Telegram Web Link
«ውይ በጣም! ከአዲስ ጋር ያሳለፍኩትን ግዜ እወደዋለሁ። እንደሰው ብዙ ያደግኩበት እና የተማርኩበት ጊዜዬ ነው። ስላገባሁትም! ስለፈታሁትም! በሁለቱም ውሳኔዬ ደስተና ነኝ!! አሁን ደግሞ እንደምታዪው {ብላ ከባል እና ሁለት ልጆቿ ጋር የተነሳችውን ፎቶ አሳየችኝ} በጣም! ባሌን እወደዋለሁ! አዲስ በሰጠኝ ስጦታ ነው የራሳችንን ቢዝነስ ጀምረን የምንኖረው። {ሳቅ ብላ } ህይወት ደስ ይላል። »

ስታወራኝ አዲስ እሷ ውስጥ ምን እንደሳበው ለማወቅ አልተቸገርኩም። ሽራፊ አዲስ ውስጧ አለ። የቀለለ ስሜት እንዲሰማኝ ልታስቀኝ ስትሞክር ቆይታ ወደቤቴ ተመለስኩ።

«የአዲስ ሚስቶች ማህበር ነገርማ መመስረት አለብን! ብታዪ አሁን እኔና ሰብሊ በጣም ጓደኛሞች ነን። የሆነ ቀን አብረን ሻይ መጠጣት እንችላለን!» ብላ እንደቀልድ ያወራችውን አሰብኩት። ከእነርሱ ጋር ሻይ መጠጣት አልነበረም ፍላጎቴ! ፍቅር በዚህ ልክ ያቃቂላል? የሚስቶቹን ታሪክ እየሰማሁ ከራሴ ጋር በማነፃፀር መፍታት ያልቻልኩትን እዚህም እዛም የተበታተነ አመክንዮ አጋጭቼ ራሴን ለማፅናናት ነው። እቤት እንደተመለስኩ የጣልኩትን ሰውነቴን ሰብስቤ አፋፍሼ በቁሟ ያለች ሴት ለመምሰል ተጣጥቤ ለባበስኩ።

አራቱን ዓመት አብረን ስንኖር ምን ብለብስ እንደምደምቅለት አስቤው አላውቅም። ልብሴን አይቶ አያውቅም! ሁሌም እኔን ነው የሚያየው የነበረው። አሁን ግን እኔን ማየት አቁሟል። የልብስ ምርጫውንም አላውቅም! አንዱን ሳነሳ አንዱን ስጥል ቆይቼ የሆነ ቀሚስ ለበስኩ። እራት ላይ ተቀብቼ የማላውቀውን ቀይ ሊፒስቲክ ተቀብቼ ተገኘሁ። ለወጉ እልሉን ፊቴ አስቀምጠዋለሁ እንጂ ከሁለት ጉርሻ በላይ ማላመጥ ካቃተኝ ሰንብቻለሁ።

«ደህና ዋልክ?»

«ደህና! ቀንሽ እንዴት ነበር?» ቀና እንኳን ብሎ አላየኝም። እንዲያየኝ ስለፈለግኩ ብቻ

«ዛሬ ፀዲን አገኘኋት!» አልኩት። ባለመገረም ቀና ብሎ አይቶኝ ዓይኖቹ ለውጦቼን በአንድ አሰሳ ካዳረሱት በኋላ ተመልሶ ወደ እህሉ እያጎነበሰ

«ጥሩ ጊዜ አሳለፋችሁ?» አለኝ።

«እ!» አልኩኝ ልቤ ዝቅ እያለብኝ። በልቶ ሲጨርስ ተነስቶ ወደላይብረሪው ሄደ። ወደመኝታ ቤቴ ገብቼ ጉልበቴን አቅፌ ለሰዓታት አለቀስኩ! ሰው ለምን አልወደደኝም ተብሎ ይለቀሳል? ቂልነት እየመሰለኝም ማልቀሴን አላቆምም!! በየቀኑ የማልበላውን እራት ለመብላት የማያየውን መዘነጥ እየዘነጥኩ እቀርባለሁ። የተለመደውን እይታ ገርቦኝ የራሱን እራት በልቶ ወደላይብረሪው ከዛም ወደአንዱ እኔ የሌለሁበት ክፍል ይሄዳል። ለቀናት ለሳምንታት…… የሆነኛው ቀን ወንድሜ በጠዋት ሲበር እቤቴ መጣ። ያየኝ ሰው ሁሉ <ምነው ደህና አይደለሽም?> የሚለኝን አይነት የሰውነት መቀነስ ሾቄ፣ በትክክል ማሰብ ስላቃተኝ ትምህርት ቤት መሄዱን ትቼ፣ ሰኞ እና ቅዳሜ ተምታተውብኝ፣ ጥቅምትና ሀምሌ ተሳክረውብኝ ፣ ቀንና ማታው ተምታቶብኝ ……….. “ ምነው እህቴ ደህና ነሽ ግን?» የሚል ሰላምታ አልነበረም ከአፉ የወጣው።

«እንዴት በቤተሰቦችሽ ትጨክኛለሽ? ጎዳና ቢወጡ ኩራትሽ የሚሆን ነው የሚመስልሽ?» በሚል ወቀሳ ነው የተቀበለኝ። የራሴ ችግር ያለብኝ አይመስላቸውም፣ የራሴ መከፋት ያለብኝ እንደሆነ አያውቁም፣ እኔ በቃ የሆነ የተንጣለለ ቤት ውስጥ የምኖር የኤቲኤም ማሽን ብቻ ነኝ ለእነሱ ሲቸግራቸው እንጂ ቸግሮኝ ይሆን ትዝ የማልላቸው፣ ሲከፋቸው እንጂ ከፍቶኝ ይሆን የማልታወሳቸው፣ ልደርስላቸው እንጂ ግዴታ ያለብኝ ሊደርሱልኝ እሩቃቸው ነኝ። አባቴ ድሮ የተወውን ቁማር በስተእርጅና አዲስ ካፈራቸው ወዳጆቹጋ ሲቆምር ቤቱን አስበልቶ ነው ልክ የእኔ ጥፋት ይመስል በየተራ እየመጡ የሚያስጨንቁኝ።

«ምናገባኝ! ገዝቼ የሰጠሁትን ቤት አላወጣሁበትም ብሎ አይደል በማይረባ ገንዘብ ያስያዘው? እንዴ ቆይ እሺ በምን እዳዬ ነው የቁማር ብር የመክፈል ግዴታ እንዳለብኝ የምታስቡት?»

«ምንም ቢሆንኮ ቤተሰቦችሽ ናቸው።» ያለበት አባባል። ውስጡ ምንአይነቷ ክፉ ነሽ የሚል ቅላፄ ነበረው። ትቼ ነበርኮ! የማልችለውን ለመቻል መጋጋጥ አቁሜ ነበር። ያኔ ያጎበዘኝ አዲስ ነበር። አሁን ግን ግራ ገባኝ የምርም ዝም ብላቸው እንዴት ይኖራሉ? በዛ ላይ ታናሽ እህቴ ስራም ሳይኖራት ለልጁ ወተት እንኳን ከማይገዛ ወንድ ወልዳ እቤት እነሱጋ ናት። በየወሩ ለቀለብ የምቆርጥላቸው ከአዲስ ጋር ተነጋግረን በጋራ ከምንጠቀመው አካውንት ነው። ጭራሽ አባቴ ሲቆምር ቤቱን አሲዞ ስለተበላ 400 ሺህ ብር ካልሰጠኸኝ ብዬ ልጠይቀው? አይሆንም!! ያውም አሁን!!

«አሁን ምንም ማድረግ አልችልም! የዛን ያህል ብር ከየትም ላመጣ አልችልም!» አልኩት። የሆነ እኔጋ ያስቀመጠውን ብር የከለከልኩት እንጂ እርዳታዬን የፈለገ አይመስልም አበሰጫጨቱ። ጥሎ ከቤቴ ወጣ!! የዛን ቀን እራት ሳልቀርብ ተውኩት። አቅም አነሰኝ። የራሴን ስቃይ እየዛቅኩ ስባዝን፣ የቤተሰቤን ሁኔታ እያሰላሰልኩ ስተክን በሬ ተንኳኳ! ከሳምንታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደመኝታ ቤታችን መጣ! ሁሉም ነገር ረጭ አለብኝ!! እረሳሁት! ድካሜን እረሳሁት! ስቃዬን እረሳሁት! ቤተሰቦቼን እረሳኋቸው! እሱ ስጎድልበት ሊፈልገኝ መጣኣ!!

«ደህና ነሽ? እራት ላይ ቀረሽ?» አለኝ በሩ ላይ እንደቆመ። ልለው የምፈልገው ብዙ ነው ጭንቅላቴ ውስጥ የሚራወጠው። <ግድ ይሰጥሃል? ብቀርብም ባልቀርብም ጠረጴዛውን ከከበቡት ወንበሮች ለይተህ አታየኝም ብዬ እኮ ነው የቀረሁት፣ ዓለም ካንተ ጋር አብራ ዞራብኝ ነው፣ ምግብ አልወርድ ብሎኝ ነው> ብዙ ልለው አስባለሁ። አንዲት ቃል ከአፌ ከወጣች ለቅሶዬ እንደሚቀድመኝ ስላወቅኩ ዝም አልኩ። ዋጥ!!

«ፀሃይ ዛሬ አሞሽ እንደዋለ ነገረችን፣ እህልም እየበላሽ እንዳልሆነ፤ ሀኪም ቤት ልውሰድሽ?» <ህመሜኮ አንተ ነህ ሀኪም ምን ይፈይድልኛል? > ማለት እፈልጋለሁ። ከአፌ የሚወጣ ቃል ግን የለም። አጠገቤ ደርሶ አልጋው ላይ ሲቀመጥ ማሰቢያዬ ተንገዳገደ። እጁን ግንባሬ ላይ አድርጎ «ታተኩሻለሽኮ! ሀኪም ቤት እንሂድ?» ደግሞ ተነስቶ አንደኛውን መስኮት እየከፈተ «ቤቱኮ ታፍኗል! ንፋስ ገብቶበት ያውቃል?»

ፊቴን አዞርኩ። ትራሴ ውስጥ ሸፈንኩት። ትንፋሽና ሳጌን ውጬ መዋጥ የማልችለውን እንባዬን ፈቀድኩለት። ለተወሰነ ደቂቃ እንደቆመ ይሰማኛል። ከዛ ቀስ ብሎ በሩን ዘግቶት ወጣ!! እኔም በነፃነት እሪታዬን አስነካሁት። በሚቀጥለው ቀን እራት ስላልሄድኩ ይመጣል ብዬ ጠበቅኩት። ሲመጣ እንደትናንቱ ዝም አልልም! እንዲህ እለዋለው! እንዲያ እለዋለሁ ! እያልኩ ጠበቅኩት! አልመጣም! ከቀናት በኋላ እጅግ በጣም በጠዋት ቀሰቀሰኝ።

«ሰዎች ሊያናግሩሽ መጥተዋል!» እንዲህ ሲጨነቅ አይቼው አላውቅም!! ቁምሳጥኔን ከፍቶ የምደርበው ልብስ እንደመፈለግ አደረገው።

«ማነው በዚህ ጠዋት የሚፈልገኝ?» በደመነፍስ ሲሊፐሬን አጥልቄ ያቀበለኝን ጋውን ለብሼ ወደሳሎን እየሄድኩ የመጡትን ሰዎች ሳያቸው ሳይነግሩኝ በፊት ገባኝ!! አባቴ!! እናቴ እንደትናንት ደውላ አባትሽ ደምግፊቱ ተነስቶበታል ሲነጋ መጥተሽ እዪው ብላኝ ነበር። እሱን ዞሬ አየሁት! መልሼ እነሱን አየሁ! እግሬ መቆም አቃተው! ዘሎ እጆቹን ከስሬ ሲያነጥፋቸው፣ እጁ ላይ ራሴን ስጥል፣ አይኔ ከመከደኑ በፊት ከጉሮሮው የማይወጣ ጩኸት እያማጣ ሊጮህ ሲታገል አየዋለሁ። ስቃይ ያለበት ፊት

........ አልጨረስንም..........

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል አስራ አንድ ………. ሜሪ ፈለቀ)

እሱን ዞሬ አየሁት! መልሼ እነሱን አየሁ! እግሬ መቆም አቃተው! ዘሎ እጆቹን ከስሬ ሲያነጥፋቸው፣ እጁ ላይ ራሴን ስጥል፣ አይኔ ከመከደኑ በፊት ከጉሮሮው የማይወጣ ጩኸት እያማጣ ሊጮህ ሲታገል አየዋለሁ። ስቃይ ያለበት ፊት……….

ሰከንዶች ወይ ደቂቃ አላውቅም እጁ ላይ ምንያህል እንደቆየሁ ግን እንደነበርኩ መሬቱ ላይ ስለሆነ የነቃሁት ብዙም ጊዜ እንዳልሄደ ገምቻለሁ። የረጠበ ፎጣ ደረቴና ግንባሬ ላይ አድርጎልኝ እሱ ቁና ቁና እየተነፈሰ ነቃሁ። ተጠርቶ ይሁን ማወቅ ያልቻልኩት ጎረቤት ያለው ሰውዬ ተሸክመው ወደ መኪናው እንዲወስዱኝ ይወተውታል። መርዶ ሊያረዱኝ የመጡት ሰዎች ይተረማመሳሉ። ፀሃይ ፀሎት ይሁን ወቀሳ ያልለየለት ማልጎምጎም ለአምላክም ለእኛም ታሰማለች። መተንፈስ አቅቶት ሲጨነቅ እሱን ያየው የለም። የተንተራስኳቸው እግሮቹ ይንቀጠቀጣሉ፣ ፎጣ የያዙት እጆቹ ይንቀጠቀጣሉ። ግንባሩ ላይ ላቡ ኩልል እያለ ነው። ማንም አላስተዋለም! የሚያወራው አይሰማኝም ግን አፉ ይንቀሳቀሳል። እኔን አፋፍሰው መኪና ውስጥ ካስገቡኝ በኋላ እሱ እላዩ ላይ አስተኝቶኝ ከጎረቤት የመጣው ሰውዬ እየነዳ ወደሆስፒታል ሄድን። መርዶ ነጋሪዎቹ ወደቤት ተመለሱ።

«እኔኮ ደህና ነኝ! ነቅቻለሁኮ!» እለዋለሁ እየደጋገምኩ ባለኝ አቅም የእሱ ሁኔታ ጨንቆኝ። አፉ ይንቀሳቀሳልኮ ግን ቃል አይዋጣውም። ሆስፒታል እንደደረስን ያስመልሰው ጀመር። የታመመው ማን እንደሆነ ግራ እስኪገባ እርሱ ብሶ ቁጭ አለ። በላይ በላዩ እየተነፈሰ ማስመለስ ቀጠለ። ነፍሱ ካልወጣው ብላ እየታገለችው ነው የሚመስለው። ፊቱ ላይ የተገታተሩት ደምስሮቹ ካጠመቀው ላብ ጋር ሲኦልን ያየ ነው የሚመስለው። እኔ ተወስጄ ጉሉኮስ እየተሰጠኝ ዶክተሩ ስለራሴ እየጠየቀኝ ሁላ እሱ ምን ሆኖ እንደሆነ ነው የምጠይቀው።

«panic አድርጎ ነው።» ይሉኛል። እንዲህ የሚባል ነገር ስለመኖሩ ራሱ ዛሬ ነው የምሰማው። ሰዎች ሲደነግጡ በተለይም በህይወታቸው ከዚህ በፊት ገጥሟቸው የነበረ አስፈሪ ወይም አስደንጋጭ አጋጣሚ ከነበር ተመሳሳይ ነገር ሲገጥማቸው ሊፈጠር ይችላል። አንዳንድ ሰዎች ለምሳሌ መድረክ ላይ ሲወጡ ፓኒክ የሚያደርጉ አሉ ……………. በተደጋጋሚ የሚያጠቃቸው ሰዎችም አሉ። ………… ያለማቋረጥ እየጠየቅኩ ስላስቸገርኩ አብራራልኝ። ከሰዓታት በኋላ የራሱን ህክምና ጨርሶ እኔ ወደተኛሁበት ክፍል መጣ………… ፊቱ ጥላሸት መስሎ፣ ከጣረሞትጋ ሲታገል የቆየ አይነት መስሎ ፣ ከፍ ያለው ትከሻው ወርዶ ፣ ቀና ያለው አንገቱ አቀርቅሮ ………… የእርሱ ባልሆነ አረማመድ የእርሱ ያልሆነ አመጣጥ መጥቶ አልጋው ጫፍ ላይ ተቀመጠ። የሆነ ነገር እንደተፈጠረ ቢገባኝም ምን ብዬ እንደምጠይቅ ግራ ገባኝ!


«ምግብ ስለማትበዪ አቅም ጨርሰሽ ነው አሉኝ!» አለኝ ሞገስ በራቀው ቀሰስተኛ ድምፅ ቀና ብሎ ሊያልቅ የደረሰውን ጎሉኮስ እያየው።

«አዎ እኔ ደህና ነኝ! አንተ ደህና ሆንክ?»

«ደህና እሆናለሁ! ትንሽ ማረፍ አለብኝ። ወንድምሽ እየመጣ ነው! ትንሽ እረፍት ካደረግሽ በኋላ ወደ ቤት ይወስድሻል።» አለኝ

«አንተስ?»

«ወደቤት ልሂድ!» በሚያቃጥል እጁ ፊቴን ነካካኝ። መልሶ ጉሉኮስ ያልተደረገበትን እጄን አንስቶ በመዳፉም በአይበሉባውም እያገላበጠ ሳመው። ዓይኖቼን ተራ በተራ ሳማቸው፣ በሹክሹክታ ነገር «ምንም አትሁኚ!» አለኝ። መርበትበቱ በፍፁም የእርሱ አይደለም። «ምንም አልሆንኩምኮ ደህና ነኝ!» አልኩት!!…………………የስንብት እንደሆነ ልቤ ነግሮኛልኮ ላለማመን ታገልኩ እንጂ …………………. ለደቂቃ ከንፈሬን ከሳመኝ በኋላ። ተነስቶ አሁንም ድጋሚ «ምንም እንዳትሆኚ!» ብሎኝ ወጣ!! ልቤ ተከትሎት ሄደ……. ስንብት እንደሆነ ነፍሴ አውቃለች። ሆድ ባሰኝ!! ተከትዬው ሄጄ አትሂድብኝ ማለት አማረኝ። ……

የአባቴን ለቅሶ እንኳን አልመጣም! ቀብር የለ፣ ሳልስት የለ፣ ……. «አዲስ የት ነው? እንዴት ቀብር እንኳን ይቀራል? ምን አይነት ሰው ነው?» ሲሉኝ መልስ አጣሁ። ሀዘኔን አከበደብኝ። የአባቴን ለቅሶ እንኳን በነፃነት እርሜን እንዳላወጣ አሳቀቁኝ። <እንዴት የሚስቱን አባት ለቅሶ አይመጣም?> አይነት አስተያየታቸው አንገበገበኝ። አዲስ የለም! እንኳን ለቅሶ እቤትም የለም! ከአስራ ሁለተኛው ቀን በኋላ ወደ ቤት ልሂድ ብዬ ስነሳ እናቴ ተከትላኝ ከቤት ወጥታ
«ምንድነው ጉዱ? ከባልሽ ጋር ሰላም አይደላችሁም እንዴ? ደግሞስ ምንም ቢሆን ሀዘን ሀዘን አይደል እንዴ? እንዴት ይቀራል?» ስትለኝ መከፋት፣ ንዴት፣ የአባዬ ሀዘን፣ የአዲስ ህመም……… ሁሉም የእስከዛሬ ጥርቅም ግንፍል ብሎ ተዘረገፈ።

«ዛሬ ለቅሶ ቀረ ብላችሁ ለመውቀስ ጊዜ ነው ሰላም መሆናችን የሚያስጨንቃችሁ? ትዳርሽ እንዴት ነው ብለሽ ጠይቀሽኝ ታውቂያለሽ? ደስተኛ ነሽ ወይ ብለሽ ጠይቀሽኝ ታውቂያለሽ? ንገሪኝ እስኪ እናቴ ደህና መሆኔን ለመጠየቅ ወይም ናፍቀሽኝኮ ብለሽ የደወልሽልኝ መቼ ነው? ብር ያለው ሰው ስላገባሁ የናንተ ፍቅርና መጠየቅ የማያስፈልገኝ፣ የሆነ ነገር ስትፈልጉ ብቻ የምትደውሉልኝ፣ ደበረኝ ስላችሁ ምን ጎድሎሽ ነው የሚደብርሽ አትቅበጪ የምትሉኝ፣ እናቱ የሞተችበት እና እናቱ ገበያ የሄደችበት እኩል ያለቅሳሉ እያላችሁ መከፋቴን ቅንጦት የምታደርጉብኝ። ለወቀሳ ሲሆን እና መሃን ነው ያገባችው ባል እያላችሁ ከእህቶችሽ ጋር ለማማት ጊዜ ግን ትዝ እላችኋለሁ።»

ደነገጠች። እንዲህ ተናግሬም ስለማላውቅ ዝም አለች። እንደልጅነቴ ውስጧ ክትት አድርጋ አቀፈችኝ እና «ወይኔ ልጄን!» አለች በቁጭት! «እኔ ልብሰልሰልልሽ!» በቁጭት ማልቀስ ስትጀምር እኔ ብሼ ተገኘሁ። አይኔ ሊፈርጥ እስኪደርስ ተነፋርቄ ወደቤቴ ተመለስኩ። አዲስ አልመጣም!! አሁን ሀሳብ ያዘኝ! ምን ሆኖ ነው? የት ብዬ ልፈልገው? የዛን ቀን የሆነውን እያሰብኩ የሆነ ነገር ሆኖ ቢሆንስ ብዬ ተጨነቅኩ። ስልኩ ዝግ ነው። ቢያንስ እንዴት ስልኩን ለስራ ሲል ክፍት አያደርግም? ስራ ቦታዎቹ በሙሉ ዞርኩ። ሁሉምጋ ለተወሰነ ጊዜ እንደማይመጣ ነግሯቸው ሀላፊነት እና ስራ አከፋፍሎ እንደሄደ ሰማሁ። ቢጨንቀኝ ፀዲጋ ተመልሼ ሄድኩ። ሰብለምጋ ደወልን! በፍፁም እንዲህ አይነት ባህሪ እንደማያውቁበት ቤቱን እንደቤተክርስቲያን የሚሳለም ሰውዬ ለሁለት ሳምንት ከቤቱ የሚጠፋበት ምክንያት ማሰብ አቃታቸው።

ቤተሰቦቼጋ እየተመላለስኩ ብጠይቃቸውም ባሌ ቤቱን ለቆ ከጠፋ ሰነባበተ ብዬ የምናገርበት አቅም አጣሁ። በአባዬ ሞት እማዬ ተሰብራ ስለነበር ቤቷ አይኗ እያየ በጥጋበኛ ቁማርተኛ ሲወሰድባት ዝም ብዬ ማየት ስላቃተኝ ብሩን በጊዜ ገደብ እንድንከፍላቸው ወንድሜ ተስማምቶ መጣ። በ18 ወር ቀስ እያልኩኝ ልከፍላቸው። አዲስ ይመለስልኛል ብዬ አስቤ ከመጣ እና ከጠየቀኝ አስረዳዋለሁ። ካልጠየቀኝ እሰየው ብዬ ወስኜ ነው።

ከአንድ ወር ከሁለት ሳምንት በኋላ ወደቤት ተመለሰ። ሌላ ሰው ሆኖ መጣ! ያ ሆስፒታል የተሰናበተኝ ሰውዬ አይደለም። ያ በፍቅሩ እየጨስኩ ሳልነግረው ሳለ በልዝቡ የሚወደኝ ሰውዬም አይደለም። ያ መጀመሪያ ሳቀው ጤንነት እንደጎደለው ሰው እንጋባ ያለኝ ሰውዬም አይደለም። ያ በመሃል እያለሁ እንደሌለሁ የሚቆጥረኝም ሰውዬ አይደለም። ሌላ ሰውዬ! አዲስ ሰውዬ ሆኖ ተመለሰ።
ሳየው በደስታ ጦዤ ስጠመጠምበት ልክ ምንም እንዳልተፈጠረ፣ ትናንት እዚሁ እንደነበረ ሁሉ፣ ጭራሽ <ምን ሆነሻል?> በሚል ግራ መጋባት እንደዝምብሎ አስተቃቀፍ ለእቅፌ ምላሽ ሰጥቶ ከቅድም የቀጠለው ውሎ እንደሆነ ነገር ቤት ውስጥ ይንቀሳቀስ ጀመር። ስር ስሩ እየተከተልኩ።

«ምን ሆነህ ነው? እሺ ቆይ በደህናህ ነው ይሄን ያህል ቀን? የት እንደነበርክ አትንገረኝ ቢያንስ ደህና ሆነህ መሆኑን አትነግረኝም?» እለዋለሁ።

«ደህና ነኝ አልኩሽ አይደል? ከራሴ ጋር ጊዜ መውሰድ ፈልጌ ነው!!»

«እና እንደዛ ብለህ አትናገርም? ትጨነቃለች ብለህ አታስብም?»

እያፏጨ እቤት ውስጥ ከወዲያ ወዲህ ይላል። ስለምንም ስለማንም ግድ እንደማይሰጠው። የማላውቀው ሰውዬ ነው። ንዴትም፣ መከፋትም ከዛ ደግሞ ያልገባኝ መዋረድም አይነት ስሜት ተሰማኝ። ትንሽዬ እልህም ነገር። ትቼው ወደመኝታ ቤት ገባሁ። ምን ማሰብ እንዳለብኝ ግራ ገባኝ። በምንም መንገድ ይሄን ሰው ማወቅ እንደማልችል ተረድቻለሁ። <አወቅኩት ብለሽ ስታስቢ ተቀይሬ ብታገኚኝ> ያለኝ ይሄንን መሆኑ ነው? እኔ ግን መንቀሳቀስ ቸገረኝ፣ ወዴት ልንቀሳቀስ? በቃ አዲስ ከህይወቴ ወጥቷል ብዬ ልንቀሳቀስ? ይሂድ? ይቁም የማውቀው እንኳን የለኝምኮ። ልሂድስ ብል ወዴት ነው የምሄደው? እናቴጋ? ግራ ገባኝ! ያለኝ አማራጭ የሚሆነውን ዝም ብሎ ማየት ነበር። የሚሆነው ግን ለመረዳት የቸገረ ነበር።ሌላኛውን መኝታ ቤት በቋሚነት እንድታሰናዳለት ለፀሃይ ትዕዛዝ ሰጠ። ጠዋት ከእንቅልፉ ይነሳል ልክ ምንም ዓይነት ነገር በመሃከላችን እንደሌለ የአዘቦት ቃለምልልስ እናደርጋለን። ጓደኛውን ቻው እንደሚል አይነት <ደህና ዋዪ> ብሎኝ ይወጣል። ምሳ ይመጣል። ስራ ቦታ ስለዋለው ውሎ ያወራል። ተመልሶ ይሄዳል። ማታ ይመጣል። አሁንም ልክ እንደ ትክክለኛ ነገር የቀን ውሎውን ወይም የሆኑ ፍልስፍናዎቹን፣ ወይም ስለገጠመው አዲስ ነገር ሲያወራ ይቆያል። እራቱን በልቶ ላይብረሪ ይሄዳል። ከዛ ወደራሱ መኝታ ቤት!!

እሺ ምን ላስብ? አብረን ነን? ወይስ አብረን አይደለንም? ተጣልተናል ወይስ ሰላም ነን? ልክ ያልሆነ ነገር እየሰራ ያለው እሱ ሆኖ ለማውራት እና ለመጠየቅ የምፈራው እኔ መሆኔስ ምን ይሉታል? ከብዙ እንዲህ ዓይነት ልክ የሚመስሉ ልክ ያልሆኑ ቀናት በኋላ ላይብረሪ ተቀምጦ ላወራው ሄድኩኝ።

«እስከመቼ ነው እንዲህ እንድንሆን ያሰብከው? ምነድነው? ምንድነን እኔና አንተ?»

«ምን ሆንን? ምን መሆን ነበረብን? የአኗኗር ዘይቤዬ ላይ አንዳንድ ለውጦች አድርጊያለሁ። አንዳንዱ ካንቺ ያኗኗር ሁኔታጋ ላይሄድ ይችላል። ያው እንደምታውቂው እኔ ማንንም በማስገደድ አላምንም! የግድ መስማማት የለብሽም!» በአዲስ ሰውነት ውስጥ የሆነ ጋጠወጥ ባለጌ ሰውዬ እያናገረኝ መሰለኝ።

«ምን ማለት ነው? »

«ማለትማ ራሴ ላይ ለውጥ ማድረግ ያስፈልገኝ ነበር። ያንን ነው ያደረግኩት! የሰው ልጅ በየሆነ ጊዜው ራሱን upgrade ማድረግ ያለበት አይመስልሽም?»

«upgrade እስከገባኝ ድረስ ወደመሻሻል ነው። ወደመዝቀጥ አይደለም።»

«ኑሮውን የሚኖረው ባለቤቱ አይደል? እየተሻለው ይሆን እየባሰበት የሚያውቀውም ባለቤቱ ነው። እንደቁስ ተጠቃሚው ቼክ አድርጎ በልፅጓል ወይም ቆርቁዟል የሚል ሰርተፊኬት የምንጠብቀውኮ ኑሯችን ሁሉ ለራሳችን ሳይሆን ለሰው ስለሆነ ነው። እኛ ለራሳችን የሚመቸንን ሳይሆን ሰዎች የሚመቻቸውን እኛን ነው የምንኖረው።»

« ፍልስፍናህን ተወው እና ማወቅ ያለብኝን ንገረኝ! ምንህ ነኝ? ምንስ ሆነን ነው እንድንኖር የምትፈልገው?»

«ምርጫውን ላንቺ ሰጥሻለሁ! ምንድነው ሆነሽ መኖር የምትፈልጊው? የራሴን ፍላጎት ደግሞ እነግርሻለሁ። አንድ መኝታ ቤት መተኛትም ምንም አይነት ስሜታዊ መነካካት አልፈልግም። ከዛ በተረፈ አብሮ መውጣት መግባቱ አይጎረብጠኝም። የግድ ካልተዋሰብን አብሬህ መኖር አልፈልግም ካልሽ እሱም ምርጫው ያንቺ ነው።» የሆነ ጋጠወጥ ሰውዬማ የአዲስን ሰውነት ተውሶ ነው እንጂ አዲስ እንዲህ ባለጌ አይደለም። ……………..

........ .. አልጨረስንም.....................

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል አስራ ሁለት…….. ሜሪ ፈለቀ)

«ዝናቡ ፀቡ ከምሽቱ ጋር ይሁን ከእርሱ ጥበቃ ጋር አይገባውም። የጠቆረው ሰማይ እያፏጨ ያለቅሳል። ……… »

«የመብረቁ ብልጭታ ምናምን ምናምን ብለህ አትቀጥልማ?» ከት ብሎ ሳቀ

በድጋሚ ሌላ ቀን ባዮግራፊውን ልንፅፍ ተቀምጠን ነው ከምን እንደምንጀምር ላልቆጠርነው ጊዜ የምንጀምር የምንሰርዘው። ዛሬ ባልተለመደ ሁኔታ ጥሩ ሙድ ላይ ነው።

«why not?» አለው አይደል እየሳቀ የሚያወራበት ድምፁ?

«come on you are better than this! ሰማዩ የአህያ ሆድ ሲመስል፣ ፀሃይዋ ብርቱካንማ ሆና ስትንቀለቀል አይነት ጅማሬ አንተ ብትሆን ይስብሃል? ተረኩን እያስኬድከው ባለታሪኩ ያለበትን ቦታና ሁኔታ ከታሪኩ ስሜት ጋር ተያያዥነት ካለው ሳለው። ካለዚያ ግን ምንድነው ዝናቡ፣ መብረቁ ? ዝናብ ከሆነ ሰማዩ እንደሚጠቁርና መብረቅ እንደሚኖር አንባቢው የማያውቀውን እውነት እየደጋገሙ ማደናቆር ነው።»

«አንቺ የራስሽን ባዮግራፊ ብትፅፊ ከምን ትጀምሪያለሽ?»

«ህምምም ካንተ በፊት ለመፃፍ የሚበቃ ታሪክ የለኝም! (አይኑን አሸንቁሮ አየኝ) ምናልባት በየመሃሉ አስተዳደጌን እጠቅስ ይሆናል እንጂ …… ስለዚህ በእርግጠንኝነት የምጀምረው ከሆስፒታል በዊልቸር ይዤህ ስገባ ነው።»

በመገረም እያየኝ «ምን ያህል እንደተለወጥሽ ግን ይታወቅሽ ይሆን? ከሰባት ዓመት በፊት ሬስቶራንት ያገኘኋት ለሰው መኖር የደከማት ምስኪን ሴት፣ ምን እንደምትፈልግ ግራ የገባት ሴት ድምጥማጧ ነው የጠፋውኮ!»

«thanks to you! ሰው ካንተ ጋር ኖሮ ካልተቀየረኮ ፍጥረቱ መመርመር አለበት!"

"Is that a good thing or bad?"

"Honestly both. የሚገርመኝ ሰው እንዴት ሁለቱንም perfect ይሆናል? እጅግ በጣም ደግ ደግሞ እጅግ በጣም ጨካኝ! እጅግ በጣም ሚዛናዊ ከዛ ደግሞ በውስን ነገሮች ላይ ሚዛነ ቢስ! ሁለት ተቃራኒ ፅንፍ ድንቅፍ ሳይልህ ትመታለህኮ!! ከሁለት አንዱ ተፅዕኖ ስር አለመውደቅ ከባድ ነው::"

" ተፅዕኖ አንድ ነገር ነው:: ለውጥ ግን ምርጫ ነው:: በየቀን ተቀን ውሎሽ ውስጥ ጫና በሚያሳድርብሽ ብዙ አይነት ግለሰብ እና መረጃ ተከበሽ ነው የምትውዪው ... ለየትኛው እንደምትሳቢ የምትመርጪው አንቺ ነሽ!! ለምሳሌ በፈጣሪ ላይ ባለሽ እምነት የእኔ አለማመን ያመጣብሽ ለውጥ የለም:: እምነትሽን መለወጥ ምርጫ ውስጥ የሚገባ መሰረትሽ ስላልነበረ:: ... .. አየሽ ለውጥሽ በምርጫሽ ነበር:: ይህችን ምድር ከተቀላቀልን ጀምሮ በህይወታችን በሚያልፉ ሰዎች እና በምናገኛቸው መረጃዎች እና በሚያጋጥሙን ክስተቶች ተፅዕኖ ስር ነን። ምን ያህሉ ናቸው ለለውጥ የተጠቀምንባቸው? ያገኘናቸው መረጃዎች በሙሉ እውቀት ቢሆኑን፣ ያወቅናቸው እውቀቶች በሙሉ ደግሞ ቢለውጡን አስበሽዋል? እንዲለውጡን የፈቀድንላቸው ብቻ ናቸው የሚለውጡን።»

« 100% ለውጥ በእጃችን ነው ማለት የማያስችሉን አጋጣሚዎች የሉም?። ለምሳሌ በህይወታችን የሚገጥሙን አንዳንድ መጥፎ ክስተቶች ባላሰብነው አቅጣጫ ይቀይሩናል። ፈሪ ወይም ደፋር፣ ደካማ ወይም ጠንካራ ያደርግሃል።»

«አየሽ እራስሽ አመጣሽው! ተመሳሳይ የህይወት መሰናክል አንዱን ሰው ትሁት ሲያደርገው ሌላውን ክፉ ያደርገዋል። ተመሳሳይ ገጠመኝ አንዱን ሰው ሲያስተምረው አንዱን ሰው ይገድለዋል። ሰካራም አባት ኖሯቸው አንዱ ልጅ እንደአባቱ ሰካራም ሌላኛው በተቃራኒው መጠጥ የማይደርስበት ዋለ። ሰካራሙ <ከአባቴ ምን ልማር? የማውቀው ስካሩን ነው። የተማርኩት ያንን ነው> ሲል ያኛው <ከአባቴ የተማርኩት ሰካራምነት ምን አይነት ከንቱ አባት እና ባል እንደሚያደርግ ስለሆነ ከመጠጥ በብዙ ራቅኩኝ> እንዳለው ነው። ምርጫ አይደለም?»

ፈዝዤ እያየሁት በጭንቅላቴ ንቅናቄ ልክ ነህ ካልኩት በኋላ እኔ የራሴን ምርጫ እያሰላሰልኩ ነበር። ለምን በእርሱ ክፋት መንገድ መጓዝ መረጥኩ? እርሱን ከነጭካኔው ትቼው ያልተበረዘ ልቤን ይዤ መውጣት አልችልም ነበር?

«እንሞክር ደግሞ?» አለኝ ጥዬው በሃሳብ መንጎዴን ሲያስተውል።

«እሺ ግን ያልገባኝ ያንተ ታሪክ ሆኖ ለምንድነው በአንደኛ መደብ መፃፍ ያልፈለግከው? <እርሱ> እያልክ ስትፅፈው እሩቅ ነው! ውስጥህ ያለ ሰው አይመስልም!»

«አንቺ እንድትፅፊው የምፈልገው ክፍል ስላለ!» ልፅፍ እየነካካሁ የነበረውን ኮንፒውተር አቁሜ አየሁት። ቀጠል አድርጎ «ስንደርስበት እነግርሻለሁ።»

«እንደዛም ቢሆን በተለያየ ምእራፍ ያንተን ባንተ አፍ እኔ እንድሞላው ያሰብከውን ታሪክ ደግሞ በእኔ አፍ መፃፍኮ ይቻላል። ምቾት እንደሰጠህ እሺ!» ብዬ ለመፃፍ አጎነበስኩ።

«እኩዮቼ የትምህርት ቤት የቤት ስራቸውን ወላጆቻቸው እያገዟቸው በሚሰሩበት ሰዓት እኔ እሷን ፍለጋ ከአንዱ መጠጥ ቤት ወደሌላ መጠጥ ቤት እዳክራለሁ። እኩዮቼ በሞቀ አልጋ ውስጥ በዳበሳና በተረት ሲተኙ እኔ እናቱ የምትጠጣበት መጠጥ ቤት ደጅ ላይ ተቀምጬ ዝናቡ ያረጠበው ልብሴ እላዬ ላይ ተጣብቆ እጠብቃታለሁ። ትልቅ መሆንን የምመኘው እንዲህ ባሉ አመሻሾች ላይ ነው። ሁሌም መጠጥ ቤቱ እና ሰዎቹ ይለያያሉ እንጂ ሂደቱ ተመሳሳይ ነው። አቅሏን አጥታ ሰክራ መረበሽ ስትጀምር እየጎተቱ ያስወጧታል። እንደዘመናይ እመቤት አጊጣ ከቤትዋ ስትወጣ ላያት የምሽቷ መጨረሻ ከመጠጥ ቤቱ ተጎትቶ መባረር አይመስልም። <የፈረደበት ልጅ! ና በል ውሰዳት! ምስኪን! ምፅ!> ይሉኛል ሲያዩኝ። ይሄኔ በጣም ትልቅ ብሆን ከመጠጥ ቤቱ አፋፍሼ ራሴ ይዣት ብወጣ ነውኮ ምኞቴ ………… ማንም ባይጎትትብኝ!! ማንም ባያዋርድብኝ! እንደ እኩዮቼ እናቶች <የእገሌ እናት> ብለው ቢጠሩልኝ፣ ደግሞ መጣች ብይሉብኝ። ያ ነበር ምኞቴ ……….

ማታ ስተኛ ተንበርክኬ <ትልቅ ሰው አድርገኝ> ብዬ የህፃን ፀሎት እፀልያለሁ። ትልቅ ብሆን መጠጡን እቤቷ እገዛላታለሁ። ትልቅ ብሆን መጠጥ ቤት መጠጣት ስትፈልግ እስክትጠጣ ጠብቄ ማንም ጫፏን ሳይነካት በፊት ይዣት እገባለሁ። በትንሽዬ ሀሳቤ ከምንም እንደማልጠብቃት አውቃለሁኮ ግን እቤት ተኝቼ ብጠብቃት የምትመጣ አይመስለኝም። አንድ ምሽት እንቅልፍ ጥሎኝ ባልመጣላት መንገድ ላይ ወድቃ የምትቀር ይመስለኛል። ለራሴ ይሁን ለራs4 አባቴ እሱ በብዙ እድሜው፣ በትልቅ አካሉ፣ በተከማቸ ልምዱ እና በዳበረእውቀቱ ሊጠብቃት ያልቻለውን ሚስቱን <እናትህን አደራ> ብሎኝ ሌላ ሚስት አግብቶ መኖር ከጀመረ ሶስት ዓመት አለፈው።

የተለመደ ቀኗ እንዲህ ነው። ጠዋት ስትነሳ ከእንባዋ ጋር ትምህርት ቤት ትሸኘኛለች። <ልጄን ልጠብቅህ ሲገባ ጠበቅከኝ! ይሄ የተረገመ አባትህ ትቶን ባይሄድ !> እያለች ትንሰቀሰቃለች። ከትምህርት ቤት ስመለስ ጭሰቶቿን አንዱን ከአንዱ አምታታ ስባ ራሷን አታውቅም። የምበላው አይኖርም። አንዳንዴ እንግዳ ይኖራታል። እንዲህ ባለ ቀን መኝታ ቤቴ ውስጥ ትዘጋብኝና ትረሳኛለች። የሚርበው ልጅ እንዳላት ትረሳኛለች። በሩን እየቀጠቀጥኩ ካስቸገርኳት ከቤት አስወጥታ ውጪ ትጥለኛለች። የመጠጥ ሰዓቷ እስኪደርስ እጠብቃትና እከተላታለሁ። የባሰባት ቀን «ሂድ አባትህጋ! ምን አድርጊ ነው የምትለኝ? ለምን በፀፀት ታበስለኛለህ? የአባትህ አይበቃኝም? ሂድ ጥሎ መሄድ ከዘርህ ነው ሂድ አንተም!» ትለኛለች።
አባቴ ምን እንደበደላት አላውቅም! በምን ምክንያት እንደተለያዩ እንኳን በዛን የልጅነት ጭንቅላቴ ማገናዘብ አልችልም ነበር። የአባቴን በደል እኔ እየከፈልኩ እንደሆነ ነበር የሚሰማኝ። የሱ ልጅ ስለሆንኩ ብቻ ለሱ በደል መቀጣጫ እንዳደረገችኝ። በልጅነት ትንሽዬ ልቤ የሱን በደል ልክሳት ታገልኩላት። እንደሱ ጥያት አልሄድም ብዬ ልጅነቴን ጣልኩ። የእሷን በደል ትቼ የአባቴ ዘር እንዳልሆንኩ ፣ ትቶ መሄድ በደሜ እንደሌለ ላሳያት በጥንጥዬ አቅሜ ባዘንኩላት። አልቆጠረችልኝም።

የሆነኛው ቀን በቃኝ! ደከመኝ! እናቱን የሚጠብቅ ልጅ ሳይሆን እናቱ የምትጠብቀው ልጅ መሆን አማረኝ!! ልጅ መሆን አማረኝ። እንደልጅ መባባል፣ እንደእኩዮቼ ትምህርት እንዴት ነበር መባል፣ እንደእኩዮቼ ምሳ ምን ይታሰርልህ መባል ……. እኩዮቼን መሆን አማረኝ!! ጠዋት እንደተለመደው አገላብጣ እየሳመችኝ ከእንባዋ ጋር ፀፀቷን ስታጥብ ቆይታ

«ልጄ እወድሀለሁኮ! ጠልቼህኮ አይደለም! ወድጄ አይደለም!» እያለች አገላብጣ ስማ ላከችኝ። የማላስታውሰውን ያህል ሰዓት ተጉዤ አባቴ ቤት ሄድኩ።

ከሶስት ቀን በኋላ ግን ከጭንቅላቴ አውጥቼ ልረሳት አቃተኝ። ጥፋት ያጠፋሁ መሰለኝ። የአባቴ ዘር መሆኔን ያረጋገጥኩላት መሰለኝ። እንቅልፍ አልተኛ ምግብ አልበላ አለኝ። የሆነኛው መጠጥ ቤት ደጅ ጎትተው ሲጥሏት፣ እቤት መድረስ አቅተት መንገድ ላይ ስትወድቅ፣ ስትንገዳገድ አንድ መኪና ሲድጣት፣ ደሞ እኔ ልጠብቃት እንዳልመጣሁ ስታውቅ አባቴ ጥሏት ሲሄድ እየተንከባለለች እንዳለቀሰችው ስታለቅስ………. የማስበው ሁሉ የከፋ የከፋውን ሆነ። በነገታው ለአባቴም ለእንጀራ እናቴም ሳልናገር ተመልሼ ወደ ቤት መጣሁ። በሩን ባንኳኳ አልመልስ ስትልኝ በጓዳ መስኮት ዘልዬ ገባሁ። ሳሎን ተዘርራለች። እናቴ ተስፋ እንደቆረጥኩባት ስታውቅ በራሷ ተስፋ ቆርጣ ሄዳለች። አምላክን ለመንኩት! <አንዴ መልስልኝና እስከሁሌው እጠብቃታለሁ! አንዴ ብቻ መልስልኝ!> አልኩት አልሰማኝም! » ጣቶቼ ኪቦርዱ ላይ እየተንቀለቀሉ እንባዬ ታፋዬ ላይ ይንዥቀዥቃል። ዝም አለ። ዝም አልኩ። ለደቂቃዎች ምንም አላወራንም……… የምፈልገውኮ አቅፌው እሪሪሪ ብዬ ማልቀስ ነው። ግን ከተቀመጥኩበት አልነሳም።

አልጨረስንም!!.............................

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል አስራ ሶስት…….. ሜሪ ፈለቀ)

«ሁሉም ሰውኮ አንድ የሆነ ስስ የሆነበት ጎን አለው። ሰዎች ስስ ጎንህን ማወቃቸው ሁሌም መጥፎ ነገር አይደለም። በእርግጥ አንዳንድ ሰዎች ድክመትህን ለመጥፎ ቀን አንተን ለመጣያ ጥይት አድርገው ሊጠቀሙበት ያስቀምጡታል። ለማን ምን ልንገር የሚለው ይመስለኛል እንጂ የሚወስነው ………..» ከአፌ ነጥቆኝ ቀጠለ

«ሁሉም ድክመትሽን የነገርሽው ሰው ድክመትሽን በነገርሽው ሰዓት ይረዳኛል ያልሽው፣ ወዳጄ ያልሽው፣ ያዝንልኛል ያልሽው፣ የኔ ነው ያልሽው…….. ሰው ነው የሚሆነው። አብዛኞቻችን ስንወዳጅ እንለያየን ወይም እንጣላለን ብለን አስበን አይደለም እና ቁስልሽን ቀምሞ አንቺኑ የሚጥልበት ጥይት እንደሚያደርገው የምትረጂው በሆነ ነገር ሳትስማሙ ስትቀሩ እና ስትለያዩ ነው። አየሽ እኔ ደግሞ ትዳርን ጨምሮ ምንም አይነት በሰዎች መሃል ያለ መስተጋብር አንድ ቀን እንደሚፎርሽ አውቃለሁ። ያ ማለት ሳትለያዪም ሚስቴ ያልሻት ሴት ድክመትን ያወቀችው ቀን የተጠቃች ሲመስላት መጀመሪያ የምትመዘው ያንን ስስ ጎንሽን ነው። በዛ ላይ ሰው ምፅ ሲልልሽ እንደሚቀፈው በዚህ ምድር ቀፋፊ ነገር አለ?» አለኝ። የጀመርነውን ባዮግራፊ መፃፍ በመሃል አቁመን ነው ይሄን የምናወራው። ቡና ጠጥተን መጻፍችንን ቀጠልን።

«< ምፅ ! ያላደለው ልጅ! ኖራውም ሞታም ጦስ ሆነችበት። የእናቱን እሬሳ አቅፎ ሲያለቅስ ሰይጣን አጊንቶት ነው!> ይላሉ ሲያዩኝ። የተያዘው አንደበቴ ብቻ ሳይሆን ጆሮዬም የተደፈነ ይመስላቸዋል። የእናቴን ሬሳ ካገኘሁበት ቀን በኋላ ማውራት አቃተኝ። አጋንንት ለክፎት ነው ብለው የአባቴ እህት እና እንጀራ እናቴ በየፀበሉ ይዘውኝ ዞሩ። ዲዳ የሆንኩበትን ምክንያት በየፀበሉ፣ በየመንገዱ <ምን ሆኖ ነው?> ላላቸው ሁሉ ሲያብራሩ አብሬያቸው መሆኔን ይዘነጉታል። እንደገና መሽተት የጀመረው የሬሳዋ ሽታ አፍንጫዬን ያፍነኛል ፣ የተገታተረ ደረቅ ሰውነቷ እጄን ይሻክረኛል፣ ትንፋሽ ያጥረኝና እሰቃያለሁ። <እናቱ ሞታ እሬሳዋን ……..> ማብራራታቸውን ይቀጥላሉ። የሚሰማቸው ሰው <ምፅ ምስኪን!> ይላቸዋል። ምፅ የሚል ሀዘኔታ ሰውነቴን ያሳክከኝ ጀመር። አንድ ዓመት! አንድ ዓመት ሙሉ መናገር አልቻልኩም። የተፀበልኩት ፀበል፣ መስዋእት የቀረበለት አዋቂ፣ ፈዋሽ የተባለ ፀላይ…… ማናቸውም አላዳኑኝም። ማናቸውም ያልገባቸው ካለመናገሬ በላይ መዳን የምፈልገው ጭንቅላቴ ውስጥ ተስሎ ካለው ምስሏ ነበር። በእያንዳንዱ ቀን መስማትም እያቆምኩ እየመሰለኝ ጠዋት ስነሳ ድምፅ መስማቴን እፈትሻለሁ።

በአመቱ አባቴ በጥቆማ አንድ ዶክተር ጋር ወሰደኝ። የተፈጠረውን ነገር ከአባቴ ከሰማ በኋላ የሚፈጠር ነገር መሆኑን አብራራልን። አንደኛው psychogenic mutism ከሚባሉት ውስጥ ነው። ልጆች በተለያየ trauma ውስጥ ሲያልፉ ይከሰታል። ገና አፉን እንደሚፈታ ህፃን ሀ ሁ ብዬ ድምፅ ማውጣት መማር ጀመርኩ። ለወራት ህክምና ስከታተል ቆይቼ ለመጀመሪያ ቀን ቃላት ሰካክቼ ያወራሁ ቀን በቃላት መተንፈስ የፈለግኩት የነበረው።

« ጥያት ባልሄድ ኖሮ አትሞትም ነበር።» የሚለውን ነበር።

አስተካክዬ መናገር የጀመርኩ ቀን መቃብሯ ላይ ሄጄ ስለእሷ ማለት የፈለግኩትን ሁሉ በቃሌ እያልኩኝ አለቀስኩላት። ለሰዓታት አለቀስኩ። የሆነ ነገር ቀለለኝ። የሬሳዋ ሽታ ከአፍንጫዬ ላይ የጠፋ መሰለኝ። እንደማንኛውም ልጅ ማንኛውም ዓይነት የልጅ ህይወት ለመቀጠል ትምህርቴን ካቆምኩበት ቀጥዬ መማር ጀመርኩ።

«እንረፍና እንቀጥል?» ዝም አለ። ዊልቸሩን እየገፋሁ ወደሳሎን መጣን። የሚጨንቅ ዝምታ ዝም አለ። እየደጋገምኩ <ደህና ነህኣ?> እለዋለሁ። ማለት የምፈልገው ብዙ ነበር። ያዘንኩለት ሳልመስል ማዘኔን እንዴት ነው የምነግረው? ይሄን ሁሉ ትናንቱን አውቄ ቢሆን ኖሮ የሆነውን ሁሉ መካኋናችንን ያስቀርልን ነበር? የተወኝን ፣ የገፋኝን፣ የጠላኝን ያስቀርልን ነበር?

«የዛን ቀን እንደምወድህ ባልነግርህ ኖሮ ነገሮች ይቀየሩ ነበር? ያለፉትን መጥፎ ነገሮች ያስቀሩልን ነበር?» አልኩት

«አላውቅም! ማንም ሰው ያለምንም ምላሽ እና ጥበቃ ለዘለዓለሙ አይወድም! (አይወድም የሚለውን በእጁ የትምህርተ ጥቅስ ምልክት ሰርቶ ነው የገለፀው) የጊዜ ጉዳይ እንጂ የሆነ ቀን ትነግሪኝ ነበር። ምላሹንም ትጠብቂ ነበር።»

«እና የዚህ ሁሉ ውጥንቅጥ መንስኤ እኔ እንደምወድህ መንገሬ ነው?»

«አይደለም። ባትነግሪኝም አውቀው ነበር።»

« እና እሺ ምንድንነበር? ምላሹን ስጠኝኮ አላልኩህም ነበር። ያለምንም ጥበቃኮ ወድጄህ ነበር።» አልኩኝ ድምፄ ሁላ ያኔ ወደነበረው ስሜቴ ሄዶ

«የምታስቢው ዓይነት ሰው ሳልሆንልሽ ስቀር ደግሞ የመጥላትን ጥግ ጠልተሽኝም ነበር።»

«ያንን ነበር prove ማድረግ የፈለግከው? ምንም ዓይነት ሰው ብትሆን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ አፈቅርህ እንደነበር?»

«አይደለም!»

«እኮ እሺ ምንድነው?»

«በቃ አንቺ የሌለሽበትን ህይወት መኖር ነበር የፈለግኩት! አንቺ ወደህይወቴ ሳትመጪ በፈቀድኩት መንገድ የማዝዘው ሀሳብና ስሜቴን መልሼ መቆጣጠር ብቻ ነበር የፈለግኩት!» ጮኸብኝ። መጀመሪያ ደነገጥኩ ከዛ ግን ደስ የሚል ስሜት ተሰማኝ። ብዙ ልጠይቀው ፈለግኩ ግን ያ ድሮ እፈራው የነበረውን ዓይነት ፍርሃት ፈራሁት። ዝም አልኩ።

…………….

የዛኔ! ሌላ ሰው ሆኖ ከተመለሰ በኋላ

«ምርጫውን ላንቺ ሰጥሻለሁ! ምንድነው ሆነሽ መኖር የምትፈልጊው? የራሴን ፍላጎት ደግሞ እነግርሻለሁ። አንድ መኝታ ቤት መተኛትም ምንም አይነት ስሜታዊ መነካካት አልፈልግም። ከዛ በተረፈ አብሮ መውጣት መግባቱ አይጎረብጠኝም። የግድ ካልተዋሰብን አብሬህ መኖር አልፈልግም ካልሽ እሱም ምርጫው ያንቺ ነው።» ካለኝ በኋላ

የተኳኋነው እብደት ነው። የአዋቂም የጤናም ያልሆነ እብደት…………….

ምርጫው ያንቺ ነው እንዳለኝ መረጥኩ። አዲሱ አዲስ እስኪበርድለት መታገስ፣ እንደፈለገው ሆኖ የድሮው አዲስ እንዲመለስልኝ ተስፋ ሳልቆርጥ ልጠብቀው ወሰንኩ። አልተመለሰም!! እቤት ሲመጣ እንደእህቱ ነገር ፣ እንደ ጎረቤቱ ነገር፣ እንደ ቤት ደባሉ ነገር ….. አለመቅረብም አለመራቅም የሆነ አኳኋን መሆኑን ቀጠለ። ከህይወቱ ሹልክ ብዬ እንድወጣለት ግን በራሴ እንድወጣለት እንጂ እሱ ውጪ እንደማይለኝ አውቄያለሁ። ብዙ እንደእነዚህ ያሉ የተጃጃሉ ውላቸው ያልለየ ቀኖች ካሳለፍን በኋላ የሆነ ቀን ማታ ላይብረሪ ቁጭ ብለን እያነበብን

«እኔ የምልሽ? በየወሩ ለአቶ ጌትነት የሚል አካውንት ብር የሚላከው ለማንነው? ማነው ሰውየው?» አለኝ። አባቴ ቤቱን በቁማር አስይዞት እንደነበር እና እሱን እየከፈልኩ እንደሆነ አስረዳሁት።

«ታዲያ ቢያንስ ልታሳውቂኝ አይገባም ነበር? እኔ ምን አግብቶኝ ነው የአባትሽን ቁማር ቅሌት የምሸፍነው? ከዛሬ በኋላ ከገንዘቤ ላይ በዚህ ሰበብ ቤሳቤስቲን እንዲነሳ አልፈልግም።» አለኝ

የዛን ቀን ያቺን ሰዓት ለመጀመርያ ጊዜ እልህና ፍቅሬ ፣ ፍቅርና የጥላቻ ዘር ውስጤ ተሳከረ

አልጨረስንም ...........

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል አስራ አራት…….. ሜሪ ፈለቀ)

«ታዲያ ቢያንስ ልታሳውቂኝ አይገባም ነበር? እኔ ምን አግብቶኝ ነው የአባትሽን ቁማር ቅሌት የምሸፍነው? ከዛሬ በኋላ ከገንዘቤ ላይ በዚህ ሰበብ ቤሳቤስቲን እንዲነሳ አልፈልግም።» አለኝ

የብዙ ሰዎች ባህሪ መሰለኝ። እየተገፋን እና በፍቅር የወደቅንለት ሰው በማይገባን መልኩ ክፋትና ጥላቻ እያሳየን ያየነውን መመዝበር አምነን ልባችንን ከመሰበር እንደመጠበቅ ይልቅ እዛው እንቆያለን። ምክንያቱም ከሰውየው እውነተኛ የሚታይ ባህሪ ይልቅ ሰውየው ነው ብለን በልባችን የሳልነውን ምስል እናምናለን። ከዛም አንዴም አይደለም ሁለቴም አይደለም። እየደጋገመ በማይገባን መንገድ ክፉውን እሱነቱን ያሳየንና ልባችንም ተሰብሮ ፣ ሞራላችንም ደቆ፣ ከክብራችንም አንሰን ፣ በፍቅር ልባችን ውስጥ የተሳለውንም ምስል በአውሬ ተክተን ………… ያኔ እናምናለን። በዜሮ አማራጭ እና በሚያነክስ ልብ እንለያያለን።

«በየወሩ የሚቆረጠው ብዙ ብር ስላልሆነ ነበር ያልነገርኩህ። ድሮም ቢሆን ከ50 ሺህ ብር በታች የሆነ ገንዘብ እንዳሳውቅህም ግድ ሰጥቶህ አያውቅም፤ ጠይቀኸኝም አታውቅም ነበርኮ! እውነት ለማውራት ብሩ የሚከፈልበት ምክንያትም አሳፍሮኝ ነበር ያልነገርኩህ።»

«እሱ ድሮ ነዋ! ድሮ አልሽውኮ እራስሽም! ራሴ ላይ ለውጥ አድርጌያለሁ አልኩሽ አይደል? ይኸኛው አዲስ ግድ ይለዋል። አንቺን እንጂ ቤተሰብሽን የማኖር ግዴታ የለብኝም።»

«ምን አድርጌህ ነው ግን ቆይ እንደዚህ የጠላኸኝ? ለምንድነው ክፉ እንደሆንክ ልታሳየኝ የምትፈልገው? ምንድነው ሀጥያቴ? ልወቀው በደሌንና እንድተውህ አይደል የምትፈልገው እተውሃለሁ። ምክንያትህን ብቻ ንገረኝ! እንዳምን ላደረግከኝ ማንነትህ በፍቅር ከመውደቅ ውጪ ምንድነው የበደልኩት? ጠልተኸኝም፣ ገፍተኸኝም ደግሞ <ምን በድዬ ነው?> እያልኩ እራሴን ስጠይቅ እንድኖርም ፈርደህብኝ አላሳዝንህም?» አልኩት ላለማልቀስ ከራሴ ጋር ግብ ግብ እየፈጠርኩ

« አንቺ ነው ብለሽ ጭንቅላትሽ ውስጥ ስለሳልሽው ሰው ተጠያቂ አይደለሁም። ራሴን ስለመሆን እንጂ ሰዎች የሚስሉትን ምስሌን ስለመሆን ግድ የለኝም።» ብሎኝ ጭራሽ ስለጠየቅኩትም የሆነ ያጠፋሁ ነገር አስመስሎት ያነብ የነበረውን መፅሃፍ የመወርወር ያህል ጠረጴዛው ላይ ጥሎት እየተበሳጨብኝ ወጣ!

ሲጀምር ፍቅሩን ፣ገላውን፣ ትንፋሹን ፣ እቅፉን …….. ራሱን ነበር የከለከለኝ እንጂ በንግግር የሚያስከፋኝን ወይም የሚጎዳኝን ነገር ተናግሮ አያውቅም ነበር። ሳይናገር ግን እንድፈራው ያደርገኝ ነበር። ራሱን ከኔ በማራቅ ፍቅርን ስለከለከለኝ ተስፋ ቆርጬበት ጥዬው የምሄድ ነበር የመሰለው ይመስለኛል። በዚህኛው ጊዜ <ይወደኛል! ያሳለፈው የሆነ መራራ ህይወት ፍቅርን እንዲፈራ አድርጎት ነው!! ምን ያህል እንደማፈቅረው ሲያውቅ ይመለስልኛል።> የሚል ሰበብ ነበር ለራሴ የምሰጠው። እየገፋኝ እና እንደሌለሁ እየቆጠረኝ እንኳን ስር ስሩ ከማለት ውጪ የሱን ልብ ልረታበት የምችልበት ምንም መላ ላመጣ ባልችልም በሆነኛው ተዓምር ብቻ የፍቅሬ ልክ እንዲገባው ተስፋ አደረግኩ። አልገባውም ወይም እንዲገባው አልፈለገም! ይሄኛው መንገድ እንዳልሰራ ሲያውቅ ንግግራችንንም በጥላቻ ይለውስብኝ ያዘ። ምን ያህል እንድተወው እንደፈለገ ቢገባኝም እዚህኛው ነጥብ ላይ ሰበቤ ብዙ ነው። <ይወደኛል> የሚለውን <ሊያየኝ አይፈልግም> በሚለው ተክቼዋለሁ።

የዋሁ ልቤ በልቤ የተሸከምኩትን ፣ በፍቅሩ የታመምኩለትን ፣ እኔ ራሴን ስስትበት ፓኒክ ያደረገውን፣ በልግስናው ከማንም የማላወዳድረውን ፣ ለታይታ የማይኖረውን ፣ ያ < እንባሽን ከማይ ሳምንት ፀሃይን ባላይ> የሚለኝን ፣ እንደእኔ ዓይነት ባል የታደለች ሴት የለችም ብዬ የምጎርርበትን ፣ ከነግራ ማጋባቱ የማብድለትን ………… ያን አዲስ ምስሉን ከልቤ ሳይሸረሽረው፤ ክፋቱ በዝቶ መልካም ትዝታዎቼን ሳያጠፋብኝ ፤ እንዳፈቀርኩት ማቄን ጨርቄን ሳልል እብስ ብዬ መጥፋት ያምረዋል። ሌላኛው ልቤ ደግሞ ከጭንቅላቴ ጋር ይማከር እና ከዛስ? ይለኛል።

ከዛስ? በዚህ እድሜዬ እናቴ ቤት ልገባ? ምን ቤት አላት? ቤት ገዛሁልሽ ብያት ከቀበሌ ቤቷ አስወጥቻታለሁ። ሟች ባሏ ያስያዘባትን ቤት እዳ እከፍልልሻለሁ ብያት ከዚህ በኋላ ልከፍልላት አልችልም። ትቼው የነበረውን ማስተማር እቤት እየዋልኩኝ ስብሰከሰክ ከመዋል ብዬ ድጋሚ የጀመርኩት ቢሆንም ደመወዜ እንኳን የቤቱን እዳ ሊከፍል ቤት እንኳን ብንከራይ የቤት ኪራይ አይሸፍንም! ምንስ ብዬ ነው አሁን የምነግራት? ከቤቷ ወጥታ የት ትኖራለች? የአባዬ የጡረታ ብር አይደለም የቤት ኪራይ ሊከፍልላት ብቻዋን እንኳን ብትሆን የቀለብ አይችላትም እንኳን የታናሼ እና የልጇ ሆድ ተጨምሮ። ታናሽ እህቴንስ ምንድነው የምላት? በቃ ከዛሬ በኋላ ልጅሽን የምታደርጊውን አድርጊው ልረዳሽ አልችልም ነው የምላት? አንዳንዴ ምናልባት እንደመጀመሪያ ሚስቱ ጥዬው ብሄድም ባዶ እጄን አይሰደኝም ብዬ አስብ እና ከእርሷ ጋር በሰላም ተከባብረው እንደተለያዩ ሳስበው እጣዬ እንደሁለተኛ ሚስቱ አጨብጭቦ በባዶ እጅ መቅረት ሊሆን እንደሚችል እጠረጥራለሁ። (ሰብለ ፍታኝ ስትለው ትነዳው ከነበረ መኪና ውጪ ምንም ሳይሰጣት ነው የፈታት።) እኔ ደግሞ እሱጋ ያለኝን ቦታ እንኳን ለይቼ አላውቀውም። ይጠላኛል? ይወደኛል? እንደምንስ ይሆን የሚያየኝ?

ከዛ በኋላ የተኳኋነው እብደት ነው። የአዋቂም የጤናም ያልሆነ እብደት……………. አልኳችሁ አይደል?

ይሄን ሁሉ ሀሳብ ደምሬ ቀንሼ እና አባዝቼ ደግሞ እልህ ይይዘኛል። በየቀኑ በቃላት ሊገፋኝ በጣረ ቁጥር ፍቅሬ ከክምሩ ትንሽ በትንሽ እየተናደ …….. ንዴት እና ቁጣ በምትኩ ትንሽ በትንሽ እየተቆለሉ ………. ንዴት እና ፍቅሬ እኩል መጠን ላይ ሲደርሱ ጥላቻ እና እልህ ተወለዱ። አንድ ብለው መሰረታቸውን አኖሩ ……… እፈራው ነበር። ለካንስ እፈራው የነበረው ስለማፈቅረው ነበር። የምፈራው የነበረው እንዳላጣው ስለምንሰፈሰፍ ነበር። ልክ ፍቅሬ መጉደል ሲጀምር የምፈራው ነገር እኩል እየቀነሰ መጣ።

ሁለት ወር የሰውየውን ብር መክፈል ሲያቅተኝ ሰውዬው ለእማዬ ማስጠንቀቂያ ላከ። ከዚህ በላይ መሸሽ የምችለው ሀቅ ስላልነበረ እማዬንም ሁሉንም ሰብስቤ እውነቱን ነገርኳቸው። ሁሉንም ጥቃቅን ነገር ባላወራቸውም አዲስ ደስተኛ ስላልሆነ እንዳልከፍል እንደከለከለኝ ነገርኳቸው። በወንድሞቼ ዓይን ስወርድ ታየኝ። እማዬ ግን ገባት። እንደውም ለብቻዬ ጠርታ ደህና መሆኔን ጠየቀችኝ። ከወንድሞቼጋ ተጋግዘን ልናኖራት ቤት ተከራየንላት። እቃዎቿን ስትሸጥ አይኗን ማየት ስለከበደኝ አላገዝኳትም። መከፋቴን፣ ማፈሬን ፣ ማነሴን የምነግረው ሰው ስላልነበረኝ መኝታ ቤቴን ዘግቼ ተንሰቀሰቅኩ። ቤቷን የለቀቀች ቀን ግን የሆነችውን መሆን ሳየው ቤቷን ለማጣቷ ሰበቡ አባቴ ቢሆንም ላተርፍላት ባለመቻሌ ራሴን ጠላሁት። <ልጄ ዓለሜን እንዳሳየሽኝ ድመቂ > ብላ የመረቀችኝ እናቴ ዓለሜ ያለችውን ቤቷን ራሴ የቀማኋት መሰለኝ። ከታናሽ እህቴ ጋር እና ከልጇ ጋር አንድ መኝታ ቤት ያለው ኮንዶሚንየም ነበር የተከራየንላት። በህይወቴ የተመኘሁት አንድ ነገር ለቤተሰቦቼ ኩራት መሆን ነበር። በቃ ሌላ ምኞትም ህልምም አልነበረኝም:: እስከማስታውሰው ለራሴ በሆንኩት ብዬ አጥብቄ የተመኘሁት የለኝም::

«እንዲህ ያለው ቅሌትስ በዘርም አይድረስ! በመምሻ እድሜዋ አሳይቶ ነሳት!» እያሉ ጎረቤቶቿ ከንፈራቸውን መጠጡላት።
ላፍነው የማልችለው አይነት መከፋት ከፋኝ:: መኖር የምመኝለት ዓላማ ጠፋኝ:: ለቤተሰቤ መሆን አልቻልኩበትም: ወይም መፅናኛዬ የምለው ልጅ እና የራሴ ቤተሰብ የለኝ: ወይም በፍቅሩ እካሳለሁ የምለው ባል የለኝ : ወይም ገና ወጣት ነኝ ነገ የተሻለ ነው የምለው ጊዜ የለኝ : ልደበቅበት የምለው ሙያ እና ህልም የለኝ...... ምንድነው የምኖርበት ዓላማ??

«አምላኬ ሆይ ለምን አሳይተህ ነሳኸኝ? እሺ እኔን ከሆነ መቅጣት የፈለግከው እኔን አትቀጣኝም? ለምን እናቴን? ለምን በስተእርጅና እሷ ትከፋ? ምንድነው ያደረግኩህ ?? ለምንድነው አንድም በህይወቴ የሰመረ መንገድ የሌለኝ??» እግዚዘብሄርን ማማረር ያዝኩ። እናቴን የተከራየችው ቤት አስገብቻት የመጣሁ ቀን .... አዲስ ቀድሞኝ እቤት ገብቶ ነበር:: ... መፍራቴ ትቶኝ የለ??

"በነገርህ ላይ! ምንም እንደማይመስልህ አውቃለሁ ግን እንደው ለጠቅላላ መረጃ እንዲጠቅምህ እናቴ ቤቷን አጥታለች:: .. ዛሬ ኮንዶሚንየም ቤት አስገብቻት መጣሁ::" አልኩት:: ዝም አለ:: ህመሜን እንዴትም ላጋባበት እንደማልችል ባውቅም መከፋቴ ደረቴ ላይ ተነባብሮ ካልወጣሁ ብሎ እያነቀኝ ስለነበር ዝም ማለት አቃተኝ::

"የ48 ዓመት ባሏን እና ጏደኛዋን ባጣች በወራት ውስጥ ቤቷን አጥታ : እቃዋን ሸጣ: በስተርጅናዋ መከፋት ሲሰብራት ብታያት ጥሩ ነበር:: ምንም አይመስልህ እንደው ታውቀው ነበር::" እያወራው ያለሁትኮ ከእናቴ ገንዘቡን ስላስበለጠ እንዲሰማው ላስፀፅተው ነበር:: መከፋቱም ፀፀቱም በእኔው ብሶ እንባዬ ወሬዬንም አደፈራረሰው እና እየሮጥኩ መኝታ ቤቴ ገባሁ:: ህቅ ህቅ ብዬ ተንሰቀሰቅኩ:: .... ለቀናት እየሸሸኝ መሰለኝ ወይም አስጠልቼው እንዳንገጣጠም በተቻለው መጠን ጣረ:: የሆነ ቀን ጠዋት ተገጣጠምን:: አላውቅም ምን እንዳስቆጣኝ ብቻ ግን ውስጤ ያለው እልህ እና ቁጣ ነው::

" ጥላኝ ትሄዳለች ብለህ አትድከም! ስምንት ዓመት እስኪሆን መታገስ አያቅተኝም:: በውላችን መሰረት ግን አንተ ፍቺ ከፈለግክ ይስማማኛል::" አልኩት ልክ እንደእሱ እኔም ለእርሱ ምንም ስሜት እንደሌለኝ ማሳየት ነበርኮ የምፈልገው ግን ድምፄ ልምምጥ እንጂ ቆራጥ ውሳኔዬ እንዳልሆነ አሳበቀብኝ::

ከ8 ዓመት በፊት ፍቺውን የፈለገው እሱ ከሆነ ንብረቱን እኩል የማካፈል ግዴታ አለበት:: ... በልቤ 'እሺ' ቢለኝ የሚለውን ሳስብ ገና ደስ እንደማይለኝ ገባኝ:: እሺ ብሎ ቢፈታኝ ገንዘቡ እሱን ማጣቴን ይክሰዋል? አላውቅም! እሺ አሁንስ እሱ አለኝ ነው የሚባለው?? ምን እንደምፈልግ ሁሉ ግራ ገባኝ:: ሁለቱም ትርጉሙ ያማልኮ .... አንቺ በህይወቴ ውስጥ ከምትኖሪ ግማሽ ልፋቴን ውሰጂና ውጪልኝ መባል ወይም ግማሽ ልፋቴን ከምሰጥሽማ እንዲሁ ጥዕም አልባ ቀን ብኖር ይሻለኛል መባል...... ሁለቱም ያማል:: ... ሁለቱንም በቃሉ አልመለሰልኝም::..... ከጊዜ በኃላ ግን በተግባር ምርጫው ሁለተኛው እንደሆነ አሳየኝ::

ሳምንት ሳምንትን ሲወልድ የጠላሁት ሁሉ መሰለኝ:: ... ንግግራችን እየቀነሰ መጣ:: የሆነ ቀን ምሽት ግን በቁሜ ተኩሶ ልቤን የመታኝ ያህል ተሰማኝ:: ... አምሽቶ ከሴት ጋር መጣ!! አንድ ቤት ከማደራችን ውጪኮ የእኔ እንዳልሆነ አውቃለሁ! የዛን ቀን ግን ሲገባኝ .... ይመለሳል የሚል ተስፋዬ አልሞተም ነበር:: የትኛው ይበልጥ እንዳመመኝ አላውቅም!! እዛው እቤቱ አስቀምጦኝ ሴት ይዞ መጥቶ ክብር የማይገባኝ ምንም እንደሆንኩ የነገረኝ ወይም ለዘለአለም እንደሄደ ማወቄ!! መኝታ ቤት ሆኜ የፀሃይን ያልሆነ የሴት ሳቅ ሰምቼ መኝታቤቴን ከፍቼ ብቅ አልኩ:: ወደእርሱ ክፍል ደረጃውን እየወጡ ነበር:: ... ተከትያቸው ወጥቼ ልጅቷን 'ሚስት እንዳለው ታውቂያለሽ?' ልላት አስቤ ነበር:: ወይም ከእርሱ ጋር 'ምን እያደረግክ ነው?' ብዬ ልጣላ.... ወድያው ጭንቅላቴ ውስጥ የመጣው ብዙ ነበር:: ... ይበልጥ ራሴን ማዋረድ መሰለኝ:: መኝታ ቤቴን ዘግቼው እንኳን የሷ ሳቅ ይሰማኛል:: ... ሆነ ብሎ እንድሰማ እስኪመስለኝ የመኝታ ቤቱን በር አልዘጋውም:: .... ከእነሱ እንዳላየኃቸው እንዳልሰማኃቸው መስዬ መኝታ ቤት ውስጥ ተደበቅኩ ከራሴ ግን የት ልሽሽ??

አዲስ የፈለገውን እና ያመነበትን ነገር የሚያደርግ ሰው ነው:: ነገር ግን የሚኖራቸው መርሆች ያሉት ሰው ነው:: ከእነዚህ ውስጥ አንዱ ወሲብ ላይ ያለው መርህ ነው::

"በፍቅር ካላመንክ: ልጅ ካልፈለግህ: ወሲብን በፈለግከው ጊዜ ማግኘት ትችላለህ ለምን ትዳርን ትደጋግማለህ? ያውም የዓመት ገደብ እያበጀህ "ብዬው ከመጋባታችን በፊት

"እኔ ሴሰኛ አይነት ሰው አይደለሁም!! በየሄድኩበት ባየኃት ሴት ሁሉ ደሜ አይሞቅም:: ከተለያየ ሴት ጋር መባዘን አይመቸኝም:: ከተመቸችኝ ሴት ጋር ባደርገው ነው ደስ የሚለኝ:: ከወሲብ በተጨማሪ ማሰብ የምትችል አብሬያት ብኖር ደስ የምትለኝ ሴት ስትገጥመኝ በሳምንት ሁለቴ ከቤቷ እየጠራሁ ላሽኮረምማት አልፈልግም:: አብሬያት መኖር ደስ ይለኛል እስክንሰለቻች... ይሄን ስልሽ ለሴክስ ብዬ ብቻ ሴት ቀርቤ አላውቅም እያልኩሽ አይደለም:: ግን ለሴክስ ብቻ አብሬያት እንዳለሁም እያወቅኩ ቢሆን እሷ ከህይወቴ ካልወጣች ከሌላ ሴት ጋር አልሆንም ያ መርሄ ነው::" ብሎኝ ነበር::

ቅናት ቆዳዬን ቆጠቆጠኝ:: ... የሳመኝ ከንፈር የሆነችዋን ሴት እንደሚስማት ማሰብ : ከኔ ጋር የሰራቸውን ፍቅሮች ከሆነችዋ ጋር ሊሰራው እንደሆነ ማሰብ .... ያውም እዚሁ አንድ ደረጃ ወጥቶ አናቴ ላይ.... የማይታክተኝን ለቅሶዬን ተንሰቀሰቅኩት:: ... አልወጣልሽ አለኝ:: ... ... በዛ ምሽት እናቴጋ ሄድኩ:: ስታየኝ ደነገጠች:: 'ባሌ እቤቴ ሴት ይዞ መጣብኝ!' ብዬ ልነግራት አፈርኩ:: 'ተጣላን!' ብቻ ብያት መንሰቅሰቅ ጀመርኩ::

"ባልና ሚስት ይጋጫል... እኔና አባትሽ .." ብላ የግጭት አፈታት ብልሃት ስትመክረኝ አደረች:: በነገታው እሁድ ነበር:: ከእናቴጋ ቤተክርስትያን ሄጄ ከሰዓት አካባቢ ወደ ቤቴ ተመለስኩ:: ሳየው ፍቅሬ ቁጣን አልፎ ጥላቻን ... ጥላቻን አልፎ በቀልጋ መድረሱ ገባኝ.... መናደዴን እንዲያውቅም አልፈለግኩም:: ድምፄ ልናገርበት በፈለግኩት ትክክለኛ ድምፀት ታዘዘልኝ....

"ቢያንስ ስትዳራ መኝታቤትህን ዝጋው ቢበዛ ደግሞ ማታ 5 ሰዓት ላይ ለመንደር የሚሰማ ሳቅ እንደማይሳቅ የምታውቅ ኩል ሴት የምትውልበት ዋል::" ብዬው ለፀሃይ ሲመሽ እራቴን መኝታ ቤት እንድታመጣልኝ እንደምፈልግ ነግሬያት መኝታ ቤት ገባሁ::

...... አልጨረስንም........

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል አስራ አምስት…….. ሜሪ ፈለቀ)

ሲመስለኝ ፍቅርም ይረታል። በቁጣ ፣ በክፋት እና በበቀል ይረታል። ወይም ምናልባት እሱን ከማይመስሉ ባህርያት ጋር ግብ ግብ አይገጥም ይሆናል እና ቦታ ይለቃል። ቀስ በቀስ ቁጣ እና መከፋቴ ፍቅሬን እየሸፈነው መጣ። እዚህ ነጥብ ላይ የማስበው ሁሉ በምን መንገድ እኔን ማጣቱ እንዲቆጨው፣ እንዲፀፀት፣ የእግር እሳት እንዲሆንበት እንደማደርገው ነው። በቀል መሆኑ ነው!! በምትኩ በነገረ ስራው የምነደው እኔ ነኝ። ያቺን ከሱሉልታ ፒያሳ የሚሰማ ሳቅ የምታንባርቀውን ሴት እቤቴ ይዟት ከመጣ በኋላ ለሳምንታት ቃላት አልተቀያየርንም። የተያየነውም ለሆኑ ሰከንዶች ያህል ቢሆን ነው። ምግቤን ክፍሌ አስመጣለሁ። ማንበብ የምፈልጋቸውን መፅሃፍት ክፍሌ ይዤ እገባለሁ። (እሱ ከሰጠኝ ስጦታዎች ሁሉ ሳመሰግነው የምኖረው ከማንበብ ጋር በፍቅር እንድወድቅ ስላደረገኝ ነው።) የሆነ ቀን እሁድ ከሰዓት ቢያንስ በወር አንዴ እንደማደርገው ከህፃናቱጋ ላሳልፍ የህፃናት ማሳደጊያ ማዕከሉ ስሄድ እሱ እዛ ነበር። ከህፃናቱጋ ሜዳ ለሜዳ እየተሯሯጠ ይጫወታል። እኔን ሲያዩ ልጆቹ ሰላም ሊሉኝ ወደ እኔ እሮጡ።

ልክ እንደልክ ነገር፣ ትናንት እንዳደረገው የተለመደ ነገር ፤ በመሀከላችን ምንም ፀብ እንደሌለ ነገር በልጆቹ ፊት እቅፍ ነገር አድርጎ ጉንጬን ሳመኝ። ደንዝዤ ባለሁበት ለማላውቀው ጊዜ ያህል ተገተርኩ። ለመጨረሻ ጊዜ የሳመኝን ፣ጭራሽ የነካኝን ጊዜ ለማሰብ ስባዝን እጆቹ እንኳን ቆዳዬን ከነኩት ያኔ ሆስፒታል የተኛሁ ጊዜ ዓመት አለፈው ……… ጠልቼው አልነበር? እንዴት ነው ከንፈሩ ጉንጬ ላይ ሲያርፍ ልቤ ከደረቴ ካላመለጥኩ እያለች የምትደልቀው? መገተሬን ሲያይ መለስ ብሎ አሁንም እንደልክ ነገር ወደጆሮዬ ጠጋ ብሎ

«ልጆቹ እያዩን ነው። ለእነሱ የባልና የሚስት ምሳሌያቸው ፣ የእናት እና የአባት ተስፋቸው ነው። ጨቅላ ጭንቅላታቸው ገና ከጅምሩ በፍቅር ተስፋ እንዲቆርጥ ምክንያት አንሁናቸው!» አለኝ።

ጭንቅላቴ በከንቱነቴ ብስጭት ጦዞ <መጀመሪያስ ምን አስቤ ነው? ምን ዓይነቷ የማልረባ ነኝ በአንድ ጉንጭ መሳም በበደሉ ፈርጥሞ የደደረ ልቤ የሚቀልጥብኝ?> እያለ ያስባል። ከአፌ ማውጣት የቻልኩት ቃል ግን

«እሺ» የሚል ብቻ ነው። ከሰዓቱን በፍቅር እፍ እንዳለ ባል እና ሚስት ስንተውን ከልጆቹ ጋር አሳለፍን።

«እናንተ ለምን የራሳችሁ ልጅ የላችሁም?» አለው አንዱ ተለቅ ያለ ልጅ በልፊያቸው መሃል

«እናንተስ? ይሄ ሁሉ ልጅ የማን ነው? የኛ ልጆች አይደላችሁ?» ብሎ ባኮረፈ አነጋገር ተነጫነጨ።

ልጁ የተከፋበት መስሎት በማባበል አይነት እግሮቹን እያቀፈው
«እኛማኮ ልጆቻችሁ ነን! ሌላ ልጆች ካላችሁ ብዬ ነው! እ? የኛ አባት አይደለህምኮ አይደለም ግን » ብሎ ቀና ብሎ በልምምጥ አየው።
አዲስ ልጁን አንስቶ ተሸክሞት በማላውቀው አዲስ አነጋገር ሲብራራለት እኔ አፌን ከፍቼ እሰማለሁ። ከጨዋታ የተዘናጉትም ህፃናት ገብቷቸው ይሁን አፉ ጣፍጧቸው ይሰሙታል።

«ስለጠየቅከኝ አልከፋኝም እሺ። አንተ ህፃን ልጅ ነህ! ጭንቅላትህ ውስጥ የሚመጣውን ጥያቄ በሙሉ የመጠየቅ መብት አለህ! አዋቂዎች ደግሞ ያንን የመመለስ ግዴታ አለብን! ጥያቄህ ራሳችሁ የወለዳችሁት ልጆች የሏችሁም ወይ? አይደል? እንደሱ ከሆነ የለንም! እናንተ ብቻ ናችሁ ልጆቻችን! (ፈገግ ብሎ በፍቅር ዓይነት እኔን እያየ) እናንተ ትበቁናላችሁ ብለን ነው።»

የዛን ቀን ተመልሼ ወደቤት እየሄድኩ ደብዝዞ የነበረው መከፋቴ አገረሸብኝ። መውደድ ስለማይችል አይደለም። በምርጫው ሊጠላኝ ስለፈለገ እንጂ። አዲስን እስከማውቀው ከህፃናቱ ውጪ ለማንም ሰው የተለየ ፍቅር አያሳይም። ግን ደግሞ ለማንም ሰው ጥላቻን አያሳይም። ስሜት አልባ ይሆናል እንጂ። ላመነበት ምክንያት ማንንም ቢሆን ለመርዳት አያመነታም።ያውም ሰው ስለሆነ ብቻ እንጂ በደም ስለሚጋመድ ወይም ነገ ይጠቅመኛል ብሎ ሳያስብ። ሰውን ከረዳበት ለሚያወጣው ገንዘብም አይጨነቅም። ከቤቱ እና ከመኪናው ውጪ ለየቱም ቁስና ገንዘብ ሌሎች ሰዎች በሚጨነቁት ልክ ግድ ሲሰጠው አይቼ አላውቅም። እኔጋ ሲሆን ብቻ ይለያል ………… እኔን ግን ፈልጎ ነው መግፋት የመረጠው፣ ፈልጎ ነው መበደል የፈለገው፣ ፈልጎ ነው ባልገባኝ ጥፋቴ የሚቀጣኝ። ለምን እንዳልወደደኝ ሳስብ ራሴን መውደድ እቀንሳለሁ።

መጀመሪያውኑም ራስን ስለመውደድ እሱ ነው ያስተማረኝ። ከእርሱ በፊት የረባ የፍቅር ግንኙነት ያልነበረኝ ፣ ቤተሰቦቼን ለማስደሰት ከመዳከር ውጪ ለራሴ ምን እንደምፈልግ እንኳን የማላውቅ ነበርኩ። እሱ የወደደኝ የመሰለኝ ጊዜ ነዋ በእርሱ የመወደድ ዋጋ እንዳለኝ ሳውቅ ራሴን መውደድ የጀመርኩት፣ በራሴ መተማመን መገንባት የጀመርኩት። የሚወደድ ማንነት እንዳለኝ ያሳየኝ እሱ የጠላውን ራሴን መውደድ አቃተኝ። ለሆነ ሰው ማውራት እፈልጋለሁ። ከዛ <ያንቺ ጥፋት አይደለምኮ! አንቺ አሁንም ዋጋሽ ያው ነው እሱ ነው ጥፋተኛው። ቀረበት> እንዲሉኝ። አንደኛ እንደዛ የልቤን የማወራው ጓደኛ የለኝም ሁለተኛ ባወራ እንኳን ለማወራለት ሰው ለፍቅር ያልታደልኩ ዋጋ ቢስ መሆኔን ማውራት ጭራሽ የሚያሳንሰኝ ነው የሚመስለኝ። እሱ እንዳጠፋ ለማውቀው ጥፋት እንኳን በጥፋቱ መንገድ ውስጥ የእኔ ትንሽነት እና መዋረድ ደምቆ ይታየኝና በየቀኑ አንሳለሁ።

ከማሳደጊያው ውሏችን በኋላ በመሀከላችን የነበረው ውጥረት የቀነሰ መሰለ። የጤነኛ አብሮ ነዋሪ ሰዎች ሰላምታ እና ሀሳብ መቀባበል ጀመርን። ስለተፈጠረው ነገር ማናችንም አላነሳንም። እንደውም በቋሚነት ህፃናቱን የምንጎበኝበትን ቀን ልክ እንደበፊቱ <ለልጆቹ ሲባል> ተስማማን። አልፎ አልፎ እራት በአንድ ጠረጴዛ መብላት እና <ቀንህ/ሽ እንዴት ነበር?> አይነት ንግግሮች ጀመርን። አልፎ አልፎም ላይብረሪ ውስጥ ስንገናኝ ስላነበብናቸው መፅሃፍት ማውራት። ስለሚሰማኝ ስሜትም ፣ በትክክል ምን እንደምፈልግም ሳላውቅ በእንደዚህ ያለ ስሙ ያለየለት ኑሮ ወራት ተቆጠሩ። እነዚህ ወራቶች ላይ በተወሰነ መልኩ ነገን አርቄ ሳስብ እሱ የሌለበትን ነገ ማሰብ ጀምሬ ነበር። ባይኖርበትም ግን የሆነ ሰው ሆኜ ያለእርሱ ዋጋ ኖሮኝ አሁንም እንዲያይልኝ እፈልጋለሁ። በተዘዋዋሪ ዋጋዬ ትልቅ መሆኑን ለእርሱው ለራሱ prove ለማድረግ መጋጋጤ ያናድደኛል። ግን ዞሮ ዞሮ ምኞቴ ከዛ አያልፍም።

«የሆነ ሰርግ ተጠርቻለሁ። አብረን እንሂድ?» አለኝ ከእነዚህ ቀናቶች በአንዱ

«እንዴ? አንተ ሰርግ ከመቼ ወዲህ? ማን ቢሆን ነው?»

«እንድሪያስ ሊያገባ ነው።»

ለእኛ ሰርግ ሚዜ የሆነው ሪል ስቴቱን በማናጀርነት የሚሰራለት ሰው ነው። በተለያየ ጊዜ ጎበዝ እና ታማኝ እንደሆነ ነግሮኛል። ቢሆንም አዲስን ሰርግ ሲታደም ማሰብ አስደነቀኝ። የተባለውን ሰርግ ልንሄድ ስንወጣ ልክ ከዛ በፊት ቀሚስ ለብሼ አይቶኝ እንደማያውቅ ሁላ አይኖቹን በልጥጦ እያየኝ

«ቆንጅዬ ሆነሻል!!» አለኝ። ወንድ እንደማታውቅ ልጃገረድ ተሽኮረመምኩ። ባልተረዳሁት ምክንያት የዛን ቀን ደስተኛ ሆንኩ። ችግሩ ደስታሽ አይበርክት ተብዬ ተረግሜያለሁ መሰለኝ ሰርጉ ላይ የማስተምርበት ትምህርት ቤት ባለቤት ተገኝቶ ነበር እና ከአዲስ ጋር አስተዋወቅኩት። እኛ የተቀመጥንበት ጠረጴዛ ላይ ተጋርቶን ተቀመጠ። እና በየመሀሉ ስለትምህርት ቤት እና አንዳንድ ነገሮች እናወራ ነበር። ሰውየው ተጫዋች እና ባየው ነገር ቀልድ መፍጠር የሚችል ዓይነት ስለነበር ሲደመር ከነበረኝ የደስታ ሙድ ጋር ስስቅ እንደነበር አስታውሳለሁ።
የሰርግ ዝግጅቱ ሊያልቅ አካባቢ አዲስ ተነስቶ ወጣ። ሽንቱን ሊሸና ወይም ስልክ ሊያናግር ነበር የመሰለኝ። በጣም ሲቆይብኝ ግራ ገብቶኝ ደወልኩለት ግን አያነሳም። ወጥቼ ሳይ መኪናው ከቆመበት አልነበረም። ያ ድሮ የምፈራው ዓይነት ፍርሃቴ ሆዴን አንቦጫቦጨው። ግራ እየገባኝ ደግሞም እየፈራሁ ምናልባት ከልጆቻችን አንዳቸው የሆነ ነገር ሆነው ይሁን ብዬ አስቤ ለአለቃዬም ይሄንኑ ነገርኩት። <በቃ እኔ ላድርስሽ> ብሎኝ እቤቴ ሸኘኝ። እቤቴ ደጅ ላይ አድርሶኝ ከተሰነባበትን በኋላ ቀና ብዬ ሳይ አዲስ በመስኮት እያየኝ አየሁት። ሳቅኩለት። አልመለሰልኝም። እንደገባሁ እሱ ወዳለበት ክፍል ሄጄ

«ሁሉ ነገር ሰላም ነው? ጥለኸኝ ስትመጣ እኮ መጥፎ ነገር የተፈጠረ መስሎኝ።» አልመለሰልኝም! «ሰርጉ ደብሮህ ነው?»

«ከሰውየው ጋርኮ ፊትለፊቴ ልብሳችሁን ልትጋፈፉ ትንሽ ነበር የቀራችሁ።» ሲለኝ ሳቄን መቆጣጠር አቃተኝ። ቀንቶ ነው ብዬ አስቤ ደግሞ ለእኔ ስሜት ከሌለው ምን ያስቀናዋል? ወይስ ለማንም ሰው ግምት ግድ የሌለው ሰውዬ ሰዎች ለሚያስቡት ግድ ብሎት?

«ቀንተህ አይደለምኣ? እርግጥ አለቃዬ አማላይ ነው ግን በሌላ ነገር የማስበው ሰው አይደለም!» አልኩት። መቀለዴም ነበር።

«ምን ያስቀናኛል? ሳትሳቀቂ እንደፈለገሽ እንድትሆኚ ነው ትቼሽ የመጣሁትኮ » ብሎኝ ኮስተር ብሎ ቁልፉን አንስቶ እየወጣ «እንደዛሬ ደስተኛ ሆነሽ አይቼሽ የማውቅበት ቀን ትዝ አይለኝም። ካስደሰተሽ why not? ደግሞ አብረን አንድ ጣሪያ ስር ኖርን እንጂ ከወረቀት ባለፈ ምንምኮ አይደለንም!» ብሎኝ ልነግረው አፌን መክፈቴን ከቁብ ሳይቆጥረው በቆምኩበት ጥሎኝ ወጣ።

«ደስተኛ ያደረግከኝኮ አንተ ነህ!» ልለው ነበር።
ባስከፋኝ ቁጥር ህመሙ እየቀነሰ መጥቶ ይሆን እኔ እየለመድኩት አላውቅም ብቻ ከቀን ወደቀን ህመሙ ቀንሷል። የዛን ቀን ለለሊት የቀረበ ሰዓት ከሴት ጋር መጣ። ይህችኛዋ ሳቋ ብቻ አይደለም የሚሰማው አልጋው ሁሉ ሲሸበር ይሰማኛል። ሆነ ብሎ እኔ እንድሰማው እሷን ማስጮህ ፈልጎ ካልሆነ በቀር እሱኮ እንዲህ ድብድብ ቀረሽ ልፍያ አይላፋም ነበር! እሷስ ብትሆን ምንድነው ይሄን ያህል ፆሜን አለማደሬን ጎረቤት ካልሰማልኝ ማለት? ከፍቶኛል ግን አላለቀስኩም። ራሴን ጠልቼዋለሁ ግን በዛው ልክ እሱንም ጠልቼዋለሁ። ማነሴ ተሰምቶኛል ግን እሱም አንሶብኛል። አንድ የሆነ ነገሬ ከውስጤ ክፍል ብሎ የወደቀ ዓይነት ስሜት ተሰማኝ። ደሞ የማይበቃቸው ነገርስ?

ከዚህ ቀን በኋላ ያለው ኑሯችን ህፃን ያቦካው ሊጥ ነው። ወይ ተጋግሮ ለእራት አይበቃ ወይ አልቀጠነ ወይ አልወፈረ እጅ ላይ የሚጣበቅ ሊጥ……. መላ ቅጥ የሌለው። እናወራለንም አናወራምም ለማለት የቸገረ። ምንም እንደማይመስለኝ ላሳየው እንፈራገጣለሁ። ምኑም እንዳልሆንኩ ያሳየኛል። ማንም ግን እጅ ላለመስጠት እልህ ዓይነት እንፋታ የሚል የለም። መቆናጠሩን ለመድኩት። እዚህ ወቅት ላይ ነገዬን ያለእርሱ በደብ ማሰብ ጀመርኩ። የሆነኛው ቀን ላይ ስንፋታ ምን ያህል ሀብት እንደምካፈለው ሳሰላ ራሴን ያገኘሁት ቀን በእርግጠኛነት እንደጠላሁት አወቅኩ። እራሴም የማላውቃት ሌላ ሴት ሆንኩ። ከዛ በኋላ ሀሳቤ ሁሉ ከእርሱ ከተለየሁ በኋላ ስለሚኖረኝ ህይወት ሆነ። ትቶ መውጣት የሚለውን ሀሳብ ላላነሳ ከርችሜ ጠረቀምኩት። እንዲህ ልቤ ተሰብሮ፣ እንዲህ ተዋርጄማ ባዶ እጄን ትቼው አልሄድም። ማንም ጉዴንና ውርደቴን ሳያውቅ የተከበረው አዲስ ሚስት እየተባልኩ ያቺን ቀን እጠብቃለሁ። ያኔ ባለብዙ ሚሊየን ሀብት ባለቤት ነኝ። ለእናቴ እንደገና ቤት እገዛላታለሁ። የእህቴን ልጅ አስተምራለሁ። ከዚህ በኋላ የማፈቅርበት ልብ ኖሮኝ ትዳር ስጠኝ ብዬ አልለምንም ግን አምላክ ካልጨከነብኝ አንድ ልጅ ቢሰጠኝ በቃኝ! ሳመነዥክ የምከርመው ሀሳብ እንዲህ ያለውን ብቻ ሆነ። ያ ቀን ሩቅ ሲመስለኝ <ምናለ ወይ በገደልከኝ ወይ በገደልከው?> እላለሁ።

ሴት ማምጣቱን ለመድኩት። ተኝቼ ዙር እቆጥራለሁ። <የዛሬዋ ደግሞ ለቅሶና እንጉርጉሮ l,ieta አታውቅም? እንዴት ያለው አጯጯህ ነው የምትጮኸው?> <የዛሬዋ ደግሞ በአንድ ለሊት ስንት ዙር ነው የምትሄደው እንዴ?> ፣ <የዛሬዋ ደግሞ ምን ብታክል ነው ክፍሉ አብሯት የሚንቀጠቀጠው?> እያልኩ ብዙ ዛሬዎችን ከቆጠርኩ በኋላ ……… ስራ ስሄድ ከውጪ ሲታይ እንዳማረው ዘናጭ ቤቴ ያማርኩ መስዬ ሴሚስተሮች ዘልቄ ……. ለቤተሰቦቼ ብዙ ውሸትን ሳጠግብ ከርሜ ……. ብዙ እሁዶችን እንደሚፋቀሩ ባልና ሚስት ለህፃናቱ ስተውን ባጅቼ ……… ህፃን ያቦካው ዓይነት ኑሮዬን ሳጨማልቅ ሰንብቼ ……..ስሜት አልባ ከሆንኩ በኋላ …….. ለምናፍቀው ቀን አንድ ዓመት ብቻ ከቀረኝ በኋላ አንድ ከሰዓት ስልኬ ጠራ

«ባለቤትሽ መኪናው ተገልብጦ አደጋ ደርሶበታል። ቶሎ ድረሽ!» የሚል። ሆስፒታል ደርሼ በህይወት መኖሩን እስካረጋግጥ ድረስ እንኳን የማስበውን ላውቅ ጭርሱኑ እያሰብኩም እንደነበር እንጃ ……… እንደዛ የጠላሁት ሰው እንዳይሞት መባባቴ ገረመኝ። ለአንድ ወር ሀገር ውስጥ ህክምና ካደረገ በኋላ ከሀገር ውጪ ለህክምና ሄደን ነበር። ሁሉም ተመሳሳይ ውጤት ቢነግሩትም አምኖ ለመቀበል ከበደው። ዶክተርና ሀኪምቤት ቢቀያይርም ውጤቱ ያው ነው።

«በጊዜ እና በፊዚዮቴራፒ እርዳታ እጅህና ሌላው ሰውነትህ ወደ ቀድሞ እንቅስቃሴው ይመለሳል። እግሮችህ ግን መራመድ አይችሉም።»

…………. አልጨረስንም………

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል አስራ ስድስት…….. ሜሪ ፈለቀ)

«ስድስት ዓመት ሙሉ ምን ዓይነት ቀኖች እንደነበሩህ ለአንባቢ ምንም ፍንጭ ሳትሰጥ 20 ዓመትህ ላይ ወደ ሆነ ታሪክ መሄድ ታሪኩን አያጎድለውም?»

«ምንም የሚፃፍ ታሪክ የለውም። ፊልም ቢሆን (በጭንቅላቱ ምስሉን እየከሰተ) ምን ዓይነት ትራንዚሽን መሰለሽ? ማታ 14 ዓመቱ ላይ ተኝቶ ጠዋት 20 ዓመቱ ላይ ሲነቃ የሚያሳይ ሲን ነው የሚሆነው።»

ላይብረሪው ውስጥ ዊልቸሩ ላይ ለሰአታት ከሚቀመጥ በሚል ባስገባነው ሶፋ ላይ እሱ ጋደም ብሎ። እኔ መሬቱ ላይ ተቀምጬ ሶፋውን ተደግፌ ባዮግራፊውን መፃፋችንን እየቀጠልን ነበር። ከምንፅፈው በየመሃሉ የምናወራው ይበልጣል።

«አባትህ? እንጀራ እናትህ? ወንድምህ? ከነርሱጋር የነበረህ ግንኙነት? ትምህርት ቤት? ጓደኛ ? የሆነ የሚወራ የሚወሳ ይኖረዋል። ለህፃን አይደለም ለአዋቂ የሚከብድ ሰቀቀን ያሳለፈ ህፃን እንደማንኛውም ልጄ የተለመደ ዓይነት ዓመታት ሊኖሩት አይችልም መቼም።»

«እነዛ ዓመታት የ trauma ው አካል እንደነበሩ ትልቅ ሰው ከሆንኩ በኋላ ነው ያወቅኩት። ምንም ስሜት ነበር የማይሰማኝ። በቃ ምንም! አድርግ የምባለውን ከማድረግ ውጪ ፀጥ ያለ ህይወት ነበር። አይከፋኝም! አልናደድም! አላለቅስም! ማውራት ብችልም ከማናቸውምጋ አላወራም ነበር። 2 ዓመት ያቋረጥኩትን ትምህርት ቀጥዬ ነበር ብዙም አይገባኝም እንጂ። ቤተሰቦቼን በነዛ ዓመታት አውቃቸው ነበር ማለት ይቸግረኛል። ለእንጀራ እናቴ በእናቱ ሞት ምክንያት በሽተኛ የሆነ፣ አንድ ክፍል ሶስቴ የሚወድቅ ፣አስተውላ ባየችኝ ቁጥር ከንፈሯን የምትመጥልኝ የሆነ ደደብ ልጅ ነኝ። አባቴ ብዙውን ጊዜ ሊያዋራኝ ሞክሮ ፍላጎት እንደሌለኝ በመረዳቱ ከመተው በተጨማሪ በስራ ምክንያት ከቤት ውጪ የሚያሳልፈው ጊዜ ነው የሚበልጠው። ጓደኛ ቅብጠት ነው። በምማርባቸው ክፍሎች ሁሉ በእድሜም በሰውነትም ትልቅ ልጅ፣ በዛ ላይ እንደበሽተኛ የሚቆጠር ማን ጓደኛ ሊያደርገው ፍላጎት ይኖረዋል? ወንድሜ በሁለት ዓመት ቢበልጠኝም በጊዜው ልጅ ነበር።»

«አልገባኝም አባትህ ከእናትህ በኃላ መስሎኝ………»

«ህም የተጋቡት ከእናቴ ከተለየ በኋላ ነው። እንጀራ እናቴ ከእናቴ በፊት ፍቅረኛው ነበረች። የእነሱ ታሪክ ብቻውን ሌላ መፅሃፍ ይወጣዋል። ወንድሜን ወልዳለትም እናቴን ያፈቅራት ስለነበር ለማግባት እናቴን መረጠ። በኋላ ትቷት ቢሄድም።»

«ለአንባቢ ሙሉ ስሜት እንዲሰጥ መካተት አለበት እንደእኔ።» አልኩኝ። ትከሻውን ሰብቆ ዝም አለ። የነገረኝን አሳምሬ ለመፃፍ ሞከርኩ እና ጮክ ብዬ አነበብኩለት። ማስረዳት በማልችለው ምክንያት ያለፈበትን እኔ እንዳውቀው እንጂ መጽሃፍ ሆኖ ስለመታተሙ ብዙም ግድ የሰጠው አልመስልሽ አለኝ። ምንም ከማለት ተቆጥቤ የሚቀጥለውን እሱ እየነገረኝ መፃፍ ጀመርኩ።

«መጀመሪያ እቤት የመጣች ቀን ነው ከማውቃቸው ሰዎች ለስሜቴ የቀረበች እንደሆነች የገባኝ። ቀጥታ መኝታ ቤቴ ገብታ የለበስኩትን ብርድ ልብስ ከላዬ እየገፈፈች።

<ያንተ አቻ ፈረንጅ ስንት ቴክኖሎጂ ለሀገሩ አበርክቷል አጅሬው በ20 ዓመትህ ዘጠነኛ ክፍል እየተማርክም እስከ ጠዋቱ 4 ሰዓት እንቅልፍህን ታገነፋለህ?> አለችኝ።

ማንም ሰው እድሜዬንና የትምህርት ቤት ደረጃዬን ከንፈሩን ሊመጥልኝ እንጂ እንደሷ ያውም ለራሴው ተናግሮ ሰምቼ አላውቅም። አባቴ ዘጠነኛ ክፍል ስገባ በግል እንድታስጠናኝ ብሎ የቀጠረልኝ በእድሜ እኩያዬ የሆነች የዩንቨርስቲ ተማሪ ናት። የዛን ቀን ብርድልብሱን ከላዬ ስትገፍ የዓመታት ሰቀቀኔንም ነበር አብራ የገፈፈችው።

<ማዕረግ እባላለሁ። አስጠኚህ ነኝ I think አባትህ ነግሮሃል። ጊዜዬን አትብላብኝ ሳሎን እየጠበቅኩህ ነው።> ብላ ትታኝ ሄደች።’”

እያወራልኝ የፊቱ ፀዳል ያቺ ሴት ማን እንደነበረች ሳይነግረኝ በፊት አወቅኩ። ዞር ብሎ ሳያየኝ ወቅቱን ከነስሜቱ ወደአሁን ጎትቶ ማውራቱን ቀጠለ።

«ለሳምንታት እሰማታለሁ እንጂ ብዙም አላወራም። በሷ ጣፋጭ ቃላት እና ለዛ ስታወራው ትምህርትም ህይወትም ቀላል ነው። የፊደል እና የቁጥር ሰልፍ ከመሆናቸው ውጪ እምብዛም የማይገቡኝ ፅሁፎች እሷ ስትፈተፍታቸው ትርጉም ነበራቸው። አንድ ቀን ሳሎን እያስጠናችኝ እንደምትፈልገው አልመልስ ስላት <አንተ ግን በዚህ ዓይነት እንዴት ነው ከሰው ጋር ተግባብተህ የኖርከው በአባቢ ሞት? ከአፍህ በሚወጡት ፊደላት ልክ አትከፍልም እኮ ወይም እዳ አይሆኑብህም! ምንድነው? My God! > ብላ ስትጮህ እየሰማች መሆኑን ያላወቅኳት የእንጀራ እናቴ በጣም ሳቀች። አስከትላም። < እንደውም አንቺ ከመጣሽ ጀምሮ እየተሻሻለ ነው። እናቱ ከሞተች በኋላ ጭራሽ ………> ብላ የሆነውን ትነግራት ጀመር። ማዕረግ ያለፈ ህይወቴን መስማቷ መጥፎ ስሜት እንዲሰማኝ አደረገኝ። ተነስቼ ወደ መኝታ ቤት ገባሁ። ከደቂቃዎች በኋላ ወደክፍሌ ስትመጣ ብዙ ለሊት ተኝቼ አልጋ ላይ ሽንቴን መሽናቴን ጨምሮ ምንም ያላወቀችው ገበናዬ እንደሌለ እርግጠኛ ነበርኩ። የተለመደ ነው። ስለእኔ ለጠየቀ ሰው በሙሉ ይነገረዋል። እናቴ መቃብር ላይ ካለቀስኩኝ ቀን በኋላ ግን ምንም ስሜት ሰጥቶኝ አያውቅም ነበር። ሰሚዋ ማዕረግ እስከሆነችበት ቀን ድረስ

<you are brave> አለችኝ መጥታ አልጋዬ ላይ እየተቀመጠች። <ምፅ! ምስኪን> የሚል ሀዘኔታ ነበር የለመድኩት እና ጆሮዬ ደነገጠ።

<ታውቃለህ ? ያልገባህ ነገር ያንተ ጥፋት አልነበረም! ማድረግ የምትችለው ነገር አልነበረም። ራሷን አይደለም ያጠፋችው ያን ታውቃለህ አይደል? አንተ ጥለሃት ስለሄድክ አይደለም የሞተችው! ድራጉን ኦቨርዶዝ ወስዳ ነው።> ልዩነቱን ማወቅ አለማወቄን ለማረጋገጥ አይኔን እያየች <ታውቃለህ እሱንኣ?> ዝም አልኳት <God damit መልስልኝ!> ብላ ስትጮህ ጥያቄዋ ሁሉ ጠፋብኝ እና ዘልዬ ቁጭ አልኩ። የእኔ መደንገጥ አላስደነገጣትም። ጭራሽ ተመቻችታ እየተቀመጠች። ትጮህብኝ ጀመረ።

<ስማኝ? ምናልባት አንተ እዛ ያለመኖርህም ትዝ አላላት ይሆናል። ከለመደችው መጠን ሞቅ ያለ እብደት ፈልጋ ጨምራ የወሰደችው ድራግ ነው የገደላት። አጠገቧ ሆነህም ቢሆን አታድናትም ነበር። ለሷ ሞት ያበረከትከው ምናምኒት አስተዋፅኦ የለም።>

<አጠገቧ ብኖር ተጨማሪ ላትወስድ ትችላለች፣ አጠገቧ ብኖር ስትወድቅ ሀኪም ቤት እወስዳት ነበር፣ አጠገቧ ብኖር ሞታ እንኳን ሳትሸት ትቀበር ነበር። ……….. > መቃብሯ ላይ ካለቀስኩ በኋላ ያላለቀስኩት እንባዬ በዓረፍተ ነገር ታጅቦ እናጠው ጀመር። ጭንቅላቴ ውስጥ ያለውን <ባልተዋት ኖሮ > በሙሉ ነገርኳት። አቅፋ እያባበለችኝ ግን ደግሞ ትቆጣኛለች።

<ቢሆን ኖሮ እያልክ በመላ ምት ስትጃጃል መኖር ነው የምትፈልገው? እኩዮችህ እንደ ዝግምተኛ ሲያዩህ መኖር ነው የምትፈልገው? እስከመቼ ነው ራስህን ስትቀጣ ለመኖር ያሰብከው? ምንም ጥቅም የሌለው ልጅ ሆነህ እዚሁ አልጋ ላይ ማርጀት ነው የምትፈልገው? ያን መከራ በ12 ዓመቱ ተቋቁሞ ያለፈ ልጅ በ20 ዓመቱ እንዲህ ጂል ይሆናል?>
እብድም ግልብም ናት ስታወራ። ከዛ በኋላ ብዙ ነገር ስሜት ይሰጠኝ ጀመር። ቢነኩት ይፈርጥ ይመስል የተድቦለቦለ ሰውነቴ አስጠላኝ። እስፖርት መስራት ጀመርኩ። ትምህርት ቤት ልጆቼ ከሚመስሉ ተማሪዎች ጋር መማሬ ያሳፍረኝ ጀመር። ወንድሜ ዩንቨርስቲ ተማሪ ቢሆንም ሴት በማሳደድ እና ጭፈራ ቤት ለጭፈራ ቤት እንደሚያድር ማወቅ ያሳዝነኝ ጀመር። አባቴ በእኔ ዝምታ ውስጥ ፀፀት እንደሚያንገበግበው አስተውልለት ጀመር። የእንጀራ እናቴ ድንገት እንደባነነ ሰው የመንቃቴ ነገር ደስታ እንዳልሰጣት ማገናዘብ ቻልኩ። የማነባቸው መፅሃፍት እያመጣች ትሰጠኛለች። ለሷ ስል ራሴን ልቀይር በረታሁ። እሷ ማለት ጥቅጥቅ ባለ ጨለማ ዋሻ ውስጥ በርቀት የታየችኝ የብርሃን ፍንጣቂ አይነት ነገር ናት። የድሮው አዲስ የሞተ ይሄኛው አዲስ ማዕረግ ከሞቱ ቀስቅሳው ለማዕረግ የሚኖርላት ነበር። ድጋሚ የመኖር እድሌ ነበረች።

አንደኛ ሴሚስተር ሲያልቅ በትምህርቴም በአካሌም በውስጤም ሌላ ሰው ነበርኩ። ማዕረግ የሞላችበት ሰውነት ያለው ሰው። የአንደኛ ሴሚስተር ውጤቴን አያለሁ ያልኳት ቀን በጠዋት መኝታ ክፍሌ <የታል?> እያለች ገባች። ስታየው ቦረቀችልኝ። ካርዱን ወርውራው ከንፈሬን ለደቂቃ ሳመችኝ። <ወይኔ ጉዴ ለካ ምንም አታውቅም!> ብላ ምንም እንዳልሰራች ነገር <ና እኛ ቤት እንሂድ የማሳይህ ነገር አለ> ብላ እጄን እየጎተተች ወጣች። ታክሲ ተሳፍረን እቤታቸው እስክደርስ ድረስ እኔ የማስበው ቅድም የሳመችኝን ነበር። እሷ የተለየ ነገር እንዳላደረገች ሌላ ወሬ ታወራለች። እቤታቸው ማንም የለም። በሩን ቆላልፋ <የምከፍትልህ ፖርን ነው። ተሽኮርምመህ አማትበህ ምናምን እንዳታፀፅተኝ> ብላኝ ትንፉሽ እንኳን ሰብስቤ ሳልዘጋጅ ከፈተችው። አጉል አጉል የሆነ እያሳየችኝ አጓጉል አደረገችኝ።» እኔ ራሴ ሊከሰት የሚችለውን አስቤ መፃፌን መቀጠል አቃተኝና ሳቅኩ። በሳቁ አጀበኝ።

«እብድ ናት!» አለኝ እየሳቀ።

«መድሃኒት የሆነህ እብደቷ አይደል?»

«exactly!!» (ካለ በኋላ መጥፎውን ትዝታ እንደጫረው እስከአሁን የነበረውን የክፍሉን ድባብ የቀየረ የፊቱን ፀዳል አደበዘዘው)

«እንቀጥል ወይስ ማረፍ ትፈልጋለህ?»

«am good እየፃፍሽ ያለሽውኮ አንቺ ነሽ! ማረፍ ከፈለግሽ የተወሰነኮ መፃፉንም ጣቴን ሳላደክም ላግዝሽ እችላለሁ!»

«እንቢየው! መጻፉንማ ራሴ ነኝ የምፅፈው!»

«<አፈቅርሃለሁ እኮ አንተ ዱዝ!> አለችኝ አጓጉል ባደረገችኝ ማግስት

<አውቃለሁ!> ብዬ መለስኩላት

<ወይኔ ጉዴ! ስንቱን ነው አስተምሬህ የምዘልቀው? ሴት ነኝ! ሴት ልጅ መፈቀሯን በጆሮዋ መስማት ትፈልጋለች።>

<ምርጫኮ አልሰጠሽኝም ነበር። አንቺን አለማፍቀር አልችልም ነበር።>

<ጎበዝ ሆነህ አኩራኝ> አለችኝ ያን ቀልብ የሚነሳ መሳሟን እየሳመችኝ። እብደቷን አበድኩት። ፍቅሯን ለነፍሴ ደርቤ ሞቀኝ። በሷ ውስጥ ነፍስ ዘርቼ ደስታን ቃረምኩ። አልፈልግም ብላ አውጥታ ብትጥለው ይጎዳብኛል ሳልል ስጋዬንም ነፍሴንም ልቤንም ያልሰጠኋት አልነበረም። እሷው እንደአዲስ ያበጃጀችው እኔነቴ ነበር እና ልሰስትባት አልችልም ነበር።

ዘጠነኛን ክፍል እንደጨረስኩ እሷ እናቷ ስለታመመችባት ትምህርቷን ልታቋርጥ ሆነ። አባቴን እሱጋ ስራ እንዲያስገባኝ ለምኜው እኔ ትምህርቴን ተውኩት እና እሷን ማስተማር ጀመርኩ። ለእርሷ መኖር የህይወት ግቤ ስለነበር እሷ የምታገኘው እንጂ እኔ የማጣውን የምቆጥርበት ልብ አልነበረኝም። አባቴ ትምህርቴን መተዌ ባያስደስተውም እንደጤነኛ ልጅ ዳግም ሰው መሆኔ ስላስደሰተው አልተጫነኝም። አኖረችኝ። ኖርኩላት። በአመቱ እናቷም ወደጤንነታቸው ተመለሱ። አባቴ በወቅቱ መጠነኛ የሲሚንቶ ፋብሪካ ነበረው። በአጭር ጊዜ ውስጥ ስራዎቹን ለምጄ ማሻሻያ ሀሳቦች ማቅረብ ስጀምር አባቴ በደስታ ሲቅበጠበጥ እንጀራ እናቴ በግልፅ በእኔ ስራ ብቃት እምነት እንደሌላት ያለፉትን ዓመታት እና ያለመማሬን እያጣቀሰች መናገር ጀመረች። ማዕረግ ያጎበዘችው ልቤ ለሷ ኩራት ለመሆን የማይረግጠው ቦታ የለም።

<አንተ ዱዝ አፈቅርሃለሁኮ! አንተ ባትኖርልኝ ምን ይውጠኝ ነበር? > እያለችኝ ተመረቀችልኝ። በዛው ዓመት እንደማዕረግ በማዕረግ ባይመረቅም ወንድሜም ተመርቆ ነበር። የሱ ምርቃት ድግስ ቀን የኔ ማዕረግ ውብ ሆና መጥታ ነበር። እንደሁሌውም በህይወት ውስጥ ከሷ ውጪ ዓይኔን የሚስበው ነገር እንዳለመኖሩ አጠገቤ አስቀምጬ አይን አይኖቿን ሳይ መሸ። ለአፍታ ዘወር ብዬ ስመጣ ሳሎን የለችም። ምናልባት ወደ መታጠቢያ ቤት ሄዳ ይሆናል ብዬ ልፈልጋት ስሄድ ሳቋን ሰማሁት። ከወንድሜ መኝታ ቤት ነው። ምን አስቤ ይሁን ሳላስብ አላውቅም እግሬ ወደዛ ተራመደ። ጆሮዬ የገባው

«አንተ እረፍ ልመለስ! ያወቀ እንደሆነ ደግሞ ዲዳ ሆኖ ሀሁ ሳስቆጥረው ልክረም?» የሚለውን ሳቃቸው ያጀበውን ድምፅዋን ነው። ሳቃቸውን ሳይጨርሱ ብቅ ሲሉ መንቀሳቀስ አቅቶኝ እንደቆምኩ ነበር።

አልጨረስንም

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል አስራ ሰባት ………. ሜሪ ፈለቀ)

< «አንተ እረፍ ልመለስ! ያወቀ እንደሆነ ደግሞ ዲዳ ሆኖ ሀሁ ሳስቆጥረው ልክረም?» የሚለውን ሳቃቸው ያጀበውን ድምፅዋን ነው። ሳቃቸውን ሳይጨርሱ ብቅ ሲሉ መንቀሳቀስ አቅቶኝ እንደቆምኩ ነበር። > የሚለውን እንደፃፍኩ አቁሜ

« በመድሃንያለም !ውይ ምን ሆና ነው?» አልኩኝ ራሴው ቁዝም ብዬ

«ሰው! ሰው ሆና ነው! የትኛውስ ሰው ቢሆን እንዲህ አይደለም?»

«ይሄ ሰውነት አይደለም!!» ለወሬ እየተቅለበለብኩ ኮንፒውተሩን መሬት ላይ አስቀምጬ በጉልበቴ መሬቱ ላይ ተንበርክኬ ወደእርሱ እየዞርኩ።

«ትክክለኛ ሰውነት ውስጥ ክህደት የለም። ሰውነት ተፈጥሮ ነውኮ እንዴ? ልክ እና ስህተትን በሚያሰላ ህሊና በሚባል ሞተር የሚዘወር ተፈጥሮ ነው። የማንበብህ ብዛት፣ ሀይማኖት፣ የልምድህ ክምችት አልያም ስልጣኔህ ወይም ህግ የሚሰጥህ ነገር አይደለም።»

«ህሊና ከጠቀስቻቸው ዝርዝሮች ተፅዕኖ በላይ አይደለም።»

«በሱ እስማማለሁ። ለዛ ነው ተፈጥሮ ነው ያልኩህ!! በመረጥከው መንገድ ልታሳድገው ወይም ደግሞ ልታዳፍነው ትችላለህ። ለምሳሌ የህሊናህን ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያ አልፈህ አንድን ነገር ስታደርግ በደጋገምከው ቁጥር የፀፀትህ መጠን ይቀንሳል። ያ ምናልባት ከዘረዘርኳቸው በአንዳቸው ተፅዕኖ ምክንያት ህሊናህን ላለመስማት ወስነሃል ማለት ነው እናም በሱኛው እሳቤህ ህሊናህን ትከድነዋለህ። በተቃራኒው ደግሞ እግዚአብሔርን በመፍራት ውስጥ በስነስርዓት እና በመልካም ሀሳቦች አዕምሮህን ስታበለፅግ የህሊናህን ቀይ መብራት በደንብ ለማዳመጥ ንቁ ትሆናለህ። በእርግጠኝነት ግን በምንም ተፅዕኖ ህሊናህን ብታዳፍን ሰውን መጉዳት ወይም ክህደት ሰውኛ አለመሆኑን ለመረዳት አትቸገርም።»

«ችግሩ አብዛኛው ሰውኮ ሰውን ለመጉዳት ብሎ አይጎዳም። ከሚጎዳው ሰው እና ከራሱ መምረጥ ሲኖርበት ግን እራሱን ያስቀድማል። ይሄ ደግሞ ትክክለኛ የሰው ስሜት ነው።»

«እና ማዕረግም ራሷን ነው የመረጠችው እያልከኝ ነው?»

«አዎ! ከእኔ ደስታ እና ከራሷ ደስታ መምረጥ ሲኖርባት ራሷን መረጠች ብዬ ነው የማስበው። እስኪ አስቢው ያን አዲስ? አይጨንቅም? ከጠዋት እስከማታው ማዕረግ፣ ደስታው ሀዘኑ ማዕረግ፣ መብላት መጠጣቱ ማዕረግ፣ መስራት ማወቁ ሁሉ ማዕረግ…….. በህይወቱ ከእርሷ ውጪ ምንም ግብ እና ዓላማ የሌለው ፍጡር! አይጨንቅም? በሱ ህይወት ውስጥ ያንን ሁሉ ሆኖ መኖርስ ነፃነትን ማጣት አልነበረም? እሷ ደግሞ በእንደዛ ዓይነት አጥር የማትያዝ ፣ ነፃነቷን የምትወድ ፣ እንደስሜቷ መብረር የምትፈልግ ፣ እሳትም ቢሆን ሞክራ መፈተን የምትፈልግ ዓይነት ነበረች። ከዓመት ዓመት አንድ ዓይነት ቀን ያለው ዱዝ ደስታ ወይስ የራሷን አድቬንቸረስ ቀን መምረጥ ነበረባት። ራሷን መረጠች። »

«አንተ የምርህን ነው? እሺ ንገረኝ ከዛ በኋላ የተፈጠረውን?»

« አልራበሽም? የሆነ ነገር ከበላን በኋላ አንፅፍም?»

«አልራበኝም! ከዛ በኋላ የሆንከውን ካልሰማሁ ደግሞ መብላት አልፈልግም። መፃፉን በኋላ እንፅፈዋለን። ንገረኝ! ከዛስ?» ለወሬ ስቁነጠነጥ ትንፋሼ ፊቱን የሚሞቀው ያህል ቅርበት ላይ እንዳለሁ ያወቅኩት እጁን በአንገቴ አዙሮ ማጅራቴ መጨረሻጋ ያሉትን ድፍት ያሉ ፀጉሮች ሲነካካቸው ነው። (ከግንባርሽ ይልቅኮ ከጀርባሽ ነው ቤቢ ሄር ያለሽ ይለኝ ነበር ድሮ)

«ከምኑ በኋላ?» አለኝ እጁ ምን እንደሚያደርገኝ ስለሚያውቅ ፈገግ ብሎ።

«ከወንድምህ ጋር ከሰማሃት በኃላ……. ከዛ ግን ይሄን እጅህን አሳርፈው እና ነው» ብዬ እጁን አንስቼ ወደቦታው እየመለስኩት።

«አውርቼም፣ መንካት ተከልክዬም? እሺ የሆነውን ላውራሽ ግን እጄ የፈለገበት ይረፍ?»

«የፈለገበት ማለት?»

«ሃሃሃሃ አይዞሽ የማወራውንም እንድትሰሚኝ ስለምፈልግ የሚያደነቁርሽ ቦታ አልከውም! ሙች ከአንገትሽ አላልፍም!»

«ልለፍ ብትልስ……….» ብዬ ሳልጨርስ እጁን የነበረበት መልሶ ወሬውን ቀጠለ።

«ለመጀመሪያ ጊዜ ፓኒክ ያደረግኩት ያኔ ነው። በእርግጥ የሄድኩበት ሆስፒታል ያልተስማማው ምግብ በልቶ ነው ነበር ያለኝ። (ሳቅ ነገር አለ።) ግርግሩ ሰክኖ ሆስፒታል መጣች። <ውጪልኝ ላይሽ አልፈልግም!> ብዬ ስጮህባት አባቴ እንኳን መኖሩን ከምንም ሳትቆጥረው <ተመስገን ቢያንስ ማውራት ትችላለህ> ብላ አጠገቤ እንደደረሰች በጥፊ ነው ያጮለችኝ።» ብሎ ፍርስ ብሎ ሳቀ

«እንዴ?» አልኩኝ ሳላስበው።

«ጥፊዋንም የማጣጥምበት መልስም የምሰጥበት ጊዜ ሳትሰጠኝ እሷ ማውራቷን ስትቀጥል አባቴም እንደእኔ ግራ ገብቶት ነው መሰለኝ ዝም አለ። አስተውሎ ላየን እኔ ቺት አድርጌባት እንጂ እሷን ከወንድሜጋ ይዣት አይደለም የሚመስለው። ስታወራ ግልብ ናት አላልኩሽም?

<ምን ልሁን ነው የምትለው? አንድ ሴት የሌላ ወንድ ከንፈር ሳመችብኝ ብለህ መተንፈስ እስኪያቅትህ ትንፈራፈራለህ? ለሴት ብለህ በራስህ ላይ ተስፋ የምትቆርጥ ጅል ነህ? ገና 24 ዓመትህኮ ነው። ከዚህ በኋላ ሌላ አስር ሴት በህይወትህ ውስጥ ልትመጣ እንደምትችል አታውቅም? እድለኛ ካልሆንክ ደግሞ አስሯም ልብህን ሰብራው ልትሄድ ትችላለች። መጀመሪያ ራስህን ውደድ። ከእኔ ጋር ያሳለፍካቸው አመታት ከምንም እና ከማንም በላይ ራስህን መውደድ ካላስተማሩህኮ አከሰርከኝ! ይሄ ስታነበው የከረምከው መፅሃፍ ምንም ብስለት ካልጨመረልህ ለምንድነው ጊዜህን የምታባክነው? ምን አይነቱ እንከፍ ነው በአባቢ ሞት? ምን ይጠበስ? አዎ ወንድምህን ስሜዋለሁ! እ? ለሚቀጥሉት ስድስት ዓመታት ጉልበትህን አቅፈህ ስታለቅስ እና ስትጃጃል ልትኖር ነው? ወይስ አሁንም ደግሞ የሆነ ሰው መጥቶ እስኪያነሳህ pause አድርገህ ልትጠብቅ ነው?>

እኔስ የማወራበት አቅሙም ወሬውም አፌ ላይ ስላልነበረ በዛ ላይ እሷ የጭንቅላቴም የአካሌም አዛዥ ስለነበረች ዝም ብዬ ከመስማት ውጪ ምርጫ አልነበረኝም። የገረመኝ አባቴ ደስ ያለው ነበር የሚመስለው። እሷ ያለችውን ማለት ፈልጎ በሆነ ምክንያት ያቃተው እና እሷ የልቡን የተናገረችለት ነበር የሚመስለው። የሆነው እና ያልሆነው ተምታታብኝ። ሀሳቤን እና እውነቱን አወጫበረችብኝ። ጉንጬን እንደመነካካት ነገር አድርጋኝ። ደግሞ እናታዊ በሆነ ሹክሹክታ

<በህይወትህ የሚፈጠር ነገር ሁሉ ያንተ ጥፋት ወይም ሀላፊነት አይደለም። it’s just life! Mess is just one of life’s package! ያንተ ሀላፊነት ወይም ጥፋት የሚሆነው የተፈጠረው ነገር ላይ ሙጭጭ ብለህ እዬዬ ማለት ወይም አቧራህን አራግፈህ መነሳት የቱን መምረጥህ ነው። የተፈጠረው ነገር የእኔ ምርጫ እንጂ ያንተ ጥፋት አይደለም> ብላ አባቴን አልፈራችውም። ከንፈሬን ስማኝ ተነሳች! ያለችው በወቅቱ ይግባኝ አይግባኝ አላውቅም። ቅድም ከወንድሜጋ ተሳስማ ከነበር አሁን እኔን መሳሟ ልክ ይሁን አይሁን ለማስላትም ፋታ አልሰጠችኝም። ከንፈሯ ሲስመኝ ማሰብም አይሆንልኝም። ዝም ብዬ ፈዝዤ ነበር የማያት ……… ደግሞ ወደ መጀመሪያ ቁጣዋ ተመልሳ

<እእ! ራስህን ለመጥላት እኔን ሰበብ እንድታደርግ አልፈቅድልህም! ራስህን ማንሳትህን ሳላረጋግጥ ከህይወትህ ወደየትም አታርቀኝም! እንዳትለፋ! ነገ በተለመደው ሰዓት እንገናኛለን!> ብላኝ ወጣች። እሺም እንቢም አታስብለኝም! በእኔ ላይ አዛዧ ራሷ እንደሆነች ታውቅ ነበር።» ብሎ ስለእርሷ ተመስጦ ሲያወራ አቁሞ የነበረውን መነካካቱን ቀጠለ።
«አሁንም ድረስ ትወዳታለህ?» አልኩት ሳላስበው። ስለእርሷ ሲያወራ ሳቁ ፣ ፈገግታው ፣ ዓይኖቹ ፣ የድምፁ ለዛ ……. የፊቱ ፀዳል …. በፍቅር የተሞላ ነው።

«አልጠላትም! ህይወቴን በሁለቱም ዋልታ የቀየረች ሴት ናት! ያኔ የነበረኝ ስሜት አሁንም መኖሩን ከሆነ ማወቅ የፈለግሽው። የለኝም! ከዛ በኋላ ብዙ ነገር ተፈጥሯል።»

«እሺ ከዛ በኋላ ለሌላ ሴት እንደዛ ሆነህ ታውቃለህ?»

«እንደዛ ይሁን የተለየ አላውቅም! የዝቅታን መጨረሻ፣ የጨለማን ድቅድቅ ፣ የሞትን ያህል ፍርሃት ዓይነት ጭንቅ ስሜት እንዲሰማኝ አድርጋኝ የምታውቅ ሴት አለች።» አለኝ በዓይኖቹ ሙሉ ዓይኖቼን እያየ

«ደስ የሚል ስሜትኮ አይደለም የነገርከኝ ወይም ፍቅር አይደለም።!» አልኩት የሚላት ሴት እኔ መሆኔን ልቤ እየጠረጠረ። ድምፄ ደግሞ ምናባቱ ያልሞሰሙሰዋል? ቅድም ደህና አልነበር?

«እንዳለመታደል ሆኖ ስሜትሽ ከባለቤቱ ካንቺ ይልቅ በስሜት ለተቆራኘሽው ሰው ሲያጎበድድ ደስ የሚል ስሜት አይደለም።» ድምፁን ቀይሮ ወዲያው «አልራበሽም?» አለ

«እንዴ? አልጨረስክልኝምኮ ከዛስ?»

«አያልቅም trust me! እያረፍን ይሻላል።»

«እሺ በነገታው ሄድክ ወይስ ቀረህ? እሱን ንገረኝ።»

«አልገባሽም! ና ብላኝ ልቀር አልችልም። ራሴንኮ አላዘውም ነበር! Ofcource ሄድኩላት። ያውም ላያት እየናፈቀችኝ!»

«oh my God! የዓመታት ፍቅራችሁንኮ ነው ያረከሰችው? ወንድምህን ነው የሳመችው!»

«እሱን የማስብበት ክፍተት አልሰጠችኝም ነበር በሰዓቱ! ወንድሜን ከሳመችው በኋላ ሳመችኝኮ ……. ልኩ እና ስህተቱን አማታችብኝ። ከክብሬ ከኩራቴ ከወንድነቴ በላይ ከእሷ ጋር ያስተሳሰረኝ ስሜት ያይል ነበር። ሁሌም ራስሽን እስከማታዢው ድረስ ከሰው ጋር ያለሽን ግንኙነት ካጠበቅሽው የራስሽ የሆነ ነገር አይኖርሽም! ራስሽን ጨምሮ!!»

«እሺ ከዛስ?»

« ግልብ ናት አላልኩሽም? እውነቱን ነገረችኝ። < አንተ ህይወትህ የተለመደ እና ደባሪ ነው። እኔ ደግሞ unpredictable የሆነ ቀን እንዲኖረኝ ነው የምፈልገው። አልዋሽህም አፈቅርሃለሁ። ታሳዝነኛለህ። ግን ለእኔ ያ በቂ አይደለም። ወንድምህ ደግሞ ነፃ ነፍስ ያለው አደገኛ ነገር ለመሞከር የማያመነታ ደፋር ሆኖ አገኘሁት እና ሳበኝ። ከፈለግክ እመነኝ ካልፈለግክ ተወው ከመሳሳም ውጪ ምንም ያደረግነው ነገር የለም። እንዴት እንደምነግርህ ጨንቆኝ እንጂ እነግርህ ነበር። የሚጠቅምህ እውነቱን ብነግርህ ስለሆነ እውነቱን ልንገርህ አሁን ላይ ከማፈቅርህ በላይ ስለምታሳዝነኝ ነው አብሬህ ያለሁት። ያ ደግሞ ማናችንንም አይጠቅምም። ማንም ሴት ብትሆን ስለምታፈቅርህ እንጂ ያደረግክላት ነገር ይዟት ወይም ብትለይህ ትጎዳለህ ብላ አዝናልህ አብራህ ከሆነች ልክ አይደለም። ፍቅረኛህ አልሆንም። ለመጨረሻ ዛሬ ከምስምህ ውጪ አልስምህም። በየቀኑ ግን አለሁ። በእኔ ምክንያት አይደለም እንድትወድቅ እንድትወላከፍ አልፈቅድልህም።>

ብላኝ የስንብት ያለችኝን መሳም ስማኝ ተለያየን። እንዳለችውም ከቀን ተቀን ህይወቴ አልጠፋችም። በየቀኑ እስፖርት መስራቴን፣ ስራ መግባቴን ፣ በጠዋት መንቃቴን……… በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ታረጋግጣለች። የመጀመሪያዎቹን ሳምንታት አጠገቤ ሆና ላልነካት መታገል ህመም ስለነበር ባትመጣ ሁሉ ደስ ይለኝ ነበር። እንድከፋ ወይም በሷ መሄድ ራሴን እንድጠላ ጊዜ አልሰጠችኝም። ከወንድሜ ጋር ፍቅረኛሞች ሆነው መቀጠላቸውን አልደበቀችኝም። እኔ እንዳላያቸው ወይም እንዳላገኛቸው ስለምትጠነቀቅ ለመቅናትም እድል አልሰጠችኝም። ትኩረቴን ራሴን መስራት ላይ አደረግኩ። ብዙ ማንበብ እና ማሰላሰል ላይ አተኮርኩ። ለዓመታት ጓደኛዬ ሆነች። ከጊዜ በኋላ ከወንድሜ ጋር ተለያይተው ከሌላ ሰው ጋር ሆነች። አብሮ የፍቅር ጊዜ እንዳሳለፈ ወይም ወንድሜን መርጣ ትታኝ እንደሄደች አልያም በሷ ከአዘቅጥ ወጥቼ በሷው የሚያምን ልቤን እንዳጣሁ ……… ብቻ ብዙ እንደተኳኋነ ሰው ሳይሆን ልብ ለልብ እንደሚተዋወቅ ጓደኛ ብዙ አሳለፍን።»

«ቻልከው? ጓደኛ መሆኑን? »

«መሆኑን ሳይሆን ማስመሰሉን ቻልኩት። እሷ በህይወቷ ደስተኛ ነበረች። ጓደኛ ደግሞ ያን ደስታ አይበርዝም።»

«ከዛስ? እሺ?»

«ከዛ ያለው ብዙ ነው! እያረፍን!» ብሎኝ እጁን ከማጅራቴ አንስቶ ጉንጬን እንደመቆንጠጥ አድርጎ የቆነጠጠበትን እጁን ሳመው። ዘልዬ ተነሳሁ።

………………. አልጨረስንም……….

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል አስራ ስምንት ………. ሜሪ ፈለቀ)

«ታውቂያለሽ የአዕምሮ ክፍላችን እድገት በ25 ዓመታችን እንደሚያበቃ? ከዛም ውስጥ ከ80% በላዩ የሚያድገው እስከ 5 ዓመት አካባቢ ባለው እድሜያችን ነው። ጥናቶች እንደሚያሳዩት የሰው ልጅ ከ25 ዓመቱ በፊት በሚያዳብረው ልምድ ፣እውቀት ፣ ባህል ፣ ሀይማኖት ……. Whatever ነው የሚቀረፀው። ልክ አለመሆኑን ቢያውቅ እንኳን ለመቀየር ብዙ ጥረት እና ጊዜ ይወስድበታል። ከዛ በኋላ ባለን እድሜ ምንም ያህል እውቀት እና ልምድ ብናዳብር እንኳን ሳናውቀው በsubconscious የአዕምሮ ክፍላችን አማካኝነት አስቀድመን ወዳዳበርነው ልምድ እና እውቀታችን ስንሳብ እንገኛለን።» አለኝ። አደጋው ከደረሰበት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የህፃናት ማቆያውን ሊጎበኝ መጥተን ነው። ለህፃናቱን እኔ እየተመላለስኩ መጠየቅ አላቆምኩም ነበር እና አባታቸው አደጋ እንደደረሰበት አስቀድመው ያውቃሉ። ከበውት <እግዜአብሔርን አጊንተኸው ነው የተመለስከው?> ዓይነት የህፃን ጥያቄ ሁሉ ሲጠይቁት ሲመልስላቸው ነው የዋለው።

«እንዳለመታደል ሆኖ አብዛኛው ወላጅ ስታድግ ሁሉንም የምትረሳ ይመስለዋል እንጂ እያንዳንዱ እንቅስቃሴያቸው ልጃቸው ውስጥ ልምድ እና ባህሪ ሆኖ የሚቀር አይመስላቸውም። ድሮ እንዲህ ብላችሁኝ ነበር ስትላቸው። <ቂመኛ ነሽ> ነው የምትባለው። 80%ቱ እስከ 5 ዓመት ነው የሚያድገው ነው ያልከው? ሆ! እስከ 5 ዓመትህማ እንኳን የሚናገሩ የሚያደርጉት ትርጉም ሰጥቶህ የምታስታውሰው ሆ!» አልኩኝ ልጆቹ እየቦረቁ ሲጫወቱ እያየኋቸው

«ምናልባት ድርጊቶቹን ትረሻቸው ይሆናል። ስሜቱ ግን አብሮሽ ያድጋል። ፍርሃት፣ ጭንቀት፣ ደስታ፣ በራስ መተማመን፣ ………. በዙሪያሽ የሚከናወኑ ክንውኖች ያሳደሩብሽ ስሜት እሱ አብሮሽ ያድጋል። »

ከህፃናቱጋ ስንመለስ መኪና ውስጥ «መቼ ነው ታዲያ መውጣት በለመደ እግርህ ማለቴ ዊልቸርህ ወደ ስራ የምትመለሰው?» አልኩት። በዊልቸር ሆኖ ማንም ሰው እንዲያየው አይፈልግም ነበር። የእኔን ቤተሰቦች ጨምሮ ከሀኪሞቹ ውጪ ማንም ሰው እንዲጠይቀውም እንዲያገኘውም አይፈልግም። ዛሬ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው ከሀኪም ቤት ውጪ በፍላጎቱ የወጣው።

«ለዛ እንኳን ዝግጁ አይደለሁም!!» አባባሉ በቅርብ ዝግጁ ለመሆንም ሀሳቡ ያለው አይመስልም። «አሁንማ ከሞላ ጎደል የወረቀቱን ስራ አውቀሽዋል። በየቀኑ ቦታዎቹ ላይ መገኘት ነውኮ የቀረሽ!»

«አንድ ወረቀት አንብቦ ለመፈረም አስሬ ጠይቄህ መቶ ጊዜ አንብቤ ምኑን ለመድኩት? ደግነቱ ሰዎችህ ገራሚዎች ናቸው። ታውቃለህኣ በስራህ እንደማከብርህ? ያንተ ጉብዝና አንድ ነገር ነው። ስራውን ቀጥ አድርገው የሚይዙ ብዙ አንተዎች ማፍራት ሌላ ሌቭል ነው።»

«<ውጤታማ የቢዝነስ ሰው እርሱ ቢኖርም ባይኖርም ስራው ሳይጓደል የሚቀጥልበትን የቢዝነስ ተቋም መገንባት የቻለ ነው> ይል ነበር አባቴ። እሱ ነው ብዙውን ያስተማረኝ። ምናልባት ለእኔ ሊተውልኝ ስላሰበ ይመስለኛል የለፋብኝ።»

«ኦኬ! እያልከኝ ያለኸው የሀብትህ ምንጩ የአባትህ ውርስ ነው?»

«ነበር ማለት ይቀላል!! እየፃፍን ብናወራው የሚሻል መሰለኝ። ከመፅሃፉ አንዱ ምዕራፍ አባቴ ነው መሆን ያለበት። (በምናቡ እየሳለ እንደሆነ እያስታወቀበት።) መፅሃፉ 6 ምዕራፍ ይኖረዋል። የመጀመሪያው ምዕራፍ እናቴ ሁለተኛው ምዕራፍ ማዕረግ ሶስተኛው ምዕራፍ አባቴ አራተኛው ምዕራፍ እኔ አምስተኛውም አንቺ ስድስተኛው ምዕራፍም አንቺ ።»

«ኦኦ ! ያንተ ባዮግራፊ ውስጥ እኔ ሁለቴ ምን አደርጋለሁ? የእናትህ እና የማዕረግ ምዕራፍ እስካሁን የመጣንበት ታሪክ ነው። የአባትህንም በሚቀጥለው ምዕራፍ አገኘዋለሁ እሺ! ያልገባኝ ሁሉም ምዕራፍ ውስጥ አንተ አለህ አይደል? ለምን ለብቻው ሌላ ምዕራፍ? እህህ ረስተህ ከሆነ ሁለት ሚስቶች ነበሩህ!»

«ሶስቱ ምዕራፎች አያጠያይቁም። ከሶስቱ በኋላ ነው ያለማንም ሰንሰለት አዲስ ብቻውን አዲስ ሆኖ የቆመው። ያ ነው ትክክለኛው እኔ ብዬ የምለው የህይወት ምዕራፍ! ፀዲ እና ሰብሊ የዚህኛው ምዕራፍ አካሎች ናቸው። ምዕራፍ አምስት ካንቺ ጋር የነበረኝ የህይወት ምዕራፍ ነው። እኔ የምፅፈው። ያንቺ ገፅ ካልገባበት ግን ታሪኩ ይጎድላል። ስድስተኛውን ምዕራፍ የራስሽን ገፅ አንቺ ትፅፊዋለሽ ማለት ነው። ድራፍቱን ከጨረስን በኋላ ባለሙያ እናማክራለን። ግልፅ ሆንኩ አሁን?»

«አዎን! በስሜት ረገድ ከፋፍለው ብትባል በየትኛው ምዕራፍ ነበር ደስተኛ የነበርከው?» አልኩት ምዕራፍ አምስት ቢለኝ እየተመኘሁ

«በአንፃራዊ ምዕራፍ አራት። ግን የሰው ልጅ 100% ደስተኛ ነኝ የሚልበት ምዕራፍ ይኖረዋል? የደስታ የምትያቸው ቅፅበቶች ይኖሩ ይሆናል እንጂ!»

«በህይወት ውስጥ ልንደርስበት የምንሮጥበት ስኬት ሁሉ ግቡ ደስተኛ መሆን አይደል?»

«ይሆናል። ለእኔ ግን ደስተኛ ሆኖ መኖር ከሚለው ይልቅ ትርጉም ያለው ህይወት ኖሮ ማለፍ የሚለው ብልጫ ይይዝብኛል። ከግለሰብ ደስታ አንፃር ካየሽው አንዳንድ ሰው ሆዱ ካልጎደለ፣ አልጋው ከሞቀ ፣ ለአናቱ መጠለያ ካለው ደስተኛ ነው። አንዳንዱ ደግሞ ሊያሳካው የሚያልመው ህልም ይኖረውና እሱጋ ለመድረስ ሲባዝን ባጅቶ ሲሳካለት ደስተኛ ይሆናል። አንዳንዱ ደግሞ ከራሱ ይልቅ ለሌሎች መኖርን የደስታው ምንጭ አድርጎ ይኖራል። ሁሉም ባሰመሩት የደስታቸው ሰበብ ደስተኞች ናቸው እና ከደስታ አንፃር ካየነው ሁሉም ተሳክቶላቸዋል። ስኬት ውጤቱ ነው ብዬ አላምንም መንገዱ እንጂ። እንደእኔ ያ መንገድ በደስታም ይሁን በሃዘን በመውደቅም ይሁን በመነሳት ትርጉም ያለው ሲሆን ጠዋት የምትነቂበት ምክንያት ከሰጠሽ ስኬት ነው።»

ባያብራራልኝም ምን ማለቱ እንደሆነ አውቃለሁ። 316 ህፃናት የሚያሳድግ ተቋም መመስረት እና ማስተዳደር (ያውም እንደወለዳቸው ልጆች የሚጠነቀቅላቸው እና የጎደላቸውን የሚከታተላቸው ሰው ሆኖ)፣ ባጠቃላይ ለ7293 ሰራተኞች ደሞዝ የሚከፍሉ ድርጅቶች ባለቤት መሆን( ያውም እያንዳንዱ ሰራተኛ የሚያከብረው እና በመልካምነት የሚያወሳው አለቃ ሆኖ )ትርጉም ያለው ህይወት ኖሮ ማለፍ ካልተባለ ምን ሊባል ይችላል?

እቤት ደርሰን ብዙም ሳንቆይ ሁለታችንም ላይብረሪ መሄድ ነበር የፈለግነው። ኮምፒውተሬን ይዤ ምዕራፍ ሶስትን ለመቀጠል ጓግቼ ምንጣፉ ላይ ተዘረፈጥኩ። የሆነኛው ሀሳቤ ውስጥ ይሄን ታሪክ ማወቅ የብዙ ጥያቄዬ መልስ ይመስለኛል። ምዕራፍ አምስትጋ የምንደርስበት ሰዓት እረፍት ነስቶ ያጓጓኛል። የተወሰኑ ገጾች ስለአባቱ ባህሪ እና ከእናቱጋ ስለነበረው ግንኙነት ከፃፍን በኋላ የሚቀጥለው አንቀፅ ላይ ስሜቱ ተቀያየረ።

« አብሬው ስራ ስጀምር መጠነኛ የሲሚንቶ ፋብሪካ ነበር የነበረችው። እየቆየ እየተስፋፋ እና ሌላ ቢዝነሶች ላይ መሰማራት ጀመረ። ቀስ በቀስ ብዙ ሃላፊነቶችን ይጥልብኝ ጀመር እናም ውጤታማ በሆንኩለት ቁጥር በሱስ አቅሏን ላጣች ሰካራም እናቴ ጥሎኝ መሄዱ የሚበላውን ነፍሱን ቀስ በቀስ የሚሽርለት ይመስለኛል። አንድ ቀን እኔና እሱ ባር ቁጭ ብለን ቢራ እየጠጣን <ለምንድነው ጥለሃት የሄድከው?> ብዬ ለዘመናት ልጠይቀው እየፈለግኩ ያልቻልኩበትን ጥያቄ ጠየቅኩት። መልሱ መልስ ያልሆነ ግን ሌላ ጥያቄ የማያስነሳ መልስ ነበር። <ምንም ቢሆን አንተን ለመተው በቂ ምክንያት አይሆንም ነበር።> አለኝ። ያላለኝን ብዙ ነገር ሰማሁለት። <አንተ ላይ ምንም አይነት መጥፎ ስሜት የለኝም! አሁን ትልቅ ሰው ሆኛለሁ። ብዙ ነገሮችን ያኔ በምረዳበት መንገድ አልረዳም! በህይወትህ የምትመርጣቸው ምርጫዎች
ትልቅ ሰውም ብትሆን ሁሌ ልክ ላይሆኑ ይችላሉ። ላንተ ልክ ቢሆኑ እንኳን ሌላ ሰው ትጎዳበታለህ!! አሁን ሳስበው አልከፋብህም! ምንም ይሁን ምክንያትህ በጊዜው ላንተ ልክ ነበር።> አልኩት። ትከሻዬን ቸብ ቸብ እያደረገ አባቴ ለመጀመሪያ ጊዜ እንባ ሲታገለው አየሁት። በእኔ ፊት ላለማልቀስ ትቶኝ ወጣ።

ምክንያቱ በእኔ ምክንያት የሚሰማውን ፀፀት ማጠብ ይሁን ወይም ወንድሜ ለሃላፊነት የማይበቃ እንዝህላል በመሆኑ ሲደመር አብሬው እየሰራሁ ብቃቴን ማስመስከሬ አላውቅም። ለሚስቱ የሚገባትን ድርሻ ከፍሎ በአክስዮን መልክ እና በገንዘብ ለወንድሜም ድርሻውን በገንዘብ ከፍሎ ለእኔ ገንዘብ ሳይሆን የቀረውን ስራውን በሙሉ አስረክቦኝ ነበር የሞተው።» መፃፌን ትቼ ስሜቱን ለማንበብ ቀና ስል ገባው።

«ታሞ ነው የሞተው። ቁጭ ብዬ የሱን ሀዘን እያቦካሁ እየጋገርኩ የምተክዝበት ብዙም ጊዜ አልነበረኝም። ስራው እሱ በህይወት እንደነበረው ሁሉ መቀጠል ነበረበት። ያለእርሱ እንዴት እንደምወጣው የማላውቀውን ሀላፊነት ነበር ያሸከመኝ። ሁለተኛ ፍቅረኛዬም ባትሆን ማዕረግ አጠገቤ ነበረች። በየቀኑ ማለት በሚቻል ደረጃ አጠገቤ ነበረች። ስራዬ ላይ አባቴን በሚገባ ተክቼ በየእለቱ ፍሬያማ እየሆንኩ መጣሁ። አባቴ በህይወት እያለ ብዙም ቦታ የማልሰጠው የሚስቱ ጥላቻ ይሄኔ በይፉ መታየት ጀመረ። ወንድሜም የእኔ ስራ በገንዘብ ቢተመን የሚያወጣውን እኩሌታ መጠን በጥሬ ገንዘብ ያገኘ ቢሆንም በየእለቱ እንደጥፋተኛ ይከሰኝ ነበር። እርግጥ ገንዘቡን ለመበተን አንድ ዓመትም አልፈጀበትም ነበር። ከእነርሱ ጋር መኖሩ ምቾት ስለነሳኝ የራሴን ቤት ገዝቼ ወጣሁ። የሆነ ቀን ከማዕረግ ጋር እራት እየበላን።

<አሁንማ የማይደረስብህ ሰው ሆንክኮ! በሰልክ። መቼ ነው ታዲያ የራስህ የሆነች ሴት ከጎንህ የምትኖረው? አሁን ሁሉ አለህ! በዛ ላይ ማንም ሴት አይታ ምራቋን የምትውጥልህ ወንድ ሆነሃል። ለምንድነው ፍቅረኛ የማይኖርህ?> አለችኝ። ልነግራት አስቤው አልነበረም። ብቻ ግን ብዙ ጊዜ ይሄን አጀንዳ አንስታ ስትጠይቀኝ ስቄና ቀልጄ እንደማልፈው ማለፍ አቃተኝ።

<የሴትም የፍቅርም መለኪያዬኮ አንቺ ነሽ። ሳልሞክር ቀርቼ መሰለሽ? ካንቺ ጋር አይደራረሱም! አንቺን የምትሆን ሴት ከየት ላምጣ? ካለች ጠቁሚኝና ዛሬ ነገ ሳልል ላግባት!> አልኳት።

<ሳትዋሽ አሁንም ለእኔ ስሜት አለህ?> አለችኝ

<ላንቺ ያለኝ ስሜት መቼም ጎድሎ አያውቅም!> አልኳት። በሰዓቱ አላውቅም ምን እንዳሰበች አላውቅም ምን እንዳሰብኩ። ሳመችኝ። ተያይዘን ቀለጥን። እነዚህ ጊዜያት ቀኖቼ ሰኞና እሁድ አይለዩም። ጠዋት እስፖርት ሰራለሁ ፣ በቀን ውስጥ ከ16 ሰዓት በላይ ስራ ነኝ፣ ማዕረግን አገኛታለሁ። ይኸው ነበር። ቀንህ ደባሪ እና የሚገመት ነው ብላ የተወችኝ ሴት ያው የተለመደ እና ተመሳሳይ ቀን መኖሬን ሳላቆም የእሷ ስሜት ለምን ተቀየረ ብዬ አልጠየቅኩም። <አሁን በስያለሁ> ያለችኝን አመንኩ እና የበሰለችው ማዕረግ የሰከነ ህይወት ትፈልግ ይሆናል ብዬ ለራሴ ነገርኩት። ምንስ ቢሆን ደግሞ ማዕረግ የእኔ ትሁንልኝ እንጂ ምክንያቷ ምንም ቢሆን ሂሳብ ልሰራ? ያንን ሂሳብ መስራት የሚችል ጭንቅላት ከኖረኝማ ምኑን እሷ አዘዘችብኝ? ወድያው አንድ ላይ መኖር ጀመርን።»

«እህህህ?» አልኩኝ። ሳቅ አለ። <ያልተነካ ግልግል ያውቃል > አይነት

«ከሷ ውጪ የማውቀው ሴት የለም። እንደእርሷ የማውቀውም ሰው የለም። ቢያንስ በሰዓቱ የማስበው እንደዛ ነበር። ፍቅረኛዬ ሳትሆንም በየቀኑ በህይወቴ ውስጥ አለች። ያቀፋት ክንድ የእኔ ቢሆን ስመኝ ፣ የያዛት እጅ ጣቶች የእኔ ቢሆኑ ሳልም፣ ስለፍቅረኞቿ ባወራችልኝ ቁጥር እነርሱን በሆንኩ ስል ሳላስበው የእኔ ሆነች። የእኔ መሆኗን ላክብር ወይስ ምክንያት ላስላ? አይሆንም ነበር። ለሁለት ዓመታት ሳንጋባ አብረን ኖርን! የሷ ያልነበረ ነገር አልነበረኝም። እኔ ፣ ገንዘቤ፣ ቤቴ ኢቭን ስራ ቦታ አብራኝ እንድትውል ስለፈለግኩ ከምትሰራበት ቦታ ለቅቃ አብራኝ መስራት ጀምራ ነበር። ከሁለት ዓመት በኋላ ልንጋባ ሽርጉድ ስንል ነበር የሰርጉ ወረቀት ተበትኖ ባለበት የእንጀራ እናቴ ሽማግሌዎች ይዛ መጥታ እቤት ይቅርታ ጠየቀችኝ። የማላውቀው ደመነፍሴኮ ነግሮኛል በመርዝ የተጠመቀ ይቅርታ መሆኑን። የተደገሰልኝ ሳይገባኝ ይቅርታ ተባብለን ተቃቀፍን። በሽማግሌዎቹ ፊት <ይሄ ይቅርታ አላማረኝም። ይቅርብኝ። ይለፈኝ> ይባል ነበር? ማለት ግን አምሮኝ ነበር። ወዲያው ከማዕረግ ጋር ስለሰርጉ እቅድ ሲወያዩ ያልገባኝ ስሜት ማጅራቴን እያሳከከኝ ነበር።»

አልጨረስንም........

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል አስራ ዘጠኝ ………. ሜሪ ፈለቀ)

«ማዕረጌን ከጎኔ አድርጌ የተጋበዝነውን እራት ልንታደም ስንሄድ ዘውድ እንደተደፋለት ልዑል አንገቴን ቀና አድርጌ በኩራት ነበር። ምንም የጎደለኝ ነገር አልነበረም። ማዕረጌ ከጎኔ ነበረቻ!! ከሶስት ሳምንት በኋላ እሷ እንደተመኘችው በሷው አባባል <እልልልልልልል በተባለለት ሰርግ> ወዳጅም ጠላትም ምስክር ሆኖ ባደባባይ የእኔ ልትሆን ነዋ!! ዓለም የእኔ ብቻ ነበረች። የሆነኛው ዓለም በጦርነት ንፁሃን እንደማይሞቱ፣ የሆነኛው ሀገር ህፃናት በርሃብ እንደማይሞቱ፣ የሆነኛው የዓለም ክፍል በተፈጥሮ አደጋ እንደማይተራመስ ……… በቃ ከእኔና ከእሷ ውጪ ሌላ ምንም ዓለም እንደሌለ …… ዓለም በእኔና በእሷ ዙሪያ ብቻ እንደምትዞር …… ዓለሜ እሷ ብቻ እንደሆነች ….. እንደዛ እያደረገኝ ነበር። ፈጣሪን ለሰጠኝ ዓለም እየደጋገምኩ አመሰግነው ነበር።

የሚመጣውን ሰርጋችንን እና እርቁን አስመልክቶ የተወሰነ የማውቃቸው ጎረቤቶች እና ዘመዶችን ያካተተ እራት እንጀራ እናቴ ነበረች ያዘጋጀችው። ወንድሜም ያለወትሮው ብሉልኝ ጠጡልኝ ሲል አመሸ። ለደስታችን ውድ የተባሉ መጠጦች ተከፈቱ። እያስመሰልኩ አልነበረም ውስጤ ልቤን ስልብ የሚያደርግ ፍርሃት ሃሳቤን በየመሃሉ ከመስረቁ ውጪ ደስተኛ ነበርኩ። ማዕረግ ወይን እየጠጣች ነበር እና በመሃል ውሃ መጠጣት ፈልጋ ጠረጴዛው ላይ ያለው ውሃ በማለቁ ላመጣላት ራሴው ተነሳሁ። ወደጓዳ እየሄድኩ ድሮ የእኔ ክፍል ከነበረው መኝታ ቤት ድምፅ ያለው ለቅሶ ሰማሁ እና አንኳኩቼ ገባሁ። የጎረቤታችን ልጅ ናት። ከረሜላ የምገዛላት ሚጢጥዬ ልጅ ነበረች።

<ምነው ሉሲ ምን ሆነሽ ነው እዚህ ተደብቀሽ የምታለቅሺው?> ብዬ ላባብላት አጠገቧ ተቀመጥኩ። ከእናቷ ጋር በወንድ ምክንያት ተጣልታ እንደሆነ ስትነግረኝ በጣም ገርሞኝ።

<ስንት ዓመትሽ ነው?> አልኳት።

<14> አለችኝ። የእውነቷን እያለቀሰች ስለነበር የምላት ግራ ገብቶኝ አቅፌ እያባበልኳት እናቷ ለእርሷ ብላ እንደሆነ እና በዚህ እድሜዋ ወንድ እንዳያታልላት ስመክራት የሆነ ደቂቃ ቆየሁ።

ከዚህ በኋላ የተፈጠረው ዛሬም ድረስ የሆነ መጥፎ ቅዠት ነው የሚመስለኝ። ኮሪደሩ ላይ የእንጀራ እናቴ የሰራተኛዋን ስም እየጠራች ስሰማ እና ሉሲ እሪሪሪሪ ብላ ስትጮህ እኩል ነበር። እየሆነ ያለውን የምረዳበት ምንም ሰከንድ አልነበረም። የእንጀራ እናቴ በሩን በርግዳ ስትገባ ሉሲ እኔ የሆነ ነገር ያደረግኳት ዓይነት እየተንዘፈዘፈች ሄዳ ጉያዋ ተወሸቀች። እሪሪሪሪ እያለች ትጮሃለች። ከሳሎን ሁሉም ሰው እየተሰባበረ ለወሬ ሲመጣ እንጀራ እናቴ ትደነፋለች

<ምን አይነቱ አውሬ ብትሆን ነው ትናንት አይንህ እያየ ያሳደግካትን ህፃን ለማባለግ ሰውነትህ እሺ ያለህ! ቱ!> የቀረው አሟሟቂ ያማትባል፣ በስመአብ ይላል።

<ሉሲ? እንዴ ንገሪያቸው እንጂ ምን እንደተፈጠረ? በስመአብ እንዴት እንደዛ ያደርጋል ብላችሁ ታስባላችሁ?> ብዬ ወደፊት ከመራመዴ ሉሴ ድራማዋን ከወነችው። ሸሽታ እንጀራ እናቴን እየተጣበቀች እና እንባ እና ሳጓን እየደባለቀች
< እንዳልጮህ አፌን አፍኖኝ! ህህ ህህ ወይኔ እናቴ! > የሰዎቹ ፊት ዱላ ሆኖ የሚጋረፍ ቢሆን የሚታይ የሰውነት አካል እስከማይኖረኝ ሰንበር በሰንበር እሆን ነበር። የማዕረግ እይታ ግን ከሁሉም የከፋ ነበር። <ከአውሬ ጋር ነበር የምኖረው?> አይነት እይታ!

<ኸረ ባካችሁ ሰዎች እኔ ምንም አላደረግኩም! ውሸቷን ነው!> ብል ማን ይስማኝ። ወንድሜ

<መጠጡንኮ በላይ በላዩ ስትለው ይህቺን ዓመልህን ስለማውቅ ቀስ በል ብዬህ ነበር።> ብሎ በልግጫ እሳቱ ላይ ጋዝ አርከፈከፈ። በአካባቢው ያልነበረችው የልጅቷ እናት ግርግሩን ከመቀላቀሏ ፖሊስ ካልተጠራልኝ ማንም ከዚህ ንቅንቅ አይልም ብላ ቀወጠችው። ሁሉም ነገር የሆነ በድካም ካለፈ ቀን በኋላ ያለ ቅዠት ነበር የሚመስለኝ።

ፖሊስ ጣቢያ ሄጄ ሳድርም የማስብ የነበረው ማዕረግ ልታየኝ ስትመጣ የሆነውን ሁሉ እንዴት እንደማስረዳት እንጂ የተከሰስኩበትን ምክንያት እንኳን በውል አላሰላሰልኩትም <በስካር መንፈስ የ14 ዓመት ህፃን በመድፈር!> ከአፋቸው ስሰማው ራሱ አንዳች መዘግነን ዘገነነኝ። ከዚህ ሁሉ በላይ ግን ስንት ዓመት ለምታውቀኝ ማዕረግ ማስረዳት ህመምም መዘግነንም ነበረው።

<አታውቂኝም ማለት ነው? ምን ላገኝ ብዬ ነው ህፃን የምደፍረው? እንኳን አስገድጄ ልደፍር ደስታሽ ከስሜቴ ጋር ካልተመጣጠነ ሰውነቴ እንደማይታዘዝልኝ አታውቂም?> አልኳት ልቤ እንክትክት ሲል እየታወቀኝ

<አላውቅም! ማንን ማመን እንዳለብኝ አላውቅም! እሷስ ምን ልታገኝ ትዋሻለች? እንደዛ ሰውነቷ እየተርገፈገፈ ውሸቷን ነው ብዬ ማመን ከበደኝ። አንተን ስለማውቅህ ደግሞ እውነቷን ነው ብዬ ማመን ጨነቀኝ። ጠጥተህ ነበርኮ! አላውቅም ምን ማሰብ እንዳለብኝ!> አለችኝ

<ልብሽን ስሚው! ልብሽ አዲስ ይሄን ያደርጋል ብሎ ያምናል?> አልኳት ድክም ብሎኝ። ያላደረግኩትን ነገር አለማድረጌን ለማሳመን የምሄደው እርቀት ጭራሽ ለጥፋቴ ማስተባበያ እየሰጠሁ ዓይነት ስሜት እንዲሰማኝ እያደረገኝ።

<እሺ ምንድነው የምሆነው? ከተፈረደብህ ምንድነው የሚውጠኝ?> ስትለኝ ለመጀመሪያ ጊዜ የፍርድ ሂደት ላይ መሆኔን አስታወሰኝ።

<እንዴ በፍፁም አይሆንም! ባላደረግኩት ነገር ሊፈረድብኝ አይችልም!>

<አለማድረግህን በምንድነው የምታረጋግጠው? የህክምና ማስረጃዋ መደፈሯን መስክሯል። በቦታው የነበሩ ሰዎች የእንጀራ እናትህን ጨምሮ ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል። ይሄን የሚሽር ምን ማስረጃ ታቀርባለህ?>

<እንዴ? ኸረ በእግዚአብሄር?> ከማለት ውጪ ማለት የቻልኩት የለም።

<ጎበዝ የተባለ ጠበቃ ቀጥሪያለሁ። አላውቅም ሌላ ምን ማድረግ እንደምችል። ከሰዓት መጥቶ ያገኝሃል> ብላ አባብላኝ ስትሄድ ልቤ ወደቀ። እሷ በሙሉ ልቧ ካላመነችኝ ማንንም ማሳመን እንደማልችል ገባኝ። ወደ ፈጣሪ ደጋግሜ አጉተመተምኩ። ምን ብዬም እንደምፀልይ ግራ ገባኝ። <ሌላ ሰው ባያውቅ አንተ ንፅህናዬን ታውቃለህ አይደል እንዴ? በውሸት ሲመሳጠሩብኝ ዝም ብለህ አታይምኣ? አንተ ሁሌም የእውነት ፈራጅ ነህ! በሰው ሳይሆን ባንተ እተማመናለሁ!> አልኩት። ከዚህ በኋላ የነበረው እልም ያለ አስፈሪ ቅዠት ነበር። ከእርሷ ውጪ የማምነውም የምቀርበውም ሰው ስላልነበረ የፍርድ ሂደቱ የሚወስደውን ጊዜ ስላላወቅን ስራዎቹን ውክልና ለእርሷ ሰጠኋት።

<ጥሪ የደረሳቸውን ሰዎች ሰርጉ መሰረዙን ለማሳወቅ በተቻለኝ መጠን ለማዳረስ ሞክሪያለሁ።> ያለችኝ ቀን የእርሷን ህይወት ስላበላሸሁ ራሴን ጠላሁት። ፊቷ ላይ የነበረው መሰበር እኔን አደቀቀኝ። የሆነውን ሳስበው ራስምታት ይለቅብኛል።> » ብሎኝ ራሱን እንዳመመው ነገር የግንባሩን ጠርዞች ይነካካ ጀመር።

«ታርፋለህ? ወይ በቃ ነገ እንቀጥል?» አልኩት ስለእውነቱ ግራ ገብቶኝ እንጂ ልለው የፈለግኩትስ <ምን ጉድ ነው ያሳለፍከው? አንድ ሰው ይሄን ሁሉ መከራ አልፎ እንዴት ይቆማል? ኸረ ይሄ ሁሉስ የአንድ ሰው ህይወት ነው?> ነበር።

«ኖ! እዚህ ምዕራፍ ላይ መመለስ አልፈልግም! ጨርሼው መገላገል ነው የምፈልገው! ይልቅ ልቀመጥ! አስቀምጪኝ !» አለኝ። ሶፋው ላይ እንዲቀመጥ እያገዝኩት የእውነቴን አሳዘነኝ። በእያንዳንዱ ትናንቱ ውስጥ የበደለኝን በደል እየሸረፈው እየሸረፈው ከራሴ ህመም በላይ ለእርሱ መታመም ጀምሬያለሁ።
«በናትህ አትከልክለኝ ልቀፍህ?» አልኩት። አይዞህ መባል ሞቱ ነውኮ አውቃለሁ! ሲታዘንለት የተሸነፈ ነው የሚመስለው ያንንም አውቃለሁ። ግን በቃ አቅፌው ዝም ማለት ፈለግኩ። ራሱ አቀፈኝ! በሱ ህመም እኔ ተባበልኩ። ደረቱ ላይ እንዳቀፈኝ ብዙ የማፅናኛ ቃል ብለው ብዬ አስባለሁ። እንደማይወደው ስለማውቅ ዝም ብዬ ለደቂቃዎች ከታቀፍኩ በኋላ ወደ ፅሁፋችን ተመለስን።

«የትኛው ይበልጥ እንደሰበረኝ አላውቅም። ባላደረግኩት ነገር መከሰሴ ወይስ ምስክሮቹ የራሴው ቤተሰቦች መሆናቸው? ምንስ በደል ብበድላቸው ነው በዚህ መጠን ሊከፉብኝ የቻሉት? እኔ የማውቀው ወንድሜንም ሆነ እንጀራ እናቴን የበደልኩት ትዝ አይለኝም። እነሱ ግን ፍርድ ቤት ቆመው ምለው በውሸት ሲመሰክሩብኝ ዓይናቸው ውስጥ የነበረው የበቀል እርካታ በምንም ልኬት የማልገልፀው ነበር። 7 ዓመት! 7 ዓመት ተፈረደብኝ! ከእውነት ጎን የሚቆመው አምላክ ከእነሱ ጎን ቆመ!»

«እመቤቴ ድረሽ!» አልኩኝ መጻፉን ትቼ

«አዎ! 7 ዓመት የሚለውን ዳኛው ሲናገር ዞሬ ማዕረግን አየኋት። አንጀቷን በአንድ እጇ ደግፋ ድምፁ የማይሰማ ለቅሶ ስታለቅስ አየኋት። እጅ የሰጠ ለቅሶ ፣ ተስፋ የቆረጠ ለቅሶ ፣ ዛሬም ድረስ ጭንቅላቴ ውስጥ ያለ ምስሏ ነው። ለመጨረሻ ጊዜ የተወችልኝ ምስሏ ነው። የፍርድቤቱ የእንጨት ወንበር ላይ ወደኋላ ተደግፋ በቀኝ እጇ የተጣበቀ አንጀቷን ደግፉ ስቅስቅ ብላ የማይሰማ ለቅሷ የምታለቅሰዋ ማዕረግ!! ለመጨረሻ ጊዜ ያየኋት ያኔ ነው። የእስር ቤት የመጀመሪያዎቹ ሳምንታት ከዛሬ ነገ ማዕረግን መጥታ አያታለሁ በሚሉ ናፍቆቶች የተሞላ ስለነበር የእስር ቤቱን ድብርት ፣ አለመመቸት ፣ ምግብ አለመጣፈጥ አላስተዋልኩትም። ብደውል ባስደውል ስልኳ ዝግ ነው። ወር አለፈ። ስራ ቦታ መታሰሬን ማንም እንዳያውቅ ፈልጌ ስለነበር ለማንም እኔ በበኩሌ ምንም አላልኩም! የሷን ደህና መሆን አለማወቅ ሊያሳብደኝ ሲሆን ለእንድርያስ ደወልኩለት። ሊያየኝ እስር ቤት መጥቶ ማዕረግ ስራ ቦታ ብቅ እንደምትል ግን ድባቴ ውስጥ እንደሆነች ነገረኝ። መኖሯ አፅናናኝ። ልታየኝ አለመፈለጓ ደግሞ አመመኝ። ሁለት ወር ሶስት ወር …… ሲለቃት ትመጣልኛለች እንጂ የእኔ ማዕረግ አትተወኝም ብዬ ጠበቅኳት። ቀኑ በጨመረ ቁጥር መጠበቄ እየቀነሰ ፣ ተስፋዬ እየሞተ ፣ በምትኩ ውስጤ ጨለማ እየነገሰ መጣ። ወራት ነጎዱ…….. ውስጤ ፀጥ እያለ፣ ውስን ድምጾች ብቻ ውስጤ እየቀሩ፣ የማዕረግን የመጨረሻ ምስል ጨምሮ በጣም ውስን ምስሎች ብቻ ጭንቅላቴ ውስጥ እየቀረ ከቀን ወደ ቀን እየሞትኩ እንደሆነ ይሰማኝ ጀመር።

ሁለት ድፍን አመት! ልታየኝ አልመጣችም። ስራ ቦታ በጣም አክቲቭ ሆና እየሰራች እንደሆነ ሰማሁ። ደጋግሜ ደወልኩ። ደጋግሜ ደብዳቤ ላኩላት። ልታየኝ አልፈለገችም። በሁለተኛው ዓመት ጎብኚ መጥቶልሃል ተብዬ ስጠራ ልቤ ዘላ ምላሴን ነክታው ነበር የተመለሰችው። በመጨረሻም ልታየኝ መጣች ብዬ!! በምትኩ በቁሜ ልትጨርሰኝ የተከሰተችው የእንጀራ እናቴ ነበረች። እንደወዳጅ ሰላም ካለችኝ በኋላ
<ከሌላ ሰው ከምትሰማው ብዬ ነው ራሴው ልነግርህ የመጣሁት> ብላ የሰርግ ቴንኪው ካርድ አቀበለችኝ። ያየሁትን ከማምን የራሴን ጤንነት አለማመን ተሻለኝ እናም ሰሞኑን ጭንቅላቴ ልክ አይደለም አይደል? የእኔ ማሰቢያ ተናግቶ ነው እንጂ የእኔ ማዕረግ ሰርጋችን በተሰረዘ በሁለት ዓመቱ አትሞሸርም! ያውም ደግሞ መቀመቅ ሊከተኝ ካሴረብኝ ወንድሜ ጋር! በፍፁም!!

<እናትህ ህይወቴን ቀምታኝ እሷ ስትስቅ እኔ ባዶ ቤቴን እና ልጄን ታቅፌ እንባዬን ቁርስ እራት ስበላ ለዓመታት ኖሬያለሁ። እጅ ሳልሰጥ ነው አባትህን የመለስኩት። አንተ ደግሞ በተራህ የልጄን ህይወት ስትቀማው ዝም ብዬ የማይህ ነበር የመሰለህ? ሙትቻ ! እያየሁህ ከሞት ተነስተህ ልትነግስ?> ያለችኝን ሰምቻታለሁ። ምን ያህል እንደምትጠላኝ ድምፅዋም ፊቷም ላይ ይሰማል ይታያል። እግሬን እየጎተትኩ ማዕረግ ከወንድሜ ጉያ በነጭ ቬሎ አጊጣ ያለችበትን ካርድ በእጄ ይዤ ከኋላዬ ትቻት ሄድኩ። የሚቀጥለው ሲዖል ነው። ራሴን የምስት ይመስለኛል ግን አውቃለሁ። ጭንቅላቴን ድቅድቅ ጨለማ ተቆጣጥሮታል። የእናቴ ሬሳ ሽታ እንደገና አፍንጫዬ ላይ ነገሰ። ሁለት ድምፆች ብቻ ጭንቅላቴ ውስጥ ይሰሙኛል።

<አዲስ አንተ ካልሞከርክ እኔ ላግዝህ አልችልም! መናገር ከፈለግክ ታገል። አንተ ብቻ ነህ ራስህን ልታድነው የምትችለው> የሚለው ያኔ ከእናቴ ሞት በኋላ መናገር ሲያቅተኝ ያከመኝ ዶክተር ንግግር እና

<አንተ ደግሞ በተራህ የልጄን ህይወት ስትቀማው ዝም ብዬ የማይህ ነበር የመሰለህ?> የሚለው የእንጀራ እናቴ ድምፅ።

ከጨለማው ሌላ ጭንቅላቴ ውስጥ ያለው ያ ከእጄ የማይጠፋው የወንድሜ እና የማዕረግ ምስል ነው። አዕምሮዬ የእኔ ሳይሆን ቆይቶ ስነቃ ይታወቀኛል። እታገላለሁ። ግን አቅም ያንሰኛል። እንዳለፈው ጊዜ ዲዳ እንዳልሆንኩ አውቃለሁ ግን ምንም ቃል ታዝዞ ከአፌ አይወጣልኝም። የሆነ የማላውቀው ሃይል አስፈሪ ጨለማ ውስጥ የጣለኝ ይመስለኛል። ፍርሃቴ ሰውነቴን ያርደዋል። ቀኑ ቅዳሜ ይሁን ሰኞ፣ ወሩ ሀምሌ ይሁን ጥር ቀኑ ጠዋት ይሁን ውድቅት ለሊት አላውቅም። የሆነ ቀን ጭንቅላቴ ምልስ ሲልልኝ ልብሴ ላይ ሽንቴን ሸንቻለሁ። የዛን ቀን የአዕምሮ ህክምና ሆስፒታል ተወሰድኩ። እጅ ላለመስጠት እታገላለሁኮ ግን ከራሴ ጨለማጋ እንዴት እንደምዋጋ አላውቅበትም። ጨለማው ይዞኝ ሲሄድ ይታወቀኛል። ከምስሎቼ እና ከድምፆቼ ጋር በሚያርድ ፍርሃት ውስጥ ሲነክረኝ ይታወቀኛል። እንዴት ልውጣ? መንገዱ በየት ነው? መሞት እፈልግ እና አስበዋለሁኮ! ከዚህ ስቃይ ሞት ይሻላል እላለሁ። ግን አይሆንልኝም! »

እጆቼ ይፅፋሉ እንጂ እንባ እና ንፍጤ እየተቀላቀለብኝ እየተነፋረቅኩ ነው። እሱም ተመልሶ ይሄን ክፍል ላለማሰብ በሚመስል ቶሎ ለመገላገል ዓይነት እያወራኝ ፊቱ ግን አሁን ከሚያወራልኝ ጨለማ ጋር ግብ ግብ የገጠመ ይመስል በስቃይ ተሸፍኗል።

«ሁሉን ያያል ይሰማል የተባለው ፈጣሪ ሊያድነኝ አልመጣም! ማዕረግ ከሞት ልትቀሰቅሰኝ አልመጣችም! አባቴ ሊታደገኝ የለም! እኔ እና እኔ ብቻ! ቀስ በቀስ የሰላሜ ሰዓት እየረዘመ፣ የትግሉ ሰዓት እየቀነሰ መጣ። እዚህጋ ሌላ ድምፅ ጭንቅላቴ ውስጥ ተጨመረ ድምፁ የአባቴ ነው ቃላቶቹ ግን እኔ የማስባቸው ናቸው። <ይሄን ሁሉ አልፈህማ እዚህጋ እጅ አትሰጥም!> የሚለኝ! በመሃል ረጭ ሲልልኝ <ብቻ አንዴ ከዚህ ስቃይ ልውጣ እንጂ መቼም እዚህ ድቅድቅ ጨለማ ውስጥ አልመለስም> እላለሁ። ወደ ራሴ ስመለስ 11 ወር እንዳለፈኝ አወቅኩ። ሌላ ሰው ሆንኩ። ፍጹም ሌላ ሰው ……. ከዚህ በኋላ ያለውን አዲስ እወደዋለሁ። ማንም ይወደዋል። ምክንያቱም ብዙ ዋጋ ተከፍሎበታል።» ብሎኝ በረዥሙ የመገላገል ትንፋሽ ተነፈሰ። እየተነፋረቅኩ እንደሆነ አሁን ነው ያየኝ። እንደመደንገጥ ብሎ እቅፉ ውስጥ እንድገባ ዘረጋልኝ። ጭራሽ ብሶብኝ አረፍኩት።

«ለምን አልነገርከኝም? ምንአለ ነግረኸኝ ቢሆን?»

«ከዛስ? ነግሬሽ ቢሆን ልታስተካክዪኝ ትሞክሪ ነበር። ዳሜጅ ሆኗል ብለሽ ያሰብሽውን ፓርቴን ልታበጃጂ ትደክሚ ነበር። ከዛ ለማጠፋው ጥፋት ሁሉ እንደሰው በጥፋቴ ሳይሆን ባለፈው ቁስሌ እየዳነሽ ይቅር ትዪኝ ነበር። አይደለም?»

«እሺ ከዚህ በኋላ አስቸጋሪ ወቅት የለኝም በለኝ?»

«አልነበረኝም! አንቺ እስከመጣሽበት የህይወቴ ምዕራፍ!»
«እኔኮ ግን ለትናንት ስቃይህ ያበረከትኩት አንዳችም ነገር አልነበረም። በሙሉ ልቤ ከማፍቀር ውጪ የበደልኩህ አልነበረም። የእናትህን፣ የማዕረግን ፣ የወንድምህን፣ የእንጀራ እናትህን …… ሁሉንም እኔን አስከፈልከኝ። ነግረኸኝ ቢሆን ፍቅሬ አይጎልም እንደውም ይበልጥ አፈቅርህ ነበር።»

«አልገባሽም! እዛ ጨለማ ውስጥ ራሴን ከምመልስ ምንም አደርግ ነበር።» ላለፉት ዓመታት ያላለቀስኩት እንባዬ ሁሉ ይግተለተል ጀመር። ስቃዩ የሱ ሳይሆን የእኔ ይመስል ያባብለኝ ያዘ።

«እሺ ከዛስ?»

«ከዛማ አዲስን ከተበታተነበት እፍ እፍ ብዬ አራግፌ ገጣጥሜ አቆምኩት። እስር ቤት ሶስት ዓመት ከሁለት ወር እንደታሰርኩ በምህረት ተፈታሁ እና ከተበዳይ ቤተሰብጋ እርቅ መፈፀም ግዴታ ስለነበረብኝ ያን አደረግኩ። ወንድሜ እና ማዕረግ ድርጅቶቹን እንዳልሆነ እንዳልሆነ አድርገው በእዳ እና በቋፍ ሁለቱ ጭራሽ ተሽጠው። የቀረኝ እዳ እና ማሽኖች ብቻ ነበሩ።እነርሱ ከሀገር መውጣታቸውን ሰማሁ። ቤቴ ብቻ በእኔ ስም ስለነበር ተከራይቶ ኪራዩ ለእንጀራ እናቴ ገቢ እየሆነ ጠበቀኝ። ቤቴን ሸጬ እዳዎቹን ከፋፍዬ ሀ ብዬ ቢዝነሱን ጀመርኩ። አዲስ አዲስን ሰራሁ። ትናንት እና ትናንት ላይ የነበሩኝን ሰዎች ሁሉ ከማህደሬ ሰረዝኩ። ትንሽ ቢያታግለኝም እንደገና ወደመስመር ገባሁ። እሺ አሁን የምታለቅሺው ለምንድነው?»

«እኔእንጃ! አልወጣልኝማ!»

.......አልጨረስንም…….

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል ሀያ ……….)

«ትናንትህ ላይ በበደሉህ ሰዎች ነው ዓለምን በሙሉ እየዳኘህ ያለኸውኮ! በዙሪያህ ያሉ ሰዎች በሙሉ እንደእነሱ ናቸው ማለት አይደለም! በተቃራኒው የሆኑ ሰዎች አሉ። አንተ ያደረግከው ለማንም ምንም እድል አለመስጠትን ነው።» ከምሳ በኋላ ፀሃይ ቡና አፍልታ ሳሎን ቡናችንን እየጠጣን ነው ስላለፉት ውሳኔዎቹ የጀመርነውን የሀሳብ ልውውጥ የቀጠልነው።

«ካለፈው ውድቀትሽ ወይም ስህተትሽ መማር ማለት ታዲያ ምንድነው? ትናንቴን አልደግምም ማለት አይደል? ያለፈውን ስህተትሽን አለመድገም አይደል? ያለፈው ስህተቴ አለልክ ሰዎችን ማመኔ ፣ ያለገደብ ራሴን እስኪያሳጣኝ ከሰው ጋር መቆራኘቴ አይደል? ያንን ነው ያስወገድኩት!! የሰዎችን ስሜት ለውጥ፣ ክፋት ወይም ቅንነት ልትቆጣጠሪ አትችዪም። ልትቆጣጠሪ የምትችዪው የራስሽን ስሜት እና ራስሽን ብቻ ነው። ሰዎች ለምን እንደእኔ አልተሰማቸውም ማለት አትችዪም። በጠበቅሻቸው ልክ ሳይገኙልሽ ሲቀሩ እንዴት ማለት አትችዪም! ምክንያቱም እንዳንቺ ጥበቃ ሳይሆን እንደራሳቸው ስሜት እና እውቀት ነው ህይወታቸውን የሚመሩት። እነሱን መቀየር አትችዪም! አንቺ ስለእነሱ ያለሽን መጠበቅ እና ቅርበት ግን መወሰን ትችያለሽ!! ከማንኛውም የሰው ፍጡር ምንም ባለመጠበቅ ውስጥ እና ባለመተሳሰር ውስጥ ራሴን አትርፊያለሁ።»

«በፍፁም ከማንም ምንም አልጠብቅም ወይም በምንም ማንንም አልደገፍም አልያም ከማንም ጋር በስሜት አልቆራኝም ማለት አትችልም። ያንተም ህይወት ከዛ እጅግ የራቀ ነው። ለምሳሌ ከልጆችህ ጋር ያለህን ቁርኝት እየው! ለእነርሱ የምትሆነውን መሆን ለማንምና ለምንም ስትሆን አይቼህ አላውቅም! ሌላ ምሳሌ እንጥቀስ ቢያንስ በትንሹ ከሰራተኞችህ ጥንቅቅ ያለ ስራ ትጠብቃለህ! አንተ ባትኖር እነርሱ እንደማይኖሩት ሁላ እነርሱ ባይኖሩም ያንተ ቢዝነስ የለም!»

«የሆነ ጊዜ ነግሬሻለሁ መሰለኝ። በህይወት ውስጥ ለደስተኛነት ከመኖር ትርጉም ያለው ህይወት መኖር እንደመረጥኩ። ከዛ የጨለማ ውድቀት በኋላ ስነሳ ባለፈው አንቺ እንዳልሽው ደስተኛ ህይወት ለመኖር ዳከርኩ። እኔ ባለፍኩበት ዓይነት መንገድ ላለፈ ሰው ደስታ ከፍርሃት ጋር የተለወሰ ነው። እዛ የዝቅታ ወለል ላይ ደርሰሽ ካላየሽው ምን እንደምል ብዙም ላይገባሽ ይችላል። የሆኑ የሆኑ ጠርዞች አሉ ፍራሃትሽ የሚፈጥረውን ሀሳብሽን እና እውነታውን መለየት የሚያስቸግርሽ ጠርዝ። እሱ ጠርዝ ላይ መቆም አለብሽ ትግል አይጠቅምሽም። ምክንያቱም ያቺን ጠርዝ ካለፍሽ አለቀ። አዲሱን አዲስ መስራት ስጀምር ማን መሆን እንደምፈልግ እና ምን ዓይነት ህይወት መምራት እንዳለብኝ የራሴን የህይወት መመሪያና መርህ መቅረፅ ነበረብኝ። የማንንም ህይወት መኮረጅ አያዋጣኝም ነበር ምክንያቱም ማንም እኔ ያለፍኩበትን መንገድ አላለፈም። ለውጡ ይሄ ነው ያለማንም እርዳታ ሲሆን ራስሽን የሰራሽው ምርጫ አለሽ ምንና ማን መሆን እንደምትፈልጊ። እናም ደስታን ውስጤ ስፈልገው ከፍርሃቴ ጋር የተለወሰ ነበር እና በምትኩ የምኖርለት እና ትርጉም የሚሰጠኝ ዓላማ ላይ ራሴን ቢዚ ማድረግን ተማርኩ። ስለዚህ ልጆቼን እና ስራን እንደ ዓላማ ነው የምወስዳቸው።»

«በዚህ መጠን ትኩረት እና ጊዜ ለምትሰጠው ዓላማ ታዲያ ምንም ዓይነት የስሜት ቁርኝት የለኝም ማለት ትችላለህ?»

«ራሴን አያሳጣኝ እንጂ ትኩረቴን የማሳርፍበት ዓይነት ቁርኝት አይጎረብጠኝም። ጥያቄው የሚመጣው እኔን ጥያቄ ውስጥ ካስገባ ነው። ከራሴ እና ከምንም ወይም ከማንም መምረጥ ካለብኝ ራሴን ነው የምመርጠው። እውነቱንስ እናውራ ከተባለ ማንስ ራሱን አይደል የሚመርጠው?»

«እንዴ በፍፁም ራስህን የምትሰጥለት ሰው አለ። ኤጭ በምን ላስረዳህ ፍቅርን ታጣጥልብኛለህ እንጂ (ይሁን ቀጥዪ ዓይነት በእጁ እና በጭንቅላቱ ንቅናቄ ምልክት አሳየኝ።) እሺ! አይደለም ፍላጎትህንና ስሜትህን ነፍስህን ብትሰጠው worth የሚያደርግ የፍቅር ልክ አለ» ስለው ከት ብሎ ሳቀ

«መቼም ፍቅር እስከመቃብርን ወይም ሮምዮ እና ጁሌትን አትጠቅሺልኝም! ለስሜት ትስስር ብለሽ ሞትን ከመረጥሽ ቂል ነሽ ነው የምልሽ!! እኔና አንቺ እውነቱን አይደል የምናወራው? እስከሞት ልወድ የምችለው ራሴን ብቻ ነው!!» ብሎኝ ዊልቸሩን አንቀሳቀሰ። ስሜቱ ጥሩ ስላልነበር ለሁለት ቀን መጻፋችንን አቁመን ነበር።

«ለምን ዛሬ ቦታ አንቀይርም? እዚሁ እንፃፍ ወይም ውጪ!» አልኩት
«ውጪ አሪፍ!» አለኝ። ለፀሃይ ሳሩ ላይ ፍራሽ እንድታነጥፍ ነግሬያት ኮምፒውተሬን ላመጣ ወደ ላይብረሪ ሄድኩ። ፍራሹ የተነጠፈበት ዛፍ ስር የጥላው ቅዝቃዜ እና የቅጠሉ ቀዝቃዛ አየር እያጫወተን እሱ ትራስ ደራርቦ ተጋድሞ እኔ ቁጭ ብዬ መፃፍ ቀጠልን።

«ምዕራፍ አምስት!» ብሎ ሊቀጥል ሲል ሳላውቀው ጮህኩ።
«እንዴ? አራትን በአንድ ገፅ ልታልፈው አትችልም! ብዙ ያልተመለሱ ጥያቄዎች አሉኮ! ከዛ ሁሉ ድቅድቅ ጨለማ በኃላ አዲስን በቃ ሰራሁት ብለህ አንባቢን ልታሳምን አትችልም። ኸረ ደግሞ ፀዲን እና ሰብለን እዚህ ምዕራፍ ውስጥ ልናነባቸው አይገባም? ከቤተሰብህ ጋር እና ከማዕረግ ጋር የነበረህ ታሪክስ እንደዛው በእንጥልጥል ይዘጋል? »
«ኸረ ቆይ እሺ (ከት ብሎ እየሳቀ) የት ሄድኩብሽ አለሁ አይደል?» ብሎ ቀጠለ።

« ለተወሰነ ጊዜ የመረጥኩት መንገድ ራሴን በስራ ቢዚ ማድረግ ነበር። ጎን ለጎን ሙያዊ ድጋፍ ያስፈልገኝ ስለነበር ሳይካትሪስት ጋር ክትትል ማድረግ ነበረብኝ። በትክክል የሚጠቅመኝን ህክምና የሚያደርግልኝ ሳይካትሪስት ማግኘት እጅግ ከባዱ ነበር። አንዳንዶቹ ዝም ብሎ መስማት ይመስላቸዋል መሰለኝ ሙያው ማስታወሻ እና እስክሪብቶ ይዘው ያስለፈልፉኛል። አንዳንዶቹ የሚሰጡሽ ምክር ደግሞ ራሳቸው ምክር እንደሚያስፈልጋቸው ያሳያል። የብዙ ሳይካትሪስት ቢሮ እና ፊት ከጎበኘሁ በኋላ በትክክል ሙያውን የሚያውቅ ፣ ለእኔ የሚያስፈልገኝ ህክምና የቱ እንደሆነ የገባው ዶክተር አገኘሁ። ከጊዜ ወደጊዜ ለውጡን የምገነዘበው ዓይነት ነበር። ከህክምናው ጎን ለጎን ራሴን በማንበብ ጠመድኩ። ንባብ ስልሽ እገሌ የሚባለው ደራሲ እንዲህ ብሎ ፅፏል ወይም እንትን መፅሃፍ ላይ ያለው ገፀባህሪ ምናምን እያሉ ጥቅስ ለማጣቀስ የሚረዳ ማንበብ ሳይሆን ልኖረው የምችለው እና ከራሴ ጋር የማዋህደው እውቀት ፍለጋ ነበር የማነበው። ለምሳሌ ሰዎች ያነባሉ። አንድን ርዕስ ነጥለን ብንወስድ ስለይቅርታ እልፍ ጥቅስ ይጠቅሱልሻል። የማይኖሩትን ህይወት ሊመክሩሽ ይችላሉ። ነገር ግን በህይወታቸው ለመጎዳት ምክንያት የሆናቸውን ሰውጋ ይቅርታ ማድረግ ዳገት ይሆንባቸዋል። ያውቁታል እንጂ እውቀታቸው የእነርሱ አካል አይደለም ወይም አይኖሩትም። ከእውቀቴ ከስሜቴ ከህክምናዬ እና ካለፈው ልምዴ ጨምቄ የመኖሪያ መተዳደሪያዬን ፃፍኩ። በየቀኑ ያን ለመኖር ራሴን አሰለጠንኩ። አዲሱ አዲስ የዚህ ውጤት ነው። አለቀ!!» ብሎ ትንፋሽ ሰበሰበ። የምፅፈውን ገታ አድርጌ

«የተነበበ ሁሉ እኮ ግን አይኖርማ?»

«ያስማማናል። የትኛው እውቀት ብትኖሪው እንደሚበጅሽ የምታውቂው አንቺ ብቻ ነሽ!! የምርጫ ጉዳይ ነው።» አለኝና እንደገና ቀጠለ።
2024/09/22 13:34:11
Back to Top
HTML Embed Code: