስት በርባራ "*+

=>በዘመነ ሰማዕታት (በ3ኛው ክ/ዘ) የነበረች:
*በአረማዊ ንጉሥ አባቷ ጣዖት እንድታመልክ ብትገደድ "እንቢ" ያለች:
*ከባልንጀራዋ ዮልያና ጋር በፍጹም ትእግስት የታገለች:

*የአባቷን ምድራዊ ክብር ንቃ ስለ ክርስቶስ መከራን የተቀበለች:
*በአባቷ እጅ ከቅድስት ዮልያና ጋር የተገደለች:
*እጅግ ብዙ ተአምራትንም የሠራች ቅድስት: ወጣት ሰማዕት ናት:: (ዛሬ ዕረፍቷ ነው)

+" አባ ኤሲ "+

=>በዘመነ ሰማዕታት በግብጽ (ቡጺር) ከደጋግ ክርስቲያኖች የተወለደ:
*ከልጅነቱ ጀምሮ ዓለምን የናቀ:
*በወጣትነቱ የነዳያንና የእሥረኞች አባት የተባለ:
*ቅድስት ቴክላ የተባለችና እመቤታችን የምታነጋግራት እህት የነበረችው:

*ቅዱስ ዻውሎስ ከሚባል ባልንጀራው ጋር ሰማዕታትን በመንከባከብ ያገለገለ:
*በመንፈሳዊ ቅናት ከዻውሎስና ቴክላ ጋር ለሰማዕትነት የቀረበ::

*እጅግ ብዙ መከራዎቸን የተቀበለ::

*ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሱርያል ወደ ሰማይ አሳርጐ ክብረ ቅዱሳንን ያሳየው::

*ቅዱሳንን የሚዘክሩ ሰዎችን ክብር አይቶ የተደነቀና::
*ከብዙ ተከታዮቹና ቅድስት እህቱ ጋር የተሰየፈ ታላቅ ሰማዕት ነው:: (ዛሬ ዕረፍቱ ነው)

+*" ቅድስት እንባ መሪና "*+

=>በዘመነ ጻድቃን በምድረ ግብጽ የተወለደች::

*ከአባቷ ጋር መንና ወደ ወንዶች ገዳም የገባች::

*ወንድ መስላ የወንዶችን ቀኖና በምንኩስና የተቀበለች::

*ያለ አበሳዋ (ወንድ መስላቸው) "ዝሙት ሰርተሻል" ተብላ ወደ በርሃ የተባረረች::

*ያልወለደችውን ልጅ ያሳደገች::

*ያለ ምግብና ውሃ ለ3 ዓመታት የተሰቃየች::

*ብርድና ፀሐይ የተፈራረቀባትና:

*ስታርፍ ክብሯ የተገለጠላት ቡርክት እናት ናት:: (ዛሬ ልደቷ ነው)

+*" አቡነ ተክለ አልፋ "*+

=>በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን በኢትዮዽያ የተነሱ::

*ደብረ ድማሕን / ዲማን (ጎጃም) የመሠረቱ::

*በፍጹም ተጋድሎ የኖሩ::

*ምድረ ጎጃምን በስብከተ ወንጌል ያበሩ::

*በሊቅነታቸው የተመሠከረላቸው::

*መልክአ ኢየሱስን እንደ ደረሱ የሚነገርላቸው::

*ብዙ ተአምራትን የሠሩ (ዛሬም ድረስ የሚሠሩ)::

*የሃገራችን ትምክህት የሆኑ ታላቅ ሐዋርያዊ አባት ናቸው:: (ዛሬ ዕረፍታቸው ነው)

+*" ቅዱስ ገብረ ማርያም "*+

=>በ16ኛው መቶ ክ/ዘ በምድረ ኢትዮዽያ የተወለደ::
*ስም አጠራሩ ያማረ:
*ዛሬ እናንተና እኔ ለምናደርገው የቅዱሳን መታሰቢያ መሠረት የጣለ
*በዓመቱ የሚከበሩ ሁሉን ቅዱሳን የሚዘክር

*365ቱን ቀናት በምጽዋት የተጠመደ:
*የነዳያን አባት የሆነ:
*በአፄ ልብነ ድንግል ግራኝ አህመድ መምጣቱን ሲሰማ ያልደነገጠ:
*ሃብት ንብረቱን ለነዳያን አካፍሎ: ነጭ ልብስ ለብሶ ገዳዮቹን የጠበቀ::
*እንዲያ እንዳማረበት የግራኝ ወታደሮች የሰየፉትና ሞገስ የሆነን አባት ነው:: (ዛሬ ዕረፍቱ ነው)

=>እነዚህንና ስማቸውን ያልጠራናቸውን ሌሎች ቅዱሳንን ዜና ማንበብ: በስማቸው መልካሙን ማድረግና መዘከር ዋጋው በሰማያት ታላቅ መሆኑን ገድለ አባ ኤሲ እና ታላቁ ቅዱስ መጽሐፍ ይናገራል:: (ማቴ. 10:41, ዮሐ. 4:36, ዕብ. 6:10)

=>አምላከ ከዋክብት ቅዱሳን ከዓመጸኛው ትውልድ ይሰውረን:: በረድኤታቸው ጥላ ጋርዶ: ለበረከታቸው ያብቃን::

=>ታሕሳስ 8 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ታላቁ አቡነ ኪሮስ
2.አባ ሳሙኤል ዘደብረ ቀልሞን
3.አባ ዮሐንስ ዘደማስቆ (ሊቁ)
4.አባ ኤሲና ቅድስት ቴክላ
5.ቅዱሳት በርባራና ዮልያና
6.ቅድስት እንባ መሪና
7.አባ ተክለ አልፋ ዘደብረ ድማሕ
8.ቅዱስ ገብረ ማርያም ተአማኒ
9.አባ ያሮክላ ሊቀ ዻዻሳት
10.አቡነ እስትፋሰ ክርስቶስ (ልደታቸው)

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ሙሴ ሊቀ ነቢያት
2.አባ ብሶይ (ቢሾይ)
3.ቅዱሳን 4ቱ እንስሳ (ኪሩቤል)
4.ቅዱስ ማትያስ ሐዋርያ (ከ12ቱ ሐዋርያት)

=>+"+ እግዚአብሔር ቅዱሳንን ስላገለገላችሁ: እስከ አሁንም ስለምታገለግሏቸው ያደረጋችሁትን ሥራ: ለስሙም ያሳያችሁትን ፍቅር ይረሳ ዘንድ ዓመጸኛ አይደለምና:: በእምነትና በትእግስትም የተስፋውን ቃል የሚወርሱትን እንድትመስሉ እንጂ ዳተኞች እንዳትሆኑ ተስፋ እስኪሞላ ድረስ እያንዳንዳችሁ ያን ትጋት እስከ መጨረሻ እንድታሳዩ እንመኛለን::+"+ (ዕብ. 6:10)

<ወስብሐት ለእግዚአብሔር>
Encoderbot file id92219 64k 16k
ስንክሳር ዘወርሃ ታህሣሥ ስምንት(፰)
https://www.tg-me.com/SinkisarZekidusan2
2024/09/30 22:28:52
Back to Top
HTML Embed Code: