Telegram Web Link
«እኔኮ ግን ለትናንት ስቃይህ ያበረከትኩት አንዳችም ነገር አልነበረም። በሙሉ ልቤ ከማፍቀር ውጪ የበደልኩህ አልነበረም። የእናትህን፣ የማዕረግን ፣ የወንድምህን፣ የእንጀራ እናትህን …… ሁሉንም እኔን አስከፈልከኝ። ነግረኸኝ ቢሆን ፍቅሬ አይጎልም እንደውም ይበልጥ አፈቅርህ ነበር።»

«አልገባሽም! እዛ ጨለማ ውስጥ ራሴን ከምመልስ ምንም አደርግ ነበር።» ላለፉት ዓመታት ያላለቀስኩት እንባዬ ሁሉ ይግተለተል ጀመር። ስቃዩ የሱ ሳይሆን የእኔ ይመስል ያባብለኝ ያዘ።

«እሺ ከዛስ?»

«ከዛማ አዲስን ከተበታተነበት እፍ እፍ ብዬ አራግፌ ገጣጥሜ አቆምኩት። እስር ቤት ሶስት ዓመት ከሁለት ወር እንደታሰርኩ በምህረት ተፈታሁ እና ከተበዳይ ቤተሰብጋ እርቅ መፈፀም ግዴታ ስለነበረብኝ ያን አደረግኩ። ወንድሜ እና ማዕረግ ድርጅቶቹን እንዳልሆነ እንዳልሆነ አድርገው በእዳ እና በቋፍ ሁለቱ ጭራሽ ተሽጠው። የቀረኝ እዳ እና ማሽኖች ብቻ ነበሩ።እነርሱ ከሀገር መውጣታቸውን ሰማሁ። ቤቴ ብቻ በእኔ ስም ስለነበር ተከራይቶ ኪራዩ ለእንጀራ እናቴ ገቢ እየሆነ ጠበቀኝ። ቤቴን ሸጬ እዳዎቹን ከፋፍዬ ሀ ብዬ ቢዝነሱን ጀመርኩ። አዲስ አዲስን ሰራሁ። ትናንት እና ትናንት ላይ የነበሩኝን ሰዎች ሁሉ ከማህደሬ ሰረዝኩ። ትንሽ ቢያታግለኝም እንደገና ወደመስመር ገባሁ። እሺ አሁን የምታለቅሺው ለምንድነው?»

«እኔእንጃ! አልወጣልኝማ!»

.......አልጨረስንም…….

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል ሀያ ……….)

«ትናንትህ ላይ በበደሉህ ሰዎች ነው ዓለምን በሙሉ እየዳኘህ ያለኸውኮ! በዙሪያህ ያሉ ሰዎች በሙሉ እንደእነሱ ናቸው ማለት አይደለም! በተቃራኒው የሆኑ ሰዎች አሉ። አንተ ያደረግከው ለማንም ምንም እድል አለመስጠትን ነው።» ከምሳ በኋላ ፀሃይ ቡና አፍልታ ሳሎን ቡናችንን እየጠጣን ነው ስላለፉት ውሳኔዎቹ የጀመርነውን የሀሳብ ልውውጥ የቀጠልነው።

«ካለፈው ውድቀትሽ ወይም ስህተትሽ መማር ማለት ታዲያ ምንድነው? ትናንቴን አልደግምም ማለት አይደል? ያለፈውን ስህተትሽን አለመድገም አይደል? ያለፈው ስህተቴ አለልክ ሰዎችን ማመኔ ፣ ያለገደብ ራሴን እስኪያሳጣኝ ከሰው ጋር መቆራኘቴ አይደል? ያንን ነው ያስወገድኩት!! የሰዎችን ስሜት ለውጥ፣ ክፋት ወይም ቅንነት ልትቆጣጠሪ አትችዪም። ልትቆጣጠሪ የምትችዪው የራስሽን ስሜት እና ራስሽን ብቻ ነው። ሰዎች ለምን እንደእኔ አልተሰማቸውም ማለት አትችዪም። በጠበቅሻቸው ልክ ሳይገኙልሽ ሲቀሩ እንዴት ማለት አትችዪም! ምክንያቱም እንዳንቺ ጥበቃ ሳይሆን እንደራሳቸው ስሜት እና እውቀት ነው ህይወታቸውን የሚመሩት። እነሱን መቀየር አትችዪም! አንቺ ስለእነሱ ያለሽን መጠበቅ እና ቅርበት ግን መወሰን ትችያለሽ!! ከማንኛውም የሰው ፍጡር ምንም ባለመጠበቅ ውስጥ እና ባለመተሳሰር ውስጥ ራሴን አትርፊያለሁ።»

«በፍፁም ከማንም ምንም አልጠብቅም ወይም በምንም ማንንም አልደገፍም አልያም ከማንም ጋር በስሜት አልቆራኝም ማለት አትችልም። ያንተም ህይወት ከዛ እጅግ የራቀ ነው። ለምሳሌ ከልጆችህ ጋር ያለህን ቁርኝት እየው! ለእነርሱ የምትሆነውን መሆን ለማንምና ለምንም ስትሆን አይቼህ አላውቅም! ሌላ ምሳሌ እንጥቀስ ቢያንስ በትንሹ ከሰራተኞችህ ጥንቅቅ ያለ ስራ ትጠብቃለህ! አንተ ባትኖር እነርሱ እንደማይኖሩት ሁላ እነርሱ ባይኖሩም ያንተ ቢዝነስ የለም!»

«የሆነ ጊዜ ነግሬሻለሁ መሰለኝ። በህይወት ውስጥ ለደስተኛነት ከመኖር ትርጉም ያለው ህይወት መኖር እንደመረጥኩ። ከዛ የጨለማ ውድቀት በኋላ ስነሳ ባለፈው አንቺ እንዳልሽው ደስተኛ ህይወት ለመኖር ዳከርኩ። እኔ ባለፍኩበት ዓይነት መንገድ ላለፈ ሰው ደስታ ከፍርሃት ጋር የተለወሰ ነው። እዛ የዝቅታ ወለል ላይ ደርሰሽ ካላየሽው ምን እንደምል ብዙም ላይገባሽ ይችላል። የሆኑ የሆኑ ጠርዞች አሉ ፍራሃትሽ የሚፈጥረውን ሀሳብሽን እና እውነታውን መለየት የሚያስቸግርሽ ጠርዝ። እሱ ጠርዝ ላይ መቆም አለብሽ ትግል አይጠቅምሽም። ምክንያቱም ያቺን ጠርዝ ካለፍሽ አለቀ። አዲሱን አዲስ መስራት ስጀምር ማን መሆን እንደምፈልግ እና ምን ዓይነት ህይወት መምራት እንዳለብኝ የራሴን የህይወት መመሪያና መርህ መቅረፅ ነበረብኝ። የማንንም ህይወት መኮረጅ አያዋጣኝም ነበር ምክንያቱም ማንም እኔ ያለፍኩበትን መንገድ አላለፈም። ለውጡ ይሄ ነው ያለማንም እርዳታ ሲሆን ራስሽን የሰራሽው ምርጫ አለሽ ምንና ማን መሆን እንደምትፈልጊ። እናም ደስታን ውስጤ ስፈልገው ከፍርሃቴ ጋር የተለወሰ ነበር እና በምትኩ የምኖርለት እና ትርጉም የሚሰጠኝ ዓላማ ላይ ራሴን ቢዚ ማድረግን ተማርኩ። ስለዚህ ልጆቼን እና ስራን እንደ ዓላማ ነው የምወስዳቸው።»

«በዚህ መጠን ትኩረት እና ጊዜ ለምትሰጠው ዓላማ ታዲያ ምንም ዓይነት የስሜት ቁርኝት የለኝም ማለት ትችላለህ?»

«ራሴን አያሳጣኝ እንጂ ትኩረቴን የማሳርፍበት ዓይነት ቁርኝት አይጎረብጠኝም። ጥያቄው የሚመጣው እኔን ጥያቄ ውስጥ ካስገባ ነው። ከራሴ እና ከምንም ወይም ከማንም መምረጥ ካለብኝ ራሴን ነው የምመርጠው። እውነቱንስ እናውራ ከተባለ ማንስ ራሱን አይደል የሚመርጠው?»

«እንዴ በፍፁም ራስህን የምትሰጥለት ሰው አለ። ኤጭ በምን ላስረዳህ ፍቅርን ታጣጥልብኛለህ እንጂ (ይሁን ቀጥዪ ዓይነት በእጁ እና በጭንቅላቱ ንቅናቄ ምልክት አሳየኝ።) እሺ! አይደለም ፍላጎትህንና ስሜትህን ነፍስህን ብትሰጠው worth የሚያደርግ የፍቅር ልክ አለ» ስለው ከት ብሎ ሳቀ

«መቼም ፍቅር እስከመቃብርን ወይም ሮምዮ እና ጁሌትን አትጠቅሺልኝም! ለስሜት ትስስር ብለሽ ሞትን ከመረጥሽ ቂል ነሽ ነው የምልሽ!! እኔና አንቺ እውነቱን አይደል የምናወራው? እስከሞት ልወድ የምችለው ራሴን ብቻ ነው!!» ብሎኝ ዊልቸሩን አንቀሳቀሰ። ስሜቱ ጥሩ ስላልነበር ለሁለት ቀን መጻፋችንን አቁመን ነበር።

«ለምን ዛሬ ቦታ አንቀይርም? እዚሁ እንፃፍ ወይም ውጪ!» አልኩት
«ውጪ አሪፍ!» አለኝ። ለፀሃይ ሳሩ ላይ ፍራሽ እንድታነጥፍ ነግሬያት ኮምፒውተሬን ላመጣ ወደ ላይብረሪ ሄድኩ። ፍራሹ የተነጠፈበት ዛፍ ስር የጥላው ቅዝቃዜ እና የቅጠሉ ቀዝቃዛ አየር እያጫወተን እሱ ትራስ ደራርቦ ተጋድሞ እኔ ቁጭ ብዬ መፃፍ ቀጠልን።

«ምዕራፍ አምስት!» ብሎ ሊቀጥል ሲል ሳላውቀው ጮህኩ።
«እንዴ? አራትን በአንድ ገፅ ልታልፈው አትችልም! ብዙ ያልተመለሱ ጥያቄዎች አሉኮ! ከዛ ሁሉ ድቅድቅ ጨለማ በኃላ አዲስን በቃ ሰራሁት ብለህ አንባቢን ልታሳምን አትችልም። ኸረ ደግሞ ፀዲን እና ሰብለን እዚህ ምዕራፍ ውስጥ ልናነባቸው አይገባም? ከቤተሰብህ ጋር እና ከማዕረግ ጋር የነበረህ ታሪክስ እንደዛው በእንጥልጥል ይዘጋል? »
«ኸረ ቆይ እሺ (ከት ብሎ እየሳቀ) የት ሄድኩብሽ አለሁ አይደል?» ብሎ ቀጠለ።

« ለተወሰነ ጊዜ የመረጥኩት መንገድ ራሴን በስራ ቢዚ ማድረግ ነበር። ጎን ለጎን ሙያዊ ድጋፍ ያስፈልገኝ ስለነበር ሳይካትሪስት ጋር ክትትል ማድረግ ነበረብኝ። በትክክል የሚጠቅመኝን ህክምና የሚያደርግልኝ ሳይካትሪስት ማግኘት እጅግ ከባዱ ነበር። አንዳንዶቹ ዝም ብሎ መስማት ይመስላቸዋል መሰለኝ ሙያው ማስታወሻ እና እስክሪብቶ ይዘው ያስለፈልፉኛል። አንዳንዶቹ የሚሰጡሽ ምክር ደግሞ ራሳቸው ምክር እንደሚያስፈልጋቸው ያሳያል። የብዙ ሳይካትሪስት ቢሮ እና ፊት ከጎበኘሁ በኋላ በትክክል ሙያውን የሚያውቅ ፣ ለእኔ የሚያስፈልገኝ ህክምና የቱ እንደሆነ የገባው ዶክተር አገኘሁ። ከጊዜ ወደጊዜ ለውጡን የምገነዘበው ዓይነት ነበር። ከህክምናው ጎን ለጎን ራሴን በማንበብ ጠመድኩ። ንባብ ስልሽ እገሌ የሚባለው ደራሲ እንዲህ ብሎ ፅፏል ወይም እንትን መፅሃፍ ላይ ያለው ገፀባህሪ ምናምን እያሉ ጥቅስ ለማጣቀስ የሚረዳ ማንበብ ሳይሆን ልኖረው የምችለው እና ከራሴ ጋር የማዋህደው እውቀት ፍለጋ ነበር የማነበው። ለምሳሌ ሰዎች ያነባሉ። አንድን ርዕስ ነጥለን ብንወስድ ስለይቅርታ እልፍ ጥቅስ ይጠቅሱልሻል። የማይኖሩትን ህይወት ሊመክሩሽ ይችላሉ። ነገር ግን በህይወታቸው ለመጎዳት ምክንያት የሆናቸውን ሰውጋ ይቅርታ ማድረግ ዳገት ይሆንባቸዋል። ያውቁታል እንጂ እውቀታቸው የእነርሱ አካል አይደለም ወይም አይኖሩትም። ከእውቀቴ ከስሜቴ ከህክምናዬ እና ካለፈው ልምዴ ጨምቄ የመኖሪያ መተዳደሪያዬን ፃፍኩ። በየቀኑ ያን ለመኖር ራሴን አሰለጠንኩ። አዲሱ አዲስ የዚህ ውጤት ነው። አለቀ!!» ብሎ ትንፋሽ ሰበሰበ። የምፅፈውን ገታ አድርጌ

«የተነበበ ሁሉ እኮ ግን አይኖርማ?»

«ያስማማናል። የትኛው እውቀት ብትኖሪው እንደሚበጅሽ የምታውቂው አንቺ ብቻ ነሽ!! የምርጫ ጉዳይ ነው።» አለኝና እንደገና ቀጠለ።
«ስለእነፀዲ ስለእውነት ምን መፃፍ እንዳለበት እንጃ!! ፀዲን መፅሃፍ መደብር ነው ያገኘኋት። እውነተኛ ሀቀኛ ግን የምትፈልገውን ጠንቅቃ የምታውቅ ብልህ ነበረች።በዛ ላይ ታነባለች። ለተወሰነ ጊዜ አብረን ካሳለፍን በኋላ ተጋባን። በጊዜ ብዛት የምትቀይረኝ ይመስላት ስለነበር ብዙ ታገሰችኝ። በተለይ ለልጅ የነበራት ፍቅር ግን በእኔ የምትቀይረው ዓይነት አልነበረም እና መለያየት መረጠች። አሁንም ቢሆን ጓደኛሞች ነን። አብረንም ሳለን ጓደኝነታችን ያመዝን ነበር። ከዚህ የተለየ ይሄ ነው የሚባል የተለየ ዓመታት አልነበረም። ሰብሊ ትለያለች በግልፅ ከስምንት ዓመት በኋላ ስለምትካፈለው ንብረት ብላ እንደምታገባኝ ነግራኝ ነው የተጋባነው። ቀጥተኛነቷን እወደዋለሁ። ጭንቅላቷ ያስባል። በባህል ወግ ሀይማኖት ተፅዕኖ ያልሳሳ ራሷን የሆነ ማንነት ነው ያላት። አልጋ ላይ ጎበዝ ናት! እውነት ለማውራት ለማቴሪያል ያላት ጥማት ትንሽ ከመጭነቁ ውጪ የማትሰለች ዓይነት ነበረች። እየቆየች ከእኔጋር ፍቅር እንደያዛት ነገረችኝ። ምላሹን እንደማታገኝ ስታውቅ ሂሳብ ሰራች። በዛ ላይ ዓለምን እየዞሩ ማየት ህልሟ ነበር። እኔ ደግሞ በተቃራኒው መብላት እና መጠጣት እንኳን እቤቴ የሚያስደስተኝ ሰው ነበርኩ። ሰለቸኋት! እንደሷ የመዞር አባዜ ካለበት አንድ ሀብታም ጋር ተጣብሳ ፈታችኝ።» ትንሽ እንደማሰብ ብሎ

«ስለማዕረግ እስከአሁንም ምንም መረጃ የለኝም። እውነት ለማውራት ማወቅም አልፈልግም። እንጀራ እናቴም ብትሆን ከዘመናት በኋላ ቢሮዬ አፈላልጋኝ እስከመጣችበት ቀን ድረስ የማውቀው ነገር አልነበረም። ይቅርታ ልትጠይቀኝ ነበር የመጣችው (በፌዝ ሳቅ አለ) አንተ ላይ ላደረስኩት በደል እግዜያብሄር ቀጥቶኛል። ልጄ እንኳን ይሙት ይኑር አላውቅም! አለችኝ»

«እና ምን አልካት? ይቅር ብዬሻለሁ አላልካትምኣ?» ያልኩት አስቤው አልነበረም። ከት ብሎ ሳቀብኝ
« የምታምኚው አምላክ ይቅር በሉ ይል የለ? አየሽ ቅድም ያልኩሽን? የምናውቀውን ሁሉ አንኖርም እናወራዋለን እንጂ እኔን ለበደለችኝ በደል አንቺ ስላመመሽ ይቅር መባል እንደሌለባት አሰብሽ።» አለኝ ሳቁን እየቀጠለ
«እግዜር ራሱ ይቅር የሚላት አይመስለኝም። ይልቅ ንገረኝ።»
«አላልኳትም። በተቃራኒው ውስጤን በጥሩ እምነት ሞልቼዋለሁ ብዬ ያመንኩትን የተጠራጠርኩት የዛን ቀን ነው። ያቺ ስትራመድ ሞገሷ መንገዱን የሚቀድላት የምትመስል ሴትዮ የእርሷ ያልሆነ ሰውነት እና አለባበስ አጅቧት ቢሮዬ ሳያት የማላውቀው ጭካኔ ነው የተሰማኝ። ዘበኞች ጠርቼ እንዲያስወጡልኝ ሳደርግ እያለቀሰች እንኳን ልቤ ምንም ርህራሄ አልተሰማውም። ለቀናት ስላየኋት ብቻ ስሜቴ ተረበሸ። ያለችበት ሁኔታ እንዳለችው ስቃይ ከሆነ ነፍሴ ደስታን መቃረም ስለሻተች እንዲያጣሩልኝ አደረግኩ። የማይሆን ባል አግብታ ቤቷን እና ንብሯቷን አሽጧት እንደእናቴ ሰካራም ሆና ከንቱ ህይወት እንደምትኖር ሰማሁ። ከዛ በኋላ ያየኋት ባለፈው እቤቴ ስትመጣ ነው። አደጋ እንደደረሰብኝ ስታውቅ ጮቤ እንደረገጠች አልጠራጠርም። ወይም ሽባ ስሆን የሚራራ ልብ ይኖረኝ ከሆነ ልታረጋግጥ ይሆናል። አላውቅም! ማወቅም አልፈልግም! ሳያት ሲኦል ነው ትዝ የሚለኝ!» አለኝ እየዘገነነው።

የሆነ ነገር ትዝ እንዳለው ሰው ብንን ብሎ። « የሆነ ቀን ቁጭ ብዬ ቴሌቭዥን ሳይ ሉሲን አየኋት። (ሳቅ ብሎ) ተዋናይ ሆና! በቲቪ ባየኋት በወራት ውስጥ ታዋቂ ሾው ላይ ኢንተርቪው ስትሰጥ ያልሆነ ነገር ተናግራ ህዝበ ኢትዮጵያ በስድብ ሲቀባበላት ከረመ። ባጋጣሚ ወሬውን ሰምቼ ፕሮፋይሎቿን ሳጣራ እያለቀሰች ህዝቡን ይቅርታ የጠየቀችበት ቪዲዮ አየሁ። የኛ ህዝብ የሚገመት ስድቡን እና ዘለፋውን ጨመረላት። ላገኛት ፈለግኩ ምናልባት ልጅ ስለነበረች ወይም አሁን አወዳደቋ ተሰምቶኝ፤ እድል ሰጥቻት ለምን ያንን እንዳደረገች መስማት ፈለግኩ። አገኘኋት! ያለችኝን አመንኩ። እሷ የእናቴ እና የእናቷ መጠቀሚያ ብቻ ነበረች። በሰዓቱ አባቷ ታሞ ብዙ ብር ያስፈልጋቸው ነበር። ያን እኔም አውቅ ነበር። አባቷን ለማዳን የሚጠበቅባት ያቺን ድራማ መስራት እንደነበር እና የቀረውን ተንኮል እና ማስረጃ እነርሱ እንደሚጨርሱት አሳመኗት። ያን በማድረጓ ለተወሰነ ዓመትም ቢሆን ለአባቷ እድሜ ቀጥላለታለች። የሚገርመው <አንተን ጎድቼ ባይሆን አባቴን ያተረፍኩት እመርጥ ነበር። ምንም አማራጭ በሌለበት ግን አባቴን በመምረጤ አልተፀፀትኩም! ለደረሰብህ ነገር ግን ይቅርታ!> ነበር ያለችኝ። (ፈገግ አባባሉ ስለሆነች የሚወዳት ልጅ የሚያወራ እንጂ መቀመቅ ስላስወረወረችው ልጅ የሚያወራ አይመስልም ነበር።)»

«ልገምት በህይወቷ ውስጥ የሆነ መልካም ነገር አድርገሃል?» አልኩት ከፈገግታው እየገመትኩ
«በጣም ዲፕረስድ ሆና ነበር። ከሀገር ወጥታ የምትማርበትን መንገድ አመቻችቼላት እንግሊዝ ነው ያለችው።» አለኝ
«ግራ የሆንክ ሰው ነህኮ!» አልኩት
«አውቃለሁ!! አትወጂውም ግን አንድ ሀሳብ አለኝ! ምዕራፍ አምስትን እኔ ልፃፈው! አንቺ ከፃፍሽው አስቢው በየመሃሉ የመልስ ምት ልትሰጪኝ ነው። ከፈለግሽ እኔ ልፃፈውና እያነበብሽ ማውራት እንችላለን!! ከዛ ደግሞ ስላንቺ ላንቺው መተረክ ደስ አይልም። ነፃነቴን አጊንቼ እራሴ ልፃፈው እና አንብቢው።» ልደርስበት የጓጓሁበትን ምዕራፍ ለመፃፍ ስለተከለከልኩ ከፋኝ ግን ደግሞ ነፃነት ያለውን አመንኩለት እና ቅር እያለኝም ቢሆን ተስማማሁ። ኮንፒውተሬን ዘግቼ ዝም ተባብለን ፍራሹ ላይ ጋደም እንዳልን ከንፋሱ ጋር ማውራት ያዝን

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ….. እኔ የቀጠልኩት
(ክፍል ሀያ አንድ…………….. meri feleke)

ፅፎ እስኪጨርስ እረፍት አጣሁ። አስሬ ላይብረሪ እመላለሳለሁ። ጣቶቹ አሁንም 100% ስላልሆኑ ቀስ ብሎ ነው የሚፅፈው።
«እሺ የፃፍከውን ላንብበውና ትቀጥላለህ?» እለዋለሁ።
«አይሆንም ህፃን አትሁኚ!» ይለኛል።
«ጮክ ብለሽ አታንብቢልኝ! የምትጠይቂኝ ነገር ከሌለ በቀር! ለራስሽ አንብቢው» ብሎኝ ሶፋው ላይ አጠገቡ እንድቀመጥ በእጁ እየመታ አሳየኝ። መስገብገቤ የሆነ እርቦት ውሎ ምግብ እንደሰጡት ርሃብተኛ ነው።

«ከድምፅ ጋር የተለየ ፍቅር አለኝ። ሰውን ሳላየው በድምፁ ብቻ መልክ እስላለሁ። ከድምፁ ቃና ፐርሰናሊቲውን መገመት ደግሞ የበለጠ ደስ ይለኛል። ሬስቶራንት ውስጥ ከጀርባዬ ድምፅዋን ስሰማው ጠይም ጎራዳ ፣ ጥርት ያለቆዳ ያላት ፣ ጥርሷ የሚያምር ፣ ከንፈሯ ስስ ……… ገመትኩ። ድምፅዋ ውስጥ የዋህነት ደግሞ ለዛ ሙሉነት ነበር በመጀመሪያ የሰማሁት። ዞሬ ሳላያት ከውጪ ከመጡ ተለቅ ያሉ ሴት ጋር ስታወራ ድንገት ድምፅዋ ወደ ቁጣ ሲቀየር ግን ቃላቶቿን ደምሬ ስሰማት የሆነች መብረር ፈልጋ ክንፎችዋን የፊጥኝ የተያዘች ነፍስ ያላት ሴት …… እድሉን ብታገኝ እልም ብላ የምትበር ዓይነት። ሲትየዋ ጥለዋት ሲሄዱ ዞሬ አየኋት እና ወንበር ቀይሬ አጠገቧ መጣሁ። መልኳን ከከንፈሯ እና ከቀለሟ ውጪ ብዙ አልሳትኩም። ቀይ ናት የጎራዳ ውብ፣ ቆዳዋ ከመጥራቱ የተነሳ ውሃ ስትጠጣ በረዥሙ አንገቷ ወደሆዷ ሲንቆረቆር ውሃው ኩልል ብሎ የሚታይ የሚመስል። ከንፈሯ ብዙ ስጋ የፈጀ አበባ የመሰለ ፣ ጥርሷ በድዷ ጥቁረት ደምቆ የሚያጥበረብር ፣ ሴት ልጅ ከኋላ የፀጉሯ ማብቂያጋ የተደፉ ሉጫ ፀጉሮች ሲኖሯት ባላውቃት እንኳን እጄን ሰድጄ መንካት ይቃጣኛል። እሷ ደግሞ ወደላይ ባስያዘችው ጥቁር ፁጉሯ ጆሮዋ ስር ድረስ ለጥ ብለው ንካኝ ንካኝ የሚሉ ሉጫ ፀጉሮች ነው ያላት። የዓይኖቿን ውበት ውስጡ በጉልህ የሚነበበው ሀዘን አደብዝዞታል።

ስለስብዕናዋ ግን ሁሉንም ልክ ነበርኩ። ለመነበብ የማትከብድ ያልተወሳሰበች፣ የዋህ፣ ለዛ ሙሉ፣ ልዝብ ያለች ፣ ስርዓት ያላት ግን ደግሞ ግልፅ ነገር፣ ባህልን ባታምንበትም ለቤተሰብ እና ለማህበረሰብ ግምት ብላ የምትኖርበት፣ ሀይማኖትን ግን አምናበት የምትከተል (ብዙ የማውቃቸው ሰዎች ሀይማኖት ያላቸው ሲኦል እና ገነት አለ ስለተባሉ ነው። ከክፋት የሚቆጠቡት ሲኦልን ፍራቻ እንጂ መልካም መሆን ምንም ሽልማት የለውም ክፉ መሆንም ምንም ቅጣት የለውም ቢባሉ ለክፋት የሚግደረደሩ ናቸው። በሰውነት ሰው ስለመሆን ሳይሆን እግዚአብሔር ወይም አላህ ወይም ሌላኛው አምላክ በክፋታቸው ይቀጣናል ፤ በመልካም ስራቸው ይሸልመናል ብለው ስለሚያምኑ ነው ሚዛን የሚሰሩት። እስኪ እውነት እናውራ ከተባለ የብዙ ሀይማኖቶች መደምደሚያ ከሞት በኋላ ያለ ሽልማት ወይ ቅጣት ባይሆን ምን ያህል ሰው ሀይማኖት ይኖረው ነበር? ምን ያህል ሰው ቅዱስ የሚለውን ስራ ለመስራት ይጋጋጣል? ምን ያህሉስ ሰው ወደሀይማኖት ተቋማቱ እየሄደ አቴንዳንስ ያስመዘግብ ነበር?) የሷን ሀይማኖተኝነት የምወድላት ቅጣትን ከመፍራት እና ሽልማትን ከመሻት ባለፈ አምላኳን በየቀን ህይወቷ ታምንበታለች።

እያወራን ሳለ የምትኖርበት ትርጉም ያጣች ጣዕም አልባ ነፍሷን ሰማኋት። ማምለጥ እየፈለገ የታነቀ ስብዕናዋን አየሁት። ሙሉ አደርጋታለሁ ብዬ አስቤ አይደለም። በህይወቴ ውስጥ ከዚህ በፊት የነበሩት ሴቶች ከሰጡኝ የተለየ የምትጨምርልኝም ነገር አለ ብዬ አስቤ አይደለም። እሷ ቤተሰቦቿን የምታስደስትበት ባል ትፈልጋለች። እኔ ደግሞ አጉል ባልከረረ ትስስር ቀኔን የምታጅብልኝ ሴት እፈልግ ነበር። የዛኑ ቀን እንጋባ አልኳት። በዛ ላይ በየቀኑ የምነካው የኋላ ቤቢ ሄር አላት። እያወቅኳት ስመጣ ባወቅኳት በደቂቃዎች ውስጥ እንድታገባኝ መጠየቄ ልክ መሆኑን አወቅኩ። ምንም ነገር ላይ የተሰማትን እና ያመነችበትን አስተያየት ከመስጠት ወደኋላ አትልም። የማታውቀውን ነገር አላውቅም ለማለት አታፍርም! እንደአዋቂ ለመታየት እና እኔን ለማስደመም ቅንጣት አትሄድም። ጠያቂነቷን እወድላታለሁ። ትጠይቃለች። መልሴ ካላሳመናት ለምን አዳር አይሆንም ትጨቃጨቀኛለች። ጭንቅላቴን ስለምትፈትነኝ ከሷ ጋር የማሳልፈውን ጊዜ እወደው ነበር። ገና ሳንጋባ አንድ የኑሮ ህጌን አስፈረሰችኝ። ሰውን እርዳታ መጠየቅ! ልታገባኝ ስትስማማ ሰርግ እፈልጋለሁ አለችኝ። ምክንያቷ ለራሷ ከእገሊት የተሻለ ሰርግ ነበረኝ ለማለት ወይም ሰርግ በራሱ ትርጉም የሚሰጣት ነገር ስለነበረ አልነበረም። በቤተሰቦቿ አይን ለመሙላት ፣ አጎደልኩባቸው ብላ ያሰበችውን ለመካስ ፤ ውርደታቸው ሆንኩ ብላ ያሰበችውን ክብር ልትደርብላቸው፣ በሷ ሰርግ እነርሱን ለማድመቅ ነበር እና እውነት ለማውራት አሳዘነችኝ። ሰው በ34 ዓመቱ የራሳቸውን ህይወት ኖረው ላገባደዱ ቤተሰቦቹ ይኖራል? ማስደሰት አንድ ነገር ነው። እሷኮ የህይወት ግቧም ፣ ስኬቷም ፣ ደስታ ሀዘኗም፣ ህልሟም፣ ትርጉሟም እነርሱ ናቸው። ዘመኗን ሙሉ በፈጠሩባት የትንሽነት እና የከንቱነት ስሜት ለእነርሱ ኖራ ራሷን ፕሩቭ ካላደረገች (የማለፊያ አረንጓዴ መብራት ካላሳይዋት) የራሷን ኖሮ መኖር እንደማይገባት ለራሷ አሳምናለች። እንኳን የራሴን ሰርግ ልደግስ የሰው ሰርግ የማልታደም ሰው ሰርግ ልደግስላት ተስማማሁ። ችግሩ ከእኔ ወገን የሆነ ሰርጌን የሚያጅበኝ ዘመድም ሆነ ጓደኛ አልነበረኝም። ወይም ማንንም በዛ ልክ ማቅረብ አልፈልግም።

የእኔ ሚዜ አልባ መሆን ወይም ዘመድና ጓደኛ አለመኖር ለሰርጉ የነበራትን ደስታ ወደጭንቀት ቀየረባት። ይሄም ለራሷ አልነበረም!! ዘመድ አልባ ባል አገባች ብለው ቤተሰቦቿ እንዳያዝኑባት እንጂ! 34 ዓመት አልጨበጥ ብሏት ስታሳድደው የኖረችውን ህልሟን በሳምንታት ላስቀይራት አልችልም ነበር። በህይወቴ ውስጥ ከምጠላቸው ዋና ዋና ነገሮች ውስጥ አንዱን አደረግኩ። ስራ ቦታ አብረውኝ ብዙ የሰሩ የስራ አጋሮቼን ሚዜ እንዲሆኑኝ ጠየቅኩ። በእርግጥ ከስራ ውጪ ማርስ ላይ ልደር ወይ ጎዳና፣ ሚስት ይኑረኝ ቅምጥ ምንም መረጃ ለሌላቸው ለብልጫዎቹ የስራ ባልደረቦቼ የቅርበት ምልክት አድርገው ስለወሰዱት በደስታ ነበር የተቀበሉኝ። የስራ ህይወቴን እና የግል ህይወቴን ማዳቀል የፈጠረብኝን መወላገድ ድጋሚ ልደግመው ስለማልፈልግ የግል ህይወቴን በአድራሻም በወሬም አርቄ ነው ያኖርኩት የነበረው። ተጋባን!!

መጀመሪያ ላይ ድንበሩን የጠበቀ፤ ያልከረረም ያልላላም፣ ያልሳቀም ያልተኮሳተረም፣ የማያቃጥልም የማይበርድም ዓይነት ትርጉም የነበራቸው ዓመታት ነበረን። እንደአብዛኛዋ ሴት ስም ያለው ቦርሳ መሸመት ፤ አዲስ የወጣ ፋሽን ልብስ እና ጫማ አሳዶ ማጌጥ ፣ አዲስ በተከፈቱ ሬስቶራንቶች መታየት ፣ ፊቷን ሜክአፕ ለመሰራት ጊዜ መፍጀት …….

አታውቅበትም። የመኪና መንጃ ፈቃድ እንኳን ያወጣችው እኔ ጨቅጭቄያት ነው እንጂ ራሴው ነበርኩ የማመላልሳት። ከመሰረታዊ ነገሮች ውጪ ገንዘብ ካወጣች ባትነግረኝም አውቃለሁ። ለቤተሰቦቿ ነው!! ገንዘብ አንዱ የነፃነት በር መሆኑን ባውቅም ከሚያስፈልገኝ ውጪ ባለ ትርፍ ገንዘብ የሚያሳምነኝ ምክንያት ይሁን እንጂ አልሳሳም። ለፍቼ ያመጣሁት ገንዘብ ነውና ሚዛን በማይደፋ ምክንያትም እንዲበተን አልፈቅድም። (ገንዘብ የነፃነት በር ነው ያልኩት በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ለነፍሳችን አስተዋዕፆ ስላለው ነው። እንደአለመታደል ሆኖ ሀይማኖቶቻችንም ሆኑ ባህሎቻችንን ድህነትን የሚያሞካሹ እና ገንዘብን ልክ ከአምላካቸው ወይ ከስርዓታቸው ወይም
ከደስታቸው የሚያርቅ መዓት አድርገው ይጠምዱታል። ድህነት ውስጥ ደስታ ያለ ሀብት ደግሞ እንቅልፍ አልባ ለሊቶችን ያቀፈ አድርገው ስለነገሩን ሁሌም ገንዘብ ያለው ሰው ለገንዘቡ ሲል በደልን የፈፀመ እንቅልፍ አልባ ምስኪን ይመስለናል። ያለኝን ህይወት እወደዋለሁ። ማድረግ የምፈልገውን ነገር ማድረግ በፈለግኩ ሰዓት ማድረግ መቻሌን እወደዋለሁ። ከማንም ምንም ፈልጌ አላጎበድድም። ከማንም ምንም ስለማልፈልግ ድንበሬ ይከበርልኛል። ሰውኮ እንዲህ ነው …….. በተለይ በኢኮኖሚ እንደተደገፍከው እና የእሱ መኖር እንደሚያስፈልግህ ሲያውቅ ከሱ በምታገኘው ጥቅም ክብርህን ሊገዛህ ይዳዳዋል። በማጣትህ ሽንፈት ይጠቀምበታል። ገንዘብ ይሄን ነፃት ይሰጥሃል። በማንም በምንም ተሸናፊ ያለመሆንን። ከዚያ በተጨማሪ ገንዘብ ስላለኝ ነው ከእስርት ዓመታት በላይ የጭንቅላቴን ውጥረት ማርገብ በፈለግኩ ሰዓት የምሄድበት ዶክተር ያለኝ። ብዙ በተለያዩ ትራውማ እና የአዕምሮ ህመም እየተሰቃዩ አቅሙ ስለሌላቸው መታከም ያልቻሉ ሰዎች አሉና)

ግንኙነታችን ያሰመርኩትን መስመር መች እንዳለፈ አላውቅም። ከአራት ዓመታት በኋላ የሆነ ቀን እንደተለመዱት ምሽቶቻችን ልንተኛ ስንል የከንፈር ብቻ ያልሆነ መሳም ሳመችኝ። ስትስመኝ ወፍራም ከንፈሯን እወደዋለሁ። የዛን ቀን ከተለመደው ስሜት ውጪ ለእኔ መልዕክት ያደረሰ መሳም ሳመችኝ። አስቁሚያት መሳሟ ለውጥ እንዳለው ስነግራት ለውጡ እንዳልተሰማት ነገረችኝ። የዛን ቀን ለመግለፅ የሚከብድ ቅር የሚል ስሜት ተሰማኝ። የሆነ ያልተለመደ ወይም የረሳሁት ቅሬታ!! ከዚህ ስሜት በኋላ ብዙም ባልራቀ ቀን አልጋችን ላይ ጨዋታና ፍቅር ደርበን እየፈተልን

«እኔ ከዚህ በላይ ማስመሰል አልችልም! ከአቅሜ በላይ ነው የምወድህ!» አለችኝ እንደገረፉት የሁለት ዓመት ህፃን ልጅ ህቅ ህቅ እያለች። የሆነ መኪናዬን እየነዳው ተጋጭቶ ኤርባጉ ተነፍቶ ፊቴን ሲጠልዘው ያለው ዓይነት ስሜት ነው የተሰማኝ። ያ ስሜት እንደነበራት ባትነግረኝም አውቀው ነበርኮ የማላውቀው ከአፏ ሲወጣ እኔጋ ሊፈጥር የሚችለውን ስሜት ነበር። እንጂማ ብዙ የማውቃቸው ሴቶች ብለውኛል። የማናቸውም እኔጋ የፈጠረው ስሜት አልነበረም። የተሰማኝ ፍቅር አይደለም። ፍርሃት ነበር።»

(ይሄን ሳነበው ልቤ ዝቅ ሲልብኝ ተሰማኝ!!)

«ማብራራት የሚከብደኝ የማጣት ዓይነት ፍርሃት ፤ ላላስታውሰው ረስቼዋለሁ ያልኩት ድሮዬ ላይ የማውቀው የመለየት ፍርሃት ፤ የዛሬውን አዲስ ከአንድ ጠጠር እና አሻዋ ጀምሬ ከመገንባቴ በፊት ሰውነቴን የወረረኝ መሸነፍ!! የምትፈልገውን እንድታደርግ እና በፈለገችው ቁልምጫ እንድትጠራኝ ፈቅጄላት የመጨረሻዬ እንደሆነ የወሰንኩትን ፍቅር ሰራን። ደረቴ ላይ ሆና የፈገገ ፊቷን ሳትመልሰው እንቅልፍ ወስዷት ምን እንደማደርግ ሳስብ አደርኩ። ከራሴ በላይ እንዳላጣው የምሳቀቅለት ነገር እንዲኖረኝ አልፈልግም!! ከማዕረግ በኋላ ያለው አዲስ ስሜቱንም ውሳኔውንም ለማንም ለመናገር አይደለም ሊፈራ ሁለቴ አያስብም ነበር። አዲስ ፍርሃትን ከላዩ ከገፈፈ ዓመታት ተቆጥረዋል። የተሰማኝን ልነግራት መጨነቄ ይበልጥ ያለሁበትን ሁኔታ እንድጠላው አደረገኝ።

የኑሮ ዋና መርሄን ተፈታተነችው! በስሜቴ ከእኔ ውጪ ማንም አያዝበትም የሚለውን!! አዲሱ አዲስ ስሜቱ ራሱ የሚያዘው ፤ ማንም የማይሰለጥንበት ነው። አልነገርኳትም! በነገታው የእርሷን በቅርቤ መኖር ጠላሁት! ራሴን እንዳላዘው እየሆንኩ እንደሆነ ገባኝ። ትቻት ሌላ ክፍል ተኛሁ። እንቅልፍ ግን አልወሰደኝም። በመሃል በሩን ከፍታ መኖሬን አረጋግጣ ስትመለስ እሰማታለሁ። ሲነጋላት መጥታ

«……… ላፍቅርህ ብዬ ነው ወይ ያፈቀርኩህ? ለምን ትቀጣኛለህ?» ስትለኝ ውስጤ ሲረበሽላት ሰማሁት። ከማዕረግ ውጪ ለማንም ያልሆንኩት መሆን ስሆነው ታወቀኝ። ያ ስሜት ደግሞ ከደስታው በላይ ስቃይ እና ሰቀቀኑ ነው ትዝ የሚለኝ። «እንፋታ» ስላት ራሴን ሰማሁት። ከዛ በኋላ ለሳምንታት ከልቧ ልታወጣኝ እየታገለች መሰለች። አብራኝ መዓድ ብትቀመጥም ብዙ አታወራም!! ያሰብኩት ወይም የተመኘሁት ልክ እንዳልሆነ ፀዲ ስትደውልልኝ ገባኝ! ፀዲ የደወለችልኝ ቀን እራት ላይ ፀዲጋ እንደሄደች ስትነግረኝ የማውቀው ነገር በመሆኑ አልተገረምኩም። የተገረምኩት አድርጋ የማታውቀውን ሜካፕ እና ሊፒስቲክ ፊቷ ላይ ማየቴ ነበር። እቤት ውስጥ በቱታ ወይ በቁምጣ አልያም በኔ ቲሸርቶች እንጂ የማውቃት ቀሚስ ለብሳ አላስታውስም! የእኔን ትኩረት ለመሳብ መሆኑን ሳስብ አሳዘነችኝ። ያንን ግን እሷ እንድታውቀው ማድረግ አልፈለግኩም። በነጋታው ሀኪሜጋ ሄጄ የተፈጠረውን ነገርኩት።

«ወደሃታል! በፍቅር መሸነፍን እንደድክመት የምታይበት የራስህ በቂ ምክንያት አለህ ያን እረዳልሃለሁ! ግን ይህችኛዋ የተለየች ብትሆንስ? ከመስበር ይልቅ የምታጎብዝህ ብትሆንስ? ከእውነቷ የምታፈቅርህ ብትሆንስ? » አለኝ

«ዶክተር ባትሆንስ? ብትሆንስ በሚል ግማሽ እምነት ባትሆን የማጣውን መቋቋም አልችልም።»

«በባትሆን ፍርሃትህ በፍቅር ውስጥ ያለውን ደስ የሚል ህይወት ራስህን እያሳጣኸው ነውኮ! ራስህን እየቀጣኸው ነው!»

«am fine ፍቅር በሚሉት ግማሽ ደስታ ግማሽ ሰቀቀን ያለበት እሳት መጫወት ለጊዜው ምርጫዬ አይደለም። ደስታው ይቅርብኝ እና ሰቀቀኑንም ይዞልኝ ይሂድ!» አልኩት ተነስቼ ቢሮው ውስጥ እየተንጎራደድኩ።

«አዲስ! እንዳንተ በጥንካሬ የማይታለፈውን ያለፈ ሰው አላውቅም። የምትኖራቸው ህጎች እና መርሆች ስለፈወሱህ I appreciate that! ከነዚህ ዓመታት በኋላ እንኳን ይሄን ሁሉ በራስ መተማመንህን እና የገነባኸውን እውቀት የሚከድን ፍርሃት ካነቀህ አሁንም ከትናንት ህመምህ አልዳንክም! ስለሸሸኸው ደግሞ አታመልጠውም! እባክህ አስብበት! ደጋግሜ ከዚህ በፊት እንዳልኩህ እሱን ፋይል ገልጠህ ለማውራት ራስህን አዘጋጅ!» አለኝ

ያን ህመም ቀስቅሼ ላወራ መቼም አልዘጋጅም!! የሬሳ ሽታ፣ የጨለማ ጣር ፣ የሚያደነዝዝ ድምፅ……… ያለበትን ፋይል ከፍቼ መተንፈስ አቅቶኝ መንፈራገጥ የቅርብ ዓመታት እቅዴ ውስጥ አልነበረም!! ወደቤቴ ተመልሼ ላለፉት ሳምንታት እንደተለመደው ዓይነት መግባት መውጣቴን ቀጠልኩ። የሆነ ቀን እራት ላይ ሳትመጣ ቀረች። ፀሃይን እንድትጠራት ስጠይቃት።

«አሟታልኮ ተኝታ ነው የዋለችው! አላስተዋልካትም እንጂ ምንም ደህና አይደለችምኮ! እንደው በማያገባኝ መግባት አይሁንብኝና እንደው በመሃከላችሁ ምን ክፉ ዘልቆ ነው?»

«ገባሽ ፀሃይ! በማያገባሽ ገባሽ!» ብያት ወደመኝታ ቤት ላያት ሄድኩ። ስታለቅስ እንደዋለች ታስታውቃለች። እንፋታ ካልኳት ቀን በኋላ በትኩረት ያየኋት የዚህን ቀን ነው። ከሰውነቷ መክሳት የፊቷ መገርጣት አስደነገጠኝ። አጠገቧ ሄጄ ስነካት ታተኩስ ነበር። እጠይቃታለሁ። አትመልስልኝም! ክፍሏ በታመቀ አየር ተሞልቷል። መስኮቱን እየከፋፈትኩ ሀኪም ቤት እንድወስዳት ደጋግሜ ጠየቅኳት። ቃል አልመለሰችልኝም። ፊቷን አዙራ በትራሷ ተሸፈነች። እራሴን ከመውደዴና ከፍርሃቴ ያየለ ስሜቴ አቅፌ ምን ሆንሽብኝ? ሁላ ልላት እያመነታብኝ ተንጎራደድኩ። ኮቴዬን እየሰማች እስክወጣላት እንደምትጠብቅ ነገር በትራሷ እንደተከለለች ዝም አለች። ይሄኛው አዲስ ስሜቱን መለየት ተቸግሮ አያውቅም ነበር። ዝብርቅርቅ ያለ ስሜት ተሰማኝ። ጠልታኛለች ልታየኝም ልታናግረኝም የማትፈልግበት ደረጃ ደርሳለች። ግን ደግሞ ብትጠላኝ እንዲህ ትጎሳቆል ነበር?»
«ፊቴን አዙሬብህ አልነበረም! (የዛኔው ህመሜ ከማንበቤ ጋር መጣ) ባለቅስም እንደማታዝንልኝ አስቤ ሳታየኝ በትራሱ ተሸፍኜ እያለቀስኩ ነበርኮ!» አልኩት በቀዘቀዘ ድምፅ። እጁን ሰዶ የኋላ ቤቢ ሄሮቼን መነካካት ጀመረ።

«የትኛው ምን አይነት ስሜት እንደሰጠኝ አላውቅም። ብትጠላኝ እና አልፈልግህም በቃ ብላ ጥላኝ ብትሄድ ደስ ይለኛል። ግን ሙሉ በሙሉ ደስ ይለኛል? በእኔ ምክንያት እንዲህ መሆኗ ደግሞ የሚያስጠላ ስሜት ሰጠኝ። ለተከታታይ ቀናት እኔ ያለሁበት ላለመሆን ወሰነች። ፀሃይን ደህና እንደሆነች ስጠይቃት

«ዛሬ ምንም አትል! ቅድም አየር ልትቀበል ብቅ ብላ ነበር» አለችኝ። ልታየኝ አለመፈለጓን አከበርኩላት!!! ከቀናት በኋላ ግን አባቷ ሞተው በለሊት ደውለው መርዶውን ሊነግሯት ሽማግሌዎች እንደሚመጡ ነገሩኝ! ሳሎን ቁጭ ብዬ ስጠብቃቸው ሊነጋጋ ገደማ መጡ! ገና እሷ መርዶውን ሳትሰማ በፊት እጄ እና እግሬ ሲንቀጠቀጥ ይታወቀኛል። ሳሎን ብቅ ከማለቷ ሰዎቹን ስታያቸው የተፈጠረውን አውቃለች መሰለኝ በቁሟ ተገነደሰች። የሚርበተበት ሰውነቴ እንዴት እንደታዘዘልኝ አላውቅም። መሬቱ ላይ ከመውደቋ በፊት እጄ ደረሰ።

እስከዛሬ የሆንኩትን ሁሉንም በአንዴ ሆንኩት። እናቴ ሬሳ ላይ ስደርስ ከአፌ ቃል አልወጣ ብሎኝ ያማጥኩትን ከነሬሳ ሽታው፣ ማዕረግ ወንድሜ ክፍል ስትሳለቅብኝ ያደረግኩትን ፓኒክ ፣ ማዕረግ ወንድሜን እንዳገባች የእንጀራ እናቴ ከነገረችኝ በኃላ የከደነኝ ጨለማ ……. የለም ብዬ ያመንንኩትን እግዜር ለመንኩላት። <እሷ የምታምንህ አምላክ ካለህ ምንም አታድርጋት! ለእኔ ብለህ ሳይሆን ለእርሷ ብለህ ስማኝ ምንም አትሁን!> አልኩት። ሆስፒታል ተሰናብቻት እንደወጣሁ ታክሲ ጠርቼ ዶክተርጋ ሄድኩ።

. አልጨረስምንም .

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሰይጣን ወይ እግዜር የጀመሩት ………. እኔ የቀጠልኩት

(የመጨረሻው ክፍል)

ሜሪ ፈለቀ


«ዶክተር ራሴን ሀኪም ቤት ካገኘሁት አልድንም ይብስብኛል እመነኝ! ትንሽ ቀን አይተኸኝ ከባሰብኝ ቃል እገባልሃለሁ ራሴው ሄዳለሁ» አልኩት። ከህክምና ጣቢያ ህክምናዬን መከታተል እንዳለብኝ ሲነግረኝ
እቤቱ ይዞኝ ሄደ። በዚህ ጊዜ እንዳለፈው ለማላውቀው ጊዜ ያህል ጨለማና ፍርሃቴ ውስጥ አልነከርም!! አስፈሪው ደቂቃ ትንሽ ነው። ያቃተኝ እንቅልፍ ሲወስደኝ የምቃዠውን ቅዠት ነው። የእናቴ ሬሳ ሆኖ ይጀምራል። በእጄ እንደታቀፍኳት ማዕረግ ትሆንብኛለች። ወይም ሚስቴን! በሌላኛው ቀን ደግሞ ልክ የአባቷን ሞት ስትሰማ እጄ ላይ እንደወደቀችው ስትወድቅ እጀምራለሁ። እንደታቀፍኳት ወይ ማዕረግን ወይ እናቴን ትሆንብኛለች። ለቀናት መተኛት ፈራሁ። ዶክተር መድሃኒት አዘዘልኝ። ለሳምንታት እሱጋ ቆየሁ። አሁንም ግን እሱ የሚለውን ፋይል ለመክፈት ዝግጁ አልነበርኩም! እቤቴ ለመመለስ ዝግጁ ስሆን ተመለስኩ። ከተመለስኩ በኃላ የአባቷን ለቅሶ አብሬያት ስላልነበርኩ ታኮርፈለች ብዬ ስጠብቅ ጭራሽ የእኔ ደህንነት አሳስቧት ደህና መሆኔን ትጠይቀኛለች። ትታኝ እንድትሄድ እፈልጋለሁ። ግን ደግሞ ራሷ ጠልታኝ እንድትሄድ እንጂ በእኔ ምክንያት ከሆነችው መሆን ሲደመር ከአባቷ ሀዘን ጋር ሌላ የከባድ ሀዘኗ ሰበብ መሆን አልፈልግም! ያን የማላደርገው ራሴን ላለመጉዳት ይሁን እሷን አላውቅም። ምናልባትም እናቴ እንዳስታቀፈችኝ አይነት ፀፀት ድጋሚ ላለመሸከም ፈርቼም ይሆናል።
ተናግሬ በማላውቃት ለቤተሰቦቿ በምትልከው ገንዘብ ተናገርኳት። የማትደራደርበት ዋልታዋ ስለሆነ ከጠላችኝ በላይ የምትጠላበት ምክንያት ያቀበልኳት ነበር የመሰለኝ። ትጥላኝ ትውደደኝ አላውቅም ግን ትታኝ አልሄደችም። ከሆነ ጊዜ በኋላ ማታ ላይ እራት ልበላ ተቀምጬ ምስቅል እንዳለች ወደሳሎን ገባች። የእናቷን ቤት መወረስ ስትነግረኝ ደነገጥኩ። አላወቅኩም ነበር! ስለእውነት ትኩረት ሰጥቼም ብሩ መከፈል ማቆም አለማቆሙን አላስተዋልኩም! ከእኔ ቃል እና ከእናቷ የእኔን ቃል እንደምታከብር ልገምት አልችልም ነበር። እያለቀሰች ትታኝ ስትገባ ተከትያት መሄድ ፈለግኩ። ለቀናት ሸሸኋት። ይሄ የመጨረሻዋ ይሆናል ብዬ ጥላኝ እንድትሄድ ስጠብቃት የሆነ ቀን ጠዋት ትታኝ እንደማትሄድ ቁርጥ አድርጋ ነገረችኝ። ዓመቱን ጠብቃ ብሯን ተካፍላ እንደምትሄድ ነገረችኝ። ንግግሩም ሀሳቡም የእሷን ስለማይመስል ግራ ገባኝ። ከፈለግክ አንተ ፍታኝ ብላኛለችኮ እንድትሄድ እፈልግ የለ? ለምንድነው በቃ እንፋታ ማለት ያቃተኝ? ለራሴኮ ደጋግሜ እነግረዋለሁ። እሷን አጊንተህ ራስህን ከምታጣ እና እሷን አጥተህ ራስህን ከምታተርፍ የቱ ይበልጥብሃል? ሁለቱንም በራሴ መወሰን አቃተኝ እሷንም ማጣት ፈራሁ ራሴንም ማጣት ፈራሁ። እሷ እንድትወስንልኝ ፈለግኩ። ራሷን ይዛልኝ እንድትሄድ!! ያገባኋትን ቀን ረገምኩ! አብረን ያሳለፍናቸውን ዓመታት ረገምኩ። የሆነ ቀን ያለወትሮዬ እሷን ሳላገባ በፊት አልፎ አልፎ የምሄድበት ባር ሄጄ ስጠጣ ድሮ እንጎዳጎድ የነበረች ኤክስ ተንጎዳጓጄን አገኘኋት። ድንገት የመጣልኝ ሀሳብ ከሷ ጋር ወደቤት መሄድ! ሊፈጠር የሚችለውን አሰላሁ። እንዴት ሴት ይዘህብኝ መጣህ ብላ በተደፈርኩ ትቀውጠዋለች ፣ ምንም ሳይመስላት ታልፋለች ፣ ትቀናለች ፣ ትከሰኛለች ……….. ምንም ሳትል ተነስታ ጥላኝ ትሄዳለች። አንዱ ይሆናል ወይም የቱም አይሆንም ብዬ ሄድኩ። ብቅም አላለችም!! ምንም ዓይነት ከሴት ጋር የመነካካት ፍላጎቱ ስላልነበረኝ ትንሽ እንደተጫወትን ተኛን። በነገታው ከሰዓት ማታ የተፈጠረውን እንዳወቀች የእርሷ ባልሆነ ስርዓት የለሽ ንግግር ነገረችኝ።
እዚህጋ ጥላቻዋ በደንብ ይታይ ነበር። የመከፋት ሳይሆን ከእኔ ከዚህ የተለየ እንደማትጠብቅ ዓይነት ንቀት ያለበት ነበር አነጋገሯ። እንድትጠላኝ አይደል ስፈልግ የነበረው? ደስታ ግን አልተሰማኝም! የዛን ቀን የእረፍቱ ቀን ቢሆንም ዶክተርጋ ደወልኩ። በምልልሳችን መሃል።
«አዲስ! የጥንካሬዬ መሰረት ናቸው የምትላቸውን መርሆችህን ማጣት መጀመርህን እያስተዋልክ ነው? እሷ ከህይወትህ እንድትወጣልህ መፈለግህ አንድ ነገር ነው። ከእርሷ እና ከራሴ ራሴን መረጥኩ አልክ እንጂ እሷንም ራስህንም እያጣህ ነው። ስሜትህን ለመካድ ወይም ለመሸሽ ስትል በጤነኛ ጭንቅላትህ የማታደርጋቸውን ነገሮች እያደረግክ ነው። አልመረጥክም አዲስ!» አለኝ።
ስለእርሷ መሄድ ወይም መቅረት እዚህና እዛ የሚረግጠውን ውል የለሽ ሀሳብ እና ስሜቴን ለማደብዘዝ ስራ እና መፅሃፎቼ ውስጥ አብዝቼ ጠለቅኩ። አብራኝ አትበላም። ላይብረሪም አትመጣም። ከክፍሏ አትወጣም!! አንድ እሁድ ልጆቼ ጋር በሄድኩበት እዛው መጣች። ልጆቼ እሷን ሲያዩ እየተንደረደሩ እናታችን መጣች ብለው ተጠመጠሙባት። በእነርሱ ፊት የተኳረፈ መምሰል ስላልፈለግኩ ጉንጯን ሳምኳት። የሳምኳትን ቦታ በእጇ ዳብሳ ፍዝዝ ብላ ቆመች። ለመጀመሪያ ጊዜ እንደሳምኳት ነገር። ከልጆቹጋ እየተጫወትኩ ትኩረቴን ከሷ ላይ ማንሳት አቃተኝ። ፍዝዝ ብላ እያየችኝ አይኗ እንባ አቀረረ። ደረስ መለስ የሚለው ፍርሃቴ ተመለሰ። ልጆቹን ማጫወት ትቼ እሷን ማባበል አማረኝ። አሁንም ድረስ አልጠላችኝም። ይሄን ሁሉ አድርጌያትም አልጠላችኝም! የዛን ቀን ተጨማሪ በደል ላልበድላት ለራሴ ቃል ገባሁ! መቆየት እስከፈለገች ጊዜ ትቆይ መሄድ በፈለገች ቀን ትሂድ! አልኩ። ራሴን ረገምኩላትኮ! ከአሁን በኋላ ላልከፋባት ራሴን አስጠነቀቅኩላት!! ማታ ላይ ሻይ ልትወስድ ከክፍሏ ስትወጣ ያለቀሱ አይኖቿ አባብጠው ደፈራርሰዋል። ሳሎን መኖሬን ስታይ እንዳላያት ፊቷን ደበቀችብኝ ግን አይቻታለሁ።»
እያነበብኩ አንገቴ ላይ የሚርመሰመስ እጁን አንድ እጄን ልኬ ያዝኩት። የመከልከል ሳይሆን የመደረብ። የሰርጉ ቀን አጋጣሚ ላይ ስደርስ መጮህ ቃጣኝ።
«የረሳሁትን ሳቋን ተፍለቀለቀች። አውርቶ ሳይጨርስ ይግባባሉ። መቼ ነበር እንዲህ ደስተኛ የነበረችው? እሩቅ!! የማላስታውሰው ቀን ላይ ነበር እንዲህ ስትፍለቀለቅ ያየኋት ! ይሄን ሳቋን ቀምቻታለሁ። በአንድ በኩል ራሴን ረግማለሁ። በሌላ በኩል ደግሞ እንዲህ የተፍለቀለቀችለት ሰው እኔ ብሆን ብዬ አስባለሁ። ሰው እንዴት ሁለት ጠርዝ ላይ ያለ ስሜት እኩል ይሰማዋል? በጣም ስቀርባትም የምትፈጀኝ ስርቃትም የምትፈጀኝ ዓይነት ነገር ናት። መሃል ስሆን ደግሞ እሷን የምጎዳት!! ቀስ ብዬ ወጥቼ ወደቤት ሄድኩ። እቤት ሸኝቷት በሩ ላይ ከመኪናው ስትወርድ አቅፎ ሲሰናበታት አየኋቸው። ፍልቅልቅ ፊቷ አልተለያትም። »
«አንተኮ ቆንጆ ሆነሻል ስላልከኝ ነው እንደዛ ደስ ብሎኝ የነበረው! ለማዕረግ ያልካትን ታስታውሳለህ? ለእኔም የወንድ መለኪያዬ ነበርክኮ አድስዬ! ያንተን ሚዛን ተለካክቶ አይኔን የሚሞላ ማንም አልነበረም! (ለምን ዝም ብለሽ አታነቢም? ዓይነት አየኝ) እሺ ከአሁን በኋላ ዝም ብዬ አነባለሁ!» ብዬው ማንበቤን ቀጠልኩ።

«ውስጤ ያለው ብዙ ስሜት ቢሆንም ጎልቶ የሚሰማኝ ንዴቴ ነው። ማን ላይ እንደተናደድኩ አላውቅም! በትክክል በየትኛው ምክንያት እንደተናደድኩም አላውቅም!! ተነስቼ ወጣሁ። ድብልቅ ያለ አወዛጋቢ ስሜት ናጠኝ። ከሷጋ ለመጨረሻ ጊዜ ከሁለት ዓመት ከምናምን በፊት ለመጨረሻ ጊዜ ካደረግነው ጉድጉድ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ከሆነች ሴት ጋር መሆን ፈለግኩ። በትክክል ምን ፈልጌ እቤት እንዲሆን እንደፈለግኩ አላውቅም! አብራኝ ያለችው ሴት የሆነ ነገር ያደረገችኝ ይመስል እንግልት የበዛበት ነገር እያደረግኳት እንደሆነ ገብቶኛል ግን አላቆምም።
የወጠረኝ ደም ሲበርድ የምፀፀት ነበር የመሰለኝ። በምትኩ የሆነ መገላገል አይነት ስሜት ተሰማኝ። የሚራወጥ ጭንቅላቴ እርግት እንደማለት።
«ቀንተሃል! ተናደሃል! በራስህ በሽቀሃል! ያን ግን እየተወጣኸው ያለኸው ትክክለኛ ቦታ አይደለም! በፊት እንደምታደርገው በመፅሃፎችህ ወይም በስራህ ራስህን ልትሸውደው ሞክረህ ሀሳብህ አልሰበሰብ ብሎሃል! ያን በወሲብ እየተካኸው ነው! የቀኑን ውጥረትህን ትቀንስበታለህ እንጂ ቋሚ መፍትሄ አይሆንህም! አንተ ራስህን ልትረዳው ካልፈለግክ እኔ ምንም ላደርግ አልችልም አዲስ መፍትሄው አንተጋ ነው!! ። ራስህን በጊዜያዊ እፎይታ ልትሸውደው አትሞክር! ውጥረት በተሰማህ ቁጥር ያን እፎይታ ፍለጋ በወሲብ ልትወጣው ትሞክራለህ! ስትደጋግመው ልክ እንደማንኛውም ድራግ ነው። የሚሰጥህ እፎይታ መጠን እየቀነሰ ይመጣና ዜሮ ይሆናል። ይሄኔ ውጥረቱ ብቻ ሳይሆን አንተ ባልሆነው ማነነትህ ብስጭትህና ፀፀት ይጨመሩበታል። ወይ ሌላ የምትተነፍስበት ሱስ ትፈልጋለህ ወይም ወደምትሸሸው ጨለማህ ትመለሳለህ!!» አለኝ ዶክተር የሆነ ቀን በሀኪም ለዛ ሳይሆን በአባት ቁጣ!!
በትክክል ሂደቱን ጠብቆ የተከሰተው ያ ነው። ደጋገምኩት! በደጋገምኩት ቁጥር እርካታን ሳይሆን የባሰ ጭንቀትን እያስታቀፈኝ መጣ!! እዚህጋ እሷንም ዘነጋኋት ራሴንም እንደዛው። ከወራት በኋላ ዶክተርጋ ሄጄ
«አሁን ዝግጁ ነኝ የሆንኩትን ሆኜ መዳን እፈልጋለሁ።» አልኩት። ደስ ብሎት ትከሻዬን እየመታ ተቀመጠ። ማውራት የጀመርኩኝ ቀን አስመለሰኝ ሁላ! የእናቴን አልፌ የመጀመሪያ የማዕረግ ክህደቷን አልፌ ሶስተኛው ጋር ስደርስ ተሰምቶኝ የነበረውን ዲቴል ማውራት ያቅተኛል። በየቀኑ ከመጀመሪያው እጀምራለሁ። በየቀኑ ትንሽ እየገፋሁ አቆማለሁ። በዚህ መሃል ለስራ ከከተማ ወጥቼ ስመለስ ነው መኪናዬ የተገለበጠው። እያሰብኩ እንደነበር አስታውሳለሁ ምን እንደሆነ ግን አላውቅም! ከፊቴ የሚመጣ መኪና ጡሩንባውን ሲያስጮኸው ነው እንደመባነን አድርጎኝ መሪዬን ያጠመዘዝኩት።»
«ለእኔኮ ግን እስከመጨረሻው ነገርከኝ አይደል? ያ ማለት?» አልኩት ካለፈው ስቃዩ የመዳን ምክንያት ሆኖት ከሆነ በሚል
«እናያለና!» አለኝ
«እሺ ቆይ በቃ? ከዛ በኋላ ያለውስ?» አልኩት ኮንፒውተሩን እያስቀመጥኩት።
«ከዛ በኋላ ያለውን አንቺ የማታውቂው የለም ራስሽ ትፅፊዋለሽ!» አለኝ በእርግጠኝነት
«እህ! ያንተን ስሜት ግን በትክክል ላሰፍረው አልችልም!»
«come on! ካንቺ በላይ የሚያውቀኝ ሰው የለም። በስሜት ደረጃ ከማንም ጋር መቆራኘት የማልፈልግ ሰው ዊልቸር ላይ ተቀምጬ በአካልም የሰው እርዳታ የምፈልግ ጥገኛ መሆኔ ምን እንዲሰማኝ እንደሚያደርገኝ ካንቺ በላይ የሚረዳ ሰው አለ? »
«የሰውን ድጋፍ ማግኘትኮ ሁሉም ሰው በሆነኛው የህይወቱ ጊዜ የሚገጥመው ነው! አንተ ሰዎችን ትረዳ የለ? ሰዎች ሲረዱህ ውድቀት የሚሆንብህ ለምንድነው?»
«በቃ እኔ ነኛ! (ትከሻውን ምን ላድርግ አይነት እየሰበቀ) በሰው ድጋፍ የምንቀሳቀስ ሰው መሆን ሞቴ ነው! ያን ታውቂያለሽ!! ለዘመናት የለፋሁትኮ በስሜትም በአካልም በገንዘብም ማንንም ያልተደገፍኩ ነፃ ለመሆን ነው» አለኝ የእርሱ ባልሆነ ማባበል ድምፅ! አላውቅም ምን እንዳሰብኩ ማጅራቴ ላይ ያለ እጁን ስቤ ሳምኩት። ሲጠብቀው የነበረ እርምጃ ይመስል አስከትሎ ከንፈሬን ሳመኝ። እየሳመኝ ያወራ ጀመር እንደበፊቱ ወሬው ግን የቀን ውሎአችንን አይነት አይደለም። ጆሮዬን ማመን እስኪያቅተኝ አዲስ በፍቅር ቁልምጫ ስም እየጠራኝ ነው። ደንግጬ ለሰከንድ በርግጌያለሁ ሁላ! ረዥም ሰዓት ከተሳሳምን በኋላ አቁሞ እንደመሳቅ ነገር እያለ
«ንግስቴ እንደምታደርጊኝ ካላደረግሽኝኮ እግሬን አላዘውም!» አለኝ አባባሉ ውስጥ <አየሽ ለዚህ እንኳን ያንቺን እርዳታ መጠየቅ ግድ ሲለኝ?> አይነት የመሰበር ድምፀት አለው። ሶፋው ስላልተመቸን ምንጣፉ ላይ ወርደን ማላብ ጀመርን! ከላይ ሆኜ እያየሁት እሱ በሚጠራኝ የፍቅር ቁልምጫ ሁሉ ልጠራው እፈልጋለሁኮ! ግን ከአፌ አይወጣም! አንዴ ቢለኝ ብዬ አምላኬን የለመንኩትን ቃል አለኝ። «ልትገምቺው ከምትችዪው በላይ እወድሻለሁ!» አለኝ። ስሰማው እፈነጥዛለሁ ብዬ ያሰብኩትን ያህል አላስፈነጠዘኝም! ንግስቴ ፣ ፍቅሬ ፣ ልዕልቴ ……….. ያላለኝ የለውም። ለዓመታት ያላለውን ማካካስ የሚመስል ፍቅር ……. ስንጨርስ አጠገብ ላጠገብ ተኝተን ዝም ተባባልን። ከሴክስ ስሜት ውጪ ያ የተስገበገብኩለት ፍቅር ስጨብጠው ምንም አልመስልሽ አለኝ ብዬ እውነቱን ነው የምነግረው ወይስ እንደዚሁ እንቀጥላለን ? በተጎዳው ላይ ጉዳት መጨመር መሰለኝ! ምናልባት ሽባ ስለሆንኩ ነው የጠላችኝ ይለኛል እያልኩ ሳስብ
«ይሰማኛል ብለሽ ያሰብሽውን ስሜት ውስጥሽ አጣሽው?» አለኝ
«ለምን እንደእሱ አልክ?»
«አውቅሻለሁ እኮ! በደንብ።»
«ታዲያ ካወቅክ?» ብዬ እንዴት መጠየቅ እንዳለብኝ ግራ ሲገባኝ
«ፍቅርሽን ከጨረሽ እንደቆየሽ አውቃለሁ። ከዛ ሁሉ በደል በኋላ ያ ስሜት ሊኖር አይችልም!»
«የበደልከኝንኮ ግን ትቼልሃለሁ!»
«አውቃለሁ! ይቅር ስትዪኝ ላለፍኩት መንገድ አዘንሽልኝ። ፍቅርን እና ሀዘኔታን ነው ያልለየሽው!»
«እሺ ካወቅክ ለምን?»
«ምንም እንዳልቀረብሽ እንድታውቂ!! ከተመኘሽው ምንም እንዳይጎድልብሽ!» አለኝ።
መኝታ ቤታችን ገብተን አቅፌው ተኛሁ። ነጋችንን እንዴት እንደምንኖረው እያሰብኩ እንቅልፍ ወሰደኝ። አይኖቼን ስገልጥ አንዳች ሸክም ከላዬ እንደተነሳ ቅልል ብሎኝ ነበር። አይኖቹን እንደጨፈነ ነው። ተገላብጬ ደረቱ ላይ ተጠግቼ ተኛሁ።
«አዲስዬ ! አዲስዬ!» ልቀሰቅሰው ሞከርኩ «ዛሬ እኔ ስራ ቦታ ደርሼ ልምጣ?» አይመልስልኝም። ቀና ብዬ አየሁት! «አታደርገውም አዲስዬ!!» ራስጌውጋ ያለውን መጠቀም ያቆመውን ያኔ ከባድ ህመም ሲሰማው ይወስድ የነበረውን ከባድ ፔንኪለር እቃ አየሁት!! «አታደርገውም! አዲስ አታደርገውም!» እቃው ባዶ ነው! ተነስቼ ይሰማኝ ይመስል ደረቱን እየደበደብኩ ማልቀስ ጀመርኩ።
መጠርጠር አልነበረብኝም ሲሸነፍልኝ? ያቺን ከዲያቢሎስ ጋር ሲማከር የሚያመጣትን ፈገግታ ፈገግ ካለ በኋላ ድንገት ቅይር ስል መጠርጠር አልነበረብኝም? አውቀው አልነበር ክፉ ሲያስብ? ከምንም ተነስቶ እንደዛ ቅይር እንደማይል እንዴት ጠፋኝ? ይሄን አስቦት ነው ማታ የሆነውን ሁሉ የሆነው! መጠርጠር አልነበረብኝም ፍቅሩን ሲያምንልኝ? መጠርጠር አልነበረብኝም በደሉን ሲያምንልኝ?? እስከሞት ራሴን የምወደው ራሴን ነው ሲለኝ መጠርጠር አልነበረብኝም? ሁሌም አፍቃሪ ሰውነቱ በተገለጠ ማግስት መዘዝ ተከትሎት እንደሚመጣ እንዴት ዘነጋሁት? ከመሸነፍ ሞትን እንደሚመርጥ አውቀው አልነበር? ድምፅ የወጣው ለቅሶ ማልቀስ አቃተኝ። እንባዬ ጉንጬ ላይ እየተንዠቀዠቀ አገላብጬ ሳምኩት። እያለቀስኩ ወደሳሎን ሄጄ ፀሃይን ጎረቤታችንን እንድትጠራ ስነግራት
«ምነው እናቴ? ምን ሆንሽ?» ስትለኝ
«አዲስ አዲስ » ብዬ መጨረስ አቃተኝ።

«በጠዋት ስትነሳ ስጫት ብሎ ይሄን ወረቀት ሰጥቶኝ ነበር ትናንት! ምነው አመመው እንዴ?» አለችኝ ወረቀቱን እያቀበለችኝ።
«እባክሽ ይሄ ከንቱ ሞተ ብለሽ እንባሽን አታባክኚ! ሞት መጥፎ ነገር ነው ያለ ማን ነው? ማን ያውቃል ከህይወት የተሻለስ ቢሆን! በህይወቴ አንድ ቁምነገር ሰርቼ ባልፍ ትይኝ አልነበር? መፃፋችንን ጨርሺው። ልጆቼን አደራ! ስወድሽ ኖሬያለሁ!!»
የሆነ ጊዜ ላይ ስለሞት ያወራኝን አስታወስኩት። ከ80 ዓመት በላይ መኖር አልፈልግም ይለኝ ነበር ሁሌ። ምክንያቱም መዝረክረክ ስለማይፈልግ!
«ሞትን እንደመጥፎ ነገር የምናየውኮ ማንም ከሞት በኋላ ያለውን ህይወት ስለማያውቅ ነው! ሰው ሲሞት በህይወት ያለው ሰው የሚቀርበውን ስለሚያጣ ሞትን ክፉ ነገር አድርጎ ያወራዋል። ለምሳሌ አስቢው በህመም ሲሰቃይ ለነበረ ሰው ሲሞት ማልቀስ ልክ ነው? ሰውየውኮ ስቃይ ላይ ነበር? የምናለቅሰው ሰውየው ስለተገላገለ ነው? ለራሳችን ነው ለሰውየው ነው የምናለቅሰው? ደግሞስ ከሞት በኋላ ያለው ምናልባት ከህይወት የተሻለ ሁላ ቢሆንስ?» ብሎኝ ነበር። ጭራሽ ድምፅ አውጥቼ እያለቀስኩ።
«እሺ ይሁንልህ! የተሻለ ይሁንልህ!» ብዬ በቂጤ መሬቱ ላይ ተዘረፈጥኩ!!


ጨርሰናል!!!

@wegoch
@wegoch
@paappii
ፍቅር በዚያ ወራት

፤፤፤ ሚካኤል.አ ፤፤፤

(ክፍል 1)

ስሜ ንፁህ ይባላል ። የስሜ እዳ አለብኝ። እንኳን ለሰው ልጅ ለመላዕክት እንኳ ያልተገባ መጠሪያ መያዜን ሳስበው እሸማቀቃለሁ።
ከክፍል ጓደኞቼ ጋር እየጨፈርን.. .ሺሻ እያጨስን በምናሳልፋቸው ወቅቶች ስሜን የሚጠራኝ ሰው ባይኖር ስል እመኛለሁ።
ደግሞ ማንም እንደሚያውቀው የትምህርት ቤት ህይወት (ላይፍ ይሉታል ጓደኞቼ በቋንቋቸው) ፈታኝ መሰናክሎች አሉት ።
ጥሩ ፋሽን የማይለብስ ...የማያጨስ ...የማይጨፍር ተማሪ ፋራ ተደርጎ ይቆጠራል። ከማህበራዊ ህይወት ገሸሽ ይደረጋል። ከዚህ ክበብ መውጣት የማይፈልግ ሰው ደግሞ በሰዎች ፍላጎት መሾር ይጀምራል።
ስጨፍር የሰው ነኝ...ከወንዶች ጋር ስላፋ የሰው ነኝ...አጭር ቀሚስ አድርጌ እንደ እሳት የሚጋረፉ ወላፈን ጭኖቼን ሳሳይ የሰው ነኝ።
ስስቅ የሰው ነኝ ። ሁሉ ነገሬ አርቴፊሻል !
ከዚህ ግብግብ ስወጣ ግን ጥያቄ አለብኝ።
የህሊናዬን ጥያቄ ማፈን ስለምፈልግ መጠጥ እጠጣላሁ።
ለምን ትጨፍሪያለሽ?
ለምን ከወንዶች ጋር የውሸት ትስቂያለሽ?
ለምን ትቅሚያለሽ?
ለምን ታጨሻለሽ?
ከዛ መጠጣት.. . መጠጥ ደግሞ ጀንትል ያደርገኛል። ህሊናዬን እናትህን እለዋለሁ ።
እጠጣለሁ.. .እጨፍራለሁ...እቅማለሁ...አምራለሁ ...
እንቅልፍ ይወስደኛል።
ስተኛ ም ዝም አልልም...ተኝቶ ማሰብ ይቻላል ወይ? ለምትሉኝ ሰዎች መልሴ ድብን አድርጎ ማሰብ ይቻላል የሚለው ነው።
የማስበው ዶክተር ዘካርያድን ነው። ምርጥ መምህሬ ... ማኔጅመንት ያስተምረናል...ራሴን ማኔጅ ማድረግ ለተሳነኝ ሴት የድርጅት ማኔጅመንት መማር ግን አያስቅም?
ዛኪ መደበቂያዬ ነው። በሱ ክፍል እኔን ጨምሮ የብዙ ሴት ጓደኞቼ አይን ይስለመለማል ። የሄዋን ዘር ይውደድህ ተብሎ የተመረቀ መምህር ።
አይቅለበለብም...አይቸኩልም...
እርጋታው...እውቀቱ.. .ንፅህናው (ፍንትው ያለ ነጭ ሸሚዝ የሚያደርግ ብቸኛው መምህር እኮ ነው)... ሁሉም ባህሪያቶቹ የሴትን ልጅ ልብ መክፈቺያ ቁልፎች ናቸው።
ቆፍጣና ወንድ !
ከትምህርት በተረፈው ሰዓት ማህበረ ቅዱሳን እንደሚያገለግል ሰምቻለሁ።
እሱ ሰላም ሲለኝ ሀጥያቴ ተሰርዮ የተቀደስኩ ይመስለኛል። ሳቁ.. .ጨዋታ አዋቂነቱ አይምጣብኝ ። በመሀል ጣል የሚያደርጋት ስብከት ለኔ የህይወት ስንቅ መሆኑን ማን በነገረው?
እንደ ሌሎች ቀለብላባ ወንድ መምህራን ለሴት ልጅ ባትና ዳሌ እጅ ስለማይሰጥ የፍቅር ፋኖስ ልቤ ውስጥ ተለኮሰ!
ቡም !
አዲስ ወጋገን...አዲስ ፍኖት ተለኮሰ !
ከእንቅልፌ ስነሳ ትራሴን ጭምድድ አድርጌ አቅፈዋለሁ። ዛኪ ነፍስያዬን ያግላታል። ሰውነቴን ሲተኩሰኝ እሰማዋለሁ። ትንፋሹ ከሱ ጋር ሳይሆን ከኔ ጋር ያድራል።
ከሁለት ሰዓታት በኋላ አይኑን ማየቴን ሳስበው ሀሴትን አደርጋለሁ።
ሆኖም ከደስታዬ ሲለጥቅ አንድ ጥያቄ ገረፍ አድርጎኝ ያልፋል።
ኪሩ ከዚህ ሁሉ አፍቃሪ ሴቶቹ መሀል እኔን እንዴት ሊመርጠኝ ይችላል?
ከኔ በላይ ቆንጆ ሴቶች ደግሞ አሉ። ልቤ ን ግን አያክሉትም...ልቤ ተራራ ነው። ማንንም ማንበርከክ ...ማንም እንዲያሸረግድልኝ የሚያደርግ ቅብዓ ቅዱስ አለኝ።
ሰለዚህ እሱን አማልሎ ወጥመዴ ውስጥ የማስገባበት ብልሀት ወጠንኩኝ...ትምህርት ቤት ስሄድ እሱን እንደምረታው ለራሴ እየነገርኩት ነው።
ንፁህ ታሸንፊያለሽ ! ብሎ የሚፎክር ጀብደኛ ልብ አለኝ።
ዶክተር ኪሩ መጣሁልህ !

(ይቀጥላል...)

@wegoch
@wegoch
@paappii
ፍቅር በዚያ ወራት 

ክፍል 2

(ሚካኤል .አ)

የክፍላችን በር ጋር እስክደርስ የነበረኝ በራስ መተማመን ስሜት እምን ጉድጓድ እንደገባ አላውቅም። ዶክተር ዛኪን ሳየው ልቤ በአፌ ልትወጣ ታገለችኝ። 

እንደ ልማዱ ፅድት ብሎ መጥቷል። (በጣም የሚገርመኝ ነገር ጫማው ላይ እንኳ ብናኝ አቧራ የለምኮ ) ... ለነገሩ ከቤቱ ወጥቶ በኔ ልብ ላይ ተራምዶ ክፍል እየደረሰ በየት በኩል አቧራ ሊነካው ይችላል?

በማስተማሩ በፊት ሁላችንንም በስስት እያየ ሰላምታ ይሰጠናል...ጨዋታ አዋቂ ነው። 

ቢያንስ ፊት ለፊት ከሚቀመጡ አንድ ሁለት ልጆች ጋር ሳይጨዋወት ወደ ማስተማሩ አይገባም። ሲስቅ ከልቡ ነው ... ነጭ ባይሆንም ፈዛዛ ሽሮ መልክ ያላቸው ስድር ጥርሶች አሉት ። ድዱ በእጅ ሳይወቀር ተፈጥሮ አሽሞንሙና ሰርታዋለች ። 

እሱ ይስቃል.. .ልቤ ታለቅሳለች ። ስድር ጥርሶቹ የኔን ነፍስ የሚያጠፋባቸው ድርድር ጥይቶች መሆናቸውን ማን በነገረው ?

ፈገግታው ደስም ይለኛል.. .ያስቀናኛልም። 

በተለይ ለነጃት ሲስቅላት እነዳለሁ ።

ደግነቱ እንደዚህ አይነት አክራሪ ክርስትያን ሙስሊሟን ነጃት ሊወድ ስለማይችል ለራሴ ቅናት መፅናኛ አላጣም።

ይሁንና ግን ይሄን አስቤ እንኳ ልቤ እርፍ አትልልኝም...ያቺ ጣውንቴ አይኖቿ ያምራሉ ...ሰውነቷ ከኔ ይበልጥ የሚስቡ ይመስለኛል...ብዙ ጊዜ ዛኪ አቀርቅሮ ትምህርት ሲተነትን እነዛ ሎጋ የእግር ጣቶቿን እያየ ስለሚመስለኝ እበሽቃለሁ ።

የሆነ ቀን ላይ የፊት ኒቃቧ ሲወርድ መልኳን አየሁት ...ለክፋቱ ደግሞ ዶክተር ፊትለፊታችን ነው። መልኳን ሲያይ መደንገጡን አይቼበታለሁ ...(ድንገትም ስለማፈቅረው መስሎኝም ሊሆን ይችላል )

ከሁሉም ተማሪ በላይ ዘልዬ ፊቷን የሸፈንኩላት እኔ ነኝ። ሙስሊም ጓደኞቿ አላህ ይባርክሽ ብለው መረቁኝ... (ይሄን ያደረኩት ከነጃት የውበት ፆር ዛኪዬን ለመደበቅ መሆኑን የሚያውቀው አላህ ሲባርከኝ እኮ ታየኝ !)

በቃ ከዛን ቀን በኋላ አይኖቼ ሁለቱንም ይከታተላቸዋል። ለሴት ልጅ ውበት ግድ አልባው ዛኪ ለነጃት ግን የተመየ ስሜት ያሳደረ ይመስለኛል....። ክፍል ውስጥ ፊትለፊት ስለምትቀመጥ ሳያሳስቃት ምንም ነገር አይጀምርም። 

ደግሞ ሌላ የሚያበሽቀኝ ነገር የሷ ሳቅ ነው። ስታየው ገና አይኖቿ ይበራሉ.. .ትንሽ ያወራት ጊዜማ ነፍስያዋ ትዘላለች) 

በዚህ ቅናት ተነሳስቼ እኔም እንደሌሎች ቸካይ ተማሪዎች ፊትለፊት ሄጄ ተቀመጥኩ ።

ብዙ አልምጥ ጓደኞቼ ተሳለቁብኝ። ትምህርት እንደሚደብረኝ ብቻ ሳይሆን እኔም ትምህርትን እንደምደብረው ሁሉም በዙሪያዬ ያሉ ልጆች ያውቃሉ። የኔ ፊት ወንበር ሄዶ መቀመጥ ተማሪውን ብቻ ሳይሆን መምህሬንም ገርሞታል ።

"ዛሬ እንዴት ነው? ... የመማር ሞራልሽ መጥቷል ማለት ነው" ፈገግ አለልኝ ።

ሞትኩለት !

ክለብ ለክለብ የሚቅለበለበው ምላሴ ጉሮሮዬ ላይ ገብቶ ተሰነቀረ ።

የሆነ ቅጥ የሌለው መልስ መለስኩኝ.. .

"አ....አ......መ...ሰ....ለ....እ....ኝ "

ስደናበር ነጃትና ጓደኞቿ ተያይተው ሳቁብኝ። 

በቃ ጠመድኳት ይህችን ሴት !

"ንፁህ ምን ሆነሻል እጅሽ እየተንቀጠቀጠ ነው እኮ!  አመመሽ እንዴ? "

"አዎ ቲቸር !" 

ይኸው የኔ ትሁት ዛኪ ደገፍ አድርጎ ከክፍል እንድወጣ ዕድል ሰጠኝ ።

አለንጋ ጣቶቹ ወገቤን ሲይዙኝ የእውነት ታመምኩለት ...ሰውነቴን እሱ ላይ ጣልኩት ።

የክፍሉን በር ከፍቶ ወጣን ።

"አይዞሽ ንፁህ.. ."

እንዲህ ሲለኝ የነጃት የቅናት ዛር አናቴ ላይ ተፈናጠጠ ።

በድፍረት ከናፍሩን ስሜ ፍቅሬን ልገልፅለት ደፈርኩ ...

አንድ 

ሁለት

ሶስ.....

     (ይቀጥላል)

@wegoch
@wegoch
@paappii
ፍቅር በዚያ ወራት
(ሚካኤል.አ)
#ክፍል 3
ከንፈሮቹን ልጎርሳቸው ተጠጋሁት.. ወደ ከናፍሩ ስጠጋ የውብ ትንፋሹ መዓዛ አወደኝ ። የተቀባው ሽቶ በአፉ ከሚያላምጠው ሜንት ማስቲካ ጋር ሲዳበል የገነት መግቢያው የሱ መዓዛ ነው ቢሉኝ ውሸት ነው አልልም።
ወድያው "አይዞሽ ውዴ! " የሚል ድምፅ ሰማሁ ።
ሺት !
የፈራኋት ጣውንቴ መጣች ። የነጃት ጥላቻዬ አስራ አንድ በመቶ ሲያድግ ተሰማኝ (ፖለቲካ አይደለም !)... በሷ ቤት አንድ ቀን ኒቃቧ ከፊቷ ሲወርድ ቀድሜ ስለደረስኩላት በችግሬ ጊዜ ቀድማኝ መድረሷ ነው። ችግሬ እሷ እንደሆነች ብታውቅ ስል ተመኘሁ።
"ነጅዬ እባክሽ handle " አድርጊያት ብሎ ዶክተር ወደ ክፍሉ ገባ። ነጅዬ ሲላት ደግሞ ነብር ሆንኩኝ... ከየት መጣ ያልተባለ ቀዝቃዛ ውሀ ፊቴ ላይ ከነበለችብኝ።
የዛክዬን ከናፍር ከመጉረስ ስታግደኝ ነው መቀዝቀዝ የጀመርኩት ።
"ተረጋጊ እንጅ ፀጉሬን ..." ብዬ ጮህኩባት ።
እሷ እንኳን ልትደነግጥ ወገቤ ስር ገብታ አነሳችኝ ። በጥፊ ጉንጯን ባቀላው ስሜቴ ነው ።
እሷና ጓደኞቿ አንከብክበው ጥላ ያላት አፀደ ስር አኖሩኝ ። ንፋሱ ከውሀው ቅዝቃዜ ጋር ተዳብሎ በረደኝ ።
ጥርሶቼ በእልህና ቅዝቃዜ ተንገራገጩ።
"አይዞሽ ንፁህ.. . "
ራስሽ አይዞሽ ብዬ ልመልስላት ይሆን?
አይኖቿ የሚስቁለት.. .ነፍሷ የምትፈነጥዝለት ዛኪን ልቀማት መሆኑን ማን ሹክ ባላት ?
...
ከዛ ክስተት በኋላ ወደ መደበቂያዬ ሮጥኩ !
ክለብ.. .
ጠጣሁ.. . አምሮቴ ንቅል እስኪልልኝ ጠጣሁ ።
ሞቅ እንዳለኝ ያየ አንድ ጎረምሳ የሚያጨሰውን ሺሻ ትቶ ወደኔ አቅጣጫ መጣ።
"ቆንጆ ነሽ" አለኝ።
ዝም!
"ምነው የከፋሽ ነገር አለ ?"
ዝም!
ምናለ ከዛኪ በስተቀር የዓለም ወንዶች ሁሉ ባያናግሩኝ? አባቴና ወንድሜ እንኳ እንዲያናግሩኝ የምፈልግ አይመስለኝም።
አሁን ይሄ የሰማይ ስባሪ የሚያህል ወደል እንዴት ያናግረኛል ?
ጠጪ ...አጫሽ ወንድ ነው ያስጠላኝ።
ያዘነ ለመምሰል ሞከረ !
ውሸት.. . አይኖቹ ውሸት! ...ሳቁ ውሸት...ንግግሩ ውሸት ...
ቆንጆ ነሽ ሲለኝ አመሰግናለሁ ቢለኝ ...አብረን እንፍታታ ብሎ ይቀጥላል ።
እሺ ብለው እኔ ጋር ለማስመሰል ውስኪ ያወርዳል።
ምድር ላይ ያፈቀራት ሴት እኔ ብቻ የሆንኩኝ ያህል አስመስሎ ይንከባከበኛል...ከዛ መተኛት !
አንዴ ጭኔ ስር ገብቶ በለሴን ከቀጠፈ እኮ በነጋታው ስልክ አያነሳልኝም።
ይሄ ህይወት ሰልችቶኛል.. . ነፍሴ ዛኪ ጉያ ገብታ መሸሸግ ትፈልጋለች ።
ሀጥያቴ የሚጠራው በሱ ላቦት ነው።
"ማሬ አመልሽም ?"
"ማርህን ጎዣም ፈልግ !" አንባረቅሁበት ። ከመቅፅበት ከስሬ በሮ ጠፋ ። ፈሪ ወንድ !
አሁን ይሄ ነው የኔን ጀንታላ ዛክ የሚተካልኝ?
ሌላ ብስጭት.. .
መጠጥ.. . ሻት ...
በቃ ራሴን አጣሁት ። የክለቡ ብልጭ ድርግም መብራት ...መጠጡ.. .ሙዚቃው ናላዬን አዞረኝ ።
ምንም ሆንኩ !
እንደምንም ተንገዳግጄ ሰው መሀል ገብቼ ጨፈርኩ።
እንደ ልማዴ የሰው ሆንኩ...ሳቄ ...ደስታዬ ሁሉ የሰው ሊሆኑ ራሳቸውን ከመቃብር ቀስቅሰው ተነሱ።
ከሩቅ ለሚያየኝ ሰው ደስተኛ ነኝ...ነፈዝኩ...ነጎድኩ ...ብንንንንንንንንንን....
አላልኩም ?
ስጠጣ የሰው ነኝ ብዬ አልነበረምን ?
ማልዶ ስነሳ ራሴን ከሰው ጋር አገኘሁት ።
አንሶላዬን ገልጬ ተስፈንጥሬ ተነሳሁ ።
አብሮኝ ያደረው ወንድ እንደ ጆንያ ተንደባሎ ፊቱን ወደኔ አዞረ?
እንዴ?
ይሄ የኢኮኖሚክስ መምህሩ እዘዝ ነው እንዴ?
ዛኪ የነፍስና ገላዬን መርከስ አይቶ የጠላኝ መሰለኝ...
"አንተ ማነህ ?"
.
(ይቀጥላል)

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሥዕል በማሳል ለ ወዳጅ ዘመዶ ስጦታ ያበርክቱ
በ+251984740577
ወይም @gebriel_19 ላይ ፎቶ በመላክ በ ተመጣጣኝ ዋጋ ማዘዝ ይችላሉ!
#ሥዕል_ብቻ የቴሌግራም ገፅ


@seiloch
@seiloch
ፍቅር በዚያ ወራት !
ክፍል 4
(ሚካኤል አ)
"አንተ ማነህ ?"
የደነገጥኩት ክፉኛ ነው ። ራሴን ለዶክተር ዛክ አሳልፌ ሰጥቻለሁ ብዬ ስለማስብ ብቻ ገላዬን ከሱ ነጥቄ ያረከስኩ ነው የመሰለኝ።
ንፁህ ረከሰች !
ያ ህሊናዬን የሚኮረኩመኝ ፀፀት አገረሸ።
"ማር ነሽ አለኝ " አጠገቤ ተንጋሎ የነበረው ጎረምሳ።
"እንዴ ዶክተር እዘዘ?"
በሳቅ ተንከተከተ ። የዶክተር ዛኪ ጓደኛ ...
"ከተማሪዬ ጋር በዚህ መልኩ ይነጋል ብዬ አላምንም "
እንዲህ ሲለኝ ደግሞ አለቀስኩ ... አልጋው ጠርዝ ላይ ተቀምጬ አለቀስኩ ። እንባዬ ይቅርታ ነው ... ዛኪዬ ማረኝ ብሎ የሚግፈለፈል እንባ በልቤ ውስጥ ፈልቶ በጉንጬ ላይ ፈሷል። የፊት ጉንጬን ይለበልበኛል ።
እዘዝ ግንኙነታችን በኮንዶም መሆኑን አስረድቶ ሊያባብለኝ ሞከረ። ያሳሰበኝ የገላዬ ጤና አልነበረም...የልቤ...የህሊናዬን ህመም የአካል ጤንነቴ አያክመውም።
ብዙ እብዶች.. . የአካል ጤነኞች ነን። ህሊናችን ግን ስለሚያነክስ ታማሚዎች ነን።
ሰው ከውስጡ ካልታረቀ በስተቀር በሽተኛ ነው። ንዋይም...ቤተሰብም ... ሀሴትም እኔን ከህመሜ አይታደጉኝም። መንፃት የምፈልገው ለስሜ ክብር ለመስጠት ነው።
ለስሜ ክብር ስሰጥ ህሊናዬን እወለውለዋለሁ ። ህሊናዬ ሲነፃ ለዛኪ እገባዋለሁ የሚል የራስ መተማመን ይኖረኛል። ለዛኪ እስካልተገባሁት ድረስ ደግሞ ስንኩል ነኝ።
የዛሬው አጋጣሚ ደግሞ ሌላ የሽንፈቴ ገፅ ነው። ለእዘዝ ከብሬ ባገኘው እንኳ የቅርብ ጓደኛውን ባየሁት ቁጥር መርከሴ ይታሰበኛል ።
"ንፁህ ተረጋጊ..." እጆቹን አይኖቼ ላይ ሊያሳርፍ ሲሞክር ገፈተርኩት ።
እዘዝ ባለጌ ነህ ትለዋለች ነፍስያዬ ። የጓደኛህን ገላ አታለህ የቀማህ እርኩስ ነህ ይለዋል ውስጤ ።
እያየሁ ጠላሁት ... መርከስ መልክ ቢኖረው እዘዝ ነው ። መርከስ መልክ ቢኖረው ንፁህ ናት ።
ልብሴን ለባብሼ ክፍሉን ለቅቄ ወጣሁ ። ከሲኦል የማመልጥ ይመስለኛል። የሆቴሉ የመጀመርያ ኮሪደር ስደርስ እያመለጥኩ ነው።
ብንንንንንንንን.. ..
።።።።።።።።።።
ከዛች ቀን በኃላ ትምህርት ቤት አልሄድም። እንደ እርጎ የሰከነው ዛኪን ማየት ሌላ ፀፀት ነው ለኔ ።
የነጃትን አይኖች ማየት ለኔ ተጨማሪ አርጩሜ ነው ።
የፍቅር አምላክ የዛኪን ልቦና ወደ ነጃት አዙሮ ለሽልማት ሲያጫት አየሁ።
አፈርኩ ... ለአምስት ቀናት አፍሬ ከክፍል ቀረሁ ።
ከሰመመኔ ለቀናት አልነቃሁም።
የፀፀት በትር ገላዬን አድቅቆት ቆዘምኩ ...
ከዚህ መዛል ንቂ ሲለኝ ግን ሀሙስ የምትባል ቀን ሌላ ተዓምር ይዛ መጣች።
ሀሙስ የቀን ቅዱስ ። ማለዳውን በቅድስና አልያም የፀፀት ቤንዚኗን ለማርከፍከፍ በላዬ ላይ ተሰየመች ።
ጉዱ የስልክ ጥሪዬ ነው ።
እንደ ኤሊ እየተንቀራፈፍኩ በዳበሳ ስልኬን አገኘኋት ። አንድ አይኔን ሳልገልጥ ደዋዩን አየሁት ።
መንቃት ብቻ አይደለም ...
ከአልጋዬ ተስፈንጥሬ ቆምኩኝ። ደዋዩ ነፍሴን ሙሉ የሚያደርጋት ሀኪሜ ነው ።
Teacher zaki.. .
ስልኬ ከእጄ በምን ፍጥነት ወድቆ ወለሉ ላይ እንዳረፈ አልገባኝም።
በምን ተዓምር ዛክ እኔ ጋር ደወለ ?
ላንሳው ይሆን?
(ይቀጥላል.. . )

@wegoch
@wegoch
@paappii
"ሸግዬ ሸጊቱ" መፃፍ በቅርቡ ትመጣለች ይጠብቁን
ኩባያው
(በማዕዶት ያየህ)

አይደለም በጀማ የተሰራ የጊቢ ምግብ በሰራተኛ የተበሰለና በቅመማቅመም ራሱን የሳተ የቤት ምግብ የሚያማርጠው ጨጓራዬ በሆነ ምትሀት ከሳምንት 5 ቀን ክክ መብላት ለመደ።እርሾ እንደበዛው ሊጥ የሚቆመጭር ፍርፍር በዚሁ ምትሀት ጣፈጠኝ።የሰማያዊ ኩባያ ልክፍት ከጊቢው ካፌ የማይጠፋ ረሀብተኛ አደረገኝ።

ያችን ሰማያዊ ኩባያ የነካ ከንፈር የኔን ከንፈር እስኪነካ ደጅ ጠኚ ሆንኩ።የሆነ ቀን(ትዝ ይለኛል አርብ ነበር ቀኑ)በጧት ስነሳ ጤነኛ ያልሆነ ረሀብ ነፍስ ዘርቶ ጨጓራዬ ላይ ስዕል ሲስል ታወቀኝ።የትምህርት ሰዓቴ ስለደረሰ ከጊቢ ወጥቼ ምግብ አዝዤ ለመመገብ የሚሆን ጊዜ እንደሌለኝ ሲገባኝ ከጓደኞቼ ጋር ወደጊቢው ካፌ ሄድኩ።ምግቤን ተቀብዬ ከመቀመጤ የሆነ ምትሀት የሚመስል ድምፅ ሰማሁ።ቀና ስል የመግቢያው በር አካባቢ የተማሪ መመገቢያ ካርድ ላይ ምልክት የሚያደርገው ሰውዬ ከአንዲት ልቅም ያለች ቆንጆ ጋር የጦፈ ክርክር ይዟል።ልብ ብዬ ሳጤነው የክርክሩ መነሾ የልጅቱ አፍሮ ፀጉር ነው።

"ፀጉሬ አጭር ስለሆነ አይያዝም።ሲሰራ እና ሲበጠር ደግሞ ሀይለኛ ራስ ምታት አለብኝ ያመኛል።ምናለ ብታስገባኝ ጋሼ? ክላስ እየረፈደብኝ ነው'ኮ"ትላለች በማስተዛዘን።

"የኔ ጉዳይ አይደለም!ስትፈልጊ ከስር በምላጭ ተሞሽለቂው!ይህ አይነበብም?ምን ይላል?ጠጉር አንጨባሮ መግባት አይቻልም አይልም?"ሲል አንባረቀ ሰውየው።ልጅቱ አስተዛዝኖ መለመኑ እንደማይሆንላት ስታውቅ ጎንበስ አለችና ያንን የህወሀት ተጋዳላይ የመሰለ ፀጉሯን መሀል ለመሀል በእጆቿ ከፍታ መሀል አናቷን ለሰውየው አሳየችው።ደንግጦ አማተበና እንድትገባ ፈቀደላት።ዳቦ ተቀብላ በግራዋ ፣ በሰማያዊ ኩባያ ደግሞ ሻይ በቀኝ እጇ ይዛ ከፊትለፊቴ ያለ ወንበር ስባ ተቀ

ተቀመጠች።ከያዘችው ዳቦ ግማሹን ቆርሳ በሻዪአ እያማገች ተመገበችው ።ኩባያውን ወደአፏ አስጠግታ ከንፈሯን ስታስነካው አላት የሆነ ምትሀት!ያኔ እንደኔ አትኩሮ ያያት ካለ በእርግጠኝነት ትን ብሎታል ።የውበት ትንታ...የማማር ትንታ...የሰማያዊ ኩባያ ትንታ...የአፍሮ ትንታ...እኔንም ትን ብሎኝ የጀመርኩትን ሻይ ሳላጋምስ ዳቦዬን ለጓደኞቼ ትቼ ተከትያት ወጣሁ።ሮጠች...ሳይረፍድ ለመድረስ...ሮጥኩ...ዕድሌን ላለማሳለፍ...ደረስኩባትና እያለከለክሁ ያንን ኩባያ የያዘችበትን ቀኝ እጇን ለቀም አደረኩት።ደንግጣ ዘወር አለችና እጇን ከጄ መንጭቃ አስለቀቀችው።

"ረጋ በይ ሰዓት ገና ነው"አልኳት የእጅ ሰዓቴን ወደሷ ጠጋ አድርጌ ለመጀመሪያው ክፍለ ጊዜ ገና 20 ደቂቃ እንደሚቀራት እያሳየሁዋት።በስሱ ረጋ አለች።

"ራስሽን ምን ሆነሽ ነው?"ጠየኩ ወደፀጉሯ እያየሁ።ቅድም ለካፌ ተቆጣጣሪው እንዳሳየችው ጎፈሬዋን ለሁለት ከፍላ መሀል አናቷን አሳየችኝ።ከግንባሯ ማብቂያ አንስቶ ወደሁዋላ የሚሄድ በግምት አምስት ሳንቲ ሜትር የሚሆን የትኩስ ቁስል ስፌት!ቅፍፍ አለኝና ፊቴን ከሰከስኩት።

"አየኸው?"
"አዎ. ...ምን ሆነሽ ነው?"
"የብረት ዱላ አርፎብኝ?"
"ምን?😳"(እዚህጋ ሳልጮህ አልቀረሁም)
"ኧረ ቀስ እንዴ!መስኮት መቶኝ ነው የብረት መስኮት...እኔ ራሱኮ ሲመታኝ እንዲህ አልጮህኩም ሆሆሆ "
"ቆይ መቼ ነው የመታሽ?"
"ሳምንት ሆነው"
"የት ነው?"
"ቤቴ...ሲቆላኝ!የሚያደርገኝን ሲያሳጣኝ"
"እንዴት ማለት?"
"ከሆነ ሰው ጋር ተጣልቼ ወደክፍሌ ገባሁና ከተኛሁበት ስነሳ መከፈቱን ያላስተዋልኩት መስኮት ተንፈስ አረገኝ።"
"እንዲህም አርጎ መተንፈስ የለም እቴ!እሺ ከዛስ ወዲያ?"
"ከዚያማ ቁስሉም ተሰፋ እኔም አፍሮ ሆኜ ቀረሁ ይባላል።"
"ይህን ያህል ምናይነት አመታት ቢሆን ነው የመስኮት ጫፍ መቶሽ ለስፌት የደረስሽው?"
"መስኮቱ ለተጣላሁት ሰው ወግኖ አይመስልህም?"
"ሃሃሃሃ...ሃሃሃሃ...ማነው ባክሽ የመስኮት ረዳት ያለው?ታድሎ!"
"ሆሆ ገላዬነህ አንተ ከሰሙህ ብዙ ትጠይቃለህ...አሁን ረፍዶብኛል ቻው!"ብላኝ ስትሮጥ
"እሺ ቢያንስ ስልክሽን ስጭኝ!"አልኩ ሰው ሰምቶ እስኪታዘበኝ ጮክ ብዬ።
በፈገግታ ተሞልታ ዘወር አለችና
"ለሌላ መስኮት እሚበቃ ጭንቅላት የለኝም"አለችኝ።ቅር እያለኝ ተመለስኩ።ከዛች አርብ በሁዋላ ጨጓራዬ ድኖ ያገኘውን እየበላ ሳንቀያየም ማደር ያዘ።እንዳታልፈኝ ብዬ ከማለዳው 12:50 ጀምሬ ካፌ እሰለፋለሁ።ግን አላያትም...ያንን አምፖል የሚያህል ዐይኗን...የተከመከመ አፍሮዋን...ችምችም ያሉ ጥርሶቿን ዳግም ባይ ብዬ ከታሪካዊ ጠላቴ ከክክ ጋር እርቅ ፈፀምኩ።ዳሩ የት ተገኝታ?ሰማያዊ የሻይ ኩባያ በደረሰኝና ባየሁ ቁጥር ጥቁር ከናፍሯን እያስታወስኩ እጃጃላለሁ።ግን እሷ የለችም..ብቻ የሆነ ቀን አያታለሁ...የሆነ ቀን...

#Maedot (Tizur_12)

01/10/2014 ዓ.ም.

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሽቶና ትዝታ
።።።።።።።።

መኖሬን ሳላዳምጠው ለሞት በሬን መክፈት አልፈልግም።የነፃነቴን ወጋገን እስከ ገደሉ ጫፍ ነው የማሳድደው።እና በ29 ዓመቴ የሞዴል የሚመስል ቁመና ይዤ፣የጋብቻ ቀለበት ከጣቴ ሳይገኝ፣ፀጉሬን አፍሮ አድርጌ ፣በመለሎ ቁመቴ ላይ ሂል ጫማ ጨምሬበት፣ጥቁር ቻፕስቲክ በስሱ ተቀብቼ ከቀጭን ወገቤ ጋር የልቤን እያወራሁ መራመድ ያስደስተኛል።የሆነች ንግስት እንደሆንኩ ይሰማኛል።ሳባን የሆንኩ ዓይነት።"ጥንቅቅ ያልሽ ወይዘሪት ነሽኮ መዓዚ!"ይሉኛል የስራ ባልደረቦቼ ሲያሞካሹኝ።

ወደ አዲሱ ተመድቤ ወደማስተምርበት ክፍል ስደርስ የሆነ ሽቶ ይሸተኛል።የመጀመሪያ ባሌ ሽቶ...ልወልድለት ቀን ስቆርጥ ቁርጤን አሳውቆኝ የተወኝ ባሌ ሽቶ።ልክ ወደ ክፍሉ ከመቃረቤ ነው ያ ሽቶ ከነአዳፋ ትዝታው እየተጎተተ በአፍንጫዬ የሚገባው።ከነዱላው፣ከነስድቡ፣ከነኩራቱ፣ከነትዕቢቱ...ልሸሽ ብል የማልሸሸው ዐይነት ኩራቱ ድቅን ይልብኛል።ባስ ሲል በስጋ አምሮት ነድጄ ስገላበጥ ሰክሮ ገብቶ ጥቅልል ብሎ የሚጋደመው ነገር ሽው ይልብኛል።

ለራሴም ለልጄም የሚሆን ጥሩ መሰረት ሳላዘጋጅ መውለድ የማይዋጥልኝ ሴት ነኝ።ለልጄ ተገቢውን ትምህርት እንደማስተምረው፣እንደማላስርበው፣እንደማላስበርደው፣እንደማያዝንብኝና ከኔ በመወለዱ አንድም ቀን እንደማያማርር እርግጠኛ ሳልሆን አላረግዝም ማለቴ ነበር ነገር ያበላሸው።

"ሰው እንዴት ሳይኮሎጂ ተምሮ የባሉን ፍላጎት መረዳት ያቅተዋል?"ይለኝ ነበር ያልሰከረ ጊዜ።እኔም አለት ነበርኩ ሀዘኔታ አይሰማኝም ነበር።

"You are beyond the science Mister"እለዋለሁ።

"ተይ እንጂ!ሃሃሃሃ"ጥቅልል ብሎ ለጥ ሲል እጮሀለሁ።(ተራ ጩኸት እንዳይመስላችሁ ደግሞ...ሆረር ፊልም የሚያይ ህፃን ጩኸት ነው የምጮኸው)
ደንግጦ
"ሴትዮ ምነካሽ አበድሽ?"
"አዎ አብጃለሁ...እና ምን ይጠበስ?"
"ምን ሆንኩ ነው ምትይው ቆይ"
"ለምንድነው ወደኔ ዞረህ እማትተኛው?"ስለው ዝምምምምም ይላል።ስቃጠል አድሬ ጧት ጠግቦ እንዳደረ ሰው ተነስቼ ወደስራዬ አዘግማለሁ።የኔ ጭቅጨቃ ሲደጋገም ዝምታው ድንበሩን ጥሶ ወደማመናጨቅና ወደመሳደብ አደገ...አለፍ ሲል ወደ ዱላ...በሁዋላ ጦመኛ መሆኔ ሳያንስ ዱላውን የምቋቋምበት አቅሜ ሲከዳኝ ፈታሁት።አልክድም ብዙ ሌሊቶችን ነፍርቄአለሁ።ደግነቱ ሆዴ ቶሎ ቆረጠልኝ።ልጅ ከመውለድ ባልን መፍታት የሚል ትልቅ እብደት አዘል ውሳኔ ወሰንኩ።

ስሙና ግብሩ ተጣልተው ፍስሐ ሆኖ ፍስሐ ያልሰጠኝን ፍስሐ ረሳሁት ብዬ እፎይ ስል ይኸው አሁን ደግሞ ሽቶው ወደሁዋላ ሶስት ዐመታትን ጎትቶ እነዚያን የቃጠሎ ሌሊቶች አስታወሰኝ።ከተማውን አካልዬ አለ የሚባለውን ስስ ፒጃማ ገዝቼ ፣በቀይ ቻፒስቲክ ከንፈሬን ኢንጆሪ አስመስዬ ለራት ጠረጴዛው ላይ ስሰየም ከቀረበለት ግማሹን እንኳን ሳይበላ ስልክ እየደወለ ወደ በረንዳ ይወጣል።ሲጨርስ እንደልማዱ ተጠቅልሎ ይተኛል።

የልጅ አምሮቱን ለሁለት ዐመታት ማስታመም ተስኖት አይገፉ አገፋፍን ገፋኝ።"መውለድ የምፈልገው ከሁለት ዐመታት በሁዋላ ነው"ስላልኩ ብቻ ጭኔ ስር ባለው እሳት እኔኑ ቀጣኝ...ከፈታኝ በሁዋላ ወዲያው ነው አግብቶ የወለደው...ፍጥነቱ በጌታ!ልክ ቀለበታችንን ባወለቅን በአስረኛው ወር ከማሞቂያ ያልወጣች የጨቅላ ህፃን ፎቶ ላከልኝ።ከታች

"Am dad now...my beautiful mule😁😁"ከሚል መልዕክት ጋር...
ይኸው ደግሞ ሽቶው መጣ..."ከዚህ በሁዋላ ሽቶ እንዳትጠቀሙ "ብዬ ተማሪዎቼን አልከለክል ነገር...ኤጭ!!

ማዕዶት ያየህ(@Tizur_12)

02/10/2014 ዓ.ም.

@wegoch
@wegoch
@paappii
ፍቅር በዚያ ወራት !

(ክፍል 5)
ሚካኤል.አ

ለምን እንደሆነ ባላውቅም የዛኪን ስልክ አለማንሳት አልቻልኩም። ድምፁ ናፍቆኛል.. .

"ሄሎ "

"ሄሎ ንፁህ.. ."

ዝም አልኩት ። ረጋ ያለ ድምፅ!  ... 

ንፁህ ብሎ ሲጠራኝ እንባዬ ፈሰሰ ። አፍቃሪው ልቤ በክህደት ሰንሰለት ተተብትቦ በፀፀት አርጩሜ እየተወገረ ነው።

"ሄሎ " .. የድምፄን መጥፋት ሲረዳ ደግሞ ተናገረ ።

"ሄሎ ቲቸር "

"በሰላም ነው የጠፋሽው? ህመሙ አልተሻለሽም እንዴ?"

የተሻለኝ ህመም የለም። ጭራሽ የማይድን ሌላ የውስጥ ቁስል አመርቅዣለሁ ።

እወደዋለሁ.. .

የንሰሀዬ መንገድ የሱ ስክነት ነው። እሱ ቢያቅፈኝ...እሱ ቢያስብልኝ... እሱ መዳፉን አውሶ ቢዳብሰኝ እንደስሜ እነፃ ነበር ።

"ምንድነው ለቅሶ ነው የምሰማው ?" 

"አዎ ዛክ "

"ምን ሆነሻል ?" 

"እወ.. .."

ሰውን እወድሀለሁ ብሎ መናገር ለካ ይከብዳል ።

ቃላቶቼን ከምኔው እንደዋጥኳቸው አላቅም። ለሱ ፍቅሬን መግለፅ ስሜቱን የሚገድልብኝ ይመለኛል። ዛክ ከወንዶች ሁሉ ይለያል ብዬ ባስብም ሁሉም ወንዶች ደግሞ የሚያመሳስላቸው የጋራ ባህሪ እንዳላቸው አምናለሁ ። 

ሴት ልጅ ለወንድ ልጅ የውስጧን ስሜት በግልፅ ከነገረችው ለሷ ያለው አመለካከት ይወርዳል። ወንድ ልጅ ከአፍቃሪው ይልቅ በኩራት ገመድ ወጥራ ለምታሰቃየው ሴት የልቡ በራፍ ይከፈታል ።

ኩራት !

ወንዶች መለመን ይፈልጋሉ.. . እንደ ወርቅ ተደብቃ የማህደሯ ክርታስን ለመቆፈር የምታታግል ሴት የወንዶችን ልብ ቁልፍ በእጇ ይዛ ትዞራለች ።

"ምን አልሽ?"

"አወ...ቅማ ዶክተር እባክህ ትንሽ ህመሜ ስለጠነከረ ተጨማሪ ቀናትን ባልመጣ እንዳትቀየመኝ። "

"ለምን እቀየምሻለሁ?  ትምህርትም...ስራም.. .ከጤና በላይ አይሆኑም። ስትኖሪ ነው ሁሉ ነገር የሚኖረው።

በይ ፈጣሪ ይማርሽ ።"

"አሜን !" አልኩት ።

ይሄን ያልኩት ግን ለበሽታዬ ድህነት አይደለም። ፈጣሪ እኔ ላይ የሰራሽውን ሀጥያት ይቅር ብሎ ይማርሽ እንዳለኝ ነው የተረዳሁት የኔ ካህን ።

ስልኩ ሲቋረጥ ከንፈሬን ወደ ስክሪኑ ሰድጄ ሳምኩት ።

እኔ የሱ መቅደላዊት ማርያም ... 

በደሌ በፍቅሩ የሚነፃ ከሆነ ብዬ በእንባዬ ራስኩኝ።

....

በዛኑ ቀን ዶክተር እዘዝ ደወለ።

በሙት ስሜቴ ስልኩን አነሳሁት ። እድለ ቢሶች ከምንወደው ነገር ይልቅ የማንወደው ነገር ይከተለናል ። ዶክተር እዘዝ ን አልወደውም። በተለይ ከዛ ክስተት በኃላ የርኩሰቴ ቤንዚን ሆኖ ይሰማኛል።

"ጣፋጯ " አለኝ።

መራሩ ልበለው ይሆን?

"ይቅርታ ዶክተር ...እንደዚህ አትበለኝ "

" ምነው አንዴ የቀመሽውን ገላ መድገም አትወጅም መሰለኝ። ይሄ እኮ የሴቶች ሳይሆን የእኛ ባህሪ ነበር ለወትሮው ...

ቂ....ቂ...ቂ ..."

ሳቅ ይሄን ያህል ይቀፋል?

"ሁሉም ነገር ባጋጣሚ ነው የሆነው "

ቲቸር እዘዝ ቀፋፊ ሳቁን ቀጠለው ።

"ቂ....ቂ ...ቂ 

ለማንኛውም ተረጋጊ ...ጥሩ ጊዜ ነበረን። ጥሩም ሆነን ሴሚስተሩን እንጨርሳለን"

ይሄን ሲል እየዛተ ነው። ለኔ ጥሩ ካልሆንሽ ጥሩ ጊዜ አይኖረንም ሊለኝ እንደፈለገ ግልፅ ነው።

"እባክህ..."

አላስጨረሰኝም ። ስልኩ ከወዲያኛው አቅጣጫ የመዘጋት ድምፅ አሰማኝ። 

ካሁን በኃላ ትምህርት ቤቴ ገሀነሜ ነው። 

ዶክተር እዘዝ የሰይጣኑ ቁንጮ ሉሲፈሬ ነው።

ዛክን በድዬ ከሱ ጋር ያሳለፍኩትን የአልጋ ላይ ጨዋታ እንደማልደግመው አውቃለሁ።

ገላዬን ስነሳው ደግሞ ነጥብ እንደሚነሳኝ እሙን ነው ። 

የኔና የሱ ግንኙነትን ደግሞ ዛክዬ ከሰማ ሌላ የህይወት ፍላት ላስተናግድ ነው ።

ሁለት ፍላት በአንድ እስትንፋሴ የምሸከምበት አቅም ያለኝ አይመስለኝም።

አልጋዬ ማህፀን ገብቼ ተሸፋፍኜ ተኛሁ ።

የውሸት እንቅልፍ ነበር ...

ሰኞ ትምህርት ቤት ስሄድ ለሚገጥመኝ ጦርነት ልቦናዬን ማዘጋጀት ጀመርኩ ።

አሸናፊው ማን እንደሚሆን እናያለን! 

@wegoch
@wegoch
@paappii
Forwarded from ❀ርብቂ Ribki Photography (Ribka Sisay)
በጠዋቱ በበሩ ሳልፍ ባንዲራውን ውጪ አስጥቷል....ባዶ እግሩን በራፉ ላይ ዘፍ ብሏል...ለንቦጩ አጀብ ነው...በደስታ የተወረረ ሰው ቢያየው ያኮርፋል...የሚጋባ ለንቦጭ አጣጣል...ወይ ጉድ!!!

ማንን ይሆን ያኮረፈው?
ባንዲራውን??

ነገሩ ትላንት ማታ ሰክሮ ሲዘፍን ሰምቼው ነበር.....

ተደጋግፈን እንዳወጋን ...እኔም ያንቺ አንቺም የኔ ወገን....ተለጣጥፈን እንዳዜምን ...እኔም ያንቺ አንቺም የኔ ዘመን...መኩሪያራዬ መነሻዬ የኔ ዘለበት....መከታሽን ደጀንሽን ምን ባጠፋው ተውሽኝ....ተለየሽኝ

እያለ ሲያላዝን ነበር ...በስተመጨረሻማ በታተንሽኝ እያለ ይጮህ ጀመር...ይሄ ማህበር የሆነ ሰውዬ😏
.............
Photo: Mar,11,22
Addis Ababa,Ethiopia
© Ribka Sisay
@ribkiphoto
................
2024/09/26 21:46:30
Back to Top
HTML Embed Code: