Telegram Web Link
በአንድ አፍታ በእጄ የያዘኝን እጁን አጥብቄ ስይዘው እና ዓይኖቼ የበለዘ አይኑን ሲያዩ እኩል ሆነ... አጥብቄ ያያዝኩት እጄ ህመም እንደሰጠው ፊቱ ላይ ስቃዩ ታየ:: እያየሁት እንደሆነ ሲያስተውል ህመሙን ለመዋጥ ታገለ:: እጁን ስቤ አየሁት:: እንደማበጥም እንደመቁሰልም ብሏል::

"አምላክ ሆይ!! ምን ሆነህ ነው?" ብዬ ጮህኩ:: እሱ ከአፉ ቃል ሳይወጣ የሆነው ነገር ከእኔ ጋር የተያያዘ እንደሆነ ገባኝ::

"ምንም አልሆንኩ! እንዲያው ዝም ብሎ ነገር ነው!" ይለኛል ደጋግሜም ብጠይቀው:: ቅስስስ ብዬ ተነስቼ እየተቀመጥኩ አገጬን በእጆቼ ወደራሴ እያዞርኩ ፊቱን አየሁት....

"እሺ የተፈጠረውን አትንገረኝ!! ተጎድተሃል?? ሌላ ቦታ ተመትተሃል?"

"ምንም አይደልኮ ትንሽ ነገር ነው!" ይበለኝ እንጂ ትልቅ ነገር እንደሆነ ሆዴ ነግሮኛል:: የዛን ቀን ከሰዓታት በኃላ ያላሰብኩት እንግዳ ጎበኘኝ..... ማንነቱ የገባኝ ከደቂቃዎች በኃላ ነው:: ... የዛን ምሽት ከደበደቡኝ ውስጥ አንዱ ነው:: ..... ጎንጥ አጠገቤ ቆሞ እንኳን ፍርሃት ልቤን ከደረቴ ጎትቶ ሊያስወጣት ታገለኝ:: ... ሳይታወቀኝ አይኔን ከድኜ እግሬን ሰብስቤ ጉልበቴን አቅፌ ጥቅልል አልኩ:: ....


        .......... ይቀጥላል........

@wegoch
@wegoch
@paappii
ፓብሎ ኢስኮባር- ቱጃሩ የናርኮቲክ ወንጀለኛ
----
ጸሐፊ: አፈንዲ ሙተቂ
----
ፓብሎ ኢስኮባር ማለት በአንድ ዘመን በCIA በጥብቅ ሲፈለግ የነበረ ቱጃር ነው። በዜግነቱ ኮሎምቢያዊ ነበር። ይህ ሰው በዓለም ታሪክ የሚታወቀው ትልቁ የአደንዛዥ እጽ አምራችና አከፋፋይ ድርጅት የሆነው Medellin Cartel መስራችና ባለቤት በመሆኑ ነው። በዚህ ድርጅት አማካኝነት በየወሩ እስከ ሰማኒያ ቶን የሚደርስ የኮኬን እጽ ወደ አሜሪካ ያስገባ ነበር። ይህ መጠን በሂደት እየጨመረ ሄዶ በ1980ዎቹ መጨረሻ ላይ ድርጅቱ በየቀኑ 15 ቶን ኮኬን ወደ አሜሪካ መላክ ጀምሯል።

ታዲያ ይህ ትልቅ መጠን ያለው እጽ ወደ አሜሪካ ይገባ የነበረው እጅግ በተደራጀ የኮንትሮባንድ መስመር እና የትራንስፖርት ቻናል ነው። ኢስኮባር ከዚህ ንግድ እጅግ ብዙ ሀብት መሰብሰብ ችሏል። ድርጅቱም በዓለም ዙሪያ ከሚመረተውና ከሚሸጠው ኮኬይን የሰማኒያ በመቶ ድርሻ ነበረው።

ኢስኮባር የተሰማራበት የኮኬን ኤክስፖርት በዓለም ታሪክ እጅግ ሀብታሙ ወንጀለኛ እንዲሆን አስችሎታል። ኢስኮባር በ1993 በተገደለበት ወቅት የተጣራ ሀብቱ ከሰላሳ ቢሊዮን ዶላር በላይ ደርሶ ነበር።
----
ኢስኮባር ንግዱን ሲያካሄድ መንገዱ አልጋ በአልጋ አልነበረም። ከእርሱ ጋር ከሚወዳደሩ የኮኬን ነጋዴዎች፣ ከፖሊሶች፣ ከወንጀል መርማሪዎችና ከድንበር ጠባቂዎች ጋር ብዙ ህይወት የጠፋበት ውጊያ ውስጥ ገብቷል። በዚህም የተነሳ በሀገሩ በኮሎምቢያ እና በአሜሪካ መንግሥት በጥብቅ ይፈለግ ነበር። የአሜሪካው CIA ሊገድለው ብዙ ሙከራ አድርጓል።

ኢስኮባር በ1991 ከኮሎምቢያ መንግሥት ጋር የገባበትን ውዝግብ ለመፍታት ሲል ድርድር ጀመረ። በድርድሩም "ለአሜሪካ መንግሥት አሳልፋችሁ ካልሰጣችሁኝና ራሴ በሰራሁት እስር ቤት እንድታሰር ከፈቀዳችሁልኝ እጄን እሰጣለሁ" በማለት አስታወቀ። የኮሎምቢያ መንግሥትም በዚህ ተስማምቶ ለፍርድ አቀረበው። ፍርድ ቤቱም የአምስት አመት እስራት ፈረደበት። ኢስኮባርም La Chatedral ብሎ በሰየመው የግል እስር ቤቱ የወህኒ ጊዜውን ጀመረ።

ከአንድ ዓመት በኋላ የኮሎምቢያ መንግሥት ወደ መደበኛ እስር ቤት ሊወስደው ሲሞክር ግን ኢስኮባር ሊያስሩት የመጡትን ፖሊሶች ገድሎ አመለጠ። የኮሎምቢያ መንግሥት እና የአሜሪካው CIA በቅንጅት ያሳድዱት ጀመር። ከአስራ ስድስት ወራት ፍለጋ በኋላም ለብዙ ዓመታት በነገሰባት የሜዴሊን ከተማ በተደበቀበት አንድ አነስተኛ ፎቅ ቤት ውስጥ ተገደለ።
----
ፓብሎ ኢስኮባር የ'"ናርኮ-ቴሬሪስት" ወንጀለኛ ተብሎ በብዙ የዓለም ሀገራት መፈረጁ እውነት ነው። ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ ግን ሰውዬው በሁለት ነገሮች ዘወትር ይታወሳል።

የመጀመሪያው ፓብሎ ኢስኮባር በቤቱ ውስጥ የኖረበት ምቾት በብዙ ሀገራት ቤተ መንግሥታት እንኳ የሌለ መሆኑ ነው። ኢስኮባር በሰፊው ግቢ ውስጥ ከገነባቸው ታላላቅ ቪላዎች በተጨማሪ በርካታ እንስሳት ያሉት የግሉ Zoo ነበረው። በተለይም በግቢው ውስጥ ብዙ ጉማሬዎች ያሉት መለስተኛ ሐይቅ ይገኝ ነበር።

በሌላ በኩል ፓብሎ ኢስኮባር በከተማዋ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ድሆችን ሕይወት ለመቀየር የSocial Service ፕሮጀክት መዘርጋቱ ተመዝግቧል። በዚህ ፕሮጀክት አማካኝነትም ለብዙ ድሆች የመኖሪያ ቤቶችን አሰርቷል። ልጆቻቸው የሚማሩበትንም ትምህርት ቤት ከፍቶላቸዋል። በዚህም የተነሳ በ1982 የከተማዋ ህዝብ የፓርላማ አባል እንዲሆን መርጦት ነበር። ከከተማዋ ድሆች መካከል አንዳንዶቹ እስከ ዛሬ ድረስ "ፓብሎ ቅዱስ ሰው ነበር" ይሉታል።

ከዚህ በተጨማሪም ፓብሎ ኢስኮባር Atheltico Nacional የተሰኘውን የሜድሊን ከተማ ታዋቂ የእግር ኳስ ቡድን በገንዘቡ ይደግፍ ነበር። ይህ ቡድን በ1989 የላቲን አሜሪካ ክለቦች ዋንጫ (Copa Libertadors) አሸናፊ ለመሆን የበቃ ነው።
-----
አፈንዲ ሙተቂ
ጥቅምት 13/2013 ተጻፈ።

@wegoch
@wegoch
@paappii
#የመኖር አካፋይ ፣ የመ ፤ ሞ ፣ ት ሲሶ ፣ መንገድ መሃል ………… (ክፍል ዘጠኝ)
(ሜሪ ፈለቀ)

ፍርሃት ልቤን ከደረቴ ጎትቶ ሊያስወጣት ታገለኝ። ሳይታወቀኝ ዓይኔን ከድኜ እግሬን ሰብስቤ ጉልበቴን አቅፌ ጥቅልል አልኩ። ጎንጥ በፊት ለፊቴ መጥቶ ጉልበቴን ያቀፍኩበትን እጄን አምባር ማሰሪያው ጋር ያዝ ሲያደርገኝ ዘለልኩ። ሰውነቴ በሙሉ እየተንቀጠቀጠ ነበር። በሌላኛው እጁ ጀርባዬን እንደልጅ አሸት አሸት አደረገኝ እና ወደጆሮዬ ጠጋ ብሎ

«እትይ ይቅርታ ሊጠይቆት ነው የመጣው! እኔ እዚህ ቆሜ ማን አባቱ ምን ያደርገኛል ብለው ነው የሚፈሩት?» ያለኝ መርበትበቴ አናቴ ላይ ወጥቶ የሰማሁት የቅዠት ድምፅ ይሁን ወይም ያለው ነገር ከነጭራሹ የገባኝ ይሁን እንጃ ብቻ የተናገረበት ድምፅ እና ጀርባዬን ከላይ ወደታች እያሸ የሚያባብለኝ እጁ አላውቅም በአፌ ልትወጣ ጉሮሮዬጋ እየደረሰች የምትመለስ ልቤን በቀስታ ወደቦታዋ መለሳት። በቀስታ ዓይኔን ገልጬ ሰውነቴን ዘና ለማድረግ እየሞከርኩ እየሆነ ያለውን ማጤን ጀመርኩ። እንግዳው ሰው በእኔ አልጋ እና በበሩ መሃል ያለ ቦታ ላይ ቆሞ አንዴ እኔን አንዴ ጎንጥን ያያል። ይሄኔ ነው ከደበደቡኝ ሰዎች መሃል አንዱ መሆኑ የገባኝ እንጂ የዛን እለት ምሽት ፊታቸውን በስርዓት የማይበት እድል ስላልነበረኝ ላውቀው አልችልም ነበር። አይቼው የነበረ ቢሆንም እንኳን በዛሬው ሁናቴው ላስታውሰው አልችልም ነበር። ፍርሃቴ ትንሽ ገለል ሲልልኝ ፊቱ ‘ንፋሱ ተንፍሶ ህፃናት እየተቀባበሉ የተጫወቱበት ኳስ’ መስሎ መጨረማመቱን አየሁ። ግንባሩ ላይ ሁለት ትንንሽዬ ፕላስተር ተለጥፎበታል። ጎንጥን አየሁት። በዓይኑ ሰውየውን ወደ እኔ እንዲጠጋ አሳየው። በዓይኑ ገፈተረው ብል ይቀለኛል። ወደ እኔ እየተራመደ ሲጠጋ እያነከሰ መሆንኑን አስተዋልኩ።

«ይቅርታ!» አለኝ አጠገቤ ደርሶ መሬት መሬቱን እያየ። ጎንጥ የሆነ መልእክት በማስተላለፍ አይነት ጉሮሮውን ጠረገ።

«ይቅርታ አድርጊልኝ! አንቺ ላይ እጃችንን ማንሳት አልነበረብንም! በእኔም በጓደኛዬም ስም ይቅርታ እንድታደርጊልን ልለምንሽ ነው የመጣሁት!» ብሎ እሱም የሆነ መልእክት እንደማስተላለፍ ጎንጥን አየው። ጎንጥ ጭንቅላቱን በአወንታ ነገር ነቀነቀ።

«እሺ» ከማለት ውጪ ግራ የገባው ጭንቅላቴ መልስ አላቀበለኝም። እንደአመጣጡ ፊቱን አዙሮ እግሩን እየጎተተ ሲወጣ ጭንቅላቴ ያልተዘጋጀበትን ጥያቄ አፌ ጠየቀ

«ለምን? ለምንድንነበር ግን እንደዛ ያደረጋችሁት?» አልኩኝ። መለስ ብሎ እኔን ሳይሆን ጎንጥን አየው። እኔም ወደእሱ ዞርኩ።

«የተጠየቅከውን መልስ!» አለው እንደትእዛዝ

«እህቴን …… ፍሪታን ስለቀማሽኝ። ተናድጄ ነበር። በፀባይ ላናግርሽ ስራሽ ቦታ ድረስ ብመጣም አላገጥሽብኝ። እኔ አቅሜ ጉልበቴ ብቻ ነው። አንቺ የገንዘብ አቅም አለሽ ፣ በአንድ ፉጨት ያልሽውን የሚፈጽሙልሽ ቁልፍ ሰዎች አሉሽ፣ ፖሊሶቹ በእጅሽ ናቸው፣  በዛ ላይ ጉልበትም መሳሪያም አለሽ! ........ በእህቴ ገላ አንቺ ገንዘብሽን ስታካብቺ አንጀቴ እየተቃጠለ ዝም ከማለት ውጪ ምንም ማድረግ አልቻልኩም ነበር። ባለፈው ሳምንት አደጋ ደርሶብሽ ምንም እንደማታስታውሺ ስሰማ ደስ አለኝ። (ቀና ብሎ ጎንጥን አይቶ ቀጠለ) እየተከታተልኩሽ ነበር። » ብሎኝ ትከሻውን ሰበቀ። ምንም እንደማላስታውስ ካወቀ የነገረኝ ነገር እንደማይገባኝ እንዴት ጠፋው? ቀና ብዬ የአልጋውን ራስጌ ተደግፌ ተቀመጥኩ። ከምን ጀምሬ ምን እንደምጠይቀው ግራ ገባኝ። ከነአካቴው መጠየቁ ራሱ ልክ ይሆን አላውቅም! የተናገረው ነገር ውስጥ ምንም ለልክ የቀረበ ድርጊት መች አለ? አሰላስዬ ሳልወስን አፌ ቀደመኝ።

« እህትህን? ምን አድርጌ ነው የነጠቅኩህ? በእህቴ ገላ ያልከኝ እህትህ ምንድነው የምትሰራው? እንዴት ነው እኔ በእህትህ ….. (እሱ ያለውን መድገም ዘገነነኝ) እየተከታተልከኝ ከነበር ምንም እንደማላስታውስ የሰማኸው እውነት መሆኑን ማረጋገጥ አይከብድህም መቼም? » አልኩኝ ፍርሃቴ ድምጥማጡ ጠፍቶ። እሱ አሁንም በማስፈቀድ አይነት ጎንጥን አየው። በቁመት ከጎንጥ ጋር ተቀራራቢ ናቸው። ጎንጥም ግዙፍ ዓይነት ወንድ ቢሆንም ደብዳቢዬ ግን የበለጠ ጡንቻው የተወጣጠረ እና ደረቱ የተነፋፋ ነገር ነው። እጅ በእጅ ቢያያዙ ማንም ሰው የሚያሲዘው በደብዳቢዬ ጡንቻ ነው። ታዲያ ጎንጥ ምን ቢያደርገው ወይስ ምንስ ቢለው ነው ይሄን የሚያክል ሰውዬ እንዲህ የሚንበጨበጨው? የተነፈሰ ባሎኒ ኳስ ካስመሰለው በኋላ እንኳን እዚህ ድረስ መጥቶ ይቅርታ እንዲጠይቀኝ ያስደረገው ያልገባኝ ነገር ምን ተከውኖ ነው?

«እናንተ ቤት ስትሪፐር ናት! (እንደማፈርም እንደማዘንም የቀላቀለው ስሜት ድምጹን ወሮታል። ያለኝ ነገር እንዳልገባኝ ሲያውቅ አሁንም ጎንጥን ዞሮ አየው። ጎንጥ በአይኑ <ቀጥል> እንደማለት ነዳው።) አንድ እህቴ ናት ያውም ታናሼ! ልጠብቃት ይገባ ነበር። ማታ ማታ ሆቴል ውስጥ ሪሴፕሽንነት ስራ አገኘሁ ስትለኝ እንኳን <አይሆንም አንቺ አርፈሽ ተማሪ። እኔ አኖርሻለሁ> ብያት ነበር። እንቢ ብላ ስራውን መጀመሯን ነገረችኝ። የምትሰራበትን ቦታ ልትነግረኝ አለመፈለጓ ስለከነከነኝ የሆነ ቀን ተከተልኳት እና እናንተ ክለብ ደረስኩ። (ለሰከንዶች ዝም አለ። የሆነ የሚቀጥለውን ለመናገር ጉልበት እንደሚሰበስብ ያለ ዝምታ) በአይኔ እንኳን ጫን ብዬ ላያት የምሳሳላት እህቴ ስራዋ እቤታችሁ ለሚመጡ ነውረኛ ባለስልጣናት እና ባለሃብቶች እርቃኗን እየደነሰች ማስደሰት መሆኑን አየሁ።» ብሎ ሆነ ብሎ ይመስለኛል ፊቴ ላይ አተኮረ። መደበቅ ያልቻልኩት ድንጋጤ እና መደናገር ፊቴ ላይ ተተረማመሰ። እሰራ የነበረው ስራ ፅድቅ ያለበት አለመሆኑን ምንም በማያስታውስ ወና ጭንቅላቴ እንኳን መገመት ከባድ አልነበረም። ሴትን ልጅ ራቁት እያስጨፈሩ ገንዘብ ማግኘት ግን ሌላ ደረጃ ብልግና መሰለኝ። ከዳዊት ጋር ቀን የሄድኩኝ እለት ያየሁት …… ቤቱ ውስጥ የነበሩት የተለያዩ ክፍሎች…….. ክፍሎቹ ውስጥ የነበሩት ሶፋው መሃል የተንጣለሉት አልጋ የመሰሉ መሃከላቸው ላይ የቆመ ብረት ያለባቸው ሰፊ ክብ መድረኮች ……. መድረክ ነገሩ ላይ አለመልበስ ለብሳ እንቅልፍ ወስዷት የነበረችው በጡት ማስያዣ እና በፓንት የነበረችው ቆንጅዬ ልጅ ……. አንድ በአንድ ከነገረኝ ጋር ላዛምድ ሞከርኩ። ልጅቷ ስታየኝ እየተደነባበረች  «አሁኑኑ ተጣጥቤ ፏ እላለሁ! ይቅርታ»  ብላኝ የነበረው ይሄን ልትሰራ ነበር? እሷው ልጅ ትሆን እንዴ እህቱ?

ጭንቅላቴ ውስጥ የሚተረማመሱትን ጥያቄዎች ሁሉ መጠየቅ ቢያምረኝም የሰውየው ሁኔታ ለመጠየቅ የሚጋብዝ አይደለም። ተገድዶ ቆመ እንጂ በጣም እንደሚጠላኝ ያስታውቃል።

«አሁን ላይ ሆኜ ……ምን አድርጌ እንደነበር ወይም ለምን እንዳደረግኩ የማውቀው ነገር የለም። ምንም ይሁን ብቻ እህትህንም አንተንም ስለበደልኳችሁ ነገር በጣም ይቅርታ! ባለፈው ህይወቴ በጣም ክፉ፣ እግዜአብሄርን የማልፈራ ጨካኝ ፣ ሀጢያትንም ወንጀልንም የምደፍር ሴት እንደነበርኩ ቀስ በቀስ እያወቅኩ ነው። የእኔ ዛሬ ሌላ ሴት መሆን ወይም ምንም አለማስታወስ የደረሰብህን በደል እንደማይሽረው አውቃለሁ። በቃ ግን በጣም ይቅርታ አድርግልኝ ከማለት ውጪ ማድረግ የምችለው የለም።» አልኩት ከልቤ። ምንም እንዳልተዋጠለት ያስታውቃል። <አሁንስ መሄድ እችላለሁ?> በሚል አስተያየት ጎንጥን አየው። የጎንጥን ፈቃድ በምልክት ሲያገኝ ወጥቶ ሄደ።
በትክክልም ክፉ ሴት ነበርኩ ማለት ነው። የሚያዩኝ ሰዎች ዓይን ውስጥ ለሞላው ጥላቻ እና ፍርሃት ምክንያት ከክፉነቴ ውጪ ሌላ ሰበብ የለም። ባለፉት ቀናት ሁሉ የምሰማውን ድርጊቴን ምክንያት እያጋባሁ <እንዲህ ስለሆነ ሊሆን ይችላል ይሄን ያደረግኩት> እያልኩ ድርጊቴን በሰበብ እየደገፍኩ ራሴን ይቅር ለማለት ፣ ያለፍኩትን ጥፋት ለመካስ፣ በንሰሃ ተመልሼ የበደልኳቸውን በመልካም ስራ ልዋጅ ……… አውጠንጥኜ ነበር። የትኛውን ሀጢያቴን ከምን ጀምሬ ነው ይቅር የምለው? ማን ያውቃል ከዚህ የባሰም ፀያፍ ነገር ሰርቼ ይሆናል።

«ጎንጥ?» አልኩት ሰውየው ከወጣም በኋላ እዛው በቆመበት የነበረውን ጎንጥን

«አቤት እትይ?»

«ህገ-ወጥ አይደለም በሴቶች መነገድ? ያለው በሙሉ እውነቱን ይመስልሃል? መቼም ህግ መንግስት ባለበት ሃገር እንዲህ አይነት ነገር ስሰራ አንድ እንኳን ለህግ የሚያቀርበኝ ሰው ጠፍቶ ነው? ወይስ ህገ-ወጥ አይደለም?»

«አላውቅም እትይ! ስለነገርየውም ሰምቼ አላውቅ!»

«ነውረኛ ሴት ነበርኩ አይደል? አንተም አውቀህ እየደበቅከኝ እንጂ ብዙ የሰማኸው እና የምታውቀው ነውር አለኝ አይደል? ንገረኝ እስኪ ምን ዓይነት ሴት እንደነበርኩ እያወቅክ አሁንም ድረስ ለምን ትጠብቀኛለህ? ለአንተም ለተናኜም ቢሆን ክፉ ሴት እንደነበርኩ ግልፅ ነው። እንዴት ነው በደሌን ረስታችሁ ከጎኔ የቆማችሁት? እስኪ ንገረኝ አንተንስ ምን ቀምቼህ ይሆን? »

«እትይ ደክሞዎታል ትንሽ ይረፉ ግድ የለም!»

«አንቱ አትበለኝ ማለት አይሰማህም?» በማን እንደተናደድኩ አላውቅም ግን እየተቆጣሁ ነው።

«ይሁን! ይሰማኛል! አንቺ እሎታለሁ። ግን እንደው እትይ በማያስታውሱት ነገር መብሰክሰኩ ምንም ፋይዳ የለውኮ! …….»

«አንቱ አትበለኝ! አንቱ የሚባለው የሚከበር ሰው ነው። አንቱ የሚባለው ክብርን ለመግለፅ ነው። ለየትኛው ክብሬ ነው አንቱ የምትለኝ?» አሁንም እየተቆጣሁ እና እየጮህኩ ነው። እየተቆጣሁ ያለሁበት ምክንያትም እየተቆጣሁ ያለሁትም ሰው የቁጣዬ መንስኤ አለመሆናቸውን ባውቅም ልቆጣጠረው ግን አልቻልኩም። አልጋው ጫፍ ላይ በአንድ ጎኑ ተቀምጦ በግንባሩ እያየኝ እኔ ከምናገርበት ድምፅ በተቃራኒ በእርጋታ እና በለሆሳስ

«እትይ ማንም የነበሩ ቢሆን አለቃዬ ነበሩ! ኖትም! አለቃን አንቱ ማለት ያደግኩ የጎለመስኩበት ስርዓት ነው። ተው ካሉኝ ካስከፋዎት እተዋለሁ። ግን ከበሬታዬን  የተውኩ እንዳይመስልብኝ!»

«አዎ ተው!» አልኩኝ ስናገር በነበረበት ቁጣ

«እሺ እተዋለሁ!» አባባሉ የተረጋጋ ነገር ....... የተከፋ ሳይሆን ለእኔ ያዘነ ዓይነት ነው። ለምን እሱ ላይ እየተናደድኩ እንዳለሁ አላውቅም። የሚያውቀውን ሁሉ አልነገረኝም ብዬ ስላመንኩ? ጭርሱኑ አብልጦ ሊጠላኝ ሲገባ አብልጦ ስለተንከባከበኝ? ወይስ የክፋቴን ልኬት በሱ ጥላቻ ልክ መመዘን ፈልጌ? ከሁሉ ከሁሉ ሚዛኔ እሱ እንዲሆን ለምን ፈለግኩስ?  ለደቂቃ ዝም ማለቴን ተከትሎ እንደቅድሙ ጀርባዬን በቀስታ ወደላይ እና ወደታች ማሸት ጀመረ። ውስጤ እየጎፈላ የነበረ ንዴቴ እየበረደ በምትኩ ሀዘን እና ተስፋ መቁረጥ ተተካ። የፈለግኩት ማልቀስ ነበር።

« እንዴት አገኘሃቸው? ፖሊስ እንኳን ፈልጎ ያላገኛቸውን አንተ እንዴት አገኘሃቸው?» አልኩት ድንገት

«ፖሊስ አልፈለጋቸውም። ያልተፈለገ ወንጀለኛ እንዴት ይገኛል? መድሃንያለም ብቻ በሚያውቀው ምክንያት ፖሊሶቹ ይሄን ጉዳይ መንካት አልፈለጉም። እንደው እትይ ልቤ ሲነግረኝ የተኮሰቦትንም ሰው መፈለጉን እርም ብለው ትተውታል።»

«እነሱ እንዴት አላገኟቸውም አይደለም ያልኩህ አንተ እንዴት አገኘሃቸው ነው ያልኩት። ደግሞ አሁንም አንቱ ማለትህን ተው!» አልኩት በደከመው ለዛ

«መንገዱ ምን ያደርጋል እትይ? ዋናው መዳረሻውም አይደል? እንዴት እንዳገኘሁት ዝርዝሩ ምን ይፈይዳል? ዋናው መገኘቱም አይደል?»

«ለእኔ ዝርዝሩ ይረባኛል! ማወቅ እፈልጋለሁ። አውቀህ ነው የምትጠመው?» አልኩት መልሼ እየተቆጣሁ።

«ካሉ መልካም ….. ይቅር ይበሉኝ  ካልሽ ይሁን! የሰው ፊት አየሁ!» ብሎኝ ይቀጥላል ብዬ ስጠብቅ ልክ የጠየቅኩትን የመለሰ ይመስል ዝም አለ።

«ምን ማለት ነው?»
«እንዴት አገኘኻቸው? አይደልም ጥያቄ …. ዎ …ሽ ? <የሰው ፊት አይቼ!> ነው መልሱ! ከሰው ፊት ቆምኩ!» አለ መልሶ። ከሰው ፊት መቆም ወይም የሰው ፊት ማየት ሀሳቡ የደበደቡኝን ሰዎች ከማግኘት ጋር የሚያያዝበት ገመድ በግልፅ ባይገባኝም እሱ ሲለው ደስ የሚል ነገር እንዳልነበረ ለማወቅ አልተቸገርኩም። ቃላቶቹን እየረገጣቸው ባለመደሰት ነው ያወራው።

«የማንን ፊት ነው ያየኸው? ማን ፊት ነው የቆምከው?» እያልኩት በጭንቅላቴ ውስጥ ድንበር ላበጅለት የማልችለው ሀሳብ ይጓዛል። ጎንጥ ራሱ ማን ነው? ፊቱን አይቶት ወይም ፊቱ ቆሞ ከመኪና ታርጋቸው ውጪ ስለማንነታቸው ምንም ፍንጭ ያልነበራቸውን ደብዳቢዎቼን ያስገኘለት ማነው? ለሰከንድ ክፉ ሀሳብ ሽው አለ። ጎንጥ ራሱ ነኝ ያለኝን ሰው ባይሆንስ?


                                         ………………….  ይቀጥላል   …………………………

@wegoch
@wegoch
@paappii
#የመኖር አካፋይ ፣ የመ ፤ ሞ ፣ ት ሲሶ ፣ መንገድ መሃል ………… (ክፍል አስር)
(ሜሪ ፈለቀ)


«ንገረኛ? የማንን ፊት ነው ያየኸው?»

«የሚያውቋቸው  እ የምታውቂያቸው ሰዎች አይደሉም!! ከራሴ ያለፈ ህይወት ጋር እንጂ ካንቺ ጋር የሚያያዙ ሰዎች አይደሉም!»

«ንገረኛ ልወቃቸው? አሁንኮ ከእኔ ህይወት ጋርም የሚያገናኛቸው ድርጊት ኖረ አይደል?»

«እትይ አያስጨንቁኝ ስለራሴ ማውራት አልፈልግም!» ካለ በኋላ አንቱ ማለቱ ሲታወሰው «አይ እንግዲህ! እትይ ሱሪ ባንገት አያድርጉብኝ ቀስ ብዬ ልልመደው!» አለ እጁን አየር ላይ እየወረወረ። የሆነች ጥርጣሬ ልቤ ውስጥ ተሰነቀረች። ቅሬታ ያቀፈች ትንሽዬ ጥርጣሬ …… መከፋት ያዘለች ትንሽዬ ጥርጣሬ …… በእንባ የዳመነ ዓይኔን ያስከተለ ትንሽዬ ጥርጣሬ ……. የገባው መሰለኝ አልጋው ጠርዝ ላይ እየተቀመጠ ድምፁን ዝግ አድርጎ

«እትይ ጠረጠሩኝ እንዴ?» ሲለኝ በትክክል የጠረጠርኩት ምን እንደሆነ ጠፋኝ! ቅሬታዬ ማን መሆኑን አለማወቄ እንጂ ልቤን በየትኛውም ጠርዝ ብበረብረው ይጎዳኛል የሚል የጤፍ ፍሬ የምታክል ጥርጣሬ አጣሁ። እንዴት ነው ማን መሆኑን የማያውቁትን ሰው በዚህ ልክ ማመን የሚቻለው?

«አላውቅም! አትቀየመኝ ጎንጥ አላውቅም! …….. በየትኛውም አቅጣጫ ብዞር ካንተ ሌላ ፊቴን ላዞር የምችልበት ሰው የለኝም ፤ ብቸኛው የማልፈራበት ሰዓት አንተ አጠገቤ ስትሆን ብቻ ነው ፤ ያለቅዠት የምተኛው እንኳን አንተ እጆቼን ስትይዘኝ ነው። በዚህ ርቀት የተደገፍኩት ሰው ማን እንደሆነ አለማወቅ ……. » ሳልጨርስ ሀሳቤን ቀማኝ

«እትይ ያለፍኩትን መንገድ አለማወቅዎ የሚያውቁትን እኔን እንዴት ያጠፋብዎታል? (<እኔን > ሲል ደረቱን በቡጢ ነገር ደለቅ ደለቅ አደረገ።) ትናንት ምንም ዓይነት ሰው የነበርኩ ቢሆን እንዴት ዛሬ ላይ የሆንኩትን እኔን ይውጠዋል?» አለኝ ማባበል ባለው ድምፅ

ይሄ <ትናንት> የሚሉት ጦስ ይኸው ዛሬዬን መዞሩን አልተወም!! የሰው ልጅማ ትናንቱን ነው ብያችሁ አልነበር? ነው ግን?

ጎንጥ ዛሬ የማውቀው ፣ ልቤ ያለገደብ የተደገፈው ደግ ፣አማኝ ፣ ለሳምንታት ለሊቶቹን ጎኑን ሳያሳርፍ የሆስፒታል አልጋ ላይ አንገቱን ደፍቶ እጆቼን ይዞ የተኛው ፣ ጎንጥ ነው ወይስ የማላስታውሰው እና የማላውቀው ያለፈ ትናንቱ ውስጥ ያለው እሱነቱ? አያድርገው እና በማላውቀው ትናንቱ ክፉ ሰው የነበረ ቢሆን ዛሬ የሰጠኝን የደግነት ጥግ አጣፋበታለሁ? እሱ ለትናንቱ ክፋቴ ሳይሆን ለዛሬ መሸነፌ ህይወቱን አደጋ ላይ ጥሎ የደበደቡኝን ሰዎች ደብድቦልኝ የለ?

ትናንትማ የዛሬ ማንነታችን መንገድ እንጂ የእኛነታችን መገለጫ አይሆንም። ትናንት ማንነት ቢሆን የትናንት ትውስታ የሌለኝ እኔ ማንነት ላይኖረኝ አይደል? ትናንት ለዛሬ ማንነታችን መንገድ ነው!! እርግጥ መንገዱ ለዛሬ መዳረሻ የሚያዋጣው ምሰሶ እና ማገር ዛሬ ለቆምንበት እኛነት መሰረት ነው።

«ቃሌን እሰጥሻለሁ!! አቅሜ በፈቀደ ሁሉ እጠብቅሻለሁ!! በምችለው ሁሉ ማንም እንዳይጎዳሽ መድረስ ያለብኝ ጥግ ድረስ እደርሳለሁ። እትይ? እንዲያምኑ …. እንድታምኚኝ እፈልጋለሁ? እ? በአምላክ ስም እምልልሻለሁ አንቺን የሚጎዳ ነገር አላደርግም! እ?» እያንዳንዱን ዓረፍተ ነገር <አንቺ> ብሎ ለመጨረስ እየታገለ <እትይ> ማለቱ ፈገግ አስባለኝ።

«እንደማትጎዳኝ ልቤ ያምንሃልኮ …… አላውቅም! ምናልባት እኔ አንድም ነገሬ ሳይቀር ለትናንትም ለዛሬም እንዳመንኩህ ሁሉ ትናንትህን ልትነግረኝ እንድታምነኝ ፈልጌ ይሆናል። አላውቅም!»

«አሁን አይደለም! እትይ እባክዎ አያስጨንቁኝ! ጊዜው ሲሆን አወጋዎታለሁ!»

«እሺ!» ብቻ አልኩኝ። እንደቅድሙ ጀርባዬን እያሻሸ በዓይኖቹ ሌላ ቦታ ተጓዘ። ልቡም ዓይኑን እንደተከተለው ያስታውቃል።

«እትይ ካልከኝ ቀጥለህ አንቺ ልትለኝ አትችልም! በስሜ ጥራኝ ! ስሜን አትወደውም እንዴ ለምን ከበደህ?» ስለው እንደመባነን ነገር ብሎ

«ኸረ ይቅር ይበሎት!» ካለ በኋላ ራሱ ሳቀ …….. ብዙ ጊዜ አይስቅም! ከንፈሩን ለወጉ ሸሸት ያደርጋል እንጂ! ሲስቅ የሚያማምሩት ችምችም ያሉ ጥርሶቹ ብቻ አይደለም የሚስቁት ዓይኑም ፣ ግንባሩም ፣ ጉንጩም ይስቃሉ። እያየሁት እንደሆነ ሲያውቅ ጥርሱን ከድኖ በከንፈሩ ብቻ ፈገገ።

«ሜ - ላ - ት » አለ የሆነ አጠገቡ ያለሁትን እኔን ሳይሆን እሩቅ ያለ ሰው አስታውሶ የሚጠራ በሚመስል ድምፅ

«አየህ ? አያንቅህም ወይ ትን አይልህም! ደግሞ አፍህ ላይ ያምራል!» ብዬው ሸርተት ብዬ ተኛሁ። እንደተለመደው ወንበሩን ወደ አልጋው ጠጋ አድርጎ ተቀምጦ ሲያበቃ እጄን ያዘኝ። መልእክቱ ዓይንሽን ከድነሽ ማረፍ ትችያለሽ ነው። እንደማመስገን ነገር የያዘኝን እጁን ጨበጥ ሳደርገው ጥርሱን ነክሶ ፊቱን ቀጨም አደረገ።

«ውይይ ይቅርታ ረስቼው ነው» ብዬ እጄን አስለቀቅኩ። ከንፈሩን አሽሽቶ መልሶ እጄን ያዘኝ። እንደደከመው ያስታውቃል። ምናልባት እንቅልፉን ከተኛ ብዙ ሰዓታት አልፈውት ይሆናል። ምናልባት እህል የአፉን ደጃፍ ካለፈ ቆይቷል። ምናልባት ያበጡት እጆቹ እና የበለዘ አይኑ እየቆጠቆጠው ይሆናል። ለመጀመሪያ ጊዜ ከፀጉሩ ጀምሮ ፍትፍት አድርጌ በዓይኔ አስተውለው ጀመር። እያደገ ያለ ያልተበጠረ ጥቁር ፀጉሩ ፊት ላይ በጎን በኩል ሆነ ብሎ ያቀለመው የሚመስል ሽበት አለው። ግንባሩ ላይ ያሉት የሚኮሳተርባቸው መስመሮች ሞገስ ነገር ሆነውታል ልበል? ዓይኖቹ ብቻቸውን መሳቅም መኮሳተርም ያውቁበታል። ዓይኖቼን በዓይኖቹ ሲቀልብብኝ አፍንጫ ፣ ከንፈር ፣ አገጩን ዘልዬ ትከሻው ላይ ደረስኩ። ትከሻው ስፋቱ ተጣበው ቢቀመጡ ….. ሁለት በአንደኛው ጎን ሁለት በሌላኛው ጎን አድርጎ  አራት ህፃናት ያሰፍራል። ደረቱ ቀብረር አድርጎ አስር ኪሎ ፍትግ ገብስ ያሰጣል። ክንዱ ……… ክንዱ እየደማ ነው! የለበሰውን ግራጫማ እጅጌ ያለው ቲሸርት እያረጠበው ነው።

«እየደማህ እኮ ነው! » ብዬ ጮህኩ። ዓይኔን ተከትሎ እየደማ ያለ ክንዱን አየት አደረገ እና ህመሙን ሊደብቀኝ እንደፈለገ በሚያቃጥርበት ሁኔታ

« እ ትንሽዬ ቁስል ናት!» ብሎ በእጁ ደገፍ አድርጎት ተነሳ። ከዓይኖቼ ርቆ ደሙን ሊጠራርግ እንደሆነ ገብቶኛል።

«አሳየኝ?  ትንሽዬ አይሆንም አሳየኝ !» ብዬ ስጮክበት የለበሰውን ቲሸርት በቀስታ በአንድ እጁ በኩል ወደላይ አውልቆት ተቀመጠ። ቁስሉ በነጭ ፋሻ ታሽጓል። እኔጋ ከመምጣቱ በፊት ሀኪም ቤት ሆዶ የነበረ ሰውዬ ነው ይሄን ሁሉ ሰዓት ህመሙን ውጦ አጠገቤ የተቀመጠው? ወይስ ስቃዩን አላስተዋልኩለትም?  የታሸገበትን አልፎ ነው ደሙ ልብሱን የነካው።

«በምንድነው የተመታኸው?» አልኩት

«ስለት ነው! » ካለ በኋላ ፊቴን አስተውሎት «መድሃንያለም በሚያውቀው ብዙ አይደለም! ከላይ ነው ጨረፍ ያደረገኝ! ደሙ ዝም ብሎ ሲያዳምቅ ነው!» አለኝ።

«እሺ የታሸገበትን ይቀይሩልህ እና እቤት ሄደህ እረፍ! ተናኜን ላካት!» አልኩት አልሰማኝም! ወጥቶ ቁስሉን አሳክሞ ተመልሶ መጣ ወደቤት ግን አልሄደም!



                                                 *****
ቁስሌ አገግሞ ከሆስፒታል ከወጣሁ በኋላ ፤ ጎንጥ አንቱ እና አንቺ ማምታታት ካቆመ በኋላ ፤ እቤት እንደገባሁ ሰፋፊ ጅንሶች እና ብረታ ብረት የበዛባቸው ልብሶቼን ካቃጠልኩ በኋላ ፣ ብዙ ነገሮችን እንደአዲስ ከተማርኩ በኋላ ፤ እናት እና ወንድሜን ለማግኘት ብዙ ያልተሳካ ፍለጋ ካደረግኩ በኋላ ፣ አባን ደግሜ አጊንቼ ጉልበታቸውን ተደግፌ ከተመከርኩ በኋላ ፣ ብዙ ቀናት ዳዊት ደውሎ ከተልመጠመብኝ በኋላ …….. ስልኬ ጠራ!

«ሜላት ነሽ? አስካለ ደውዪላት ብላኝ ነው።»

«አስካለ? አስካለ?»

«እናትሽ !» አባባሏ መገረም ነበረው። ከተቀመጥኩበት ዘልዬ ተነሳሁ።

«የት ልምጣ?» አልኩኝ ሳላስበው።

«ህም! እቤት ገብታለች። ዛሬ ነገ ሳትዪ መጥተሽ እያት! ጥሩ ሁኔታ ላይ አይደለችም!» ያለችኝ ቤቱን እንደማውቀው እርግጠኛ ሆና ነው።

«እባክሽ የቤቱን አድራሻ ንገሪኝ?» አልኳት ገና ሳትጠይቀኝ እንዴት የእናቴን ቤት እንደረሳሁት ማብራራት እያደከመኝ። አልጠየቀችኝም። እጅግ ግርምት ባለበት አነጋገር ሰፈሩን ነገረችኝ።

«ስትደርሺ ደውዪልኝ እና እመራሻለሁ!» ብላ ስልኩን ዘጋችው። ለተወሰነ ደቂቃ በቆምኩበት ደርቄ ቆየሁ። እየቆየሁ እንደመባነን ነገር አደረገኝ እና ልብሴን መቀያየር ጀመርኩ። ከታች ቀይሬ ከላይ ሳልቀይር ወደሳሎን ተመልሼ ጎንጥን መጣራት ጀመርኩ።

«በትክክል እናትሽ ባይሆኑስ?» ብሎ ያላሰብኩትን ጥርጣሬ አቀበለኝ የተደወለልኝን ስልክ ስነግረው

«ማረጋገጥ የምንችልበት ብቸኛ መንገድ ስንሄድ ብቻ አይደል?» አልኩት። ተመልሼ የቀረኝን ልብስ ቀያይሬ ስመለስ እሱ መኪናውን ከጊቢ እያወጣ ነበር።

በስልክ እየተመራን ደረስን። ልቤ እየዘለለች በአፌ ልትወጣብኝ ታገለችኝ። በስልክ ያናገረችኝ ሴት በሩ ላይ ጠብቃን እየመራችን ወደጊቢው ስንዘልቅ ጎንጥ እጄን ያዝ አድርጎ ከፊቴ ቀደመ። በአንድ እጁ አንድ እጄን እንደያዘ ሌላኛውን እጁን ወደ ወገቡ አካባቢ ሲሰድ ዓይኔ እጁን ተከትሎ የጨበጠው ነገር ላይ አረፈ። በደረበው ጃኬት ስር ሽጉጥ ይዟል። መጮህ ቃጣኝ ነገር እና የሆነ ድምፅ አወጣሁ።የያዘውን እጄን ሳላውቅ መነጨቅኩት።  ሴትየዋ ስትዞር ደንግጬ ቆምኩ። ከዚህ በኋላ ልቤን እንዲህ የሚያስደልቃት የጎንጤ ሽጉጥ ይሁን እናቴን ማግኘት አልገባኝም። እግሬን ብርክ ያዘው። ጎንጥ መልሶ እጄን ቀለበብኝ እና ወደጆሮዬ ጠጋ ብሎ

«ምን እንደሚገጥመን አናውቅም! መሳሪያ ቢገጥመኝ በባዶ እጄ ልጠብቅሽ አልችልም!! » አለኝ ድምፁ ቁጣ ነገር አለው። የሆነ <ዋጥ አድርጊያት> የሚል ዓይነት ቁጣ …… ምርጫ ነበረኝ? ማሰቢያ ጊዜ አልሰጠኝም። ድንጋጤዬን ዋጥ አድርጌ ተከተልኩት። ሴትየዋ እየመራች የሆነ ድክም ያለ ባለሁለት ክፍል ቤት አስገባችን!!

                  ………. ይቀጥላል ………..

@wegoch
@wegoch
@paappii
#የመኖር አካፋይ ፣ የመ ፤ ሞ ፣ ት ሲሶ ፣ መንገድ መሃል ………… (ክፍል አስራ አንድ)
(ሜሪ ፈለቀ)

ጭንቅላቷ ከአልጋ ልብሱ ወጥቶ ባይታይ ኖሮ የደቀቀ ሰውነቷ ከአልጋው ተጣብቆ አልጋው ላይ ሰው የተኛ አይመስልም ነበር። ፊቷ አጥንቱ ቢገጥም መልኳን የት እንደማውቀው ለማስታወስ አልተቸገርኩም። ስልኬ ውስጥ ካገኘኋቸው ፎቶዎች ውስጥ አይቻታለሁ። እናቴ ትሆናለች ብዬ ጠርጥሬም ነበር። አጠገቧ ከተቀመጥኩ ደቂቃዎች ቢያልፉም ከጥቂት የ<ደህና ነሽ?> ቃላት ልውውጥ ውጪ ከምን ጀምሬ ምን እንደምነግራት ወይም ምን እንደምጠይቃት ግራ ገብቶኝ ተጎለትኩ። እሷም እንደእኔ ግራ ገብቷት ይሆን ወይም ስትናገር እያማጠች በመከራ በመሆኑ ደክሟት አላውቅም ዝም ብላለች። በዝምታዋ መሃል እንባዋ ወደጆሮዋ ፈሰሰ። የእኔም እንባ የሚወርድበት ሰበብ እየጠበቀ ያለ ይመስል ተንደረደረ።

«ልጄ ማሪኝ!?» አለችኝ እንባዋን ዋጥ እያደረገች። ላቅፋት እፈልጋለሁ። ወይም እንድታቅፈኝ እፈልጋለሁ። ልጅ እናቱ ጉያ ሽሽግ ብሎ ፍቅር እንደሚምገው እቅፏ ውስጥ ገብቼ ይሄ ብርዳሙ ልቤን ላሞቀው እፈልጋለሁ። ባልገባኝ ምክንያት ልቤ ባዳነት ነው የሚሰማው ……….  እሩቅነት ….. ማን ብዬ ነበር ይሆን የምጠራት? እማዬ? እማ? እናቴ? እትዬ? አስካለ? አቅፋኝ ታውቅ ይሆን እንደዛ? የተፈጠረውን በአጭሩ ነገርኳት።

«ምህረት የምትጠይቂኝ ለምን እንደሆነ አላውቅም!! አንቺንም አላውቅም! ያሳለፍነው ምን እንደሆነም አላውቅም! ራሴንም አላውቅም! ምንም ይሁን ይቅር ብዬሻለሁ። የበደልሽኝ ነገር ካለ እሱን አትንገሪኝ ይቅር። አብረን ያሳለፍነውን ጥሩ ጊዜ እና ፍቅር ብቻ ንገሪኝ። ማወቅ ያለብኝን ራሴን ብቻ ንገሪኝ።» አልኳት አባ ያሉኝን አስታውሼ። <ለበቀል ነው የኖርሽው ልጄ በተሰጠሽ አዲስ ህይወት ለፍቅር ኑሪ! > ብለውኝ ነበር። የቱን እንደምትነግረኝ ጨንቋት ይሆን ዝም አለች ለብዙ ደቂቃ ከዛ መልሳ ማልቀስ ጀመረች።

« አሁን ብሞትም አይቆጨኝ! » አለች ደግሞ ደስ የተሰኘች ነገር መስላ። ግራ አጋባችኝ። ምኑ ነው ደስ ያላት? የእኔ ምንም አለማስታወስ? ወይስ ይቅር ብዬሻለሁ ማለቴ? ግራ እንደገባኝ ስታይ
«የእኔ አበባ ብታስታውሺውም ከሚያንፅሽ የሚያፈርስሽ ታሪክ ይበዛናል። ያለፈውን ለማስታወስ የምታጠፊውን ግዜ አዲስ ህይወት ለመገንባት ብትጠቀሚበት ነው የሚጠቅምሽ የሚመስለኝ። ካለፈው መንገድሽ የሚጠቅምሽን ብቻ አንስተሽ ተጓዥ» ስትለኝ ሳላውቀው ተናደድኩ

«ለምንድነው ማናችሁም የማይገባችሁ? የሚጠቅመኝንም የማይጠቅመኝንም የማስታውሰው ምንም የለምኮ ነው የምልሽ! የገዛ እናቴን አላስታወስኩሽም እኮ ነው የምልሽ! ወንድሜ የት እንዳለ አላውቅም! የት እንደማገኘውም አላውቅም! የማውቀው የነገሩኝን ነው የነገሩን ደግሞ የሰይጣን ቁራጭ እንደነበርኩ ነው። ቢያንስ ያን የሆንኩበትን ምክንያት ማወቅ የለብኝም? ራሴን እንኳን ከማን እንደምጠብቅ ጠላቶቼን እና ወዳጆቼን ለይቼ የማላውቅ ሰው ነኝ። ሌላው ይቅር ለእናቴ ምን አይነት ልጇ እንደነበርኩ ማወቅ እፈልጋለሁ። » ስጮህባት እጇን ሰዳ እንባዬን ጠረገችው።

«ለእናትሽ መተኪያ የሌለሽ ጀግና ልጇ ነበርሽ» አለችኝ ተረጋግታ! እኔ እየጮህኩ እሷ ፈገግ የምትልበት ምክንያት አልገባኝም። ልክ አባ ያለፈውን መርሳቴን ሲያውቁ እንደሆኑት ነው እየሆነች ያለችው። « ልጅም ሆነሽ እንደአባትሽ ጀብደኛ ነበርሽ» አለችኝ ያለፈውን ዘመን ልጓም ስባ በምናቧ ወደዛሬ እያመጣች ፈገግ ብላ

«እኔ ነኝ ሜላት ያልኩሽ! አባትሽ የመጀመሪያ ልጁ  እሱን የሚተካ ወንድ እንዲሆን ይመኝ ስለነበር <አምሳል> ነው የሚልሽ የነበረው። (አባቴ በህይወት አለ? ብዬ ልጠይቃት ፈለግኩ እና ወሬውን ብታቋርጥብኝስ ብዬ ፈርቼ ዝም አልኩ።) መቼም እንዴት ይሳሳልሽ እንደነበር ምንም ቃል አይገልፀውም! የትም ቦታ ሲሄድ ትከሻው ላይ ሰቅሎሽ ነበር የሚሄደው። ከአራት አመት በኋላ ወንድምሽን ብንወልድም አባትሽ ከወንድምሽ ይልቅ ትኩረቱ አንቺ ነበርሽ። እያደግሽ እንደእኩዮችሽ እንጀራ ማስፋት ከመማር ይልቅ የአባትሽን መሳሪያ መወልወል እና ፈትቶ መግጠም ነበር የሚያስደስትሽ። አድገሽ ምን መሆን ነው የምትፈልጊ ስትባዪ <ሽፍታ> ነበር የምትዪው (ፈገግ አለች እና የሽፍታ ትርጉም እንዳልገባኝ ጠርጥራ መሰለኝ ቀጠለች።) አባትሽ ወታደር ነበር። ከውትድርና ከተመለሰ በኋላ ቀዬአችን በማይረባ የይገባኛል ሽኩቻ ስትታመስ አባትሽ ራሱን የቀዬው ጠባቂ አድርጎ ሾመ። ዋጋ እንደሚያስከፍለው ብነግረውም አልሰማኝ። የእርሱ ቢጤ ደጋፊዎቹን አስከትሎ ጫካ ገብቶ ሸፈተ።»

«አባቴ ያጨስ ነበር?» አልኳት

«ከጊዜ በኋላ ያመጣው ዓመል እንጂ አጫሽስ አልነበረም።» ካለችኝ በኋላ በጥርጣሬ ዓይን አተኩራ አየችኝ።
«የወታደር ልብስ ቀለም ያለው የሲጋራ መለኮሻ እቤቴ ካዝና ውስጥ አጊንቼ ነበር። የሆነ ብልጭ የሚል ምስል ጭንቅላቴ ውስጥ ሽው ይላል። የሆነ ደም የነካው እጅ ያንን የሲጋራ መለኮሻ ይዞ …… ፊቱ ወይም የቀረው ሰውነቱ አይመጣልኝም። ፍርጥም ያለ ሰፊ በደም የራሰ ጠይም እጁ ብቻ ነው የሚታየኝ።» እያልኳት ጭንቅላቷን በአወንታ እየነቀነቀች ፊቷ ላይ የነበረው ደስታ በአንዴ ድፍርስርስ ብሎ ሃዘን ይንጣት ጀመር። ማስረዳት የማልችለው ስሜት አባቴ እንደሞተ ነገረኝ። ያ ቀን እጁ …..የሚታየኝ ቀን ….. አባቴን ያየሁበት የመጨረሻ ቀን መሆኑን ገመትኩ። 

«ሞቷል አይደል? ምን ሆኖ ነው የሞተው? ሰው ነው የገደለው? ሲሞት አጠገቡ ነበርኩ አይደል? የሚታየኝ ምስል የሞተ ቀን ነው አይደል?» ቃላት ከአፏ ማውጣት አቅቷት በጭንቅላቷ ንቅናቄ ብቻ አዎ አለችኝ ከእንባዋ ግብግብ እየገጠመች። ዝም አልኩ። ዶክተሩ የሲጋራ መለኮሻ ላይተሩን ፣ ሽጉጡን ፣ ንቅሳቴን ሳይ ሽው የሚልብኝን አንድ የሰው እግር እና ጨለማ ክፍል ፣ ፎቶውን ሳይ የተሰማኝን የሳር እርጥበት ስነግረው

«ምንም እንኳን ያለፈ ትውስታሽን ብታጪ ጭንቅላታችን ያሳለፍነውን ከባድ ጊዜያት ወይም ትሮውማ የፈጠሩብንን አጋጣሚዎች በተለየ መዝግቦ የመያዝ አጋጣሚው ሰፊ ነው። ከገጠመኙጋ የሚያያዙ ነገሮች ስታዪ ጭንቅላትሽም ሰውነትሽም ሪአክት ያደርጋል። ምናልባት በተለየ ያስታወስሻቸው ነገሮች እንደእነዚህ ያሉ ክስተቶች ይሆናሉ።» ብሎኝ ነበር። ያ ቀን ፣ ያ የሲጋራ መለኮሻ ላይተር ፣ የሚታየኝ የአባቴ እጅ …….. የመራራዋ ሜላት ጥንስስ ሊሆን እንደሚችል አሰብኩ። ስለዛ ቀን እንድትነግረኝ ፈለግኩ ግን ደግሞም ፈራሁ። ክፉ ትውስታዎቼ ሁሉ ግልብጥ ብለው የሚመጡብኝ መሰለኝ። ትናንቴን መፈለጌ ውስጥ እስከዛሬ ያላሰብኩበት ነገር ሰውነቴን አደነዘዘኝ።

ትናንቴን ሳገኘው ተመልሼ የትናንትናዋን ሜላት ብሆንስ? ከትውስታዬጋ ማንነቴም ተመልሶ ቢመጣስ? ያቺን ሴት ተመልሼ መሆን እንደማልፈልግ እርግጠኛ ነኝ። ግንሳ ያቺን ሴት ያደረጉኝን መንገዶቼን ሳውቅ ቂሜ ፣ መከፋቴ፣ ንዴቴ ፣ መራርነቴ ፣ ሁሉም ስሜቶች ከትውስታው ጋር መጥተው ይወሩኝ እና ያቺን ሜላት እንቢ ብዬ ላመልጣት ባልችልስ?

«ማነው የገደለው?» አልኳት ሳላስበው ውስጤ የሆነ የተለየ ስሜት እያፈነው። ምናልባት ያቺ አባ የነገሩኝ በቀለኛዋ ሜላት ተሸፍና እንጂ አልጠፋች ይሆናል።

« የእኔ አበባ አባትሽን የገደሉትን ሰዎች አድገሽ አንድ በአንድ ተበቅለሻቸዋል። አታስታውሺው ይሄ ይቅርብሽ!! » አለችኝ በልመና።
«አባቴ ሲሞት ስንት ዓመቴ ነበር?» አልኳት ውስጤን የአባቴን መልክ የማስታወስ ከፍተኛ ፍላጎት እያተራመሰው። ወዲያው ቀጥዬ «አባቴ ምን ይመስል ነበር?»
«13 ዓመትሽ ነበር። አባትሽ ሲሞት 13 ዓመትሽ ነበር። አባትሽ አንቺን ነበር የሚመስለው። መልካችሁ ብቻ መሰለሽ? ቁመትሽ ሳይቀር የሱ ነው። ነገረ ስራሽ የእርሱ ቅጂ መሆንሽ አይጣል ነው።» አለችኝ ለቅሶዋን ገታ አድርጋ። ከዚህ በኋላ የምጠይቃት ነገር ሁሉ ከእርሱ ሞት ጋር የተያያዘ እና የሚያስለቅሳት ስለመሰለኝ ምን ዘልዬ ምን እንደምጠይቃት ግራ ተጋባሁ።

«ኪዳን የዘጠኝ ዓመት ልጅ ነበር። እሱ እንዳንቺ ጠንካራ አልነበረም። (ቅስስ ብላ ነው ይሄን የምታወራው) ክፉ እንዳያይ ጠበቅሽው፤ ክፉ እንዳይነካው ጠበቅሽው። እህትም እናትም ሆንሽው።» ብላኝ ፊቷን አዞረች።

«አንቺስ? እንዴት ነው ከህይወቴ የጎደልሽው? ለምን ተለያየን? ኪዳን አሁን የት ነው?»

አልመለሰችልኝም። ፊቷን ከእኔ መደበቅ ነው የፈለገችው። በእጇ አልጋ ልብሱን ጨመደደችው። ከአባቴ ሞት በላይ ሀዘኗን የሚያበዛ ሌላ ነገር መኖሩ ገባኝ።

«እ? ንገሪኝ ምንድነው የተፈጠረው? » አልኳት

«ኪዳን ካናዳ ነው ያለው። ዶክተር ሆኗል አልሽኝ። አሁንም ትምህርቱን ቀጥሎ የጭንቅላት ቀዶ ህክምና እየተማረ ነው ያለው አልሽኝ መሰለኝ በትክክል ካስታወስኩ።» አለችኝ ፊቷን ሳታዞር

«አንቺስ? ምንም ቢሆን ንገሪኝ እና ታሪኬን የተሟላ አድርጌ ልገጣጥመው።» ልበላት እንጂ በምንም መርፌ የማልሰፋው ብዙ የተቦጫጨቀ ጎዶሎ እንዳለው ገብቶኛል።

«አባትሽ ከሞተ በኋላ (ዝም አለች ለሆነ ሰከንዶች። ተገቢውን ቃል እየፈለገች መሰለኝ) አባትሽ ከሞተ በኋላ አቃተኝ። እናት መሆን አቃተኝ። ያንቺን ፊት በየቀኑ ማየት አቃተኝ። ለአጎታችሁ ትቻችሁ ከተማ መጣሁ። ይኸው ነው!! እኔ የማልረባ እናት ስለሆንኩ ነው የተለያየነው። ራስ ወዳድ ስለነበርኩ ነው ከህይወታችሁ የጎደልኩት።» እያለች ትንሰቀሰቅ ጀመር። የሚሰማኝ ስሜት ተደበላለቀብኝ። ምንም ቢሆን ይቅር ብዬሻለሁ እንዳልኳት አልቀለለኝም። አባታቸው የሞተባቸው ልጆችዋን እንዴት ትታን ትሄዳለች? ልቤ የለመደው ብርድ በረደው። ውስጤ ተከፋባት ግን ደግሞ ከነገረችኝ ታሪክ የተለየ ያልነገረችኝ ምክንያት እንዳለ ይሰማኛል።

«በቃ? ይሄ ብቻ ነው ምክንያትሽ? ለምንድነው ያልነገርሽኝ ሌላ ነገር እንዳለ የሚሰማኝ? እ?» ከዚህ በኋላ የጠየቅኳትን ጥያቄ አንዱንም አልመለሰችልኝም። እቤቴ ይዣት ልሄድ ብለምናትም እንቢ አለችኝ። ልቀየማትም እፈልጋለሁ ልታረቃትም ያምረኛል። እሺ ልጅ ሆኜ ትታኝ ሄደች አሁን እንኳን በሞቷ አፋፍ ላይ ሆና የቀራትን ቀናት ፍቅሯን እንደተራብኩ እንዴት አይገባትም? ያልጠገብኩት እቅፏ እንደሚያስፈልገኝ እንዴት አትረዳም? ልጮህባትም ያምረኛል። ደግሞ እቅፏ ውስጥ ገብቼ ለሰዓታት ጠረኗን መማግም ያምረኛል። ለብዙ ደቂቃዎች ያለምንም ንግግር ዝም ብለን ቆየን። ትቻት ብወጣ ስመለስ የማላገኛት ዓይነት ስሜት እየተሰማኝ ከልክ በላይ ከፋኝ። ከየት መጣ ሳልለው እንባዬ ገነፈለ።

«ምንም አልጠይቅሽም። ምንም አትመልሽልኝ። አጠገቤ ብቻ ሁኚልኝ። የቀረሽ ቀን ቀንድም ቀን ይሁን አንድ ዓመት አብረሽኝ ሁኚ። አንድ ቀንም ቢሆን እማዬ ልበልሽ? አንዲት ሰዓትም ቢሆን ልጅሽ ልሁን?» ብዬ እሪሪሪ ስልባት እሷ ከእኔ ባሰች። በጭንቅላቷ ንቅናቄ እሺ አለችኝ። ከነመድሃኒቶቿ ይዣት ወደ ቤት ተመለስኩ።

ለቀናት ከእሷ ውጪ ስለምንም ነገር ማሰብ አልፈለግኩም። ህመሟ እየፀናባት ስለሆነ ብዙም አትንቀሳቀስም። ምግብ ለመብላትም ታስቸግራለች። ምንም አልጠይቃትም። እሷም ከአባቴ ሞት በፊት ስለነበረን ውብ የልጅነቴ ጊዚያት አንዳንድ ነገር ከማውራት የዘለለ አለመጠየቄ የተመቻት ይመስላል። አብሬያት እተኛለሁ። እሷን ከማጣጣም ውጪ ሌሎች ጥያቄዎቼን እና እውነታዎችን ሆነ ብዬ ችላ አልኩ። እሷ ስለኪዳን እኔ ከነገርኳት ውጪ የምታውቀው መረጃ የለም። እሷ እንደምትለኝ እንደዛ የምወደው እህቱ ከነበርኩ እንዴት ይሄን ሁሉ ጊዜ አይፈልገኝም? የሚለው ሀሳብ በመሃል ይጠልፈኛል። የጎንጥን ሽጉጥ መታጠቅም ልቤ አልረሳውም። አሁን ግን ከእናቴ ውጪ ምንም ነገር ላይ መጠመድ ስላልፈለግኩ ችላ አልኩኝ። ከቀናት በኋላ እናቴ ስትፈራ ስትቸር ቆይታ

«ከሀገሬ ከወጣሁ በኋላ ድጋሚ አልተመለስኩም። ከመሞቴ በፊት ቀዬዬን ብረግጠው ፣ ቤተኞቼን በአይኔ ባያቸው፣ ያ ከርታታ ወንድሜ ምን ላይ እንዳለ ባውቅ፣ ኸረ እንደው ሞቴም እዛ ቢሆን አይከፋኝ። እዛው በአፈሬ ብቀበር። » አለችኝ እንደ እሩቅ ምኞት

ምን ሊፈጠር እንደሚችል ሂሳብ አልሰራሁም። የመጀመሪያው ሀሳቤ የእናቴን ምኞት መሙላት ነው። የሆነኛው ልቤ ውስጥ ግን ናፍቆት አለው። ያ የሳር እርጥበት፣ ያ ቤቴ የሚመስለኝ አረንጓዴ አውድማ …… ልጅነቴ ….. ያደግኩበት መንደር ….. የማላውቀው ግን የማልቆጣጠረው ናፍቆት …….

እናቴ ተቀምጣ ብዙ መጓዝ ስለማትችል የሚመቻት መኪና ተከራየን እና ጎንጥ እየነዳ ከአዲስ አበባ ርቀን ወጣን። ሰው የሚፈልገውን ነገር እንዴት ይፈራዋል? እዛ አውድማ ላይ ስቆም ትውስታዬ እየተግተለተለ የሚመጣ እየመሰለኝ ፍርሃት ያንቀኛል። አውድማው ላይ ስቆም እንዳሰብኩት ትውስታዬ አልመጣም። አውድማው እንደፎቶው አረንጓዴ አይደለም። እናቴ እና ወንድሟ ሲገናኙ የተሰበሰበውን ሰፈርተኛ በእንባ ያራጨ ትእይንት ሆነ። በየቤቱ እየተዞረ የተነገራቸው ይመስል ግልብጥ ብሎ ለመጣው ሰፈርተኛ ሁሉ ጭንቅላቴ ስለማያስታውስ አላውቃችሁም ብሎ ማስረዳት አድካሚ ስለነበር እያቀፉ የሳሙኝን ሁሉ በፈገግታ እያቀፍኩ ስስም ቆየሁ። እናቴ ቀስ በቀስ የትኛው የስጋ ዘመዴ የትኛው ጎረቤት መሆኑን አስረዳችኝ።

መንደሩን ለቅቄ ወንድሜን ይዤ የወጣሁት በ19 ዓመቴ እንደነበር አወቅኩ። የቤቱ ግርግር ሲሰክን እናቴም ድካሟ ጠንቶ ስትተኛ ከቤት ወጥቼ እግሬ ወደመራኝ ዘወር ዘወር ማለት ጀመርኩ። ጎንጥ እየተከተለኝ እንደሆነ ሳውቅ ቆሜ ጠበቅኩትና እኩል መሄድ ጀመርን። የሆነች ትንሽዬ ቤተክርስቲያን አልፈን፣ እጅብ ያሉ ቤቶች ካሉበት አለፍ ብለን የሆነ የፈረሰ ቤትጋ ስደርስ ቆምኩ። ለዘመናት ማንም እንዳልኖረበት የሚያስታውቅ፣ አረም እና ሀረግ የበቀለበት ግድግዳ ፣ የወለቀ በር፣

ደረቴን ደቅቶ ያስቆመኝ የሆነ ነገር ያለ ይመስል ቆምኩ። ጎንጥ ደንግጦ ያዝ አደረገኝ እና «ምነው?» አለኝ። አፌ ቃል አላወጣም። እግሬ የዛለ ስሜት ስለተሰማኝ ዘጭ አልኩ መሬቱ ላይ በቂጤ።

«ይሄ ቤታችን ነበር። አባቴ እዛጋ ነው የሞተው።» አልኩት በጣቴ እየጠቆምኩት።

              አልጨረስንም

@wegoch
@wegoch
@paappii
#የመኖር አካፋይ ፣ የመ ፤ ሞ ፣ ት ሲሶ ፣ መንገድ መሃል ………… (ክፍል አስራ ሁለት)
(ሜሪ ፈለቀ)


ከተቀመጥኩበት ሳልነሳ ለደቂቃዎች ቆየሁ። ምን ያህሉን እንዳስታወስኩ ባላውቅም ደጁን እያየሁት ምስሎቹ ጭንቅላቴ ውስጥ ቅርፅ እየሰሩ ተደረደሩ። ከቤት ተንደርድሬ ስወጣ በዛ ያሉ መሳሪያ የታጠቁ ወንዶች በድል አድራጊነት እየተወጣጠሩ ጊቢያችንን አልፈው እየወጡ፣ የመጨረሻው ሰውዬ አባቴ በወደቀበት ተራምዶት ሲያልፍ ፣ ዘልዬ አጠገቡ ስደርስ የቱጋ እንደተመታ እንኳን እንዳይለይ ሆኖ ልብሱ በደም ርሶ በእጁ የያዛትን የሲጋራ መለኮሻ መጨበጥ አቅቶት እጁ ሲዝል፣ እሪሪሪ ብዬ ስጮህ  እንኳን መንደርተኛው ባለመሳሪያዎቹን ፈርቶ ስለተሸሸገ ብቅ ያለልኝ ጠፍቶ ባለመሳሪያዎቹ ተመልሰው ቢደፉኝ እንኳን ግድ ሳይለኝ ድምፄ እስኪዛጋ ስጮህ እና ስሳደብ ……… የጎረቤታችን ቤት በእሳት ተያይዞ እየነደደ የእነርሱ ጩኸት ከእኔ ቢብስም ሊረዳቸው ብቅ ያለ አልነበረም። እናቴ እግሯንም ቅስሟንም እየጎተተች ከቤት ውስጥ ብቅ ስትል አባቴ ነፍሱ ወጥታ ነበር። አላለቀሰችኝም። አጠገቡ መሬቱ ላይ ቁጭ ብላ በደም የራሰ ደረቱ ላይ ተኛች። ጩኸቴን አቁሜ አየኋት። አታወራም ፣ አታለቅስም፣ ምንም ስሜት አይታይባትም። ከአባቴ ፊት ይልቅ የሞተ የሚመስለው የእርሷ ፊት ነበር። ብርግግ ብዬ ተነስቼ ወደ ቤት ውስጥ ሮጥኩ።

በቃ እዚህ ድረስ ብቻ ነበር ለጊዜው የታየኝ። ከተቀመጥኩበት ተነስቼ ሀረግ ወደወረረው ቤት ውስጥ ገባሁ። ደጁ ላይ የበቀሉት አረሞች እሾህ ያላቸው ስለነበሩበት ልብሴን እየያዘኝ ነበር ያለፍኩት። ጎንጥ አንዴ ፊት ፊቴን አንዴ መንገድ መንገዱን እያየ በዝምታ ይከተለኛል። ቤቱ ውስጥ ሳሎን አሮጌ አግዳሚ ወንበር እና የተበታተኑ ቆሻሻዎች አሉ። እንደገመትኩት አንዳንዱ ሰፈርተኛ ቆሻሻውን እያመጣ እዚህ ይጥላል። በቆሻሻ እና በዓይነምድር የሞሉትን ክፍሎች እየዞርኩ ግማቱ እንኳን አልታወቀኝም። ያ ቤት ያደግኩበት ልጅነቴ መሆን አለበት። ነገር ግን አንድም ከልጅነቴ ጋር የተያያዘ ትውስታ አልመጣልኝም። የዛን ቀን የሆነው ግን አንድ በአንድ የአሁን ያህል ሰውነቴን እስኪወረኝ ታወሰኝ። ጭንቅላቴ የፈለገውን መርጦ አንዲት ክስተት ብቻ አስታውሶ ነው ወይስ ቦታው ላይ ስገኝ ሌሎቹንም ትውስታዎቼን አገኛቸዋለሁ? አልገባኝም! ከሆነም ለምን ልጅነቴን አላስታወስኩም?

ዶክተር እንዳለኝ አስፈሪ ገጠመኞቼን ከደበቀበት እያወጣ ሊሆን ይችላል ……. ጭንቅላቴ ራሱ ክፋቱ እንጂ ወይ ሙሉውን ባያስታውሰኝ አልያም እናቴ አውርታ የማትጠግበውን ደጉንም ልጅነቴን ቢያስታውሰኝ ምን ነበረበት?

የዛን ቀን ከሆነው ውስጥ ያላስታወስኩት ይኑር አይኑር የማረጋግጥበት ምንም ማመሳከሪያ የለኝም። ያስታወስኳቸው ምስሎች ግን የጎደለ የሚመስል ትዕይንት የላቸውም።

አባቴ እና እናቴ ሲጨቃጨቁ ሌላኛው ክፍል ከኪዳን ጋር ሆነን እንሰማቸዋለን። እናቴ አባቴ ላይ ትጮሃለች።

«እኔ የምልህን አንዴ ሰምተኸኝ ቢሆን ይሄ ሁሉ አይመጣም!! ያንተ ፉከራ ዛሬ ከምን እንደሚያድንህ እናያለን! እሺ ልጆቼን ምኔ ውስጥ ልደብቃቸው? ሄዳችሁ ባትተነኩሷቸው ዛሬ አሳቻ ሰዓት ጠብቀው መንደራችንን ባልወረሯት ፤ እሺ አሁን ምንድነው የምሆነው?» በበሩ አጮልቄ አያቸዋለሁ። እሷ ወገቧን ይዛ እየተንጎራደደች ነው። እሱ ትልቅዬ መሳሪያ ወደበሩ አነጣጥሮ መንደራችንን ወረሯት የተባሉትን ሰዎች በሩን አልፈው ቢገቡ ሊቀልባቸው ይመስል ይጠብቃል። እናቴ አታቆምም።

«እናንተ የእነሱን መንደር ሄዳችሁ አቃጥላችሁ <ጉሮ ወሸባዬ> እያላችሁ ስትመለሱ እጃቸውን አጣጥፈው የሚቀመጡ ነበር የመሰላችሁ?»

«አንቺ ብዙ የማይገባሽ ነገር አለ አስካል! የአያት የቅድመአያቴን መሬት ካልፈነጨሁበት ሲሉ እኔስ ኑና በላዬ ዘብጡ ብዬ ዘንባባ አንጥፌ እንድቀበላቸው ነው ምኞትሽ?» እየጮኸ ነው እሱም የሚመልስላት። ከውጪ የብዙ ወንዶች ዘፈን ይሁን ፉከራ ያልለየለት ድምፅ እየቀረበ እየቀረበ ይሰማል። በመሃል የሚያወሩት በትክክል ባይሰማም ጮክ ያሉ ድምፆች ትእዛዝ ሲያስተላልፉ ይሰማል። ደግሞ ያጨበጭባሉ። ደግሞ አንዴ ሆ ብለው የደስታ ጩኸት ይጮሃሉ። እናቴ እሮጣ መጥታ ከሽቦ አልጋው ስር እንድንገባ ታደርገናለች።

«ምንም ቢፈጠር እንዳትወጡ! ምንም ብትፈሩ ድምፅ እንዳታሰሙ!» እያለችን መሬቱ ላይ በደረቷ ተደፍታ እያየችን እጇ ይንቀጠቀጣል። ኪዳን ማልቀስ ጀምሯል። ጆሮዎቹን በእጄ ደፍኜ ይዤለት እሹሩሩ እንደማለት እየወዘወዝኩት ወደራሴ አጣብቄ ያዝኩት። ከውጪ የሚሰማው ሁከት መስኮታችን ጋር ደረሰ። እናቴ የመላእክትን ሁሉ ስም በሹክሹክታ እየጠራች ትፀልያለች። አባቴ እኛ ወዳለንበት ብቅ ብሎ

«አንቺም ከእነርሱ ጋር ተሸሸጊ! እነርሱ የሚፈልጉት እኔን ነው!» አላት በትእዛዝ

«ያንተ ሚስትኮ ነኝ አይምሩኝም! እኔን ሲፈልጉ ልጆቼን ካገኟቸው ይገድሉብኛል። እኔን ካገኙኝ ግን ልጆቼን አይፈልጓቸውም በፍፁም አልሸሸግም! የመጣ ይምጣ!» አለች እንጂ ሰውነቷ እየራደ ነው። ላቤ ከጀርባዬ ወደቂጤ ሲወርድ ይሰማኛል። የልቤ ትርታ ሁከተኞቹ ድረስ የሚሰማ ነው የሚመስለው። ብዙም አልቆየም! ድብልቅልቅ ያለ ጩኸት ፣ የበሩ መገንጠል፣ ተኩስ ድብልቅልቁ ወጣ። ሽንቴን እላዬ ላይ ለቅቄ እንዲያ ሰውነቴ የእኔ እስከማይመስለኝ በድኖብኝ ኪዳንን አልለቀቅኩትም። ድንጋጤው በዝቶበት ነው መሰለኝ ትንፋሽ እንደሌለው ሰው ዝም አለ። እናቴ ከአልጋው አጠገብ ተነስታለች ግን አትታየኝም። ፍርሃቴ ሽባ ስላደረገኝ የመነቃነቅም ድፍረቱ አልነበረኝም። ሳሎኑ ውስጥ የተፈጠረው ምን እንደሆነ ባላውቅም ድብልቅልቁ የወጣ ትዕይንት እንደሆነ ከድምፆቹ ያስታውቃል። ከሳሎን ድምፁ እየቀለለ የተወሰኑ ሰዎች ድምፅ ብቻ መሰማት ሲጀምር የእናቴ እሪታ ተከተለ። ነፍስ ከስጋዬ የተላቀቀች መሰለኝ። የሞት ሞቴን ለማየት ስሞክር መኝታ ቤቱ ውስጥ ማንም የለም።

«ሚስትና መሬቴን አለ ይሄ እንከፍ?» የሚል ድምፅ ለመኝታ ቤቱ ቀርቦ ተሰማኝ። ቁጥራቸውን መገመት የሚቸግረኝ ሌሎች ሳቅ ተከተለ። እናቴ ትለምናቸዋለች። የምትለምንበት ድምፅ ሆዴን ረበሸው። መሸነፍ፣ ተስፋ መቁረጥ፣ ረዳት ማጣት…….. ሆድ የሚደበላልቅ ልመና ነው። የእናቴ ልመና ፍርሃቴን አስዋጠኝ። ምን ሊፈጠር እንደሚችል የማስብበት የብስለት ልክም አልነበረኝም ይሆናል። ኪዳንን ከአልጋው ስር ወደየትም ንቅንቅ እንዳይል አስጠንቅቄው በቀስታ እየተንፏቀቅኩ ገርበብ ያለው የመኝታ ቤት በርጋ ደረስኩ። እግሬ የቆመበት ተተክሎ ቀረ። ልሳኔም የተቆለፈ መሰለኝ። ከእናቴ ጋር ተያየን። መሬቱ ላይ በጀርባዋ ወድቃ የለበሰችው ሻማ ቀሚስ እስከደረቷ ተገልቦ አንደኛው ካኪ የለበሰ ሰውዬ በማሸነፍ ስሜት ቀበቶው ተፈትቶ ወደታች ዝቅ ባለ ሱሪው ቂጡ እየታየ እላይዋ ላይ ይፈነጫል። ሌላኛው ደግሞ የመሳሪያውን አፍ ወደ እርሷ አዙሮ ነውር እያየ ሳይሆን ትክክል ነገር ዓይኑ ስር እየሆነ ይመስል እየገለፈጠ ያያቸዋል። ፊታቸው ከእኔ በተቃራኒ አቅጣጫ ስለሆነ አያዩኝም። ሌላ ማንም የለም ሳሎኑ ውስጥ። አባቴ የት ሄዶ ነው እሷ የሚደርስላት አጥታ የተዋረደችው? አትታገልም! አትንቀሳቀስም! አፉ ብቻ ነበር የሚለምነው። እኔን ስታይ እሱንም ተወችው። በሚያሳዝን አስተያየት አየችኝ። ልመና ያለበት አስተያየት። እንዳያት አልፈለገችም! ልመናዋ ዞር እንድልላት ነው።  ይሄኔ ኪዳን ከየት መጣ ሳልለው አጠገቤ ደረሰ። እየሆነ ያለውን እንዳያይ አይኑን ከደንኩት። ይሄኔ ሌላ አንድ ሰው ከውጪ ገባ። ቀና ቢል ስለሚያየኝ ኪዳንን ይዤ በበሩ ተከልዬ ማጮለቅ ቀጠልኩ። ሰውየው ሲገባ
እናቴ ያቆመችውን ልመና በለቅሶ ታጅባ ቀጠለች። የሰማት አይመስልም። ቢሰማትም ግድ አልሰጠውም። ይልቅ እንደመቆጣት እያለ

« ስንት ነገር እያለብን አንተ እዚህ ወገብህን ታላቅቃለህ? ተነስ ወደዚያ!» ብሎ አምባረቀ። አለቃቸው ነገር ይመስላል።

መሳሪያውን ይዞ የቆመው ሰውዬ «መሬቱን ወስደንበታል። ሚስቱንም እንቅመስለት ብለንኮ ነው!» ብሎ አስቀያሚ ሳቅ እየሳቀ ከእናቴ ላይ መነሳት ሲጀምር ሰውየውን በልቤ አመስግኜ ሳልጨርስ እሱም የአጋንንት ሳቅ የመሰለ ቃጭል ማስካካት አስካክቶ
«እንዲያ ነው …..» ብሎ ሱሪውን መፍታት ሲጀምር ከእኔ የሚበልጥ እልህ እና መጠቃት ሰውነቴ ውስጥ ነደደ። ወዲያው ከውጪ የሆነ ሰው ተጣራ

«ሙሉሰው? ሙሉሰው?» ይሄኔ ሊፈታ የጀመረውን ሱሪ ወደቦታው እየመለሰ በተሸከመው መሳሪያ እነርሱም እንዲወጡ ምልክት አሳይቷቸው ወጣ። መሳሪያ ይዞ በመቆም ሲያጅብ የነበረው ሰውዬ ወዲያው ተከተለው። እናቴ ላይ ሆኖ ሲያሰቃያት የነበረው ግን ቆሞ አዘቅዝቆ እያያት በፀያፍ ንግግር ይዘልፋት ጀመር። እያየኋት እንደሆነ አውቃለች። ፊቷን ወደበሩ አዙራ በስቃይ ታያለች። ከየት በመጣ ጉልበቴ እንደሆነ አላውቅም ኪዳንን ሽክም አድርጌ አልጋው ላይ ወሰድኩት እና በጩኸት እኔ እስክመለስ ንቅንቅ እንዳይል አስጠነቀቅኩት። እየተንሰቀሰቀ በጭንቅላቱ እሺ አለኝ። አልጋው አጠገብ የተቀመጠውን ሳጥን ከፍቼ ከሳጥን ውስጥ አነስ ያለች ቦርሳ አነሳሁ። ጠባብ ዚፕ ኪሱ ውስጥ ያለ ቁልፍ ወስጄ አልጋው እራስጌጋ ያለውን መሳቢያ ከፈትኩ። ከፍቼው ውስጡ ያለውን ሽጉጥ ሳየው ተርበተበትኩ። በሚንቀጠቀጥ እጄ ወጥተው ተበትነው የተቀመጡ ቀለሃዎቹን ሰካክቼ ወደሳሎን ሄድኩ። አንስቼ ሊወጣ የነበረው ሰውዬ ላይ ቀስሬ ስጠጋ እናቴ ከመሬት ብድግ አለች። አልተኮስኩም። ልተኩስ የነበረ ይመስለኛል ግን እጄ እየተንቀጠቀ ያቃተኝ። ሰውየው መርበትበቴን እና ህፃንነቴን አይቶ መሰለኝ ምንም ሳይመስለው በንቀት ወደእኔ ሲመጣ እናቴ ከለለችኝ። ግንድ በሚያክል እጁ ሲገፈትራት ተንገዳግዳ ወደቀች። እጄ መንቀጥቀጡን አቁሞልኝ ልስብ ስል የወደቀችው እናቴ ከየት እንዳገኘችው ያላየሁትን የቡና ዘነዘና አንስታ ጭንቅላቱን ከኋላ መታችው። ሰውየው ተገንድሶ ደሙ እየተንዠቀዠቀ እሱን ዘወር ብላ ሳታይ ዘላ የያዝኩትን ሽጉጥ እየቀማችኝ።

«ለእድሜ ልክ የሚበቃሽን ክፋት አይተሻል። ደግሞ ነፍስ አጥፍተሽ ስትቃዢ ልትኖሪ?» ያለችው ለእራሷ እንጂ ለእኔ አይመስልም። የተቀበለችኝን ሽጉጥ ይዛ የተገነደሰው ሰውዬ አጠገብ ዘፍ አለች። ደንዝዛ በድኗ እየተንቀሳቀሰ ነው የሚመስለው። ሰውየው ደሙ መስመር እየሰራ ወደበሩ ይፈሳል። አይንቀሳቀስም። እሮጬ ወደ ውጪ የወጣሁት አባቴን ፍለጋ መሰለኝ። መሬቱ ላይ ተዘርሮ ያገኘሁት።

እናቴን የአባቴ ሬሳ ላይ ትቻት የፈረጠጥኩት <እንዳትንቀሳቀስ> ያልኩት ኪዳን ፈርቶ ወደሳሎን ቢመጣ የወደቀውን ሰውዬ አይቶ ይደነግጣል ብዬ ነው። ካስቀመጥኩት ቦታ አልተነሳም። የሄድኩት እሱን ልጠብቀው ነበር። አልጋው ላይ አስጨንቄ አቅፌው ስወዘወዝ ምን ያህል ደቂቃዎች እንዳለፉ አላውቅም። ብቻ ወተት እንደሚንጥ ሰው ከፊት ወደኋላ ስናጥ የእናቴ ወንድም እያለቀሰ ገብቶ ኪዳንን ከጀርባ እኔን ከፊት አፋፍሶ ተሸክሞን ወጣ  ……… እዚህ ድረስ ያለው ምስል ምንም ብዥ ሳይል ነው ያስታወስኩት የሚቀጥለው ግን ብዥታ አለው አጎቴ እንደተሸከመን «ወየው ወንድሜን!» እያለ ድምፅ አውጥቶ እያለቀሰ የሆነ መንገድ የሄድን ይመስለኛል። ላስታውሰው ስሞክር ይጠፋብኛል።

እዛው የመኝታ ቤት ውስጥ ቆሻሻ ተሞልቶ የተቀመጠ ማዳበሪያ ላይ ጭብጥ ብዬ ተቀምጫለሁ።

«እያስጨነቅሽኝ እኮ ነው። ምንድነው ያስታወስሽው? ሰውነትሽኮ ያንቺ አይደለም!» ይለኛል ጎንጥ። ከደቂቃዎች በኋላ እሩጫ እና እርምጃ እየደባለቅኩ እናቴጋ ደረስኩ እና ተጠመጠምኩባት። ገባት! እሪሪሪ ብላ ማልቀስ ጀመረች። ስላስታወስኩ  «ምንአልኩህ አምላኬ? ለልጄ አዲስ ህይወት ሰጠህልኝ ብዬ አመስግኜ ሳልጨርስ?» እያለች አምላኳን መውቀስ ጀመረች። የሚሰማኝን ስሜት መለየት ከበደኝ። ከነበሩኝ ጥሩ ቀኖች ተለይቶ አስፈሪ ቅዠት የመሰለ የህይወቴን ክስተት ማስታወስ ሊያሳብደኝ አልነበር የሚገባው? ቁጣ፤ ንዴት፣ ጥላቻ ፣ ፍርሃት ፣ ሀዘን ……. አልነበር ሊሰማኝ የሚገባው? የሚሰማኝ የሆነ ቅዝቅዝ ያለ ፀጥተኛ ስሜት ነው።

«ከእናቶች ሁሉ በላይ እናት ነሽ!!» አልኳት እናቴን እንዳቀፍኳት ብዙ ከቆየሁ በኋላ። አመሻሽ ለእራት ስንሰበሰብ ማስታወስ የቻልኩት ያቺን ቀን ብቻ እንደሆነ ነገርኳቸው። የነገርኳቸው የሆነ አስደንጋጭ ነገር ይመስል ገበታውን የከበበው ሁሉ ረጭ አለ። አጎቴ ሊጎርስ የጠቀለለውን እንጀራ የመወርወር ያህል ትሪው ላይ ጣለው።

«መቼም ከዚህ የባሰ የስቃይ ቀን አለ አትሉኝማ? ምንድነው?» ብዬ ስጮህ

«እንደዛ አይደለም። ለሁላችንም ከባድ የጨለማ ቀን እሱ ነበር። እንደው …… » እያለ ፊደሎቹን አፉ ውስጥ ያውደለድላቸዋል። ከብዙ ንትርክ በኋላ የተፈጠረውን ነገሩኝ።

እንደዚያ ደም ያቃባቸው ፀብ ለዘመናት የከረመ የጎሳ ፀብ ነበር። ለዘመናት ያንተ ጎሳ ገላመጠኝ ፣ ያንተ ጎሳ ድንበሬን አልፎ ሽንቱን ሸና ዓይነት ገለባ ሰበብ እየመዘዙ ሲጣሉ ነበር የኖሩት። የአባቴ ዘመን ከፀቡ ሁሉ የከፋው ነበር። ፀቡ ፖለቲካዊ ይዘት እንዲኖረው ተደረገ። የእነዛ ወገን በቁጥር የምንበልጠው እኛ ብንሆንም ሰፊ ለም መሬት የያዙት እነዛ (የአባቴ ወገኖች) በመሆናቸው የመሬት ይገባኛል ነጠላ ጥያቄ ይዞ ነበር የተነሳው። ሲቀጥል ገበያውን የኛ ሰዎች ይቆጣጠሩት ፣ ሲቀጣጠል በማእከላዊ ደረጃ በአብላጫው ስልጣን ላይ ያሉት  የአባቴ ወገኖች መሆናቸው ሌላ ዘመናዊ የመሰለ የፀብ ድፍድፍ ጋገረ። ፀቡ በከረረ ቁጥር ከላይ ወታደር ይመጣል። ለቀናት ጋብ ይላል። ደግሞ ተመልሶ ይጋጋላል። አባቴ ነው አሉ የእኛን ጎሳ የሚመራው። አጓጉል ጉልበት መለካካት። የእኔ እበልጣለሁ ፉክክሩ ጦዞ ከተማ እስከማቃጠል ዘለቀ። የመጨረሻው ፀባቸው አባቴ ህይወቱን የገበረበት ነው። ራሴን እስክፈራው ድረስ ሰውነቴ ውስጥ የሞቀ ደም እንዲሮጥ ያደረገው መጨረሻው ነው። የእነዛ ጎሳዎች ሽማግሌ ላኩ። ከዚህም ወገን ሽማግሌ ተቀመጠ። ታረቁ!!

የተበደልኩ ዓይነት ስሜት ተሰማኝ። እነርሱ ተጣሉ ከዛ ታረቁ። እኔስ በአስራ ሶስት ዓመቴ አባቴ ሲሞት እናቴ ስትደፈር ያየሁት እኔስ? እኔን ይቅርታ ጠይቀውኛል? እናቴስ? በአንድ ቀን ባሏንም ክብሯንም ያጣችው እናቴስ? ስትደፈር ያየቻትን ልጇን ዓይን እያዩ መኖር ስቃይ ሆኖባት መኖሪያዋን ጥላ የጠፋችው እናቴስ? በቃ! እነሱ እንደቀልድ ታረቁ? ማንም ላጠፋው ቅጣቱን ሳይቀበል ታረቁ! በሰላም ኖሩ! ተጋቡ! ተዋለዱ! የሚባለው የሰው ነፍስ እንዴት ሲናቅ ነው? እኔ እና የዛን ቀን የህይወት ሚዛናችንን የሳትን እኩዮቼስ? ንዴቴ ይንቀለቀል ጀመር። ከነቃሁ ጀምሮ ይሄን ስሜት አላውቀውም! እናቴ ትለምነኝ ጀመር። አጎቴ የፈራው ነገር የደረሰ ዓይነት ተሳቆ ሲያየኝ ቆይቶ ያኔም ልክ እነሱ ታረቁ ተብሎ በሰላም መኖር ሲጀምሩ እንዲህ መሆኔን እና ከዛ በኋላ ህፃንዋ ሜላት ድራሽዋ ጠፍቶ አስፈሪዋ ሜላት ማደግ መጀመሯን ነገረኝ።

          ………………. አልጨረስንም ………..

@wegoch
@wegoch
@paappii
" አንዳንድ ሰው የኔ ብለን ተንከባክበን ምቾት ስንፈጥርለት በምቾት ሰበብ ሌላ ተድላ ለማግኘት ወደ ሌላ ሚያማትር የፍቅር ወንፊት ይሆናል ። "

( ካሊድ አቅሉ )


አስሬ ሰአቴን አያለው በየፌርማታው የሚቆመው ታክሲ ከኔ አርፍዶ መውጣት ጋር ተደምሮ የንዴት ቃሎችን በየሰከንዱ ለራሴ አሰማለው ።  ሳርቤት ጋር አንዲት ቀጠን ያለች ልጅ ወራጅ አለችና ለመውረድ ወደ በሩ ተጠጋች ። መኪናው ቦታ ለመያዝ ፍጥነቱን ሲቀንስ  ጥንዶቹ ለመግባት ወደ በሩ ተጠጉ ።

ልጅትዋ በፍጥነት ወርዳ እረዳቱ   "ሜክሲኮ ናቹ " አለ በስስት የሚተያዩትን ፍቅረኛሞች በጎላ ድምፅ ጠየቀ ። ተጠምጥሞ አንገትዋን ከሳማት ብሃላ "ቤት ስትገቢ ደውይልኝ " ብሎ አፈገፈገ በአካልዋ እሺታዋን ገልፃ ከሃላ መቀመጫ አራተኛ ሆና ተቀላቀለችን ።


ታክሲው ከቅድሙ በተሻለ ፍጥነት ይሄዳል እፎይታ ተሰምቶኝ መድረሴን እያሰብኩ ስንጓዝ አጠገቤ የወንድና የሴት ምልልስ ጆሮዬ ገባ ። 

" ይሄን የሚያህል ፀጉር ለብቻ መያዝ አያስቀጣም ?" ይላል አሁን የተሳፈረችዋን ጉብል

"ሃሃሃ ምን አረግሽ ተብዬ ፈጣሪ አይደል እንዴ የሰጠኝ " አለች አሁን በፍቅረኛዋ የተሸኘችው ወጣት ።

" ወጪውስ እራሱ መከራ እኮ ነው በየሳምንቱ እሱን መሰራት " አለ በተቀደደው ቦይ መፍሰስ የፈለገው ቀጠን እረዘም ያለው ጀንጃኝ

" የምር አስቤው አላውቅም ግን እንዳልከው ከባድ ነው "  አለች የልጁ አቀራረብ እንደመሰጣት በሚያሳይ የሰውነት ንግግር  ።

ፊቴን ወደ መስኮቱ ባዞርም ሁለመናዬ በጆሮዬ መሪነት ከነሱ ዘንድ ነው ። ፊቴን ትንሽ መለስ አድርጌ ልጅትዋን ገረፍ አረኳት ባይኔ ፁጉርዋ ትከሻዬ ላይ ተዘርርዋል ።  " አንተስ አውራት እንጂ ምን ትጠብቃለህ😊 "  ሚለኝ መሰለኝ . . .

መኪናው ዳገቱን ተያይዞታል እነሱም የጋለ ወሬ ላይ ናቸው ። አይ ምስኪኑ  አፍቃሪ የሚወዳትን ልጅ ሸኝቶ መመለሱ ነው ልብዋ አብሮ እንደተጓዘ አውቆ በሆነ አልኩኝ በልቤ ሜክሲኮ መውረጃችንን ጥግ ለመያዝ መኪናው ቦታ ሲፈልግ ስልኩን ወጣ አረገና ሳቅ እያለ
" እስኪ ቁጥርሽን ንገሪኝ ልያዘው"  አለ እንደማይከለከል በተማመነ ቅላፄ

" እእ ይሻላል እሺ 091672 . . .   "
መጨረሻው ነው ብሎ እረዳቱ በሩን ከፈተው ተስፈንጥሬ ወጥቼ ጉዞዬን ቀጠልኩኝ .     .     .    .

" አንዳንድ ሰው የኔ ብለን ተንከባክበን ምቾት ስንፈጥርለት በምቾት ሰበብ ሌላ ተድላ ለማግኘት ወደ ሌላ ሚያማትር የፍቅር ወንፊት ይሆናል ። "

ስልኬን ወጣ አድርጌ ደወልኩና " ማኪ ደርሻለው ይሄው  "  አልኳት እርምጃዬን ጨምሬ ።

ይሄኔ ማኪም ታክሲ ውስጥ ለአንዱ ምላሳም ቁጥርዋን ሰታ መታ ይሆናል እኮ አልኩኝ ፈገግታ ባለው ከራሴ ጋር ምልልስ።

@kalidakelu

@wegoch
@wegoch
@paappii
#የመኖር አካፋይ ፣ የመ ፤ ሞ ፣ ት ሲሶ ፣ መንገድ መሃል ………… (ክፍል አስራ ሶስት)
(ሜሪ ፈለቀ)

«አባቴም እንደእነሱ መጥፎ ሰው የነበረ ቢሆንስ? የሆነችን ልጅ አባት የገደለ ቢሆንስ? የሆነኛው ሰው ሚስት ስትደፈር ቆሞ አይቶ ቢሆንስ? መቼም ከተማቸውን በእሳት ሊለኩስ  ሲሄድ <የእግዜር እንግዳ> ብለው አልተቀበሉትም! ተታኩሰዋል አይደል? በተኩሱ መሃል የገደላቸው ሰዎች እነሱም የሆነች ህፃን አባት ፣ የፀቡ ግብም አላማም ያልገባት የሆነች ምስኪን ሴት ባል ይሆናሉ።» አልኳት እናቴን ከቀናት ድንዝዝና እና ማሰላሰል በኋላ የሆነ ቀን። ከአሁን አሁን ትጎፈላለች ብሎ በዓነቁረኛ የሚከታተለኝ አጎቴ ዝግንን እያለው

«ውይ በስመአብ!!! እውነትም አባትሽን ዘንግተሽዋል። ምነው ልጄ? እሱ እንደው አንዳንዴ አጓጉል ጀብደኝነቱ ከልክ ያልፋል እንጂ እንዴት ያለ ለሰው አዛኝ እና ደግ ሰው መሰለሽ? አባትሽን መጥፎ ሰው? ኸረ ተይ መንደሬው እንዳይሰማሽ? የሀገሬው ሁሉ አጉራሽ አልባሽ ነበር።» አለኝ።

«ለወገኑ ነዋ! በመሰረቱ ሁለቱም ወገኖች ለየራሳቸው ወገን መከታ ለመሆን አይደል የሌላውን ወገን ሲያጠቁ የኖሩት። እነዛም ወገኖቻቸው የሚመሰክሩላቸው ደግ ሊሆኑ ይችሉ ይሆናልኮ!! ምናልባትም <ማ? የእኔ አባት? እንኳን በሰው በዝንብ ላይ እጁን አያነሳም> የሚሉላቸው ልጆች ይኖሯቸው ይሆናል። ሁሉም ሰው በራሱ እስካልደረሰ በስተቀር ምክንያታዊ እና ልክ ነው። በራሱ ሲደርስ ነው ሚዛናዊነቱን የሚያጣው። ለምሳሌ የእኛዎቹ ተደፈርን ብለው ሲያስቡ ከተማቸው ድረስ ሄደው አጥቅተው ሲመለሱ፣ የሰራነው ልክ አይደለም ብለው ለአንዴ እንኳን ተፀጽተዋል? ምናልባትም ልክ አይደላችሁም ያለ አዋቂ ይኖር ይሆን? እስቲ ለትውልድ የሚሻገር ቁርሾ ከማኖራችን በፊት ሳንጫረስ መፍትሄ እንፈልግ ያለ ይኖር ይሆን? እነዛ ተመሳሳዩን ሲያደርጉ ህመማችንን የምናየው ከእኛ ወገን ስለሆነ አውሬነታቸው እና እንስሳነታቸው ነው የታየን። » አልኩኝ። እናቴ ፈገግ አለች።

«ምነው?» አልኳት

«ኸረ ምንም አለች!» አሁንም ድካም በተጫነው ፊቷ ላይ ፈገግታ እየነገሰ።

«እንዴ አስካል እንዲህማ ፊት አትስጫት!! የአባቷንም ነፍስ መና ማድረግ ነው። ሰው ነውና ምኑንም ያህል ጥፋት ባይጠፋው፣ ህይወቱን ጭምር የገበረው ለዝህች መንደር ነው። ያ መረሳት የለበትም!!» አለ የእውነቱን እየተቆጣ!! ምናልባት ሰው የመሆን የአፈር ልውሳችን ውስጥ ያለ ነገር ይሆን? የእኛ ወገን ቢያጠፋም ( ወይም እናውቃለን አጥፍቷል) ቢሆንም የእኛ ወገን ስለሆነ ጥፋቱ እናኮስስለታለን። ከዛሳ? ከዛማ የእሱን ሀጢያት ደርምሰን የኛ ወገን ላልሆነ እንደርባለን። ከዛማ በንፅፅሮሽ የኛ ወገን ለመልዓክ የቀረበ ፃድቅ አድርገን እናርፈዋለን!! አጎቴ ሰሞኑን ከሚነግረኝ የመንደራችን ታሪክ በብዙ የተረዳሁት ያንን ነው።

«አዛኝቷን ነው የምልሽ እንዲህ ተልፈስፍሰሽስ ከማይ ከነማስጨነቅሽ የድሮዋ ሜላት ትምጣብኝ!!» ሲለኝ እናቴ በተሟጠጠ አቅሟ ልትነሳ ሁላ ቃጣት። «እረፍ ብያለሁ!» ብላ ጮኸች ፣ አጎቴ አፍንጫውን እየነፋ ወጣ!

ማለቂያ የሌለው የጥያቄ ጎርፍ ሳንፎለፉልለት ቆይቼ አጎቴ ከነገረኝ ገጣጥሜ የገባኝ እድገቴ እንዲህ ነው። ከዛን የመዓት ቀን በኋላ እናቴ የሆነችውን ለወንድሟ ነግራው አባቴ እንኳን ሳይቀበር እኛን ትታ ተሰደደች። አጎቴ ልጅም ሚስትም ያልነበረው ላጤ ስለነበር ምድር ዞሮበት እንደነበር ነገረኝ። አባቴንና በዛን ቀን በሞት ያጣናቸውን ወገኖቻችንን ቀብረን መንደሬው ማቁን እንደለበሰ ከረመ። ከዛን ቀን በኋላ ቀሚስ ጠላሁ። ስለብሳቸው ቀሚስ የሚያካክሉትን የአባቴን አላባሾች መልበስ ጀመርኩ። ቁጭ ብዬ የአባቴን ሱሪዎች ለእኔ እንዲሆኑ ቆርጬ እና ሰፍቼ መልበስ ጀመርኩ። አንድ እለት ለበዓል በጌጥ ያሸበረቀ ቀሚስ ገዝቶልኝ መጣ።

«እኔ ይሄን አልለብስም! ሴት መሆን አልፈልግም።» አልኩ። ምናልባት በሴትነት ውስጥ የእናቴን ስቃይ በወንድነት ውስጥ የአባቴን ጀግንነት ነድፌ ይሆናል እናቴን ከመሆን አባቴን ሆኜ ሞትን እንኳን ለመግጠም ራሴን መሞረድ የጀመርኩት። ሴት ሊያደርጉኝ የሚችሉ ድርጊቶችን ማጀትን ጀምሮ ሸሸሁ። አጎቴ ትምህርት ቤት ከኪዳን ጋር ቢልከንም ትምህርቴን አልቀጥልም ብዬ አሻፈረኝ አልኩ። ትኩረቴ ሁሉን ሁሉ ጉልበት እና ጡንቻ ማካበት ላይ አደረግኩ። ውሎዬ ከጎረምሳ ጋር ኳስ መራገጥ ፣ ጅራፍ ማጮህ ፣ እንደእኩዮቼ ወንዶች ጡንቻ መለካካት ፣ ከሰፈሩ ፈልፈላ ጋር ሜዳ ላይ ማን ስንት ፑሽ አፕ ይሰራል አፈሩን ስንልስ መዋል ፣ የሰፈሩን አህያና ውርንጭላ ሁላ መጋለብ ….. ሆነ። ይሄን ሲነግረኝ አጎቴ ፈገግ ብሎ

«በአዛኝቷ! እንደው ሞገደኛ ነበርሽኮ!! ቆሜ ካልሸናሁ ብለሽ ጉድ አፍልተሽ ነበርኮ!» ብሎ ክትክት ብሎ ሳቀ። ቆሞ እንደወንድ የመሽናት ሀሳቡ አብሬው እንድስቅ አደረገኝ።

በየቀኑ የምደባደበው ሰው ፈልጌ ተደባድቤ እገባለሁ። በምለብሰው የአባቴ ልብስ ሲስቁብኝ እጣላለሁ።  ሁሌም አሽተው አሰባብጠው ይለቁኛል በነገታው አሁንም ነገር ፈልጌ እወቀጣለሁ። በተለይ ትልቁ ገበያ ስንሄድ ከጠላቶቻችን ወገን የሆነ ሰው ከገጠመኝ ፍፃሜዬ ደማምቶ መምጣት ቢሆንም ነገር ከመፈለግ አልቦዝንም። በዱላ ብዛት የትኛውም ድብደባ ቅም የማይለኝ ደነዝ ሆንኩ። ቁጥር አልባ ቡጢ እና ሽመል ከፈጀሁ በኋላ አንድ ቀን አሸንፌ መጣሁ። ውጤቱ ማሸነፍ ሆነ እንጂ አፍንጫ እና ጉንጬ እስኪደባለቅ ተወግሬ ነበር።

«በጭራሽ አልገባኝም ነበር። <እንደው ከዚህ ሁሉ ምናለ ድብድቡ ቢቀር? መቼም አንድ ቀን አንዱ አጉል ቡጢ የሰነዘረብሽ እንደው 32 ጥርስሽን በእጅሽ ይዘሻት መምጣትሽ ነው። እንደው ምን ባደርግሽ ይሻለኛል?> ስልሽ <ተደባድቤ ጉልበቴን ካልፈተንኩ እንደምችላቸው በምን አውቃለሁ? ድንገት ብንገጣጠም ሽመል ወይ ኮረት ፍለጋ ልዟዟር ነው?> ብለሽ መለሽልኝ። ለካንስ አጅሪት አባትሽ ከሞተ ቀን ጀምሮ የአባትሽን ገዳዮች እንዴት እንደምትበቀዪ ስታሰዪ ነው ውሎ አዳርሽ።» አለ በሰዓቱ ስላልተረዳኝ እየከፋው።

ወንድ የመሆን ትጋቴን መቼም እንደማላቆም ሲያውቅ ፣ በራሴ ልጅነት ውስጥ መኖሬን አቁሜ በአባት እና በእናቴ በደል ውስጥ እየዋኘሁ እንደሆነ ሲረዳ ለምኜው እንቢ ብሎኝ የነበረውን የሆነ ከከተማ የመጣ ልጅ የእድር ቤቱ አዳርሽ ውስጥ የሚያስተምርበት ካራቴ ቤት በ15 ዓመቴ አስመዘገበኝ። እንደዛ ቀን የተደሰትኩበትን ቀን አይቶ እንደማያውቅ ነገረኝ። ኪዳንን ትምህርት ቤት አድርሼ የምመልሰው እኔ ነበርኩ። በኮባ የተሰራ ጠብመንጃ ትከሻዬ ላይ አንግቼ ፣ እንጨት ፈቅፍቄ የሰራሁትን የእንጨት ሽጉጥ ወገቤ ላይ ሽጬ …….. ከፍተኛ ጥበቃ እያደረግኩለት እንደሆነ አስመስላለሁ። ሰውነቴ እየፈረጠመ …..  ልቤም በማንአለብኝነት እያበጠ ….. <ፀብ ሆይ ወዴት ነህ?> ብዬ እያልኩ ማሸበር ስጀምር ….. የሰፈሩ ሰው ወንድ ልጆቻቸውን እንኳን <እሷ የሴት ተፈጥሮ አልፈጠረባትም። ወንዳወንድ ናት ከእርሷ ጋር እንዳትገጥሙ> እያሉ መከልከል ሲጀምሩ ……. የጠገበ ልቤን የሚወጥር ሙገሳ ጆሮዬ ገባ። ኪዳን ከልጆች ጋር ተጣልቶ ሲያለቅስ የሰፈር ማቴ ለእኔ ሊያሳብቅ ሲሮጥ አንድ አልፎ ሂያጅ
«አሁን አንተ የአባትህ ልጅ ነህ? ያ አባትህ ቢያይህ እንዴት ይክፉው? ወንድ አይደለህ እንዴ ምን ያነፋርቅሃል? ልጅማ ወልዷል የሴት ወንድ፣ የአባቷ ልጅስ እሷ ናት።» ያለውን ኪዳን ሲነግረኝ ጥጋቤ አናቴ ላይ ወጥቶ አጎቴን አሳር አሳየሁት። እየሰነባበተ የሆነ ቀን አንድ የኛ መንደር ልጅ እና የአባቴ ገዳዮች ወገን ልጅ ገበያ መሃል በተነሳ የግል ፀብ ሲያያዙ መሃል ጥልቅ ብዬ  <እጇ ላይ መሞቱ ነው> ብሎ ሰው ጠልቃ እስኪገባ ድረስ በጥላቻዬ ልክ ቀጠቀጥኩት። ከአጎቴ ውጪ ማንም የከፋው አልነበረም። ይባሱኑ መንደርተኛው «ቁርጥ አባቷን፣ የአባቷ ቢጤ አመፀኛ ፣ ይህቺማ የመንደሩ መድሃኒት ናት ፣ ቱ በሉ የአባቷን ደም ትመልሳለች። » እያለ ልክ እንዳደረግኩ ዓይነት በየቡናው እና ጠላ ቤቱ በወሬ ሲቀባበለኝ ባሰብኝ።

«እንደአባቴ ጫካ ካልገባሁ አልሽ!» ብሎ ሳቀ አሁንም ይሄን ሲያስታውስ «አንድ ቀን እርሻ ውዬ ስመለስ አጅሪት ለካ ያንቺ ቢጤ ወጠጤ ጎረምሶች ሰብስበሽ ሄደን ጠላቶቻችንን ካልገጠምን ብለሽ ልባቸውን ዝቅ አድርገሽ ልከሻቸው፣ ይሄ ውሻ ቢያሯሩጠው ሱሪው ላይ የሚንበጫበጭ ማቲ ሁላ <መሸፈቴ ስለሆነ ስንቅ አዘጋጁልኝ> ብሎ እናቱን ሲያውክ የሰፈሩ እናቶች ተሰብስበው ጠበቁኝ። <ይህችን ልጅ አደብ አስይዝልን! የልጆቻችንን ልብ ወደ ጫካ እያሸፈተች ነው።> ቢሉኝ እንደው ሳቄን መቆጣጠር ተሳነኝ ስልሽ! (አሁንም ከት ብሎ እየሳቀ) በሽመል ጦርነት ልትገጥሚ መሆኑ ነውኮ!!» እንባው እስኪወርድ ሳቀ። አጎቴ ሲያወራው ልጅነቴን ከመራራነቱ ይልቅ የተዋዛ ጨፍጋጋ ያደርገዋል። እያንዳንዷን ክስተት በቅደም ተከተል ሳይስት ሲያወራኝ ያኔ ተሰምቶኝ የነረውን ነገር ባላውቅም ዛሬ ላይ ግን ስሰማት ሜላት ምሬት ብቻ አልነበረችም።

17 ዓመት ሲሆነኝ ከአባቴ ሞት በኋላ ረጭ ብሎ የነበረው የሁለቱ ወገኖች ቁርሾ በሽመል የማይመከት የፀብ ጉርምርምታ ሆኖ ተጀመረ። ወጣቶቹ መሳሪያ ያለው በመሳሪያ የሌለው በጦር እና በጎራዴ እንዴት ጠላቶቻቸውን እንደሚመክቱ ሲመካከሩ አንደኛ የነገር ጠንሳሽ ሆኜ ተገኘው። ለካንስ ፀብ ፈጥሬ ቁምነገራቸውን ሳይቋጩ ስለምረብሻቸው ፈርተው ዝም አሉኝ እንጂ ከሴት ጋር በፀብ አውድማ መሰለፍን እንደውርደት ቆጥረውት ኖሮ ለአጎቴ መጥተው ነገሩት። ብመከር ብዘከር የ<አባቴን ገዳዮች፣ የእናቴን ደፋሪዎች የማገኝበት ብቸኛ አጋጣሚዬ ይሄ ነው። ቢከለክሉኝ ራሱ ተደብቄ እከተላቸዋለሁ።> ብዬ ፈረጠምኩ። የዛን ቀን በሩን ቆልፎብኝ የእህል ማዳበሪያ ሊቀበል ደርሶ እስኪመለስ የሳንቃውን በር ገንጥዬ ወንዶቹ የሚመካከሩበት ጫካ ሄጃለሁ። አጎቴ በጥቆማ ከቦታው ሲደርስ ከወንዶቹ መሃል ቆሜ <እኔ ነኝ ያለ ወንድ እጅ በእጅ አንድ ለአንድ ይግጠመኝ። አንዳችሁ ካሸነፋችሁኝ እቀራለሁ። አልበጠብጣችሁም። ሁላችሁንም ካሸነፍኩ ግን አብሬያችሁ እሄዳለሁ።> እያልኩ የሚጣላኝ ስጋብዝ ደረሰ። አጎቴ እንዳለኝ ከሴት ጋር ተደባድበው ቢሸነፉ ቅሌት እንደሆነ ስለገባቸው ሊደባደበኝ የደፈረ የለም። <መቼም አንቺም አንዱን ከጣልሽው በኋላ ወንድ ነኝ ያለ ደፍሮ ለመውደቅ አይመጣም ብለሽ እንጂ ያን ሁሉ ወጠምሻ እንደማትጥዪው ታውቂው ነበር።> አለኝ እንደመኩራት እያደረገው።

ከዛ በኋላ በምንም ሴትነቴ እንደማይመለስ ተስፋ ቆረጠ። እኔ እንዳላገኘው ደብቆ ያስቀመጠውን የአባቴን ሽጉጥ እና ታጣቂዎች በየቤቱ እየፈተሹ ነው ተብሎ ተቆፍሮ የተቀበረ ክላሽንኮቭ ጠመንጃውን አውጥቶ ሰጠኝ። ከመንደር አርቆ ወስዶ ኢላማ ያስለምደኝ ጀመር። አባቴ ከልጅነቴም መሰረታዊ ነገሮችን ከእናቴ ደብቆ ይዞኝ እየሄደ ያሳየኝ ስለነበር ብዙ አላስለፋሁትም። በመጨረሻም የአባቴን ገዳዮች የመጨረስ ሀሳብ ብቻውን ልቤን በሀሴት ሲሞላው ነው ሽማግሌ ልከው ፀቤ ላይ ውሃ የቸለሱበት።

ከእኔ ውጪ የቀረው ወጠምሻ መሳሪያውን ለታጣቂ አስረክቦ ጦርና ጎራዴውን ቀጥቅጦ የሽንኩርት መክተፊያ ቢላ አድርጎ ለሚስት እና ለእናቱ ሰጠ። ምንም እንዳልሆነ ሁሉ ሰላማዊ ህይወት መኖር ጀመረ። ጭራሽ ገበያ መሃል ሲገናኙ ሰላምታ መለዋወጥ ጀመሩ። ሚስቶች በመሃከላቸው ያለ የትዬለሌ ኪሎሜትር ርቀት ሳያግዳቸው ሽሮ መበዳደር ጀመሩ። እንደአጎቴ እምነት ከዚህ በኋላ ሴትነቴን ብቻ ሳይሆን ሰውነቴንም በከፊል ከዳሁ። የበቀል ጥሜን ያብርድልኝ እንጂ በመንገዴ የሚመጣ ማንም ሰው ቢሆን ከማስቀየም ወደኋላ የማልል አውሬ ሆንኩ። ቁጣዬን የምገልፅበት የማውቀው ብቸኛ መንገድ ፀብ ስለነበር <የምትጣዪው ብታጪ ከቆመ ግንድ ተጣልተሽ ትገቢ ነበር። የማደርገው ጭንቅ ጥብብ አለኝ።> ነበር ያለኝ አጎቴ። ሰላሙን የተቀበለ ሁሉ አጎቴንም ጨምሮ ጠላቴ ሆነ። መራር ሆንኩ። የቀን ተቀን የሆነ ቀን እንደምገድላቸው ነበር። አጎቴ በማያውቀው ምክንያት እንደዛ ሰፈርተኛውን እያሳቀቅኩ ግን ቆየሁ። አንድ ቀን ጭንቅህ ይብዛ ሲለው አንድ ወዳጁ ቲቪ ገዝቶ ሊያሳየን ተለማምኖ ይዞኝ እስከሄደ ቀን ድረስ። ቲቪ እንግዳ የሆነበት ብዙ መንደርተኛ ሰብሰብ ብሎ እስክሪኑ ላይ ባፈጠጠበት ያ ሰውዬ …… እናቴ ስትደፈር መጥቶ አይቶ ሱሪውን ሊፈታ ብሎ ሲጠራ የወጣው ሰውዬ አመዳም ካኪውን አውልቆ በውሃ ሰማያዊ ሱፍ ንግግር ያደርጋል። ሰውየው ሚንስትር ሆኖ ተሹሞ ብልግናውን ከአንድ ከተማ ወደ ሀገር አቀፍ የማዛመት እድል ከማግኘቱ በላይ የመንደሬው ማሽቋለጥ አንድዶኝ በጠበጥኩኝ።

«ሙሉሰውን አያችሁት? አሁንማ ጆሮው ቢቆረጥ የማይሰማ ባለስልጣን ሆነ።» እየተባባሉ ከዓመታት በፊት መንደራችንን አጋይቷት ፣ ሬሳ አስታቅፎን እየፎከረ እንደሄደ ረስተውት በኩራት ያወሩለታል። ብቻዬን የተበደልኩ አድርጌ የተሰበሰበውን ሰው ተሳድቤ ወጣሁ። በሚቀጥለው ቀን ኪዳንን አስከትዬ አጎቴ በሌለበት ቀዬውንም ለቅቄ ወጣሁ።

«ከዛስ?» አልኩኝ ተመስጬ ስሰማው ቆይቼ

«ከዛማ በእጄ ያሳደግኩሽ ልጄ ወሬሽን በእሩቅ የምሰማ ባዳዬ ሆንሽ። ብፈልግ ባስፈልግ እንዳትገኚ ስለፈለግሽ አጣሁሽ። አንቺም እንደእናትሽ ላትመለሺ መሄድሽን አምኜ ተስፋ በቆረጥኩ ሰዓት አንድ ቀን መንደርተኛው ጠላ ቤት ውስጥ ጉድ ጉድ እያለ ወሬ ሲፈጭ ደረስኩ። የምሽት የቴሌቭዥን ፕሮግራም ላይ መታየትሽን <ልጅህ ዘንጣለች> ብለው ነገሩኝ። ምን ስታደርግ ታየች ብል <አታውቅም ኖሯል እንዴ የሚንስትሩ የሙሉሰው ሚስትም አይደለች? ከእርሱ ጎን ሆና ነው ባለፊልሙ የቀረፃት> ብለው መርዶዬን እንደምስራች ጋቱኝ።» ሲለኝ ጆሮዬም መሰለኝ።

«ሙሉ ሰው እናቴ……. » መጨረስ አንቆኝ ስንተባተብ

«ልትገያቸው ከመዘገብሻቸው ሰዎች መሃል ዋንኛውን ማግባትሽን ስሰማ የፍቅር እንዳልሆነ ጠርጥሬ ተከፋሁ። እንደባዳ ዜናሽን ከሰውም አይደል የምሰማው ? እንደፈራሁትም <ሚንስትሩ በገዛ ሚስታቸው በአሰቃቂ ሁኔታ ተገደሉ።> የሚለው ዜና ሀገሪቷን ይንጣት ጀመር።» ብሎ ኩርምት ብሎ ተከዘ።

እቤት ካዝና ውስጥ ያገኘሁት የጋብቻ ሰርተፊኬት ትዝ አለኝ። ሙሉሰው!! ጠላቴን ነው ያገባሁት? ምን ምክንያት ይኖረኝስ ይሆን?


   .......... አልጨረስንም ...........

@wegoch
@wegoch
@paappii
በሳቅ ድክም እያለች ድንግልናዬን የወሰደችበትን ቀን የትላንትና ያህል አስታውሰዋለሁ። ለነገሩ ልርሳውስ ቢሉ እንዴት ተብሎ ይረሳል? እሷን በሴክስ ያሳ'ኩትን ያህል እኮ ማንንም በቀልድ አስቄ አላውቅም።

ስትስቅብኝ ተናድጄ ያለኝን ወንድነት ሁሉ አሟጥጨ ታገልኳት። መፍጨርጨሬን ስታይ እንደምንም ሳቋን ለመቆጣጠር እየሞከረች <<አ...አ...አል...አልገባም'ኮ!>> አለች በተንጋለለችበት እንባዋ ኮለል ብሎ እየወረደ።
የሰማይ አምላክ ምስክሬ ነው ከዛች ቀን ውጭ በኔ ምክኒያት እንባ ወጥቷት አያውቅም። ቆንጆ ክረምት ነው ያሳለፍነው። ለቀጣዩ ክረምት ልንገናኝና የጀመርነውን ፍቅር...ጫፍ ልናደርሰው ቃል ተገባብተን ተለያዬን።
ከዛ ቡኃላ ያዬኋት አንድ ማለዳ ሳታስፈቅደኝ ቤቴ ገብታ ነው። ኢቢኤስ ቲቪ ላይ ፕሮግራም እየመራች ነበር።

እውነት ለመናገር...ፈልጋችሁ ያጣችሁትን ሰው....ችግር ሳይገጥመው...ደስተኛ ሆኖ ስታዩት...የሆነ ግራ የሚያጋባ ነገር አለው። ስትፈልጉት'ኮ <<በጤናው ባገኘሁት!>> እያላችሁ ነው ስትመኙለት የነበረው። የምርም በጤናው መሆኑን ስታውቁ ግን ግራ ያጋባል። ግራ ያጋባል ብቻ ሳይሆን ያሸብራል። ናፍቆታችሁ ወደ ንፁህ ጥላቻ ይቀዬራል። <<ደህና ከሆነ ለምን አልፈለገኝም?>> ትላላችሁ። ያንኑ ሰው በየቀኑ ቲቪ ላይ እያያችሁት እንደመኖር ያለ ደግሞ ለመልመድ የሚከብድ ህመም የለም። ምክኒያቱም ያ ሰው...ያለመፈለጋችሁ ቋሚ ምልክት ነው!

የአቢቲ ትልቁ ችግሯም ይሔ ነው። በተራዬ ልጠፋት እየፈለግኩ ልጠፋት አልችልም። ካለችበት ሁና ያለሁበት ድረስ ትመጣለች። እስመ አልቦ ነገር...ዘይሳኖ ለዚች ቢች!

በአራት አመት የምትበልጠኝ የዩንቨርስቲ ተማሪ ጋር መተኛቴ ተሰምቶኝ የማያውቅ ወንድነት እንዲሰማኝ አድርጎኝ ነበር። ጥንን ብዬ ላዩዋ ላይ ወጣሁ። ሳትኳት። ተንከትክታ ሳቀች። ስትስቅብኝ የደነገጥኩት ድንጋጤ መልሶ ዛጎሌ ውስጥ ከተተኝ። በዛው አልተወችኝም። መልሼ በራስ መተማመኔን እስካገኘው ድረስ ደጋገመችኝ።
አልጋ ላይ ስንወጣ እንደፈለገች አይደለም የምታደርገኝ...እንደፈለገች ነው የምሆንላት።
አንዳንዴ ሳስበው <<የሚያዬኝ የለም...እሱም ልጅ ነው አያውቅብኝም!!>> ብላ ኢሞሽናሊ አቢውዝ ያደረገችኝ ይመስለኛል! (እሷ አስራ ዘጠኝ...እኔ አስራ አምስት ነበርን። የመሆን ዕድል አለው።)
ታዲያ የሆነ ነገሬን ብታዛባው ነው'ጂ ለምንድን ነው ዛሬም ድረስ ሁለት ወልደው የፈቱ ሴቶች ሳይ ራሴን መቆጣጠር እስኪያቅተኝ አምሮት የሚያናውዘኝ? ለምንድን ነው እኩያዎቼ የሚከብዱኝ? ወንድ በሴት አቢውዝ ይሆናል ብሎ የሚያምንም አልነበረም በዛ ጊዜ። <<አቢውዝ ተደርጌያለሁ>> ብትል በተዘዋዋሪ መንገድ እየተጎራህባቸው ነው የሚመስላቸው። (በፖሊስ ነበር'ኮ ላስፈልጋት የሚገባ የነበረው። ይቺ ሬፒስት!! ይቺ ያልተያዘች ወንጀለኛ!! ይቺ...)

ቆም ብዬ የዛሬውን አለባበሷን አስተዋልኩት።

ልዩነታችን እንዳለ ሆኖ የለበሰችው አጭር ቀሚስ "መጥፎ ነው" የሚባል አይደለም። ኧረ እንዲያውም "ደህና" ነው። "ያምራል" ልለውም እችላለሁ።
ንፋስ ሲነፍስ ተሰማኝ።
መስኮቱን ዘጋሁ። ንፋሱ አልቆመም። በሩን ዘጋሁ። ንፋሱ አሁንም አላቆመም። ከበሩ ወደ መስኮቱ ስመላለስ...የተራቆቱ እግሮቿ ከቲቪው እስከ ሳሎኔ ድረስ ዘርግታ አሰናከለችኝ። ተንገዳግጄ ቲቪው ፊትለፊት ካለው ወንበር ላይ ተቀመጥኩ። ለካስ ንፋሱ የተነሳው ከውስጤ ነበር። እግሮቿን ደግሜ እያዬሁ በእግሮቼ መሀል እጄን ላኩት። "ወቀሳ የሚገባኝ ከንቱ ሰው ነኝ!" የሚለው የበውቀቱ ትረካ ጆሮዬ ላይ እያቃጨለብኝ ቀጠልኩት። የስሜት ጫፍ ላይ ደረስኩ። የጀመርኩትን ሳታስጨርሰኝ <<አሁን ደግሞ ወደማስታወቂያ እንለፍ!>> ብላ አቋረጠችኝ። በሷ የጀመርኩትን...በደርባ ሲሚንቶ ጨረስኩት!

እንዲህ ነች አቢቲ። ሁሉንም ነገር ታስጀምርና ልክ ሲለምዷት ጥላ እብስ ትላለች። መጎብኘት እንጂ መለመድ አትወድም። የአማልክቱን እግር አሳይታህ ሰፍ ስትል ለ'ነደርባ ሲሚንቶ አሳልፋ ትሰጥሀለች።

ከተቀመጥኩበት ሳልነሳ...ተመልሳ መጣች። ሀፍረት ተሰማኝ። ሪሞቱን አንስቼ ቲቪውን አጠፋሁት። ቲቪው ውስጥ የሆነ ሰውዬ ሳይ <<የማነው ዥልጥ?>> ልል ብዬ...ካፌ አድርሼ መለስኩት። የጣዲቁ ያለህ!...ቲቪውን መልሼ አበራሁት። እኔ ጠፋሁ። እሷ በራች።

<<...ማስታወቂያው እስኪያልቅ ታግሰው ስለጠበቁን ከልብ እናመሰግናለን! የትም እንዳትሔዱ ብዙ ፕሮግራም ነው ያለን ዛሬ!!>> አለች።
እንጀራ ሁኖባት ነው እንጂ እንደዚህ አይነት አሰልቺ ፕሮግራም የሚያይ አንድም ጤነኛ ሰው እንደማይኖር'ኮ ታውቀዋለች። እኔም "እግር ጥሎኝ" ነው!
<<Blue Fashion የተሰኘው ሳምንታዊ ፕሮግራም አርባ አንደኛ ክፍል ዛሬ ማታ በጊዮን ሆቴል ይካሔዳል። እኛም አንቀርም እርሶም ተጋብዘዋል። እዛው እንገናኝ!>> አለች በቀጣፊ አይኖቿ እየተስለመለመች።
<<ዝምብለሽ ማስታወቂያውን ስሪ...ያንቺ መምጣት አለመምጣት ግድ የሚሰጠው የለም!!>> አልኩ ሳላስበው ቲቪው ላይ እየጮህኩ።
ግን በቃ የሚመክራት ሰው የለም ማለት ነው? ዛሬም ትላንትና ላይ ነው ያለችው? ዛሬም እሷ መሪ ተዋናይ እኛ ደቃቅ ገፀባህሪዎች እንደሆንን ነው የምታምነው? አሁን ዝግጅቱ ላይ የሷ መመምጣትና አለመምጣት ለኛ ምናችን ነው?

አንድ ያለሁት ግድ የሚሰጠኝ ሰው እኔ ነበርኩ። እኔንም እንዳይለመደኝ አድርጋ አስተምራኛለች።

<<አንጣ እጅህን ልምታልህ? ማሪያምን ክረምት ላይ ማለት ነው? እ?...ልክ ትምሕርት እንዳለቀ ወዳንተ ነው እየከነፍኩ የምመጣው! እንገናኛለን!!>> ነበር ያለችኝ የዚያኔ ስንለያይ።

የልጅ ልቤ አመናት። የህይወቴን ረጅሙን በጋ አሳለፍኩ። የናፈቅኩት ክረምት መጣ። ጭል ጭል ሲል የከረመው ወንዝ ሞልቶ መሻገሪያ ጠፋ። ወበቅ በካፊያ...አቧራውም በጭቃ ተተካ። "ከአመት አመት ያድርሰን" እያሉ የሔዱት ልጆች "ሆያሆዬ" እያሉ ተመለሱ። ክረምት አለቀ። ደመራ ተለኮሰ። የመስቀል ወፍ መጣች። እሷ ግን ቀረች። ቀጠሮ በማክበር ወፍ በለጠቻት።
በመሀከላችን የነበረው ነገር ትክክለኛ ግንኙነት መስሎኝ...አቤት ስንት ግጥም ፃፍኩላት?! አቤት ስንት ወግ ወገወግኩላት?! አቤት ስንት ቀን በናፍቆት ተወዘወዝኩላት?! ካደግኩ ቡኃላ ነው ነገሩ የተገለጠልኝ። ለካስ <<እንገናኛለን>> ያለችኝ በስንብት ጊዜ የሚመጡ አላስፈላጊ ስሜቶችን ለመሸሽ ነው። ለካስ በአዋቂዎች አለም <<እንገናኛለን!>>....የ<<ቻው>> ሌላ ስሙ ነው!

አሁን አደግኩ። እፀ-በለሱን በላሁ። አይኖቼ ተገለጡ። ክፉና ደጉን ለዬሁ። በእንዲህ አይነት ዲስኩሮች መሸወድ አቆምኩ። እሷንና መሰሎቿን ተፀይፍኳቸው። ቢቀርቡኝም ላልቀርባቸው ለራሴ ቃል ገባሁ።
እሷ ለኔ አበባ አይደለችም። የአበባ ለምድ የለበሰች መቀስ ነች።

<<ከፕሮግራሙ ጥሩነት አንፃር ካዬነው የትኬቱ ዋጋ በጣም ተመጣጣኝ የሚባል ነው። አምስት መቶ ብር ብቻ ከፍለው ያገኙታል...>> እያለች ትንበለበላለች።
እንደው ለመታዘብ ብዬ የተወሰነ አዬኋት።
<<ብዙ ነው!!>> ብላ ያካበደችላት ፕሮግራም ወዲያውኑ አለቀች።
ለምን እንደሆነ አላውቅም የሷ ፕሮግራም ሲያልቅ ቻናል መቀዬሩ አይመጣልኝም። ቲቪውን አጥፍቼ ልብሴን እያስተካከልኩ ተነሳሁ። ደሞ አምስት መቶ ብር አስገቡታ ያንን ትኬት? አሁንስ ምርር ያለኝ በየሳምንቱ ዋጋ የሚጨምሩት ነገር ነው!!

@wegoch
@wegoch
@paappii

By #Mickel Azmeraw
#የመኖር አካፋይ ፣ የመ ፤ ሞ ፣ ት ሲሶ ፣ መንገድ መሃል ………… (ክፍል አስራ አራት)
(ሜሪ ፈለቀ)


«ከዛ ሰውዬ ጋር አብሬው ተኛሁ? ምንድነው ያደረግኩት?» መልሱን ማናቸውም እንደማያውቁት እያወቅኩ ደጋግሜ እጠይቃቸዋለሁ። እነርሱም መልሱን ጠብቄ እንዳልጠየቅኳቸው ስለልገባቸው አይመልሱልኝም። ከዚህ ቀዬ ከወጣሁ በኋላ የተፈጠረውን ነገር ካወቀ ሊያውቅ የሚችለው ኪዳን ብቻ ነው።

እናቴን ካገኘሁ በኋላ ያለፈውን ራሴን የመፈለግ ውጥረቴ ትቶኝ ነበር። አጎቴ ታሪኬን ነግሮኝ ሲያበቃ እንደአዲስ ያቅበጠብጠኝ ጀመር። ምንድነው ያደረግኩት? ምን ዓይነት አቅል መሳት ላይ ደርሼ ነው ያን ሰውዬ ያገባሁት?

«እናቴ? ስለኪዳን የነገርኩሽን የምታስታውሺውን ሁሉ እስኪ ንገሪኝ! ከተመታሁኮ ሁለት ወር አለፈ። እንዴት አይፈልገኝም? እንዴት አይደውልልኝም?»

«እኔ እንጃ ልጄ! ብዙውን ያወራሽኝ ስለመውደድሽ ፤ ጎበዝ ተማሪ ሆኖ በማዕረግ ስለመመረቁ ፣ ፈረንጅ ፍቅረኛ እንዳለችው እና ሰርጉ ሀገሩ እንዲሆን ፈልጎ አንቺ እንቢ ማለትሽን …… እንዲህ እንዲህ ያለ ነገር ነው የነገርሽኝ እንጂ የምትገናኙበትን መንገድ አላውቅም ልጄ። ከመሞቴ በፊት ባየው ብዬሽ <በህይወት መኖርሽን አያውቅም። እንዴት እንደምነግረው እንጃ ግን እነግረዋለሁ> አልሽኝ።» እያለችኝ ሌላ የምታስታውሰው ነገር መኖሩን የጭንቅላቷን ጓዳ ትበረብራለች

«ለምን እንቢ አልኩት? ማለቴ ሰርጉን?»

«አንቺን ማጥቃት የፈለገ ሰው ሊያጠቃሽ የሚችልበት ብቸኛ መንገድ እሱ በመሆኑ አንድ ነገር እንደሚያደርጉብሽ ነው የነገርሽኝ። ሁኔታውን ልትነግሪኝ አልወደድሽም እንጂ ከዚህ በፊት በእሱ እንዳገኙሽ ነግረሽኛል።»

ድፍንፍን ያለ ነገር ሆነብኝ። ወደቤቴ መመለስ ፈለግኩ። ፍለጋዬን የት እንደምጀምር ባላውቅም እዛ የሆነ ፍንጭ አላጣም መሰለኝ። ያቺ መልእክት አስቀምጣ የነበረችው እመቤትስ? ያ የደወልንለት ሰውዬ ቃሊቲ እስር ቤት ናት ያላት እመቤት! ማን ያውቃል ለእሷ የሆነ ነገር ነግሬያት ይሆናል። ግን እስር ቤቱጋ ሄጄ በደፈናው እመቤትን ነው የምለው? ምናልባት አንድ ሀገር እመቤት የሚባል ሴት ይኖራል። አላውቅም ብቻ እዚህ ተቀምጬ ሀሳብ ከማመነዥክ መሞከሩ አይከፋም!

ምናልባት ደግሞ ያ ስልባቦት የመሰለ ዳዊት የሚሉት ፍቅረኛዬ! ለእርሱስ ምንም ልነግረው አልችልም ኸረ! ማን ያውቃል ግን? ግን እንዴት ባለ ዘዴ ነው ትውስታዬን ማጣቴን ሳልነግረው ስለኪዳን የሚያውቀው ነገር መኖሩን የማወጣጣው?

እናቴ የቀሯትን ቀናት እዛው መሆን መፈለጓን እኔ እንዳይከፋኝ በማባበል በማስፈቀድ ለዛ ስትጠይቀኝ ግራ ገባኝ። በሽታዋ የማህፀን ካንሰር ነው። ምንም ማድረግ እስከማይችሉበት ሰዓት ድረስ ሀኪሞች ብዙ ትሪትመንት ሞክረውላታል። ያገኘኋት ጊዜ ሀኪም ቤት ካልወሰድኩሽ ብዬ ስነዘንዛት

«ልጄ አንቺው እኮ ነሽ ስታሳክሚኝ የቆየሽው! ከሀገር ውጪ ወጥተሽ ካልታከምሽ ብለሽኝኮ ምንም ፋይዳ እንደሌለው ሀኪሞቹ ነግረውሽ ነው የተውሽው። አምላክ በታምሩ ይሄን ደስታ ቀምሰሽ ሙቺ ሲለኝ እንጂ እንዲህም መች ትቆያለች ተባልኩ?» ብላኝ ነበር። ሀኪሞቹ ከገመቱት ቀን በላይ መቆየቷ ተዓምር እንደሆነ ሁሉ ብትታከም ድጋሚ ተዓምር ሊፈጠር ይችል ይሆናል ብዬ ላሳምናት ብሞክርም <ደከመኝ> አለችኝ። ማረፍ ብቻ ነው የፈለገችው። መሞትን ሳትፈራው ቀርታ ይሁን ወይስ እንዳይታወቅባት ውጣው ለመሞት የተዘጋጀች ነው የምትመስለው። በመጣ ቀን <እንኳን ደህና መጣህ! ስጠብቅህ ነበር> ብላ የምትቀበለው።

«እሺ!» አልኳት እና ወደጎንጥ ዞሬ «አንተ ነገውኑ ባሻህ ሰዓት ተመለስ! እኔ እዚህ ከእናቴ ጋር እሆናለሁ! » አልኩት

«ማይደረገውን!! እኔ እዚህ መሆኔ ካልከበዳችሁ በቀር ወደየትም የመሄድ መሻት የለኝም!!» (አለ ወደአጎቴ እያየ)

«ኸረ ምን ከብደኸኝ? ባደረገውና እዚሁ በባጀህ! እኔማ የሚያነጋግረኝ አገኘሁ!» አለ አጎቴ።

ከመጣን ጀምሮ ጎንጥ ከዚህ በፊት የሚያውቀው ቤት እና ቤተሰብ ውስጥ የተቀላቀለ ነበር የሚመስለው። እጅጌውን ሰብሰብ አድርጎ እንጨት ለመፍለጥ ሰዓታት አልፈጀም። ሊወድቅ ያዘመመውን የከብቶቹን ቤት ያጋደለውን እንጨት እያስተካከለ ሲተክል በእንግድነት ውሎ አላደረም ነበር። ሱሪውን ሰብስቦ እንደቁምጣ አሳጥሮ የአጎቴን የጓሮ ማሳ ሲያርም …… የኖረበት …. የሚያውቀው እንደሆነ ያሳብቅበት ነበር። አጎቴ በእርሱ መገኘት ደስ መሰኘቱን ለማወቅ ብዙ ሂሳብ አያሰራም።

«እኔ እዚህ ምን እሆናለሁ? እዚህ ጠላት የለኝም ሲገባኝ። ዝምብዬ ነው የምፈራው እንጂ ምናልባትም ማንም እያደባብኝ አይደለም። የሚያስፈልግ ነገር ሲኖር ባይሆን ትመጣለህ።» አልኩት እናቴን ላገኛት የሄድኩ ቀን እንደዛ ተንበጭብጬ ምንም ያለመፈጠሩን እያሰብኩ።

«ህም!! ክፋት የከጀለ ልብ አይደለም እዝህች ሲኦል ከመውረድ የሚያግደው የለም!» አባባሉ ስለእርሱ ያለኝን ጥርጣሬ ቀሰቀሰብኝ። የሆነ ያልነገረኝ የሚያውቀው ነገርማ አለ።

«አይሆንም አንቺም እዚህ አትከርሚም!» አለች እናቴ ጠልቃ ገብታ « ….. በአካል ባልዳብሰው እንኳን የኪዳንን ድምፅ ሰምቼ አንዴ አውርቼው ባልፍ …… ይሄ ባይሆን እንኳን ለወንድምሽ ታስፈልጊዋለሽ። አግኝው!» አለችኝ አሁንም በልምምጧ። ልቤ መሃል ላይ ዋለለብኝ። እሺ የት ብዬ ነው የምፈልገው? እሱን ለማግኘት እኔ ስዳክር እናቴ ብታመልጠኝስ? ምን ያህል እንደሆነ የማላውቀውን የቀረንን ቀን ትቻት እንዴት ነው የምሄደው?

«የእኔ አበባ ? አትከፊብኝ! እዚህ አብረሽኝ ብትሆኝም ሞትን አታስመልጪኝም! ለእኔ አምላክ በእድሜዬ ማታ አንቺን መልሶልኝ ሀሴት ሰጥቶኛል። ወንድምሽን ባላገኘው እንኳን ደህና መሆኑን ማወቄ እረፍት ነው!! ስንት ቀኖች እና ስንት ለሊቶች <ልጆቼን ለየትኛው ጅብ ዳርጌያቸው ይሆን? ምን ዓይነት ህይወት እየኖሩ ይሆን? ትቻቸው ባልሄድ የተሻለ ህይወት ይሆንላቸው ነበር?> እያልኩ በፀፀት ነድጃለሁ መሰለሽ? ያንቺ እናት ስለሆንኩ እኔ እድለኛ ነኝ። ብቻ አንድ ነገር ቃል ጊቢልኝ! ያለፍሽውን ብታስታውሺም ባታስታውሺም ወደቀደመው ህይወትሽ ላትመለሺ ቃል ጊቢልኝ!! ልብሽን ያየ አምላክ ሁለተኛ እድል ሰጥቶሻል። ያለፈውን ለመድገም ሌላ አዲስ ህይወት ባላስፈለገሽ ነበር። አዲስ ህይወትን ገንቢ የእኔ አበባ! ……. » የስንብት የሚመስል ብዙ አለችኝ። ያለእርሷ የኖርኩትን ህይወት እንዴት እንደኖርኩት ባላውቅም አሁን ያለእርሱ የምኖራቸውን ቀናት ሳስብ በረደኝ።

ግማሽ ልቤን እናቴጋ ትቼ፤ ፈጣሪ ትንሽ ቀን ቢጨምርላት፣ ኪዳንን ባገኝላት እና ብትሰማው ወይ ብታየው እየለመንኩ በተከፋች ግማሽ ልቤ ከጎንጥ ጋር ወደቤት መንገዱን ተያያዝነው።

«ይገርማል! የዛን ቀን ሞቼ ቢሆን ኖሮምኮ መሞቴን እናቴም አጎቴም አይሰሙም። በዚህ አይነት ኪዳንም አይሰማም ነበር። ሊቀብረኝ ራሱ የሚመጣ ሰው ይኖር ይሆን?» አልኩኝ 

« ህም የሌላውን እንጃ። እኔ የት ሄጄ ነው የማልኖር?»

«ሬሳዬን የሚሸኝ ስለማይኖር ሰብአዊነት ተሰምቶህ እንጂ መቼም <ወየው እትይ!> እያልክ አትቀብረኝም ነበር።» ስለው አይኑን ለአፍታ ከመንገዱ ወደእኔ አዙሮ ፈገግ ብሎ ዝም አለ። በሱው የፈገግታ ለዛ ቀጥዬ  «ሆስፒታል እንኳን መጥተህ እየኝ ብዬ ብልክብህ <የቀጠሩኝ ደጆን እንድጠብቅ ነው > ብለህ አልላክብኝም? ዛሬ ቤቱን ጥለህ ገጠር ለገጠር አብረኸኝ ልትንከራተት?»
«ህም መች ሰው ባሰበበት ይውላል?» አለ ከንፈሩን ብቻ ሸሸት አድርጎ። እኔ አንድ ሀገር አውርቼ ከአምስት ቃል ያልዘለለ ነው የሚመልስልኝ። ያለማቋረጥ መለፍለፌ ለራሴ እንኳን እንግዳ አይነት ስሜት ሰጥቶኛል። መልሼ ይሄንንም ያንንም ሳወራ ራሴን አገኘዋለሁ እንጂ። ምናልባት ከእናቴ ጋር የነበረኝ ጊዜ፣ ወይ ደግሞ ያስታወስኩት የትውስታዬ ሽራፊ፣ ወይም ትውስታዬ የመመለስ ተስፋ እንዳለው ማወቄ፣ አልያም አጎቴ ያወራልኝ የህይወቴ ክፍል …… አላውቅም! አንዳቸው ወይም ሁሉም ተደምረው ግን የሆነ ስሄድ ከነበረው ቅልል ያለ ስሜት ስመለስ እንዲኖረኝ አድርገውኛል።

«ከመመታቴ በፊት ለመጨረሻ ጊዜ ያደረግኩት ምን ይሆን? ለመጨረሻ ያገኘሁት ሰው ማን ይሆን? ያስቀየምኩት ወይስ በጥሩ የሚያስታውሰኝ ሰው ይሆን?» ያልኩት እንዲመልስልኝ አልነበረም።

«የዚያን እለት ከቤት ወጥተሽ ብዙም ሳትቆዪ ነው የሆነው ነገር የሆነው። በመንገድሽ የገጠመሽ ካልነበረ ለመጨረሻ ያወራሽው እኔን ነው የሚሆን!» አለ ስሜቱን ለማንበብ በሚከብድ ፊት። ያልጠበቅኩት መልስ ሆኖ መሰለኝ ተስተካክዬ ተቀመጥኩ።

«ምንድነው ያወራሁህ? መጥፎ ነገር ነው? ጥሩ?»
«ያለፈውን ከኋላችን እንተወው ተባብለንም የለ?» መመለስ የማይፈልገው ነገር ሲሆን የሚያመልጥበት ዘዴው ነው።
«በናትህ? ለምንድነው ግን ያለፈውን ስጠይቅህ የምትሸሸው? ልቤ የሚነግረኝ ከነገርከኝ በላይ ብዙ የምታውቀውን ነገር እንደደበቅከኝ ነው ግን ዝም ብዬ እያመንኩህ ነው።» ….. ብዬ ጥርጣሬዬን ላስከትል ስንደረደር የሚቀጥለውን ለማስቆም በሚመስል

«ፀያፍ ነገር ነው!! እኔ አሁን የማልደግመውን ፀያፍ ነገር ብለሽኝ ነው የወጣሽ! እንደእውነቱስ አፍሽን ከፈትሽ ነው የሚባል።» አለ እንዲመልስልኝ ስላደረግኩት እየተናደደብኝ።

«እሺ በሙሉ ልቤ እንዳምንህ አስረዳኝ! እንደዛ ፀያፍ ነገር የምናገርህ ሴት ሆኜ እቤቴ ምን አቆየህ? ስራዬ ፣ እንጀራዬ ምናምን ብለህ ልትሸነግለኝ አትሞክር! እኔ የምከፍልህን ደመወዝ ብዙ እጥፍ ከፍሎ የሚያሰራህ ሰው አታጣም ባንተ ብዙ ችሎታ! ሲጀመር የአንድ ቤት ዘበኛ፣ መኪና መንዳት የሚችል፣ ሽጉጥ የታጠቀ ፣ ክብር ሀቅ እውነት እሴቶቹ የሆነ ሰው ……  አፏን የምትከፍትበት ሴት ደጅ ምን ያደርጋል?»

«ውል የሌለው አድርገሽ አትቆጣጥሪውማ! ሹፍርና እሰራ እንደነበርኮ አውግቼሽ ነበር። ወታደር ቤት ስለነበርኩ መሳሪያውም አዲሴ አይደለም። ሽጉጡንም ያስታጠቅሽኝ አንቺው ነበርሽ! ይከው ነው!!» አለ

«አሁን ያልከው በሙሉ ለምን እኔጋ እንደቆየህ አያብራራም! እሺ ንገረኝ እስኪ የት ነው የተገናኘነው? ማለቴ ስራውን እንዴት አገኘኸው? ወይም እኔ እንዴት ቀጠርኩህ?»

ለማውራት አፉን ከመክፈቱ በፊት በረጅሙ ተነፈሰ። ግንባሩ ላይ ያሉት መስመሮች ብዛታቸው ጨመረ። ዞር ብሎ ሳያየኝ

«ሰው ነው ያገናኘን! አንቺ ጠባቂ እንደምትፈልጊ እኔ ስራ እንደሚያስፈልገኝ የሚያቅ ሰው!» አለ በድፍኑ። አጀማመሩ እስከነገ የማያልቅ ታሪክ ሊያወራኝ ነበርኮ የሚመስለው።

«በቃ!? ሰው?» ድምፄን ጨመርኩ።
«ቆይ እኔ የምጎዳሽ አለመሆኔን እንድታምኚ ምንድነው ማድረግ ያለብኝ?»
«እያወራን ካለነው ጋር ይሄ የሚያገናኘው ነገር የለም! ትጎዳኛለህ ብዬ ባስብማ አብሬህ አልገኝም!! አንተ መናገር ያልፈለግከው ወይም እየደበቅከኝ ያለ ነገር እንዳለ እየተሰማኝ ግን ምንም ሳትጠይቂ በጭፍኑ እመኚኝ ማለት አይዋጥልኝም።» አልመለሰልኝም። አሁንም በረዥሙ ተንፍሶ ዝም አለ። በዝምታችን ውስጥ ከራሴ ሳወራ ለካንስ ምንም ነገር ለእኔ የማስረዳት ግዴታም የለበትም። <የራስሽ ጉዳይ> ብሎ ጥሎኝ ቢሄድስ መብቱ አይደል? ያኔም ለምን አብሮኝ እንደቆየ አሁን ለምን አብሮኝ እንዳለ ምክንያቱን ማወቅ አልችልም። ስለእርሱ የማወቅ መብት እንዳለኝ እንዲሰማኝ ያደረገኝ ራሱ አይደል ግን?

ሀሳብ ሳዛቁል ስልኬ ጠራ። የማላውቀው ቁጥር ነው። ለምን እንደማደርገው ባላውቅም የማላውቀው ስልክ ሲደወል ጎንጥ አጠገቤ ካለ ድምፁን ስፒከር ላይ አደርገዋለሁ። ምናልባት የመጀመሪያ ቀን ስልኬ ሲከፈት ድንብርብሬ ወጥቶ ስንተባተብ እሱ ስልኩን ተቀብሎኝ ስላወራ እንደልምድ ወስጄው ይሆናል። አነስቼ ሀሎ አልኩ።

«እሺ ሜላት!! ሁልጊዜ ጀግና አይኮንም! አንድ ቀን አገኝሻለሁ ብዬሽ አልነበር?» ወፍራም ድርብ የወንድ ድምፅ ነው።
«ማን ልበል?»
«ማን እንደሆንኩማ አሳምረሽ ታውቂዋለሽ!! ዛሬውኑ እስከማታ ድረስ የምልሽን ታደርጊያለሽ!! ህም እመኚኝ ይሄ እንደሌላ ጊዜው ማስፈራሪያ አይደለም። ምንም አይነት ወጥመድ ከጀርባዬ ሸርባለሁ ብትዪ ወንድምሽን 12 ትንንሽ አድርጌ በየተራ እልክልሻለሁ። ……. » ጎንጥ መኪናዋን ሲጢጥ አድርጎ አቆማት። እየሆነ ያለው ነገር በቅጡ ሳይገባኝ ሰውየው ማውራቱን ቀጠለ « …… ልታናግሪው ከፈለግሽ አጠገቤ ነው። ቪዲዮ ላድርግልሽ ከፈለግሽ?» (እያላገጠብኝ ነው የሚያወራው) ይሄኔ ጎንጥ ከመኪናው ፊትለፊት ያለ ወረቀት አንስቶ ከኪሱ እስኪሪብቶ አውጥቶ የፃፈውን አሳየኝ። <ምንድነው የምትፈልገው? በይው።> ሰውየው ይሄን ሲሰማ እንደመደሰት አደረገው።

« የሰውን ስስ ጎን ማግኘት ደስ ሲል።አየሽ  የምትሳሺለት ነገር ሲያዝብሽ እንዲህ ነው የሚያንገበግበው። ከገባሽ! አንደኛ ወለም ዘለም ሳትዪ የቪዲዮን ያሉሽን ቅጂዎች በሙሉ ካስቀመጥሽበት ሰብስበሽ ነይ የምልሽ ቦታ ይዘሽ ትመጫለሽ። ሁለተኛ አንቺን ማመን ስለማይቻል ማስተማመኛ እንዲሆነኝ እዚህ ከመጣሽ በኋላ በይ የምልሽን እያልሽ እንቀርፅሻለን። ይቅርታ እንግዲህ ባላምንሽ … ያለመታመን ልምድሽ አቻ ባይኖረው ነው።» እኔ እሱ የተናገረው ምኑም አልገባኝ እሱ ይገለፍጣል። ጎንጥ ፅፎ ያሳየኛል።

«እኮ ምንድነው እንድቀርፅልህ የምትፈልገው?»
«ቆቅ አልነበርሽ? ይህቺ ትጠፋሻለች? በማስፈራራት ያለፍሻቸውን እዚህም እዛም የሰራሻቸው ህገወጥ ነገሮች ሲሰበሰቡ እድሜ ልክ ዘብጥያ የምትበሰብሺበት ሆኖ አጊንቼዋለሁ። ብዙም እንዳትቸገሪ መረጃዎቹንም ሰብስቤልሻለሁ። አንቺ የሚጠበቅብሽ የሰራሻቸውን ወንጀሎች በመረጃ አስደግፈሽ አምነሽ ቃል መስጠት ነው። ከምታምኛቸው ውስጥ ፌክ የምስል ቅንብር እና መረጃ ሰርተሽ እኔን በማስፈራራት የግል ጥቅም ለማግኘት ያለመታከት መልፋትሽ ይካተትበታል። ያው እዝህችጋ ምንም ያህል የረቀ ሴራ ብትሰሪ እኔ ወደር የሌለኝ ለሀገሬ ታማኝ አገልጋይ መሆኔን አክለሽ ብትጠቅሽም አይከፋኝም። ሃሃሃሃሃ» እኔ ምኑም እየገባኝ ካለመሆኔ እየተነጋገሩ ያሉት ሰውየውና ጎንጥ ናቸው የሚመስሉት

«ኪዳንን አገናኘኝ? ማስረጃ እፈልጋለሁ።» ብሎ ጎንጥ የፃፈልኝን አነበብኩለት

«ምን ችግር። ቆዪማ ቪዲዮ ላድርገው?» ሲለኝ ጎንጥ ስልኩን ዘጋው እና እኔ ላይ አፈጠጠ።

«ወንድምሽን ስታዪው የተደናገጠ ሰው እንዳትመስዪ ፣ ድሮ የሚያውቋትን ሜላት መሆንሽን አሳምኛቸው። ምንም እንደማያውቅ ሰው አትምሰዪ ….. የማታውቂውን ነገር አትጠይቂ!! ምንም ቢፈጠር እንደማታስታውሺ እንዳትናገሪ ….. የምልሽን ብቻ አድርጊ!!» ብሎ በቁጣ እያስጠነቀቀኝ ስልኬን ተቀብሎኝ የሆነ ነገር እንደሚፈልግ ሰው ጣቱን ካመላለሰ በኋላ ከመጡለት ዝርዝሮች የሆነች ቀይ ምልክት ነገር ተጭኖ እየመለሰልኝ ስልኩ ጠራ። ድንብርብሬ ሲወጣ በሁለቱም እጆቹ ትከሻዬን በሁለቱም በኩል አጥብቆ እየያዘ « ታምኚኛለሽ?» ያለኝ ስለምን እንደሆነ ሳይገባንኝ ጭንቅላቴን ወደ ላይ ወደታች ናጥኩ!! «ተረጋጊና ያልኩሽን አድርጊ!!»
«እኔኮ ኪዳንን እንኳን ላልለየው እችላለሁ?» አልኩ አፌ ውስጥ ምራቄ ደርቆብኝ ትን የሚለኝ እየመሰለኝ። ስልኩ ጠርቶ እንዳይዘጋ እየተቻኮለ ስልክ ያልያዝኩበትን እጄን ቀለብ አድርጎ ጨብጦ ከቅድሙ በተረጋጋ ድምፅ

«ትለይዋለሽ ግድ የለም!» አለኝ። የድምፁ መርገብ ይሁን የያዘኝ እጁ ያረጋጋኝ መርበትበቴን ገትቼ የያዘኝን እጄን አስለቅቄ ስልኩን ካነሳሁ በኋላ እንዲይዘው መልሼ ሰጠሁት።                                                      

........ አልጨረስንም.....

@wegoch
@wegoch
@paappii
« ለቅሶ አለብኝ... ልብስ ምረጥልኝ» ብላ የተከፈተ ቁምሳጥኗ ፊት ለፊት አቆመችኝ። የተጠቀጠቀ የጥቁር ልብስ መአአአአአት።

'ይጥቆር እንጂ ደግሞ ለለቅሶ ልብስ መረጣ የምን ቅብጠት ነው። ' አልኩ በሆዴ ... ታዝቤያት። እጄን በግዴለሽነት ሰድጄ አንዱን ጥቁር ጎተትኩትና ፊቷ ዘረጋሁት። ቀሚስ ነበር።

“ ውይ ... ይሄንን ቀሚስማ ሰዓሊው ወዳጄ ሲሞት ለቅሶ ደርሼበታለሁ ፤ አልለብስም።»

«ለለቅሶ የለበስሽውን ቀሚስ አትደግሚም? »

«ሀዘን ይደገማል? » ጥያቄዬን በጥያቄ። «በል ሌላ ምረጥ!»

ምን አከራከረኝ፤ ያነሳሁትን ወለል ላይ ጥዬ ሌላ ጥቁር መዘዝኩ። ባለአንገት ሹራብ።

«ዘፋኙ ጓደኛዬን ቀብሬበታለሁ እሱን። ቀይር»

ሆሆ... ጥዬ ሌላ መዘዝኩ። ሸሚዝ

« የጋዜጠኛ እህቴን አስከሬን በሱ ነበር የሸኘሁት። »

ጣልኩ። አነሳሁ። አንዱን ቀብራበታለች።
ጣልኩ.. አነሳሁ። ለአንዷ አንብታበታለች።
ወለሉ በጥቁር ልብስ፣ ጆሮዬ በሙታን ፕሮፋይል ተሞላ።

እንደ ድንገት አንዷን ሳብኳት። የምታምር ጥቁር ሱሪ። አማረችኝ።

«አታምርም? »

«በጣም ታምራለች። ለምን ይህቺን አትለብሻትም? »

«ቆጥቤያት ነውኮ። በጣም የምወደው ሰው ሲሞት ነው የምለብሳት። »

«ማን ሲሞት?»

«አንተ ነሃ የኔ ፍቅር!»

« ያድኅነነ ከመዓቱ ይሰውረነ ! ምነው በናትሽ»

«ከልቤ ነውኮ። የዛሬ ወር ሾፒንግ ወጥቼ ተሰቅላ ሳያት ትዝ ያልከኝ አንተ ነህ። እንዴት እንደምወድህም ያወቅኩት ያኔ ነው። »

« እርፍ!»

« እርፍ ስትል ነውኮ እለብሳታለሁ ያልኩህ! በዛ ላይ ሰሞኑን እያሳለህ ነው... »

«ምን በወጣኝ ነው የምትወጂኝ በማርያም? ካልጠፋ ሰው እኔን ለምን ወደድሽኝ በሩፋኤል?! »

« ኧረ አንተ ብቻ አይደለህም ውዴ። ያንተን እንደውም ከገዛሁት ቆየሁ። ቁም ሳጥን ውስጥ አልከተትኳቸውም እንጂ... አባቴ... መምህሬ... ክርስትና እናቴ ፣ የእህቴ ባል ፣ ያ ደሞ አቀናባሪው... በየተራቸው ሲታመሙ ጊዜ... “ድንገት ከሞቱ ብዬ” የምለብሰው ገዝቼ አስቀምጫለሁ። እኛ የኪዳነምሕረቱ ቄስ... እኚያ ሰባኪው አወቅካቸው? የምወዳቸው ? ቄሱ... ? ከሰሞኑ ታመዋል ሲሉ ሰምቻለሁ። ከዛሬው ቀብር መልስ... ለሳቸው ለቅሶ የሚሆን ነገር ታጋዛኛለህ »

አሃ... !
ለካ አልቃሾች አዲስ ጥቁር ሲሸምቱ..፣ አዲስ ድንኳን ሲጎትቱ፣ አዲስ ሙሾ ሲሸመድዱ፣ አዲስ አለቃቀስ ሲለማመዱ... መደንገጥ ነበረብን?

ለካ የሞት መላዕኮቻችንን ከምንጠብቅ ፣ አልቃሾቻችን አዲስ ጥቁር ልብስ እስኪገዙ ብንጠብቅ፣ መች እንደምንሞት ይገለጥልን ኖሯል !?

አሳዘነችኝ።
ቁም ሳጥን ሙሉ ልብስ አገላብጣም፣ ለዛሬው ለቅሶ የምትለብሰው ጥቁር አላገኘችም። በርግጥ... እኔ ጋር ገና ያልለበስኩት ጥቁር ካፖርት አለ። «ልስጥሽ?» አልላት ነገር ፈራኋት።

«ሲያምር! እኔ ስሞት ለብሰኸው ትቀብረኛለህ!»
ብትለኝስ?

@wegoch
@wegoch
@paappii

By Rediet aseffa
#የመኖር አካፋይ ፣ የመ ፤ ሞ ፣ ት ሲሶ ፣ መንገድ መሃል ………… (ክፍል አስራ አምስት)
(ሜሪ ፈለቀ)

በአትኩሮት ቢያየኝ እኮ በአፌ ልትወጣ የደረሰች ልቤ ስትደልቅ የለበስኩትን ሸሚዝ እያርገበገበችው ነው። በጀርባዬ የሚንቆረቆር ላቤ ለአፍታ ሌሎች ድምፆች ረጭ ቢሉ፤ ከማጅራቴ ወደ መቀመጫዬ ሲወርድ እንደ ዝናብ <ጠብ> ሲል ይሰማ ነበር። ስክሪኑ ላይ ያለውን የራሴን ምስል ሳየው ለመኮሳተር (የማላስታውሳትን የድሮዋን ሜላት ለመምሰል) በታገልኩ ቁጥር የዞረበት ፊት እያሳየሁ እንደሆነ ገባኝ። እጄን የያዘው የጎንጥ እጅ (ገባቶት ነው መሰለኝ) እንደመጭመቅ ሲያደርገኝ ትኩረቴን ከራሴ ፊት ላይ ወደ ኪዳን መለስኩ። መስሎኝ የነበረው ከወንበር ጋር ታስሮ እየተሰቃየ የማየው ወይም ያ ድምፁን የሰማሁት ሰውዬ ግንባሩ ላይ ሽጉጥ ደግኖበት አልያም ፊቱ በድብደባ ብዛት አባብጦ እና በደም ተለውሶ ነገር የማየው ነበር የመሰለኝ። የሆነው ግን ሌላ ነው። ኪዳንና ሰውየው እየተዝናኑ እንጂ አጋች እና ታጋች በማይመስል ሁኔታ አጠገብ ላጠገብ ተቀምጠዋል። ኪዳንን ለመለየት አልተቸገርኩም። የስልኬ ስክሪን ላይ ካለው መልኩ ምንም ለውጥ የለውም። አስቀድሞም በግራ መጋባት የጦዘውን ጭንቅላቴን ልክነት ያጠራጠረኝ የኪዳን መረጋጋት ነው። የሆነ ልክ ሰላም ልንባባል የተደዋወልን አስመስሎ

«ሜልዬ! ደህና ነሽልኝኣ?» አለ። ምንድነው እየሆነ ያለው? ኪዳን አይደለም ይሆን? ሰውየው ቅድም 12 ቦታ ቀነጣጥሼ እልክልሻለሁ ሲለኝ አልሰማም ማለት ነው? አሁንም የጎንጥ እጅ አነቃኝ።

«እኔ ደህና ነኝ! አንተስ?» ይባላል ቆይ? ከአጋቹ ጋር የተቀመጠ ሰው ደህና እንደማይሆን ግልፅ አይደል? እሱ ዝንቡ እንኳን እሽ እንዳልተባለ ሰው ዘና እያለ ታዲያ ምን ልበል? ምናልባት ለእኔ ብሎ ይሆን? እኔን ለማረጋጋት?

«አታስቢ ደህና ነኝ! ከልቤ ደህና ነኝ።» እያለ ምንም ያለመጎዳቱን ሊያሳየኝ ስልኩን እያራቀ ከተቀመጠበት ተነስቶ መላ አካላቱን አሳየኝ። እያባበለኝ ነገር መሰለኝ።

«እንዴት ነው የማላስበው? መዝናኛ ቦታ …… » እኔ ባልገባኝ  ምክንያት  ለእርሱ ግን ልክ በመሰለ እንድናገር አልፈለገም። ወዲያው አቋርጦኝ

«ሜል እንዲሁ ተጨነቂ ስልሽ ነው። እኔኮ ደህና ነኝ አልኩሽ። » ሲለኝ ጎንጥ ምን እንዳናደደው ሳይገባኝ ተበሳጭቶ ጥርሱን ነክሶ እኔን ባልያዘው እጁ አየሩን በቦክስ ጠለዘው። እየሆነ ያለው ነገር አፍና ጭራው የጠፋኝ እኔን ብቻ ነው? እኔ ሳይገባኝ እሱ የገባው አብረን ከሰማነው የደህና ነኝ መልእክት ውጪ ውስጠ ወይራ አለው? « በኋላ እንገናኝ የለ? እስከዛ ደህና ሁኚልኝ! ደግሞ አምላክን በልመና አታድክሚ!!! የምትችውዪውን አድርጊና በተረፈው አመስግኚው። ያመሰገንሽው አምላክ የጎደለውን ይሞላልሻል።» አለኝ ጭራሽ። የድሮዋ ሜላት ፀሎተኛ እንዳልነበረች ጠፍቶት ነው? ይሄንኑ ዓረፍተ ነገር ግን ከዚህ በፊት የሆነ ሰው ብሎት ሰምቻለሁ!! የት ነው የሰማሁት?

እስካሁን ድምፁ ያልተሰማው ሰውዬ ስልኩን ተቀበለውና በአይኑ እንደመጥቀስ አድርጎኝ ዘጋው!!  አፌን እንደከፈትኩ ስልኩ ላይ አፍጥጬ ቀረሁ።

«ይሄ የውሻ ልጅ አውቆታል!» አለ ጎንጥ። መኪና ውስጥ ሆነ እንጂ ሜዳ ላይ ቢሆን <ዘራፍ> የሚል ነው የሚመስለው።
«ምኑን?» አልኩኝ ከድንዛዜዬ ሳልወጣ

«እየቀረፅሽው እንደሆን !» ብሎ ስልኩን እንድሰጠው እጁን ዘረጋልኝ። ስሰጠው ስልኩ ስክሪኑ ቆልፎ ስለነበር እንድከፍትለት መልሶ ሰጠኝ። ያለኝን የምከውነው ምኑም ገብቶኝ አይደለም። ያለውም የገባኝ ነገር የለውም።

«ማን ነበርኩ? ከምን ጋር የተቆላለፈ ህይወት ነው የነበረኝ? የምን ቪዲዮ ነው የምወስድለት? ስልኬ ውስጥ ያለ ነገር ይሆን?»

«ህም! ስልክሽ ውስጥ ልታኖሪው አትችዪም!» ሲለኝ አፌን ከፍቼ ቀረሁ። ስለቪዲዮው ያውቃል!!

«ምን ይመስልሃል ቪዲዮው?»

«እሱን በምን አውቄው! ብቻ ቅሌቱን የተሸከመ ነገር ነው የሚሆን»

ድንዝዝ እንዳልኩ አይኔ ብቻ ሲንቀዋለል ስልኩ ላይ ቅድም የተጫናት ምልክት ስክሪኑን መቅጃ መሆኗን እና ሰውየው እንደመረጃ እንዳንይዝበት ኪዳንን ምንም የተለየ ምልክት እንዳይሰጥ አስጠንቅቆት እንደሆነ እርግጠኛ ሆኖ ከነገረኝ በኋላ እኔን ረስቶ የተቀዳውን ቪዲዮ እየደጋገመ ወደፊት ወደኋላ ቅርብ …. ራቅ እያደረገ ያያል። እኔ ደግሞ ዝም ብዬ እሱን አየዋለሁ።

«በስተመጨረሻ ልመና አታብዥ ያለው ነገር ያላስፈላጊ ቦታ የተዶለ አይመስልሽም? ላንቺ የሚያስታውስሽ ነገር አለ?» አለኝ አሁንም ከስክሪኑ አይኑን ሳይነቅል።

«የሆነ ሰው ሲለው የሰማው ይመስለኛል። አላውቅም!! ራሴም እለው የነበረ ነገር ይመስለኛል። ምንም መጨበጥ አልቻልኩም።» ስለው እንባዬ ዓይኔን ሞልቶታልኮ እሱ ግን አላየኝም። ቪዲዮውን ኪዳን ስለምስጋና ያነሳበት ጋር አቁሞ

«ተመልከች እዚህ!!» ብሎ ሰውየውን ጠቆመኝ « ልክ ኪዳን ሲናገር ፊቱ አንድ አፍታ ይቀየራል። ተመልከች! ያ ማለት ይህ መስመር እንዲናገር ከተፈቀደለት ውጪ ነው ማለት ነው! ሊገልጥልሽ የፈለገው አንድ መልእክት ቢኖረው ነው።»


«ጎንጥ?» አልኩት ፍስስ ባለ ድምፅ

«ወይ!» አለ አይኑን እዛው እንደሰነቀረ

«ማ ነ ህ? » አልኩት እንባዬ አብሮ ከቃላቱ ጋር ዱብ ዱብ እያለ። እዛ ነጥብ ላይ ጎንጥ ዘበኛዬ ብቻ እንዳልሆነ ገብቶኛል። የሚያስለቅሰኝ በትክክል ምን እንደሆነ እንጃ።

«ኸረ በመድሀንያለም?! » አለ ደንግጦ የሚያደርገው ጠፍቶት ። እጄን ሊይዘኝ እጁን ሲሰድ መንጭቄ ቀማሁት

«እንዳትነካኝ! ሁሉንም ነገር ታውቃለህ! ይሄን ሁሉ ጊዜ ስሰቃይ እያወቅክ ምንም እንደማያውቅ አብረህ ስታፋልገኝ ነበር። ሰውየው ያወራው ሁሉ ነገር ገብቶሃል። ንገረኝ አንተም የእነሱ ወገን ነህ? ምን ፈልገህ ነው?» እንባዬ ባይቆምልኝም ሰውነቴ ሲቆጣ ፣ ደሜ ሲሞቅ ይታወቀኛል።

«መድሀንያለም በሚያውቀው እንደሱ አይደለም!! አንች ያሰብሽውና የእኔ ድርጊት ለየቅል ነው!! ሀሳቤ ጠላትነት ከነበር ምን እጠብቅ ነበር? ከጠዋት እስከማታ እጀ ላይ አልነበርሽ?»

«አላውቅም! የሆነ የምትፈልገው ነገር ይኖራላ!!» ተነስቼ ከመኪናው ወረድኩ። ትንፋሽ እስኪያጥረኝ ድረስ ንዴቴ ያጨሰኝ ጀመር። የመኪናውን ጎማ በሃይል መጠለዜን ያወቅኩት የእግሬን አውራ ጣት ሲያመኝ ነው። የሆነ ውስጤ ተኝቶ የነበረ አውሬ የነቃ ይመስል የምቦጫጭቀው ነገር ፣ ቁጣዬን የምወጣበት ነገር ፈለግኩ። እሪሪሪ ብዬ መጮህም ፈለግኩ። የመኪናውን ኮፈን በቡጢ እየነረትኩ ማቆም እፈልጋለሁ ግን እጄን የምሰነዝርበት ቁጥር በጨመረ ልክ ሰውነቴ እየረገበ ፣ ቁጣዬ እየበረደ ስለተሰማኝ አላቆምኩም። ከመኪናው ወርዶ መምጣቱን ያወቅኩት አጠገቤ መጥቶ ሁለቱን እጄን ለቀም አድርጎ ሲያስቆመኝ ነው።

«አትንካኝ አልኩኮ!! » ብዬ ከመጮሄ እኩል በምን ቅፅበት እንደሰነዘርኩት ያልተቆጣጠርኩት ለቡጢ የተጨበጠ እጄ ጉንጩ ላይ አርፏል። ያደረግኩትን ሳውቅ ደንግጬ የመታሁበትን እጄን እንደበዓድ እጅ አየሁት። ከመኪናው ኮፈን ድብደባ ይሆን ከእርሱ ጉንጭ እጄ በልዟል። ወደኋላ ዞሮ አፉ ውስጥ የሞላውን ደም ከተፋ በኋላ ወደ እኔ እየዞረ በሱ ብሶ ይጮህ ጀመር
« ከበረደልሽ ድገሚኝ!! እ? በያ!» እያለ ለፀብ ይጋብዘኛል። ትቼው ወደመኪና ልገባ ስል እየተከተለ ሆነ ብሎ ይገፋፋኛል። «ይህችን ታህል ነው የተናደድሽብኝ? ለዝህችው ነው የጎፈላሽው?» ሲለኝ እንዴት ዥው ብዬ እንደዞርኩ አላውቀውም። እጄን ስሰነዝር በሚያስደነግጥ ፍጥነት በመዳፉ ቀለበው። ያልቆጠርኩትን ያህል ጊዜ ተከላክሎ አንዴ ነው አጓጉል ያገኘሁት። ዋጥ አደረጋት!! ቁጣዬ ረጭ ማለቱን ያወቅኩት ይሄኛው የድሮዋ ሜላት ማንነት መሆኑን መገንዘብ ስጀምር ነው።

«ደግ! አሁን ከሰከንሽ እየተጓዝን ስለኪዳን እናውጋ?» አለኝ የመታሁትን ጉንጭ እያሻሸ ወደመኪናው እየገባ
«ጉንጭህን አገላብጠህ ስለሰጠኸኝ እንዳምንህ ነው የምትጠብቀው?»
«እና ምን ይሁን ነው የምትይ? እዚሁ ቁመን ይምሽ? አንዱን አካሉን እዚሁ እንዲልኩልሽ ነው ያሰብሽ?» እየጮኸብኝኮ ነው። ከቃላት ሁላ በላይ ሆነብኝ እና አፌን ከፍቼ አፍጥጬ አየው ጀመር

«አንተ ግን የምርህን ነው? ካንተም ብሶ …….. » አልጨረስኩትም እየሮጥኩ መኪና ውስጥ ገባሁና ስልኬን አነሳሁ። አጎቴጋ ደወልኩ። ተከትሎኝ ገብቶ የማደርገውን በትኩረት ያያል።

«አጎቴ እናቴን አገናኘኝ እስቲ የሆነ ሳልጠይቃት የረሳሁት ነገር ትዝ አለኝ።» አልኩት

«እናቴ ? በቀደም <አምላክን በልመና አታድክሚ!!! የምትችውዪውን አድርጊና በተረፈው አመስግኚው!! ። ያመሰገንሽው አምላክ የጎደለውን ይሞላልሻል> ብለሽኝ ነበርኣ?»

«አዎ የእኔ አበባ ምነው?»

«አጎቴንም እንደዛው ስትዪው ሰምቻለሁኣ?»

«ሁሌምኮ የምለው ነገርኮ ነው ልጄ?» አለች ግራ እየገባት።

«የተለየ ትርጉም ነገር አለው እንዴ?»
«ኸረ ምንም ቅኔ የለውም ልጄ! ምን ጉድ ነው?»
«እንዲሁ ነው የሆነ ሚስጥር የያዘ አረፍተነገር ይመስል ውስጤ ተመላለሰ። ድንገት ሌላ መልዕክት ካለው ብዬ ነው።»
«በፍፁም! ሁሌም ሰዎች እጅ እግራቸውን አጣጥፈው በቀላሉ መስራት በሚችሉት ነገር ሁሉ ሳይቀር ፈጣሪን በልመና ሲያደክሙ እንደዛ እላለሁ። »

«እሺ በቃ እናቴ» ስልኩን ዘግቼ አስባለሁ። ምንም ሳይለኝ መኪናውን መንዳት ቀጠለ።

«እኔን አይደል የሚፈልጉት? እኔ ሄድላቸዋለሁ! እኔን የሚያደርጉትን ያድርጉና ወንድሜን ይለቁታል።» አልኩኝ ለራሴ ያሰብኩትን ድምፄን አውጥቼ እየተናገርኩት

«ህእ! አንቺን ቢፈልጉ እስከዛሬ ላንቺ የሚሆን አንድ ጥይት ጠፍቷቸው ይመስልሻል? ካንቺ በላይ የያዝሽባቸውን መረጃ ይፈልጉታል።» አለ <ቂል ነሽ እንዴ?> በሚል ለዛ

«ሊገድሉኝ ሞክረው የለ?»
«እኔን ከጠየቅሽኝ በፍፁም እነሱ አይመስሉኝም!!»

«እሺ ያለውን ቪዲዮ የምናገኝበት ፍንጭ ታውቃለህ? መቼም የማታውቀው ነገር የለም!» አልኩት አፍንጫዬን እየነፋሁ።
«አላውቅም!!» አለኝ በመድከም አይነት።

«ስለዚህ እሄዳለሁ። አትከተለኝም። እውነቱን እነግራቸዋለሁ።» አልኩኝ ፍርጥም ብዬ
«የማይደረገውን!!» አለ ኮስተር ብሎ

                            ............ አልጨረስንም ..........

@wegoch
@wegoch
@paappii
2024/09/22 07:45:25
Back to Top
HTML Embed Code: