Telegram Web Link
[ በመጀመሪያው መንገድ የሚተውሽ ሰው ደስታሽን ይሰርቅሻል ]

የፍቅር ግንኙነት ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው በተመሳሳይ ግለት እና ስሜት አይዘልቅም። የትኛውም ፍቅር የራሱ ኡደት አለው።

የፍቅርን ተአምር ለማየት ጊዜ ያስፈልግሻል። ፍቅር ጥንካሬን ብቻ ሳይሆን ብልሀትን ይፈልጋል። የተሳካ የፍቅር ጉዞ ተለዋዋጭ ነገሮችን ተቀብሎ እራስን እያስተካከሉ መሄድን ይፈልጋል።

ፍቅርን ስንጀምር እጃችን ውስጥ የገባውን ውድ ሀብት እናስተውለውም። ለራሳችን የምንሰጠው ግምት ነገሩን ቀለል አድርገን አይተን ለጨዋታ አይነት በሚመስል መንገድ እንድንጀምር ያደርገናል። እንደቀልድ የፅሁፍ መልዕክቶችን ከመለዋወጥ ወደ ስልክ ማውራት፤ ለደቂቃዎች ከማውራት አብሮ ሲያወሩ ሌሊቱን ወደ ማንጋት ይሸጋገራል። በቃ ሁሉም ነገር ደስታ እና ፈንጠዝያ ብቻ ይሆናል። በአጋጣሚ ትንንሽ አለመግባባቶች ከተፈጠሩ ግብረ መልሶቻችን ከልክ በላይ ይሆናሉ።

ተስፋ እና ፍርሀትን ጎን ለጎን ይዘሽ ለመሄድ ትሞክሪያለሽ። ሁሌም አሁን ያለው ወንድ ከበፊቶቹ የተሻለ እንደሆነ ታስቢያለሽ። ከጥሩ ጥሩው ነገር በዛ ያለውን፤ ከመጥፎ ከመጥፎው ደግሞ አነስ ያለ (አንዳንድ ጊዜ ጭራሽ ድክመት የሌለው) ነገሮችን የያዘ ወንድ እንዳገኘሽ ይሰማሻል። ችግሩ አብሮሽ ያለው ወንድ "የገባው" ካልሆነ ሊጫንሽ ይሞክራል። አንቺ ደግሞ ነፃነትሽ አሳልፈሽ መስጠት አትፈልጊም። ይህ ነገር ሲደጋገም አንቺ ፈላጊ እሱ ተፈላጊ አይነት ስሜትም ሊሰማሽ ይችላል።

ይሄንን ፍቅር ለማስቀጠል ፍርሀትሽን ተቋቁመሽ ሊመጡ የሚችሉትን ያልተገመቱ ነገሮች እየፈታሽ፤ ራስሽን ገዝተሽ ለመኖር ትገደጃለሽ። ይሄ ግንኙነት ወደ ፍቅር ካደገ ለሰዎች ድብቅ የነበሩ ማንነቶችሽን ለዛ ወንድ ቀስ በቀስ መግለጥ እና ማሳየት ይመጣል። እነዚህን ነገሮች አብሮሽ ያለው ወንድ ለማሸነፊያነት ሊጠቀምባቸው ሲሞክር ይሄንን ተከትሎ ጭንቀት፣ ውጥረት እና አለመረጋጋት ሊሰማሽ ይችላል። በስሜትሽ ለራስሽ "ትልቅ" ነኝ ብለሽ ስታስቢ የኖርሽውን ሴት በአንዴ እንደ ህፃን የሆንሽ መስሎ ይታይሻል።

እዚህ ጋር ነው አዲሱ ፍቅር ጉልበትሽን እየጨረሰው፣ ትኩረትሽን እየሰረቀሽ፣ አንድ ሰውን ከማሰብ በስተቀር ሌላ ነገር ለማድረግ አቅም እንዳሳጣሽ፣ ጨቅጫቃ እና ነዝናዛ የሆንሽ የሚመስልሽ፣ በግንኙነቱ ቀጣይነት ላይ ፍራቻ የሚሰማሽ ከሆነ፣ ከእነ አካቴው ረስተሽው የነበረው የቀደመ የፍቅር ህይወትሽን አፈፃፀም እየደጋገምሽ ማሰብ ከጀመርሽ ህልምሽ እንጂ ፍቅርሽ ሩቅ ተጓዥ አይደለም።

ለዚህ ሁኔታ አብቅቶሽ ጥሎሽ የሚሄድ ወንድ ፍቅርን እንድትሸሺ ባያደርግ እንኳን ደስታሽን ይነጥቅሻል !

by Abby

@wegoch
@wegoch
@paappii
ከተለቀቀ ቡኃላ በሁላችንም ዘንድ እጅግ የተወደደው አልበም ሊያልቅ አንድ ዘፈን ቀርቶታል። ሙዚቀኛው "የመጨረሻዋን ዘፈን ነፍሷን አላገኘሁትም" በሚል ጭንቀት ከተወጠረ ወራት ተቆጥረዋል። ድምፃዊው ጥበቃው ደክሞት ዘፈኖቹን ከስቱዲዮ አስዘርፎ ስለሚያወጣበት መንገድ እያሰበ ነው።

"የቀረው ግጥሙ ብቻ ነው አይደል? እሱን ደግሞ በአምስት ደቂቃ መጨረስ እንደምትችል በተደጋጋሚ አይተናል። ችግሩ ምንድን ነው?" አለ እየተማረረ።

(ድካም ተሰማው ሙዚቀኛው) "እውነቱን ልንገርህ? ... እኔ አንተ እንደምታስበው አይነት እውነተኛ አርቲስት አይደለሁም።" አለ በተሸነፈ ድምፅ።
"እንዴ? እና ታዲያ ምን ልትባል ነው?"

"....እኔ አርቲስት ሳልሆን ሙዚቃ በመስራት የሚያገግም በሽተኛ ነኝ።"
"አልገባኝም!"
"ማለቴማ...የሆነ ህመም ሲያንሳፍፈኝ እንጂ እንደ'ናንተ በፈለግኩት ሰዓት ተነስቼ መብረር የምችልበት ክንፍ አልታደልኩም። እኔን አርቲስት ማለት እፉዬ ገላን 'በራሪ ፍጡር ነች' እንደማለት ነው።"

"እስኪ ተው በናትህ!...አንተ አርቲስት ካልተባልክማ እኛ ስቱዲዮ ድርሽ ማለት የለብንም።"
"አያይ...እናንተማ ባሻችሁ ሰዓት ድምፃችሁን ማዘዝ ትችላላችሁ። አዬህ? ክንፉ ተሰጥቷችኋል። ትክክለኛ ስታሮች እናንተ ናችሁ።"
"ትሰማኛለህ?!...እኛ ኮከብ ከተባልን አንተ ፀሀይ ነህ። ምክኒያቱም የምናፀባርቀው ያንተን ብርሀን ነው። ይሔንን መቼም እንዳትረሳ።" (ሁኔታው ስላስፈራው በራስ መተማመኑን ሊመልስለት ታገለ።)

"ፀሀይ?!.." ፂም አልባ ፊቱን እየደባበሰ "...ታውቃለሀ እሷንም እኮ ከርቀት ስለምናያት ነው እንጂ የምታበራ የሚመስለን ጠጋ ብለን ስናያት እየነደደች ነው። The sun is actually burning. ...እንደምትለው 'ፀሀይ' ከሆንኩ እንኳን... ወይ ነድጄ አልቄያለሁ። ወይ ደግሞ የሚለኩሰኝ አጋጣሚ አጥቻለሁ።"

"እንዲህ እንደዋዛ የምትነግረኝን ወሬዎች ቤት እንዲመቱ ብታደርጋቸው እኮ ጨርሰናል ወንድሜ።"
"ግጥሙ በውስጡ አምቆ የሚይዘውን ታሪክ ሳናገኝ? በድኑን ብቻ ልናውጣው? ያለ ነፍሱ? ተው እንጂ!!..ስንቴ ነው የምነግርህ እንደዚህ እንደማይሆን?!"
"ምናለበት አንዳንዴ እንኳን ቀለል ብትል አንተዬስ?! ሁሉንም ነገር ካላመናፈስክ ደስ አይልህም እንዴ?!..." ሊስቅ ብሎ ፊቱ መቀያዬሩን ሲያይ ደንግጦ ዝም አለ።

(ሙዚቀኛው እንዳኮረፈ ስቱዲዮውን ጥሎለት ወጣ።)

ዘፋኞቹ ሁላ ወሬ አስጀምረውት ጠለቅ እያለ ሲሔድባቸው ጨዋታውን ወደ ሹፈት የሚቀይሩበት ነገር ሊለመደው ያልቻለ የጋራ አመላቸው ነው። "..'በልተህ ላትበላ አታስፈትፍተኝ፤ ጠተህ ላትጠጣ ጋን አታስከፍተኝ' የሚለው እኮ ወዶ አይደለም አያ ሙሌ።" እያለ ብቻውን እያነበነበ ወጣ።

ሰዎች እንዳይለዩት አፉን በስካርፍ...አናቱን ደግሞ በኮፍያ ከልሏል።
በአይኖቹ አካሔዱን የሚኮርጀውን ጉብል፤ ፈገግታዋን የሚዋሳትን ሴት ያማትራል።
"በህይወት ካሉ ሰዎች ላይ ብቻ ነው ታሪኬን የምወስደው እንጂ ፈጥሬ አልፅፍም!" የሚል ፍልስፍና አለው። ለዚህም ነው ደራሲ ሲሉት "ደራሲ አትበሉኝ...የአምላክ ጋዜጠኛ ነኝ!" እያለ የሚሟገተው። (ሀይማኖተኛ ነኝ ቢልም ፍልስፍናው ሳይበዛ አይቀርም።)

ጎዳናው ላይ እየኳተነ መሸበት። ቢጨንቀው ከአመታት ቡኃላ ግሮሰሪ ገብቶ ተቀመጠ። ሲገባ በተስፋ መቁረጥ እንጂ "ፍለጋዬ የሚቋጭበት ቀን ይሆናል!" በሚል ጥርጣሬ አልነበረም።

ከተቀመጠበት ጠረጴዛ ላይ ብዙም ሳይቆይ ሁለት ጠብደል ጎረምሶች ሳያስፈቅዱት ተቀመጡ። ውሀውን ጨበጥ እያደረገ በሰቀቀን አያቸው። አንደኛው ሁኔታውን አይቶ..."ከደበረህ መነሳት ትችላለህ!..ይሔ የኛ ቦታ ነው።" አለው።
"ኧረ...ኧረ ችግር የለውም። እንዲያውም ልሔድ ስል ነው የመጣችሁት።" አለና ሒሳቡን ለመክፈል አስተናጋጁን በእጁ ጠራው። ወዲያው ሶስተኛ ሰው ወደነሱ ጠረጴዛ መጥቶ እየተቀላቀላቸው..."አንድ ጮማ ወሬ ብነግራችሁ ድራፍት ትጋብዙኛላችሁ?" አለ።
"እንደ ወሬው ጮማነት ይወሰናል!" አሉት።
"በሱ ምንም ጥርጥር አይግባችሁ።"
"እሺ ቀጥል!"

ሙዚቀኛው ለአስተናጋጁ ሂሳብ መክፈሉን ትቶ ለራሱም ቢራ እያዘዘ ጆሮውን ቀሰረ።

"እሺ..." አለና ወንበር ስቦ ድራፍት ካዘዘ ቡኃላ ግማሽ አድርሶ እስኪያስቀምጠው ድረስ "ቆዩ" እያለ ትግስታቸውን ተፈታተነው። ሙሉ ትኩረታቸውን ማግኘቱን ሲያውቅ...."ትላንትና ማታ ሌላ ሰፈር ሂጄ እየተዝናናሁ ነበር።" ብሎ ወሬውን ጀመረ።..."ከዛ ማንን ባገኝ ጥሩ ነው?"
"ማንን አገኘህ?"
"የቢኒን ሚስት ማሒን!"
"እንዴ? ምን እየሰራች?" (ሌላኛው)
ዘና ብሎ ወደኋላ እየተደገፈ..."ቂጧን አስጥታ እ የ ሸ ረ ሞ ጠ ች ነዋ!"

ባለማመን አዩት።

ስልኩን አውጥቶ ፎቶ እያሳያቸው ሌላ ድራፍት አዘዘ። ሙዚቀኛው ሰረቅ አድርጎ ሊያይ ቢሞክርም አልመቸው አለ። ጠብደሎቹ ፎቶውን በግርምት እያዩ .. "ጭራሽ ተኝተሀታል?...የፈጣሪ ያለህ!"
(ፎቶው ከጠረጴዛ ጠረጴዛ መዟዟር ጀመረ። ግሮሰሪዋ ባንድ እግሯ ቆመች።)

ድንገት አንድ ሰው እየገነፈለ ወደ ውስጥ ከገባ ቡኃላ ወሬኛውን ልጅ ተንደርድሮ በቦክስ ነረተውና ወለሉ ላይ ዘረረው። ሁሉም ፀጥ ብሎ ሲያይ ሙዚቀኛው ሩጦ ገብቶ መገላገል ጀመረ። ሌሎቹም ከድንጋጤያቸው ነቅተው መሀላቸው ገቡ። የወደቀውን ልጅ አፋፍሰው ወደ ጓዳ ወሰዱት። የሚገለገለው ልጅ መንጭቆ ወደ ገላጋዩ ሲዞር...ያዬውን ሰው ማመን አቅቶት...."እንዴ ኤላ? እዚህ ምን ትሰራለህ?" አለ ግራ ተጋብቶ።
ሲያገላግል ስካርፍ እና ኮፍያው መውደቁ ታውቆት ፀጉሩን እያከከ ዝም አለ ሙዚቀኛው።
"የምትተዋወቁ ከሆነ አንተ እሱን ይዘህልን ውጣ ወንድሜ!" አለው አንደኛው ወደ'ሱ እየመጣ። ተያይዘው ወጡ።

ወጣቱ ከግሮሰሪው ከወጡ ቡኃላም በግርምት ማዬቱን አላቆመም። ጠቁሮበታል። ተጎሳቁሎበታል። ግን ሊጠይቀውም አልፈለገም። እንዳይሰማው ብሎ ... "ያው ብዙዎቻችን ከካሜራ ጀርባ ያሉ አርቲስቶችን በመልክ ስለማናውቅ ነው እንጂ ስምህን ብነግራቸው ሁሉም ያውቁህ ነበር!" አለ።
"ይገባኛል።" አለ ሙዚቀኛው እንዴት ወሬውን እንደሚያስጀምረው እያውጠነጠነ።

ትንሽ ዝም ዝም ተባብለው ቆዩ።

ልጁ አሁንም እጁን እያፍተለተለ "ባይዘዌ ሚስቴ ሴተኛ አዳሪ አይደለችም።" አለ።
"ኧረ? አይ ጥሩ...ጥሩ ነው።" አለ በሀፍረት አቀርቅሮ።
"የምሬን ነው!..መንታ እህቷ ነች ያን ስራ የምትሰራው። ውሀ እና ፀበል ናቸው። መልካቸው እንጂ ውስጣቸው አይገናኝም። ወይም ጨረቃ እና ፀሀይ በላቸው። ቅርፃቸው እንጂ ብርሀናቸው አይመሳሰልም።" እጁን በእልህ ጨበጥ ዘርጋ እያደረገ..!
"እና ውሸት ከሆነ ምን ስሜታዊ አደረገህ? ማስረዳት አይቀልም ነበር?"
"ልክ ነህ እሱማ ግን....ባልዋለችበት ስሟ ሲነሳ...ባልሰራችው ወንጀል እየተቀጣች ሳይ በጣም ከፋኝ። ትዕግሥት አጣሁ እውነት!! መጀመሪያ ላቅምሰው አልኩ።" ሳቀ!

ሙዚቀኛው ከረጅም ጊዜ ቡኃላ እፉዬ ገላ ነፍሱ ከያዛት አጥር ተላቅቃ በህይወት ንፋስ ወደላይ ስትንሳፈፍ ተሰማው። እሱም ፈግግ አለ። የዛኑ ምሽት ስቱዲዮ ገብቶ የመጨረሻዋን ዘፈን በግጥም ሞልቷት አደረ። ድምፃዊው ሲያዬው "እንኳን ጠበቅኩህ!" እያለ በደስታ አቀነቀነው። እንዲህ እያለ...

"ግልፅ እውነትሽ መች ጠፋኝ?
ባላዩት እንጂ ባሙሽ የከፋኝ!

"ሌትም ወ'ታለች አሉ
አንቺን በማታ...ጨረቃ እያዩ!..

"ስትመጭ አይን ያያል...መውጣትሽን
ጧት ሲነጋ..ሲመሽ መግባትሽን
የሞቀው ወርቃማ ብርሀንሽን
ጨፍኖስ ማን ያጣል ተፈጥሮሽን? (×2)..
"አውቃለሁ አንቺ አይደለሽም! ... አንቺ ቀን ነሽ በቃ
'እሷው ነች አታርፍም' ቢሉም...ቢያሙሽም በጨረቃ
እያዬው ሳይመሽ በጊዜ ... ቀን ተግተሽ ስትሰሪ
ማታ ግን ተራሽ አይደለም...ምን በወጣሽ ልትበሪ?!..

"ጀንበርዬ ጀንበርዬ ጀንበርዬ ጀንበርዬ
ጀንበርዬ ጀንበርዬ ጀንበርዬ ጀንበርዬ..."



(፨ የግርጌ ማስታወሻ:- ይሕ "እንዲህ ቢሆንስ?" በሚል ስራ ፈትነት የተፃፈ ልብወለድ ብቻ ነው)

@wegoch
@wegoch
@paappii

By mickel Azmeraw
[ የዘገያችሁ ከመሰላችሁ .... ገና ናችሁ]

አንዳንድ ሰው በ24 አመቱ ተመርቆ ስራ ለማግኘት 6 አመት ሊፈጅበት ይችላል

አንዳንዱ በ24 አመቱ የድርጅት ስራ አስኪያጅ ሆኖ በ30 አመቱ ሊሞት ይችላል

ሌላው ስራ አስኪያጅ ለመሆን የ26 አመት ልምድ አስፈልጎት 80 አመቱ ኖሮ ይሆናል

አንዳንዱ በ49 አመቱ ገና ላጤ ሆኖ ህይወቱን ለመቀየር ሲታገል የትምህርት ቤት ጓደኛው የልጅ ልጅ አይቶ አያት ለመሆን በቅቶ ይሆናል

ኦባማ በ55 አመቱ ጡረታ ሲወጣ ትራምፕ በ70 ባይደን በ77 አመታቸው ነው ፕሬዝዳንት የሆኑት

በዚህች ምድር ላይ ሁሉም የራሱ ጊዜ አለው

ሰዎች የቀደሙህ ወይም አንተ የዘገየህ ሊመስልህ ይችላል። አንተ ወደፊት ገስግሰህ ሌላው ወደኋላ የቀረ መስሎ ሊታይህም ይችላል።

እውነታው ግን ሁሉም ሰው በራሱ ጊዜ፣ በራሱ ፍጥነት እየሮጠ ነው።

አንተም በራስህ እነሱም በራሳቸው ጊዜ ከተፃፈላቸው ቦታ አይቀሩም።

ልጅ ለመውለድ፤ ገንዘብ ለመያዝ፤ ትዳር ለመመስረት፤ አገራችሁ ለመግባት፤ ተምሮ ለመመረቅ፤ ለመዝናናት ...... የዘገየህ ለመሰለህ ....

አልዘገየህም፤ ከማንም አትቀድምም፤ በራስህ ጊዜ ላይ ነህ !!

By Abby abby

@wegoch
@wegoch
@paappii
ፉንግግ ያለ ፉንጋ ነበር። የጥርሶቹ ትልቀት፣ የአፍንጫው አቀማመጥ፣ የፀጉሩ ግንባሩ ድረስ አመጣጥ፣ አጉጩን ሳይቀር አለማስተዋል አይቻልም ... ተፈጥሮ እንዴት እንደጨከነችበት ሳየው ይገርመኛል ተቀራረብን... ከፉንጋነቱ ጎን ለጎን ጥሩ ያስባል አዛኝ ልብ አለው።

እይታው ጥሩ ነው ፣ ጭንቅላቱ ላይ ቀድሞ የተንሻፈፈ ነገር አይታየውም ፣ ፉንጋነቱ አይታወቀውም ፣ መልኩ ላይ እየቀለደ ፉንጋነቱን ኖርማል ለማድረግ አይሞክርም፣ የፊቱን አቀማመጥ እረስቶታል ....

ብዙ መደዋወል ያዝን .....ይሰማኛል፣ ይጠይቃል አሰማሙ እና አጠያየቁ እሱ ኑሮ ያለው አይመስልም ፤ ገጠመኝ የሚያገኘው አይመስለኝም።

በመስማት ብቻ ለካ መጉላት ይቻላል !!

ከአልአዛር ጋር ተዋደድን ። አልአዛር ፉንጋነቱ ተረሳኝ ...አይደለም ውበቱ ታየኝ ። አልአዛር ቆንጆ ነው። አንድ ቀን ከፍቶኝ ቤቱ ሄድኩ አልጋው ላይ ተኛን አስተቃቀፉ አለሁልሽ አለው ።

እንደ እህቱ እንደታናሹ አቀፈኝ ። ቀዝቀዝ ያለ ውሃ በማስታጠቢያ አምጥቶ ቀለል አድርጎ፣ ለግልግል እንዳላመች አድርጎ እግሬን አጠበኝ። እንደቀዝቃዛ ውሃ መንፈስ የሚያረጋጋ ነገር የለም እያለ በውሃ ዙርያ ትንታኔ አቀረበ ።

ንግስት የመሆን ስሜት ይሰማኛል ከሱ ጋ ስሆን Safe Zone
ነው ።

አልአዛር ቆንጆ እንደሆነ የማውቀው እኔ ብቻ ነኝ መሰለኝ ። እናቱ ሳይቀር መልኩ ላይ እንደሚቀልዱ በጨዋታ መሃል አንድ ሁለቴ ነግሮኛል ።

መቼ ነው ፎንጋነቱ የተነነብኝ ?
መቼ ነው ከበጣም ቆንጆ ልጅ በላይ የደመቀብኝ??
መቼ ነው የቆነጀብኝ ??

አላውቅም ግን አላዛር ቆንጆ ነው !!

አልአዛር ጋር ሳንገናኝ ወይ ሳንደዋወል አንውልም ። ገጠር ሄጄ ስመለስ ከድፍን ከተማው አልአዛር ብቻ ነው የሚናፍቀኝ ። ከአልአዛር ጋር ብሄድ ምን ምክንያት አለ ተመለሺ ተመለሺ የሚለኝ ??

አልአዛር ጋ አብሬው ተኝቼ ለሊት ላይ የተገለጠ ገላዬን ያለብሰኛል። ለጥቃቅኑ ስሜቴ ቦታ ይሰጣል ።

አብረን እቤቱ ስናድር
በጠዋት ተነስቶ የሆነ ነገር ገዝቶ ስነሳ የምንሰራው ወይ የምንበላው ያመጣል ...ለምዶኝ ችላ አላለኝም።

ምቾት ተሰማኝ ፤ ማንም አይቀማኝም ብዬ መሰለኝ ፣
ጨዋ ነው ብዬ መሰለኝ፣ የሚሰማኝ፣ የሚያግዘኝ ስላገኘሁ ነው መሰለኝ እለት እለት ፍቅሬ ጠነከረ ።

ድንገት የሆነ ቀን "እንለያይ" አለኝ ....ሳኩኝ። በርግጥ አንድ ሁለት ሳምንት ሙሉ ደብዝዞ ነበር ፣ እየራቀኝም ነበር። እኔ ከራሱ ጋር የተጣላ ነበር የመሰለኝ ።

ላለማስጨነቅ ነበር ምን ሆንክ ላለማለት የሞከርኩት

እሱ ፀቡ ከኔ ጋ ነበር መሰለኝ ...

ቀለል አድርጎ ነበር እንለያይ ያለኝ ።እኔ እና እሱ መሃል ጭቅጭቅ፣ መዋደድ ፣ መሳቅ እንጂ የመለያየት ፅንሰ ሃሳብ እንዳለ አላውቅም ነበር ።

"እንለያይ" አለኝ ..... "እየቀለድክ ነው አልአዛር ?"
"እውነቴን ነው ሶሲ "

የሆነ መፍራት ነገር ወረረኝ ። "ባይሆን አሪፍ ጓደኛ እንሆናለን እንደ ድሮ አለ ።"

የማደርገው ስላጣሁ ዝም አልኩ: እምባዬ ግን ፈሰሰ።
" ምን አደረኩ?
፣ ምን አደረገች ብለው ነግረውህ ነው? ፣
ምን ያልኩት ነገር ልብህ ውስጥ ሃዘን ፈጥሮ ነው? "

"ተይ አታወሳስቢው ሶሲ ተይ you are one of the strongest women I know ጓደኝነታችን አይቆምም እኔ ሪሌሽንሺፕ ይሰለቸኛል።"

እንዴ?! እንዴ ?! አላዛር አልመስል አለኝ

ጥሩ ልብ መኖሩ ፣ አዛኝነቱ ፣ አይነግቡ አለመሆኑ
መውደዴ .....የቱም እንዳይተወኝ ዋስትና አልሆነኝም ። ያስደነገጠኝ ፊቱ ላይ ያስነበበኝ የበቅቶኛል ሁኔታው ነው ።

ደነገጥኩ !!

ፈራው.

አዘንኩ መጠን አልባ ሃዘን ልቤ ውስጥ ተንከላወሰ።

መለመን ፈልጌ ነበር ፣ የሆነውን ማወቅ ፈልጌ ነበር ፣ተረጋግቼ ላናግረው ፈልጌ ነበር፣ ሲያቅተኝ ከተቀመጥንበት ጠረጴዛ ላይ አጎንብሼ አለቀስኩ ሰዎች ትኩረታቸው ወደ እኛ ሲሆን መሰለኝ ፦

"ኧረ አንቺ ልጅ This is totally attention-grabbering

አረጋጊው !

ሁኔታው ንግግሩ ከእንለያዩ የበለጠ ጎዳኝ ።ቀጥ ብዬ እያለቀስኩ ከፊቱ ከካፌው ከኑሮው ሄድኩኝ

አልተከተለኝም .....

በነጋታው ይመስለኛል ከእንቅልፌ ስነቃ ተስፋ ሙቁረጥ መላ አካላቴ ላይ ተጥለቅልቋል ። መነሳት አልቻልኩም ሁኔታው፣ አወራሩ፣ አኳኋኑ ፣ ልቤ ላይ መከዳት ተንጋለለብኝ ።
የአልፈልግሽም ውሳኔው ፣ ለሱ የነበረኝ ቦታ ፣ ክህደቱ በደም ዝውውሬ ተሰራጭተው ስነቃ አላላውስ ብሎኝ ነበር ።

ለሦስት ወር ከሃያ ቀን በራችን ጋ ካለው ሱቅ በቀር የትም አልሄድኩም።

ስልኬን ዘጋሁት ፣ ተብሰለሰልኩ፣ ተምሰለሰልኩ ፣
ሙዚቃ አልሰማሁም፣ ፊልም አላየሁም፣ ከወዳጆቼ ጋር አልተገናኘሁም ፣

ስለገንዘብ አላሰብኩም ፣ ሁሉን እርግፍ አድርጌ ተውኩት ። ከአልጋዬ አልተላቀኩም ፣ ከተከረቸምኩበት ስወጣ ከብዙ ግዜ በኃላ መስታወት አየሁ ሽበት ጣል ጣል ብሎብኝ ነበር ፣ ገርጥቼ ነበር፣ ብዙ ግዜ ጨለማ ክፍል ውስጥ የነበርኩ እመስል ነበር ።

የሆነ ቀን፤ ከሆነ ግዜ በኋላ ለፆታዊ ግንኙነት ያለኝ ቦታ ቀዝቅዟል። በወሬ መሃል ሳይታወቀኝ ከልቤ ግድ ነው እንዴ መጥበስ ? ግድ ነው እንዴ ፆታዊ ግንኙነት ፣ማግባት ግድ ነው ? የሰው ልጅን የተባለ ፍጡርን አምኖ ነገን በጋራ አብሮ ማለም መራመድ ይቻላል? ?

ምንስ ፉንጋ ቢሆን
ምንስ አዛኝ ቢሆን
ምንስ አሳቢ ቢሆን
ምንስ ቆንጆ ቢሆን

የሆነ ቀን ቢከዳንስ ዋስትናችን ምንድን ነው ?? እያልኩ ለነገ ዋስትና የሚሰጠኝ ፍለጋ ስሞግት ድምፄን ሰማሁት

ከጉዳቴ ያገገምኩ መስሎኝ ነበር ! ቁስሌ አልደረቀም ማለት ነው ? መዳን ስንት እድሜዬን ይበላ ይሆን ??

By Adhanom Mitiku

@wegoch
@wegoch
@paappii
እማማ እንዴት እንደሞተች...!
...
አባባ የስራ ሰው ነው። ሰፈር ውስጥ ስለሱ ሲያወሩ «ከስራው በቀር ምንም የማያውቅ ጨዋ» ይሉታል። እሱ ደግሞ አንድ ቀን እማማን አይን አይኗን እያየ «ትርንጎየ…እኔኮ ከስራዬ ቀጥሎ እወድሻለሁ» ብሎ ሲያስቃት ሰምቼዋለሁ። እሷ ትሳቅ እንጂ እኔ ግን የምሩን እንደሆነ አውቅ ነበር።
ብዙ ጊዜ ቀን ቀን ሲሰራ ውሎ ማታ በጊዜ ነው የሚመጣው። የሆነ ወቅት ላይ ግን ይህ ልምዱ ተቀየረ። የተቀየረው ባንዴ አይደለም ፤ ሚስቱ ትርንጎዬ እና እኔ ልጁ ሳናውቅበት ቀስ በቀስ ነው።

በመጀመርያ ሰሞን… ትንሽ አምሽቶ ነበር የሚመጣው። ያኔ እማማ እና እኔ እራታችንን ሳንበላ ቴሌቬዥን እያየን እንጠብቀዋለን። እሱ ካልመጣ አንበላም። እኔ በርግጥ ስለሚርበኝ እሱን የምጠብቅበት ትዕግስት አልነበረኝም። ግን እማማ እሱ ካልመጣ አትበላም። አንድ ጊዜ ለምን እንደሆነ ጠይቄያት «የነፍስ ጉዳይ ቢመጣ እንኳ ትቼው አልበላም» ነበር ያለችኝ። እኔ ደግሞ እሷ ካልበላች አልበላም። እጆቿን እንደገዛ መዳፌ ለምጃቸዋለሁ። ለስሙ እሰየማለሁ እንጂ በጉርሻዋ ነው የምጠግበው።

ይህንን አኗኗር ከለመድነው በኋላ ከበፊቱ የበለጠ አምሽቶ መምጣት ጀመረ። የእራት ሰአት አልፎ እንኳ ቶሎ አይደርስም። አሁን እማማ የምትፈተንበት ሰአት ደረሰ። የእኔ ረሀብ እና በትዕግስት የሚያስጠብቃት የአባባ ፍቅር። ግን ለመምረጥ አላመነታችም። ለራሷ አንድ ለእኔ ሁለት እያጎረሰች እራት በላን። የዚያ ሰአት «የነፍስ ጉዳይ ቢመጣ እንኳ ትቼው አልበላም» ያለችውን አስቤ… እናቴ ለካ ቃሏ ከልብ አልነበረም ብዬ… ተገረምኩ። የነፍስ ጉዳይ ቀርቶ የእኔ መራብ ሲመጣ እንኳ ሳታቅማማ አባባን ትከዳዋለች።

ከዚያ አባባ የበለጠ ማምሸት ጀመረ። ማታ ማታ በፍጹም አላየውም። ጠዋት ወይም ቀን ብቻ ነው የማገኘው። ማታ የት እንደሚሆን አላውቅም።

«አባትህ ስራ በዝቶበታል እሺ?» ትለኛለች ። እሷ እንደዛ ስትለኝ እየዋሸች ይሆናል ብዬ አላምናትም።ምክንያቱም ሌሎችን ልትሸውድ ትችላለች እንጂ እኔ ግን አንዳንዴ እንደምትዋሽ አውቃለሁ። አባባን ጠይቄው አዎ ሲለኝ ግን በደንብ አምነዋለሁ። በቃ እሱ የስራ ሰው ነው እላለሁ።

ታድያ የሆነ ሰአት ለመጀመርያ ጊዜ ሲጨቃጨቁ ሰማኋቸው። … በወቅቱ በጣም ልጅ ብሆንም የተነጋገሩትን ግን አሁንም ድረስ አስታውሳለሁ።
«…ሰምቻለሁ! ያዩ ሰዎች ነግረውኛል!…እኔን ከዳሺኝ ትርንጎዬ…እኔን?» ... በጣም እየጮኸና በእልህ እየተንቀጠቀጠ
«…ልጄን ይንሳኝ እልሀለሁ!…ውሸት ነው! የነገሩህ ሁሉ… ውሸት ነው!»
ትንሽ ከተጨቃጨቁ በኋላ ወዲያው ተስማሙ። አባባ ይቅርታ ጠይቋት… እየተሳሳቁ አየኋቸው።

ምስኪን አባት በእኔ ከማለች ያምናታል ማለት ነው። እኔ ግን በጣም ተጠራጠርኩ…ለምን? ምክንያቱም ማታ ማታ የሌላ ሰው ድምፅ መስማት ጀምሬ ነበር። አባባ በጣም አምሽቶ ምናልባትም ሌሊት ነው የሚመጣው። እሱ በሚመጣበት ሰአት ስለምተኛ ሲገባ አላየውም። ግን ምሽት ላይ … የሌላ ሰው ድምፅ እሰማለሁ። የመኝታ ክፍሌ ውስጥ ሁኜ <<ገጭ ጓጓጓ! ገጭ ጓጓጓ!>> የሚል የእግር ኮቴ እሰማለሁ። የአባባ ኮቴ እንደዛ አይደለም። አባባ ሲገባ ደረጃ የሚወጣበት ስልት የለመድኩት ዜማ አለው። <<ገጭ ገጭ ጓ>> የሚል። ይሄ ግን ሌላ ኮቴ ነው። ከኮቴው በኋላ የተኮላተፈ አንደበት ሰላምታ (ት…ል..ን..ጎ..የ.. የሚል)…ከዚያ ደግሞ የመሳሳም ድምፅ ይሰማኛል። ያ የሚመጣው ሰው አንዳንድ ጊዜ ያስለቅሳታል። አላውቅም ለምን እንደሚያስለቅሳት። ከዚያ በኋላ ግን እየሳቀች ስትስመው ድምፁ ይሰማኛል። እና ደግሞ…ሲጥ ሲጥ የሚል የአልጋ ድምጽ!

እስከሆነ ጊዜ ድረስ ሰውየውን በመልክ አላውቀውም ነበር። ሰውየው ከመምጣቱ በፊት እማማ የመኝታ ክፍሌ ውስጥ ስለምትቆልፍብኝ አይቼው አላውቅም። ነገር ግን ኮልታፋ እና የመራመድ ችግር ያለበት ሰው እንደነበር እርግጠኛ ነበርኩ። የሆነ ቀን ይህንን ሰው መንገድ ላይ ፊት ለፊት አገኘሁት። ዘሪሁን ነው ስሙ…ሲናገር ኮልታፋ እና...እግሩ ደግሞ ችግር ያለበት ነው። አንዳንዴ እኛ ቤት ሲመጣ እማማ እንጀራ ትሰጠው ነበር። ፊት ለፊት ስንገጣጠም አገላብጦ ከሳመኝ በኋላ << ያቺ ደግ እናትህ ት..ል…ን..ጎ..የ.. ደና ናት?>> ብሎ ሲጠይቀኝ ከእቅፉ ወጥቼ ሮጥኩ። አባባ እንደዛ አይኮላተፍም። የአባባ ድምፅ እንደሰውየው አይሻክርም። አባባ አያነክስም። አባባ በየመንደሩ እየዞረ እንጀራ አይለምንም። ታድያ ለምንድን ነው የተሻለ ሰው እያላት ከዚህ ሰው ጋር የምትገናኘው? ሁሌም እገረም ነበር። ለአባባ ለመንገር ብዙ ጊዜ ሞክሬ ፈራሁ።

አንድ ቀን ምሽት እራት ካበላችኝ በኋላ ክፍሌ ውስጥ ልትቆልፍብኝ ስትል «እንቢ»አልኳት።
<<ምን ሆንክ?>>

«የሚመጣውን ሰው ማየት እፈልጋለሁ!!» ደነገጠች። ሲሰርቅ እንደተያዘ ሌባ… በረት ውስጥ ገብቶ ባለቤቱ እንደመጣበት ወሮበላ ፣ ማንም አያውቅብኝም ያለው ሚስጥር እንደወጣበት ወራዳ ሰው!…ተንቀጠቀጠች። እኔም ድርቅ ብዬ ቆምኩ። ቁና ቁና እየተነፈሰች ካፈጠጠችብኝ በኋላ ማጅራቴን አንጠልጥላ ወደ ክፍሌ አስገባችኝ። ከዚያ ቆለፈችው።

ከሶስት ቀን በኋላ ት/ቤት ልሄድ ስል አባባን በር ላይ ቁሞ ጢሙን እየከረከመ አገኘሁት። አይኖቹ ደም ለብሰዋል ፤ የስራ ልብሱን እንደለበሰ ነው። አቅፎ ከሳመኝ በኋላ « ምን ሁነህ ነው? » አለኝ። ትኩር ብዬ ተመለከትኩት። ጉዳዩን ከዚያ በላይ ሚስጥር አድርጎ መሸከም ከብዶኛል። መናገር ነበረብኝ።

« አባባ…ማታ ማታ የሚመጣ ሰው አለ »አልኩት… ድንጋጤ ለቅጽበት ድርቅ አደረገው!
«እርግጠኛ ነህ አይተኸዋል?» እየተንቀጠቀጠ
«ፊቱን አላየሁትም…ሰውየው ሊመጣ ሲል…እማማ ትቆልፍብኛለች»አባቴ እጆቹ ተንቀጠቀጡ። በንዴት ጦፈ
«…እሺ የሰማኸውን በሙሉ ንገረኝ..»

ነገርኩት…ስለ እግሩ ኮቴ…ስለ..ኮልታፋነቱ….እንደሚያስለቅሳት…እንደምትስመው….ስለ አልጋው…
ከዚያ በኋላ አባባ ብድግ ብሎ ያደርጋል ያላልኩትን ነገር አደረገ። ጓዳ ገብቶ…መሳቢያውን ከፈተ….ከዚያ ሽጉጡን አወጣ…ከዚያ….
ሁለት ጥይቶችን ተኮሰ…ሞተች!!!!! ዷ! ጠሽ! የሰፈሩ ሰው ግልብጥ ብሎ ወጣ…ጉድ! ጉድ!.ኡኡኡ! ብዙ ድምጾች!!..ቀስ በቀስ የማየው ሁሉ ብዥዥዥ እያለብኝ .መሬት ላይ ወደኩ።

ፖሊስ አባባን ፍለጋ ብዙ ደከመ። እሱ ግን ዱካውን አጥፍቶ ተሰወረ። ከዘመዶቹ ፣ ከጓደኞቹ ቤት…ብዙ ቦታ ተፈለገ! የውሃ ሽታ ሁኖ ቀረ። እኔም ከዚያች ቀን ጀምሮ ከአጎቴ ጋር መኖር ጀመርኩ። መጀመርያ ላይ አጎቴ ከራሱ ቤት ነበር የሚያኖረኝ። ትንሽ ቆይቶ ግን ከወላጆቼ ቤት እንድንኖር ይወተውተኝ ጀመር። በተደጋጋሚ አንቢታየን በለቅሶና በጩኸት ገለጥኩለት። እሱ ግን ከእኔ የስነልቦና ጉዳት ይልቅ የቤቱ ማማር ማርኮት አስገድዶ አመጣኝ።
ህይወት የጊዜ ባቡር አይደለች? ጥቂት አመታት እንደቀልድ አለፉ...
በየ ቀኑ እንቅልፍ እንደራቀኝ…ሌሊት ሌሊት እንደቃዠሁ ነበር። ብዙ ጊዜ የማስበው ደግሞ…ያ….ዘሪሁን የተባለን ሰው መበቀል ነበር። ህይወታችንን ያመሰቃቀለው እሱ ነው !

አንድ ግዜ በተኛሁበት ላብ ሰውነቴን አጥምቆኝ ከቅዠቴ ባተትኩ።
አልጋዬ ላይ እንደሆንኩ የሆነ ድምጽ ሰማሁ። መጀመርያ አይምሮዬ የፈጠረው መስሎኝ ነበር። በኋላ ግን ድምጹ…ጎልቶ መሰማት ጀመረ። አዎ ያን ድምጽ አውቀዋለሁ…የሰውየው ኮቴ ነው
«ገጭ ጓጓጓ! ገጭ ጓጓጓ!»…..ኮቴው ጆሮዬ ላይ አስተጋባ። አጎቴ እንዳንቀላፋ ነው። ደግሞ ምን ቀርቶት መጣ ? እማማ እንደሆነች ሙታለች! ….በተደበላለቀ ስሜት ውስጥ ሁኜ በሩን ከፈትኩ…
በሩን ከፍቼ ያየሁትን ማመን አልቻልኩም። አባባ ነው። እጁ ላይ ትልቅ የቢራ ጠርሙስ አለ…እግሮቹ ይወላገዳሉ…መቆም አልቻለም። እሱ ሲወላገድ ወለሉ«ገጭ ጓጓጓ! ገጭ ጓጓጓ!» የሚል ድምጽ ያሰማል
«ት…ል…ጎ…ዬ» …ስካር ባኮላተፈው ድምጽ

(A masterpiece by ናትናኤል ጌጡ💙)

@wegoch
@wegoch
@paappii

By mickel asmeraw
ገጠራማ እርሻ ቦታ ነው

ባል እና ሚስት የሆኑ ገበሬዎች አዲስ ስለገዙት እቃ እያወሩ ነው - ትልቅ የአይጥ ወጥመድ ገዝተው እያወሩ ነው

ይህንን ሲያወሩ ደግሞ አይጥ ሰምታለች

👇🏾

የወጥመዱ መገዛት ያሳሰባት አይጥ ዶሮ ጋር ሄዳ ትነግራታለች

"ታዲያ እኔ ስለ አይጥ ወጥመድ ምን አገባኝ" ብላ ፊት ነሳቻት

ከዚያም ፍየል ጋር ሄዳ ስትነግራት "የአይጥ ወጥመድ እኔን አያሰጋኝም :አትነዝንዢኝ" ብላ አባረረቻት

አይጧ ተስፋ ሳትቆርጥ ላም ጋር ሄዳ ስጋቷን ስታስረዳት "የአይጥ ወጥመድ ላምን አይይዛት: ምን ጨነቀኝ" አለቻት

አይጧ በመልሳቸው አዝና ልጆቿን እና ዘመዶቿን ሰብስባ ከጎሬዋ ገብታ ተደበቀች

👇🏾

ማታ ላይ ወጥመዱ የተጠመደበት ቦታ ላይ ከፍተኛ ጩኸት ተሰማ

የቤት እመቤቲቱ ወጥሙዱ ያዘልኝ ብላ ስትሄድ ለካንስ ወጥመዱ የአንድ መርዛማ እባብ ጭራ ይዟል: አላየችውምና በመርዙ ነደፋት

ባልየውም አካባቢው ያለ ሀኪም ቤት ወስዶ አሳክሟት ሀኪሙ የዶሮ ሾርባ አዘዘላት

ዶሮዋ ለሾርባ ታረደች

ቤተ ዘመድ ሚስትየውን ሊጠይቅ ሲመጣ ለመስተንግዶ ፍየሏ ታረደች

ሴትዮዋ አልሆነላትም: ሞተች

ባልየው ቀብር ማስፈፀሚያ አልነበረውምና ላሚቷን ለቄራ ሸጣት

👇🏾

አይመለከተኝም አትበል !!

@wegoch
@wegoch
@paappii

By Zemelak endrias
የእድሩ ስም ጠሪ
-----
ከተስፋዬ ገብረአብ
----
እለቱ ሰንበት ነው:: ደብረዘይት። የቢሾፍቱ ቀበሌ የሃዲድ በላይ እድርተኞች ለቀብር ቃጂማ ጊዮርጊስ ተሰብስበዋል። ሰንበት ስለሆነ ነው መሰል ቀብር ላይ በርከት ያለ ሸኚ ተገኝቶአል። በኦርቶዶክስ ሃይማኖት አማኞች ልማድና ደንብ መሰረት በቀብር የተገኘና ያልተገኘውን ለማጣራት የስም ጥሪ ይካሄድ ጀመር። ስም ጠሪው ባሻ መላኩ እርጅና ተጭኖአቸዋል። ቢሆንም ግን ድምፃቸው እንደ ባቡር ጡሩምባ ነው። በፀጥተኛው የመቃብር ስፍራ እየተምዘገዘገ ያለችግር ከአስከሬን ሸኚው ጆሮ ይደርሳል፣
“ወይዘሮ ፈትለወርቅ ሞላ”
“አቤት!”
“አስር አለቃ እርገጤ ሺባባው”
“አለሁ!”
“ወይዘሮ ከበቡሽ ደሜ”
“አቤት!”
“አቶ ዳኜ ተማም”
ምላሽ አልነበረም፣
“አቶ ዳኜ!?” አሉ ስም ጠሪው በድጋሚ፣
“አለሁ! አለሁ! “ የሚል ድምፅ ተሰማ፣
ይህን ጊዜ ሽማግሌው ስም ጠሪ እብድ የሚያህለውን ዶሴ አጥፈው እርሳሳቸውን ጆሮአቸው ላይ ሰክተው ከፊታቸው ለተኮለኮሉት የእድሩ አባላት ማስጠንቀቂያ ይሰጡ ጀመር፣
“ስሙኝ ቀባሪዎች! እኔ ላንቃዬ እስቲዘጋ የምጮኸው እንደ ፊልፕስ ሬድዮ ባትሪ ውጬ አይምሰላችሁ። በዚህ እድር በቀን አንድ ሰው ይሞታል። በየቀኑ እጮሀለሁ! በ75 ብር ስጮህ መዋሌ ወገኖቼን ልጠቅም ካልሆነ ገንዘቧ ምን አላት? ስለዚህ ካንድ ጊዜ በላይ አልጠራም! ቀሪ ተባልሁ ተብሎ ቅያሜ እንዲመጣብኝ አልፈልግም። ተቀጣሁ ተብሎ ወቀሳ እንዲወርድብኝ አልፈቅድም። ጆሮአችሁን ተክላችሁ ስማችሁን አዳምጡ። እኔ የቁራ ዘር የለብኝም። በየሜዳው የሚጮህ ቁራ ነው። በየባህር ዛፉ፣ በየገደሉ፣ በዋርካ ላይ ተጎልቶ ሲጮህ የሚውል ቁራ ነው፣ እኔ ግን ቁራ አይደለሁም”
ስም ጠሪው በተጨማደደች መሃረም ግንባራቸው ላይ ያቸፈቸፈውን ላብ አደራረቁና ጥሪውን ቀጠሉ፣
“ወይዘሮ የሁዋላሸት አለሙ”
“አለሁ!” አለ የወጣት ወንድ ድምፅ፣
“ደሞ አንተ ማነህ?”
‘ልጃቸው ነኝ!”
ጥሪው ቀጠለ፣
“አቶ ከበደ ማሞ”
ምላሽ የለም፣ ቀሪ።
“ፊታውራሪ የሽዋሉል ግርማቸው”
ምላሽ የለም፣ ቀሪ።
“እመት ጌጤ እሸቴ”
“ታመዋል!” የሚል ድምፅ ተሰማ።
“አቶ ተሰማ ታደለ”
ምላሽ የለም፣ ቀሪ። የእድሩ ስም ጠሪ ግምባራቸውን በመሃረም እያበሱ ቀና አሉ፣
“ስሙኝ ቀባሪዎች! ቀሪ በዝቶአል። እንዴት ነው ነገሩ? አዲስ ድንኩዋን ገዝተን የምረቃ ግብዣ የተባለ ለታ ግን እድርተኛው ግልብጥ ብሎ ነበር የመጣው። ትርፍ ሰው ሁሉ ነበር። የቀበርናቸው ሰው ወክለው ነው? ቀብር ሲባል ግን ቀሪ ይበዛል? ነግ በኔ ነው። ዛሬ ያላቃበርነው ነገ አይቀብረንም…”
ምክርና ተግሳፁን እንዳበቁ ጥሪውን ቀጠሉ፣
“አቶ ሃይለራጉኤል ተካ”
“አቤት”
“ወይዘሮ ኪሮስ ገብራይ”
“አለሁ!”
“ወይዘሮ አረጋሽ አባተ”
ምላሽ የለም፣ ቀሪ።
“አቶ ኩራባቸው ታዬ”
“አቤት!”
“መምህር ገረመው ደበላ”
“አቤት!”
“ወይዘሮ የወርቅውሃ ታደሰ!”
ምላሽ የለም። የእድሩ ስም ጠሪ በድጋሚ “ወይዘሮ የወርቅ ውሃ! ‘ሲሉ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ጠሩ። መልስ የለም። ሽማግሌው እንዲህ ሲሉ ተናገሩ።

"እኝህ ሴትዮን ምን አግኝቷቸው ነው? በጣም ደግ ሰው ናቸው። ቀብር ቀርተው አያውቁም። ወይዘሮ የወርቅውሃ!"

በዚህ ጊዜ አጠገባቸው ቆሞ የነበረ አንድ ጎልማሳ ወደ ጆሮአቸው ጠጋ ብሎ አንሾካሾከ።
“ይዝለሉት ባሻ፣ ዛሬ የቀበርነው ወይዘሮ የወርቅውሃን ነው”
-----
(ልቦለድ፣ 1989 አዲስ አበባ - ተስፋዬ ገብረአብ)

@wegoch
@wegoch
@paappii
ከ 35 እስከ 40 አመት እድሜ ክልልን ስትመታ ወይም ስትቃረብ ነገሮች ይቀየራሉ

ምን ይቀየራል?

👇🏾

ወላጆችህን: ቤተሰብህን: ወዳጆችህን: ፍቅረኛህን: ልጆችህን ወደህ ወደህ በስተመጨረሻ ራስህን መውደድ ትጀምራለህ

የአለም ችግር በአንተ ጫንቃ ላይ የወደቀ ነገር አለመሆኑን ትረዳለህ: የሚያብሰለስሉህ ነገሮች እና ምክንያቶች ይቀንሳሉ

ከምስኪኖች ጋር በጉሊት ንግድ ሂሳብ መከራከር ታቆማለህ: ተፍ ተፍ የሚል ሰው ስትመለከት ከአንተ ኪስ ይልቅ የእነርሱ ላብ እና ድካም ይበልጥብሃል

አንድ ሰው የሆነን ታሪክ ደግሞ ቢነግርህ "ነግረኸኝ ነበር እኮ" ብለህ አታሳቅቅም: መደመጥ ምን ያህል ዋጋ እንዳለው ስለምትረዳ ታሪኩን ታስጨርሳለህ - ምናልባት ሰውዬው ታሪኩን ሲያወራ ትዝታውን እያደሰ ይሆናል

ሰዎችን በየሚሰሩት ስህተት ፌርማታ እያቆምክ ማረም ይደክምሃል: የዚህችን አለም ስህተቶች የማረም ሃላፊነት የአንተ እዳ እንዳልሆነ ትረዳለህ

ከልብስ ይልቅ ማንነት እንደሚበልጥ ትረዳለህ: ከምግብ ይልቅ የውስጥ ሰላም ዋጋ እንዳለው ይገባሃል

ከአንተ በእድሜ ያነሱ ሰዎች አጉል አራዳነት ሲጫወቱ እና ያለፍክበን መንገድ ሲሄዱበት አያናድድህም: "እድሜያቸው ነው" ብለህ ታልፋለህ እንጂ አትበሳጭም

ከማያከብሩህ ሰዎች እና የማትፈለግበት ቦታ አትውልም: ራስህን አክብረህ ገለል ትላለህ እንጂ

የሚተናነቅህ ግብዝነት አይኖርም: በመተው ታምናለህ - ሰዎችን ከማሳደድ ይልቅ ለህሊናቸው አሳልፈህ መስጠት ትመርጣለህ

@wegoch
@wegoch
@paappii

By Zemelak endrias
" ትወደን የለ አበርታን "

( መውደዱን ለመግለፅ ማኖሩ አይበቃም ? )

ካሊድ አቅሉ

~   ~   ~   ~   ~    ~   ~    ~    ~    ~

ትወደኝ የለ አበርታኝ ትለዋለች አንድዬን እንደሚወዳት እንዴት በእዚህ ልክ ተማመነች ? መማፀንዋ አጊንታው መውደድዋን የገለፀችለት ይመስላል ምንዋ ተነክቶ ነው በእዚህ ልክ ፈጣሪን የተማፀነችው ?  ልጠይቃት አስቤ በማያገባኝ መግባት መስሎ ተሰማኝና እራሴን ቆጠብኩ ። ለሶስት ሰዓት ሙሉ ሊክቸሩ ሲያስተምር እሷ አርሚቸር ወንበርዋ ላይ " ትወደኝ የለ አበርታኝ " ብላ ፅፋ እሱኑ ታደምቃለች ፊትዋ ጥቁር ብልዋል ከፍቅረኛዋ ጋር ተጣልታ ይሆን ?

" ይቅርታ የኔ ውድ ካስከፍሁ እንታረቅ " ብላ  ባለንጋ ጣቶችዋ ፀጉሩን ስትዳብስ በምናቤ ታየኝ ። ፍቅር አለብኝ መሰለኝ የእሷዋን መከፋት ከወንድ ጋር ብቻ አያያዝኩት ። እሷ ቃሉን በማድመቅ ላይ ናት ። አይንዋ ያሳሳል ሆድ ያስብሳል አላያትም ብለው ቢገዘቱ የሚረታ ውበት አላት ። በሀሳቤ ፈረስ ስጋልብ የተማሪዎች ጫጫታ  አነቃኝ አይኔን  ቀና ሳደርግ ከሰሌዳው ላይ (Quiz) የምትል ፅሁፍ አስተማሪው አሳርፈው አየው ። ከሴት ፈተና ወደ ቀለም ፈተና ይሄን እስተማሪና ህይወትን ሚያመሳስላቸው ነገር ሳይናገሩ መፈተናቸው ነው ። እኔም ወረቀት አወጣውና እንዲ ብዬ ቃል አሳረፍኩ ( ትወደን የለ አበርታን )
" በእዚህ ልክ እንደሚወዳቹ በምን ተማመናቹ ?" ለምትሉን ጭንቁ ሲጠናብን አንድ መልስ አዘል ጥያቄ እናቀርባለን . . .
(መውደዱን ለመግለፅ ማኖሩ አይበቃም ?)
~  ~  ~  ~  ~   ~    ~   ~   ~ ~ ~  ~

@wegoch
@wegoch
@paappii
"  ብሌኔ ትለኝ የል?"
"አዎ"
"ያላንቺ በድን ነኝም ብለኸኛል"
"ነኝኮ"
"ታዲያ ትተኸኝ አትኺዳ? በሌን ብቻዋን ምን እርባን ይኖራታል"
"እማዬ ሆዴ! አዎን ማያዬ ነሽ።የእናቴ  ቤት እየተቃጠለ ዓይኗን እየጠነቆሉባት ዓይኖችሽን እያየሁ በፍስሃ ልኑር? አተላ ነገር ነው የሚሆነው።"
" አንተ ብቻህን ምን ትፈይድላታለህ?"
"ለዛ አይደል መኼዴ?   እንደኔ አይነት ብዙ ወዳሉበት"

   "የኔ ጌታ እሺ በለኝና አትሂድ....ምንም አልዋጥልሽ እያለኝ ነው"
"እእእ አሁንስ?" አላት ከአገጯ ቀና አድርጎ ከንፈሯን ከሳማት ኋላ።

ምንም ቃል ሳይወጣት ለደቂቃ አሻቅባ እያየችው ቆየችና ድንገት በሁለቱም ዓይኖቿ እንባዋን ታረግፍ ጀመር

"እናት እንዲሁ ከብዶኛል እንባሽ ተጨምሮ አልችለውም " አለና ለራሱ ደረቱ ላይ አጥብቆ አቀፋት።

"አንቺን ሲነኩሽ ማሰብ አልችልም ።ያቺ ሰባት ወንዶች የደፈሩዋት .... ተይው ግን እሳቱ የተቀጣጠለበት ኼደን ካላጠፋነው እሱ  መቶ ያቃጥለናል ።"

"እግዜሩ ካልቀጣቸው ሰው በምን አቅሙ ያኚን ጋኔን ይመክታል?  አላማረኝም ተው......"
"አልተውም 😂"ግንባሩዋን ጉንጮችዋን አገጭዋን አይኖችዋን ከንፈሩዋን ተራ በተራ ስሞ ሲያበቃ "
"አንቺን የመሳሰሉ ጥኒኒጥ ልጆቼ አኚህ የሳጥናኤል ተኩላዎች ባሉበት ተወልደው እንዲያድጉ አልፈልግም" አላት በዓይኖቹ ዓይኖቿን አተኩሮ እያየ።

ምንም ብል ድካም ነው ብላ አሰበችና ዝምታን መረጠች።  ዓይኖቻቸው እንደተገለጡ እኩለሌሊት ካለፈ ወዲያ እንግላል በተኛበት  ክንዱዋን ደረቱ ላይ አስሞርክዛ ቀና አለችና ቁልቁል ስትመለከተው

"ባንቺ አየን ያንድዬን ስራ
ያለእቅድ እንደሚሰራ
ፈጣሪ ተራቆብሻል
ጥበቡን ማሳያ አርጎሻል"እያለ ማንጎራጎር ጀመረ።
"ስሜትህን ለመደበቅ አትጣር ,የእውነት ምን እየተሰማህ ነው?"
                 "እስከዛሬ ሽቅብ አይቼሽ አላውቀውም ወይ ቁልቁል አይተሺኝ አታውቂም? መኮሮኒ አፍንጫ አይደለሽ እንዴ""
"ጌታ የምሬን ነው" አለች ቆጣ ብላ።
"ጌታን እውነታው ጎራዳ ነሽ"
"ታውቃለህ ግን.......ኡፋ እንደውም ተወው በቃ"አለችና ደረቱ ላይ ተኝታ እጇን ፀጉሩ ስር ሰዳ ማሻሸት ጀመረች።
" ዎ አትነካኪኝ,  ለሊት መንገደኛ ነኝ ይደክመኛል"
"ስድ ! ሂድ ወደዛ"
"ነይ ወደዚ😂😂" ከትከት እያለ ሳቀ።ከደረቱ ላይ ተነስታ ጀርባዋን ሰታው ተኛች።እየሳቀ ዞረና ፊቱን አንገቱዋ ስር ሸጉጦ እጁን በወገቡዋ አዙር ሆዷ ላይ አደረገና እቅፍ አደረጋት።

ዓይኗን ስትገልጥ ወገግ ብሏል ።ዞር ስትል ብቻዋን ነች።የሌሊት ልብሷን እንደለበሰች ወርዳ ሩጫ ጀመረች።ቦታውጋ ስትደርስ ማንም አልነበረም።ጠጋ አለችና የመስሪያ ቤቱን ጥበቃ
"ምልምሎች የሚሳፈሩት ከዚህ አልነበር እንዴ? አባቴ"
" አዎን ከዚሁ ነው በለሊት ወጡ እኮ"

እጢዋ ዱብ አለ።
" አላለቅስም!! ሰው መንገድ ሲኼድ አይለቀስም ሰላም ተመለስ ነው ሚባለው"ብቻዋን እንደእብድ እያወራች ወደ  ቤቷ ገባች።ከዚያች እለት በኋላ ያወቁዋት ሰዎች
"ፍንጭታም ነች ወይንም ጭርሱንም ጥርስ የላትም ይሆናል" እያሉ ያሟታል።ቀበሌ የሚሰራ ሰው ቤቷ አቅራቢያ ስታይ ጉልበቷ ይከዳታል በእጃቸው ወረቀት ይዘው ከሆነ ደግሞ ሰው "አበደች?"
እስኪላት አሪ እያለች ታለቅሳለች።ቤቷ ሚመጣ ሁሉም ሰው ሊያረዳት የመጣ ይመስላታል ።

   የፈሩት ይደርሳል ሚሉት እውነት ይመስላል።ጎህ ሳይቀድ ተሰብስበው በሯን አንኳኩ ።ከፍታ እንዳየቻቸው እንባዋ ረገፈ። ደብዳቤው ምን ይላል አላለችም ።ሃገሬው ለሁለት ተከፍሎ ገሚሱ በሷ የደረሰ በማንም አይድረስ ሲል ሌላው አሟርታ ገደለችው አላት።

ይህ ከሆነ ከወራት በኋላ ሰፈሩ ዳግም በለቅሶ ድብልቅልቅ አለ።

     መጣ!!!
ሞቷል የተባለ ሰው በህይወት ሲመለስ እንዲህ ያስለቅሳል ማለት ነው በማለት እየተገረመ መልሶ መልሶ
"የታለች?" ሲላቸው ።
"ሞትህን መቋቋም ከብዷት እራሷን አጠፋች" ብለው መለሱለት።ተሰብስቦ የሚያለቅሰውን ሰው እየከፈለ ወቶ ኼደ።አልተመለሰም።

ሰብሰብ ብለው ከቤተክርስቲያን እየተመለሱ እመንገድ ዳር ላይ የተቀመጠውን እብድ እየተመለከቱ
"አዪዪ ያን የመሰለ ልጅ እምጽ ...እንዲ ከምያንገላታው በገደለው" ያሻቸውን እንዳሻቸው ፈረዱበት።ስንቱ ይሆን ለነሱ ጋሻ ልሁን ብሎ በተመሰቃቀለ "በገደለውን" ያተረፈ አመድ አፋሽ ።
    
ጫሪ Enat Kassahun @ethioma1

@wegoch
@wegoch
@wegoch
ከፋኝ ብዬ ነበር ብቻዬን የሆንኩት ። የምፈልገው ነገር አልሆነም ብዬ ነበር የተሸሸግኩት ።

ጠይም ናት ሳቂታ ። ደሞ ስትስቅ ታምራለች ስታወራኝ ረጋ ብላ ነው ። ተገናኝተን ሳንስቅ ሳንሿሿፍ ቀርተን አናውቅም ። ከሆነ ግዜ በፊት የሆነ ወቅት ባገኛት ብዬ አስቤ አውቃለሁ ።

ለምን ለኛ የሚሆኑ ሰዎች ወይ ፈጥነው ወይ ዘግይተው ይመጣሉ ? በሰዓቱ ለምን አይመጡም ??

አለመገጣጠም ከመተላለፍ ይሻላል !!።

ናይል ድብርት የሚያጠቃት ናት ። ናይል ድብርቷ እየተባባሰባት ነበር። "አግዘኝ መደበር ተስፋ ቢስ መሆን ደክምኛል" አለች።

"እሺ" ብዬ አቀፍኳት ። እንድለቃት አልፈለገችም ነበር። ስለድብርቷ ገምቼ አውቄባት እንጂ በቃሏ ምንም ብላኝ አታውቅም ነበር ። ከእቅፌ ሳስወጣት አይኗ እምባ ነበረበት ።

ከሶስት ቀን በኋላ ሁሉ ነገር ሲሰለቸኝ ። ስልኬን ዘጋሁት ብቻዬን ሆንኩኝ በተቻለኝ መጠን አልጋዬን ላለመልቀቅ ሞከርኩ ።

ከአስራ ሶስት ቀን በኃላ ስልኬን አበራሁኝ ። ናይል ቴክስት ልካልኝ ነበር "ፈልጌሃለሁ" የሚል ወድያው ናይል ጋር ደወልኩ ስልኳ ዝግ ነበር ደጋገምኩት ያው ነው ። በአስራ አራተኛው ቀን እቤቷ ሄድኩ : ናይል አልነበረችም ።

ሰፈሯ ስሄድ የሚጠራልኝ ልጅ ፣ባለሱቁ ፣አከራይዋ ሁሉም ራሳዋን አጥፍታለች አሉኝ ።

ስላላመንኳቸው ሁሉንም ደጋግሜ ነው የጠየኳቸው ሁሉም ፊታቸው እውነታቸውን እንደሆነ ያስታውቃሉ ።

እንዴት እንደከፋኝ ....

መኖር እፈልጋለሁ አግዘኝ እያለችኝ ። እራስ ወዳድነት ነው መሰለኝ እንዳልሰማት ከለከለኝ ።

ሞቷ ውስጥ እጄ አለበት ። ለመሞት ስትመቻች ሸኝቻት ነበር ።
ስቅስቅ አልኩ ። ድብርት ሀዘን ከፀፀት ጋር ከባለፈው በላይ አዝረከረከኝ ። ስልኬን መዝጋት ፈልጌ ነበር እንደ ባለፈው መደበቅ ፈልጌ ነበር ።

ፈራሁ የሆነ ሰው ሲጠራኝ ባልሰማውስ ?፣ ቢያመልጠኝስ ?

ለራስ ብቻ መኖር ለካ አይቻልም!!


By Adhanom Mitiku

@wegoch
@wegoch
@paappii
አባቴ ሁሉ ነገርን መጋፈጥ ይሰብራል ይላል ። ጀግና ሁኔታን የሚረዳ ነውም ይላል ።

እኔ የምጋፈጠው ለማሸነፍ ጀግናም ለመሆን አይደለም ሲደርሱብኝ ነበር ።

አፈግፍጌ አውቃለሁ ። ያፈገፈኩኝ ግዜ የሚሰማኝ ስሜት መጥፎ ነው ።

አባቴ "የማያፈገፍግ ታጋይ በቶሎ ይሞታል" እያለ የውትድርና ገጠመኙን ያጣቅስልኛል ።

በሂወቱ ምድር ላይ እንደኔ የሚጨነቅበት ጉዳይ ያለ አይመስለኝም

"እሱ ማስረዳት አይችልም በዛ ላይ ያፈጣል ....ችግር የሚፈታው አንገት ለአንገት በመተናነቅ ይመስለዋል" ይላል ።

"አንዱ ይገለዋል አጉል ቦታ ይመቱታል የሰው ሰው እጁ ላይ ይጠፋል" ይላል

"እኔ በሂወት የኖርኩት እጅ ሰጥቼ ነው ። ይሄው ከዛ በኃላ ያገኘሁት መዓረግ እና ደስታ ይቆጠራል ?? "

አባቴ ትኩረቱ ስለሆንኩ መሰለኝ
ልጁ ስለሆንኩ መሰለኝ
ስላሳደገኝ መሰለኝ
ስለሚያስብልኝ መሰለኝ

ከኔ በተሻለ እኔን ያውቀኛል ። ስለኔ ገምቶ የተሳሳተበት ግዜ አላስታውስም

"በጠበል አልወጣ ያለ ጂኒ አለበት" ይላል ።

የሆነ ቀን ተሳካልኝ ልጄ ልብ ገዛልኝ ስለቴ ሰመረልኝ ብሎ በመሃበርተኛው ፊት ተናዞ ስለቱን እንዳስገባ የመሃበርተኛው ልጅ አዲሱ ነገረኝ

ስለት ካስገባበት ቀን ጀምሮ ሳሰላስል ልብ ገዛ እንዳለው አይነት ሰው ሆኛለሁ ።
ደርሰውብኝ ያለፍኳቸው ቀምተውኝ የተውኳቸው ትተውኝ ያለቀስኩበት ስፍራ ብዙ ነው ።

ምን ብሎ ተስሎ ይሆን ስለቱ የሰመረው??

ምን አለ አሁን ትልቅ ህልም እና ህልሙን መተግበርያ ጥንካሬ ስጠው ብሎ ቢሳልልኝ

By Adhanom Mitiku

@wegoch
@wegoch
@paappii
በሰርጓ ቀን ያማረባት ብቸኛዋ ሴት ናት ለኔ ­-የአጎቴ ልጅ ሜሪ።

እንደሌሎቹ የሜካፕ ናዳ ፊቷ ላይ አዝንባ፤ አዲስ መልክ ይዛ አልመጣችም፤ ያው...እግዜር አንዴ ተጠብቦ ተጨንቆ ሰርቷት የለ? ከዚ ወዲያ የሜካፕ ባለሞያዎች ከማበላሸት በቀር ምን ይጨምራሉ?- ምንም።

ንጥት ያለው ቬሎዋ መሬት ላይ፤ የተፈጥሮ ፀጉሯ ደሞ ጀርባዋ ላይ ተንፏሏል፤ ውብ ገጿ ላይም አንዳች ሚያክል ደስታ ድሩን ሰርቷል።
ሁሌም ደስተኛ ነች የምትባል ሴት ብትሆንም፤ የዛሬው ግን የተለየ ነው፤ የደበዘዘ ሮዝ ቀለም የተቀባውን ከንፈሯን ከፈት እያደረገች፤ሀፍረት የቀላቀለ ፈገግታ ትጋብዘናለች።

ፀጉሯ ላይ የሚያንፀባርቅ ነገር ይታያል፤ አክሊል ካናቴራ ነው፤ ሄዶባታል አጥገልፀውም ምክንያቱም... የምር ንግስት የሚያስመስል ግርማ ሞገስ አላት።

በቀኝ እጅዋ እንደሷ የፈኩ ነጫጭ አበቦችን፤በግራ እጅዋ ደሞ የመጪው ባሏን ክንድ ቆልፋ ይዛለች፤ በኤሊ እርምጃ ወደ አዳራሹ በማዝገም ላይ ናቸው፤ ብዙዎች ከሁዋላ ሀይሎጋ እየጨፈሩ ያጅቧቸዋል።

እኔ እና አጎቴ(የሙሽራዋ  አባት) አዳራሹ መግቢያ ላይ ተሰይመናል፤ በትንሹ እያጨበጨብን፤ በፍቅር አይን ሙሽሮቹን እናያቸዋለን።

ሁለታችንም ተመሳሳይ ሱፍ ነው የለበስነው፤ እንደወጣትነቴም፤ እንደ ቁመና ባለቤትነቴም፤ እኔ ላይ ይበልጥ ሳያምርብኝ አይቀርም።
በቃ ተውኩት፤ 'ስለ ራስ አይወራም!' ያለኝ ማን ነበር?...ብቻ ማንም ይሁን ማን ልክ ሳይሆን አይቀርም።

በአሁኑ ሰአት ግን ሙሽሮቹን ማጀብ ሲገባኝ፤ እዚ ፈዝዤ የቆምኩበት ምክንያት አልገባኝም፤ በርግጥ ሜሪ ቀድማኝ በማግባቷ ትንሽ ደብሮኝ ነበር፤
«አትቀድመኝም!»
«አትቀድሚኝም!» የሚል የፌዝ ውርርድ ስለነበረን፤ በመሸነፌ ትንሽ ቅር ብሎኛል። ግን የሷ ደስታ ደስታዬ አይደለም እንዴ?...ይሄን ያክል ፋራ ሆኛለሁ?...ሳምንቱን ሙሉ ጠብ እርገፍ ስል የነበር፤ ዛሬ እንዲ ለመሆን ነው?
ራሴን ተቆጣሁት፤ደሞስ የሷ ሰርግ ያልጨፈርኩ የማን ልጨፍር ነው?

ከሰመመኑ እንደ ነቃ ሰው ደንገጥ አልኩና ፤ወደ አጃቢዋች ሄጄ ተቀላቀልኩኣቸው። ሜሪ አስተውላኝ ነበር፤ ዲምፕሎቿን አስከትላ  ፈገግ አለችልኝ። ደስ ስላላት፤ ደስ አለኝ። ድምፄን አጠብድዬ እኔ እመራቸው ጀመር፤ የጭፈራውውን ዙር አከረርኩት...።

* * *

ልጅ እያለሁ ነው ፤ ወደ አስራዎቹ መግቢያ ላይ። ከእናቴጋ ለመጀመሪያ ጊዜ መነሀሪያ ሄድኩ፤ ተገድጄ ነው እንጂ፤ የመምጣቱ ፍላጎት አልነበረኝም። ቆይቶ ግን አብዛኛውን የማየው ነገር አዲስ ስለሆነብኝ፤በሆድ ማማረሬን አቆምኩ።

ገና ከመግባታችን አንድ ሱቅ በደረቴ አዟሪ ልጅ መጥቶ እናቴን ይለማመጣት ጀመር፤
«እናት ሶፍት ይፈልጋሉ?..ማስቲካም አለ ጦር..ባናና..» ምንም እንደማትፈልግ ከይቅርታ ጋር ነግራው፤ መቀመጫ ወዳለበት ሄደን ተቀመጥን። ሲመስለኝ የምንቀበለው ሰውዬ ገና አልደረሰም።

ከጥቂት ደቂቃዎች በሁዋላ፤ እናቴ ሁለት ባሶች ተከታትለው መግባታቸውን አስተውላ፤ ባለሁበት እንድጠብቃት አስጠንቅቃኝ ሄደች።

የግቢው(የመነሃሪያው) ስፋትና የመኪኖቹ ብዛት አስገርሞኝ፤ አይኔን ወዲያና ወዲ እያቅበዘበዝኩ ትንሽ እንደቆየሁ፤ ውሃ ሰማያዊ ቀሚስ ያደረገች ሴት ወደ እኔ አቅጣጫ ስትመጣ ተመለከትኩ። ይሄኔ ነው እንግዲህ ጉዴ የሚጀምር።

እድሜዋ ከኔ ጋ ተመጣጣኝ ይሆናል፤ አልያ ደሞ በትንሽ ትበልጠኛለች። ከሩቅ እንዳየኋት ቆንጆ መስላኝ ነበር፤ እየቀረበች ስትመጣ ግን እጅግ በጣም ቆንጆ ሆነችብኝ። ከላይ እስከ ታች ባይኔ አላመጥኩኣት፤ ስጋ እንዳየ ውሻ ምላሴን አውጥቼ ለሀጬን ማዝረክረክ ነው የቀረኝ።

አፌን እንደከፈትኩ እርምጃዋን ስቆጥር ከአይኗጋ ገጠምኩኝ፤ በጣም ማፍጠጤ ታወቀኝና አይኔን ሰበርኩ፤ ዝቅ አልኩ።

ወዲያው የየሆነ ሰው ጥላ እየቀረበኝ መጥቶ ካጠገቤ ሲቀመጥ ተሰማኝ። እሷ መሆኗን ላረጋግጥ ቀና ስል፤ በድጋሚ ካይኖቿጋ ተጋጨሁ፤ እዛው ስብር። ሆ! በምን ሃቅሜ፤ ልቋቋማቸው?

ልቤ በፍጥነት እየመታ ነው፤ ሰውነቴም በላብ ተጠምቋል፤ ወደሷ መዞር አቃተኝ፤ የተሸከምኩኣት ያክል ከብዳኛለች።
በእርግጥ በጣም የተቀራረብን መስሎ ተሰማኝ እንጂ በመሀከላችን ያለው ርቀት አምስት ሰው ያስቀምጥ ነበር።

ከትንሽ መንቀጥቀጦች በኋላ አላስችለኝ ሲል፤ እንደምንም ሰረቅ አድርጌ አየሁአት፤ 'ተመስገን'! አልኩ ከአይኖቿ ጋ ስላልተጋጨሁ መሆኑ ነው ሂሂሂ!!።

እንደዚህ አይቼ የደነገጥኩላቸው ሴቶች ጥቂት ነበሩ፤ ግን አንዳቸውንም አውርቼአቸው አላውቅም። ይህቺን ልዕልት መሳይ ግን ዝም ብሎ ያልፋት ዘንድ ልቤ አልቻለም፤ ውስጤ 'አናግራት!..አናግራት!' በሚል የድምፅ ማእበል ተናወጠ።

እሷን የማናገር ፍላጎቴ ናረብኝ፤ ከዚህ የፍርሀት አዘቅት ወጥቼ እንዴት እንደማወራት ግራ ቢገባኝም፤ ውሳኔ ላይ ደረስኩ።

ቀረብ ብዬ ልተዋወቃት፤ የተሰማኝን ሙሉውን ባልነግራትም፤ የመጣልኝን ብዬ ከበኋላ የህሊና ፀፀቴ ለመዳን ወሰንኩ። ራሴን በራሴ motivate ማድረግ ጀመርኩ፤ እንደሚችል ነገርኩት፤ ተቀበለኝ (ማለቴ ተቀበልኩት)።

መመለሷን ስጠብቅ የነበረውን እናቴን ከነ እንግዳው በዛው እንዲቀሩ እየተመኘሁ ፤እግሬን አዘጋጀሁ፤ ጉሮሮዬን ጠረኩ፤ ልብሴን አስተካከልኩ በስተመጨረሻ ብድግ ስል፤ እናቴ ሻንጣ እየጎተተች ካንድ ሰውዬጋ ወደ እኔ ስትመጣ አየኋት።

በእውነቱ ያን ጊዜ የተሰማኝን የመንፈስ ስብራት ልገልፅላችሁ አልችልም። ክው ነው ያልኩት፤ እዛው በቆምኩበት ክርር፤ ድርቅ፤ ዝም፤ ምንም። እንባዬን እየታገልኩ መለስኩት፤ ዋጥ!።

ደረሱ። እናቴ አጎትህ ነው ብላኝ ከሰውየውጋ አስተቃቀፈችኝ።
ሰላም ብዬው አብቅቼ ዞር ስል፤
« አልተዋወቃችሁም እንዴ? » እናቴ ነበረች።

« ከማንጋ? » መቼም አጎትየውን እንደማይሆን አውቄ ጠየኳት።

« ከ ሷ'ጋ ነዋ! » ጎኔ ተቀምጣ ስታስጨልለኝ ወደነበረችው እንስት በግንጭሏ እየጠቆመች። ይሄኔ ነበር ከቅድሙ በበለጠ በላብ የተዘፈቅሁት። ጉልበቴ ይርበተበት፤ ሰውነቴ ይንቀጠቀጥ ጀመር፤
እንዴት የልቤን አወቀችብኝ?

ግራ ግብት አለኝ። የምለው ባጣ፤ አናቴን በአሉታ ግራ ቀኝ ወዘወዝኩላት «በፍፁም!» እንደማለት። ወዲያው ልጅቱን እጅዋን ይዛ አስነሳቻትና..
« እስከዛ ተዋወቂው ብለን ነበርኮ ወዳንተ የላክናት... ለማንኛውም ያጎትህ የሙሌ ልጁ ነች...በሉ ሰላም ተባባሉ »

ፈዘዝኩ፤ ህልም ህልም መሰለኝ፤ ስሜቴ ድብልቅልቅ አለ፤ ልደሰት ወይስ ልዘን?

እጇን ዘረጋችልኝ፤ ከበድን አካሌ በድን እጄን ልኬ ጨበጥኩዋት፤ እጇ ይለሰልሳል፤
« ሜሪ እባላለሁ! » ፈገግ ብላ ስሟን አከለችልኝ፤ ፈገግ ስትል ጉንጮቿ ሰርጎድ አሉ። ደስ የምትል ልጅ ደስ የሚል ስም አላት።
እኔ ግን ስሜን የምናገርበት አቅም አጣሁ፤ ምላሴ ተሳስሯል፤ አንደበቴ ተዘግቷል፤ ዝም አልኩኝ ፤ ዝም።

ምናልባት ብዬ ከህልሜ እስኪያባንነኝ፤ ሳምንታትን ጠበቅሁ...ልነቃ ግን አልቻልኩም...እውን ነበር።



By BINIAM EJIGU

@wegoch
@wegoch
@wegoch
በእድሜ የገፉ አዛውንት ባልና ሚስት በወጣትነት ዘመናቸው ያሳለፉትን የፍቅር ግዜያት ለማስታወስ ይፈልጉና ባልየው
" ነስሩ ሱቅ አጠገብ ያለው ጎረምሶቹ የሚቀመጡበት ድንጋይ ላይ ቁጭ ብዬ እጠብቅሻለሁ ... አንቺም ተሽሞንሙነሽ በአጠገቤ ስታልፊ ለክፌ አስቆምሽና እጅሽን ይዤ እያሽኮረመምኩ አዋራሻለሁ " ይላታል ሚስትም በደስታ ተውጣ ትስማማለች ።
.
ባል ድድ ማስጫው ላይ ለሁለት ሰዓታት ተቀምጦ ቢጠብቅም ሚስት የውሃ ሽታ ትሆናለች ። ይሄኔ " ምን አጋጥሟት ይሆን ?" በማለት ወደ ቤቱ ያዘግማል....
ቤቱ ሲደርስም ያልጠበቀውን ነገር ተመለከተ ሚስት አቀርቅራ ትንሰቀሰቃለች፣
ጠጋ ብሎ ምን እንደሆነች ሲጠይቃት
" እናቴ ከቤት መውጣት ከለከለችኝ "😂

@wegoch
@wegoch
@paappii

By lulit Tadesse
በነገራቹ ላይ መልክ ብቻ ሳይሆን ድምፅም ስታድጉ ይለወጣል:: እኔና ወንድሜ ድምፃችን አንድ አይነት ነበር::

ክፍለሃገር ለዘመድ ጥየቃ የሄደው አባቴ : በጠዋት በቤት ስልክ ደውሎ አነሳሁ:: (እስካሁን በህይወቴ ከነበሩ ትዛዞች ዝንፍ ሳልል ያከበርኩት ስልክ ሚነሳው 3ጊዜ ሲጠራ ነው ሚለውን ብቻ ይመስለኛል)😂😂😂

ከዛ አባቴ ሄሎ ስል የወንድሜ ስም ጠራ:: ልክ ወንድሜን እንደሚያዋራ: ደህና ነህ ምናምን አለኝና.... እናቴ እንደሌለች ጠይቆኝ ስነግረው.....የአንድ ዘመዳችንን ስም ጠርቶ አባቱ እንደሞቱ እና እሱ ቅዳሜ ስለሚመለስ እሁድ መርዶ ስለሚነገረው እንድትዘጋጅ እንድነግራትና ለማንም እንዳልናገር አስጠንቅቆ ነገረኝ::

ስልኩን እንደዘጋው እኛ ሰፈር አካባቢ ካለ ጋራዥ የሚሰራው አባቱ የሞቱበት ልጅ ጋ ሄድኩና... አባቱ እንደሞቱ እና እሁድ ሊነግሩት እንደሆነ ነገርኩት:: ልጁ ተንፈራፈረ :አለቀሰ ምናምን:: እናቴ የግድያ ሙከራ ስታደርግብኝ.... አያቶች ከለላ ሰጥተውኝ እዛ ተወሰድኩ::

እሁድ ለታ...አባባ ሲመጣ ወንድሜን ካልገደልኩ አለ.... ወንድሜ ምንም እንዳላደረገ : በስልክ እንዳላወሩ እየደጋገመ እየማለ ይናገራል::

አባቴ ወንድሜን እየተማታ "ጭራሽ ውሸትም ጀምረህልኛል?.... የሷን እና ያንተን ድምፅ መለየት ያቅተኛል? አንተም አድገህ ልትሸውደኝ? ....."
"ሂጂ ንገሪ ብለሃት እንጂ....." አባቴ ጥፍጥፍ አደረገው::

አባቴ በሌለበት ምግቤን ይቀማኝና: ይመታኝ ስለነበር ደስስስ አለኝ::

By ma hi

@wegoch
@wegoch
@paappii
Radric Davis ( ጉቺ ሜን ) አሜሪካዊ ራፐር ነው ። ከጎኑ ያለችው ደሞ Keyshia Ka'Oir ትባላለች ፡ ሞዴሊስት ፡ ጎበዝ አክትረስና ፡ ኢንተርፕረነር ነች ።

እና ፡ ከአመታት በፊት ፍቅረኛዋ ጉቺ ሜን ፡ በአንድ ወንጀል ተከሶ ፍርድ ቤት ቀረበና ፡ የሶስት አመት እስር ተፈረደበት ።
.....
ጉቺ ሜን ፡ ይህን የዳኞቹን ውሳኔ እንደሰማም ፡ ፍቅረኛውን ኬይሽያን ፡ ወደ እስር ቤት እንድትመጣ ላከባት ።
....
እየውልሽ ፡ በእስር ቤት ቆይታ ምን እንደሚፈጠር አላውቅም ። ስለዚህ በስሜ ያለውን ሁለት ሚሊየን ዶላር ፡ ወደ አንቺ ባንክ እንዲዛወር እፈልጋለሁ አላት ።
...
እና በባንክ ያለውን ብር በሙሉ ለፍቅረኛው ኬይሽያ ሰጣት ።
ጓደኞቹ ቀለዱበት ። ታስረህ ስትፈታ ጎዳና ልትወድቅ ነው ? ይህን ሁሉ አመት ትጠብቀኛለች ብለህ አታስብ አሉት ።
.....
Keyshia Ka'Oir ፍቅረኛዋ የሰጣትን ገንዘብ ከባንክ ያወጣችው ብዙም ሳይቆይ ነበር ። እናም በገንዘቡ የራሷን Ka'Oir የሚባል የኮስሞቲክስ ማምረቻ ከፍታ መንቀሳቀስ ጀመረች ።
....
ጊዜው ሳይታወቅ ሄዶ ፡ ፍርደኛው ራፐር ጉቺ ሜን የእስር ጊዜውን ጨርሶ ወጣ ። ጓደኛው ኬይሺያ ፡ በስራ ምክንያት ቢዚ ብትሆንም ፡ አልፎ አልፎ እየመጣች ትጠይቀው ነበር ። እና እንደተፈታ በዘመናዊ መኪና መጥታ ፡ ወደ አዲስ ቤት ይዛው ሄደች ። ከዚህ ሁሉ አመት መለያየት በኋላ ትጠብቀኛለች ብሎ ባያስብም ፡ እሷ ግን ከአመታት በኋላም ሳትቀየር ነበር ያገኛት ።

እና ቤት ደርሰው አረፍ ካሉ በኋላ ፡
" ጉቺ እስር ቤት ስትገባ ፡ በወቅቱ ሚስትህ ሳልሆን ፡ ትክደኛለች ሳትል ፡ ሁለት ሚሊየን ዶላር ሰጠኸኝ ነበር አይደል የገባኸው ? " አለችው ።
አዎ አላት ።
ይኸው ስድስት ሚሊየን ዶላር ሆኖ ጠብቆሀል አለችና ፡ የባንክ ቡኳን እንዲያየው ሰጠችው ።
.....
ዛሬ ላይ ፡ ጉቺ ሜን ፡ ከዛች ፍቅሩን ብቻ ሳይሆን የሰጣትንም ገንዘብ በእጥፍ አሳድጋ ከጠበቀችው Keyshia Ka'Oir ፡ ጋር ተጋብተው ፡ ትዳራቸው በልጅ ደምቆ , አብረው ይኖራሉ ።
.....
መታመን !

@wegoch
@wegoch
@paappii

By Wasihun Tesfaye
አንድ - ፩

ሶስት ግዜ  ነው በጣም የፈራሁት ።

ጎበዝ ተማሪ ነበርኩ ።አምቦ  university economics   ነበር የምማረው አያይ  አሞታል ና አለቺኝ ታላቅ እህቴ ። አያይ ልጆቹ ያወጣንለት የአባቴ ስም ነው ።

ቅዳሜ ነበር አራት ሰአት አካባቢ  ቁምጣ እና ቲሸርት አድርጌ ደራራ ሆቴል ጋ ነበርኩ የህቴ ድምፅ ጥሩ ስላልነበር አብራኝ ከነበረችው ቤዛ ሁለት መቶ ብር ተቀብዬ ግቢ ሳልገባ በዛው ቤት ሄድኩ

አባቴ ሞቶ ነበር ። ከመሰላል ላይ ወድቆ ግማሽ ቀን ታሞ ነው የሞተው አሉ ።ስምህን ሲጠራ ነበር አሉ ። ይበርታልኝ አለ አሉ ። ምንም ሳላደርግለት አለ አሉ ።እሱ የኔ ነገር አይሆንለትም አለ አሉ .... ብዙ ነገር አለ አሉ

ሞት አፋፍ ላይ ሆኖ እንኳን ይፈልገኛል ። ሞት አፋፍ ላይ ሆኖ ያላረገልኝ ነገር ነው የሚቆጨው፣ ሞት አፋፍ ላይ ሆኖ እንዳልሰንፍ ያሳስበዋል ፣ ሞት አፋፍ ላይ ሆኖ እንደምወደው ያውቃል ፣ ሞት አፋፍ ላይ ሆኖ ይጠራኛል ።

እውነት እንዳይሆን ፈለኩ ከቅዠት እንድነቃ ከዚ ቀደም ሲናፍቀኝ ሞቶ አይቼ ስባንን ውሸት ሆኖ ሲለሚያቅ እንደዛ ፈለኩ አልሆነልኝም ።

አንገቴን እንደደፋው እንዳላዛር ከሞት አስነሳልኝ አልኩት እግዜርን። እግዚአብሔርም ምላሽ አልሰጠኝም ።

ከሶስት ቀን በኃላ የአባቴ ገላ የሚመስለኝን ኮት ለብሼ ካምፓስ ተመለስኩ ። 

ማታ ማታ ሁሌ እፈራ ነበር ። አባቴን ሳስበው ልቤ በሃይል ይመታል ። ኮቱን ሳልቀይርለት ጠጅ ሳልጋብዘው የተሸከመኝን ኢምንት  ሳልሸከመው አይነት ድብርት  ።  አለመኖሩን የማመን ፍርሃት ተጫወተብኝ ።
   
By Adhanom Mitiku

@wegoch
@wegoch
@paappii
ወደ ስራ ስሄድ አንድ የስልክ እንጨት ላይ የተለጠፈ ወረቀት አየሁኝ: ጽሁፉ እንዲህ ይላል

“እዚህ መንገድ ላይ 50 ብር ጠፍቶብኛል: ያገኘ ሰው ካለ እባካችህን አድራሻዬ በሚቀጥለው መንገድ በቀኝ በኩል ስትታጠፉ ያለው አሮጌ ቤት ነው:: አይኔ እንደፈለግኩኝ አያይም: እድሜዬም ገፍቷል: ልጆችም የሉኝም"

ይህንኑ ጽሁፍ ተከትዬ ወደ አሮጌው ቤት ስሄድ አንዲት ሴትዮ ደጃፍ ላይ ተቀምጠዋል: የእግር ኮቴየን ሰምተው "ማነው? ማን ልበል?" አሉኝ

"እዚህ መንገድ ላይ 50 ብር አግኝቼ ነው: እሱን ልሰጥ ነው የመጣሁት" ብዬ መለኩላቸው

አሮጊቷ እንባ ቀደማቸው - "ልጄ! እስካሁን ድረስ ከ40 በላይ ሰዎች 50 ብር መንገድ ላይ ወድቆ አገኘን ብለውኝ መጥተዋል"

ቀጠሉ አሮጊቷ - "እኔ ይህንን ጽሁፍ አልጻፍኩኝም: ጽሁፍ ለመጻፍም ሆነ ለማንበብም አይኔ እሺ አይለኝም"

50 ብሩን በእጃቸው አስጨበጥኳቸው

ጽሁፉን ከስልክ እንጨቱ ላይ እንድቀደው ቢነግሩኝም አላደረግኩም: የመጣውን ሰው ሁሉ ይህንኑ ነበር የሚሉት

ይህንን ጽሁፍ የጻፈውን ሰው እንዴት እንዳደነቅኩት : እኚህን ሴትዮ ለመርዳት የሄደበት ርቀት በጣም ነው ያደነቅኩት

ከሴትዮዋ ቤት ስወጣ አንዲት ወጣት ልጅ አስቆመቺኝ

"ወንድሜ! እዚህ መንገድ ላይ 50 ብር አግኝቼ ነበር: የቤቱ አቅጣጫ በየት በኩል እንደሆነ ታውቃለህ እንዴ?"

በልቤ እየሳቅኩኝ ቤቱን ጠቆምኳት


ሰው መሆኛ መንገዱ ብዙ ነው


By zemelak endrias

@wegoch
@wegoch
@paappii
2024/09/21 08:48:00
Back to Top
HTML Embed Code: