Telegram Web Link
የሰማኸው?"

"ካንቺ በጣም መጠንቀቅ እንዳለብኝ:: ካለበለዚያ እንደምታባልጊኝ " እየሳቀ ነው...

ማሚ በሩጋ ቆማ እየጠበቀችኝ ነው:: ..... አስተያየቷ 'ደሞ በምን አገኘሽው?" አይነት ነው::

........ አልጨረስንም......

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ሁለቱን ባሎቼን ላስማማ እያሸማገልኳቸው ነው !!
(ክፍል ሁለት)

የሳመኝ ቀን "በናትህ ይሄን ነገር በምስክር ፊት አድርግልኝ" ብለው ደስ ባለኝ። ስሜ መራራ ነዋ። ሳመችው እንጂ ሳማት አይባልልኝማ! እርግጥ የሳመኝ እለት ያልኳችሁ ቀን ማለት በዋዛ የተገኘ እንዳይመስላችሁ

"ጌታ ሆይ ይሄ ሰው በወንድምነት ይሁን በባልነት ፍቅር የሚወደኝ መለየት የምችልበት ፀጋ ስጠኝ! .... ወይ ምልክት ነገር አሳየኝ! ..... ቢያንስ በህልሜ አንድ ጋቢ ለሁለት ስንለብስ ምናምን ....... አለ አይደል የሆነ ምልክት በቃ ...... እኔ ልጅህ በውዝግብ ስንገላታ በቤትህም እንደሚገባህ እያገለገልኩህ አይደለም! (ይሄኛው በእርግጥ ለራስህ ስትል ባሪያህን አስባት አይነት ልምምጥ ነው። ውለታዬ አለብህ በዚህ እንኳን ክፈለኝ አይነት ሰፋጣም ነው።) ብዬ ፆም ፀሎት ልይዝ ትንሽ ሲቀረኝ ነው ያው ምልክት መሆኑ ነው መሳሙ!!

ከምልክቱ አስቀድሞ ከወራት በፊት
ሲሊፐር ያጠለቁ እግሮቼ የቸርቹን በር አልፈው ሲገቡ ራሴን አገኘሁት። ከቤት የወጣሁት ቁምጣዬን ሆዴን በሚያሳይ አላባሽ ለብሼ ከእግዜሩ የተጣላሁበት የወንድሜ መቃብር ጋር ለመሄድ ነበር። እንደለመድኩት

"የማይሰማ ፀሎት ለምን እፀልያለሁ? ወይም ቁልጭ አድርገህ በዚህ ጉዳይ አትፀልዩ ምናምን ብለህ ህግ ብታወጣ ጥሩ ...... በደፈናው ብቻ አንኳኩ ...... ብቻ ፀልዩ አልክ ...... ከዛ ግን የማትሰማው ፀሎት ብዛቱ ....." እያልኩ ከራሱ ከፈጣሪ ጋር እየተነታረኩኝ በእግሬ እስኪደክመኝ ከተጓዝኩ በኋላ ነው ድንገት አቅጣጫዬን ወደቸርቹ ያዞርኩት ......... ገባሁ።

ለወራት ያላዩኝ አስተናጋጆች በፈገግታ ሰላም እያሉኝና አለባበሴን እየገላመጡ ክፍት ቦታ አሳዩኝ። እሱ መድረኩ ላይ አይኑን ጨፍኖ ፒያኖውን እየመታ ይዘምራል።

ከተደረገልኝ በጎነትህ
አንዳችም ለእኔ የማይገባ ነበር
በቸርነትህ አድርገሃልና እደነቃለሁ
አብዝቼ ተመስገን እላለሁ ......

እያለ በሚጣፍጥ ድምፁ ይዘምራል:: ህዝቡ ቆሞ ግማሹ እጁን ወዳፈጣሪ አንስቶ .... ግማሹ ወሬ እያየ ግማሹ ጨፍኖ አብሮት ይዘምራል። መግባቴን ያወቀ ይመስል አይኖቹን ገልጦ አየኝ። ተያየን!! ፈገግ ብሎ አይኖቹን ጨፍኖ ማስመለኩን ቀጠለ። ያስተዋለ ሰው ምላስ ማሟሻ ሆኜ መክረሜን እያወቅኩት ሳቅ ብዬ ተቀመጥኩ። የዛን ቀን ስንወጣ ሲንደረደር መጥቶ አቀፈኝ (በጌታ ፍቅር ነው ይህኛው)

"ስለመጣሽ ደስ ብሎኛል። ሳይሽ በጣም ነው ደስ ያለኝ" አለኝ ወደጆሮዬ ጠጋ ብሎ "ምንም እንኳን ቸርች ለመምጣት አስበሽ ባትመጪም!" አለኝ። አለባበሴን መሆኑ ገብቶኛል።

ከዛን ቀን በኋላ የጌታ ፍቅር ይሁን የሱ ፍቅር መጀመሪያ ሰሞን ባልለየሁት ምክንያት ቸርች እመላለሰው ጀመር። በሳምንት እሮብና እሁድ መደበኛ የቸርቹ ፕሮግራም አልበቃ ብሎኝ ...... አርብ የአገልጋዩች ፕሮግራም ...... ቅዳሜ የወንድሞች ፕሮግራም ...... ማክሰኞ የማለዳ ፀሎት ..... ብቻ ምንም ይሁን እሱ ካለ እኔ አለሁ!!

ፕሮግራሞቹ ሲያልቁ እስከቤት መንገድ እያራዘምን ወክ እያደረግን የባጥ የቆጡን እናወራለን። ጠዋት ተነስቶ ትምህርት ቤት ድረስ ሸኝቶኝ ይመለሳል። የማነባቸውን መፅሃፍቶች ተከራይቶልኝ ይመጣል:: ... አንብቦ ነው የሚሰጠኝ... እኔ አንብቤ ስጨርስ መፈጠራችንን ለማያውቀው ደራሲ ሂስ እንሰጣለን.... እንከራከራለን....

ማታ በየቀኑ ደብዳቤ ይፅፍልኛል... እኔም እፅፍለታለሁ ... ጠዋት ስንገናኝ ደብዳቤዎቹን እንቀባበላለን:: ከሰዓት ከስራ የሚወጣበት ሰዓት ከኔ ጋር ስለማይዛመድ ከሱጋር ሳይክሌን እየገፋሁ በእግሬ 40 ደቂቃ የሚወስድብኝን መንገድ በሳይክል በ10 ደቂቃ እልሰዋለሁ።

ደጋግመን የሄድንባቸው መንገዶች ኮቴያችንን ሰምተው እስኪያውቁት .... በየመንገዱ ያሉ የንግድ ቤት ዘበኞችና ቋሚ የኔቢጤዎች እንደወዳጅ ሰላምታ መስጠት እስኪጀምሩ ...... ቤተኞቼም የኔና የእሱን አብሮ መውጣትና መግባት ከመልመዳቸው የተነሳ እሱ የአጥሩን በር ሲያንኳኳ 'ሜሪ መጥቷል!' ብለው መጥራት እስኪለምዱ ..... ከዚህን ያህል የጊዜ ለውጥ በኋላ ነበር የሳመኝ። (መፀለይ ይነሰኝ?) እንደጠጣ ሰው ጀብረር አድርጎኝ ነበር አሳሳሙ ሳልዋሻችሁ (ቤተኞቼ አንድም እሱን ስለሚያምኑት 'የጌታ ሰው' ስለሆነ ... ሁለትም ለወትሮው በየቀኑ የሆነ ጥፋት የማጠፋ የነበርኩትን ልጅ ስላለዘበላቸው ... በተጨማሪም ወደ ቸርች ስለተመለስኩላቸው .... ከእርሱ ጋር መውጣት መግባቴ ብዙም አልጎረበጣቸውም)

ይሄ በሆነ በጥቂት ቀን "የስራ እድገት አጊንቼ ሌላ ሀገር ልሄድ ነው አለኝ!" እንዴት እንደሚነግረኝ አፉ ላይ ቃላቶቹን ሲያንገዋልላቸው ቆይቶ

"እኔስ? ስምንት ወር ሙሉ እጅህን ተመርኩዤ ሀዘኔን የረሳሁት እኔስ? ትተኸኝ ስትሄድ ምን ልስራ? በቀን ሁለቴ የማይህ እኔስ አንተ የሌለህበትን ቀን እንዴት ልለፍ? ምን ልስራ? አንተ ሳትኖር ማነኝ? ንገረኝ ምን ልሁን?"

እንደሚሄድ እርግጠኝነት ነበረው ድምፁ ስለዚህ 'ቅርልኝ' ልለው አቅሙ አልነበረኝም። ምን ያህል በፍቅር ሙክክ ብዬ እንደበሰልኩ የገባኝ የዛን ቀን ነው። ለወትሮ በሰው ፊት ማልቀስ ያውም ለማልቀስ ምክንያት በሆነኝ ሰው ፊት ማልቀስ ሽንፈት የሚመስለኝ እኔ ....... በሱ ፊት ተዝረከረኩ።

"በቃ አልሄድም እቀራለሁ::" አለኝ "በቃ አንቺ ትምህርትሽን እስክትጨርሺ የትም አልሄድም ይቅር !" አለኝ አቅፎ እያባበለኝ። አዲሱ ስራው አዲስ በተከፈተው የአቢሲንያ ባንክ ማናጀር ሆኖ ነው የሚሄድ የነበረው። ገና እንደተመረቀ ነው አሁን የሚሰራውን ስራ አጊንቶ የጀመረው። በአንድ አመቱ አሁን ያገኘው እድገት ለእሱ ምን ያህል ትልቅ ነገር መሆኑን አውቃለሁ። 'ትቼልሻለሁ' ሲለኝ የባሰ ሙክክ ከማለት ውጪ ምርጫ ነበረኝ? እኔ ደግሞ አስራ ሁለተኛ ክፍልን ገና መጀመሬ ነበር። ተስማማን!! በሆነ መልኩ ራስ ወዳድ እንደሆንኩ ገባኝ።

"ይዘኸኝ ሂድ!" አልኩት በነገታው ጠዋት ትምህርት ቤት ሊሸኘኝ እንደመጣ እስክነግረው ጓጉቼ እላዩ ላይ እየተንጠለጠልኩ ምን እንዳልኩ ገብቶታል። ግን ማመን አልፈለገም።

"የት ነው ይዤሽ የምሄደው? የምትዪው የማስበውን ከሆነ.... አይሆንም!!" አለኝ ኮስተር ብሎ

"ለምንድነው የማይሆነው?"

"ስለምወድሽ ነው የማይሆነው!! ...የኔ ሚስት በስነስርዓት ለቤተሰቦቿ ሽማግሌ ልኬ .... ቸርች ቆሜ በጌታ ፊት ቃል ገብቼላት .... በቤተዘመድ ተመርቀን ..... ነው የማገባሽ! በፍፁም እንደወመኔ ብድግ አድርጌ ይዤሽ አልሄድም። ትምህርትሽን በጥሩ ውጤት ትጨርሻለሽ .... እንደህልምሽ ህግ ትማሪያለሽ ..... ስትመረቂ ከፈለግሽ የምርቃትሽ ቀን ሰርጋችንን ማድረግ እንችላለን።" አለኝ ኮስተር ብሎ ቀጠል አድርጎ "አንቺ ግን የምርሽን ነው?"

"እሱማ የምሬን ነው። ቆይ ምንድነው ያልከውን ሁሉ ከማድረግ የሚያግደኝ? ሰሞኑን ሽማግሌ ትልካለህ .... ከዛ ቸርች ሄደን ቃል እንገባባለን.... ይዘኸኝ ትሄዳለህ .... አንተም ስራህን እኔም ትምህርቴን ..."

"እ እ አይሆንም አልኩ አይሆንም!" አለኝ ከአፌ ቀምቶ "እብድ እኮ ነሽ ..."

ማታ ምን አቅብጦኝ እንደሆነ ሳላውቅ ለማሚ ነገርኳት። በቤቴኮ 'እንዴት ያለ የተባረከ ልጅ ነው::' ብላ እንድታሞግስልኝ ነበር:: ቦንብ ማፈንዳቴ አልታወቀኝም። ከዛን ቀን በኋላ እሱ እኛ ቤት በምንም ሰበብ ቢሆን እንዳይመጣ ለእርሱም ለወንድሜም ማስጠንቀቂያ ተሰጠ። ትምህርት ቤትም ሆነ ቸርች ወይ ማሚ ወይ አባቴ ሆኑ የሚያደርሱኝ። ቸርች
የምሄድባቸው ቀናት ተወሰኑልኝ። እሱም ቸርች ማስጠንቀቂያ ደረሰው። አንድ ሳምንት ሳናገናኝ አለፈ። ... እንደዛ እንደመልዓክ የሚያዩት ቤተኞቼ .... ሲያዩት ሁላ የሞት መንፈስ እንዳዩ ይሸሹት ጀመር ... ማሚ ጭራሽ ተከርብታ 'ባንተ ተመስሎ ልጄን ከአላማዋ ሊያሰናክል ያለ መንፈስ ወጋሁ!!" ብላዋለች🤣 ለትምህርት ቤት ሁላ ማንም ቢጠራኝ እንዳያስጠሩኝ መልእክት ተላለፈ። በርቀት መድረክ ላይ ብቻ አየዋለሁ።

(ምንም አልገቡኝም:: ቀላሉ መንገድ ከኔጋር ማውራት ነበርኮ ... እውነቱንኮ ነግሬያቸዋለሁኝ... )

ከዛ ግን ያቺ እንቢ ባዩዋ እኔ ሁሉንም "የራሳችሁ ጉዳይ!" አለች ከትምህርት ቤት አሞኛል ብዬ አስፈቅጄ ስራ ቦታው ስበር ደረስኩ ሲያየኝ ሊጮህ ሁላ ዳዳው በደስታ ከመሬት አንስቶ አየር ላይ አሽከረከረኝ።

"የማብድ መስሎኝ ነበር::" አለኝ ፀጉሬን.. አንገቴን .. ጉንጬን ... ከንፈሬን ... እየሳመ... እንደሌላው ቀን ለሚያየው ሰው ሁላ ሳይጨነቅ

"አሁንስ ይዘኸኝ አትጠፋም?" አልኩት

ፈገግ ብሎ "መቼ?" አለኝ

........ አልጨረስንም ......

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ሁለቱን ባሎቼን ላስማማ እያሸማገልኳቸው ነው!!
(ክፍል ሶስት)

ሁለተኛውን ባሌን እስክተዋወቀው ሰዓት ድረስ ዓለሜ ሁሉ እሱ ነበር (የመጀመሪያው ባሌ) ትምህርቴ .... ትዳሬ .... ፍቅሬ .... ቤተሰቤ ... ጓደኛዬ .... ወንድሜ ....... ይሄን ሁሉ ከኋላዬ ትቼ እርሱን መርጫለሁኛ!!

እንዲህ ነበር የሆነው
«ይዘኸኝ ጥፋ!» ያልኩት ቀን ከተማ ይዞኝ ሄዶ ቀለበት ገዛን። ማንም በሌለበት ቸርች ሄድን። ልክ እኔና እሱ ሙሽራ እንደሆንን ... የቸርቻችን ፓስተር እያጋቡን እንደሆነ አስመስለን መድረኩ ፊት ቆምን።

"ክርስቶስ ቤተክርስቲያንን በወደደበት መውደድ በፍፁም ልቤ ልወድሽ በህመምሽ በጤናሽ በማግኘት በማጣት....." ብሎ ቃል ገባልኝ! በእንባው ቃሉን አተመልኝ።

"ሚስት ለባሏ እንደምትገዛው ልገዛልህ! በጤናም በህመምህ በማግኘት በማጣትህ ልኖርልህ ....." ብዬ ቃል ገባሁለት። የደስታ እንባዬን እያነባሁ ቃሌን አተምኩለት።

'Now you can kiss the bride' የሚለውን ክፍል የኛ ቸርች ፓስተሮች የማይሉት ቢሆንም እኛ ለራሳችን ብለን ተሳሳምን።

'just married' ብለን መኪና ጀርባ ላይ ባንለጥፍም ወደ እሱ ቤት እንዲያደርሰን ለያዝነው ባለላዳ ሹፌር 'ተጋብተን መምጣታችን ነው!' ብለን ነግረነዋል። እንደሙሽሪት ወግ ከነዩኒፎርሜ ወደላይ ተሸክሞ አቅፎኝ ወደተከራየባት አንድ ክፍል ቤት (አንድ ክፍል ቤት ለማለት እንኳ ይከብዳል። አንድ አልጋ ቢባል ይቀላል። ክፍሏ ከመጥበቧ የተነሳ ያለማጋነን በሩን ከፍተን አልጋው ጋር ላይ ነው ያረፍነው። ላለመሳሳት ሀሳብ ኖሮን ቢሆን እንኳን ክፉኛ ፈታኝ ነበር።) ልብሶቻችንን ምኑጋ እንዳወለቅነው ሳናውቅ ተጣመድን!! (ብዙም አታስቡት የመጀመሪያዬ አይደለም። የመጀመሪያው አይደለም። ሁለታችንም አሳምረን ያወራነው ጉዳይ ስለሆነ ቀጥታ ወደስራ) ካላብን በኋላ የምንጠፋበትን ቀን እስክንቆርጥ ደብዳቤ እየተፃጻፍን ትምህርት ቤት ደጅ ያለ ሱቅ ልናስቀምጥ ተነጋግረን ወደቤት ሄድኩኝ። አባቢ ትምህርት ቤት ሊያመጣኝ ሄዶ ገና በጠዋቱ 'አመመኝ' ብዬ መውጣቴ ተነግሮት ስለነበር እሳት ለብሰው ነገር ጎርሰው ሲንጎራደዱ ጠበቁኝ። ልቤ አብጧል:: ፍቅር ጠግቤ ነዋ የመጣሁት

"አዎ እሱጋ ነበርኩ" አልኩ

"ምን ልሁን ነው የምትዪው?" ማሚ ቀወጠችው።

"ማግባት ነው የምፈልገው። ላገባው ነው የምፈልገው። አስገድዳችሁ ከሱ ልትለዩኝ አትችሉም!" ደሞኮ እያለቀስኩ ነው ምኑ እንደሚያስለቅሰኝ ባላውቅም

"እንዴት እንደማልችልማ አሳይሻለሁ። ትዳር? አንቺኮ ህፃን ነሽ? ጌታ ሆይ ልጄን ምንድነው ያስነካብኝ?"

"18 ዓመት ሞላሁ::" አልኩ ፍርጥም ብዬ። ይሄኔ በምንም የማልሸነፍበት ግትርናዬ ላይ መድረሴን ስታውቅ መውረግረጓን ትታ ተቀመጠች። እስከዛ ምንም ያላለው አባቴ

"ህልምሽስ? ትምህርትሽስ?" ሲለኝ ሃሳቤ ሊከፈል ምንም አልቀረውም። አባቴ ኩራቱ እንደሆንኩ አውቃለሁ። ልጄ ህግ ተምራ ወነጀል ነክ መፅሃፍ መጻፍ ነው የምትፈልገው ብሎ ሲጎርርብኝ በእርግጠኝነት ነው። ትምህርት ቤት በየተርሙ ውጤት ሊያይልኝ ይሄድ የነበረው እሱ ነው። 'ሜሪ በትምህርቷ ጎበዝ ናት!' ብለው ውጤቴን ይዘረዝሩለትና በመደዳ ያጠፋሁት ጥፋት ሲነገረው 'እኔ እቆጣታለሁ ትታረማለች!' ይልልኛል። ስንወጣ ግን ለጥሩ ውጤቴ እጋበዛለሁ እንጂ ለጥፋቴ ቁጣም ሆነ ተግሳፅ አያዘንብብኝም። ልጁ ከነረባሽነቴ ኩራቱ ነኝ!! በፊት ወንድሜ በህይወት እያለ ወደቤት ሲገባ የሚጠራው የሱን ስም ነበር። ከሱ ሞት በኋላ 'ሜሪ' እያለ ነው ወደቤት የሚገባው

"እማራለሁ። እሱ እንዳልማር አይከለክለኝምኮ!" ድምፄ ወደማባበል ሄደ። "እማራለሁ። ተመርቄ አኮራሃለሁ። እሱን አጥቼ ግን መማር አልችልም።" በቃ አባቴ ከዚህ በኋላ አልተናገረም። ማሚ ቀጠለች።

"ትዳር እንደምታስቢው ቀላል አይደለም ልጄ!" ልምምጥ ..... ከዛ ደግሞ ቁጣም ታደርገዋለች።

"አይሆኑ ሆነን ያን ሁሉ ብር እየከፈልን ያስተማርንሽ ለከንቱ ነው? ሽሮ እየበላሁ ስጋ የቋጠርኩልሽ ሰው እንድትሆኚልኝ እንጂ ማንንም አግብተሽ የትም እንድትቀሪ ነው?" ደግሞ ድምፅ አውጥታ ታለቅሳለች:: ሆዴ ቡጭቡጭ ከማለቱ ደግሞ እልህ ይይዛታል መሰለኝ(የእኔ እናት አይደለች)

"እስኪ ልብ እዚህ ቤት አስተዳዳሪው ይለያል። እኔ በህይወት እያለሁማ እንዲህ አይደፍረኝም። "

በተዘባረቀ ስሜት ከረምኩ። ከሱጋር በደብዳቤ መገናኘታችንን ቀጠልን። እሱም የቢሮ ፕሮሰሱን እየጨራረሰ ሳለ የሆነ ቀን እቤት ጠዋት ማሚ ከእንቅልፌ ቀስቅሳ

"እውነቱን ንገሪኝ እርጉዝ ነሽ?" አለችኝ። አበድኩባት::

"ምንድነውሱ? ከየት ያመጣሽው ነው?" ብዬ እየቀወጥኩት ፔሬዴ መምጫውን ቀን እቆጥራለሁ።

"ማታ በህልሜ አይቻለሁ::" ብላ ገገመች። በፍፁም ብዬ ገገምኩ። እንደለመድኩት ከትምህርት ቤት ጠፍቼ ልመረመር ከሱጋ ሄድን። አርግዣለሁ!!

ደስታም ድንጋጤም ብቻ መላው ያለየለት ስሜት ተተራመሰብን። እዛው የሆስፒታሉ አግዳሚ ላይ እንደህፃን ልጅ ውስጡ ጥቅልል አድርጎ አቅፎኝ ለአንድ ሰዓት ተቀመጥን። ብቻ እየደጋገመ

"እኔ አለሁልሽ አይደል?" ይለኛል። ምንም ቃል ከአፌ ባያወጣም ግራ የገባው ስሜት ነበር የሚሰማኝ።

ከዚህ ብዙም ባልራቀ ቀን ጨርቄን ማቄን ብዬ ሁለታችንም ከዛ በፊት ረግጠነው ወደማናውቀው ከተማ ሄድን። እንደማንኛውም መደበኛ የዘመናችን ትዳር አንድ ፍራሽ ... ሁለት ብርጭቆ ... አንድ ድስት .... አንድ መጥበሻ ... አንድ ጭልፋ ..... ቢላ ...... ብለን ቤት ተከራይተን መኖር ጀመርን። በእርግጥ አንዳንዴ እቤት ውልብ ይሉብኝና ከሆርሞኑ ጋር ተደርቦ እነፋረቃለሁ።

እናቴ መጥፋቴን ስታውቅ የምትለውን አስባለሁ አባቴ እንዴት አዝኖብኝ ይሆን እላለሁ። ባሌ ግን እናቴም አባቴም ወንድሜም ፍቅረኛዬም ጓደኛዬም ሆነ።

የአራት ወር እርጉዝ ሆኜ ነው አዲሱ ባሌ የመጣው። በዓል ሆኖ እሱ ዶሮ እያረደልኝ። አጠገቡ ቆሜ እያየሁት ነው። ከጎናችን ያለው ተከራይ አሁን በውል የማላስታውሰውን ነገር ያወራኛል። እመልስለታለሁ። ባሌ ሲናደድ አየሁት ምክንያቱ ስላልገባኝ ወሬዬን አላቆምኩም:: ደግሞ መገልፈጤስ? ጨርሰን ስንገባ ደም የነካካውን ቢላ እና ሞረድ እያጣጠብኩ

"አባ ምን ሆንክ?" አልኩት

"ባለትዳር አይደለሽ እንዴ? ከላጤ ጋር ምንድነው እንዲያ መሆን?" ሲለኝ ሳቄን ለቀቅኩት እሱ መሳቄ ይባስ አናደደው

"አባ አንደኛ ባለትዳር እንደሆንኩ ያውቃል። እርጉዝም እንደሆንኩ። በዛ ላይ አንተን ከመውደድ የሚተርፍ ልብ ኖሮኝ ነው ሌላ ሰው ታስብበታለች ብለህ የምትቀናው?"

አንድ ሁለት አንድ ሁለት መመላለስ ጀመረ። እኔም በፍቅር ማባበሌን ትቼ በቁጣ መመላለስ ጀመርኩ።

ይሄኔ የሆነ ሌላ የማላውቀው ሰው ሆነ። ሌላ ፈጡር !!! ድምፁ ሻከረ። ደምስሩ ተገታተረ። ከመቼው ዘሎ አጠገቤ እንደደረሰ ሳላውቅ አጥቤ ያሰቀመጥኩትን ቢላ አንስቶ አንገቴ ላይ አደረሰው። ሰውነቴ በደነ። እንባዬ እጁና ቢላው ላይ ተንጠባጠበ። አሰፈሪ ህልም አይቶ እንደባነነ ህፃን ሰውነቴ ተርበተበተ። በዛች ደቂቃ ሁሉ ነገር ፀጥ አለብኝ:: 'አባ' ብዬ የምጠራው ባሌ ውስጥ ሌላ የማላውቀው ሰው አለ:: .....

በርትታችሁ እዚህ ድረስ ከዘለቃችሁ .........አልጨረስንም!!........

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ሁለቱን ባሎቼን ላስማማ እያሸማገልኳቸው ነው!!
(ክፍል አራት)

በሚንቀጠቀጡ እጆቼ ደመነፍሴን ቢላ አንገቴ ላይ ያደረገ እጁን ለቀም አድርጌ ያዝኩት። ያዝኩት እንጂ እንዲያሸሽልኝ ልገፋው ወይ ራሴን ላሸሽ አቅሙ አልነበረኝም። የአቅሜ ጥግ ሳጌ ድምፁ እንዳይሰማ አፍኜ እንባዬን ማዝነብ ብቻ ነበር። እጁ አንገቴ ላይ ቢላዋ መደገኑን እጆቼ ሲይዙት ገና ያወቀ ይመስል ደነገጠ። በጣም ቀስ ብሎ እጁን አወረደው ........ ቢላውን ወረወረው ........ በጣም ቀስ ብሎ መሬቱ ላይ ተቀመጠ። አንገቱን ወደመሬቱ ደፍቶ እንባው መሬቱ ላይ ተንጠባጠበ። ይሄኔ 'ዋጥ አድርጋት' ተብሎ ታፍኖ እንደተገረፈ ህፃን "ህእእ ህእእእ ......" ብዬ ድምፄን አውጥቼ ማልቀስ ጀመርኩ።

ይሄኛው ሌላ ሰውዬ ነው። የእኔ ባል እንኳን ቢላዋ አንስቶ አንገቴ ላይ ሊያደርግ እጅሽን ይቆርጥሻል ብሎ ሽንኩርት የሚከትፍልኝ ...... ትልልቅ አይኖቹ እያለቀሱ ሲያስቸግሩት

"እማ ቆይ ወጥ ያለሽንኩርት ቢሰራ ምን ይሆናል?" የሚለኝ

"እሺ አንተ ነጭ ሽንኩርቱን ላጥልኝ ሽንኩርቱን እኔ ልጠዋለሁ" ስለው ሊልጥ ይታገልና

"እማ ቆይ ወጥ ውስጥ ነጭሽንኩርት ባይገባ ምን ይሆናል?" የሚለኝ።

"እህ? እና ያለሽንኩርት ያለነጭሽንኩርት ዘይት ላይ በርበሬ አድርገን እናቁላላ? "

"አንቺ ከምትቃጠዪብኝ አይሻልም?" እያለ የሚያባብለኝ። ሁሉ ነገር ከእሱ ሲወዳደር የሚያንስብኝ የኔ ባል ይሄ ነው።

የኔ ባል በቀደም በእግር እየሄድን ከእርግዝናው ጋር ተያይዞ በመጣ ደም ማነስ አዙሮኝ ስወድቅ እንደህጻን በእጆቹ አቅፎ ሀኪም ቤት ያደረሰኝ።

"አባ መራመድ እችላለሁ እኮ!" ስለው

"እኔ ምን እሰራለሁ?" የሚለኝ ዶክተሩን

"ደም ማነስ እንዴት አዙሮ ይጥላታል? ደግመህ መርምርልኝ ካለበለዚያ የሆነ ነገር ብትሆንብኝ እጣላሃለሁ!" ብሎ የሚቀውጠው

"ፈሳሽ ነገር በብዛት መውሰድ አለባት!" ብሎ ሲለው። ያለ የሌለ የጁስ መዓት እያስጠጣኝ በሽንት ብዙት የረጋ እንቅልፍ የማያስተኛኝ

ለእኔ ከሆነ ምንም የሚያደርግ የትም የሚሄድልኝ።

የኔ ባል ገና ለከተማው አዲስ ሆነን እንደመጣን አንዱ ቸርች ይዞኝ ሄዶ "ባለቤቴ ናት የሚያምር ድምፅ አላት እኔም እሷም ጌታን ማገልገል እንፈልጋለን ብሎ ኮስተር ብሎ ሲያወራ (ማስፈራቱ ግርማሞገሱ ደግሞ ) ከሳምንታት በኋላ አብሬው ማስመለክ የጀመርኩት ......

ከእግዜር ጋር ያለኝን ፀብ በሚገባኝ ጣፋጭ ቃል አይኔን ከሰዎች ላይ እና ካልተደረገልኝ ነገር ላይ አንስቼ ትልቁ አምላክ ላይ እንዳደርግ ያስተማረኝ መምህሬ .......

እንኳን እኔ ወንድሜ እጁን ይዞ ፒያኖ ያስተማረው። ወንድሜ ምን መሆን ትፈልጋለህ ቢባል "እሱን" የሚልለት የሚያስቀና ስብእና ያለው (ያሸነፈኝ ምን ሆነና?)

የኔ ባል
ጎረቤት ዶሮ ወጥ ተሰርቶ አይቼ ከስራ ሲመጣ እያለቀስኩ "ወጥ ሰርተው እንብላ እንኳን ሳይሉኝ ወደቤት አስገቡት!" ብዬ ስነግረው በአንድ እርምጃ የሰው ቤት ገብቶ

"እንዴት ሚስቴ እርጉዝ መሆኗን እያወቃችሁ ወጣችሁን ከለከላችኋት?" ብሎ የሚጣላልኝ። በሰው ዶሮ ወጥ 'እሷ የምትወደው እግር ነው' ብሎ መርጦ ይዞልኝ የሚመጣ ...

የኔ ባል "መንገድ ላይ ጮክ ብሎ መዘመር አማረኝ" ስለው እንዘምራለና ታዲያ ብሎ በሰው ሀገር መንገድ ላይ ቀውጢ አምልኮ ፈጥረን ሰው ከመንገዱ የምናሰናክል .....

"አባ ደከመኝ ትንሽ እንረፍ!" ስለው እሽኮኮ ካላደረግኩሽ ብሎ የሚያስቸግር ...

መንገድ እየሄድን በሃሳብ ተውጬ የሆነኛው መንገድ ላይ የተንጠለጠለ ሙዝ ላይ ሳፈጥ የሰው ማሳ ገብቶ ያልበሰለ ሙዝ ሰብሮ ከጠባቂው ጋር ግብ ግብ የሚገጥምልኝ ....

የኔ ባል ሁለት ልጆች አንድ ሴትና አንድ ወንድ ወልደን ስማቸውን አውጥተን ስናረጅ ምን እንደምንሰራ አቅደን። ፀጉራችን ነጭ ሆኖ ጥርሳችን አልቆ ምን እየተባባልን እንደምንፎጋገር አውርተን የጨረስን ....

የኔ ባል "ባንተ ድምፅ ሲሆንኮ ሲጣፍጠኝ" ስለው ቁጭ ብሎ መፅሃፍቶች የሚያነብልኝ።

ሰው ውጪ ምሳ ልጋብዝህ ሲለው ሚስቴ ብቻዋን ናት ብሎ የሚመጣልኝ ...

የእኔ ባል ብዙ ነው ...... በእያንዳንዱ በሚያደርጋቸው ጥቃቅን ነገር ሁላ ሳይቀር ከምንም እንዳላወዳድረው ሆኖ ልቤን የሞላ ነው
.....
ይሄኛው የኔ ባል አይደለም:: እንዴት ሁለት ማንነት አንድ ስጋ ውስጥ ይቀመጣል???
.....
.....

ለሰዓት ያህል ከተቀመጥንበት እሱ ቀድሞ ተነሳ

"ሄጄ አምሳሉን (ስራ በመስራት የምታግዘን ልጅ ናት) ልጥራትና እሷ ወጡን ትስራው በቃ ወይም ይቅር በቃ ስጋ ገዝተን ጠብሰን እንብላ .....አይሻልም ? ..... አንቺ ተነሺ በቃ አረፍ በይ እ?" ሊወጣ መንገድ ከጀመረ በኋላ

"የትም አትሄጂብኝምኣ?" አለኝ እግሬ ስር መጥቶ ጉልበቴን እያሻሸ

"ልሂድ ብል የት እሄዳለሁ?" አልኩት ሳላስበው። በዛ ቁመቱ ዝርፍጥ ብሎ ስሬ ቁጭ አለ። በእርግዝናው ሳቢያ ማበጥ የጀመሩ እግሮቼን ከጫማው ላይ አንስቶ ሁሌን እንደሚያደርገው እያሸልኝ

"እማ እባክሽ ማሪኝ!" አለኝ እንባው ጠብ ሲል እግሬ ላይ ያርፋል:: እሺም ..እንቢም ... ሙግትም ... ትግልም ... የለኝም ብቻ ፀጥ !!

"እማ እባክሽ አትተይኝ! ???ይቅር በይኝ!??" ከማልቀስ ውጪ መልስ አልሰጠውም:: ሁሉም ነገር ግልብጥብጥ ብሎብኛል የተፈጠረው ቅፅበት ህልም ቢሆን ..... እሱን ክፍል ብቻ መደምሰስ ብችል ከጭንቅላቴ ውስጥ ..... ለምን? እንዴት? ጭንቅላቴ ውስጥኮ ብዙ ጥያቄ ይንከላወሳል።

እንዴት አንድ የዚህኛውን እሱን ምልክት ይሄን ያህል ጊዜ አላየሁበትም? ግን አፌን ለቆ የሚወጣ ምንም ቃል የለም። ልጅ ልኮ የምትሰራልንን ሴት አስጠርቷት አመት በአል አስመስላው ሄደች እንደነገሩ እራታችንን ቀማመሰን በጊዜ ተኛን። እኔና እሱ ኩባያ የምንለውን አስተኛነት (ለምን እንደዛ እንዳልነው አላስታውስም) ጀርባዬን ሰጥቼው በጎኔ በእጆቹ በሃል ታቅፌ ጀርባዬና ደረቱ ተጣብቀው .... እጥፍ ያለ ጉልበቱ መሃል እግሮቼን አጥፌ ተኛኝ። ማልቀሴን ማቆም አቃተኝ:: ሳጌ እንዳያመልጠኝ እታገላለሁ።

እያለቀሰ ነው። ሳጉን እንዳልሰማው ውጦታል። እንባዬ ክንዱን ሲያርሰው ይሞቀዋል:: እንባው አንገቴ ስር ሲያርሰኝ ይሞቀኛል። አልቅሼ እንባዬ ሲያልቅ ነው መሰለኝ ...

"ምን ያህል እንደማፈቅርህ ህቅ ህቅ (ሳጌ ያቋርጠኛል) አልገባህም ማለት ነው?" አልኩት ዞሬ

"እማ እባክሽ ማሪኝ?" አንገቴን ፀጉሬን እጄን በእንባ የራሱ ጉንጮቼን አይኖቼን ይስማቸዋል። ለደቂቃዎች ምላሳችን ላይ እንባችን ጨው ጨው እያለን ስንሳሳም ቆይተን ደረቱ ላይ እንቅልፍ ይዞኝ ሄደ።

በነገታው ለሱ ሳልነግረው ከቤት ወጥቼ እናቴጋ እቤት ስልክ ደወልኩ። የተፈጠረው ነገር ለሱ ያለኝን ፍቅር አልነበረም የቀነሰው። እኔኑ ራሴኑ ነበር በሆነ መጠን የሸረፈኝ። ምክንያቱም ከትናንት በፊት የነበረችው ሜሪ ለማንም ብላ ማንንም የምትፈራ ሴት አልነበረችም።

በስልኩ ውስጥ የእናቴን ድምፅ ስሰማ:: ማውራት አቃተኝ!!! እንባ እና ህቅታ ብቻ ....

......... አልጨረስንም እንግዲህ.......

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ሁለቱን ባሎቼን ላስማማ እያሸማገልኳቸው ነው!!
(ክፍል አምስት)

"ማሚ" ከማለቴ እናቴ በስልኩ እልልታዋን አቀለጠችው። ፀሎት አይሉት ወሬ
"ጌታ ሆይ ምን ይሳንሃል? ጸሎቴን ሰማኸኝ እልልልልል ...... ልጄ? ደህና ነሽ?"

"ደህና ነኝ!" እያልኳት እሪታዬን እለቀዋለሁ

"ምን ሆነሽ ነው? የት ነው ያለሽው ?አሁኑኑ ልምጣ ?"

"ምንም አልሆንኩም! ናፍቃችሁኝ ነው።"

ስለእሱ ላወራት አልችልም። እሱን ከማሳማው ያን ቢላ አንገቴ ላይ ድጋሚ ባገኘው ይቀለኛል። እሱን እንድትጠላብኝ አልፈልግማ!! ልጇን ያደረጋትን እንጂ ልጇ ለሱ ያላት ገደብ የለሽ ፍቅር አይገባትማ! ግን የእናት ሆዷ ነግሯታል።

"እሺ ይሁን እንዴት ሆንሽ? ትምህርትሽን እየተማርሽ ነው? "

"አይደለም ማም እርጉዝ ነኝ። በዚህ ዓመት አልማርም። ልጄን ከወለድኩ በኋላ እማራለሁ!"

ዝም አለች። ወደፊቴን አስባው ልቧ ዝሎባት መሰለኝ ዝም አለች። ከወለዱ ኋላ ያለውን አቀበት አይታው ነው መሰለኝ ዝም አለችልኝ። የምትለው የማታጣው እናቴ ዝም

"ማም ?"

"ወዬ? እስኪ ይሁን ብቻ አንቺ ደህና ሁኚ!..... እሱ አሁን አጠገብሽ አለ? (አባባሏ ይሄ እንትን .... ብላ የሆነ ስድብ የመቀጠል ነገር ነው። )ምንም ባልላትም ጠምዳዋለች።

"የለም ስራ ነው!"

"ይሁን እንደምትዪው ..... በወጉ ሽማግሌ ላክ በዪው ..... ሳትወልጂ በስነስርዓቱ ተደግሶ ቃልኪዳን ትፈፅማላችሁ። በምንም ሁኔታ ቢሆን ልጄን እንደማልተውሽ ማወቅ አለበት።"

"ማሚ እሱኮ ከእናንተ እንድጣላ አይፈልግም ለምን እንደጠላት ታዪዋለሽ? ምርጫዬን የመረጥኩት እኔ ነኝ እሱ እንደውም ሁሌ ደውዪላቸው ነው የሚለው።" (ደግሞ የምሬን ነው። በከፋኝ ቁጥር ለምን አትደውይላትም ነበር የሚለው)

"እሱን እንኳን ተይው .... የውልሽ ልጄ ወንድ ልጅ ብቻሽን ሲያገኝሽ እና መሄጃ እንደሌለሽ ሲያውቅ ጥሩ አይደለም። ያኔ ከርሱ ውጪ ምርጫ የሌለሽ ንብረቱ ነሽ። ያን ክፍተት አትስጪው ...... አይደላደል ..... ተንከባክቦ በፍቅር ካላኖረሽ አማራጭ ያለሽ መሆንሽን ሲያውቅ እንደሚገባሽ ያከብርሻል!!"

የኔ ባል ይለያል ብዬ እንዴትም ላስረዳት አልችልም። እናቴ አንድም በህይወቷ ሴትነትን ከፍ አድርጋ የምትኖር ሁለትም ሴቶች ጉዳይ የምትሰራ ያውም በከፍተኛ ሃላፊነት ደረጃ ላይ ያለች ሴት ናት።

"What happen to ስታስተምሩ ያሳደጋችሁኝ 'ሚስት ለባሏ ትገዛ?'"

"ሚስት ለባሏ ትገዛ ሲል ለባልም ሚስቱን ነፍስን እስከመስጠት ባለ የክርስቶስ ፍቅር የመውደድን ሀላፊነት እንደሰጠው አትርሺ!" አለችኝ ኮምጠጥ ብላ።

"ማሚዬ እንደዛ ይወደኛል።" አልኳት ለእሷ ... ለራሴ መልሼ ግን 'እንደዛ ይወደኛል?' ብዬ አሰብኩ። ያልጠየቀችኝ ነገር የለም።

"ለመሆኑ ቤቱን በትክክል ያስተዳድራል?" ምን ማለቷ እንደሆነ አውቃለሁ። ገንዘብ ይሰጥሻል ወይ ነው?

"ማሚ ደሞዙን አምጥቶ ለእኔ ነው የሚሰጠኝ (የምሬን ነው። ሙሉውን ደሞዝ አምጥቶ ለእኔ ነበር የሚሰጠኝ። ልክ አባቴ ለእናቴ እንደሚያደርገው። በወር የሚያስፈልገንን ፅፌ አዘጋጃለሁ። ለሱ የኪስ ብር እሰጠዋለሁ። የሚደረገውን ሁሉ እኔ ነኝ የማደርገው። )

"እሺ ጉዳዩ ላይ እንዴት ነው?"

"ማሚ ኸረ በጌታ ?" ለቅሶዬን አስትታ አስፈገገችኝ

"እህህ የምሬን ነው። ከዚህ ሰው ጋርኮ ነው የምታረጂው። ትዳር እኮ ቆይ ለጉዳዩ ለጉዳዩ ጊዜ ወጣ ብዬ ልምጣ አይባልበትም!"

መጨረሻ ላይ አባቴን ላወራው እንደምፈልግ ስነግራት። እሷ ሰበብ ብትነግረኝም አባቴ ሊያናግረኝ እንዳልፈለገ ገባኝ። ዝምተኛው አባቴ በዝምታው ሊቀጣኝ ፈልጓል። ሁሌም እንደዛ ነው። ጥፋት ሳጠፋ ተቆጥቶኝ አያውቅም። በዝምታ ነው የሚቀጣኝ። ጥፋቴን እስካርም ወይም ይቅርታ እስክጠይቅ ድረስ አያዋራኝም። ይሄኛውን ግን ለማረም ዓመታት ሊፈጅብኝ ይችላል። እሱ የሚስላትን ልጁን ሆኜ ላሳየው ብዙ ይፈጃል እና በዝምታው የሚቀጣኝ እስከዛ ከሆነ?......

የዛን ቀን ማታ ከስራ መጥቶ ወክ እያደረግን ለእናቴ እንደደወልኩ ልነግረው ፈራሁት። ምኑ እንዳስፈራኝ አላውቅም። ካፈቀርኩት ጀምሮ ከሱ ጋር ሳልማከር አድርጌ የማውቀው ነገር ባለመኖሩ ስለደበቅኩት? 'ግን እናቴጋ ለመደወል የግድ ከእርሱ ጋር መማከር አለብኝ?' እላለሁ ለራሴ ነገሩን ለማቅለል።

"አባ ዛሬ ማሚጋ ደወልኩኮ!" መገረምም መደንገጥም ፊቱ ላይ እያየሁ ምንም እንዳልመሰለው ለመሆን ጣረ ሁለታችንም እየተቀየርን እንደሆነ አሰብኩና ፈራሁ። መደባበቅ እየጀመርን ነው። ፈራሁ!!

"ቆንጆ አደረግሽ! ምን ተሰማሽ? ደስ አለሽ? ማሚ ምን አለች? ደህና ናቸው?" ስሜቱን ለመደበቅ በጥያቄ ያጣድፈኛል። ያለችኝን ነገርኩት

"ደስ ይላል እማ!" አለኝ ማንን ሽማግሌ እንደሚልክ ምናምን ሰርጋችን ላይ ማን እንደሚጠራ ምናምን ማውራት ጀመርን!!

ስለሰርጋችን ማውራቴ ትቼው ልሄድ አለማሰቤን ስለነገረው ይመስለኛል ቀለል አለው። እኔ ግን ከፋኝ !! እኔ እና እሱ መሰለኝ እየተባባልን ስሜታችንን አንገማመትም:: ይነግረኛል አውቃለሁ። እነግረዋለሁ ያውቃል።

"ቤተሰቦችህጋ ትደውላለህ?" አልኩት።

"አላውቅም!" አለኝ ከቤተሰቡ ጋር ለረዥም ዓመታት ተገናኝቶም ደውሎም አያውቅም።

ማውራት የማይፈልገው አጀንዳ ነው። እሱ ጴንጤ ከሆነ በኋላ ምንም አይነት መጠያየቅ ተጠያይቀው አያውቁም። ትዳራችን ላይ የሚያመጣው መዘዝ አለ ብዬ አስቤውም ስለማላውቅ ትኩረት ሰጥቼው የማውቀው ነገር አልነበረም።

ከዚህ ክስተት በኋላ ከዋነኛው ባሌጋ የምናነባቸው መፅሃፍት ውስጥ እንዳሉት ፍቅረኛሞች የሚያስቀና ትዳራችንን ቀጠልን። መፅሃፍቶቹ ውስጥ ያሉ ባለትዳሮችም ሆነ በገሃዱ አለም ያሉ ባለትዳሮች ሳይነግሩሽ የሚዘሏቸው ጥቃቅን የሚመስሉ ከባባድ ነገሮች አሉ። ለምሳሌ ምስር ወጥ ለመስራት ከወጡ ሙሉ ሂደት ምስሩን መልቀም እንደሚያደክም አይነግሩሽም ....... እርጉዝ ሆነሽ እንጣዬ ስታደርጊ ልጄን እየነካው ይሆን? የሚለው ሀሳብ ከስሜት እንደሚያወጣ አይነግሩሽም። (ምነው እማ? ሲለኝ በመሃል ልጁን ትነካው እንደሆነ ሃሳብ መጥቶልኝ ስለው አቋርጠን ለሰዓታት በሳቅ መዛላችንስ?)

የሰርጋችን ቀን ተወሰነ። ሽማግሌ ተላከ። ሆዴ እየገፋ ሲመጣ ደም ማነሴ እየጨመረ መጣ። ስለሚያዞረኝ ድንገት እንዳልወድቅ እርሱ እንደህፃን እጄን ይዞኝ ካልሆነ በቀር ከቤት አልወጣም። የሆነ ቀን እንጀራ የሚጋግሩልኝ ሴትዮ 'ምጣዱ ተሰበረ' ሲሉኝ። አብሪያቸው ምጣድ ላጋዛ ገበያ ሄድኩ።(ይሄንንም አይነግሩሽም በነገርሽ ላይ)

ገበያው መሃል ጎንበስ ብዬ ቀና ስል አዙሮኝ ወደቅኩ። እኔ እቤት ሳልደርስ ወሬው ባሌጋ ደርሷል። ሲመጣ እጅ እግሩ እየተንቀጠቀጠ ደባብሶ ደህና መሆኔን ካረጋገጠ በኋላ ..... ልቡ በአፉ ልትወጣ እስኪደርስ ደንግጧል። ከዛ ያልገባኝ የድንጋጤው ብዛት ወደ ቁጣ ተቀየረ።

"አትውጪ አላልኩሽም? አይቀርም? ለምን ሰው የሚልሽን አትሰሚም? የሆነ ነገር ሆነሽ ቢሆንስ? " (ያ ደባሉ ባሌ መጣ) ረስቼው ነበር እና አላስተዋልኩትም።

"በቃ ምንም አልሆንኩምኮ ! በጣም አካበድክ" ከተኛሁበት ብድግ አልኩ እሱ በሚናገርበት ድምፅ ጮክ ብዬ (ምላሴ ቢያርፍስ ?)

አንዴ በጥፊ ሲያልሰኝ እኔ ከሲኖትራክ ልውደቅ ሲኖትራኩ በኔ ላይ ይሂድ አላውቀውም! ብቻ ስሜቱ እንደዛ ነው። የሰው ጥፊማ እንዲህ ጭው አይልም።
አመንኩ። ይሄ የአንድ ቀን ስህተት አይደለም። ባሌ ሁለት ነው። እሺ ምን የሚሉት ነው? ፍቅር ነው ጥላቻ? በምነኛው ዘርፍ ልቀበለው? ነፍሱ እስክትወጣ ስለሚያፈቅረኝ የሆነ ነገር ሆነሽብኝ ቢሆን ኖሮስ ብሎ ተናዶ እርጉዝ ሚስቱን እሱ በነፃ በአንድ ሲኖትራካዊ ጥፊ የሆነ ቦታ ደርሶ መልስ ትኬት የሚያስቆርጠኝን ባሌን በምን ዘርፍ ልመዝግበው? ለሁለት ባል እያወቅኩት ልሞሸር?


........... አልጨረስንም ባይዘዌያችሁ ላይ......

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሁለቱን ባሎቼን ላስማማ እያሸማገልኩ ነው
(ክፍል ስድስት)

ሳፈቅር ገገማ ነኝ!! ግግም ያልኩ ሰገጥ!! የተመታሁት እኔ ...... ቢላ አንገቴ ላይ የተደረገው እኔው ...... እሱ ለሰራው ጥፋት ማስተባበያ የምሰጠውም እኔው ....... ሁለቱንም ጊዜ እኔ ስቆጣ ነው ሌላ ሰው የሆነው ስለዚህ እኔ እሱ ሲቆጣ ባልፈው ያኛው እሱ አይመጣም ብዬ አሰብኩ!(ሰገጥ ነኝ አላልኳችሁም?)

እንዴት እንደማስተካክለው .... እንዴት ሁለቱን ማንነቱን እንደማስማማ እንጂ የማስበው ከሱ መለየት በፍፁም ለምርጫ የሚቀርብ አይደለም። ከሚሆነው ሁሉ እሱን የማፈቅርበት ጥግ ያልፋል። እናም ሁለቱን ባሎቼን በአንድ ሱፍ አገባኋቸው!! አባቴ እግሩን ስሜ እንኳን ስወጣ በሙሉ ዓይኑ አላየኝም። እሱኛው ቅፅበት ባሌ ካላሰኝ ጥፊ በላይ ያም ነበር።

በሆነ ጊዜ አንዴ የሚመጣውን ያኛውን እሱን በየቀኑ እንደሚሰበር ነገር ለሚጠነቀቅልኝ እሱ ስል ልችለው ወሰንኩ!! ምን እንደሚያስከፍለኝ የማውቅበት የእድሜም የብስለት ደረጃም ላይ አልነበርኩም። የማውቀው ያለእድሜዬ ያነበብኳቸው የፍቅር መፅሃፍት ውስጥ እና ያየኋቸው ፊልም ላይ ያለውን አድቬንቸር የሆነ ፍቅር ነው። ያ ደግሞ እንኳን ጥፊ ሞት ይጨለጥበታል።

ማሚ "የመጀመሪያ ልጅ እናት ቤት ነው የሚወለደው" ብላ አላፈናፍን ስትለን እሱ ደስ ሳይለው ሄድኩ። ወለድኩ!! ፀግዬን ወለድኩ!! ልክ ተገላግዬ ክፍሉ ውስጥ ሲገባ አልጋዬ አጠገብ በጉልበቱ ተነበርክኮ የሆነው መሆን ....... አምጥተው ህፃኗን ሲያስታቅፉት የተሰፈሰፈው መንሰፍሰፍ በጥይት መቶኝ ቢሆን ሁላ እረሳለት ነበር። (ሰግጣለሁ አልኳችሁኮ)

ልጄን አቅፎ በሚያምር ድምፁ እየዘመረ ሲያስተኛት እያየሁት ለሁለቱ ስል ምንም መሰናክል እንደማልፍ ወሰንኩ። ማሚ ህፃን ማጠብ ለእኔ ሳይሆን ለሱ ነበር ያስተማረችው። ለሊት ተነስታ ስታለቅስ ልናስተኛት አሳራችንን ስናይ የምታሰቃየን ልጅ ልክ እሱ አቅፏት መዘመር ሲጀምር ትተኛለች። እና በዚህ ፍቅር ቂም መያዝ ይቻለኝ ነበር?

የእናቴ ቤት ድሎት ኮሰኮሰኝ ምክንያቱም እሱ ስራ መግባት ስለነበረበት ተመልሶ ሄደኣ። በየቀኑ ስልክ እየደወለልኝ ለሰዓትት እናወራለን። አባቴ አሁንም ከ'ደህና አደርሽ?' እና 'ህፃኗ እንዴት አደረች?' ያለፈ አያወራኝም። ጭራሽ ሆድ ባሰኝ እሪሪሪሪ ብዬ በ45 ቀኔ ወደ ባሌ እቅፍ ተመለስኩ። (መሰስ ብዬ ቦክስ ሪንግ ውስጥ መግባቴ የታወቀኝ ሰንብቶ ነው።)

የሚናደድበት ምክንያትና ሰዓት እስኪዋቀጥብኝ የሚናደድባቸው ነገሮች እየበዙ መጡ። ሲናደድ ምን እንዳደረገ የሚያውቀው ካደረገ በኋላ ነው። ጭራሽ አያውቀውም። ካደረገው በኋላ ለቀናት በሙሉ ዓይኑ አያየኝም። የተለመደ ይቅርታ.... የተለመደ ማሪኝ.... የተለመደ ለቅሶ.... ለሰርጋችን ያልመጡት ቤተሰቦቹ መውለዴን ሲሰሙ ደወሉ። እናቱ ልክ የሆነ አንዳንዴ መክሰስ መብላት ይዘላል አይነት ነገር ቀለል አድርገው

"አንዳንዴ ሲናደድ አብሾ አለችበት ቦግ ይላል !! አይዞሽ ታገሺው ..... እንጂ ልቡ ወርቅ ነው!!" ብለውኝ አረፉት።

"ለምን ነርሲንግ አትማሪም?" አለኝ የሆነ ቀን አለ አይደል? 'ገና አስራሁለተኛ ክፍል ተምረሽ ዩንቨርስቲ መግባት ከልጅ ጋር ይከብድሻል' የሚል አንድምታ የያዘ። ማሚ ናት ለኳሿ እሷን አልሰማ ስላልኩ ነው በሱ በኩል የመጣችው!!

"አባ 12 እማራለሁ አሪፍ ውጤት አመጣለሁ። ህግ እማራለሁ። ምንም የሚቀየር እቅድ የለም።"

"እሺ ካልሽ ከጎንሽ ነኝ አለሁልሽ" አለኝ። ማሚም ንቅንቅ እንደማልል ስታውቅ ይጠቅማታል ያለችውን ሀሳብ ሰነዘረች። እሷጋ ከነልጄ ሄጄ እንድማር እና ስጨርስ ወደባሌ እንድመለስ ወይም ልጄን እሷጋ ትቼ ከባሌጋ ሆኜ እንድማር። ሁለቱንም እንቢ አልኩ። ልጄን እያሳደግኩ ከባሌጋ ሆኜ እማራለሁ። ያለችኝን ነገርኩት። በሆነ መልኩ እናቴ እኔን እየነጠቀችው እንደሆነ ተሰማው ተጠማመዱ።

ማሚ በደወለች ቁጥር ቤታችን በአንድ እግሩ ይቆማል። ሁሌ እምላለሁ "እሱ ሲናገር አልመልስለትም ዝም እላለሁ" ብዬ ሁሌ ያን ማድረግ ያቅተኝና የተዋበች ቡጢ ስቀምስ ፀጥ እላለሁ። እየተደጋገመ ሲሄድ የሚቀጥለው ህይወቴ ቀላል እንዳልሆነ ገባኝ። ይሄ ሁሉ ሆኖ ለእሱ ያለኝ ፍቅር ንቅንቅ አለማለቱ ይገርመኛል። ሁሌም እሱን ብቻ ጥፋተኛ ማድረግ አይሆንልኝም። እንዲህ አድርጌ ቢሆን እንዲያ አድርጌ ቢሆን እላለሁ ግን አይሆንምኮ ሲቆጣ እንደማዕበል ከየት መጣ ሳልለው ነው ዱብ የሚልብኝ። በተጣላን ቁጥር ወይም ሊያስቆጣው ይችላል ብዬ የማስበው ነገር ሲፈጠር ስለት ያላቸውን ነገሮች ሰብስቤ እቆልፋለሁ። ....

የሆነ ቀን እሱ እየተቆጣ ሲያወራ ፀጊ አልቅሳ አላባራ አለች። "ዝም አስብያት" ብሎ ጮኸ። ምንም ባደርጋት ጭራሽ ዝም አልል አለች። ይሄኔ ልብ አይሞትምኮ የሱ ብስጭት ቅውስ አድርጎኝ እኔ ብሼ ተገኘሁ።

"ለጸብ ሰበብ ነው እንዴ የምትፈልገው? ምን ልሁን ነው የምትለው? ጭራሽ ልጅህ አለቀሰች ብለህ ፀብ ታጋግላለህ?" ብዬ ፊጥ ፊጥ ማለት።

ፀጊን ከእጄ ተቀብሎ ሊያባብላት ሲሞክር እኔን ማን ያቁመኝ ብሶቴ ሁሉ ተሰብስቦ መጣብኝ። እያለቀስኩ እደነፋ ጀመር። ፀጊም እሪታዋን አላቆም አለች።

ሰይጣኑ ቆንጆ ተቀባብሎ ሰፈረበታ!! ልጅቷን እንደሆነ ነገር አልጋው ላይ ጥሏት። ብቻ በጠረባ ከታች ወደላይ ሲያነሳኝ አየር ላይ ትንሽ ተንሳፍፌ .... ጣራውጋ ያለችውን እስከዛሬ እርቃኝ ያልደረስኩባትን የሸረሪት ድር እግረመንገዴን አፅድቼ ተመልሼ ፈረጥኩ። የዛን ቀን በዛው ወጥቶ አምሽቶ ገባ። ቁጭ ብዬ አሰብኩ። የትኛው ህመም እንደሚብስ ልጄን ለእናቴ ሰጥቼ ቡጢዬን ለምሳ እየሸከፍኩ ትምህርቴን ከእርሱ ጋር ሆኜ መቀጠል። "አልፈልጋችሁም እሱ ይበልጥብኛል" ያልኳቸው ቤተሰቦቼጋ "እንደወደዳችሁ አድርጉኝ" ብዬ ሽንፈቴን መዋጥ(ይሄ እሱን ማጣት አለው) ወይም ልጄንም ይዤ ቡጢዬንም ችዬ ትምህርቴን መቀጠል። የመጨረሻው የማይታሰብ እንደሆነ የገባኝ ልጄን አልጋው ላይ ወርውሮ እንደጨርቅ ሲያነጥፈኝ ነው። እሱን ማጣትም አልችልም!! ከዛ በሚያነክስ ልብ ትምህርቴን ተምሬ ውጤት ማምጣት እንደማይሆንልኝ ገባኝ። ልጄን ለማሚ ልሰጣት እንደሆነ ስነግረው "በፍፁም!" ብሎ በጣም ተጣላን።

"ልጄ ናት በልጄ ላይ የመወሰን መብት አለኝ!" አለኝ

"ያ ማለት ሰይጣንህ ሲመጣ እየወረወርካት ማለት ነው? ይቅር አልማር? ከዛ ቁጭ ብዬ ልጄን ላሳድግ? ያውም ባሻህ ጊዜ እየጠፈጠፍከኝ?" ይሄ ድክመቱ ነው!! ብቻ ከብዙ ጭቅጭቅ በኋላ ተስማማ ግን ለሚቀጥሉት ብዙ ቀናት የፀብ እርሾ ሆነ። 'ልጄን ቀማሽኝ' የሁል ጊዜ ፀብ ሁለት ነጥብ ሆነ::

መስከረም መጥቶ ትምህርት ሊጀመር ሲል ፀግዬ 6 ወሯ ነበር። ለማንም ስለእሱ አንዲት ነገር ተናግሬ አላውቅም። ልጄን እያጠባሁ ወስጄ ለእናቴ ሰጥቻት ተመለስኩ። ከመሳሳቴ የተነሳ ብዙ ጊዜ ሀሳቤን ልቀይር ዳዳኝ።

'ለምን ትምህርቱ ራሱ ጥንቅር ብሎ አይቀርም ልጄን ለምን አርፌ አላሳድግም እኔ ከሌሎች ሴቶች በምን ተለይቼ ነው ዓላማ ቅብርጥሶ እያልኩ የምጋጋጠው? ወይም ለምን ልጄ ከፍ ብላ ትምህርት ቤት ስትገባ ከዛ አልማርም?' ብዙውን አሰብኩ

የጡቴ ወተት ሞልቶ ማጅራቴን ህመሙ እያሰቃየኝ ከሀዋሳ አርባምንጭ እንባዬን እየዘራሁ ልጄን ትቼ ተመለስኩ። እንደዛ እንደምሆን ገብቶት ስለነበር ፈቃድ ወስዶ ምግብ ሰርቶ ቤቱን አስተካክሎ ጠበቀኝ። እሱን ሳገኘው ጭራሽ ማን ይቻለኝ ? በነገታው ተመልሼ አልፈልግም በቃ ልጄን ስጡኝ የምል ነበር የመሰለኝ። ለቀናት አለቀስኩ:: እየደወልኩ መንሰቅሰቅ ስራዬ ሆነ ..
ሁለቱን ባሎቼን ላስማማ እያሸማገልኳቸው ነው
(ክፍል ሰባት)

ይሄ ሁሉ ሲሆን በጌታ ነን 🤣🤣 በጌታ ፍቅር ጥላ ስር ሆነን ነው የምንፋቀረውም የምንቧቀሰውም። ቸርች እናስመልካለን። የምሬን የምፀልይለትስ “ጌታ ሆይ ቁጣውን እንዲገታ እርዳው” ብዬ እሱ በተቃራኒው “ጌታ ሆይ ዱላዬን የምትችልበት ፀጋ ስጣት!” እያለ እየፀለየ ይሁን እንጃ አይደለም ተመትቼ ጮክ አድርገው ተናግረውኝ ቤት የማምስ ልጅ ዝም አልኩ ......... ውርድ አልኩ.....

"ትቼለትለሁ የእኔን ጉዳይ ትቼለታለሁ የእኔን ታሪክ
መላ አለው እንዴት እንደሚያደርግ ያውቃል
ዘዴ አለው እንዴት እንደሚያደርግ ያውቃል"

የሚለው የሊሊ መዝሙር እየዘመርኩ ስነፋረቅ አመሻለሁ። ዛሬም ድረስ ስሰማት እንባዬ ይመጣልኮ

ጎበዝ ተማሪ ከመሆን ውጪ ለሌላ ምንም ምርጫ ጭንቅላቴ ዝግ ነው። ገና ትምህርት ቤት እንደገባ ህፃን ቦረቅኩ ሰው በማትስ ይወሰወሳል? በቃ በትምህርት ጠፋሁ ...... ከሱ ውጪ ጓደኞች ኖሩኝ። Bilen ቢዬ መጣች ...... ሳልነግራት ገባኋት። እሱን እንዴት እንደምወደው ማውራት ከጀመርኩ የሚሰማኝ ሁሉ ጤንነት አይመስለውም። ጓደኞቼን አስተዋወቅኩት ወደዱት። እያደር እየዋለ ግን በአጠገቤ ዝንብ ራሱ ብታልፍ ጾታዋን ማጣራት ጀመረ። እንዴት እንደምወደው እንዴት እንደማይገባው ይነደኛል። ወንድ አይደለም እኔ አይቼው እሱ አይቶኝ ነገር አከተመ። ችግሩ ትምህርት ቤት ውስጥ አንድ ነጠላ ማገር በህይወቷ ዝንፍ ያለባት የማልመስል ተጫዋች ነኝና ወንዱም ሴቱም ይቀርበኛል። እቤት ስመጣም ቆንጆ ነገር ይቀርብልኛል። "ቅድም አብሮሽ ሲገለፍጥ የነበረው ልጅ አስተያየቱን አልወደድኩትም ሁለተኛ አብረሽው እንዳላይሽ"

ቆዩኝማ መሆን የነበረበትኮ ተቃራኒው ነው። እኔ ነኝ መቅናት የነበረብኝ። ቁመቱ ሜትር ከ83 ሰውነቱ ገራሚ አይኖቹ ጥርሱ ከንፈሩ (ልጆቼን አይታችሁ መስክሩኣ?) የትም ቦታ ሄደን ሲያወራኮ ሴቶቹ አፉ ውስጥ ሊገቡ ትንሽ ነው የሚቀራቸው ሲቀልድ ሲያምርበት ሲኮሳተር ግርማ ሞገሱ ሲደመጥ (እየቀለድኩ አይደለም! አሁን ይሄንኑ ታሪክ እየነገራችሁ ያለው እሱ ቢሆን ተከርብታችሁ እንዲህ እየወደደሽ ቢቀጠቅጥሽ ምናለበት ቻዪው ነበር የምትሉኝ!! ፍቅርንማ እሱ ያውራት) የትም ብወስደውኮ ኩራቴ ነው:: ሁሉም ሰው ይወደዋል። እሺ በዚህ ላይ ፍቅር ችሎበት ..... በዚህ ላይ ስለምንም ርእስ ቢነሳ በሃሳብ መከራከር ችሎበት.... በዛ ላይ ጉዳዩ ላይ ጉድ አርጎኝ (ከዛኛው እሱ ውጪ ሌላው ነገሩ እኮ በምድር የሌለ ሰው ነው።)

የተለወጠው ነገር ልጄን ለማሚ ሰጥቻት ከመጣሁ በኋላ በጣም ተሰብሬ ስለነበር ድጋሚ እንዳይሰብረኝ ራሱን ይፈራው ነበር። ሲናደድ መማታቱን ትቶ ጥሎኝ ይወጣ ጀመር። እንደመፍትሄ የወሰድነው ያንን ነው። ከዛ ግን ትምህርት ቤት መዋሌ ለኔ ሳቅ ሲጨምርልኝ ለሱ ስጋት ሆነበት። አስተማሪዎቼን የክፍል ተማሪዎችን በሙሉ ማለት በሚቻል ደረጃ ያውቃቸዋል።

አንድ ቀን የሆነ ርእስ ተሰጥቶን በግሩፕ በተማሪ ፊት ከግሩፑ ሁለት ሰው ወጥቶ present ሊያደርግ አሳይመንት ተሰጠን። ከኛ ግሩፕ እኔና ሙሄ የሚባል ጓደኛዬ ተመረጥን። በደስታ ተቀብለን ተዘጋጀን!! የሚቀርብ ቀን 60 የማይሞላ ተማሪ ፊት ወጥቶ ለማቅረብ ፈራሁ። እኔ ሜሪ ሰው ፊት መቆም ፈራሁ ....... በ10 ዓመቴ በሺዎች ፊት ቆሜ ግጥም ያነበብኩ ልጅ ........ ማንንም ፈርቼ የማላውቅ ልጅ እጄን ሲያልበኝ አገኘሁት ........ የምወደው ነገርኮ በሰዎች ፊት ቆሞ ያን ሁሉ ጆሮ መያዝ ነበር .... የዛን ቀን ፍቅሬን ላለማጉደል ራሴ እየጎደልኩ እንደሆነ ገባኝ። "ደህና ነሽኣ?" ይለኛል ሙሄ መቶ ጊዜ ..... ይግባው አይግባው አላውቅም " ፈሪ ሆኛለሁ ማለት ነው!" አልኩት

"አንቺ? እኮ አንቺ ... በይ አትቀልጂ ..." ብሎኝ የሱን ፓርት ቀጠለ

የሆነው ሆነና ጨርሰን ስንወጣ አስተማሪያችን ለባሌ "ሚስትህ በራስ መተማመኗ ምናምን ...." ብሎ አዳንቆ ነግሮታል። ያለፉትን ዓመታት ምርጥ ከሚባሉት ትምህርት ቤቶች ውስጥ በአንደኛው ስለተማርኩ ጥሩ መሰረት ነበረኝ። ...... እና ባልዬ ሊኮራብኝ ሲገባ (የትኛው ሰይጣን ሹክ እንዳለው መድሃንያለም ብቻ ነው የሚያውቀው) አቴንሽን ፍለጋ ሆነ ብዬ ሰበብ እየፈለግኩ ተማሪ ፊት እንደምቆም ነገረኝ። ከተፈጠረው ነገር ጋር ተደማምሮልኝ የዛን ቀን ፀቡን እኔው ጀመርኩት። ልክ ከሆነ ነገር እንደነቃ ሰው ሁሉም ነገር ዛሬ እንደተገለጠልኝ ነገር። ..... የተዋበች ቡጢዬን ቀምሼ ባበጠ ፊቴ ትምህርት ቤት ገባሁ። ወድቄ ነው አልኩ። ... ለመጀመሪያ ጊዜ ባሌ መታኝ ብዬ ለሰው ተናገርኩ። ለቢዬ !! ምሳ እየበላን ብቻችንን ቁጭ ብለን ነገርኳት። እቤት ስመጣ ግን ከፋኝ!! እሱን ማንም በዛ መንገድ እንዲያውቅብኝ አልፈልግማ!! ማንም እሱን ከዛ ማንም ከሚያውቀው ተወዳጅ ስብዕናው እንዲያወርደው አልፈልግም!!

አንዳንዴ ምልክት ኖሮኝ ትምህርት ቤት እገባለሁ:: ሙሄ "እሺ ዛሬስ ምንላይ ወድቀሽ ነው?" ይለኛል:: ቢዬ ታውቃለች:: .... የልጄ ናፍቆት ሊያስነቅለኝ ይደርሳል:: እንዲያም ሆኖ ዓመቱ አለቀ::

ማትሪክ ሰኞ ልፈተን ቅዳሜ እሱ ታመመ። ቅዳሜ ለሊት ሀኪም ቤት ሄድን። እጄ ላይ ያለው ገንዘብ 1000 ብር አይሞላም። ለሊት 6 ሰዓት ገደማ ነው። አሁኑኑ መተኛት አለበት ሰርጀሪ መደረግ አለበት ተባልኩ። የሆስፒታሉ በረንዳ ላይ በቂጤ ዘጭ ብዬ ተቀመጥኩ።

"ለምን? ምን አድርጊ ነው የምትለኝ? ለምንድነው አንዱን በአንዱ የምትጭንብኝ? እላይ ሆነህ ሙድ ነው የምትይዝብኝኣ? ለመሆኑ ትሰማኛለህ ግን?" ከሰው ጋር እንደሚያወራ ሰው ከእግዜሩ ጋር ጭቅጭቅ ጀመርኩ። ገንዘብ ልጠይቀው የምችለው ብቸኛ ሰው በዛ ሰዓት ቢዬ ብቻ ነበረች። ደወልኩላት!! ከእናቷ ጋር ሲመጡ ሳያቸው ላለማልቀስ ታገልኩ። ተኛ። ሆስፒታል እያደርኩ ፈተናዬን ተፈተንኩ።

ከሆስፒታል ሲወጣ ብር ስላልነበረኝ እናቴ ለሰርጌ የሰጠችኝን ወርቆች ሸጬ የሚደረገውን ሁሉ አደረግኩ። ሳድግ እንዳየሁት ሰው ከታመመ በግ ይታረዳል:: ወግ ነው ብዬ በግ ገዝቼ አሳረድኩ:: (እራሴው እንባባባባ ብል ይሻለኝ ነበር) ሲሻለው በቀረኝ ብር ለልጄ የሆነ የሆነ ነገር ገዝቼ ልጄጋ ሄድኩ። አንዳንዴ ምኑም አይገባኝም። ወርቆቼን እንደሸጥኳቸው ሲያውቅ እኔ ለሱ ብዬ የምሄደው ርቀት ሳይሆን የታየው "ለምን አልነገርሽኝም" ብሎ መቀወጥ ነበር። ደከመኝ። ልቤ ዛለ ...... የምር ደከመኝ። ..... ምን ባደርግ ደስተኛ እንደሚሆን አላውቅም:: ያስቆጣዋል ብዬ የማስበው ነገር ምንም ሳይመስለው ያልፋል:: ጭራሽ ያልጠበቅኩት ነገር እብድ ያደርገዋል:: ክረምቱን ልጄጋ ከሱ ተለይቼ አሳለፍኩ። እዛ እያለሁ ውጤት መጣ።

ውጤቴ መጣ። ከትምህርት ቤቱ ከፍተኛውን ውጤት አምጥቼ አለፍኩ። ቅብርር ያለ ውጤት አምጥቼ። ውጤቴን ያየልኝ እሱ ነበር። በስልክ እየነገረኝ አላስጨረስኩትም ሳቅና ለቅሶዬ ተደባለቀብኝ። ነፍስ ዘራሁ ነገር..... አለሁኝ አልኩ.... ለእናቴ ስነግራት እልልልልልልል አለች። አባቴ ውጤቴን ሲሰማ አቀፈኝ። በቃ ዝም ብሎ ለደቂቃዎች አቀፈኝ። ምንም ሳይናገር ሁሉንም አለኝ። .... ልጄ ይህቺ ናት ያለ መሰለኝ...... ኮራሁብሽ ያለ መሰለኝ..... ከዛ በኃላ ምንም ዳገት የሚወጣ አቅም እንዳለኝ አመንኩ:: .... ትችያለሽ አልኳት ራሴን!!!

የዛኔ ልክ ውጤት ሲመጣ ነበር የትምህርት ምርጫችንን የምንሞላው።

"አባ በቃ ሙላልኝ እና አስገባ!" አልኩት ምክንያቱም የትና ምን እንደምፈልግ ያውቀዋል። እኔን
የሚያውቀኝ በሙሉ ያውቃል ህግ መማር እንደምፈልግ። ከተማ የመጀመሪያ ምርጫ ሀዋሳ ሁለተኛ አዲስ አበባ

ወደ እሱጋ ተመልሼ መጣሁ:: አቃቤ ህግ ነሽ ወንጀለኛ መቅጫ ብቻ ሊጠቅመኝ ይችላል ብዬ የማስበውን በሙሉ መፅሃፍ ከላይብረሪ እያወጣሁ ማንበብ ሆነ ስራዬ እዚህ ወቅት ላይ ምንም ተጨማሪ ፈጣሪዬን የምጠይቀው ነገር አልነበረኝም።

አዳራሽ ውስጥ ተቀምጠን በፕላዝማ ምድባችን ሲነገር ስሜ ብቅ አለ አርባምንጭ ዩንቨርስቲ FBE Faculty ...... ተማሪው አብሮኝ “WHAT?” አለ.... ዓይኔን ማመን አቃተኝ...

እግሬ እንዴት እየረገጠልኝ እቤት እንደደረስኩ አላውቅም። ለመጀመሪያ ጊዜ እሱ ከልቤ ግምስ ሲል ታወቀኝ። ለመጀመሪያ ጊዜ ልለየው እንደምችል አሰብኩ። በቃ ለመጀመሪያ ጊዜ ሞልቶ ከጠበበው ልቤ ሲቀነስ ታወቀኝ።

"እንኳን ደስ ያለህ እዚሁ ነው የደረሰኝ" አልኩት ማታ ሲመጣ

"እማ እርቀሽኝ እንድትሄጂ ስላልፈለግኩ ነው። ....ስለማፈቅርሽ አንቺን ላለማጣት ......." እንባው ለመጀመሪያ ጊዜ የማንም ሰው እንባ ዓይነት ሆነብኝ።

"አላሳዝንህም? ቢያንስ ህግ እንደምማር አምኜ ያን ሁላ መፅሃፍ በፍቅር ሳነብ 'እማ ተይ የሞላሁልሽ ሌላ ነገር ነው እንዲህ አትልፊ አትለኝም?' ልቤ እንደሚሰበር መገመት ከባድ ነበር? አላሳዝንህም? የ5ተኛ ክፍል አስተማሪዬ እንኳንኮ ህግ መማር እንደምፈልግ ያውቃል። እንዴት አንተ ከአይንህ እንዳታጣኝ ህልሜን ትቀማኛለህ? እስቲ ራስህን ጠይቅ የእውነት ትወደኛለህ? እኔስ ራሴን ነጥቀኸኝ... ህልሜን ነጥቀኸኝ ... ከዛም ዝም ብዬ ማፍቀሬን ልቀጥል?"
......
.....
.....
................ አልጨረስንም.................

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ሁለቱን ባሎቼን ላስማማ እያሸማገልኳቸው ነው
(ክፍል ስምንት)

'ጊቢ ግቡ' እስኪባል ድረስ ምን መወሰን እንዳለብኝ ግራ ገባኝ። ማንም FBE በLAW እንደማይቀይረኝ እያወቅኩ ሞከርኩ። ላለመማርም አስቤያለሁ። ከዛ ልጄን ይዤ የሆነ ቦታ እልም ብዬ መጥፋት ....... ማንም የማያውቀኝ ቦታ ሄጄ ከዜሮ መጀመር። በእኔ እልህ ልጄን ማስከፈል የማይታሰብ ነው። እጅ መስጠትም ምርጫዬ አልሆነም። ልክ ጊቢ ግቡ ሲባል አሁንም አቧራዬን አራግፌ ተነሳሁ ....... እማራለሁ ........ ጥሩ ውጤት አመጣለሁ ..... ለሚጠብቀኝ ሁሉ ኩራት እሆናለሁ ...... ከማንም በላይ ራሴን እና ልጄን አኮራለሁ ........ ቀና ብላ የምትሄድ ሴት እሆናለሁ ....... ህይወቴን ሳሸንፍ የሆነ ቀን ህግ እማራለሁ። ራሴን ሳፅናና "ያውም ህግ መማር የምፈልገው ወንጀል ነክ መፅሃፎች ለመፃፍኣ? እደርስበታለሁ"

እሱን? ግራ ቂጡን ትወጋዋለች ብላችሁ ነው የምትጠብቁትኣ? አልገባችሁም ግራ ቂጤ እስኪጨስ እንደማፈቅረው።

"አምላክ ሆይ እባክህ ለሱ ያለኝን ፍቅር ውሰድልኝ አልችልም ብዙ ነው" ብዬ የምፀልይ ሰገጥ እንደሆንኩ አልገባችሁም። በዚህ ሁሉ ውስጥ እንዴት እንደምወደው ቢያውቅልኝና ድሮ እንደማውቀው 'እሱ' ፍቅራችንን ብንኖረው ስለቴ እንደሆነ አልገባችሁም። በዚህ ሁሉ ውስጥ ለነገ አብሮ ኑሮኣችን መሰረት ይሆነናል ብዬ ከወር ደሞዙ ላይ የሚከፈል መሬት በሊዝ እንደዳስገዛሁት አታውቁማ (ለዛዛ በሉኝ ስትፈልጉ።)

እናም ተውኩለት "ይቅር ብዬሃለሁ" አልኩት "ካንተ አይበልጥብኝም!" አልኩት በአዋቂ ደንብ ቁጭ ብለን አወራን (እኔ 20 ዓመቴ እሱ 25 ነበርን ይሄ ሲሆን ለሚያጠፋቸው ጥፋቶች ለራሴ ከምሰጠው ምክንያት አንዱ 'ስላልበሰለ ነው ወደፊት እንዲህ አይሆንም' የምለው ነገርስ? የሆነች አሮጊት ሴትዬማ ውስጤ ነበረች )

"ይሄን ማሪኝና ሁን ያልሽኝን ልሁን" አለኝ። ከዛም እሱም የማታ ኢኮኖሚክስ MA ሊማር ተመዘገበ።

ጊቢ የገባሁ ቀን አብሮኝ ሄደ። ከዘበኛው የጀመረ በጋሞኛ ሰላምታ እየሰጠ ሚስቱ መሆኔን አበክሮ እየነገረ። ፕሮክተር ነሽ ወጥ ቤት ያልዞረበት የለውም እጄን ይዞ ....... እንዴት እንደሚያወራ ያውቅበታል። ስቆ አያውቅም የሚባል ሰፊ ፊት ማስፈታት ያውቅበታል።

"ባልሽ ግን 'የሜሪ ባል ነኝ' እያለ ራሱን የሚያስተዋውቀው ማነሽ ብሎ ነው የሚያምነው ሴሌብሪቲ ነው እንዴ የምትመስዪው?" ብሎኛል አንዱ የአርክ ተማሪ 'ሚስቴ ናት' ሲል ኩራቱን አይቶት .....

አብረን ዶርም ድረስ ሄድን:: አልጋዬን አንጥፎልኝ። ዶርሚተሪዎቼን ተዋውቆ ሲያስቀን ቆይቶ ወደቤት ተመለሰ።

"ወንድምሽ ነው?" ሲሉኝ የምበሳጨው መበሳጨት

"ባሌ ነው። የልጄ አባት እሺ" እላለሁ:: በነገታው አዳዲስ ልብሶች ገዝቶልኝ መጣ። ግራ ገባኝ ምክንያቱም ብር እንደሌለው አውቃለሁ። ከሁለት ቀን በኋላ እቤት ስሄድ ቴሌብዥኑን እንደሸጠው አየሁ። እኔ እንደሱ 'አልበላ አልጠጣ ብዬ የገዛሁትን ...... እንዴት አትነግረኝም' አላልኩም:: ዶርም የገባሁ ቀን ቱታ እንደለበስኩ ነው የሄድኩት ሴቶቹ ዘንጠው ሲያያቸው ሚስቴ ከነሱ አትነስብኝ ብሎ እንዳደረገው ገብቶኛል አቅፌው አለቀስኩ ብዙ እንደምወደው ነገርኩት.....

እኔ የሀብታም ልጅ አይደለሁም። ግን ቤተሰቦቼ ባላቸው አቅብጠውኝ ነው ያደግኩት። እሱን እስካገባሁበት ሰዓት ድረስ እግሬን ሰራተኛ ያጥበኝ ነበር። ሀብታሞች የሚማሩበት የግል ትምህርት ቤት ነው የተማርኩት። ይሄ ሁሉ ሆኖ ካነበብኳቸውም መፅሃፍት ሆነ መፅሃፍ ቅዱስ ከሚታየው የላይ ለውጥ ራሴን ውስጤን ስለመቀየር እንድጨነቅ ነው አብዝቼ የተማርኩት። ልብስና እህል በፍፁም ብርቄ አይደሉም። ስለእውነቱ ከእኩዮቼ በተሻለ የምፈልገውን በእድሜዬ አጊጫለሁ። እዛ እድሜዬ ላይ ቁሳቁስ የሚያሳስበኝ ሴት አልነበርኩም። ሀብት ካፈራሁ የምመኘው ከእርሱ ጋር ስለምናፈራው ሀብትና እኔና እሱ ከልጆቻችን ጋር ስለምንኖረው ድሎት እንጂ ጊቢ እገሊት የለበሰችው ቀሚስ ግድ የሚሰጠኝ ሴት አልነበርኩም። ለእሱ ግን ለእኔ የሚያስፈልገኝን አለማሟላት ሞቱ ነበር። የቤተሰቤ ቤት የሚናፍቀኝ ...... የማያቸው ሰዎች የሚያስቀኑኝ ይመስለው ነበር ....... ላስረዳው ይቸግረኛል።

ተማሪዎቹ ስልክ ስለነበራቸው የሱን ስልክ ለእኔ ሰጠኝ። 'ስትናፍቂኝ እኔ መጥቼ አይሻለሁ ስልክ እኔ ምንም አያደርግልኝም' አለኝ ስለእውነቱ ለእኔ ከሚያደርግልኝ በላይ ለእርሱ ያደርግለት ነበር።

አንደኛ ሴሚስተር አርባምንጭ ተማሪ በማባረር አንደኛ ነው ብለው አስፈራርተውኝ ስለነበር ድምፄን አጥፍቼ ትምህርት ላይ አደፈጥኩ። ያው በሳምንት ብዙውን ቀን ነው እሱጋ የማድረው ዶርም ያደርኩ ቀን ደግሞ ስለእርሱ እያወራሁ ሳደነቁራቸው አድራለሁ። እሱም በሳምንት ብዙውን ቀን ትምህርት ቤት ጊቢ ይመጣል። ማታ ከክላስ መልስ ጊቢ ውስጥ አቅፎኝ ሲንጎራደድ ትምህርት ቤቱን የገዛ ባለሃብት ነው የሚመስለው። የሚያየን ሁላ ታድለሽ ባልሽ ደስ ሲል እንዲህ ዓይነት ባል ቢኖረኝ' የማይቀናብኝ የለም።

ነፃነቴን በሆነ መልኩ እንደያዘው ባውቅም አልጎረበጠኝም። ለምሳሌ ከጠዋት እስከማታ የለበስኩትን ያገሳሁትን የበላሁትን የሄድኩበትን የፈሳሁትን ፈስ ቁጥር ልክ የሚነግሩት ሰዎች አሉት። አውቃለሁ። ከእሱ ተደብቄ የማደርገው ነገር ስላልነበረ ግድ የለኝም። ቢበዛ 'ዛሬ ለብሰሽ የነበረው ቦዲ ግን አልሳሳም? ደረብ አታደርጊም?' ቢለኝ ነው። ወይም ከጓደኞቼጋ ሻይ ልንጠጣ ወደከተማ ስንወጣ ከየት መጣ ሳንለው ዱብ ብሎ ሰላም ብሎን ይሄዳል። ወይም ስንጨርስ 'ባልሽ ሂሳብ ከፍሎላችሁ ነው የሄደው' እንባላለን ሳናየው

"ይሄ መንፈስ የሆነ ባልሽ ትከሻዬ ላይ ዱብ እንዳይል" ይሉኛል ጓደኞቼ ሙድ ሲይዙ የሆነ ቦታ ስንሄድ

ደስተኛ ሆንኩ። ደሞኮ ብዙ የማልፈጀው ነገሬ ..... በቃ ደስተኛ አደረገኝ ...... የመጀመሪያ ሴሚስተር ውጤት መጣ። ሁሉንም ትምህርት A ሳመጣ ካልኩለስ B አመጣሁ። ካልኩለስ አስተማሪያችን ሴት ናት (ይሄን ፅሁፍ አታየውም ብዬ ተስፋ ላድርግ) ቂጧ ትልቅ የሚያምር ...... ስታስተምረን ፊቷን አዙራ አዳሜ ይቸክልና ልክ ስትዞር ሁሉም በልቡ ኤጭ የሚል አይነት ይመስለኛል። ያልሰራሁት ጥያቄ በጣም ቀላሉን ስለነበር በዛ ላይ ሴት መሆኔ በዛ ላይ ሌሎቹን በሙሉ A ማምጣቴ ይመስለኛል ቢሮ አስጠራችኝ።

"ከባዱን ሰርተሽ ቀላሉን ነው የሳትሽው" አለችኝ

"ካልኩለስ የመጨረሻ ቀን አልነበር? የልጄ ልደት ነበር ፈተናውን ቶሎ ሰርቼ ሀዋሳ መሳፈር ነበረብኝ ስቸኩል መሰለኝ የሳትኩት!" አልኳት

"ልጅ አለሽ?" አለችኝ

"አዎ ሁለት ዓመት ሆናት። ቤተሰቦቼጋ ነው ያለችው እኔና ባሌ እዚህ ነው የምንኖረው ብዬ " ያልተጠየቅኩትን መቀባጠር። ዝም ብልስ ኖሮ?
ደስ ብሏት ስታደንቀኝ ቆየችና ምንም ብፈልግ እንደምታግዘኝ ከጎኔ እንደሆነች እንደምታግዘኝ ምናምን ነገረችኝና

"ባልሽ እዚህ ከተማ ነዋሪ ነው?" አለችኝ ባትጠይቀኝስ እሷስ ቢቀርባት? እኔ ደግሞ ስለእሱ እንኳን ተጠይቄ ሳይጠይቁኝ የፍቅር እስከመቃብርን ትረካ ያህል ክፍሎች ያለመታከት እተርካለሁ።

"አዎ እገሌ ይባላል! እንዴ ታውቂዋለሽኮ የማታ ታስተምሪዋለሽኮ ስላንቺ እንደውም አውርቶልኛል .... ረዥም እንኳን .... ጠይም ቆንጆ ዓይኖቹ ትልልቅ ......" እኔ እለፈልፋለሁ እሷ ስሙን ከሰማች በኋላ ደንዝዛለች። በልፍለፋዬ መሃል አስተዋልኳት አሳዘንኳት ወይም ለራሷ አዘነች ወይም አላውቅም እጄን ጥብቅ አድርጋ ይዛኝ

"አንቺ ብርቱ ሴት ነሽ ምንም ነገር እን
ዳይበግርሽ እሺ? ልብሽን ጠብቂው በናትሽ። አደራ በርቺ" አለችኝ። እንስ ስል ታወቀኝ..... በቃ ቅንስ ...... ኩምሽሽ ።

ስለሷ ያወራነውን ሁሉ ገጣጠምኩት። ብትን ብዬ የምፈነዳ ነገር መሰለኝ። ከምሽቱ 4 ሰዓት ወደከተማ የሚሄደውን የመጨረሻ ታክሲ ይዤ እቤት ደረስኩ። በሩን በርግጄ እንደገባሁ ፈነዳሁ።

"አንተ በእኔ ላይ? ያውም ከአስተማሪዬ ጋር (ያውም ከዛ ቂጥ ጋር ብለው ደስታዬ ነበር?) ወይኔ ሜሪ !!

አበድኩ ሊሰደቡ የሚችሉ ስድቦችን ሁላ ብልግና ስድቦች ሳይቀር ለመጀመሪያ ጊዜ ተሳደብኩ። ብቻዬን እየተቀነጣጠስኩ ስውረገረግ ለመጀመሪያ ጊዜ ዝምምምምምም አለ።

...........አልጨረስንም ....

@getem
@getem
@paappii

#Meri feleke
ሁለቱን ባሎቼን ላስማማ እያሸማገልኳቸው ነው
(ክፍል ዘጠኝ)

ከሁሉም ከሁሉም ምኑ ያስጠላል መሰለሽ? ራስሽን ባልሽ ካባለጋት ሴት ጋር ማነፃፀር ...... መድቀቅ የምትጀምሪው እዚህጋ ነው ...... ራስሽን ከሆነ ሰው ጋር ማነፃፀር ስትጀምሪ በራስ መተማመንሽ እየተምዘገዘገ ይፈጠፈጣል። ከዛ በፊት ከማንም በልጣለሁ ወይም ከማንም አንሳለሁ ብዬ ራሴን ከማንም አወዳድሬ አላውቅም እራሴን እንዳለሁ እንደዛ በብዙ እወደዋለሁ። ደግሞ ምናለ ከሆነች ጥፍጥፍ ጋር እንኳን ቢያደርገው ......... ማለት ምንም ንፅፅር ሳያስፈልገው ቆርጥማ ትበላኛለች።

እንደው ለማረጋገጥ አለ አይደል ከወንዱም ከሴቱም 'እገሊት ግን ታምራለችኣ?' ብዬ ጠይቃለሁ? ሴቱ 'ልቅም ያለች ቆንጆ ናት!' ይለኛል። ወንዱ 'ፓ ቂጥዋ ይምጣብኝ!' ይለኛል። (ይኸው በሷ የለከፈኝ ....... ትልቅ ቂጥ ሳይ አንገቴ እስኪጠማዘዝ እየዞርኩ እሸኛለሁ። ሰርች ሳደርግ ራሱ ቂጥ ለማተለቅ የሚረዱ 10 የምግብ ዓይነቶች የሚል ነገር ዓይኔን ይጠልፈዋል።)

የዛን ቀን ማታ እቤት አላድርም ብዬ 6 ሰዓት ጊቢ በሚሄድ የሰራተኞች ሰርቪስ ዶርም ገባሁ። ደጋግሞ የሆነ ጥፋት ባጠፋ ቁጥር የማለቅሰው መጠን እየቀነሰ የህመሜ መጠን እየቀነሰ መጥቷል። ማሪኝ ባለ ቁጥር ይቅርታ ሳደርግለት እንደመጀመሪያው ሁሉ ነገር ይቀጥል ነበር። ሁለታችንም ያልገባን ቀስ በቀስ ፍቅራችንን እየገዘገዘው እንደሆነ ነው። መጀመሪያ ቢላ አንገቴ ላይ ያደረገ ቀን ለሳምንታት ነው ባሰብኩት ቁጥር ያለቀስኩት የዛን ቀን ማልቀስ ብፈልግ ራሱ አላለቀስኩም። ካደረገኝ ሁሉ የከፋ ነው ያልኩት እኮ ይሄንንን ነው። ግን እንባ እንቢ አለኝ። ይልቅስ ለመጀመሪያ ጊዜ እሱ የሌለበት ህይወቴ ምን ሊሆን እንደሚችል ከአሁኑ ጋር ማነፃፀር ጀመርኩ። እሱን መጥላት የምችልበት ጉልበት አይደለም የነበረኝ ራሴን መውደዴን መጨመር የምችልበት ጉልበት አገኝሁ። ..... ዳዴ ማለት ...... ያቺ እሱ ቢሆን የሚወዳት ሴት ብዬ የሆንኳትን ሜሪ አውጥቼ ጣልኳት። እሱ ስለሚሰማው ሳይሆን እኔ ስለምፈልገው ነገር መጨነቅ ጀመርኩ። የዛን ቀን እንቅልፍ በአይኔ ሳይዞር አደረ። ጠዋት ክላስ ቀርቼ ተኛሁ። ስነሳ መከፋቴ ልቤን ቢጫነውም ከሌላው ጊዜ በተለየ በማንም ላይ ያልተደገፈ መነቃቃት ውስጤ ነበር።

"ባልሽኮ ውጪ ተቀምጧል!" አለችኝ ጓደኛዬ ወደዶርም እየገባች

"ተይው ባክሽ ይቀመጥ!" ስል ራሴን ሰማሁት።

ለሳምንታት እንደዛ አደረገ። ሊያዋራኝ አይሞክርም። አይቶኝ ብቻ ይሄዳል። ሲበርድልኝ የሆነ ቀን 'እናውራ' ብዬ ጠራሁት እና ካፌ ተገናኝኝ። (እቤት ከሄድኩ እንደምቀልጥ አውቀዋለሁ።) አንድ ጥያቄ ብቻ ነው የነበረኝ።

"ለማያቅህ ሰው ሁሉ የሜሪ ባል ነኝ ብለህ ሳትጠየቅ የምታወራ ሰው ያውም እንደምታውቀኝ እያወቅክ ለሷ መንገሩ እንዴት አልመጣልህም?"

"አላውቅም እማ! ሁሉም ነገር በአጋጣሚ የተከሰተ ነው። የአንድ ቀን ስህተት ነው። እባክሽ ዲቴሉን እንዳወራ አታድርጊኝ። ላንቺ ማውራቱ ከሰራሁት በላይ ያማል።" አለኝ።

"እንለያይ?" አልኩት። የሰማውን ማመን አቃተው።

"እንለያይ! አባ እንዲህ እንዳፈቀርኩህ እንለያይ! አልጥላህ .... እውነቱን ልንገርህ በፊት እንደምወድህ አሁን አልወድህም! በዚህ ከቀጠልን ግን ጭራሽ ላልወድህ ነው። እኔ መኖር የምፈልገው ካሉን ጥሩ ትዝታዎች ጋር ነው። አንተን ሳስብ ካፈቀርከኝ ፍቅር በልጦ የጎዳኸኝ እንዲያመኝ አልፈልግም። ሳስብህ ፈገግ ማለት ነው የምፈልገው።" አልኩት

"አልችልም። እኔ አንቺን አጥቼ መኖር አልችልም። ቤተሰቤ እኮ አንቺ ነሽ! ማን አለኝ? እንለያይ? ከዛስ? ሰው አልሆንብሽምኮ! እማ እታመምብሻለሁ ተይ!" አለኝ (እሱ እውነት ነው ከኔ ውጪ ቤተሰቤ ብሎ የሚጠያየቀው የለም። ቤተሰቦቹም ከሁለቴ በላይ ደውለውልን አያውቁም። ዛሬም ድረስ የማይገባኝ የተወሳሰበ ግንኙነት ነው ያለው ከቤተሰቡ ጋር። ብቻ እንዲህ ሆንኩ የሚባባለው ቤተሰብ የለውም። ይሄም ሌላኛው ለራሴ ከምሰጣቸው ምክንያቶች አንዱ ነበር። ቤተሰቤ ለእኔ ምን ማለት እንደሆነ አውቃለሁና 'ከኔ ሌላ ማንም የለውም'

"እኔ ደግሞ እንዲህ መኖር አልችልም።"

"ልጃችንስ?"

"እኔ እየሞትኩ ለልጄ እንዴት ነው እናት የምሆናት?" (በዚህ ጉዳይ ያለኝን አቋም ያውቃል። እውነቱን ነው ልጄን ሳላስባት ቀርቼ አይደለም። ባሌ ለልጆቼ ጥሩ አባት ከሆነ መቻል አይከብደኝም ብዬ የማምን ዱዝ እንደሆንኩ ያውቃል።)

"እማ በፍፁም አይሆንም! እኔና አንቺ ገና ነጭ ፁጉር እስክናበቅል አብረን እንሆናለን። ፍቅርን እንወልዳለን (ፍቅር የሁለተኛ ልጃችን ስም ነው።) የፈለግሽውን ጊዜ ውሰጂ ብቻ ተመለሺልኝ .... አትተይኝ" አለኝ

ብዙ ነገር አውርተን። 'እንለያይ' ያልኩት ልጅ ከንፈሩን ስሜው የምለየውስ ነገር? ሸኝቶኝ ልንለያይ ስንል

"ካንተ ውጪ ከሌላ ወንድ ልጅ አልወልድም። ምናልባት ወደፊት ፍቅርን የመውለድ ሃሳብ ከመጣልኝ ትቸገርልኛለህ።" ብዬው ተሳስቀን ተለያየን። የእውነቴን ነበር ከሁለት አባት ልጅ አልወልድም።( እሱ ሌላ ታሪክ ነው ግን የራሴ ምክንያት አለኝ።) በዛ ላይ come on እሱኮ ጣኦቴ ነበር።

ወደ ዶርሜ ተመለስኩ። ከትምህርቴ በተጨማሪ ትምህርት ቤት ውስጥ የማልገባበት መድረክ ነገር የለም። እሱን የማስብበት ጊዜ እንዲኖረኝ አልፈልግም በተጨማሪ እሱ ደስ ስለማይለው ተውኩ እንጂ የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ላይ መሳተፍ እወድ ነበር። ብሄር ብሄረሰቦች ቀን ....የሴቶች ቀን ....ኪነጥበብ ምሽት ....ብቻ ምንም ይሁን ...... እንደቀይ ወጥ መሃል ላይ ዱቅ ..... ግጥም ....አጭር ልብወለድ .... ዘፈን መዝፈን ..... መድረክ መምራት .... ብቻ ምንም አልኩ ......የአባቶች ቀንም መድረክ አስመሩኝ ብዬ ከልክለውኝ ነው።

"ትቼለታለሁ የኔን ጉዳይ ..." ያልኩትን ጌታ ራሴ ትቼ

"ይማርሽ ይሉኛል አሜን ይማረኝ
አንተ ልጅ ፍቅርህ እንዳልሄድ ይዞኝ " ማቀንቀኑን ያዝኩት (የምሬን ነውኮ ይሄንኑ ዘፈን ጊቢ ዝግጅት ላይ ዘፍኜዋለሁ)

እኔ መድረክ ዝግጅት ሲኖርብኝ ወፎቹ ይነግሩታል። ይመጣል። ያየኛል። "ዛሬ ታምሪ ነበር" ብሎኝ ይሄዳል። እርግጥ አንዳንዴ "ይሄ ነገር ትንሽ አላጠረም?" ይላል። በሱ እልህ የሃመሮቹን ቆዳ ብለብስ ራሱ ውስጤ ነበር። ወደቤቴ ሳልሄድ ወራት አለፈ። መጥቶ ያላየኝ አንድም ቀን የለም። እንለያይ ካልኩት በኋላ ግን ቢያንስ ሰላም እንባባላለን። 'ምንድነው አንተ እህል አትበላም እንዴ? ከሳህኮ?' 'ምንድነው ሸሚዝህን አትተኩሰውም እንዴ?' ዓይነት ንግግሮች አሉበት። በጠዋት አንድ ቀን አይኔን ስገልጥ ጊቢ ሳየው 'ለመሆኑ ቁርስህን በልተሃል?'ነው መጀመሪያ ከአፌ የወጣው።

ሀቁንኣ የምናወራው? በጣም ከመናፈቄ የተነሳ ብዙ ቀን "በቃ አባ ይቅር ብዬሃለሁ ወደ ቤት እንሂድ" ልለው አስቤ አውቃለሁ። ሰላም ስንባባል አለው አስተቃቀፍ ውስጡ ክትት የሚያደርገኝ ለቅጽበት የሆነውን ሁላ እርስት የሚያስደርገኝ። እልሄ ያንን ያልፍ ነበር።

የሆነ ቀን አስተማሪያችን ቢሮ አስጠራችኝ። ምንም የሚያገናኘን ኮርስ ስላልነበረ እየገረመኝ ሄድኩ። ገና እንደገባሁ ቀለበቴን እጄ ላይ ቼክ ስታደርግ አየኋት::

"አላወለቅኩትም" አልኳት

"እባክሽ አታውልቂው በናትሽ። የልጅሽ አባት ነው። ይቅርታ ልጠይቅሽ ነው የጠራሁሽ። በጉዳዩ መጠየቅ ካለብኝ እኔም ነኝ ጥፋተኛ! እኔም እሱም አስበን ያደረግነው ነገር አይደለም። እናቴ ትሙት ባለትዳር መሆኑን ግን አላውቅም ነበር።" እያለች ነገሩን ስታብራራልኝ
እኔ ያደረጉት ነገር በስዕል መልክ እየተከሰተብኝ ደሜ መንተክተኩን አልክድም። ብዙ መጠየቅ የምፈልገው ነገር ነበር ዲቴሉን ማወቅ ህመም እንጂ የሚሰጠኝ መልስ እንደሌለ ሳውቅ ተውኩት። ከእርሷ ጋር ያወራሁ ቀን ድብዝዝ ብሎ የነበረው ቁጣዬ ፈላ!! ማታ ላይ ሳየው ሀገር ሰላም ብሎ ሲያቅፈኝ። ለነገር ሲሊፐሬን አቀብሉኝ አልኩ። ... ሌላ የማላውቃት ሴትዮ ከውስጤ ወጣች .... እያለቀስኩም እየተሳደብኩም... እየተራገምኩም..... የሆነ የማልወዳት የመንደር ነገረኛ ሴት ነገር ሆንኩ:: ........ ... ዝም አለኝ። በሚቀጥለው ቀን አልመጣም። .......... ማለት ሲቀርብኝ ጠበቅኩትኮ። 'እንለያይ' ብዬው ነበርኮኣ? ምን ሆኖ ይሁን ብዬ ስጨነቅ አደርኩ። በሚቀጥለውም ቀን አልመጣም። ማታ ላይ ማሚ ደወለችልኝ።

"በይ ነይ እቤት እየጠበቅኩሽ ነው!"

"የት ቤት ነው?"

"እቤትሽ!"

"አርባምንጭ ነው?"

"አዎ!" ማሚ ከሀዋሳ ልትመጣ የምትችልበትን ምክንያት ማሰብ ቸገረኝ። .... የሆነ ነገር ሆኖ ቢሆን ግን ድምፅዋ እንዲህ አይረጋጋም::

....................... አልጨረስንም................

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
……… ርዕሱን አላውቀውም………


አተኩሬ አየሁት ፣ አየኝ . . . . ተንጋዶዋል ፣ ተንጋድጄበታለው………

ደብዛዛ ፊት፣ የጨፈነ ግንባር ፣ በሲጋራ ጢስ
የተፈረካከሰ ከንፈር ፣ በሃሳብ የተዳጠ እራስ
ያጨመጨሙ አይኖች ……… ግማሽ ሰው
. . .ግማሽ አካል . .

በድጋሚ አየሁት መንጋደዱ ትክክል ነው ። ቀጥ ብሎ አያውቅም ………

ሁለት መለክያ ውስኪ ይጎነጭና . . .

"ውሃ ልኬ ይሄ ነው " ይለኛል . . .

ሲቅም ፣ ሲያጤስም የውሃ ልኩ ነው . . . ብሎም ያምናል. . .

ማመን እሱ ጋር መሆን ነው ፣ መደረግ ፣ መጨበጥ ልክ እደ ሚጠጣው የውስኪ መለክያ።. . .

መጥመቂያ አፉን ስስመው ፣ ህቅ ፣ ህቅ እያለኝ ይጣፍጠኛል።


"በፀጥታ ነው ማስታውስሽ ፣ ተው እንዳትይኝ ፣ መንፈሴ ሲረበሽ እረሳሻለው ፣ ማስታውስሽ በዚህ መለክያ ውስጥ ነው. . . ." ይለኛል ሳልጠይቀው ፣ ሳልከለክለው. . . .

ብዙ ቀን ይረሳኝና ሊያስታውሰኝ ሲፈልግ. .

"እድትሄጅም ፣ እድትመጪም አልፈልግም ፣ ከመሄድሽ ግን መምጣትሽ የበለጠ ጣፋጭ ነው" ይለኛል።. . . . ስልኩን ዘግቼ እየበረርኩ ሄድለታለው። . .

. . . አይሰክርም ፤ ይሰክራልም። . . .

"ለምን እደምትለዪ ታውቂያለሽ?" ከሶስት መለክያ በኃላ ይጠይቀኛል. . .

እኔጃ . . . .

"አትቆጥቢኝም………"

በቃ እለዋለው እየከፋኝ

"በቃ " . . . ..


ዝም . . . ትካዜ የደኮነ ዝምታ . . .

* * *

በአንደኛው ቀን ላይ ………

" አርግዣለው " አልኩት

"ውለጂው ፣ ጠንካራ ሴት ነሽ ፣ በእውቀትም በገንዘብም አታቀነጭሪውም " ግድ የለሽ ሆኖ ነው የመለሰለኝ . . . ውስጡን ጠልቄ ለማየት ሞከርኩ ያው ነው. . . .

ትቼው ሄድኩ. . . .

. . . ከአራት ወራቶች በኃላ ደወለ. . . .

"አመሽኛል"አለኝ

ሄድኩለት. . . ሳይፈልገኝ ስሄድ ይጠላኛል ፣ እስከሚፈልገኝ ጠብቃለው።

"ልጅሽ አላደገም " ሆድ ፣ ሆዴን እያየ ፈገግ አለ. ,


" ልትነካው ትፈልግ ይሁን ?" መልሱ አዎ እንዲሆን እየተመኘው ጠየኩ. . .

"ሁለ……ቱንም " አለኝ . . . የወጡት ቃላቶች ሲሰባበሩ ወጉኝ . . . እሱንም እያመሙት ነበር. .

"ለምን. . ?"

"ሂጂ በቃ. . !"

"አሁን ነው የመጣሁት እኮ ጌት"

"ድኛለው ፣ ከቆየሽም ያመኛል"

ወጣሁኝ………

* * *

"አደራ ብሰጠው አደራ ልቤን
በልቶ ተገኘ አሉ በጣጥሶ አንጀቴን
የደከመን ገሎ ፉከሬ ምንድነው
ቀን የጣለው ለታ እሱም እንደኔ ነው
እርም የናቴን ስጋ እምልልሀለው
ፍቅር ካልሰጠኽኝ እሞትብሀለው
ያንእምቢ ያንእምቢ ስለመን ከርሜ
ይኽው ተጃጃልኩኝ ደግሜ ደግሜ " . . . ጂጂ እያዜመች እሱ እየሰማት ደረስኩ ጠርቶኝ . .

"ስንት ወር ቀረሽ "

"ሰባት ወሬ ነው "

"ለምን ጂጂን እደምወዳት ታውቂያለሽ ?"

"አይ………"

"በራሷ ውስጥ ነው የበቀለችው. . .ውበት እንዲህ ነው!" ሲጋራውን ተነፈሰው. . . እኔ ሳብኩት. . .

"ለምን እዲህ ሆንክ "

"ምን ሆንኩ " ተረጋግቶ ጥያቄዬን በጥያቄ አጣፋው. . .

ዝም አልኩ ………

"አፈቅርሻለው " . . . ደነገጥኩ አየሁት . . . ብሎኝ አያውቅም . . . ጠጋ አልኩት . . . ሳመኝ . . አይኔን ፣ ግንባሬን ፣ ከንፈሬን . . ጎንበስ ብሎ ሆዴን . . .

"እናቷ ስለምትሆኚ እድለኛ ነች !"

"ወንድ ነው !"


. . . .

"ዛሬ አልሂድ " ጠየኩት . .

"ነገ ነይ ፣ አትቅሪ " አለኝ . . . ተነሳው እጄን ያዘው
. . . .

"ሁለት ደቂቃ ልስማሽ "

"ምን ልንገርህ ?"

"ስሙን ማነው ምትይው?"


"አላወጣሁለትም "

"ዛብሎን . . . በይው "

"ምን ማለት ነው ?"

"መኖሪያ. መኖሪያ ቤት. . . ማለት ነው . . . ሁሉን ሚያኖር ሆኖ ያድጋል . . . አንቺ ስለሆንሽ እናቱ" አለኝ. . .

. . . ሳምኩት. . . .

* * *

ከስራ እደወጣው ቤቱ ሄድኩ . . . ገመድ አንገቱ ላይ ተንጠልጥሎ ዝም ብሎዋል . . .

* * *

ቀበርኩት ፣ አልቅሼ ሳይሆን ታምሜ ቀበርኩት ፣ ቆስዬ ፣ ተለብልቤ ለአፈር ሰጠሁት. . ሳልረዳው ፣ ሳላውቀው ፣ ሳይገባኝ ሸኘሁት . . .


* * *

ከብዙ ዓመታት በኃላ የዛብሎኔ ልጅ ጠየቀኝ

"አያቴ . . "

"ወዬ "

"ወንድ አያቴ . . . ምን አይነት ሰው ነበር?"

"በአባትህ ነው ማውቀው ልጄ " አልኩት!

######
/ትዝታ/
@tiztawe
@wegoch
@wegoch
@wegoch
ሁለቱን ባሎቼን ላስማማ እያሸማገልኳቸው ነው
(ክፍል አስር)

ልታሸንፈኝ የምትችለው እሷ ብቻ እንደሆነች ያውቀዋል። እንዴት ብሎ እንደነገራት አላውቅም። ግን እንዳልኳችሁ ነው ..... ይሄን ታሪክ እንኳን እየነገራችሁ ያለው እሱ ቢሆን እንዴት አንጀት እንደሚበላ ያውቅበታል። 'አንቺ ልዩ ነሽ' ያልሽ ሁላ ክርብት ብለሽ 'ምን ልሁን ነው የምትዪው?' ማለትሽ አይቀርም ነበር። በእርግጥ እንደወሰለተ ነው እንጂ የነገራት ሌላ ጣጣችንን አልነገራትም።

መፅሃፍ ቅዱሱ እንኳን ፍቺን የሚፈቅድበት ብቸኛ ምክንያት ውስልትና መሆኑን እያወቀች። እሱን አልፋ ስለይቅርታ ስትሰብከ አመሸች።

"ውይ አንጀቴን በላው! ሌላ መሄጃ የለኝም .... ጉዴን ልንገርሽና እንደፈለግሽ አርጊኝ ብዬ ነው አንቺጋ የመጣሁት አንቺው አማልጂኝ! ያለእሷ መኖር አልችልም ብሎ እግሬ ላይ ሲወድቅ አንጀቴን በላው! በጣም ነው የሚወድሽ" ብላ ጭራሽ ልትቆጣኝ ሁላ ዳዳት።

ከዛ ግን ለብቻዬ እንዲህ አለችኝ

"ትዳር አንዴ ከገባሽበት በኋላ ያውም ልጅ ካመጣሽ በኋላ በሰበብ አስባቡ ብድግ እያልሽ ወጥቼበታለሁ የምትዪበት አይደለም።" (በሰበብ አስባቡ አይደለምኮ ብዬ የሆነውን ሁሉ ልነግራት እፈልግና እተወዋለሁ። ምናልባት 'መጀመሪያ እረፊ ብዬሽ ነበር' መባልን ፈርቼ? ወይም 'ልክ ነበርሽ እሱን ተከትዬ መምጣት አልነበረብኝም' ማለት ሽንፈት መስሎኝ ወይም አሁንም ለእሱ ያለኝ ፍቅር እርሱን እንዳትጠላብኝ እንድሰስት አድርጎኝ። ዝም ብዬ ሰማሁ ብቻ)

"አግብተሽ ያውም ከልጅ በኋላ ብቻሽን ህይወትን መግፋት ለሴት ልጅ ከባድ ነው። አንቺ ገና ህፃን ነሽ ለዛ አልተዘጋጀሽም! ቅስምሽ ይሰበራል። ምንም አድርጎሽ ውጪ ዝቅ ተደርገሽ የምትታዪው አንቺ ነሽ። ምንም በደል ደርሶብሽ ትዳርሽን ፍቺ ያው ፈት ነሽ! የምታገኚው ወንድ እንኳን ፈት መሆንሽን ሲያውቅ ያጎድልሻል።" አለችኝ (ይሄኛው ምን ማለት እንደሆነ የገባኝ ዘግይቶ ነው።)

ከምክሩ በኋላ በዘይትም በእጅ መጫንም ተፀልዮልን። "በጌታ ስም ትዳራችሁ ካሁን በኋላ የሰይጣን ሴራ መጠቀሚያ አይሆንም። ልጆቼን ልትዋጋ በአየር በባቡር በየብስ ...... የምታንዣብብ በየሱስ ስም የከሸፈ ይሁን" ተብለን ታረቅን።

እኔና እሱ መሃል ሶስተኛ ሰው ገባ! ያ ለእኔ የትዳራችን መፍረስ ጅማሬ ነበር። በዚህ ሁሉ መሃል እያለፍን ሌላ ሰው የማይረዳው የእኔና የእሱ ስሜት አለ። በቃ ለሌላ ሰው የማይገባው ያንን ድንበር አልፈን ተጣልተን እንዲያሸማግለን ሶስተኛ ሰው ስንጠራ መግባባት አቅቶናል።

ክረምቱን ፀጊ መጣች እኛጋ። ሁሉ ሞላልኝ። እሱም ቦረቀ። ሁለቱን ወር እራሱ ፈጣሪ ተገልጦ 'ምን ልስጥሽ?' ቢለኝ

'እያየኸኝ? ከዚህ በላይ ምን እፈልጋለሁ?' ነበር የምለው። ደስታ አልፈጅም ብያችሁ የለ? በቃ ምንም ነገር ከዚህ ደስታ አይበልጥም አልኳ!! የልጄና የአባቷን መፍለቅለቅ እያየሁ ይሄን ቤት ለማቆየት መክፈል ያለብኝን እከፍላለሁ አልኳ!

አልኩ ነው እንግዲህ ........ ትምህርት ሲጀመር ጸግዬን ወደነበረችበት ወሰድኳት። ንትርኩ የተጀመረው ይሄኔ ነው። "ልጄ አብራኝ ትሁን!" አለ። እኔም ልጄ አብራኝ ብትሆን ደስታዬ ልክ የለውም። ግን የሚያስከፍለኝን ደግሞ አውቀዋለሁ። ልጄን እቤት እየተውኩ ምን አይነት ትምህርት ነበር የምማረው? ከዛ ደግሞ እነማሚን በቃ ልጄን ወስጃለሁ ካልኳቸው በኋላ የሆነ ቀን ቢባርቅበት አይ በቃ ደግሞ ትመለስ ልላቸው ነው? በዛ ላይ እዛ የለመደችውን ድሎት በሰዓቱ እኔ አልሰጣትም። የነበረው አማራጭ ሁለት አመት ታግሼ ልጄን በሙሉ አቅሜና ትኩረት ማሳደግ ነበር።

"ለሁለተኛ ጊዜ ልጄን ቀማሽኝ!" የንትርክ ሁለት ነጥብ ሆነ። ይችልበታል! እናም በዚህ ጉዳይ ሁሌ ራሴን እንድወቅስ ..... ራስ ወዳድ እንደሆንኩ እንዲሰማኝ አደረገኝ። እናም ይሄን ነጥብ አንስቶ ንትርክ ሲጀምር እንደጎዳሁት ስለሚሰማኝ ሁሌ ይቅርታ እጠይቀዋለሁ። እውነታውንኮ ልቤ አሳምሮ ያውቀዋል። ልጄን ባመጣት የሆነ ቀን ትምህርቴን አቆማለሁ። ግን ደግሞ እሱም ልክ ነው ልጁን ነው ከአጠገቡ ያጣው። እሱ እንደአባት ሃላፊነት ወስዶ ቀን ከሌት ልጁን ይንከባከባል ብዬ 100 % እሱን ማመን ልቤ ከበደው። ስለዚህ በራስ ወዳድነቴ ፀናሁ!!

ከዚህ በኋላ ያለው አንድ አመት አዙሪት ነው። እያንዳንዱን ዝርዝር ብፅፍላችሁ ምክንያቱና ሰዎቹ ይቀያየራሉ እንጂ ሂደቱ ያው ነው። አንድ ወር እፍፍፍፍ ብለን እንፋቀራለን ከዛ በሆነኛው ሰበብ እንጣላለን ወይ ይጠልዘኛል ወይ ሞልጬው ወደዶርሜ እመለሳለሁ። በነገታው ትምህርት ቤት ይመጣል እማ አይለመደኝም ይላል። ሁለት ቀን አኮርፋለሁ ከዛ ደግሞ እፍፍፍፍፍፍፍ .......

ደግሞ የሆነ ቀን እኔው ደሙን አፈላዋለሁ። እንፋታ በቃ መዝሙሬ ሆነች። ያብዳል። ይቅርታ እጠይቃለሁ ..... ደግሞ እንታረቃለን።
ለውጡ ምንድነው መሰላችሁ? ያቺ ምስኪኗ ሜሪ ድራሿ ጠፋ! ይህችኛዋ በራሷ የማትተማመን 'ሽቶ ሸተተኝ' ብላ ሀገር ይያዝ የምትል። (እርግጥ ሸቶኝ ነው። ፓንቱ ድረስ የሴት ሽቶ ምን ይሰራል? ) 'ደብዳቤ ሴት ፅፋልህ አልነገርከኝም' ብላ እሪሪሪሪ የምትል ........ ራሴን እያየሁት ሌላ ሰው ሆንኩ። በጣም የምጠላት እና ልሆን የማልፈልጋት መንቻካ ሴት ሆንኩ። በፊት እንዳይናደድ ሰማይ ከምድር የምገለብጥ ልጅ ሲናደድ እሳት ለኩሼለት ሄዳለሁ።

አሁን እንደበፊቱ ሰው ሰማ አልሰማ ችግሬ አይደለም። ይሄኔ ስንጣላም ስንታረቅ ጓደኞቼ ወይም ሰፈር ያውቃሉ። እርግጥ ዶርም ድረስ መጥቶ አንጥፎኝ ያውቃል እና ላያውቁ የሚችሉበት ሁኔታ አልነበረም። ብቻ አቡካካነው። ስንታረቅ ሁሉ እንደነበረ ቢመስለንም አልነበረም።

የሆነ ቀን ከአንዱ የፈረደበት ተማሪ ጋር የሙዝ ገበያ እያወራሁ እየገለፈጥኩ አምሽቼ ወደዶርሜ ገባሁ። መጥቶ ሲያስጠራኝ የነገር ዲዘርት ሊያበላኝ እንደሆነ ሳልጠረጥር ዊን ዊን እያልኩ ተንደርድሬ ወረድኩ። ሁለቱን እጆቼን ጭብጥ አድርጎ እያሳመመ አርገፈገፈኝ። የተፈጠረው ስላልገባኝ የያዘኝ እጁ ስለሚያም ለማስለቀቅ እታገላለሁ።

"ማነው?"

"ማነው ማን?"

"ቅድም አብሮሽ የነበረው? ከዛሬ ጋር ብዙ ጊዜ ነው አብረሽው የነበርሽው! ማነው?" ሲለኝ የፈረደበት ልጅ ትዝ አለኝ

"ኸረ ማንም አይደለም በጌታ ! ከሰው ሰው ጋር እንዳትጣላ?" ዘግይቻለሁ ልጁን ዘመዶቹን የሚያስረሳ ቡጢ ጠብቶት ነው እኔጋ የመጣው።
ልጁ ደግሞ ወሬ አማረልኝ ብሎ ከሰይጣን ጋር እንደተፋጠጠ ሳይገባው "ሜሪ ቀሽት ልጅ ናት" ምናምን ብሎ ዘላብዷል።እኔኮ ብድግ እያልኩ ባምፅም መጽሃፍ ቅዱስ ሳጠና እንደማደጌ እግዜሩን እፈራለሁ። መጀመሪያ የዘፈንኩ ቀን ዝናብ ሲዘንብ በኔ ምክንያት መብረቅ ሊዘንብ ነው ብዬ የፈራሁ ሴትዮ ነኝ። አንድ የሆነ ቆንጅዬ የክፍላችን ልጅ ቸኮሌት ገዝቶ ሰጥቶኝ ስለበላሁ በከፍተኛ የፀፀት መንፈስ የምናዘዝለት ካህን ባገኝ "አባ በድያለሁ በትዳሬ ላይ ማግጫለሁ" ልል ትንሽ የቀረኝ ሴትዮ ነኝ።

የዚን ቀን ዓይኖቹ ሲያስፈሩ
"የሌላ ሆነሽ ከማይ ገድዬሽ ሞታለሁ!" ያለኝን አመንኩት። የንዴት አይደለም። የምሩን እንደሚያደርገው ያስታውቅ ነበር።

የሚያውቀን ሁሉ "አንድ ቀን ይገላታል!" ይላል። የኔ ቤተሰቦች "የሆነ ነገር አድርጎባት!" ነው ብለው ወጥረው ይፀልያሉ። ጭራሽ ከጅምሩ ያልነበሩ የሱ ቤተሰቦች በተቃራኒው ባለቀ ሰዓት መጥተው "ልጃችንማ የሆነ ነገር ሆኖ ነው በሴት ፍቅር እንዲህ አይኮንም ፀበል ይግባ!" ይሉኛል ከነሱ ብሶ
ጓደኞቼ ቢሞቱ እሱን በእኔ ፊት አያሙትም።
ምንም ሆኜ ብመጣ

"ኸረ አርፈሽ
ቁጭ በይ እነሱ ነገ ታርቀው አልጋቸው ላይ ሆነው። 'ይህቺ ወሬኛ እንዲህ አላለች መሰለህ?' ሊባባሉብን ዝም በይ ነገ ይታረቃሉ" ይባባላሉ።

ደግሞ የምራቸውን ነውኮ 'ውይ በቃ ይሄማ የመጨረሻቸው ነው!' ሲባል በነገታው እኛ እፍፍፍፍፍፍ ብለን የሚሪንዳ ቆርኪ ለሁለት ሻወር ለመውሰጃ ይበቃናል። እንላለን። እዚህጋ ብጠየቅ ምን እዛ ትዳር ውስጥ እንዳቆየኝ አላውቅም። በየቀኑ አዲስ ነገር እንደማይፈጠር አውቃለሁኮ ግን በቃኝ አልልም። ምን እንደፈራሁም አላውቅም። ብቸኝነቱን ነው የምፈራው? ፍቺውን? እሱን ማጣቱን? አላውቅም ምናልባት እሱ ናት ያላትን ሜሪ እወዳታለሁ ይመስለኛል። ልዩ እንደሆንኩ እንዲሰማኝ የሚያደርገኝን ........ ብቻ አላውቅም። ለስድቡ ለምቱ ለሌላው ለእያንዳንዱ ጥፋት የራሴን ምክንያትና ሰበብ እደረድራለሁ። ለውስልትናው ግን ምንም ሰበብ ብሰጠው ልክ አይደለም። ልክ እንዳልሆነ እያወቅኩም አልፈዋለሁ። እንደበፊቱ አያምም ........ እንደመጀመሪያው አይጠዘጥዝም። ግን አዙሪት አለው ተመሳሳይ ሂደት እዞራለሁ!!

ቸርቹን እሱም እርግፍ አድርጎ ተወው ጭራሽ ክለብ ይዞኝ ወጣ። ድሮ በመዝሙር እንዳልተባረክን ሙዚቃ መገባበዝ ያዝን .....በዛኛው ህይወቱ ዲጄ ሁላ ሆኖ የሚያውቅ ቀውጢ እንደመሆኑ ሙዚቃ ምርጫ ሲያውቅበት ..... ማሪንጌ ሬጌ ፖፕ ብለን ጨፈርን። (እነዚን ሁሉ ነገሮች አላውቅም ለምን ብሎ እንዳደረጋቸው። እሱ አንቺን ለማስደሰት ደስ የሚልሽ መስሎኝ ነው የሚለው። )

ከዓመት በኋላ ለክረምት ፀጊ እኛጋ መጣች በድጋሚ። እንደተለመደው ፈንጠዝያችን ተጀመረ። ይሄኛው ክረምት ግን ከአንድ ወር አላለፈም። አሁን ምክንያቱን በማላስታውሰው ምክንያት ንትርክ ጀመርን። ጸቡ እየተጋጋለ ሲሄድ ልጄ ስላለች ዝም አልኩ። አልቀረልኝም አንዴ በጥፊ ሲለኝ ልጄን ነው ያየኋት ፊቷ ላይ የነበረው መሳቀቅ ድንጋጤ ፊቷ አመድ መሰለ። የተመታሁ አልመስልም። የእጁ ምልክት የተሰመረበትን ፊቴን እያሸሁ ልጄን ማባበል ጀመርኩ። ምንም አልተናገርኩም። በቃ ምንም !!!

ጠዋት እሱ ስራ ሲሄድ ቀለበቴን አስቀምጬለት ልጄን ይዤ ሄድኩ። አላለቀስኩም። አልተገረምኩምም። ውስጤ ዝም ነው ያለው። በቃ እንዳከተመ ገባኝ!! ራሴን ስሰማው የገባኝ አሁን እሱ ከህይወቴ ቢጎድል አልጎዳም! ሳላየው ሳምንት ሲሆን የማብድ የሚመስለኝን ባሌን ስለመለየት ሳስብ እርፍት ነው የተሰማኝ። እቤት ስሄድ ለማሚ መፋታት ነው የምፈልገው አልኳት። ገባት! ዝም አለች አልመከረችኝም። ምንም ቢመጣ እቀበላለሁ። ተመርቄ ስራ እይዛለሁ። ልጄን አሳድጋለሁ።

ስመለስ መነጋገር አለብን ብሎ የቀጠረኝ እሱ ነው። ተገናኘኝ!! ምንም ቢፈጠር የቃልኪዳን ቀለበቴን እንደማላወልቅ ያውቃል። የእውነት የሚመስለኝ የነበረው ያ ማለት ቃሌ ነው። ያ ማለት ፍቅሬ ነው። ያ ማለት እኔና እሱ ብቻ ማንም ሳያየን በእግዜሩ ፊት እንደሚስት በህመም በድሎትም ብዬ የገባሁት ቃሌ ነው። (እርግጥ ከገባሁት በላይ ኖሪያለሁኮ ስጠለዝም ሲማግጥም ብዬ የገባሁት የለም)

"እሺ እንለያይ!" አለኝ የምር ማመን አቃተኝ።



....... ....... አልጨረስንም ........

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ሁለቱ ባሎቼን ላስማማ እያሸማገልኳቸው ነው
(ክፍል 11)

"እሺ እንለያይ!" አለኝ የምር ማመን አቃተኝ።

"ከምርህን ነው? ያ ማለት አትከታተለኝም? የፈለግኩትን እሆናለሁ ማለት ነውኣ? እንደመንፈስ ዙሪያዬ አታንዣብብም። አብሮኝ የታየ ወንድ አትደበድብም? "

"አዎ አጠገብሽ አልደርስም። እንደፈለገሽ ሁኚ ቃሌ ነው። ብቻ እንደማፈቅርሽ እወቂ!" አለኝ

"እንደምታፈቅረኝ ጠርጥሬ አላውቅም። ችግሩ ፍቅርህን የምትገልፅበት መንገድ ልክ አይደለም። 24 ሰዓት ሙሉ አይንህ ስር የምትሆን ከማንም የማትገጥም ሴት እኔ መሆን አልችልም። ስታገኘኝ ያቺን ሴት አልነበርኩም። ስትወደኝ ያቺን ሴት አልነበርኩም። ያንተ ካደረግከኝ በኋላ ሌላ ሴት አድርጌ ልስራሽ ብለህ ትግል ነው የያዝከው። አይሆንም!" አልኩት

"አውቃለሁ" አለኝ። ተለያየን። ተለያየን ስላችሁ መቶ ጊዜ መተቃቀፍ መቶ ጊዜ መሳሳም እንደነበረውም አልደብቃችሁም። ለቅሶም ነበረው ከፈለጋችሁ። ለተወሰኑ ቀናት ማመን አቅቶኝ በየሄድኩበት ድንገት ዱብ ይል እንደው ብዬ እፈልገዋለሁ። የለም። ማታ ትምህርት ቤት ሲገባ ድንገት ከሆነ ሰው ጋር ካየኝ ፈነዳ ብዬ ብጨነቅም የለም። አልከፋኝም። ይልቅስ ነፃነት ተሰማኝ። በቃ ተለያይተናል። የምጠቀመው እሱ የሚሰራበት ባንክ ስለሆነ የሆነ ቀን ስሄድ የለም። ጓደኞቹን ስጠይቃቸው ስራ መልቀቁን ሰማሁ። የሆነ ቀን የጋራ ጓደኛችን ትምህርቱን ለሴሚስተር ዊዝድሮ ሞልቶ አዲስ አበባ ለእረፍት መሄዱን ነገረኝ። ጣዖቴ እንደነበረው ባሌ ሳይሆን እንደሰው አዘንኩ። እንዴት ስራ ይለቃል? እንዴት ትምህርቱን ያራዝማል?

ከአንድ ሴሚስተር በኋላ ባሌን ከተማ አየሁት። በጣም ከስቶ ጠቁሮ አምስት ወር ሳይሆን 5 ዓመት ያልተያየን ነበር የመሰለኝ።

"በየሱስ ስም ደህና ነህ?" አልኩት ደንግጬ ሳየው

"ደህና ነኝ!" አለኝ። "እቤት ሄጄ ነበር። ከቤተሰቤጋ ከሀ ለመጀመር እየሞከርኩ ነው። ቢያንስ አሁን ጴንጤ ስላልሆንኩላቸው ደስተኛ ናቸው!" አለኝ። ደስ አለኝ ያ የህይወቱ ጉድለት እንደሆነ አውቅ ነበር።

"አሪፍ አደረግክ!" አልኩት። እኔም የማውቃትን ደብዳቤ ፅፋለት አጊንቼ የተጣላሁትን ሴት ስም ጠቅሶ (የድሮ ፍቅረኛው ነበረች። ቤተሰቦቹ የሚወዷት ፍቅረኛው ነበረች።) ከሷጋ እንደሆነ ነገረኝ። እውነት ነው በቃ ተለያይተናል። እርግጠኛ ሆንኩ። ከዛን ቀን በኋላ እሷም ተከትላው መጥታ ኖሮ አብረው ከተማ አየኋቸው። ያ ማለት እቤቴ ሌላ ሴት እየኖረች ነው። አልጋችን ላይ ከሌላ ሴት ጋር እየተኛበት ነው። ያ ማለት በይፋ ትዳራችን ፈርሷል ማለት ነው። አልተናደድኩም። ጭራሽም አልቀናሁም። በቃ ለሱ ያለኝን ነገር ጨርሻለሁ። ወይም መሰለኝ።

መመረቂያዬ እየደረሰ ባለበት ጊዜ ውስጥ በባለጌ አይን ያየኝ ከነበረ ልጅ ጋር ባለግኩ። ዌል የባለግኩ የመጀመሪያ ቀን ቁጭ ብዬ ሳለቅስ አደርኩ። ትዳሬ እንደፈረሰ እያወቅኩ እንኳን የሆነ ሀጢያት የሰራሁ የረከስኩ ዓይነት መሰለኝ። ለምን እንዳለቀስኩ እንኳን አላውቀውም። ብቻ የዛን ቀን ነው ቃሌን ያፈረስኩ የመሰለኝ:: ..... የካድኩት አይነት......... የሆነ ቀን ከልጁ ጋር ወክ እያደረግኩ ስልክ ተደወለለት።

"እገሌ ነህ?"

"አዎ ነኝ ማን ልበል?"

"የሜሪ ባል ነኝ (ባልሽ ነው አንቺ አለኝ ዞር ብሎ ጥጋበኛ ነው ለራሱ። ደነገጥኩ)

"እኔ ሜሪ ከባሏ መለያየቷን ነው የማውቀው!" አለው መልሱ ድምፁን ላውድ አድርጎት እሰማዋለሁ

"እገልሃለሁ እናትህ ሆድ ብትገባ የምታመልጠኝ እንዳይመስልህ እገድልሃለሁ።" ይለዋል። ወላ አጠገባችን ያለ መሰለኝ ተንቀጠቀጥኩ። እሱ ምንም አልመሰለውም።

"ስትገለኝ ዝም ብዬ እሞትልሃለሁ እንዴ?" ይለዋል። ሲያብድ ይሰማ

እንደዛ ከደነፋ ከቀናት በኋላ የተመራቂ ተማሪዎች ፓርቲ አዘጋጅተን ዝግጅቱ የነበረው ከተማ ነበር። ልንመረቅ ሁለት ወር ነበር የቀረን። እኔን ብሎ ደግሞኮ ተተራማሽ። መግቢያ ትኬት ምናምን እየሸጥኩ ስተራመስ ከርሜ የፓርቲው ቀን ጠዋት ከጓደኞቼጋ ጫማ ልንገዛ ከተማ ስንወጣ አገኘሁት። ምንም እንዳላደረገ ...... እንደዛ እንዳልደነፋ (ማለት ሁኔታውኮ የዛን ቀን ሳይገለው የሚያድር አይመስልም ነበር።)

"እንዴት ነሽ እማ?" አላለም?

"ደህና!" አልኩት ግራ ገብቶኝ። ሁኔታው የሰማሁትን እንድጠራጠር አደረገኝ።

"ዛሬ ፓርቲ አላችሁኣ??"አለኝ ደነገጥኩ። እየተከታተለኝ እንደሆነ ገባኝ ግን ዝግጅቱ የነበረው ማታ ከ2 ሰዓት ጀምሮ ስለነበር ቢያንስ ቺኩን ትቶ አይመጣም ብዬ ተረጋጋሁ።

"ይመችሽ ፈታ በይ!! ይገባሻል!!" ብሎኝ እንደሰላማዊ ሰው ቻው ብሎኝ ሄደ። የምር ግራ ተጋባሁ። ቀልቤ አልተመቸውም። ቢሆንም ሀገር ሰላም ብዬ ቀሽ ቋ ብዬ ፓርቲውጋ ሄድኳ!!

እስከሆነ ሰዓት ድረስ ድንገት ከመጣ ብዬ በር በሩን እያየሁ አልተረጋጋሁም። ልክ ማታ 5 ሰዓት ሲያልፍ ተነፈስኩ። የዳንስ ወለሉ ላይ ከኔ ሌላ ማን አለ አልኳ!! ከአንድ የክፍሌ ልጅ ጋር ቅንጥስ ውልቅ እያልኩ ስደንስ ልጁ ድንገት እንደጅብራ ግትር ቀጥ አለብኝ። ምን ሆኖ ነው ብዬ አይኑን ተከትዬ ያየውን ሳይ ባሌ እየገባ ነበር። (ልጁ ግን ባሌን ያየ ሳይሆን ይሄ ነጩ የበረዶ ድብ ፊቱ ቀጥ ብሎ የቆመበት ነበር የሚመስለው .....እኔ ክው ልበልለት።) እዛ መሃል ግርግር ከተነሳ የተማሪውን ቀልብ እንስብና የተማሪው ምላስ ላይ መክረሜ ነው ብዬ ፈራሁና ቀስ ብዬ እንዳማረብኝ ወደሱ ሶምሶማ (በሂል ሶምሶማ ግን ኢማጅኑልኝማ ) አጠገቡ ስደርስ እጄን ለቀም አድርጎ መራመድ ጀመረ ወደ ውጪ በሩን እስክናልፍ ዝም አልኩት። ምክንያቱም አዳራሽ ውስጥ ኮሽ ካለ ነገር ተበላሽ። ከዛ ልክ ስንወጣ እጄን መንጭቄ ፊን ፊን አልኩ ........ ተረስቶኝ ነበራ!!

"እኔን ለማስቀናት ሆነ ብለሽ ነው እንዲህ የምታደርጊው?" አላለም? የምር የምለው ጠፋኝ?

አንተ ማነኝ ብለህ ነው የምታስበው? ምን ልሁን ነው? አታፍርም ሴት እቤትህ አስተኝተህ ልታስቀኚኝ ስትል? እኔና አንተ ተለያይተኛል። ረስተህ ከሆነ ራስህን አስታውሰው? የትም ከመሄድ ምንም ከማድረግ አትከለክለኝም" እሪሪሪሪ አልኩ (ቆይ ለምስሉ በደንብ እንዲገለፅላችሁ ድመት ዝሆን ፊት ስትውረገረግ ማለት ነው ላየኝ )

አንዴ በቦክስ ሲጠጣኝ ብዙ እስካሁን ስያሜ ያላገኙ ሁላ ከለሮች ታዩኝ። በቃ የሆኑ የቀለሞች ድብልቅ .... ሀምራያዊ ..... ብርቱጓዴ .... ምናምን በስንት እጅ መጫን ቢባል በዘይት በፀሎት ያላወራሁትን ልሳን ሁላ ሳልናገር አልቀረሁም። ጥምልምል ብዬ መሬቱ ላይ ከመውደቄ በፊት ቀለበኝ። የመታኝ አይኔጋ ነበር!! ከዓይኔ ስር የቀለበቱ ፈርጥ ቀዶኝ ስለነበር ደሙ ወደላይ ተፈነጠቀ። አቅፎ ይዞኝ እሪሪሪሪ የፈራሁት አልቀረም አንዳንድ እያለ የተወሰነ ተማሪ ተሰበሰበ። ደግነቱ ያው ውስጥ ሙዚቃ ስለነበረ ሊያጨስ ... ሊሳሳም ... አየር ሊወስድ ... ዜድ ሪፖርት ሊያወጣ .... ምናምን ከወጣው ተማሪ ውጪ ውስጥ አይሰማም። የለበሰው ነጭ ቲሸርት ቀይ ጠቃጠቆ ሰራ 'እሺ ልቀቃት?' 'አልለቅም።' ዝም ሲሉት 'እርዱኝ እንጂ እየደማችኮ ነው።!' አልኮል ሲሰጡት በሁለቱም እጆቹ ወደላይ ተሸክሞኛል እንዴት ያድርግልኝ? ሊያደርጉልኝ ሲሉ 'አትንኳት እኔ ነኝ ያደማኋት ራሴ ነኝ የማደርግላት!' የሚያየው ሰው ግራ ገባው።

በልብሱ ደሜን ከፊቴ ላይ ይሞዥቀዋል። በዛ ላይ እንባው ደግሞ እኔን መልሶ ያወራኛል። "እማ እኔኮ እንዲህ ላደርግ አይደለም የመጣሁት የነበረው ምዬ ነበርኮ አልነካትም ብዬ ምዬ ነበርኮ !" ደግሞ በዚህ ሁሉ መሃል መሳምም አለው። ጉንጬን
ከነደሜ አንገቴን ይስመዋል። ከሰከንድ በፊት 'ምንዓይነቱ ነው?' ሲሉ የነበሩት 'ምፅ ምፅ ሲያሳዝን' አላሉም?

........ አልጨረስንም ......

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
2024/09/23 07:26:36
Back to Top
HTML Embed Code: