Telegram Web Link
የአረብ ሀገር ጥላቻ የተፈጠረብኝ መቼ ነው?” ብዬ ለማስታወስ ሞከርኩ። ትዝ
የሚለኝ ነገር የለም። ምናልባት ጓደኛዬ ኡስማን ስለሚጠላው እሱ
ሳያውቀው አጋብቶብኝ ይሆን? አይደለም።ልጅ እያለሁ
የጀመረኝ ይመስለኛል። አያቴ በነበረችበት ሰፈር። ባደኩበት ሰፈር፣
በነእማማ ዙበይዳ ሰፈር።
ልጅ እያለሁ ለተወሰነ ጊዜ ሴት አያቴ ታሳድገኝ ነበር። በሰፈራችን
የምንወዳቸው፣ እማማ ዙበይዳ
የሚባሉ ሴት ነበሩ። የሆኑ ደርባባ አሮጊት ሴትዬ። ሰው ዝም ብሎ
ይወዳቸው ነበር። ጎመን መንገድ ላይ ይሸጣሉ። በክረምት ደግሞ በቆሎ
ይሸጣሉ። እማማ ዙበይዳን ሰፈሩ ሁሉ ለምን ይወዳቸው እንደነበር ግን
በትክክል አላውቅም። እኔም እወዳቸው ነበር። ለምን እንደነበር ግን
አላውቅም። “ነይ እስቲ አንቺ
ሰልካካ!" እያሉ ግንባሬን ይስሙኝ እንደነበር ብቻ ነው ትዝ የሚለኝ።
እማማ ዙበይዳ ባልም ዘመድም የላቸውም። በምድር ላይ ያለቻቸው ፋጤ
ቀጮ ናት። የሳቸው ብቸኛ ልጅ ፉጤ ቀጮ ጅዳ ሄደች ተባለ። ሰፈሩ ሁሉ
እማማ ዙበይዳ በቃ ሻሩ፣ አሁን ወርቅ በወርቅ ሊሆኑ ነው ብሎ ተነበየ።
እሳቸውን ያገኘ ሰው ሁሉ “ፋጤ ቀጮ ጅዳ ነው አይደል የሄደችው?”፣
ትደውላለች”፣ “ደህና ናት ታዲያ፣ “አሁን ለመድኩ አለችፖ፣ ግህም፣
“በርቺ በሏት እንግዲህ!
ይለመዳል.ይለመዳል”፣ “ዋናው መበርታት ነውታዲያ”፣ “እ!” እያለ
ከእማማ ዙበይዳ የበቆሎ እሸት
ወይ ጎመን ገዝቷቸው ያልፋል። በበጋ ጎመን በከረምት የበቆሎ እሸት
በመሸጥ ነበር የሚተዳደሩት።
በዚያ ሁሉ የሰፈር ሰው ሳይታክቱ በዚያ እናታዊ ፈገግታቸው ታጅበው ስለ
ልጃቸው ደኅንነት ምላሽ ይሰጣሉ። “እላሙዲሊላ አላሂ ወላሂ ደህና ናት!
ዱዋ አርጉላት." ይላሉ፤ መልሰው መላልሰው።
ሲኖሩ ሲኖሩ.…የሆነ ጊዜ ላይ ልጃቸው ስልክ ደውላ አለቀሰች ተባለ።
“ምን ሆንሽ” ሲሏት አትናገርም
ሲኖሩ ሲኖሩ…የሆነ ጊዜ ላይ ደግሞ መደወል አቆመች ተባለ። ደህንነቷን
የሚነግራቸው ጠፋ። ጎመን ወይ
በቆሎ ለሚገዛቸው የሰፈር ሰው ሁሉ “አረብ አገር ስልክ ማድረግ
ታውቅበታለህ?” እያሉ ይጠይቃሉ።
የተማረ የሚመስል ወጣት ሲመለከቱ ደግሞ “ልጄ! እስኪ ባክህ የጅዳ
ስልክ ቁጥር ጽፈህ አምጣልኝ? ልጄ ናፈቀችኝ ይሉታል። የሷ ስልክ ቁጥር
ግን የላቸውም። አንዳንድ ሰው ነገሩን ሊያስረዳቸው ሞከረ።ኾኖም
ሊገባቸው አልቻለም። የሰፈሩን ሰው መሄጃ መቀመጫ አሳጡት። እርስዎ
ስልኳን ፈልገው ያምጡ! እኛ እንደውልሎታለን” ሲባሉ እኔ ቁጥሯን ከየት
አዉቄ” ነው መልሳቸው። እሷ ካልደወለች
እሳቸው ወደየት ብለው ይደውላሉ? አድራሻዋ አይታወቅ ነገር።
የሰፈሩ ሰው በሙሉ እማማ ዙበይዳ ሲያዝኑ አይቶ አዘነ። እማማ ዙበይዳ
የደግነት ምሳሌ ነበሩ። ፋጤ
ቀጮ እጅግ ስትናፍቃቸው ግን ሰው ሰላም ሳይሉ ማለፍ ሁሉ ጀመሩ።
የሚሸጡት ጎመን ጠወለገ።
ወዲያው ደግሞ ወገባቸው ጎበጠ። ከመቼው በእድሜያቸው ላይ ምዕተ
ዓመት እንደጨመሩ። ሰው የልጁ ናፍቆት እንደ ኤድስ አመንምኖ
ሊገድለው እንደሚችል ያየሁት በእማማ ዙበይዳ ነው።

©Teddy Exubirant

@wegoch
@wegoch
@Mahletzerihun
እርቃንነት ፀጉሯን እየጎነጎነች ራቁቷን ከባኞ ቤቷ ስትወጣ አይን ለአይን ተጋጠሙ። ደንግጣ ወደ ባኞው ተመልሳ በሩን በፍጥነት ዘጋችው። "ይቅርታ! በጣም ይቅርታ" አላት በሚርበተበት ድምፅ ከበሩ ኋላ ሆኖ። የተዘጋውን በር በጀርባዋ ተደግፋ በረጅሙ ተነፈሰች። "በጣም ይቅርታ!" አላት እንደገና ድምፁን ከፍ አድርጎ፣ "ለረጅም ጊዜ በሩን ሳንኳኳ አልሰማሽኝም፣ እቃዬን ልወስድ ፈልጌ . . ." . . . . . .ዝምታ . . . . . .
"አይ ምንም አይደል. . . " አለች በዝግታ፣ "ወይም ሌላ ጊዜ ልምጣ ?. . . " መለሰ፣ ጮክ ብሎ። ፎጣ አግድማ፣ በሩን በትንሹ ከፍታና ፊቷን አጮልቃ "አይ፣
እቃህ ከአልጋው አጠገብ አለልህ" አለችውና በሩን መልሳ ዘጋች። በሩን መልሳ ዘግታ ጀርባዋን አስደግፋ ወለሉ ላይ ተቀመጠች። ከእግሩን ኮቴ እያዳመጠች ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት የተሰማትን የራቁትነት ስሜት አሰበች-- ከመቼውም የተለየ እርቃንነት። ሰውነቷ ላይ ከእሱ የምትደብቀው ነገር አልነበራትም። ይልቁኑም ገላዋን ከማንም ሰው የበለጠ እሱ ጠንቅቆ እንደሚያውቀው ታምናለች። ከሁሉም አቅጣጫ አይቷታል፣ ዳብሷታል፣ ስሟታል። እንዲህ እንዳሁኑ በስሜት ሳይራራቁ በፊት በእሱ presence እርቃኗን ሆና ራቁት ስለመሆኗ አስባ አታውቅም። ዛሬ ግን አይኖቿ ከአይኖቹ ሲጋጠሙ የዛሬውንም እስከዛሬ ያየውንም ራቁት ገላዋ ታስቧት የሀፍረትና የራቁትነት ስሜት ወረራት። እጥፋቶቿን፣ ጠባሳዎቿን፣ ወጣ ገባዎቿን፣ የምትወደውን፣ የምትጠላውን አካላቷን ሁሉ ስለማወቁ አሰበች። He was undeserving of knowing that much about her. He was undeserving of being the only person to know that much about her. But she can't take it back. ከአእምሮው ጓዳ ገብታ እሷነቷን ከሀሳቡ መንጭቃ ልታወጣው ተመኘች። መሄዱን እየጠበቀች ጥያቄዎች በሀሳቧ ይመላለሳሉ "የተሰጠ ነገር ተመልሶ ይጠየቃል? መገለጥ ይመለሳል? ራቁትነት የሚሰማው በመታየት ውስጥ ነው? ባለመታየት የራቁትነትን ስሜት አርቃለሁ?"

@wegoch
@wegoch
@paappii

#hewan huletshi
በሔለን ፋንታሁን
*ሚዛን*

እግሬ መርገጡን እንጂ መድረሻውን አያውቅም ። ዓለምን እንደረሳ መናኝ ልቤ ሁሉ ቀለለበት ፤ ምንምነት ዘልቆ ተሰማው ....ሁሉ ባዶ ...ሆኖ ታየው ... ለብቻው መሆንን ተመኘ ፤ ግና እንዴት ብሎ ... ተፋቅረው እንደተጣሉ ጥንዶች ሁሉ ወዲ ወዲያ ይተረማመሳል ። ከዚህ እዚያ የሚረግጥ ዕልፍ ጫማ የግር ኮቴ ያለሁ ዜማ ...ትርምስምስ ብሏል ጯሂ ብቻ ...ግን ምን እያሰብኩ ነው ?አላውቅም ። ምን እያሰብኩ እንደሆነ አለማሰቤ አሳሰበኝ ...እሰይ ... አሰብኩ ይህንንስ ማን አየበት ... ግን መድረሻዬ ወዴት ነው ? መነሻዬስ ? አላውቅም ... ዝም ብዬ ዝምታን መፈለጌ መልስ ይሆን ? ብቻ አለሁ ። መኖር ደጉ ... ንፋስ እንዳናወጠው ውሃ ሐሳቤ መርጋት አቃተው ። ምን ሆኜ ነው ? እያልኩ እጠይቃለሁ የኔ ላልሆነው እኔነቴ ...ከራሴ ጋር ከገባሁት ሰጣገባ <<
ሚዛን >>በሚል የጎልማሳ ድምፅ አነቃኝ <<እሙዬ ተመዘኛ >> አለኝ ከመሬቱ
የተጣበቀች ሚዛኑን እየጠቆመኝ ...ከራስ ጠቤ ቢገላግለኝም ሐሳቡ የገባኝ
ዘግይቶ ነው ። አካሌን ከሚዛኑ አስቀምጬ ... የቆጠርኩትን ነገረኝ ። አሰብኩ ተመኘሁ የሐሳቤ መመዘኛ ቢኖረኝ ብዬ... አሁንም ግን መድረሻዬን አውቀዋለሁ..."የሐሳቤን ሚዛን ፍለጋ........

@getem
@getem
@paappii
#የጨረቃ ልጆች

ክፍል - 8

ሌሊቱን በሙሉ ስልኳ አልሰራ ብሎታል ለምርመራ ክፍሉ ያላስተላለፈውን ከስዕል ማዕከሉ ያገኘውን ሳንቲም በእጁ እፍን አድርጎ ይዞታል እንቅልፍ በአይኑ አልዞረም የት እንደጠፋች አልገባውም
ከቢሮው እንደገባ በአይኑ ይፈልጋት ጀመረ ግን የለችም ዛሬም ሶልያናን ጥበቃ ለስብሰባ የተቀመጡ ሰዎች እንዳሉ ሲያይ ይበልጥ ለማግኘት ፈለገ በድንገት የምርመራ ክፍሉ ፀሀፊ ወደ እሱ ስትመጣ ተመለከታት ይሄ የሶልያና የስራ መልቀቂያ ወረቀት ነው ትናንተ ልክ እናንተ እንደወጣችሁ ነው ያስገባችው ሶልያና ከእንግዲህ ከእኛ ጋር አትቀጥልም ፀሀፊው ጥላው ሄደች ምንም አልተናገረም የያዘውን ሳንቲም ጭምቅ አድርጎ ያዘው ሲጋራውን እስኪለኩስ ተጣደፈ

ሙሉ ለሙሉ ሀሳቧ ተሳክቷል ያላገኘችው ግን አንድ ነገር አለ እሱም ግዙፉን ጳውሎስ ነው አሁን ወደ ቢሮው ገብቶ መልቀቂያውን ሲመለከት ምን ይሰማው ይሆን እያለች እራሷን ትጠይቃለች ትንሽም ፈርታለች ግን ካገኘችው ደስታ አይበልጥባትም ባሳየቻቸው መንገድ ሄደው እንቅፋቷ ስላልሆኑ ተደስታለች ፈልጋ ያላገኘችው አንድ ነገር ግን አለ ስለፈለገችውም ጭምር ነው የመጽሀፍ ቅዱስ መርማሪ መስላ ከምርመራው ጣቢያ የገባችው ጳውሎስን ከብዙ ጊዜ በሁዋላ ያየችው በቴሌቪዥን መስኮት በወንጀለኞች ላይ ስለተወሰደው እርምጃ ቃለ መጠይቅ ሲደረግለት ነው እሷ በምትፈፅማቸው ዝርፊያዎች ውስጥ ግን ጳውሎስ አሳዳጇ ይሆናል ብላ አስባም አታውቅም
ጳውሎስን ደግማ ያየችው የንጉሱ ሁለተኛ ማስታወሻ በተሰረቀ ጊዜ የሰጠውን ቃለመጠይቅ አይታ ነው የድሮ አመሉ አልተወውም አሁንም በሀይል ሁሉንም የሚያገኝ እንደሚመስለው ተረዳች
ለሶስተኛ ጊዜ በፈፀመችው ዝርፊያ ላይ ካስታወሰኝ ብላ ሳንቲሙን እየጣለች መሄድ ጀመረች ጳውሎስ ግን አሁንም ጌታ ተሰቅሎ ያለበትንና ጨረቃ የሚል ፅሁፍ ያለበትን ስዕል ማስታወስ አልቻለም
ያኔ ያሰቃያት ያዛት የነበረውን ጳውሎስ ከፊቱ ቆማ ለማዘዝ ውስጧ በጣም ስለሻተ በቀጥታ የምርመራ ክፍሉ ያወጣውን መወዳደሪያ ፈተና አልፋ ከፊቱ ስትቆም እንኳ ጳውሎስ አላስታወሳትም ከፊቱ ለመጀመሪያ ጊዜ ቆማ ገለፃ ስታደርግ ተሰምቷት የነበረው ስሜት እስካሁን አይረሳትም
ሶልያና የሚለውንም ስም አለማስታወሱ እስካሁን ገርሟታል ይሄን ያህል ሰው እንደሚረሳ ያወቀችው ያኔ ነው ሀይለኛው ጳውሎስ ቁጡ ጳውሎስ ሂድ ስትለው የሚሄድ ና ስትለው የሚመጣ እንደሆነ በማወቋ ተደስታለች ሁሉንም ነገር በእቅዳ መሰረት በመሄዱ ከሷ በላይ ደስተኛ ሰው ማንም እንደማይኖር ገምታለች
ለጳውሎስ ትናንት ከሰጠችው መረጃ በላይ ምንም እሷን የሚያስታውስበት መንገድ አይኖርም በዚህ ካላስታወሳት ግን ከፊቱ ቆማ ሁሉንም ነገር ለመንገር ወስናለች
ሀይለኛው ጳውሎስ ምን አይነት ስሜት እንደሚሰማው ማወቅ ፈልጋለች ጅልነቱን ለምርመራ ክፍሉ አለመመጠኑን ሌባን ማባረር ብቻ ጥቅም እንደሌለው ወንጀለኛ ወንጀለኛን መቅጣት እንደማይችል እስክትነግረው ቸኩላለች
እስከዛሬ ጥላለት ምትሄደው የመጽሀፍ ቅዱስ ጥቅስም እሱን ሊያነቃው አልቻለም
ይሄን ሁሉ አመት እንዴት አንድ ጳውሎስ ይኖራል ብላ እራሷን ጠየቀች በጣቷ ቀሚሷን መዳበስ ጀመረች የለበሰችውን ቀሚስ ሰብሰብ አደረገችው ባቷን በመዳፏ ዳበሰች አሁንም ሲረግጣት ሲደበድባት ይሰማታል ባቷ ላይ ያለውን ጥቁረት ስትመለከት እንባ ባይኗ ሞላ በቀጥታ ተነስታ ከፊት ለፊቷ ከሚገኘው መስታወት ፊት ቆመች ቀስ ብላ በጀርባዋ ያለውን ዚፕ አወረደችው ቀሚሷ ከእግር ስር ሲወድቅ አንድ የእንባ ዘለላ ከአይኗ ወደቀች ትከሻዋ ላይ ያለውን ጠባሳ ዳበሰችው ከጡቷ ስር ያለው ሽርክት የቅርብ ጊዜ ይመስላል ጳውሎስ የሚል ድምፅ ከጆሮዋ ብቅ አለ ዘወር ብላ ጀርባዋን በመስታወቱ ተመለከተች የገረፋት ግርፊያ በአይኗ መጣ መቀመጫዋን በሲጃራ እሳት ሲጠብሳት ያለው ህመም አሁንም ተሰማት ከአይኗ የሚወርደው የእንባ ዘለላ የእንብርቷን ስርጉድ ሲያርሰው ተሰማት አመማት

ይቀጥላል.......
ብላቴናው በጨረቃ ምሽት

@wegoch
@wegoch
@wegoch
"በህይወቴ እንዳንች አይነት ቆንጆ አይቼ አላውቅም" ስልሽ

"አትዋሽ ባክህ! የህይወትህ ቆንጆ ሴት እናትህ ነች" ያልሽኝ ግዜ ነበር ሚዛንሽ ከላባነት ወደ ወርቅነት ከፍ ያለብኝ.


2 እንስቶች በህይወቴ ውስጥ አልፈዋል. ሁሉም ግን ልቤን ለማሸነፍ ብቻ ብለው ያዘጋጁትን አርቴፊሻል ማንነት ከአርቴፊሻል ውበት ጋር ለብሰው ነበር የቀረቡኝ. ልክ መሸነፌን ሲያወቁ ጣ ፋጩን ማንነት አሽቀንጥረው ጣል!...... ያኔ ነገር ብልሽት!

አንቺ ግን ገና ከጅምሩ ሳትዘንጭ የሚያምርብሽ ልታይ ልትልይ ሳትይ ጎልተሽ የወጣሽ የተለየሽ ነበርሽ...... ፈገግታና በራስ መተማመን የሰው ልጅ መተክያ የማይገኝላቸው ውድ ልብሶቹ እንደሆኑ አሳይተሺኛል. በዛ ላይ ግልፅ! የት ይቱጋ ግልፅ መሆን እንዳለብሽም የምታውቂ..

ከሞቀ ጨዋታ መሀል ተገልዬ እግርሽ ላይ ስላሉት ጥቃቅን ፀጉሮች፣ ስላልተሰራው ጥፍርሽ፣ ቀለም ስለማያውቀው ከናፍርሽ አስባለው እናም እስከዛሬ ከደቅነኳቸው እግሮች ጥፍሮች እና ከናፍሮች በእጥፍ ይበልጥብኝና ጅልነቴ ጎልቶብኝ እንደቂል ለብቻዬ ስቃለው.

ንግግሮችሽ ላፍታ ካምሮዬ አይሰወሩም.. ትዝ ይልሻል

"በጣም ልዩ ሴት ነሽ... እንደሌሎቹ አይደለሽም" ያልኩሽ ቀን ሸራ ጫማሽን አውልቀሽ የጠቆረና ስንጥቅ የከበበው ውስጥ እግርሽን አሳየሺኝ እናም
.
..
....
" እኔ ልዩ አይደለውም ካብዛኛዎቹ እንዳንዷ ነኝ... ከዚ የባሰ ከፈለክ የገበሬ ሴት ልጅ ወይም ጉልት ጨቻሪዎች ጋር ሂድ...." ያልሺኝን?

...
ልክኮ ነሽ ግን! እኛ ወንዶች መሬት ላይ ያለውን እውነታ ስርዘን በምናባችን የሳልነውን ውበት ላሟላች ሴት እንሰግዳለን... ያቺ ሴት ያንን ምናባዊ ውበት ምታመጣበትን መንገድ ስታቆም መስገዳችን ያቆማል. አዋ! ለውበቱ እንጂ ለኦርጅናሏ እሷ መች ሰገድንና? ለዚኮነው ሴቶቻችን ከጭንቅላታቸው ይልቅ ሰውነታቸው ላይ የሚሰሩት. ምክንያቱም በቀላሉ ተቀባይነትን ስለማያገኙ.
ካልቀጠነች ካልቀላች ፀጉሯ ካልለሰለሰና ካልረዘመ ጥፍሮቿ ካልተሰተካከሉ እግሯ ካልተላጨ ካልቀላ... እንገፋታለን! መገፋት ደግሞ ያምማል! ከምንም በላይ!.... ስለዚ መገፋትን ሽሽት ስንጥቁን ልሙጥ ጥቁሩን ቀይ ከፍዳዳውን ልስልስ ለማድረግ ስትጥር የአምሮዋን ነገር ትረሳለች. አስተዋይነት ልባምነት ምናምን የሚባሉ ሁሉ ወደ ገደል ይገባሉ.

"ምን አይነት ወንድ ይመችሻል?" ብዬሽ ነበር... ህም! ሰውነቱ ሞላ ያለ ..ዘናጭ... ቁመና ያለው ..cool ... ገንዘብ ያለው.. ..ሙድ የገባው..... ትይኛለሽ ብዬ የጠበቅኩትን በሙሉ ብትንትኑን ያወጣ መልስ ነበር የመለስልኝ.


" አፍቃሪ"

ይህን ብቻ ነበር ያልሽኝ.

"አፍቃሪነት ውስጥ ሁሉም አለ... ማክበር ...መታመን...ፍቅር ራሱ....ትዕግስት... ሁሉም" ደገምሽልኝ

የሆነ ግዜ ላይ 'A woman with beautifull body is good for a night ,but, A woman with beautifull mind is damn good for a life!" የሚለውን አባባል ያረጋገጥኩብሽ ብቸኛ ሴት አንቺ ነሽ. የልቤን መፍቻ ሳልሰጥሽ እንዲው ገብተሻል... አንቺ እውነት ነሽ... እውነት ደግሞ ያው እውነት ነው..... ከእሱ ጋር መኖር እረፍትም ፍሰሀም ነው..... ለእውነት ከእውነት ውጭ ምን ይስማማዋል? ምንም

አንድ እውነት ልነግርሽ ነው
:

:
እውነቴ ሆይ አ.ፍ.ቅ.ሬ.ሻ.ለ.ው.
:::::::::
:::::::::::
"ነፍስሽ ከነፍሴ ጋር በእኩል ተለክታ፣
በእግዜር ጠቃሚነት
በፍቅር መርፌ በደንብ ተሰፍታ፣
ወበቅ ማታስወብቅ ብርድ ማታስመታ፣
ሆናለች ለልቤ እፁብ ድንቅ ኩታ።

ስለዚ አንች እውነት ሆይ እንደኔያለ ድስት እንዳንች ያለ ግጣም ከወዴት ይገኛል?.... እኛው ካልተገጣጠምን? ደግመዋለው

አ.ፈ.ቅ.ሬ.ሻ.ለ.ው.

ተፃፈ by aggie

@wegoch
@wegoch
@paappii
Laphto Contemporary Art Gallery will open an art exhibition by Kirubel Abebe titled "Gestures of Mask-Ulinity" on 16 January 2021. The event which will open at 3:00pm on 16 January will stay open until 16 February 2021. @linkupaddis

@GitemSitem

@seiloch
@seiloch
አንዲት ልጅ ነበረች ማቅመሻ የምላት 3

©ጓዴ ጥላሁን

እነሆ ከማቅመሻ ጋር ወዳጅነታችን ቀጠለ፡፡ ስድቧ ግን እንደ ሽል አእምሮዬ
ውስጥ እያደገ መጣ፡፡ የበለጠ ተአምር ብታሳየኝ ብየ
“.. እስቲ ከጅል ሙገሳ የተሸለ ስድብሽን ወዲህ በይ….” አልኳት፡፡
“... አይ እኔ ፒያኒስት እንጂ ተሳዳቢ አይደለሁም ..” ስትል መለሰች፡፡
“… እስቲ እኔ ሰሞኑን ወደ አዲሳባ ልመጣ ነውና ኪራይ ቤት ፈልጊልኝ…”
አልኳት፡፡
“… እሞክራለሁ…” አለችና ተሰናበተችኝ፡፡
በማግስቱ ተገናኘን፡፡
“… ቤቱ ይመጥንህ እንደ ሆነ አላውቅም፡፡ ኦሎምፒያ አካባቢ ሆስቴል
አግኝቼልሃለሁ፡፡ ባለቤቱ በቅርብ ወደ ውጭ ሄዷል፡፡ ኪራዩም ደህና ነው
4500…. ይስማማህ ከሆነ ልጠይቅልህ?…” አለች፡፡
“… 4500 በዓመት ግድ የለም፡፡ ቆሎ እየቆረጠምኩም ቢሆን
እከፍለዋለሁ፡፡…” አልኳት 4500 ለ 12 እያካፈልኩ፡፡
“… እየቀለድክ ነው ..” ስትል መለሰች
“… ያው በአንዴ ክፈል አይበሉኝ እንጂ አዲሳባ ቤት መከራየትና እኛ ሀገር
ቤት መግዛት እኩል እንደ ሆነ አውቃለሁ፡፡… ቢሆንም ተበድሬም ተለክቼም
መክፈሌ አይቀርም…” አልኩ፡፡
“…. እየቀለድክ መሆን አለበት…” አለች፡፡
“…. ኧረ ወዴት!! ቀድሞ የዚያን ቀን ሰምቼው የማላውቀውን ስድብ እንደ
ችንካር ከቀበቀብሽብኝ በኋላ የቀልድ ሆነ የቁምነገር ቆሌ ርቆኝ አውታታ
ሆኜ እያየሽኝ…..”
“…. እሺ ልወጣ ስለሆነ የምትከራይ ከሆነ ንገረኝና ልንገርልህ….”
“…. ይሆንኮ አልኩ …”
“…. የሁለት ወር ቅድሚያ ክፍያ ስለጠየቁ 9000 ሰጥልሃለሁ… ስትደርስ
ድሪምላይነር ሆቴል ናና በሪሴፕሽኖች አስጠራኝ.. አገናኝሃለሁ….”
ኡኡኡኡኡኡኡኡኡኡኡኡኡ….. ብየ አቀለጥኩት፡፡ ቤት ውስጥ ወጥ ሲቀቀል
የነበረው ጓደኛየ ማማሰያውን ወድሮ …. ሳፋ ላይ ሲታጠብ የነበረው
ሌላው ወዳጄ ሳሙና እንደተለቀለቀ ምናምንቴውን ከወዲያ ወዲህ እያላጋ
ተንደርድረው መጡ፡፡ ለ5 ደቂቃ ያህል ካረጋጉኝ በኋላ ወደየሞያቸው
ተበታተኑ፡፡ የወደቀውንት ስልኬን አነሳሁና
“… አደራሽን የበደልኩሽን ሌላ ጊዜ እክስሻለሁ፡፡ የዛሬን አውጭኝ፡፡…” ብየ
ላኩላት
“… ምን ማለትህ ነው፡፡ ሰፋ ያለ ነበር እንዴ የፈለግከው .. እኔኮ ያንሳል
ብየ ነበር…”
“… አንዴ አዳምጭኝማ እንጉዳዬ ነሽ፡፡ እየውልሽ አንቺ የማታውቂው ብዙ
ነገር አለ፡፡ አንቺ ለካ ሰው መስዬሽ ነበር እስካሁን ስታወጊ የቆየሽው ፡፡
ነገሩ ወዲህ ነው፡፡ የጠቀስሽው ቁጥር የትምህርት ክፍላችን አጠቃላይ
በጀት ነው፡፡ በዚህ ብር ወርሃዊ ቤት ኪራይ ሊከራይ ነው የሚባል
ጭምጭምታ እንኳን ቢሰማ ጸረ ሙስናዎች በእሳት ሰረገላ ሲበሩ
መጥተው ቃሌን እንኳን ሳይቀበሉ ነው ላጭተው በእድሜ ይፍታህ አለም
በቃኝ የሚያስወረውሩኝ፡፡ እነሱ እንደሁ ላይ ያላውን አይበሏቸው እንጅ የኔ
ብጤው ላይ ነው በትር የሚያነሱት…. አደራሽን የስራ አፈጻጸም ሪፖርት
ሟሟያ እንዳታደርጊኝ፡፡…”
“… እሺ ይቅር እያልክ ነው?…”
“… ስነግርሽ ውሾን ያነሳ ውሾን ይሁን በይ በይ… በእኩዮቼ አስፈልጋለሁ፡፡
አንቺስ ምን ቁልቁል አወረደሽ እኔስ ምን ሽቅብ አንጠለጠለኝ….
ያላባታችን!!! በይ በይ ቻው!!
ተሰናበትኳትና ወደ ደባል ጓደኞቼ ቤት ልገባ በር ላይ ስደርስ ሻንጣዬን በር
ላይ አስቀምጠው እንደ ገነት ጠባቂ መልአክ ግራና ቀኝ በሩን ይዘው
ቆዩኝ፡፡
“…. ምንድነው ነገሩ…” አልኩ ግራ እየተጋባሁ
“…. በል ወንድሜ እስካሁን ጓደኝነትህን አክብረን ችለንሃል፡፡ ቤት ኪራይ
ከፍለንም ተሳቅቀንም አንችለውምና ጥግህን ፈልግ፡፡….”
አሉና ቁልፉን በውጭ እንዳለሁ ቆልፉብኝ፡፡ ቁልቁል ሻንጣዬ ላይ
ወደቅኩ……

@Wegoch
@Wegoch
@Mahletzerihun
#የጨረቃ ልጆች

ክፍል - 9

ቁጭ ብሎ የሚያስብበት አንድ ቦታ እየፈለገ ነው ከየቱ እንደሚሆን ግራ ገብቶታል ቀጥታ ወደ ቤቱ አመራ የሲጋራውን ሽታ ስለለመደው አዲስ አልሆነበትም ጨልጦ የጨረሰውን የመጠጥ ጠርሙስ ረግጦት ገባ አይኑ ለምዶታል ምንም አይነት የሚቀፍ ስሜት ሊሰማው አይችልም ተበልቶበት ያልታጠበ ብዙ ሳህን ከጠረጴዛው ይታያል ሳይበላ የተወው እንጀራ ሻግቶ ወደ ጠረጴዛው መቅረብ አይቻልም እያወለቀ የሚጥላቸው ብዙ ልብሶች በየቦታው ተንጠባጥበዋል ያላጠፋው ቴሌቪዥን የምሽት ዜና ያሰማል ካነጠፈው ብዙ ጊዜ ያስቆጠረው አልጋው ላይ ተዘረፈጠ የትራሱ ጨርቅ በቀን በቀን በሚያወጣው ለሀጭ ተጨማልቋል አንሶላው ንጣቱን እያጣ ነው መፀዳጃ ቤቱ ብቻ በፅዳት ተይዛለች ሁሌ ገላውን ውሀ ሳያስነካ ስለማይውል ጳውሎስ መፀዳጃ ቤቱን ከሁሉም ነገር በላይ በንፅህና ይይዛታል ብዙ የሚያስበው ውሀ ከጭንቅላቱ ሲፈስ ነው ሚያስጨንቀውን የውስጡን ሀሳብ ጠርጎ ሚያወጣለት ይመስል ሻወር ሲወስድ ከሶስት ሰአት በላይ ይቆያል የቤቱን ትርምስና መቆሸሿን ግን ይወደዋል የምርመራ ጓዶቹን እንኳ ወደ ቤቱ ጋብዞ አያውቅም እሱም የቤት ግብዣ የተባለ ነገር ይጨንቀዋል እንደ ልቡ መሆን ስለማይችል ብዙዎቹን ይሰርዛቸዋል ይልቅ በየ ጭፈራ ቤቶቹ መዝናናት ይወዳል ሚጋብዛቸው ሰዎች ሲኖሩ ከአንዱ መሽታ ቤት ወስዶ ሪዮ በእስፕራይት ያዝላቸዋል በረዶም እንዲያደርጉበት ይነግራቸዋል ጳውሎስ ሰው ከቤት መጋበዝ የሚል ህግ የሱ ህይወት ውስጥ የለም ሴትም ወደ ቤቱ ይዞ አይመጣም ብትንቀኝስ የሚል ፍርሀት አለበት ማታ ማታ ሞቅ ብሎት ይዟት ከሚወጣት ሴት አልያ በስካር መንፈስ ሳያስታውስ ጠዋት ሲነሳ ከአጠገቡ በአንድ አልጋ ከሚያገኛት ሴት በስተቀረ ህይወቱ ውስጥ አንድ ሴት ብቻ ነው የነበረችው እሷም ሶልያና ናት
ከተቀመጠበት አልጋ አንገቱን ወደ ላይ አንጋጦ አይኑን አፍጥጦ ብድግ አለ
በእጁ የያዘውን የመልቀቂያ ወረቀት ሲያነብ ሶልያና ዳዊት የሚል ስም አነበበ ያቺ ህይወቱ ውስጥ አንድ የሚላት ሴትም ሶልያና ዳዊት ነው ስሟ መመሳሰል ይሆናል የሚለውን ሀሳብ ሊሰማው ፍቃደኛ አይደለም ተመልሶ ከአልጋው ላይ ተቀመጠ እጁን ከኪሱ ሲከት ያስቀረውን ሳንቲም ለቀም አደረገው
ክርስቶስ በመሰቀል ላይ እያለ ያለው ምስል ድቅን አለበት ያቺ በህይወቱ ውስጥ የነበረችው ሶልያና መንፈሳዊ ስዕል ትስል እንደነበረ ትዝ አለው ሳንቲሙን ገለበጠው 40ቁጥር በግዕዝ ተፅፎበታል ሚሆነው ነገር እንደ ህልም መሰለው ከዛሬ 30አመት በፊት የሆነው ነገር እንደ ትናንት ይታወሰው ገባ
40ኛ ስዕሏን ስታሳየው የሳለችው ስዕል ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሆኖ የሳለችውን ስዕል ነበረ ገና ስዕሉን እንዳሳየችው ስዕሉ ላይ አድርጎት የነበረው ድርጊት ትዝ አለው እሷም ስትታገለው በያዘው ስለት ከጡቷ ስር የወጋት በሙሉ ከአይኑ ተደቀነ
ጭንቅላቱ መስራት ያቆመ መሰለው ከዚህ ሳንቲም በፊት ክርስቶስ በመስቀል ላይ ተሰቅሎና ጨረቃ የሚል ፅሁፍ ያለበት ሳንቲም ብዙ ጊዜ ከተዘረፉት ማዕከላት ከመፅሀፍ ቅዱሱ ጋር አብሮ እንደሚያገኝ ታወሰው #ጨረቃ-ሶልያና ልቡ በፍጥነት መታች የጨረቃ ሌላኛ ስም ሶልያና እንደሚባል የነገረችው ትውስ አለው የወጡላትም አባቷ መምህር ዳዊት እንደሆኑ አእምሮው ይነግረው ጀመረ። የአባቷን ስም ደግሞ ሲያስታውስ የበገና ማዕከሉ ስርቆት ታወሰው ከስዕል ማዕከሉ የጠፋው የስድስቱ ጨረቆች ስዕል ከአእምሮው ድቅን አለ ያቺ ሶልያና አጠገቡ እንደነበረች ግባው እግሩ ተሳሰረ
እንዴት የሚለው ቃል ከጭንቅላቱ ለሺኛ ጊዜ ተመላለሰ ከዚ ሁሉ ጊዜ በሁዋላ የሚለውም ተያይዞ
ለመጨረሻ ጊዜ የተናገረችው ንግግር ከጆሮው ተደቀነ
የሲጋራ ጭስ ስዕሎችን ሊረብሽ ስለሚችል ሲጋራ ይዘህ አትግባ ከስዕሎቹ ነው የተነገረኝ
ይሄ ንግግር ለሱ አዲስ አልነበረም ያኔም ስዕሏን ስትስል ሁሌ ሲጋራውን ሲለኩስ ትነግረው የነበረ ማስጠንቀቂያ ነው
አሁን ሁሉ ነገር ገብቶታል ጨዋታዋም እንደዛው ምን እንደሚያደርግ ግራ ገባው ልላ ትውስታ ከአይኑ እንዲደቀን አእምሮውን ለመነው በፍጥነት ስልኩን አውጥቶ ቁጥር መታ የምርመራ ክፍሉ ፀሀፊ ስልኩን አነሳችው በከተማው ውሰጥ የሚገኙትን የስዕል ማዕከላት አድራሻና ስም እንድትልክለት ነግሮ ስልኩን ጠረቀመው
ትንሽ ደቂቃ ጠብቆ ስልኩን ከፈተ ሁሉንም መረጃ ልካለታለች በትኩረት ይመለከታቸው ጀመረ የዳዊት ጨረቃ የስዕል ጋለሪ የሚል አድራሻ ላይ አይኑን አፈጠጠ እራሷ ናት በፍጥነት ተራመደ ተራምዶት የገባውን ጠርሙስ አድቅቆት አለፈ ሶልያና መጣሁልሽ አይኑ ደም ለብሷል በሩን ጠረቀመው
ያላጠፋው ቴሌቪዥን በቅርቡ የተከፈተው አዲሱ የዳዊት ጨረቃ የስዕል ማዕከል በድምቀት እየተመረቀ ይገኛል ጳውሎስ በረረ

ይቀጥላል.....
ብላቴናው በጨረቃ ምሽት

@wegoch
@wegoch
@wegoch
#የጨረቃ ልጆች

ክፍል - 10

ከማዕከሉ እንደደረሰ በቀጥታ ወደ መግቢያው ተራመደ የማዕከሉ ጠባቂዎች መግቢያ የሚል ጥያቄ አቀረቡለት ማንም ያስቆመኛል ብሎ አላሰበም መርማሪ ጳውሎስ እባላለሁ ስሙን ከመናገሩ ጠባቂዎቹ በፈገግታ ተቀበሉት ቦታ ተይዞሎታል እባኮ ይከተሉኝ ያልጠበቀው ነገር ሆነበት እንደምመጣ እርግጠኛ ነበረች ማለት ነው ብዙ ነገር አስገረመው
ከማዕከሉ እንደዘለቀ ያየውን ማመን አቃተው የስራ ባልደረቦቹ ከፍተኛ ባለስልጣናት የከተማው ከበርቴዎችና ቁልፍ ቁልፍ የሚባሉ ታዳሚዎች ከስዕል ማዕከሉ ተገኝተው ስዕሎቹን ይጎበኛሉ ቢዚ ማታለያያ ልታሸንፈው እንደማትችል አውቋል የደበቀችው ጨዋታ እስኪታወቅ ነው ይሄ ሁሉ ሳቅ እና ፌሽታ ለራሱ ብዙ ነገር እየነገረው ነው። ለደቂቃ ከቆመበት ቦታ አልተንቀሳቀሰም ወደ ቦታው ሚመራው አስተባባሪ ቀስ ብሎ አንቀሳቀሰው ስዕሎቹን አንገቱ እስኪዞር ይመለከታቸዋል ባለፉት ሰላሳ አመታት ውስጥ ድንቅ ሰአሊ ሆናለች ድንቅ አታላይም ድንቅ ጨዋታ ፈጣሪም አድናቆቱን የወደደው አይመስልም እስካሁን ልትታየው አልቻለችም አይኖቹ ሶልያናን ይፈልጋሉ
ይሄ ነው የተዘጋጀሎት ቦታ ጌታዬ አስተባባሪው ጳውሎስን አስቀምጦ ትቶት ሄደ ግራ ገብቶታል ከስዕል ከማዕከሉ ያያቸውን የስራ ባልደረቦቹን ጠርቶ የሆነው ሊነግራቸው ጨዋታዋንም ሊያጋልጥ አሰበ ሀሳቡ ብዙም አልቆየም አስተናጋጇ ምን ሚፈልጉት ነገር አለ ብላ እስክትጠይቀው ድረስ ሀሳቡ ማጋለጥ የሚለው ነበረ ጳውሎስ ከሀሳቡ ሳይነቃ ሶልያናን የሚል ድምፅ ለአስተናጋጇ አሰማት እሱም ያለውን አላስተዋለውም ከደቂቃዎች በሁዋላ ንግግር ታደርጋለች እስከዛ ምን ልታዘዘዎ ፈጠን ብሎ ውሀ አላት በዚ ሰአት ከንፁህ ውሀ በቀሮ ሌላ ምንም ሊታየው አይችልም ሁሉን ነገር ከማፍረጡ በፊት እሷን ማነጋገር ፈልጓል አይኗን አያየ ይሄ ሁሉ ጨዋታ ለምን ሊላት ፈልጓል መልስ ካላት።
የተሰቀሉት ስዕሎች እጅግ ውብ ናቸው ውብ ሴት በውብ እጇ የሰላቸው የጳውሎስ የምርመራ ባልደረባ ዮናስ ከጳውሎስ ጆሮዎች ላይ አንሾካሾከ ለካ መልቀቂያ ያስገባችው ይሄን የመሰለ የስዕል ማዕከል ለማስመረቅ ነው ጀግኒት ናት ዮናስ ማውራቱን አላቆመም ጳውሎስ በሽቋል ተነስቶ ስዕሎቹን ማየት ጀመረ አለፍ አለፍ እያለ በሚጠላት ሴት ስለተሳሉ ምንም እንኳ ውብ ቢመስሉ አርክሶ እያያቸው እንደሆነ አውቋል። አንድ ስዕል ላይ አይኑን አተኮረ በገመድ ታስራ ያለች አንድ ሴች ልብ ሲገርፋት ይታያል በደንብ ተመለከተው። እንዴት ነው ወደድከው የሰማው ድምፅ አስደነገጠው ወደዚኛው ስዕል እስክትደርስ እየጠበቁህ ነበረ ልጅቷን ልብ ነው እንዲ የሚያደርጋት ያፈቀረችው ሰው ልብ ነው ሚገርፋት አንዳንዴ የወደድከው ልብ ውብ ይመስልህና ባላወከው ሰአት ተቀይሮ ቆሻሻ ይሆናል ልባቸውን አቆሽሸው አንተንም ያቆሽሹሀል ማትረሳውን ህመም ይሰጡሀል የወደድከው ሰው በጥፊ ይምታህ እንጂ የወደድከው ሰው እግር ይርገጥህ እንጂ የወደድከው ሰው ምራቅ ይትፋብህ እንጂ ሁሉም ክፋት ከቆሸሸው ልቡ የሚመነጭ ነው እያት እስቲ ታሳዝናለች አይደለ እያት ከንፈር ታስመጥጣለች አይደለ ብዙ እንደሷ ተሰብረው ማይመለሱ አሉ እጅግ ብዙ የታሰሩበትንም ፈትተው ሚነሱ ጥቂቶች ይኖራሉ የዚህን ስዕል ጥቅስ አንብበው
ልብ ከምንም ነገር በላይ ከዳተኛ ነው
ኤር17:9
ቀጣዩን ስዕል ከተመለከተው ያቺ ምታሳዝነዋ ልጅ የታሰረችበትን ገመድ ፈታ ሚገርፋትን ልብ ስትጨፈልቀው ያሳያል እጇ በደም ተለውሷል ጭካኔ እንጂ ሀዘን የለም ከፊቷ ጨካኝ ልቦች ምንም ያህል ጊዜ ቢቆዩ አንድ ቀን ደግ በነበሩ ልቦች መጨፍለቃቸው አይቀርም 30አመትም ቢሆን ፈገግ አለች ንግግሯ አስገርሞታል አሳምሞታልም ከጎኑ ሆና ስታወራው ተመልሶ ያደረገባትን ግፍ ያስታውስ ጀመረ። ሀይለኛው ጳውሎስ በምፀት ሳቅ ዘወር ብላ አይኖቹን ተመለከተቻቸው ይሄን ስዕል ግዛው ብር ካለህ ካልሆነ ስጦታም ቢሆን እሰጥሀለሁ ታድያ አንዱን ብቻ ልጅቷ ጨካኙን ልብ ስትጨፈለቅው ያለውን ህመሜን ሳይሆን መዳኔን ማሳይበት ስለሆነ ስዕሉን ስሰጥህ ደግመህ ጥቅሱን ማንበብ አትርሳ
በትግዕስት አዛዥን ማሸነፍ ይቻላል
ምሳሌ25:14
ከመድረኩ ስሟ ሲጠራ ጥላው ሄደች ጳውሎስ ምንም ማሰብ አልቻለም ንግግሯን ለመስማት ጓጓ እጆቹ ይንቀጠቀጣሉ። በዚ ባማረ ምሽት አሸናፊዎች እና ተሸናፊዎች ፊት ለፊት በሚፋጠጡበት ምሽት ስለመጣችሁ አመሰግናለሁ ስዕሎቼንም ስላከበራችሁልኝ ስዕሎቼ ምስጋና ልከዋል ደስ የሚል ፈገግታ ለታዳሚዎቹ ሰጠች
አንዳንዴ ተጥሎ ተሰባብሮ የነበረ ነገር ሲጠገን ተመልሶ ሲተካ ልዩ ይሆኑአል ያንን ስብራት ለመጠገን ያንን የተሰበረ እቃ ለማደስ ስንጥር የውስጣችንም ስብራት ሲድን ይታወቀናል ይሄ ስዕል ከዛሬ 30 አመት በፊት ተሰባብሮ ተበጫጭቆ ተጥሎ ነበረ ከመድረኩ በመስታወት ውስጥ የተቀመጠ አንድ ስዕል መጣ እኔም ልዩ ነኝ ይህ ስዕልም ልዩ ነው ይሄን ስዕል ለመሳል ሶስት ቀን ፈጅቶብኛል ተበጫጭቆ ሲወድቅ ግን ለማደስ ድፍን 30 አመት ፈጅቶብኛል ስዕሉን ለማደስ ያን ሁሉ አመት ፈጅቶ ሳይሆን ስዕሉን በማደስ ተግባር ውስጥ የውስጤን ስብራት ለመመለስ ድፍን 30 አመት ፈጅቷል ስዕሉን ተመልከቱት ወደ ታች ቁል ቁል እየፈሰሰ ያለ ደም ይመስላል ክርስቶስ በመስቀል ሆኖ አለምን ለማዳን ሶስት ቀን ፈጅቶበታል ይሄም ስዕል በመስቀል ሆኖ የተሰቃየውን ስቃይ ያመላክታል አለም ስጢፋ ማይጠፉ ብዙ ነገሮች ሊኖሩ ይችላሉ እንደ ነፍሳችን ሁሉ ነፍስ የሚኖራቸው አንዳንድ በረከቶች ይኖራሉ። ጳውሎስ እራሱን መቆጣጠር አቃተው እንደምንም ከማዕከሉ ለመውጣት ወሰነ የሶልያና ንግግር ቀጥሏል ሁሌም እውነታ ወደ ውሸት ያስሮጣል ያሸሻል ሚነገረን እውነት ከሰራነው ውሸት ሀጥያት ሄዶ ስለሚጥለን ያሯሩጠናል ግን ውሸቱ ነው እውነትን ሚወልደው ሚሮጠው ሰው ውሸቱን ስለማያገኝ ተቅበዝባዥ ይሆናል ባሰመርክለት መስመር መጥቶ እጅህ ስር ሲወድቅ የሚሰማህ ደስታ ልዩ ነው ገራፊ ደብዳቢ ገዳይ ቢያሸነፍ ኖሮ እነዛ ገራፊዎች ክርስቶስን ባሸነፉ ነበረ ግን ሁሌም አሸናፊ ተበዳይ እና ለእውነት የኖረው ብቻ ነው መልካም ምሽት። ከመድረኩ ስትወርድ ሞቅ ያለ ጭብጨባ አስተጋባ ጳውሎስ ግን የተጨፈለቀውን ልብ ስዕል ይዞ ሸሽቷል በረጅሙ ተነፈሰች

ተፈፀመ
ብላቴናው በጨረቃ ምሽት

@wegoch
@wegoch
@wegoch
😂
ኮንዶሚኒየም መኖር ችግር ነው! ሁሉም ዶሮና በጉን በሩ ላይ አስሮ
ብሎካችንን ኤልፎራ አስመስሏታል። እኔም ትናንት ሚስቴ በግ ካልገዛህ
እያለች ስትነተርከኝ ጥቂት ብር ይዤ በግ ልገዛ ብወጣ አንድ ቀውላላ በግ
ነጋዴ ሁለት ፊታቸው ላይ ከባድ ድብርት የሚታይባቸውን ከሲታ በጎች ይዞ
ቆሞ አገኘሁና ጠጋ ብዬ
«ልትሸጣቸው ነው?» አልኩት
«እና ሐገር ላስጎበኛቸው ነው ካገሬ ይዣቸው የወጣሁት?» አለኝ
«እንደው ኩነኔ አይሆንም እነዚህን መግደል?» ስለው ፈጠን ብሎ
«አንቀህ ነው እንዴ ምትገድላቸው?» አለኝ
«አይ ያው በቢላም ቢሆን ...» ብዬ ሳልጨርስ
«ወንድሜ ካሳዘኑህ ውሰድና በጉዲፈቻ አሳድጋቸው» አለኝ
«እሺ ስንት ነች እቺ?» አልኩት ወደአንዷ እየጠቆምኩ
«በግ ታውቃለህ ማለት ነው። በጣም አስተዋይ በግ ነች እሷ» ብሎ
ጀርባዋን መታ መታ ሲያደርጋት ወደጎን ፍንግል አለችና አቧራዋን አራግፋ
ተነሳች።
«እኔ አስተውሎቷ ምን ይሰራልኛል ላስተምራት አይደለም እኮ ምወስዳት»
ስለው
«ሁለት ሺ ብር ክፈል» አለኝ
«ሁለት ሺ ብርማ አታወጣም»
«በርግጥ ላታወጣ ትችላለች ነገር ግን እኔ ሁለት ሺ ብር ነው
የሚያስፈልገኝ»
«ቀንስና ልውሰድልህ» አልኩት
«አይ ወዳጄ በጓን ግን አይተሃታል? ውስጠ ወይራ እኮ ነች። መፍዘዟን
አትይ። በዚያ ላይ በእንክብካቤ ነው ያደለብኳት»
«ጭራሽ ደልባ ነው እንዲህ የከሳችው?»
«አዎና! በርግጥ እኔ ስብእናዋ ላይ ነው የሰራሁት። በጥሩ ስነምግባር
ነው ያሳደግኋት» አለኝ ቆፍጠን ብሎ። ሳቄን ለመቆጣጠር እየሞከርኩ
«አንድ ሺ ብር ትሸጥልኛለ ...?» ብዬ ሳልጨርስ
«ውሰዳት!» አለኝ በደስታ ተሞልቶ።
ምነው ዝም ባልኩ ብዬ በይሉኝታ አንድ ሺ ብር ሰጥቼው በጓን ይዤ ልሄድ
ስል መራመድ አቅቷት በቀስታ ስታዘግም
«ቃሬዛ ቢኖርኮ ደግ ነበር» አለኝ ሰውዬው በጉን በሃዘን እየሸኘ።
ተበሳጭቼ ዝም ብዬው ስሄድ
«ወንድሜ እንደው ለነፍስ ትሆንሃለች መጀመሪያ የህክምና እርዳታ
አርግላት» አለኝ
መንገድ ላይ በጓን ያየ ሁሉ ከንፈሩን እየመጠጠ ያልፋል። አንዳንዱ እኔን
እያየ አንገቱን በሃዘን ይነቀንቃል። በግ ላርድ ሳይሆን እንደአብርሃም ልጄን
ልሰዋ ይዤ እየሄድኩ ነው ያስመሰሉት። ሽምቅቅ እንዳልኩ ቤት ደረስኩ።
ሚስቴ በጓን እንዳየቻት
«ምንድነው ይዘህብኝ የመጣኸው?» ብላ ጮኸች። በጩኸቷ ከኔ ይልቅ
የደነገጠችው በጓ ነች። አይኗን አስለምልማ መሬት ወደቀች! የመጀመሪያ
ደረጃ እርዳታ ላደርግላት ሞከርኩ። አልነቃ ስትለኝ በአፌ ትንፋሽ ልሰጣት
ሳጎነብስ ሚስቴ
«በዚህ አፍህ እኔ ከንፈር ጋር ድርሽ እንደማትል እወቀው!» ስትለኝ ቀና
ብዬ መጨረሻዋን ማየት ጀመርኩ ..
ውይይ! አረፈች! በጣም የሚያሳዝን ሁኔታ ነው የገጠመኝ ጎበዝ።
ለሚስቴ «ያ ሙታን አስነሳለሁ ሚለው ነብይ ጋር ይዘናት እንሂድ ይሆን?»
ስላት
«እሱ አክስቱ ሞታ ክፍለሐገር ሄዷል» አለችኝ። እሺ ምን ተሻለኝ ጓዶቼ?
«ቆይ ግን ...የግድ ስጋዋን ለመብላት እኛ ልንገድላት ይገባል እንዴ? ያው
ሞት ሞት ነው። በቢላም ሞተች በድንጋጤ ያው መሞቷ አይቀርም!» ስል
ሚስቴ ሶስት ግዜ አማትባ «በል አውጥተህ ጣል» አለች።
እኔ ግን ተስፋ አልቆረጥኩም! እቺን በግ እኮ ስጋዋን ፈልጌ ሳይሆን
እንደበግ እንድትተውን ነው የገዛኋት። አክተር ደሞ አይሞትም
ኦህህህህህ! ተመስገን!
ነቅታለች ጎዶች «እልልልል ...» (አሉ እትዬ ዘርፌ የቤት እቃ (ማማሰያ
ሳይቀር) እየሰረቀ ያሰለቻቸው ልጃቸው ሲታሰር)
እንዲህ ነው እንጂ በግ! ዝም ብሎ መሞት አለንዴ? እኛ ሳንፈቅድላትማ
አትሞታትም! አልኩ ለሚስቴ (አንዳንዴኮ እንደ አፍሪካ መሪዎች ሚያደርገኝ
ነገር አለ። ተመልሳ ሳትወድቅ ብሬክ ላርጋት።

© የሀገር ጥበብ

@Wegoch
@Wegoch
@Mahletzerihun
#not_polytricks_its_just_a_ወግ
...ትናንት ለአንድ ጉዳይ ወደ 6 ኪሎ ግቢ ሳመራ..በስንት ጊዜዬ አራት ኪሎን
ረገጥኳት..ከዛ በአይኔ ዙሪያ ገባውን ስቃኝ የቀድሞ ባሻ ወልዴ ችሎት
አደባባይ ገደማ ቤተሞግዚቱ በር ላይ ያለችውን peacock እንዳየው
ለሰፈሩ የእንግዳነት ስሜት ተሰማኝ...የዛ አካባቢ ድባብ ፈፅሞ መለወጡ
ገባኝ...ትንሽም አመታት ቢሆን የኖርኩባት እሪ በከንቱ ናፈቀችኝ...መከላከያ
ጋራዥ፣ ግንብ [ዝንብ] መደዳ፣ቱሪስት ጀርባ፣ ፣ሁለተኛ ፖሊስ ጣቢያ፣እሪ
በከንቱ ድልድይ፣በርጌስ ክሊኒክ፣ white house፣ ሠራተኛ ሠፈር፣ለ free
wifi ብርድ የጠጣሁበት ማዕከላዊ ስታቲክስ፣ ከፍ ብሎ ኢንሪኮ፣አሮጌ
ቄራ፣ ናፓሊዮን የሚባል ጓደኛዬ በፍቃዱ ሁሉም ሀሳቤ ላይ ለደቂቃ
ተመላለሱ.....ከዛ መለስ ብዬ ያቺን Giant peacock በተመስጦ
አየዃት..መግቢያው እጅግ አሸብርቋል....ምናልባትም አናቷ ላይ ለጌጥ
አምፖል የተሰካባት አነስተኛ የሳር ጎጆ ነገር ብትኖር የቃልቻ ደጅ ይመስል
ነበር...በራሴ ሀሳብ ፈገግ አልኩ...ከዛ ወዲያው አባባ ታምራት ትዝ
አለኝ...የት ገብቶ ይሆን እሱ ሰውዬ አልኩ? ያ ሁላ የአንድ ሰሞን ትሪኩ ትዝ
አለኝና በውስጤ ሳቅኩ...ምን አይነት ብልህ ሰው ቢሆን ነው እንደዛ
የተጫወተብን አልኩ ምን አይነት ገራገር እና ምስኪን ብንሆን ነው
አልኩ...ግን ወዲያው ምቀኝነታችን ትዝ ሲለኝ ሀሳቤን ቀየርኩ፣...በእውነቱ
አንዳንዴ የሰዎችን ድክመት እንደመጠቀም ረቂቅ ብልህነት የለም ...እና
አባባ ታምራትን በዚ ብልሀቱ አደንቀው ነበር ከልቤ...ለታዳሚዎቹ ክንፍ
እየተከልኩ ወደ አሜሪካ አስበርራችሁዋለው ይላቸው የነበረው ጨዋታ
ትዝ ሲለኝ መልሼ ፈገግ አልኩ...እሱን ተከትሎ ወዲያው ደሞ ብልፅግና
የሚለው ሀሳብ ከየት መጣ ሳልለው ድንገት ክስት አለልኝ
...ከ40 አመት በዃላ አለም ላይ 2 ሃያላን ሀገራት ይኖራሉ አንዷ
ኢትዮጵያ ትሆናለች!!...ማን ነበር ይሄን ያለው በውል ትዝ አይለኝም
...እና ዞሬ ዞሬ ከሀሳቤ መለስ ስል አብሮኝ ለነበረው ጓደኛዬ እንዲህ
አልኩት...ለምን እንደሆነ አላቅም ይሄን በርና የፒኮኮቹን ድባብ ምናምን
ስታይ የሆነ የቃልቻ ግቢ ነገር አይመስልህም ስለው ከተቀመጠበት በሳቅ
ወደቀ ...ምን እንዳሳቀው ግን ለማወቅ አልጓጓሁም...ከፈለጋቹ
እናንተው ጠይቁት

© Samson Ali

@wegoch
@wegoch
@Mahletzerihun
ልጅ ሆኜ _
ነፍሴን የዳርኩለት የልጅነት ሙሽራዬ እርሱ ነው ፤ ጧት ደጁ ልሄድ ሳስብ ሌሊቱ በቅጡ እስኪነጋ ልቤ ተሰቅሎ አሸልባለሁ ፤ ሊነጋጋ ሲል በርግጌ ተነስቼ ፊቴን አብሼ ብጣሽ ነጠላዬን አንገቴ ላይ አስሬ የሚያምር ንጋት ላይ የተኳለ ውበት የእርሱ ነው እያልኩኝ ፤ ወደቤቱ የማዘገም የማለዳ ወፍ ነበርኩ ።
ታዳጊ እያለሁ_ የሆነ ቀን እናቴ ሞተችብኝና ከሁሉ ነገር ስጣላ እርሱም አልቀረለትም ። መጋረጃ ጋርደው ያስቀመጡት ሳጥኗ ፊት በቸልታ እግሬን አጣጥፌ ተቀምጬ ካድኩት " የራስህን እናት ሞት ከማየት አንተ ቀድመኻት የሞትከው ራስ ወዳድ ብትሆን ነው..... እኔን ቁጭ አድርገኸኝ እናቴን ስለወሰድካት የሰጠኸኝ ህመም መቼም
የሚድንልኝ አይደለም ብዬ ፤ አቄምኩ አኮረፍኩ ። እና ከዚያ በኋላ መቃብሯን ላይ ስሄድ ያሳደገኝ ደጁን ትቼ በጓሮ እናቴ ጋር ደርሼ የምመለስ አኩራፊ ሆንኩኝ ስጎረምስ_ በእርሱ ምክንያት በሄሮድስ ትዕዛዝ ያለቁ ህፃናትን አስቤ የምበሳጭ ፣መስቀል ተሸክሞ ሲሄድ አግኝቶት ምን ያንቀረፍፍኻል ስላለው ብቻ ዘላለም መባዘንን ስለፈረደበት ከርታታው ይሁዲ የምብከነከን ፣ ብስጩ ሆንኩ ከዚያ_ አኩርፌ ተበሳጭቼ ከርሱ ተለይቼ ከደጁ ርቄ ፣ እየኖርኩ ባለሁበት ፣ ሌሊት ከእንቅልፌ ነቅቼ የምሰማው ምህላ አንጀቴን በናፍቆቱ የሚያንሰፈስኝ ፣ ፋሲካ ሲደርስ ህማማቱ ፀሎተ ሃሙስ ላይ እንግልቱ ነፍሴ ድረስ የሚሰማኝ ፤ ለስቅለቱ በኪራላይሶ መሃል ጎንበስ ቀና የምልለት ከክህደት ተመላሽ አማኝ ሆንኩኝ አሁን _ በቸልታ የተሞሉ ቀናቴ መሃል በልጅነቱ ስላደረጋቸው ታዓምራት አስባለሁ ። ቀራኒዮ ላይ ግራና ቀኙ የተሰቀሉ ወንበዴዎች ልጅ እያለ ከእናቱ ማርያም እና ከእጮኛዋ ዮሴፍ ጋር ሲሰደድ አግኝተውት ኋላ ላይ በግራ የተሰቀለው እንዝረፋቸው ሲል በቀኝ የተሰቀለው አይነውሃቸውን አይቶ እዝነት ልቡን ጎብኝቶት አንዝረፋቸው ብሎ ጭራሽ ጨቅላውን እንኮኮ አድርጎት ረጅም መንገድ ሸኝቷቸው ተሰናብቷቸው ሲሄድ የልብሱ ጠረን ተቀይሮ እርሱን እየጨመቀ ይሸጠው ስለነበር እንኮኮ ካለው ጌታው ወደ ልብሱ ስለተጋባ አልባስጥሮስ ሽቶ የማስብ ሆንኩ .... አለ አይደል " በዘረፋው ቀጥሎ መጨረሻው ቀራኒዮ ከሚሆን ሽቶውን እየጨመቀ አይሸጥም ነበር " እያልኩኝ ወይም ደግሞ በረሃ በስደት የደረሱባቸው የሄሮድስ ወታደሮች እንዳያዩዋቸው በእናቱ እቅፍ ሳለ ሰንጥቆት የተደበቁበትን ዛፍ ማን ቆርጦት ይሆን የምል ፤ ካልሆነም በአናጢነት ዘመኑ
የጠረበው ወንበር ላይ ማን ተቀመጠ? አልጋውስ ላይ ማን ፍቅር ሰራ? ምናምን
ብዬ የምጠይቅ ... እስከ ግራ መጋባቴ ርቄው እንኳን የሚናፍቀኝ ፣ እብሪተኛውን ልቤ በፍቅሩ የሚያንሰፈስፍ እየሱስ ልደቱ ነበር።

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Elssa Mulugeta
ምናገባቸው ቆይ! ስለኔ መክሳት መጥቆር መዘነጥ መጎሳቆል! እንዴ??

ጓዳቸው ውስጥ ያልፈቱት የራሳቸው ቋጠሮ ተከምሮ እያለ የምን የሰውን መፍታት ነው?
አላወራም ብዬ እንጅ ... የራሴን ጉዳይ አረረም ጣፈጠም ራሴው ልያዘው ስለሰው ምን አስፈተፈተኝ የራሴ ያረረው ድስት እያለልኝ የሰው ምን አማሰለኝ ብዬ እንጅ አናውቅም እንዴ? ስንት ድስት እንዳረረባቸው? ስንት ነገር ከህይወታቸው እንደተደፋባቸው?
ስንቱስ በየቤታቸው ጨለማ ታቅፈው ውጭ ውጭውን ብቻ ደምቀው እንደሚታዩ??

እንዴ በቃ ምን አገባሽ.... አጣው ነጣው አይደል? ምንሽ ተነካ እንች? ከቻልሽ ነይ አፅናኚኝ ወይ ደግፊኝ ካልቻልሽ አፍሽን ዝጊ! እንዴ???

ወደኩ አይደል? የጀመርኩት ስራ ህይወት ፍቅር ምናምን ሁሉ ገደል ገባብኝ አይደል? እና ምን ይጠበስ? ዳር ሆነህ ምን ወሬ አራገበህ? ምን በየቡናው ላይ ግዜ ማሳለፍያ አደረገህ? ምንስ መንገድ ላይ ስታየኝ አፍህን አስያዘህ? ለምን መጥተህ የምትረዳኝ ነገር ካለ አትጠይቀኝም ወይ አታወያየኝም? አለዚያ አፍህን ዝጋ! እንዴ? ሰው እንደራሱ ሆኖ መኖር አይችልም እንዴ? ጎበዝ!

መውደቁ ሳይሆን የሰው ምላስኮ ነው እየገደለን ያለው. ቢዝነስ ጀመረክ በውሀ ተበላህ..እንበል.... ከክስረትህ በላይ አላስቀምጥ የሚልህኮ የማያከትም ቡናቸውን እያንቃረሩ ወሬ የሚለቃቅሙ የወሬኞች ቀደዳ ነው.......
" የያዘችው ስራኮ በቂዋ ነበር ስትስገበገብ ነው እንጅ!ይበላት?"...." አሁን የኮራ የደራ ስራዋን ትታ ምን አንዘጠዘጣት...አወይ ሰው ? ስግብግብኮ ነው... አይ በቃኝን አለማወቅ ...ምፅ"...... ስራዬ ያስደስተኝ አያስደስተኝ ..... ማገኘው ገንዘብ ይብቃኝ አይብቃኝ ምን አባሽ የምታውቂው ነገር አለና ነው? ተራራው አናት ላይ ተሆኖና ተራራው ግርጌ ተሆኖ ከተማ እኩል ይታያል እን ዴ???

ጥቁርቁር ስትይ... ልብስሽ ላይሽ ላይ ሲውለበለብ... ምድረ አስመሳይ ከንፈር መጣጭ...ሁላ መላምቱን ያዝጎደጎደዋላ.... ከሰላምታ በኋላ ....." ምነው ከሳሽ? አመመሽ እንዴ? ከባልሽ ጋ ሰላም ናቹ?.. ምፅ አይዞሽ " ዞር ይልና ከቢጤው ጋ. ገጥሞ..... አርግዛኮ ነው?? ..... ቧሏልሽ ይደበድባታል አሉ ብታይ ...ባርያ በያት ምን ይች ሚስት ነሽ ቱ!...."
ኧረ በወላዲቱ! ምን የምታውቀው ነገር አለና ነው እንዲ የምትደሰኩረው? ከኔጋር የምትኖር አይመስልም እንዲ ስታወራ ለሚያይህ?
አንዱኮ ነው ( በለው! እዚው ጀመረችው እንዳትሉኝ እንጅ!!) ጎረቤቱ ቲቪ ይገዛል ከዛ ልጁ አላስቀምጥ ትለዋለች "አባ ቲቪ ግዛ? እነማሙሽ ተገዝቶላቸው የለ?" ሰውየው ከየት ያምጣ.... እንደምን ብሎ እቁብ ብድርም አድርጎ ገዛ!... ተወራ ስለአዲሱ ቲቪ! እንደጉድ!..... ከወራት ቡሀላ ጎረቤቱ ዲሽ ይገዛላችዋል... መቼም የልጅ ነግር ሁሌ አምጣ ነው ግዛ ነው.. ... ንዝንዝ!..... ሰውየው ጨነቀው...... ብድሩንኳ ሳይከፍል...... በስተመጨረሻ... ቲቪውን ሸጦ ዲሹን ግዝት! እና ምን ያርግ?? ልጁ በዚ ሚስቱ የሰፈሩን ሀሜት ሰምታ በዚ ስትነዘዝንዘው ምን ያድግ.??

ኧረ ተው ተው ተው ግን??


ደሞኮ ወረቱ ሲያልቅ አብረው ያሙኝ ይጣሉና እም! ያኔ ያወሯት እንድም ሳትቀር ጆሮዬ ትደርሳለች! የፈሷት ሳትቀር! አቤት ግን በቃ መበላላት ነው ስራችን? ምናለ ሁላችንም የየራሳችንን ድስት ብናማስል?

በቃ ከሳች አይደል.. እሰይ እንኳን ከሳች ከቻልኩ ምክንያቱን ጠይቄ ልረዳት ሞክራለው ካልሆነ ዝም! ዝምን ማን ገደለው?..... ከሰረ አይደል? እንኳን ከሰረ? የሚሰራ ሰው ይከስራል...መልሶ ያገኘዋል ምን እዚ ወሬ አራግባለው....

ኧረ ወገን! ተው መበላላቱ ይቅርን? ተው ተው ግን?


ተፃፈ by aggie

@wegoch
@wegoch
@paappii
ገ ' ና ነው


፡ እስካሁን "እስክቢርቶ ለምን ያገለግላል?" ብሎ የጠየቀኝ የለም እንጂ መልሴ የሚሆነው አንደኛ ስለሷ ለመፃፍ ፡ ሁለተኛ ስለሷ ለመፃፍ ፡ ሶስተኛ ስለሷ ለመፃፍ ነበር የሚሆነው። ነገር ግን ስለሷ ልፅፍ ብዕሬን ሳነሳ አቡጊዳ ያልተማረ መሀይም እሆናለው። ማለት ምፈልገውን ብዬ አላውቅም።
ገና ከበአላት ሁሉ ደስ የሚለኝ በአል ነበር የዛሬን አያርገውና ። ዛሬ ግን በአል የተባለ ነገር ያስጠላኛል። ለምን ብትሉኝ ለበአል ሰው ሁሉ ከቤት አይወጣም። እኔን ያስጨነቀኝ የሰው ከቤት አለመውጣት አይደለም። ከፈለገ ዝንት አለም ከቤት አይውጣ።የኔ ጉዳይ አይደለም። እኔን ያስጨነቀኝ ለበአል ከቤት ከማይወጡት መሀል የብዕሬ ንግስት አንዷ ስለሆነች ነው። ዛሬ ግን ፀሎት ሳላደርግ ፡ ስለት ሳልሳል ፀሎቴ የደረሰ ስለቴ የሰመረ ያክል ተሰማኝ። ምክንያቱ ደሞ የስልኬ መስታወት ላይ "ንግስቲቱ እየደወለች ነው" የሚል ምልክት እያየው ስለሆነ ነው።
"ሄሎ ቤኪ እንዴት ነህ ፤ እንኳን አደረሰህ ፤ ለነገሩ ቀድመኸኛል።"(ቀድሜ የእንኳን አደረሰሽ መልእክት ልኬላት ነበር)
ይገርማል እኔ ከደወለች እንዲ እላታለው ብዬ ለቀናት የማስበውን ነገር እሷ በሰከንዶች ውስት እንደ ቀላል ነገር ትናገራቸዋለች።
" እንኳን አብሮ አደረሰን በአል እንዴት ነው " አልኳት
" በአል ባክህ ይደብራል ፤ በአል በአል አልመስልሽ ብሎኛል" አለችኝ። በመሀል ከስልኩ ራቅ ብላ ስትስቅ እሰማታለው ፡ በምንና በማን እንደምትስቅ አላውቅም ነገር ግን ዝም ብዬ አብሬአት እስቃለው።
የኔን ወሬ አልጠበቀችም " እኔ ምልህ ቤኪ እዮብ ደውሎልኝ ' ቤተ ክርቲያን መርሀ ግብር አለ ነይ ' ብሎኛል አብረኸኝ አትሄድም?" አለችኝ። " ወደ ሞት እንኳን ቢሆን በደስታ እንደምሄድ ማን በነገረሽ " አልኩኝ በውስጤ። አፌ ግን የሚያወራው ሌላ ነበር " ስንት ሰአት ነው?" አልኳት። " ከሌሊቱ 9 ሰአት" ብትለኝ እንኳን እንደማልቀር እያወኩት ለምን ሰአት እንደምጠይቃት አልገባኝም። " ሰባት ሰአት ነው ያለኝ "አለችኝ። ሰአቴን አየሁት 4:30 ይላል የሰአቱ እርዝመት እያሰብኩኝ " በቃ ስቶጪ ደውይልኝ" አልኳት። " እሺ ቻው " አለችኝ። ቻው ከምትለኝ ዝም ብላ ጆሮዬ ላይ ብትዘጋብኝ በተሻለኝ ነበር። ሰአቱ እንደምንም እያዘገመ ደረሰ ተገናኘን። ከዚ ቡሀላ ቤ/ክ እስክንደርስ ድረስ ያወራነውን አልፅፈውም። ምክንያቱም ለሌላ ሰው ተራ ወሬ የሚመስል፤ ምንአልባትም ለሷም ጭምር ተራ ስለሚመስል ለኔ ግን ጥዑም የመላዕክትን ዝማሬ የምሰማ ያክል ይሰማኝ ነበር። ከአንደበቷ የሚወጡትን ቃላት ወድቀው እንዳይሰበሩ የምጠብቃቸው ይመስል አፍ አፏን እያየው እመሰጥ ነበር። እየሄድን ያለነው እግር መንገድ ዳገት ከመሆኑም በላይ የዘንድሮ ፀሀይ ተጨምራበት እያነደደችን ነው። በጣም ደክሟታል እኔም ደክሞኛል ድካሜ ግን ለኔ ያን ያህል ቦታ አልነበረውም። የሚታየኝ የሷ ድካም የሚሰማኝ የሷ የድካም ትንፋሽ ነበር ። ጀርባዬ እንደዛ ደክሞት እንኳን እሷን ለመሸከም ይጓጓ ነበር። አፌ ግን እንኳን ልሸከምሽ ሊላት አይዞሽ የሚል የማፅናኛ ቃል እንኳን አላወጣ አለ። በዚ ሰአት ስልጣኑና ችሎታው ቢኖረኝ አፌንና ልቤን ቦታ አቀያይራቸው ነበር። ለነገሩ ከበሮ በሰው እጅ ያምር ሲይዙት ያደናግር አይደል ሚባለው ልቤም ቢሆን የአፌን ቦታ ቢይዝ አንዲት ቃል ትንፍሽ የሚል አይመስለኝም። መንገዱ ያን ያህል እርቆ በምን ፍጥነት እንደደረስን አልገባኝም። ለምን ቶሎ ደረስን አላልኩም ፈጣሪ ነውና ፤ እንኳን ደረስንም አላልኩም ከሷ ጋር ሁኜ ምንም ነገር ማየትም መስማትም ስለማልፈልግ። ስንደርስ ፀሎት እየተደረገ ነበር ። ፀሎቱ እንዳለቀ ፕሮግራም ተጀመረ።ከገባን ጀምሮ እያወራን ስለነበር ከፕሮግራሙ ሁሉ የሰማችው (እኔ ምንም አልሰማሁም) አንዱን ብቻ ነበር። አንዷን ፕሮግራም እንኳን እንዳልሰማ ትከሻዬን ተደግፋ የኔን ጆሮ ሰርቃ ብቻዋን የእግዜርን ማዕድ ትኮሞኩማለች። እኔ ግን በዛ ሰአት ማስበው ' ትከሻዬ ይቆረቁራት ይሆን ' 'ከፍ ብዬባት ለአንገቷ አልተመቻትም ይሆን ' እያልኩ አስብ ነበር። የሷ አስተኛኘት ግን በጥጥ የተሰራ ትራስ ላይ የተኛች ነበር የሚመስለው። እንደተመቻት ሳውቅ ዘላለም ትከሻዬ ላይ ብታርፍ ብዬ ተመኘው። ብዙ ጊዜ ምኞቴ አይሳካልኝም ። ገና ከማሰቤ ትምርቱ አልቆ ከትከሻዬ ተነሳች። ተናድጃለው ነገር ግን በማን እንደተናደድኩ አላውቅም።
" በሷ ይሆን "
" አይ በሷማ አይሆንም ፤ ይሄን እንደጦር የሚዋጋ ትከሻህ ላይ ስለተንተራሰች እንደውም ልታመሰግናት ይገባል "
" ታዲያ በአስተማሪው ነው?"
"ስታስበው ይሄ አስተማሪ የማይደክመው ሮቦት ይመስልሀል"
" በቃ ጊዜው ነው ያናደደኝ "
" ሰውዬ ከጊዜ ጋር ባትጣላ ጥሩ ነው ፡ ደሞስ ለዚህ እራሱ ያበቃህ ጊዜው አይደል"
ጭንቅላቴ ውስጥ ሀሳቦች እርስ በርሳቸው እየተጋጩ እራስ ምታት አስያዙኝ። በሀሳቦች ተከብቤ ሳለ አንድ ሰው ደወለላት። አነሳችው ፡ አንስታው ያወራችውን በጠቅላላ ሰምቻለው ነገር ግን ለሚያየኝ ሀሳቤ ሁሉ ፕሮግራሙ ላይ ያለ ይመስል ነበር።የምታወራበት ሰአት እየጨመረ በሄደ ቁጥር ቅናት ይሁን ምን ውስጤን ይበላኝ ጀመር ። በዚ ቢበቃ እሰየው ብሎ ብሎ ካርድ ላከላት። " ቤኪዬ ካርድ ተላከልኝ ስንት ትራንስፈር ይደረግልህ?" አለችኝ እየሳቀች። እሷ በደግነት እንደሆነ አውቃለው ፤ ውስጤ ግን " ደሞ እሷን ማሳቁ አንሶ ጭራሽ የሱን ብር ልትቀበል ፡ ቢቻልህ ያለበት ሂደህ የፈላ ዘይት ፊቱ ላይ በደፋህበት " ይለኛል። ይህንን ንዴት ግን የኔ ፊት አያውቀውም። ዝም ብሎ በሳቀች ቁጥር አብሮ ይስቃል።

ገ ' ና ነው
የጌትነት ልጅ ፃፈ

@wegoch
@wegoch
@Mahletzerihun
"አሁን ምን ልታደርግ ነው?"
አልኩት... አንድ ....ብዙ የህይወት ጨለማዎችን እንዳሳለፈ ባገኘኝ ቁጥር የሚተርክልኝ ጓደኛዬን....... ከስንት አፈርድሜ መጋጥ ቡኋላ ተሳክቶልኝ ይኸው ሰው ሆኛለው ብሏል. ( ከሱ ሰምቼ ነው ይህንንም) በቅርቡ ነው የተዋወቅነው ባጋጣሚ!

"ሰው ልገዛ!"አላለኝም!!

ህም! ... በቃ ትንሽ ጨላ(money!) ስንጨብጥ ፈጣሪ የሆንን ነው የሚመስለን?............

ትንሽ ቆይቼ ግን ቆይ ይሄ ሰውዬ ምን ያህል መገፋት ደርሶበት ይሆን እንዲ የተናገረው? ብዬ አሰብኩ( ማለትም ያ ፈልጋል በርግጥ)


.........እውነት ግን ቆይ ወዴት እየሄድን ነው? ምን እያደረግንና ነው?

ሀብት ላለው ሰው አጎብዳጁ ብዙ ነው! ባለጠጋውንም እኮ እንዳያስተውል በሙገሳ ና በአጉል ክብር ገመድ አንቀን ገድለነው....
ሰውን በፍቅር እንጅ በገንዘብ እንደማይገዛ እንዳያስብ አደረግነው.

አሁን ይህ ሰው ምኑ ይፈረድበታል ቆይ?... ያኔ ነጫም ደሀ በነበረበት ግዜ የገፋው ሁላ አሁን ላይ እንኮኮ ሲለው ቢታየው ...ምን ይገርማል? ....ያኔ በቅጡ እንኲ ሰላምታ የማይሰጠው ማህበረሰብ ዛሬ ሲነጠፍለት ቢያልም ምኑ ይደንቃል? .....የገፋችው የህይወቱ ንግስት ካለችበት ቦታ ብረት ወደ ማግኔት እንደሚሳበው ስትመጣ ቢታየው ምኑ አጀብ ያሰኛል?...
ድሮ ብድር እንኳ የነፈጉት ሰዎች ዛሬ መንገድ ዳር ሲያዩት አከርካርያቸው እስኪቀነጠስ ተጉንብሰው ይዘይሩታል. ....... ምድር ላይ ያለ የተዛነፈ ስሌት ነው! ይሄ እንግዲ ...ምንም አያስደንቅም!

በተለይ በሴቶች ይብሳል.. ንፁ ልቡን መስዋት አድርጎ እያፈቀራት ... የሷ አይን ግን ከኪሱ ላይ ነው!(ሁሉም ማለቴ አይደለም በርግጥ) የአይናቸው ሞራ የተገፈፈላቸው ልባሞች አሉ. ችግሩ በዳበሳና በባትሪ ነው እንጅ የሚገኙት! ልቡ ባዶ ጋን ሆኖ ኪሱ ብቻ ይሙላ... ጉንዳኖች እንደሚወሩት የማር ጠብታ ግርርር!...... ከዛስ? ከዛማ.... ብሩ ሲያልቅ እብስ! .....ወዴት? ወደሌላው ልበ-ጎዶሎ ና ንዋየ-ሙሉ ተባዕት ነዋ!

ምን እሷ ብቻ ወንዱስ ቢሆን! ገንዘብን ቢያፈቅር አይደል ......እናቱ አይደለም አያቱ ከምታክል ሴት ጋር እሚዘለው? ኧረ እናንተዬ! .... ይህ ፍቅረነዋይ
አይናውጣ አድርጎን የለም እንዴ? እጅግ በጣም ተገርመሽ 'ምን ነክቶክ ነው ማሚን ከምታክል ሴት ጋር እምትዘለው?' ስትይው.....ፈገግ ብሎ ' እናቱ ቢዝነስ መሆኑን አታውቂም እንዴ?' ይልሻል!
ምን ትያለሽ ታድያ..... አግራሞትሽን ተከናንበሽ ጥርግ!

ከልክ ያለፈ ክብር መስጠት ለተቀባይ ትርፉ ልቡ በትዕቢት መሞላት ነው!

ጎበዝ! ገንዘብንኮ ሰርተነው ነው! ይህ እውነት እየተረሳ ሳሄድ አይቀርም....ወደፊት እንደውም ... አስደናቂ የአለም እውነታ ተብሎ "ገንዘብ የተሰራው በሰው ልጆች ነው!"ተብሎ መምጣቱ አይቀርም. ሁሉም ያነበበው ሰው አፉን በጁ ጭኖ ይደነቃል! ምን አለች በለኝ!

"ገንዘብ ገንዘብ ገንዘብ ያለው ያወጣ
ይስራ ያልሰራበት አገር እንድታድግ ሁሉም እንዲያልፍለት!"

ከምንመፃደቅበት...... ያገር ሴቶችን በግራ በቀኝ ከምናግበሰብስበት ........ በየመሸታ ቤቱ ገብተን አእምሮ ቢስ ና ለሆድ ኗሪ ጅብና አህያን ከምንጋብዝበት.........ለምን አንሰራበትም ቆይ? ሀብታም ተብዬው ቋጣሪ!(በኢንቨስትመንት እና በልማት ደረጃ ስንመጣ ማለት ነው) እጅህ ሊቆረጥ ነው የተባለ ይመስል ይሰበስባል! ለመደፋፋትስ? እንቡጥ ሴቶችን ለመግዛትስ?....ኪስን ወጥቆ መንደር ለመንደር ዲታ ነኝ ብሎ ለማስወራትስ አንደኛ!..... ድሀውም የባሰ ቋጣሪ! እንደውም በሱ ይብሳል!

" እንኳን ገንዘብ ሰውም ሲገላበጥ ነው የሚዋለደው!"

ላለው አንስገድ ወገን! እሱስ ኬት አባቱ ያመጣው ይመስልሀል? ከላይ ዘንቦለት? No........ ሰርቶ ነው አልያም ዘርፎ! ግፋቢል ወርሶ! እሱ ካገኘው እኔንስ ምን ገደበኝ? ያው ዝርፍያውን ማለቴ አይደለም.... ይህ ለችስታዎቹ ነው!

አንተ ደግሞ ዘርፈህም ይሁን ሰርተህ.... ወርሰህም ይሁን ሎተሪ ወቶልህ... ባለጠጋ የሆንከው..... አካፍል ...ስራበት... ለድድ አስጭዎች ስራ ፍጠርበት... የወደቁትን አንሳበት.... ካልሆነ ለኛ ስጠን... እንጅ አትኮፈስበት! ....ሰው ገዛበታለው አትበል.... ገንዘቤን ይጭነቀው አ..ት..በ..ልልልል!

እስከመቼ ድህነት ሚባለውን እከክ ታቅፈን እንዘልቀዋለን? ኧረ እንፋታው! እስቲ ይለፍልን እኛም ዘና እንበል.....በየቲቪያችን 'ዛሬ ኢትዮጵያ ለእገሌ ሀገር ይህም ያህል ብድር ሰጠች!' የሚለውን ዜና እንስማ! እስከመቼ ተበደረች! እስከመቼ ብድሯ ተሰረዘ! እስከመቼ አንገት መድፋት!

"አሥሬ ከመፍሳት አንዴ መቅዘን!" አለ መንጌ!

ይቅርብን እስቲ ለባላባት ማጎብደዱ! አጎብዳጅ ሲያጣ ሳይወድ በግዱ ወደስራ ይዞራታል............ለሥራ እናጎብድድ! እንካፈል.. እናካፍል... እንስራ....
(የሸክላውን እንስራ አይደለም ታድያ! እ!)

ተፃፈ by aggie

@wegoch
@wegoch
@wegoch
my very first superhero
{ ቀልጦ እንደሚበራ ሻማ ፤ መብራት በሌለው ከተማ }

ከድመት አፍንጫ በቀዘቀዘች ፤ አዲስ ነገሮች ከአለም እጅግ ዘግይተው በሚደርሱባት ትንሽዬ የገጠር ከተማ ውስጥ የምኖር የስድሰተኛ ክፍል ተማሪ ፤ ታዳጊ ልጅ ነበርኩ ። አንድ ቀን ሱቅ ተልኬ ስሄድ ባለሱቁ እየገነጠለ ስኳርና ቡና የሚጠቀልልበት መፅሃፍ ላይ አይኔ አረፈ። ከመፅሃፉ ላይ ጥቂት የማይባሉ
ገፆች ገንጥሎ ስኳር ምናምኑን ቢቸረችርበትም እንዲሰጠኝ ስጠይቀው በምትኩ ሌላ ወረቀት ማምጣት እንዳለብኝ ነገረኝ ። ቤት ተመልሼ የድሮ ደብተሮቼን ሰብስቤ አስረክቤ መፅሃፉን ተቀበልኩት። ያ መፅሃፍ የተክለፃዲቅ መኩሪያ 'ዐፄ ቴዎድሮስ እና የኢትዮጵያ ታሪክ" ነበር ።

{ ህይወት እንዳይሰለቸኝ ፤ ሲጨነቅ ሲጠበብልኝ}

በዛ ብዙ ነገር እንደነበረ በቀስታ በሚያዘግምበት ህይወት መኻል በታዳጊ
እድሜዬ የተደበቅኩበት ፤ ከቋራ እስከ ጋፋት ፣ ከሽርጌ እስከ መቅደላ ፣ ከዳሞት
እስከ ደንቢያ በምናቤ እንዳካልል ያደረገኝ የደጃዝማች ኃይሉ ወልደጊዮርጊስ እና የወ/ ሮ አልጣሽ ልጅ የመጀመሪያው ጀግናዬ ካሳ ሃይሉ ነው።

{ አየሁኝ ጥበብ ሰማሁኝ እውቀት ፣ ልናገር ልመስክር የዚህን ሰው ውበት፣ }

ያ በልጅነት ምናቤ በአንበሶቹ መሃል ሲንጎማለል የምስለው አፄ ቴዎድሮስ
የምርም ግርማው ብቻ ሳይሆን ተግባሩም ጀግንነት ነበር ማን አለ ከእርሱ ሌላ ? ኢትዮጵያን አንድ ለማድረግ የጣረ የለፋ የደከመ ' ሃገሬን' ሲል የራሱ ቤተመንግስት እንኳን ያልገነባ ? ማን አለ እንደርሱ ?ንጉስ ከመሆኑ በፊትም ቅጥ ና ስርአት የሌላቸው የዘመነ መሳፍንት ባላበቶች የሚቀማውን ገንዘብ ለገበሬዎች እያካፈለ ሞፈር እና ቀንበር እንዲገዙ የሚረዳ የሃበሻ ሮቢን ሁዱ? ማነው በዛ ዘመን ቁጭ ብሎ ከማዘዝ ይልቅ ራሱ ሰርቶ ህዝቡን የሚያሰራ ንጉስ የነበረ? (ማለት ለታይታ መጥረጊያ እንደሚይዙት እነ እንትና ሳይሆን ከልቡ የምሩን ) ሌላም ብዙ ብዙ ....

{ እየቀለጠ የበራልኝ ፣ እየሞተ ያኖረኝ }

እና ግን እግዜር ይሄን ታላቅ ሰው ከምን ጋር አስተላለፈው ? ከዘመን ጋር ለራሱ የሚበጀውን የማያውቅ ህዝብ መሃል ሃገሬን ከሌሎች በላይ ላድርግ ባለ
ስራችሁን ወጥራችሁ ታትራችሁ ስሩ ባለ ከዘመናቸው ብዙ ለራቀ ሃሳቡ ቀና መሆን ያቃታቸው እግራቸውን አጣምረው የሚውሉ ስራፈቶች ሁሉ ምቀኛ ሆነው
ተነሱበት እና ብርሃን ሆኗቸው ሳለ አቅልጠው ጨረሱት። ከውጪም ከእንግሊዝ ጋር የነበረው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በመቋረጡ ጦርነት መቅደላ ድረስ መጥቶ በመጨረሻ የምወደው ንጉስ የልጅነት ምናብ ጀግናዬ በክብር ወደቀ። እጄን አልሰጥም ብሎ በጀግንነት ሲዋደቅልን እኔና የሃገሬውን ሰው እርሱ ሞት ተጎንጭቶ እኛን በክብር አኖረን ።

{ የዘላለም አይደለም ወይ ፤የሰጠኝ ደስታ ከላይ }

ከጀግንነቱ ፣ ለኢትዮጵያ ካለው ፅኑ ፍቅሩ ባሻገር ዛሬ 202 ኛ አመቱ ሲከበር አንዴ ቀና ቢል ልነግረው ከምፈልጋቸው ነገሮች መካከል አንዱ " ልጅነቴን ውብ ስላደረክልኝ አመሰግናለሁ" ነው ።

{ እንደ መልከፀዴቅ ካህን ፣ ክህነቱ ከዘመን ዘመን }

ብዙ አመታት አልፈው ብዙ ነገስታት ተፈራርቀው ዛሬም እስከ ህልሞቹ እስከ አወዛጋቢነቱ እስከ ጀግንነቱ እስከ ሃዘኖቹ እጅግ የምናከብረው እና የምንወደው ንጉስ አፄ ቴዎድሮስ

@wegoch
@wegoch
@paappii

#elsa mulugeta
⛺️Camping Trip to #Ankober with #Sunsethiking!

📅camping Date :- Jan 23 - 24, 2021(tir 15 - 16, 2013)

🛫Departure:- - Piassa Tayitu Hotel

Departure Time - 2:00Am Local time 🚩

💵 contribution per person:- 1350 💰

🎉🎊Package 🎋🎊

🔵🚍 - Transportation
🔴⛺️- Tent, campfire &tea
⚫️🍝 - Traditional Roasted meat ( 🐏), Lunch and snaks🍟🍤
⚪️ Bottled water
🔵 Park entrance with Guide
🔴photograph 📷

NB.
🚫 Sanitizer & facemask mandatory!


for more join the
🔸channel @sunsethiking🍁
🔻📷 @sunsetphotography🍁

🎫 tickets available at
@Paappii ( +251922303747 )
ያለፈ ህይወትዋን ያየሁባት ይመስላል በሐፍረት አየችኝ። በዝግታ ንግግሯን
ቀጠለች፡- የህይወት ጣፋጭነትን ሳያዉቁ የሚሞቱ ሰዎች የሴትን ልጅ ስቃይ አይረዱትም። በተለየ በፈጣሪ ፍቃድ ነብሷን ለአንድ ሰዉ ሰጥታ በምድራዊ ህግጋት አስገዳጅነት ደግሞ ስጋዋን ለሌላ ወንድ የሰጠች ሴት ስቃይ አያዉቁትም። ይህ ስቃይ በሴቷ ደም እና እንባ ስለሚፃፍ ወንድ ሊያነበዉ አይችልም። ቢያነበዉም አይገባዉም። ቢገባዉም እንኳን በህመሟከመሳለቅ የተለየ ምላሽ አይኖረዉም። ይህ ማለቂያ አልባ የስቃይ ድራማ የሴት ልጅ ድክመት እና የወንድልጅ ብርታት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ የቀጠለ ነዉ። ብርቱዎች ደካሞችን በባርነት መያዝ እስኪያቆሙ ድረስ መቀጠሉ አይቀርም።በጨካኙ የሰዉ ልጅ ህግ እና በንፁሑ አፍቃሪ ልብ መካከል የሚደረግ ጦርነት ነዉ። ትናንት በዚያ የፍልሚያ ሜዳ ወድቄ ነበር ። ሆኖም ግን ብርታቴን አሰባስቤ የታሰርኩበትን ሰንሰለት በጠስኩት። ክንፎቼን ነፃ አዉጥቼ በከፍታ ወደሚገኝ ሰላም ና ፍቅር በረርኩኝ።


@wegoch
@wegoch
@paappii

#Madam Rose Hanie
ከዙኪ ገፅ ላይ የተወሰደ
አሜሪካን አገር ውስጥ ነው አሉ። ሰውዬው 7 ቢሊየን የአሜሪካን ዶላር ሎተሪ ይደርሰውና እንደደረሰው ሲነገረው በድንጋጤ እንዳይሞት በማሰብ ቤተሰቦቹ ሳይካትሪስት ቀጥረው እውነታውን ያለ ምንም ጉዳት እንዲቀበል ቅድመ ዝግጅት ያደርጋሉ። ሳይካትሪስቱ እንዴት ማሳመን እንዳለበት እቅድ አውጥቶ ሥራውን ይጀምርና ከሰውዬው ጋር በመነጋገር ተግባብተው በትንሽ ቀናት ውስጥ ጓደኛ መሆን ቻሉ። አንድ ቀን በጨዋታ መሀል ሳይካትሪስቱ ሰውየውን "7 ቢሊየን ዶላር ሎተሪ
ቢደርስህ ምን ታደርገዋለህ" ብሎ ጠየቀው። ሰውየው ቀለል አድርጎ ይመልሳል" 1 ቢሊየን ዶላር ላንተ ለወዳጄ እሰጥሃለው።" ሳይካትሪስቱ የሰውየውን ንግግር እንደሰማ ህይወቱ አለፈች።
…………
ከማሳመናችን በፊት እንመን
ከማዘጋጀታችን በፊት እንዘጋጅ
ከመምከራችን በፊት እንመከር።

@wegoch
@wegoch
@paappii
#Ab Bella 🖤
አሜን


የዘንድሮ ልጅ ግን በየትኛዋ ፀሀይ ነው ገላውን ታጥቦ የሚሞቀው? መቼም ዘንድሮ የተወለደ ልጅ በዚች ፀሀይ ሞቆ እንዴትም ፈረንጅ ቢመስል እንኳን አንድ ወር ሳይሞላው ያረረ ብረት ምጣድ እንደሚመስል አልጠራጠርም። አቤት ፀሀይ!!
ከቤት ወጥቼ የቀጠሮ ቦታዬ እስክደርስ ድረስ ከዛሬ ሁለት አመት በፊት የማሞካሻትን ፀሀይ፤ የማቆለማምጣትን ፀሀይ ፤ ለ'ናቴ ቁንጅና ተምሳሌት አረጋት የነበረችውን ፀሀይ እየረገምኳት፤ ፈጣሪዬንም ፀሀይን በመፍጠሩ እያማረርኩት የቀጠሮ ቦታዬ ደረስኩ። የሄድኩበት ቀጠሮ በጥቂት ደቂቃ ውስጥ አልቆ ያቋረጥኩትን ምሬት እየቀጠልኩ ፤ እንደ ፍሪጅ የሚቀዘቅዘውን ቤቴን ባይነ ህሊናዬ እየሳልኩ የቤቴን አቅጣጫ ተያያዝኩት።
መንገዴን በደመነፍስ እየተጓዝኩ ሳለ ድንገት አንድ ድምፅ አባነነኝ። "አባት" የሚል ድምፅ ሰምቻለው ነገር ግን አልዞርኩም። ብዙ ጊዜ ሰው የጠራኝ መስሎኝ እየዞሩኩ ብዙ ጊዜ የማርያም ብቅል እየፈጨው ነው ብዬ ተመልሻለው። በድጋሚ ሲጠራኝ ግን አንድ በጣም የማውቀው ሰው የጠራኝ ያህል ተሰማኝ። ፊቴን ሳላዞር እንባ ይተናነቀኝ ጀመር። በለሆሳስ አንገቴን አዞርኩኝ። አይኔ በፍጥነት ይርገበገባል ምክንያቱም አንድ ሰከንድ አይኔ መርገብገቡን ካቆመ እንባዬ ማቆሚያ አይኖረውም።
ያ የድምፁ ግርማ ሞገስ ሲቆጣ አይደለም ሲመክር ያስፈራ የነበረው፤ ያ ከትህትናው ብዛት 'አቤት ልጆቹ ታድለው በሁለት እናት ነውኮ ሚኖሩት ' እስከሚባል ድረስ ለሰው አዛኝ የነበረ ሰው፤ 'እንደሱ ልፋት እንደሱ ስራ ይሄም ሲያንስበት' እየተባለ በየሄደበት የሚሸለመው ሰው፤ ዛሬ በአንድ ቅፅበት ሁሉ ነገሩን ያጣ የሚመስል አንድ ሰው ፊት ለፊቴ ቆሟል። ከራስ ፀጉሩ እስከ እግር ጥፍሩ አየውት እየገላመጥኩት አልነበረም የማየው ነገር ገርሞኝ እንጂ።ፊቱ አልቀረ ፤ ቅንድቡ አልቀረ ፤ ያ'ይኖቹ ሽፋሽፍት እንኳን ሳይቀሩ መላ ሰውነቱ አቧራ የሸፈነው ከአለም ሁሉ ምስኪኑ ሰው ፊት ለፊቴ ቆሟል። "አባቴ ቡና ግዛልኝ?" አለኝ። ገንዘብ ምን ያህል ቀፋፊ እንደሆነ ተሰማኝ። የገንዘብ እጦት ለ አምስት ብር ቡና ሲባል ከታላቁ ክብር አንስቶ መሬት ይፈጠፍጣል። በአንድ ሰሞን ሰው ሁሉ ቡና ካልጋበዝኩክ እያለ ያስለመደውን ሱስ ለማስታገስ እኔን አባት እራሱን ንፋስ አንደፈለገ እንደሚያደርገው ፌስታል ቆጠረ። አንዲት ቃል ሳልተነፍስ እንባዬ ሲወርድ ታወቀኝ ።እንባዬ ጉንጬ ጋር እንደደረሰ ወዲያው በጆቼ ጠራርጌ " ና እንሂድ እገዛልሀለው " አልኩት። አይን አይኑን ማየት ስለፈለኩ ብሩን አልሰጠውትም። "እግዛቤር ይስጥልኝ" አለኝ አንገቱን እንዳቀረቀረ። ቡናውን ገና ሳልገዛለት እንደ ንጉስ አከበረኝ። ወደ ቡና መሸጫው እየሄድን እንኳን ካጠገቤ ሆኖ ሊራመድ አልደፈረም። እኔን እንደ አለቃ ፊት ፊት እየመራኝ እርሱ ግን እንደ ገረድ ከኋላዬ ይከተለኝ ነበር። ቡና ምታፈላዋ ጋር እንደደረስን " ቡና ቡና" አላት። የጠማው ቡና ሳይሆን ውሀ ነበር የሚመስለው።" ውይ ቀዝቅዟል ባይሆን ከቸኮልክ ሞቅ ላድርግልህ?" አለች "አይ ዝም ብለሽ ቅጂልኝ" ምን ያህል እየተንገበገበ እንደሆነ እያየች በድጋሚ "ቀዝቅዟል እኮ ነው ያልኩህ" አለችው። ዞር ብዬ አየት አረኩት አይኑ ይርገበገባል ፤ ሊያለቅስ ይሁን ሊመታት አልገባኝም። ገና አይኑን እንዳየች ሮጣ መታ ሲኒውን ጠረጴዛው ላይ ሳታስቀምጥ ቀዳችለት። እሱም ከ'ጇ ላይ ተቀብሎ(ቀምቶ) በአንድ ትንፋሽ ጭልጥ አረገው። የሲኒው ከንፈር ከከንፈሩ ሲላቀቅ ሰውነቱ አንዳች ነገር እንዳገኘ ይፈካ ጀመር። አጠገቡ መሆኔን ሲያውቅ ያ የማይቋረጥ ምስጋናውን ቀጠለ "አጊኝቶ ቀማጣት እመብርሀን ትሰውርህ ፣ የሰውን እጅ አያሳይህ ፤ አብልቶ ከመነከስ ይሰውርህ " አለኝ። ሂወቱን እየነገረኝ እንደሆነ ተሰማኝ። እንባዬም ከምርቃቶቹ እኩል ይፈስ ጀመር። ለመጀመሪያ ጊዜ ከልቤ ይህን ቃል አወጣውት
""""""'አሜን"""""""

የጌትነት ልጅ ፃፈ
@wegoch
@wegoch
@Mahletzerihun
2024/09/23 21:31:03
Back to Top
HTML Embed Code: