Telegram Web Link
"ስማ.. .ስማ.. .!"
ዞር አልኩኝ። ለ ሰባት ዓመታት በግዳጅ የቆየ ወታደሩ የሰፈሬ ልጅ ነው ። አጎንብሶ ስለነበር አይቼው ልደበቅ አልቻልኩም ። ኩሪ ሰፈራችን መሀንዲስ ውስጥ ከገባበት ቀን ጀምሮ ትዕቢተኛ ውሪዎችን አደብ ስላሲያዘልን እወደዋለሁ። ገና መቀመጫቸውን በቅጡ ሳይጠርጉ ቺክ ለመጥበስ ተፍ ተፍ የሚሉ...ሞተር ሲነዱ ቆሌያችንን የሚገፉ ታደጊዎችን የእጃቸውን ይሰጥልናል።
እሱ እጅ የገባ ፍንዳታ ታዳጊ በጠረባ አየር ላይ ደንሶ ይመለሳል።
ይሁንና በዚህ ተግባሩ ብወደውም ብዙ ጊዜ ብር ስለሚለምነኝ ግን በሩቅ ሳየው ገና እደበቅበት ነበር። ለሶስት ጊዜ ያህል ገንዘብ ጠይቆኝ በአሉታ ስለመለስኩለት ቂም ቆርጭሞብኛል።
ሰሜን እዝ ውስጥ ዓመታትን አስቆጥሯል። ብልግና.. .ማነው ይቅርታ ብልፅግና መንግስት ኢትዮጵያንና ኤርትራን ሲያዋህድ የተፈጠረውን ነገር ያጫወተኝ ቅፅበት አትረሳኝም።
የደስ ደስ ተብሎ ወታደሩ በገፍ ቢራ ቀርቦለት ተፍታታ...የኢትዮ ወታደር ወደ ውሀው ጠንከር ይላልና የቢራ ጠርሙሶችን እንደ ቁልፍ አቅጨለጨላቸው።
የኤርትራ ወታደር ሁለት ቢራ ልፈው ፀጥ እረጭ ሆነ ነገሩ...
የወገን ጦር "እነዚህ ሰዎች ተታርቀንም ሌላ ጉድ ሊያመጡ ነው እንዴ?" ብለው ተጠራጠሩና "ጠጡ እንጅ " አሏቸው በግብዣ መልክ ...
የኤርትራ ወታደሮች ይሄን ጊዜ ነው ...
"ኢትዮጵያ ውስጥ ከሁለት በላይ መጠጣት ይቻላል ወይ ?🤔" ብለው የተገረሙት ።
ኤርትራ ሁለት መሎቲህን ልፈህ ሌላ ቢራ ሊጨምር ካልክ የኢሳያስ መንግስት ጉድጓድ ይጨምርሀል ።
ኤርትራ በመዓቀብ ብዛት ከዘመነኛ ስልጣኔ በትንሹም ቢሆን ተኳርፋለች።
እንደውም ሀሜት አይሁንብኝና የ ATM ማሽን ሲያዩ ብርቅ ሆኖባቸው ሰልፊ የተነሱም ጓዶች አሉ ተብሎ ይወራል 🙄
እዚህ ሸገር ቤተልና 22 የሚገኙ ኤርትራውያን ተዝናኖትን የማይጠግቡበት ምክንያት ይሄ ነው።
አንድ የኤርትራ ወጣት ጀማ ሺሻ ሲነፋ ካያችሁ ጎጆ ቤት የተቃጠለ ሊመስላችሁ ይችላል ።
ደግሞ ጨላ በሽ አላቸው... አሸን ዲያስፖራ በሚልክላቸው ብር ውስኪ ውስጥ ዋኝተን ዛሬውኑ ሻርክ ካልሆንን ይላሉ ። ሀያ ሁለት ሰፈር ኤርትራውያን ሲገቡ ቤት ኪራይ ደመና ልሶ ይመለሳል። የክብሪት ቀፎ የምታክል ክፍል ስድስት ሺህ ብር ለመከራየት እጃቸውን ወደ ኪሳቸው ቀለል አድርገው ነው የሚጨምሩት ።
"ወዬ"
"ወደየት እየሄድክ ነው?"
"ቢሮ "
ፈገግ አለ ...
"ይሄ ኮብልስቶን እንዲህ ፈራርሶ ስታይ ምንም አይሰማህም ? ካሁን በኅላ መኪና በዚህ እንዳያልፍ ድንጋይ እንደርድር "
ትዕዛዙ እንደ ሞዴሊስት ወገብ ቀጠን ያለች ነች። ታናሼ ነው... ታናሼ ነው ብዬ ትዕዛዙን አልንቅ ነገር በዚህ የጅብ ግራ እግር በሚያህል ክንዱ ያደባየኛል 😑
ሸሚዜን ሰብስቤ ድንጋይ መደርደር ጀመርኩ ... ከደቂቃዎች በኋላ ሰዓት እንደረፈደብኝ በምልክት ሳሳየው የፊቱን ሌላ መልክ ገልብጦ አሳየኝ።
እግዚኦ ማስፈራቱ !
ድንጋይ ማጋዜን ቀጠልኩ ። ከሰዓታት በኋላ ቢሮ የደረስኩት ወፍጮ ቤት የተቀጠረ ፈጪታ መስዬ ነበር ።
እንደውም ፊትለፊት የምትቀመጠው ፀሀፊያችን አቧራዬን አይታ "ሳላስብ ፀልዬ የሚለው የያሬድ ነጉ ቀረፃ ላይ ነበርክ እንዴ? የዱባይ አሸዋ መስለካል" ብላ ተላላጠችብኝ።😐
ኩሪ ሰፈር ውስጥ ስለሚውል እንከን ማውጣት አይታክተውም...እኔ ወራትን የተመላለስኩበት መንገድ ኮብልስቶን መንገድ እንደሆነ እንኳ ልብ ያልኩት "የኮብልስቶኑ መፍረስ አይታይህም ወይ?" ብሎ ሲያንባርቅብኝ ነው።
በዛ ላይ ሰፈር ውስጥ ያለ ለቅሶና ሰርግ ላይ በማገልገል ማንም አይደርስበትም...ድንኳኑን ብቻዬን ካልተከልኩት ነው የሚለው !
በየቀኑ ሰፈር በመጣሁ ቁጥር አዳዲስ ነገሮች ይገጥሙኛል ።
ችጋር ያራቆታቸው ደራቃ ተክሎች ሁሉ ውሀ ጠገቡ... ጭራሽ የሰፈራችን ውሪዎች ጋሽ አበራ ሞላ ሆኑብን...መንደሩ እንደመስታወት ያንፀባርቃል።
...
ዛድያ እኔም አመሻሽ ላይ ድንጋይ ሸከማውና የቢሮው ስራ የመጠጠው ጉልበቴን ለማሳረፍ ወደ ቤቴ ከነፍኩ ።
ሆኖም ቀዬ ስደርስ እነዛ ነገረኛ ሽማግሌ ሌባ ጣታቸውን ጠቆሙብኝ። ሰፈሩ በፖሊስና ደንቦች ተወሯል። CCTV ካሜራ ሆነው ወሬ የማያመልጣቸው ባልቴቶች ወገባቸውን ይዘው "ቀ" ፊደልን መስለዋል።
አንድ ብጉራም ፖሊስ ዱላውን አንጠልጥሎ ወደኔ ተንደረደረ ...
"ምንድነው?"
አንዴ ወገቤን ነርቶ አንቆራጠጠኝ ።
"እንዴ በህግ አምላክ !"
"እናንተም ህግ ታውቃላችሁ እንዴ? እስክንድር ነጋ መንገድ እንድዘጉ ያሰማራህ ፋኖ እንደሆንክ ደርሼበታለሁ "
በድንጋጤ አይኖቼ ፈጠጡ ...
ኩሪ ደረቱን ነፍቶ ከፖሊሶቹ ጋር ተጠጋኝ ።
" ስማ መንግስት በአንካሴ የሚሄድ አካል ጉዳተኛ መሰለህ እንዴ? መንገድ በድንጋይ በመዝጋት የሚወርድ መንግስት የለም እሺ?"
ይሄን የሚያወራው ጠዋት ድንጋይ እንደርድር ብሎ ያዘዘኝ ኩሪ መሆኑን በመጠራጠር አይኖቼ ደጋግሜ አሻሸኋቸው 🙂

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Mikael aschenaki
ነግሬህ ነበር እኮ "አንተን ሳስብ ፈገግ ማለት እፈልጋለው እባክህ ሳቄን አትቀማኝ" ብዬ። አልገባውህም ወይም እኔን መረዳት አትፈልግም ነበር፤ ሁሌም እንደምትለው "አታወሳስቢብኝ" አልክና ምንም ያላልኩህ ያህል እረሳህው፤ እኔ ግን አንተ ጋር ዋጋ ማጣቴ ላይረሳኝ ከልቤ ታተመ።
እያወሳሰብኩ አልነበረም ሁሌም ለኔ ያለህን መልካምነት ፍቅርህን ለመፃፍ ብዕሬን ሳነሳ በተለመደው ግዴለሽነትህ ታንሻፍፍብኛለህ ፤እናም የማልፈልጋቸውን መስመሮች አሰፈርክበት። አላወከውም ልስለው የነበረ ድምቀትህን እንዳደበዘዝከው፤ የትዕግስቴ ፅዋ መጉድሉን አላስተዋልኩም ነበር።
ጥሬአለው፤ ስላንተ እንዳይደክመኝ ራሴን ሳበረታ ነበር ደጋግመህ እየወደክ አዛልክኝ እንጂ። ልቤን በእጆቼ ለመሸፈን ብሞክርም የምትሸረሽረውን ፍቅርህን ማስቆም አቃተኝ።
እባክህ ይቅርታ አትበለኝ፤ ስለረሳሁህ ይመስልሀል የተለየውህ? "ያለኔ መኖር ቻልሽበት አይደል" ትለኛለህ፤ ችዬ አይደለም መቻሉን ስጠኝ ብዬ እንጂ።
መሸምደድ በቀረው የንባብ ልክ የፃፍክልኝን መልዕክት ዛሬም እንደማነበው ማን በነገረህ። ይግረምህና ደጋግሜ ከማየቴ የተነሳ ተሰጥኦ ቢኖረኝ ፎቶህን ሁላ እስለው ነበር።

ቁምነገሩ ምን መሰለህ ከኔ ጋር ትሆን ይሆናል አብረህኝ መሆን እንደማትችል ግን አውቀዋለው። እንደምታፈቅረኝ ትነግረኝ ይሆናል እንዲሰማኝ ማድርግ ግን አትችልም ። አንተ እንዲህ ነህ ላይ ላዩን እንጂ ጠልቆ መኖር አታውቅበትም። ወደ አንተ ብመለስ ደጋግመህ ትሰብረኛለህ፤ ስለዚህ "ተመለሽ" አትበለኝ። እንኳንስ ብለህኝ ቀድሞውኑ እግሮቼን በትግል ነው ያቆምኳቸው። እስኪ የተሰጠውን ፍቅርና ክብር ረግጦ ወደ ችላ ባዩ አንተ ልሂድ የሚለውን ልቤን መንገድ አትክፈትለት። ፈጣሪ ክሶኝ የለ በቃ አመስግኜ ልኑር፤ ባለህበት ሰላም ሁንልኝ።

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Mahlet
ሥዕል በማሳል ለ ወዳጅ ዘመዶ ስጦታ ያበርክቱ
በ+251984740577
ወይም @gebriel_19 ላይ ፎቶ በመላክ በ ተመጣጣኝ ዋጋ ማዘዝ ይችላሉ!
#ሥዕል_ብቻ የቴሌግራም ገፅ


@seiloch
@seiloch
01/07/14
ዛሬ የቀብሯ ማግስት ነው፤ ይህቺ ጎበዝ ይህቺ ብርቱ ይህቺ ትሁት የጨለመችበት ማግስት። ግርግዳ ለይ የተሰቀለው ፎቶዋ ለይ ፀጉሯን ጉንጉን (የትግሬ ሹሩባ) የሚባለውን አይነት ተሰርታ ሰማያዊ ጥለት ባለው የሀገር ባህል ልብሷ ለይ በፈገግታ ደምቃለች። ሰዉ እሷን ማጣቱ አንጀቱን በልቶት እጥፍ ብሎ ያለቅሳል እሷ ግርግዳዋ ለይ ፈገግ ብላ ትመለከታለች። ለወትሮው የሰው ሀዘን የሚነካት ፈጥኖ ደራሽ እንባ አባሽ ነበረች ታዲያ ለምንድነው ዛሬ በዚህ ሁሉ እንባ መሀል ፈገግ ማለቷ?

ቤቷ ስገባ እግሬን መቆም እስኪከብደው ሰውነቴ ራደብኝ፤ ይሄን እልፍኝ አውቀዋለዋ ወጣ ገባ ብላ አስተናግዳናለች እንጀራውን ዘንጠፍ አድርጋ ቆርሳ አጉርሳናለች፣ እሷ ጋር "በቃኝ" የሚለው ቃል እዚህ ግባ አይባልም፤ ሰው በልቶ የሚጠግብ አይመስላትም ማዕዱ ሳይጎድል በላይ በላዩ ለመጨመር አርፋ አትቀመጥም ነበር "እረ ፀጋ በቃሽ" እንላታለን በጀ አትልም መሶብዎን እስክታራቁት ብሉልኝ ነው፤ እጅ ሰፊ ናት። ዛሬ ግን ይሄ ሁሉ እንግዳ ቤቷ ተሰብስቦ ብሉልኝ የለ ቁጭ በሉ የለ ፈገግ ማለት ብቻ።

የደግነት ልክ ናት ሰው መውደድ አይድክማትም "ፀጋ እኮ ፔርሙዝ ተሰብሮባት በጆግ ሙቅ ይዛ መጥታ የጠየቀችኝ ሴት ናት" እያሉ አንዲት እናት ያለቅሳሉ እሷ ያሮጠችበት ቤት ያለተሸከመችለት ሰው የለም። እናቴን አሟት ቡናውን ስኳሩን ከሰሉን...... እየተሸከመች መጥታ ትጠይቃት ነበር።

ያቺ ትንሽዬ ቤት ሁሌም በሰው እንደተሞላች ነበር የዘመድ ማረፊያ መሰብሰቢያ ናት። የራሷን ልጆች ጨምሮ የባለቤቷ የዘመድ ልጆች እሷ ነበረች የምታሳድጋቸው፤ የሁሉ እናት ናት።
እንደውም ከአመት ወይ ቢበዛ ከሁለት አመት በፊት ሰፈር ውስጥ አንዲት ህፃን ከነ ጡጦዋ ተጥላ ትገኛለች። ከዚህ በፊት ልጅ ባገኝ አሳድጋለው የምትል ጓደኛ የነበረቻት ፀጋ ልጅቷን ትውስዳታለች ነገር ግን ህፃኗ ክስት ያለችና ብዙ የጤና ችግር የነበረባት በመሆኑ ጓድኛዋ እንደማትፈልግ ነገረቻት። ልበ ቀናዋ ፀጋ ግን "የእግዚአብሔር ፍጡር ናት እሱ ካዳነ ያድናት ካልሆነም እንደወደደ ያድርግ እኔ ግን የቻልኩትን አደርጋለው" ስትል ሆስፒታል ይዛት ገባች። ለዚች ህፃን ስትል ያላየችው መከራ ያልተጋፈጠችው ስቃይ አልነበረም። ሰው ሁሉ "በማረፊያሽ ሰአት ከልጅ ጋር ለምን ትንገላቻለሽ እዚው ሆስፒታል ጥለሻት ውጪ" እያሉ ቢወተውቷትም እንኳን ለሰው ሟች ለሆነችው ፀጋ የሚታሰብ አልነበረም ፈጣሪም ረዳትና አሳክማት ድና ወጣች ዛሬ ወፍራ ድክ ድክ ስትል ለሚያያት ሰው ታሳሳለች።
በየቤተክርስቲያኑ ጥበቧን ለብሳ ልጇን አቁርባ አዝላ ስትመለስ ሳያት ብርታቷ ያስደንቀኝ ነበር። ማነው ባለተመቻቸ ኑሮ፣ ብዙ ልጆች እያሉት፣ ጉልበቴ ደክሟል በሚልበት ሰአት የተጣለ ልጅ ያውም በሽተኛ ለማሳደግ የሚፈቅድው? ይህቺ ናት እንግዲህ ፀጋ ማለት።

ለልጆቿ ስትል የማትጋፈጠው ፈተና አለነበረም፤ ከነ ስህተታቸው ከነ ጥፋታቸው መደበቂያ መሸሸግያቸው ነበረች "ነብር ናት" ትላታለች እናቴ በጭራሽ አታስነካቸውም ነበር፤አሳልፋ አትሰጥም። ስንቴ በእነሱ ምክንያት ዝቅ ብላለች ፣የስንቱ እግር ለይ ለይቅርታ ወድቃለች፣ ከሰው አንሳለች፣ ተሰድባለች ተንቃለች፣ ተደብድባለች፤ እንዲህ አደረጉ የሚል ቃል ግን ከአፏ አይወጣም "በቃ አጥፍተዋል ልጆች ናቸው" ብላ ስህተታቸውን ሁሉ ድብቅብቅ ታደርግላቸዋለች።
ሁሌም እየስከረ በሚመጣ ልጇ ምክንያት "የስንቱን እንባ አብሰሻል ስንቱን አቃንተሻል የኔንም ልጅ ካላስተካከልሽልኝ ድጅሽ አልመጣም" ብላ ከ ቅድስት ኪዳነ-ምህረት ጋር የተኮራረፈች የዋህ እናት እኮ ናት።

ሁሌም ስታገኘኝ "እናትሽ ልትረሳ ትችላለች አንቺ ግን አስታውሰሽ ለምርቃትሽ ጥሪኝ እሺ አደራ ሳልሰማ እንዳልቀር" ትለኝ ነበር እንዲህ ለምትቀረው፤ እንዴት ጠራታለው? ብትሰማስ የት ትገኝና ነው?
ከእናቴ ጓደኞች ውስጥ ልቤን የምትገዛኝ እሷ ነበረች። ፈገግታዋ፣የአነጋገር ለዛዋ፣ብርታቷ፣ ደግነቷ፣ፍቅሯ.....አይኔ ለይ የሚሳልላት ደርባባ ሴት ናት።
የቀናነቷን ያህል ያለቦታው ለሚነካት የማትመለስ ቁጡ ነብር ነበረች።ስንቱን በሌሎቹ በለመደው ጋጠወጥነት ላሳንስሽ ሲላት አልደፈርም ብላ ልክ ያስገባች ቆፍጣና ሴት።

አሁን አሁንማ ሀገሬን ትመሰለኝ ጀምሯል፤ እጀ ሰፊ፣ እንግዳ ተቀባይ፣ የሁሉ ማረፊያ መሰብሰቢያ አድባር፣ የደግነት ልክ፣ የቸርነት ሙዳይ፣ የትህትና ተምሳሌት፣ አትንኩኝ ባይ የክብርና የጀግንነት ምሳሌ፣ ሳቂታ ተጫዋች ደርባባ እናት!

ያቺ ትንሽዬ ህፃን ወደፊት አድጋ ሁሉ በተዋት ጊዜ ተቀብላ ተንገላታ በፈጣሪ እርዳታ ሰው ያደረገቻት ሀገር የመሰለች እናት እንደነበረቻት ስታውቅ ምን ትል ይሆን ስል አስባለው? ገመና ከታች፣ ቦርቧራ፣ ትግስቷ የማያልቅ እናታቸውን ያጡት ልጆችስ እንዴት ይችሉት ይሆን? የቤት ምሰሶ፣ የሌት ብርሃን፣ የጎጆ ሙላት፣ ክፉን መሻገሪያ ምርኩዝ፣ የወጣትነት ጌጥ፣ የእርጅና ሞገስ፣ የዘመናት ጓደኛና አጋር የልጆቻቸውን እናት ያጡት አባወራ የሀዘናቸው ጥልቀት እንደምን ያለ ነው?

አንቺ ዘወትር ከልብ የማጠፊ የሁሉ ቁጭት ነሽና ፈጣሪ በመሄድሽ ላጎደልሽበት ሁሉ መፅናናቱን ይስጠው፤ ላንቺ ደግሞ በየ አመቱ ደግሰሽ የምትዘክሪው ቅዱስ ገብርኤል በእግዚአብሔር ፊት ቆሞ ነፍስሽን በገነት ያሳርፍልሽ!!!
"እወዳቹሀለው" የሚለው ቃል አይደል ከአንደበትሽ ዘውትር የሚፈልቀው እኛም እጅጉን እንወድሻለን!!!

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Mahlet
ከብዙ ለዛ ቢስ ዙሪያ ጥምጥም ወሬ በኋላ ፤በልቧ በሰነደችው ቃላት አማካኝነት ከኔ ጋ በፍቅር መቆራኘታችን ይብቃ አለችኝ። ፈገግ አልኩ ። እሷ ለመለየት የወሰነች እለት እኔ ምን እያሰብኩ ነበር?። ለጓደኛዬ በዚህ አመት እንደማገባት እየነገርኩት ነበር ፤ ባስቀየመችኝ ተብሰልስዬ ለማስተካከል መንገድ እየቀየስኩ ነበር ።
እንለያይ ስትለኝ ፈገግ አልኩ ። እንደዚህ ስፈግ ምን እንደሚሰማኝ እንጂ ምን እንደምመስል አላቅም መለያየት የፈለገችው ሌላ የተሻለ ሰው አግኝታ ሊሆን ይችላል አልያም ድክመቶቼ ከአቅሟ በላይ ሆነውባት ወይ ደግሞ ሰልችቷት ብቻ ውሳኔዋ ከልቧ እንደሆነ ፊቷ ያስታውቃል ።
ፈገግ እንዳልኩ ቡናዬን ስኳር ሳልከትበት ፉት አልኩ ፤ የሚመር ነገር እስክንለምደው እንጂ ባይጣፍጠን እንኳን አይመረንም። ፊት ለፊቴ እንለያይ የምትለኝ ልጅ በፊት ፊቷ ከሁሉ ይለይ ነበር ፤ ከደቂቃዎች በፊት እሷ ግለሰብ ብቻ አልነበረችም ፤ ሃገር ታክል ነበር። እንቅስቃሴዋ ሁሉ ይመለከተኛል ፤ ስልጣን አለኝ ባይ ነበርኩ ።
የልጆቻችንን ስም አውጥተን ፤ ስለ ገቢ ምንጫችን አውጠንጥነን እና አደላድለን ስናበቃ
እንደዋዛ እንለያይ አለችኝ ፤ የአስተሳሰረን የአብሮነት መስመር ግዙፍ መስሎኝ ነበር። መለያየትን የማላቀው ነው የመሰላት። ዘጠነኛ B ክላስ እየተማርኩ ምሳ ልበላ እና ፀጉሬን የምቆረጥበት ፍራንክ ከእናቴ ልቀበል ስመጣ ነው ልቧን ታማ ስታጣጥር የደረስኩት። ሃያ ደቂቃ አልሆናትም ፤ በስስት እያየችኝ ነው የተለየችኝ ፤ በስስት ከሚወደኝ ጋ መለያየት በልጅነቴ እየተነፋረቅኩ ተጋፍጬዋለሁ። መለየት አዲሴ መስሏታል። የካምፓስ ፍቅረኛዬ ፤ ባህር ማዶ የጉልበት ሰራተኛ ለዛውም የአሳማ ስጋ ሻጭ የሆነን ከኔ ጋ አወዳድራ እና ፍቅሬን በሳንቲም አጣፍታው ጥላኝ ሄዳለች። እየለመንኳት ፤ ነገዬ ብሩህ እንደሚሆን እየማልኩላት ፤ ለመለየት ሰበብ ስትደረድር ፤ በፍቅር እና በሎጂክ ሰበቧን ስታገለው ፊት ለፊት እየቺች ነው ጥላኝ መሄድ ያልከበዳት። ከባሏ ጋ ደስተኛ እንዳልሆነች ፤ ልጅ እምቢ እንዳላቸው ስሰማ ፤ የአሁኑን ፈገግታ ነው
ፈገግ ያልኩት ፤ በደስታ አይደለም በግርምት እንጂ። ከእኔ ያጣችውን ሳንቲም ለመሙላት ሄዳ እኔ የነበረኝ ጎደላት። ይሄ ፈገግ ያለ ፊት ስንት መለየት እንዳስተናገደ ፤ ይሄ የምታየው ፊት በመለየት ስንቴ እንደ ተሰበረ ከእኔ በላይ ማን ያውቃል። እንለያይ አለችኝ ! መለያየት እኔ መች ይከብደኛል ? አምኖ አብሮ መኖር ነው እንጂ ፤ አሁን እኔ ቁስሌን ፣ ፍርሃቴን እያወቀች እንለያይ ማለት አለባት? ለምን የለባትም ፤ ማን አዝኖ በፍቅር ይዳበላል። ዝም ብዬ ተረጋግቼ ሳያት ። ይሄን ልነገርህ ነው የመጣሁት አለችኝ። አብረሺኝ ሁኚ ተብሎ አይለመን ፤ አብረሽኝ ሁኚ ብሎ የለመነ ፤ ተለማኙ አብሮ መሆንን እስኪያምን በፍቃድ ራስን ለባርነት አሳልፎ መስጠት ነው !
ዝምታዬ ገርሟት ፤ ዝም ብላ ስታየኝ ፤ ለጠጥ ብዬ እንደተቀመጥኩ ፤ አንዱ እግሬን አንዱ ላይ አነባብሬ ትርጉሙ በማይገባ ፈገግታ አናቴን ነቀነኩት። አልገባትም ማንን አልፈልግም እንዳለች!

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Adhanom Mitiku
መንገድ ላይ የጀበና ቡና የምትሸጥ ሴት ማፍቀርኮ ችግር የለውም። ችግሩ ፉክክርህ ከግንበኛ፣ ከተራ አስከባሪ፣ ከአናፂ ምናምን ጋር ነው።

የማስተርስ ዲግሪ ሰርቼ...ስምንት አመት ሙሉ የባንክ ስራን ቀጥቅጨ...ያሰብኩትን ሁሉ ጨብጬ...የአልማዝ ልብ ግን ከመንገድ ወያላዎች ለይቶ አያዬኝም። "የሴት ልጅን ልብ የሚያሸንፈው ያልተጫወተ ነው" የሚለው የእማዬ ምክር እዚህ ላይ አይሰራም። በኑሮ ሰባት እጥፍ የምበልጣቸውን ሰዎች በምላስም በልጨ መገኘት አለብኝ። ችግሩ መሰሎቼ ስላልሆኑ ያ ባለጌ ሽመልስ እንደ ኮሜዲያን የሚታይበት ዳስ ውስጥ የኔ ቀልድ እጅ እጅ ይላቸዋል። አንዳንዶቹማ እያወራሁ በፈጠጣው አቋርጠውኝ ሁላ ሌላ ወሬ ይጀምራሉ። ሽመልስ ማውራት ሲጀምር ግን አልሚ ራሱ ቡና መቅዳቷን ቆም ታደርጋለች (ስትስቅ እንዳያስደፋት መሆኑ ነው። ገና ሲጀምር እንደሚያስቃት እርግጠኛ ነች።) እኔ
በበኩሌ ከሚያሰቀው ነገሩ ብልግናው ስለሚበዛብኝ ሁሌ እንደተሸማቀኩ ነው።
<<አባቴ 'ሽመልስ' ያለኝ ከበቶቼን የሚጠብቅ እረኛ ተወለደልኝ ብሎ ነው። እኔ ደግሞ የህይወቴ ጥሪ ከዚህም በላይ ነው ብዬ ጠፍቼ መጣሁ። እረኝነት እጣፈንታዬ እንደሆነ የገባኝ ግን እዚህም መጥቼ መኪና ሳግድ ነው!>> <<ታዲያ የትኛው ተሻለህ...የከተማው ወይስ የገጠሩ እረኝነት?>> ይለዋል አንዱ ሰው መስሎት።
<<ተመልሼ መግቢያ የለኝም እንጂ የገጠሩ ይሻለኝ ነበር። እዛኮ ቢያንስ ሲደብረኝ አህያ እበ*ለሁ!>> ብሎ በሰላሳ አመት የሰበሰብነውን ቀልብ ይገፈዋል። የፈለገው እንስሳ ጋር ሴክስ ማድረግ ይችላል...እሱ የኔ ጉዳይ አይደለም። ችግሩ ምንም የመጀናጀኛ አየር እየሰጠኝ አይደለም። እሱ ባለበት አይደለም መጀንጀን ወሬ መጨረስ ራሱ አልቻልኩም። <<ባለፈው መኪናዬ ስታክ አድርጋብኝ...>> ብዬ ስጀምር <<አይይ!... አሁን እዚህ ማን ስለመኪና ያውቃል ብለህ ነው?>> ብሎ ያናጥበኛል። <<የተፈጥሮ አድናቂ ነኝ።>> ብዬ ረጅም ሳክስ ስጀምር <<ቡና በስኳር እየጠጣህ የተፈጥሮ አድናቂ ነኝ ብትለኝ አላምንህም>> ብሎ ባጭሩ ይቀጨኛል። አሁን አሁን ገና ከሩቅ ሳዬው እንደ ስፔን ኮርማ ተንደርድሬ ልወጋው ሁሉ ያምረኛል። ወዲያው ከሀሳቤ ብንን ስል ፍቅር የት ድረስ እንዳወረደኝ አስብና እገረማለሁ። እንዲህ አብሮ መዋል ሳያናንቀን በፊት በፊት ሽመልስ ይመቸኝ ነበር። መኪናዬን ይዤ ስመጣ ቆንጆ የፓርኪንግ ስፓት እንዳገኝ ይረዳኛል። የሆነ ቀን ከመኪናዬ ሳልወርድ <<እስኪ ቡና እዘዝልኝ>> አልኩት። አንዲት ቀይ ልጅ የጀበና ቡና ይዛ መጣች። ከቡናዋ ጋር ምን እንዳቀመሰችኝ አላውቅም ከዛ ቡኃላ ልክ አይደለሁም። ፈገግ ስትል ብቅ የሚለው የተነቀሰ ድዷ አብስትራክት ስዕል ይመስል በየ ደቂቃው የአንገቴን አቅጣጫ እየቀየርኩ አየዋለሁ። ፓንቷ ውስጥ ሻጥ አድርጋው የምትሔደው ሺቲ በተንቀሳቀሰች ቁጥር በዳሌዋ ሲያስገለምጠን ይውላል። ስትስቅ ድዷ...ስትራመድ ዳሌዋ! እህህ ሁኗል የኔ ኑሮ!
ታዲያ እኔ እሷን...እሷ ደግሞ ሽመልስን እንደምትወድ ለመረዳት ብዙ አልፈጀብኝም። በብልግና ቀልዱ መሳቅ ብቻ አይደለም...ጭራሽ <<ብልግናቸውን የማይደብቁ ሰዎች ጨዋ ነው የሚመስሉኝ>> ብላ ልትደግፈው ትሞክራለች። ፍቅር የሚባለው የበሽታ አይነት ሲይዝ መጀመሪያ የሚያጠቃው መለኪያ ሚዛንህን ሳይሆን አይቀርም። ለኔ አልማዝን አለም ላይ የትም መገኘት የማትችል እንቁ አድርጎ ያሳዬኛል። ለሷ ደግሞ ሽመልስን አርብ ሮብ የሚፆም ጨዋ አድርጎ ያሳያታል። ቢሆንም...ቢሆንም! እሷን የመጥበስ እድሌ ተንጠፍጥፎ እንዳላለቀ ይሰማኛል። አንድ ጧት እንደመጣሁ አምስት መቶ ብር የሻይ ሰጠሁትና ራቅ ወዳለ ሰፈር ላኩት።
አልሚን ብቻዋን አገኘኋት። <<የሆነ ቆንጆ ሬስቶራንት አለ። ዛሬ የሚመችሽ ከሆነ ራት ልጋብዝሽ!>> አልኳት...ስለማመድ የዋልኩት ይሔ መሆኑን ለራሴም ማመን እያቃተኝ። <<ውይ ደስ ይለኝ ነበር። ግን ዛሬ አክሴቴ ከገጠር ትመጣብኛለች። ወይ ሌላ ቀን
እናድርገው?>> <<ኧረ ችግር የለውም። ያን ያህል አንገብጋቢ ነገር አስመሰልሺውኮ!>> ከረባቴን
አላላሁትና መልሼ አጠበኩት። ተነስቼ ወጣሁ። ደሜ ፈልቷል። ውስጤ አላመናትም። ሽመልስ እንደመጣ <<ዛሬ የት ነህ? ከስራ ስወጣ ለምን አንድ ሁለት እንልም?>> አልኩት። <<ውይ በጣም ደስ ይለኝ ነበር። ግን ዝናቡን እንደምመጣ ቃል ገብቼለታለሁ!>> አለ የሰጠሁትን ብር አገላብጦ እያዬ! አያውቅም ብሎ ስም እየፈጠረ እንደሆነ ገብቶኛል። <<ዝናቡ ዝናቡ?>> <<ዝናቡ ይሔ ባለፈው 'ቶሎ ባይነሳ አፉ ላይ ያለው የጠጅ ሽታ ሊያሰክረኝ ነበር' ብለህ የቀለድክበት>> እውነት ለመናገር ሊያስመልሰኝ ነው የነበረው። <<አስታወስኩት! ታዲያ ለምን እኔ እናንተ ጋር አልመጣም?>> <<ኧረ አይሆንህም!>>
<<ግዴለም! ይልቅ ቆንጆ ጠጅ ቤት ውሰዱኝ!>> ሳይመልስልኝ ጥዬው ገባሁ። ከስራ እንደወጣሁ ባኮረፈ ፊት ይዞኝ መሔድ ጀመረ። ጠጅ ቤት ከገባን ቡኃላ ከሁሉም ተነጥለን የራሳችንን ወሬ ለመጀመር ሁለት ብርሌ ነው የፈጀብን። ያለ ሰበብ እንዳልመጣሁ ገብቶታል።
<<አልሚን ትወዳታለሀ?>> አለኝ ሌሎች እንዳይሰሙን እየተጠነቀቀ! በጥያቄው አልተገረምኩም። <<ፍቅር የሰው ልክ አያውቅም ወዳጄ። ያንንም ያንንም ሲጨብጥበት በቆየበት እጁ ነው የሚጨብጥህ! መጨበጡን እንጂ ማንን እንደጨበጠ አያውቅም። እውር ነው። የሚመመራን ግን እሱ ነው። የምለው ገብቶሀላ?>> <<ይሔ ቢገባኝ የመኪና እረኛ ሁኜ እቀር ነበር ብለህ ነው?>> <<ልልህ የፈለኩት ፍቅር ደረጃ የማይለያይ ደጋሽ ነው። የመኪናውን ባለቤት ከመኪናው እረኛ ጋር ጠጅ ያስጠጣል!>>
ፈገግ አለ። <<ተውልኝ ልትለኝ እንደመጣህ ገብቶኛል። እኔም ልልህ ነበር።>> <<እና ለምን አላልከኝም?>> <<ትርፉ ድካም ነው። እሷ የምትወደው አንተን!...ለምን ጊዜዬን አባክናለሁ?!>> ከስካሬ ነቃ አልኩ። <<እኔን እንዳጫዋች ነው የምታዬኝ። አንተ ስትመጣ ግን ያለባህሪዋ ቆጠብ ትላለች። እንድትወዳት ለማድረግ ትጥራለች። እኔ ምንም አይነት ሰው ብሆን ለሷ አይን አልሞላም።>> እንባ አቀረረ። ይሔን ንግግር እኔ ቀድሜው ባለማለቴ ደስ አለኝ። <<ይገባኛል ስሜትህ>> አልኩት ውስጤ እየተፍነከነከ። ፊቴን ያዘንኩ ላስመስል ሞከርኩ ግን አልቻልኩም። የሚታየኝ የአልሚ ቀሚስ ውስጥ ገብቼ አሸሸ ገዳሜ ስል ነው። ወዲያው ጥግ ላይ የነበረው ዝናቡ እየተንገዳገደ ተነስቶ ወደኛ መጣ። <<አንድ ሁለት መቶ ብር አላችሁ አንዴ?>> አለን
<<ለምንህ?>>
<<አሁን አይደል እንዴ ትዝ የሚለኝ? ለካስ ያቺን ቅንዝራም አልማዝን ቀጥሬያታለሁ! ህእ! >>
ሁለታችንም ደንዝዘን ቀረን። ደመናውን ሳናዬው ዝናቡ ከዬት መጣ? ሰማይ ሳያስገመግም
መብረቁ እንዴት መታን? ብሩን ተቀብሎን ሲወጣ ባለማመን እናየዋለን። በሩ ላይ ሲደርስ ዞር ብሎ <<ጠጅ እስቀምጡልኝ! ጠቅ ጠቅ አድርጊያት እመለሳለሁ>> አለንና በሁለቱም አይኑ ጠቀሰን። በህመም ስሜት አይናችንን ጨፈንን። "የሴት ልጅን ልብ የሚያሸንፈው ያልተጫወተ ነው!"

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Mikael Azmeraw
"እንደኔ እድለኛ የለም"
.........................

"እንደኔ እድለኛ የለም!" በሚሉ ሰዎች እጅግ እቀናለሁ።የዕድለኝነት ጠረፍ ላይ መድረስ ምንኛ መታደል ነው!!ምናልባትም ለመደሰት ጥቂት ነገር ከበቂ በላይ የሚሆንባቸው ሰዎች ቋንቋ ትሆናለች።በምናብ ብቻ የሚቦርቁ...እየጃጁ እንኳን ወደናታቸው ማህፀን በመመለስ ላይ ያሉ የሚመስላቸው አሉ መሰለኝ!ምናውቄ!

እኔ ለራሴ አዳሜን አስሼ ሳጣው እግዜሩ በ system ችግር ምክንያት ሴት አርጎ የፈጠረኝ የሚመስለኝ...ከማን የግራ ጎን እንደተሳብኩ ለማወቅ ድፍን 10 አመታትን በጀት መድቤና ፖሊሲ ነድፌ የተንቀሳቀስኩ የ36 አመት ሴተ ላጤ ነኝ።

ባስ ካለብኝ በመንገዱ መጨረሻ እጆቹን ዘርግቶ welcome honey የሚለኝ አንድ ጎምላላ የቀጠርኩ ይመስል አበደች እስክባል እጄን እንደ ክንፍ አስመስዬ እራመዳለሁ።ታክሲ ስሳፈር ከጎኔ የተቀመጠውን ሰው የቀለበት ጣት scan አደርጋለሁ።"ታክሲ ላይ ተዋውቀን ለዚህ በቃን..."የሚሉ እድለኞች ትዝ ይሉኝና ጅንጀናዬን እጀምራለሁ።ታክሲ ላይ ባል ሊገኝ😁

"እንዴት ዋልክ ወንድሜ?"እላለሁ።ሀፍረትና ይሉኝታ ሀገሩን እየዞሩ እንቁላላቸውን ሲጥሉ የኔን ቤት ዘለውታል። አንዱ ሙሉ ቶክሲዶውን ግጥም አርጎ ከጎኔ ተቀምጧል።

"እግዚአብሄር ይመስገን..." አለኝ ምን ልትይ ነው?ቀጥይ በሚል አይነት ቅላፄ።

"ደም ባንክ የት አካባቢ እንደሆነ ታውቃለህ?ብትጠቁመኝ..."

"አላውቅም"አለኝ ቀልጠፍ ብሎ!እውቅና ይንሳህ!!!!ከጎኑ የተቀመጠችዋ ባልቴት

"ሆስፒታሉ ግድም ነው"አለች።እኔ መች ባንኩ ጠፋኝ ባሉ እንጂ!አመስግኜ መንገዴን ቀጠልኩ....

ዕድለኝነት በሚሰማቸው ሰዎች የምቀናው ለዚህ ነው።ሙሉ ስላልሆንኩ...ብሶቴን የሚያባብስብኝ አንድ ዜማ አለ።

"ማመን አቃተኝ
የህልሜን ንግስት የኔ አረኩና
ብሩህ ቀን መጣ
ህይወት ሊታደስ ባንቺ እንደገና..."

እንኳን ህይወቴን የሚያድስ ላገኝ የተላጠ ግድግዳዬን በቀለም ለማደስ ከሚመጣ ቀለም ቀቢ ጋር እንድጃጃል እጣ ፈንታ እቶን ላይ የጣደኝ ከርታታ ነኝ...

"...ማን አለ እንደኔ
እድል የቀናው...ቀን የወጣለት
ምኞት ውጥኑ የሰመረለት..."

እነዚህ ስንኞች እኔና ብዙአየሁ(ድምፃዊው) የአርክቲክና የአንታርክቲክን ያህል የተራራቀ የስሜት ድንበር ላይ መቆማችንን ያስታውሱኛል።እንደገና እቀናለሁ!!!አለመታደልን እንደታደልኩ ሳስብ እበግናለሁ።

"...በፍቅርሽ ዜማ
ኑሮ ተቃኝቶ
ብርሀን ተሞላ
የኔ ዓለምማ....."

እኔ ፍቅር የሚያዜምልኝ...አዚሞም ኑሮዬን የሚቃኝ ባገኝ በነዛ ሰዎች አልቀናም ነበር።"እንደኔ ዕድለኛ የለም!"በሚሉት...እኔ አለሜን በብርሀን የሚሞላውን ያንን ጎምላላ ባገኘው ከዚህ በላይ እቀኝለት ነበር።

"....አልፈራም ነገን እንዳምና
አንቺ አለሽና
በፍቅርሽ ከፍ ያደረግሽኝ
እንደደመና...."

እኔ ግን ነገን እፈራዋለሁ።ምክንያቱም ነገዎቼ በሞላ ከዛሬዎቼ አይለዩም።ወራቱም አንድ ነው።የዐለም ዜና እንጂ እኔጋ የህይወት ዜና የለም።አዲስ ነገር የለማ!!!እንደደመና ከፍ የሚያደርግ ትስስር መስርቼ አላውቅም።እንደደመና ከፍ የምለው ሂል ጫማ ስጫማ ብቻ ነው።አሁንም ቀናሁ።በነዛ ሰዎች...."እንደኔ እድለኛ የለም!!"በሚሉት!!!

ተፃፈ በማዕዶት ያየህ(Geez)
17/04/2013ዓ.ም

@wegoch
@wegoch
@wegoch

#Tizur_12
የመንገድ እንቅልፍ(ክፍል አንድ)
(በማዕዶት ያየሕ)
============


እንኳን ሰበብ አግኝቼ ገጠር መሄድ እንዲሁ ያለአንዳች ምክንያት ያሰኘኛል።ገጠር እንድሄድ የሚወሰውሰኝ "አየሩ፣ልምላሜው፣የኩበቱ ሽታ..." እያሉ አማተር ዲያስፖራዎች የሚያለቃቅሱለት መልከዐ ምድሩ ብቻ አይደለም።ሰውም ጭምር እንጂ...ገጠሩ ሰው ሰው ይሸተኛል...ትክክለኛውን... ያልተቀየጠውን የአምላክን አምሳል እዚያ ብቻ የማገኘው ይመስለኛል።ወደዚያው ለመዝለቅ ወደ መናኸሪያ ስገሰግስ ልቤ በክንፋም ፈረስ ተጭና ወደ አፀደ ገነት ያረገች እስኪመስለኝ ሀሴትን አደርጋለሁ።በተቃራኒው የገጠር ቆይታዬን ጨርሼ ወደከተማ ለመመለስ የአያቴ ደጅ ላይ ወጥቼ ስቆም እረፍቱን ጨርሶ ወደ አዝል የጉልበት ስራው ሊመለስ እንደታዘ ዘ የተሸጠ ባሪያ ወሽመጤ ቁርርጥ ሲል ይታወቀኛል ።

ሰሞኑ የፋሲካ ነው።ወቅቱ የህማማት...የስቅለቱ ዕለት በማለዳ ወጥቼ ወደ መናኸሪያ በደስታ ተሞልቼ ገሰገስኩ።ወደዚያ የምድር ገነት ጎራ ከምልባቸው ዋና ዋና ምክንያቶቼ ውስጥ በዐላት ቀዳሚ ቦታ አላቸው።ያገኘሁትን ለዘመድ አዝማዱ አንጠልጥዬ ከመሄድ ሌላ ሙያ የለኝም።

ለአያቴ የገዛሁትን ጋቢ በስስ ፌስታል አንጠልጥዬ በአንድ እጄ፣ለሌሎች ዘመዶቼ ያዘጋጀሁዋቸውን ገፀበረከቶች ሰብስቤ በሌላ ፌስታል በሌላኛው እጄ አንጠልጥዬ ከመናኸሪያው ጊቢ ደረስኩ።

ሌሊቱን በስሱ ሲያለቅስ ያደረው ሰማይ የመናኸሪያውን ጊቢ አህያ የወለደችበት ጋጥ አስመስሎታል።ጭቃውን ሳይ የያዝኩትን ጋቢ ይበልጥ ጠበቅ አድርጌ ያዝኩት።

ወደየቦቅላ የሚሄደውን መኪና አጠያይቄ አገኘሁትና ከሚጋፋው ተሳፋሪ ጋር አብሬ ቆምኩ።መኪናው ሊሞላ የቀሩት ወንበሮች ጥቂት ነበሩና መጋፋት ነበረብኝ።የሚጋፉትን ተሳፋሪዎች ወዝ እየሳብኩ ስታገል በመሀል የሆነ የጥርኝ ጠረን የመሰለ ወዝ በአፍንጫዬ አልፎ ውስጤን ሲያጠምቀው ታወቀኝ።በግፊው መሀል ዞር ዞር እያልኩ የጠረኑን ምንጭ አሰስኩት።

ልቦለዶች ውስጥ ያሉትን በውብ ቃላት የተገለፁ ውብ እንስቶች የሚያስከነዳ ውበት አየሁ።ማማተብም አማረኝ.።የሀዲስን ሰብለ፣የበአሉን ፊያሜታ ፣ የሲሳይን ትዕግስት. ...የሌሎቹንም ደራስያን የምናብ ውቦች አምላክ ባንድ ላይ ጨምቆ ያወጣት የቁንጅና ጠብታ ትመስላለች።ከተመስጦ እይታዬ ስመለስ ረዳቱና ሲገፋፉ የቆዩት መንገደኞች የጦፈ ክርክር ውስጥ ገብተዋል።

ረዳቱ የሰውን ብዛት ሲያይ ጎምዥቶ ነው መሰለኝ ከመደበኛው ታሪፍ ላይ 20 ብር ጨምሮ በ 70 ብር እንደሚጭን በመናገሩ ነው ክርክሩ የተነሳው።

"በቃ 70 የሚከፍል ካለ ይግባ አለበለዚያ ከዚህ ገለል በሉ።"አለ ጋሽ ረዳት።

"ሰባይ??ደሞ ኪያው ለምንድነው ኧረ?እንደጤፉና እንደስንዴው ብር እምናበቅል መሰለህ አንተ?መቸም በግራቸው አይዘልቁትም ብለህማ አትክፋብን እንጅ አለሜነህ!"አሉ አንድ እናት በማስተዛዘን።

"ኧረ የምን መለማመጥ ነው መንገድ ትራንስፖርት ደውለን ማሳወቅ ነው እንጅ።እንዲያው ሰው በጊዜ ልግባ እያለ ያላችሁትን ቢከፍል በጠራራ ፀሀይ በግልፅ ዘረፋ?ቆቆይይይይይማ ኧረ!"አለና አንድ ወጣት በንዴት የታችኛውን ከንፈሩን እየነከሰ ስልኩን መነካካት ጀመረ።በዚህ ጊዜ ረዳቱ

"እሺ በቃ ስልሳ ስልሳ ግቡ"አለ ፈራ ተባ እያለ።

ሲንጫጫ ከነበረው ሰው የተወሰነው የባሰ ሲንጫጫ ፣የተቀረው በስልሳው ተስማምቶ እየተገፋፋ ሲገባ እኔም አብሬ ገባሁና ወንበር አማትሬ ከመስኮት አጠገብ የሆነ ወንበር አገኘሁና ቁጭ አልኩ።...

ይቀጥላል

በማዕዶት ያየሕ

25/06/2014 ዓ.ም.

@wegoch
@wegoch
@paappii
የመንገድ እንቅልፍ(ክፍል ሁለት)
====================
(በማዕዶት ያየሕ)


.....የተቀመጥኩት ከጋቢናው ጀርባ ያለው ወንበር ላይ ነው። አውቶቡሱ ከአፍ እስከገደፉ ጢን ብሎ እየሞላ ቢሆንም ረዳቱ ሰው ማስገባቱን የማቆም ሀሳብ ያለው አይመስልም።ስግብግብነቱ አበሸቀኝ።ግን ምንም አላልኩም።ቶሎ መድረስ እፈልጋለሁዋ!

ወዲያው ያ የናርዶስ ሽቶ የመሰለ መዐዛ በድጋሚ ሲያውደኝ ዙሪያዬን አማተርኩ።ያቺ እምቡጥ መሳይ ውብ እንስት ጋቢና ከሾፌሩ ጎን ተቀምጣ ሳያት የሆነ ጤነኛ ያልሆነ ንዴት ወረረኝ።

በደቂቃዎች ውስጥ መኪናው መንቀሳቀስ ጀመረ።እኔ ሙሉ ትኩረቴ ያለው እዚያችው እንስት ላይ ነው።ማታ ሰዓት አሳልፌ በመተኛቴ ከሙቀቱ ጋር ተዳምሮ እንቅልፍ ቢታገለኝም እንደምንም አይኖቼን ላለመክደን እየሞከርኩ ነው።አትኩሬ እመለከታታለሁ።ፀጉሯ ለሶስት ተገምዶ ጀርባዋ ላይ ወድቋል።ቅድም ለቅጽበት ያየሁትን ውበት አንዴ ዘወር ብላ ብታስጎበኘኝ እያልኩ በምኞት ስነሆልል ቆየሁ።

መኪናው ውስጥ ፀጥታ በመስፈኑ መርፌ ቢወድቅ እንኳን የሚሰማ ይመስላል።ከጋቢናው ወንበር አካባቢ ድምፅ ተሰማኝ።ሾፌሩ ነበር።ጅንጀና እየጀመረ መሆኑ ሲገባኝ የበለጠ ንዴት ተሰማኝ።

"እእእህህህህ..እንዴት ነው?"አለ።የድምፁ ቀፋፊነት የሚበየድ ብረትን ያስንቃል።ባላየውም መልኩን ስገምተው "monsters university"የሚለው የ cartoon ፊልም ላይ ያለውን ቀፋፊ እስስት እንደሚመስል ገመትኩ።

ይቀጥላል

በማዕዶት ያየሕ

26/06/2014 ዓ.ም.

@wegoch
@wegoch
@paappii
የመንገድ እንቅልፍ(የመጨረሻው ክፍል፣ክፍል 3)
======================

...እና የኔም ብሽቀት ጋብ የሚል እንኳን አልሆነም።ልጅቱ መልስ ሰጠችው...

"አለን ሰላም ነው?"ስትል ከድምፁዋ ሳቅ የተቀላቀለበት ቅላፄ ፈገግታዋን በምናቤ ሳልኩት...የሚጮህ አይነት ፈገግታ...አለ አይደል ክው የሚያደርግ ቢጤ?

ፈገግታዋ ለሾፌሩ የቀጥል ምልክት ስለሆነለት የበለጠ ዘና ብሎ ቀጠለ።

"ወዴት ነው ታዲያ?" ሲያወራ ግማሽ እይታው እሷ ጋ ግማሽ እይታው ደግሞ ሹፍርናው ላይ ነው።

"ወደ ቤተሰብ"

"የት ናቸው ቤተሰቦችሽ?" ምናይነት ከእንጨት የደረቀ አጠያየቅ ነው ይሄ? ልጅቱ ያለችው ከመርማሪ ፖሊስ ጋር አለመሆኑን ተጠራጠርኩ።

"መካለያ" ስትል መለሰች ልጅቱ። ለተወሰነ ቆይታ ፀጥታ ሰፈነ።በመሀላቸው ገብቼ ለዚያ እንደዘመኑ የዘፈን ግጥም ግራ ለገባው ሾፌር ሴት ልጅን መስመሩን በጠበቀ መልኩ የመግባባት ጥበብ ላይ ያለኝን ዕውቀት "አፓረንት" ወጥቼ ባሳየሁ ተመኘሁ።ይሄኔ በመቀጠል የሚጠይቃትን እያሰበ ይሆናል ፀጥ ያለው።ወዲያው ፀጥታውን ገርስሶ

"አለባበስሽን በጣም ወድጄዋለሁ...ሳላደንቅ አላልፍም"

"እህህህህ...አመሰግናለሁ"የሆነ የመለኮን አይነት ነው አሳሳቋ...ቀፈፈኝ።

አለባበሷን አላስተዋልኩትም ነበርና ይሉኝታዬን ሸጬ አንገቴን ወደ ጋቢናው አሰገግሁ።እራፊ ጨርቅ ለምልክት ያልተጣለበት ራቁት ገላ ሳይ አንዳች መንፈስ በሰውነቴ እየተዟዟረ ሲጨፍርብኝ ተሰማኝና አማተብኩ።ምን ጉድ ነው ይሄ?ለዚህ ነበር ልቤ የተሰቀዘው?

ለዚህስ ነበር ያማረ መልኳን አይቼ የቅናት ዛር አፍኖ ሲጫወትብኝ የቆየው?የተንበለጠጠ ፍም እሳት ላይ ውሀ ሲርከፈከፍ ሸሰሰሰሰሰስ ብሎ እንደሚቀዘቅዘው ነበር የኔም የዚያች ቅፅበት እይታ በውስጤ ነዶ የነበረውን የምኞት እሳት ያጠፋው።በቃ ሸከከኝ።

ሾፌሩ ግን የለበሰችው "አንኳኳ ይከፈትልሀል" የሚመስል አለባበስ ተስማምቶታል።ከአስፋልቱ ዳርና ዳር ወጣገባ የበዛበት አካባቢ ደርሰናል።የተሳፈርንበት መኪና አካሄዱ ጤነኛ አልነበረም።አንዴ ወደግራ አንዴ ወደቀኝ ዘመም እያለ...አልፎም ከልክ በላይ እየተንገጫገጨ ተሳፋሪው ሽብር ላይ ወደቀ።ከዚህም ከዚያም አቤቱታ ዘነበ።

"ኧረ ባክህ ቀስ ብለህ ንዳ እንዳትፈጀን"ይላሉ አንድ የጠነጠኑ ሽማግሌ።

"ኧረ ቀስ በል ሽታየነህ ተነ ልጀ ጉድ እንዳታረገኝ" ትላለች አንዲት በልተት ያለች እመጫት ታዝሎ የሚያለቅስ ልጇን ለማባበል እየሞከረች።ሁሉም በየፊናው ይመጣል ያላለው ሞት ያንን ቅንዝራም ሾፌር እንደፈረስ እየጋለበ ሲመጣበት ይቀባጥር ጀመር።አይ ዕድሜአችን!ለንስሀ የምትሆን አንዲት ሰዐት አጥተን ስንባክን ድንገት ሳናስበው መልዐከ ሞት ከተፍ ይላል።"ተመለስ አልተዘጋጀሁም" አይባል ነገር!

ሾፌሩ በቁጣ ወደተሳፋሪው ዘወር አለና

"አቦ በቃ ሰማሁዋችሁኮ!"አለ።

ያቺ የዝሙት መናፍስት መናኸሪያ የሆነች ሴት እየተቅለሰለሰች

"ኧረ ተረጋጋ! ንዴትኮ እድሜ ያሳጥራል ይባላል.....ሂ...ሂ...ሂ...ሂ....በቃ አትበሳጭ" ለካ ልብ ገዝቼ ስሰማው የሷ ድምፅ ከሾፌሩ የባሰ ይኮሰኩሳል።ፈገግታዋን በፈገግታ መለሰና ቀኝ እጁን ልኮ እርቃን ጭኗ ላይ ጣለው።ክውውውው አልኩ።ወዲያው መኪናው የሚሰቀጥጥ ድምፅ አሰምቶ ዙሪያ ገባው ግልብጥብጡ ወጣ።አንዴ አይደለም ሶስት አራት ጊዜ ሳይገለበጥ አልቀረም።ጩኸት በረከተ።የህፃናት ለቅሶ የእናቶች ዋይታ ተሰማ።

ኡኡኡኡኡኡኡኡኡኡኡኡኡኡኡኡ.....

እኔም ቀወጥኩት።

ቀዝቃዛ ውሀ ፊቴ ላይ ቸፍ ሲደረግብኝ ባንኜ ዙሪያዬን ቃኘሁ።ከፊት ለፊቴ አንድ አባት በፕላስቲክ ጠርሙስ ውሀ መሳይ ፈሳሽ(በሁዋላ ሲገባኝ ጠበል) ይዘው

"በስመአብ በል ልጄ...ዳቢሎስ ነው 'ሚጫወትብህ ይኸ ሰላቢ!ፃዕ እርኩስ መንፈስ!"አሉና በድጋሚ ሲያተናፍጉኝ ከቀልቤ ተዋሀድኩ።ሳስተውል መኪናው በሰላም እየተጓዘ ነው።ብርግግ ብዬ ከተቀመጥኩበት ተነሳሁና

"የታለች ያች ከይሲ?"ብዬ አምባረቅሁኝ።ሁሉም ሰው በቅዠት ያሰቃየኝ መንፈስ የሚያስለፈልፈኝ መስሎት ግራ በመጋባት አፍጥጦ ያየኛል።እኔ ግን ከምን ጊዜውም በላይ በትክክል እያሰብኩ ያለሁት አሁን ነው።

ያቺን ልጅ መኪናው ውስጥ በአይኔ አሰስኳት።ጋቢና ወንበር ላይ ከዛ ሾፌር ጎን ተቀምጣ ሳያት ፍፁም አስፋው በግጥሙ እንዳለው ፋክቱር ያለው እብድ ሆንኩኝ።አለባበሷም ያው ነው።የባሰ ሸከከኝ።

"ነይ ውጭ አንቺ የተረገምሽ!ውረጂ ከዚህ ብያለሁ አንቺ የሳጥናኤል ፈረስ!"ብዬ ላንቃት ወደሷው ተንደፋደፍኩ።ግርግር ተነሳ።መኪናው ቆመ።ሁሉም በአስር ጣቱ እብደቴ ላይ የፈረመ ይመስል እንዳልወላፈት እየተረባረበ ጠቅጥቆ ያዘኝ።

"ለምን አትሰሙኝም?ገደል ልትከተን ነውኮ!እኔ በሰላም አገሬ መግባት እፈልጋለሁ ።ሰዎቼ ይጠብቁኛል።"እያልኩ እለፈልፋለሁ።


"ዋእ!እና ምን አረገይ ልጅቱ?"ይሉኛል እየተፈራረቁ።

"እንዴት ነው ምናረገች ማለት?የሷን ጭን እያየ ገደል ይክተተን?"አልኩ ወደሾፌሩ እያፈጠጥኩ።የአብዛኛው ሰው ዐይን ወደ ልጅቷ ጭን ሲዞር ስቅቅ ብላ

"በቃ ተረጋጋ የኔ ወንድም ወንበር ልቀይርህ እችላለሁ"አለች እየተቅለሰለሰች።

"ሌላ ቦታ ተቀመጪ ስትፈልጊ እኔ ቦታዬን አለቅም"ብዬ ሳመናጭቃት ሾፌሩ በመሀል ገብቶ

"ማነህ ሰውየው!በስርዐት ስታናግርህ በስርዐት አናግራት!"አለኝ ያንን ዕውር ቂጣ የመሰለ ለምቦጩን አንከርፍፎ።

"አ?ምን ምን አልክ አንት የወንድ ሸሌ?አንተ እኔን ስለ ስነስርዓት ልታስተምረኝ ነው?ስድ ነህ እሺ!"አልኩና የጣፈጠ ቡጢ ለግራ ጉንጩ ጋበዝኩት።እሱም የዋዛ አልነበረምና የቀኝ ጆሮዬ ላይ ሊፈርምልኝ ሲል በገላጋይ ጥረት ተረፍኩ።ግርግሩ በመከራ ጋብ አለና የዚህ ሁሉ መነሻ የሆነችው ያቺ እንስትም ሌላ ቦታ እንድትሆን ተደርጎ ጉዞአችን ቀጠለ።


በማዕዶት ያየሕ

03/07/2014 ዓ.ም.

@wegoch
@wegoch
@paappii
እንደሚሞት እያወቅሁ አክመዋለሁ
(ርዕሱ ነው)

----------------------

ሲያየኝ የምገባበት ጥጋት ነው የማጣው።ደግሞ የአስተያየቱ ክፋቱ ዐይኑን አለማርገብገቡ።በቃ ትኩርርርር

አይቶኝ አይቶኝ ወደግድግዳው ዘወር ይልና ድምፅ ሳያሰማ እንባውን ያፈሳል።ሊዞር ሲል አውቅበታለሁ።የጎደጎዱ ዐይኖቹ በእንባ ሀይቅ ይሞላሉ።

መጀመሪያ የመጣ ቀን ማንኛውም ሐኪም ለታካሚው መጥፎ ዜና ሊነግር ሲል እንደሚከብደው ቃላቱ እየተናነቁኝም ቢሆን መርዶውን ሳረዳው ትዝ ይለኛል።ቢሮዬ ገብቶ ከተቀመጠ በሁዋላ

"እእእሺ ዳንኤል እንዴት ነህ?"አልኩ በውሸት ፈገግታ ተለውሼ።

"እግዚአብሔር ይመስገን"

"እእእእእእ...."ወረቀቶችን እያገላበጥኩ ሠዐት ስገድል ጭንቅ ብሎት

"ምነው ዶክተር ችግር አለ እንዴ? "አለኝ።አዎን በትክክልም ችግር ነበር።ለኔ ትልቁ ችግር በህክምና ህይወቴ ውስጥ ታካሚዬን ገዳይ በሽታ እንደያዘው ልነግረው ከፊትለፊቱ የተቀመጥኩበት የመጀመሪያው ቅፅበት መሆኑ ነበር።ለእሱ ደግሞ ትልቁ ችግር የፈራው ነገር እውነት መሆኑ ነበር።ሁለታችንም ከፍርሀታችን ጋር ተፋጠጥን።

"በመጀመሪያ ተረጋጋ ዳንኤል"ከማለቴ ከአፌ ነጥቆ

"እንደፈራሁት ነው አይደል?positive ነው አይደል የሚለው ውጤቴ?"አለና እጄ ላይ የነበሩትን ወረቀቶች መንትፎ ማገላበጥ ጀመረ።ምንም የማለት ወኔዬ መከነ።በተሰበረ ልብ የሚያደርገውን ሁሉ አስተውላለሁ።ተፈጥሮው ውብ ነው።ውብ የ 28 ዓመት ወጣት።

ከወረቀቶቹ መሀል አንደኛውን አነበበና ቀና ብሎ አየኝ።ድጋሚ ወረቀቱን አየ።ደግሞ እንደገና እኔን....

"እውነት አይደለም በይኝ ዶክተር"አለኝ ሳግ እየተናነቀው።ውሸት ነው ብለው ደስ ባለኝ።የሞት ሞቴን ተጣጥሬ ከአንደበቴ አምስት ፊደላትን አወጣሁ።

"አዝናለሁ"

"አአአአአይ....አይ....አይሆንም...ገናኮ አልደከመኝም...እንዴት እንደዚህ ጤነኛ ሆኜ ልሞት እችላለሁ?ዶክተር አንድ ነገር ማድረግ አለብሽ።ገናኮ በመጀመሪያው ደሞዜ ለእናቴ ያሰኛትን አልገዛሁላትም...ገናኮ ወደፊት ለምወልዳቸው ልጆቼ ያወጣሁትን ስም ማንም አልወሰደውም...ዶክተር የተመረቅሁ መስሎኝ ነበር....ለካ ተረግሜአለሁ..."በንግግሩ እዚህና እዚያ እየረገጠ ከልቤ አስለቀሰኝ።አቅፌ ከማባበልና የሸመደድኳትን ምክር ከማቀበል በቀር ምንም ላደርግለት አልቻልኩም።

ወድያው የ Anti retroviral (የ ኤች.አይ.ቪ ህሙማን ህክምና) ማዘዣ ፅፌ ሸኘሁት። ዶክተርነቴን ጠልቼው አላውቅም።በዚች ዕለት ግን ዶክተርነቴን ትልቁ ጠላቴ አደረኩት።የዳንኤልን ህክምና የምቆጣጠረው እኔ ሆንኩ።ሆስፒታል በመጣ ቁጥር ከቢሮዬ በር በላይ "የኤች.አይ.ቪ. ሕሙማን ክፍል"የሚለውን ያይና በልቡ ያነባል።በውስጡም ቢሆን ሲያለቅስ ይታወቀኛል።አንዳንድ ቀን ከተለመደው ምርመራ በሁዋላ

"እእእሺ ዳንኤል ዛሬ አሪፍ condition ላይ ነህ።ይህ ጥሩ ለውጥ ነው"ስለው

"ስንት ቀን ተጨመረልኝ ማለት ነው?"ይልና ወሽመጤን ይቆርጠዋል።

"Coooome on ዳንኤል! ስንት ነገር ተባብለን።look እስኪ ሁኔታህን።U r so good.ነግሬህ የለ እንዴ መድሀኒቱን በአግባቡ ከወሰድክና የምልህን ካደረግህ ነገሮች እንደማይከብዱህ"

"ዶክተር እስኪ የምትይኝን ሁሉ እንዳደርግ አንድ ነገር ብቻ ተባበሪኝ"

"እሺ ምን?"

ይቀጥላል

በማዕዶት ያየህ

06/07/2014 ዓ.ም.

@wegoch
@wegoch
@paappii
A little note from my selftalk...

@wegoch
@wegoch
@ribkiphoto
ሁሌም የሴቶች ዶርም ድረስ መጥቶ ሸኝቶኝ ሲመለስ ባለማመን ያዩታል።
<<ሔለን ግን ሙድ እየያዝሽብን ነዋ! ያን ሁሉ ወንድ ያባረርሽው ይሔ ፉንጋ ጋር ለመሆን
ነው?>> ትላለች አንደኛዋ።
<<እስኪ ተያት ምን ታውቂያለሽ? ራቁቱን ያዬችው እሷ!>> ብላ ሌላኛዋ ታሽካካለች።
እኔም አስከፋናት ብለው እንዳይደብራቸው እስቅላቸዋለሁ። ዋና ምክኒያቴን ከሚያውቁብኝ
የጠረጠሩት እውነት እንደሆነ እንዲሰማቸው ባደርግ ይሻለኛል።
ለሰው ባይመስልም ፉንጋው የፀሎቴ መልስ ብቻ ሳይሆን ጨለማ ክፍል ውስጥ ያገኘሁት
ሻማዬ ነው።
<<ሔሉዬ ሌላ ቅፅል ስም ጠፍቶ ነው 'ሻማዬ' የምትይኝ?>> ይለኛል።
<<ሻማዬ ካላልኩህ ችቦዬ ነው የምልህ...የቱ ይሻልሀል?>>
<<አይ ሻማው ይሁን በቃ!>> ይላል እየተቅለሰለሰ።
አንዲት ፀበል ለፀበል የምትመላለስ ታላቅ እህት አለችኝ። ሰዎች መንፈስ ይዟት ነው እያሉ
ያወራሉ። እኔ ግን ባሏን ፈትታ ከመጣች ቡኃላ የዘመድ አዝማዱን ወሬ አትችለው ብላ
እንዳበደች አውቃለሁ። ከዛ ጊዜ ጀምሮ ፀሎቴ አንድና አንድ ብቻ ነው። <<ጌታ ሆይ
የምወደውን ሳይሆን የሚወደኝን ስጠኝ!>>
ለዛ ነው ሻማዬ የፀሎቴ መልስ ነው የምለው። የመጀመሪያ ቀን ሰውነቱ በላብ ተጠምቆ፣
እጁ እየተንቀጠቀጠ፣ መተንፈስ አቅቶት እየቃተተ ሲጠይቀኝ እንደማገባው ወስኜ ነበር።
የግቢውን ወንዶች ሁሉ መልሼ እሱን የጠበስኩት እነሱ እንደሚሉት የተለዬ ነገር
አግኝቼበት አይደለም። ሪስክ መውሰድ ስለማልችል ነው።
የፈሪ ሰው ጥቅም?...ቀድሞ አያጠቃም!
ግቢ ውስጥ በኔ ምክኒያት ያልደረሰበት ግፍ የለም። ለሁሉም ታዋቂ ካፕሎች ቅፅል ስም
ሲሰጡ እኛን ማን ቢሉን ጥሩ ነው? "beauty and the beast" ሆሆ!
ተረባውን ችሎ አለፍ ሲል ደግሞ መምህራኖች ግሬድ ያበላሹበታል። ጉልበተኞች ዱላ
የቀላቀለበት ማስፈራሪያ ያዘንቡበታል። ዘበኞች እንኳን ባቅማቸው ያዋክቡታል። ሁሉም
እንደየስልጣኑ ይበድለዋል።
<<ሻማዬ ከዚህ በላይ እንድትጎዳ አልፈልግም>> ስለው
<<ቀላል ነው ብዬ አልዋሸሽም። ሽልማቴ አንቺ እንደሆንሽ ሳስበው ግን 'ኧረ ያንሰኛል
ጨምራችሁ ምቱኝ' ልላቸው ሁላ ያምረኛል!>>
እያሳዘነ ያስቀኛል።
ገፍተው ገፍተው ለራሱ ያለውን አመለካከት እንዳወረዱበት የገባኝ የአመቱ መጨረሻ ላይ
ነው። እሱ ተመራቂ ስለነበር ቀጣይ አመት እንደማንገናኝ ገብቶት እያለቀሰ መጣ።
<<አንተም ስራ ልታገኝ የምትችለው እዚሁ አዲሳባ ነው። እኔም እዚሁ ነው የምማረው! ምን
የተለዬ ነገር ተፈጠረና ነው የምታለቅሰው?>>
<<አንድ ነገር ብቻ ቃል ግቢልኝ!>> አለ አሁንም እያለቀሰ!
<<እሺ ምንድን ነው?>>
<<እስክትመረቂ ድረስ የፈለግሽው ወንድ ጋር ሁኚ! ከዛ ቡኃላ ግን ተመልሰሽ ወደኔ
ልትመጭ ቃል ግቢልኝ!>>
ምንም አላልኩትም። በቆመበት ጥዬው ሔድኩ። ምን ባደርገው ነው ሊተማመንብኝ
የሚችለው? እኔስ በዚህ ደረጃ ከሚወደኝ ወንድ ውጭ ሌላ ምን እፈልጋለሁ? ከሶስት ቀን
ቡኃላ የሻማዬን ልብ ያረጋል ብዬ ያሰብኩትን ትልቅ ውሳኔ ወሰንኩ።
ሲያዬው አዲስ እንደተወለደ ህፃን ስቅስቅ ብሎ ማልቀስ ጀመረ። ለነገሩ እኔም ከዛ ያነሰ
ግብረመልስ አልጠበኩም። ይሔንን ፊት ለዘላለም እንዳይጠፋ አድርጌ ጀርባዬ ላይ
ተነቅሼለት ለቅሶ ሊበዛብኝ ነው?
የሚያስቀው እንራራቃለን ብዬ ፊቱን ተነቅሼለት ሌክቸረር ሁኖ እዛው ግቢ ቀረ።
የሚያሳዝነው ደግሞ ተማሪዎች በገቡ በመጀመሪያው ሳምንት ሁሉም ስለታቱዬ አወቁ።
የፈሪ ትልቁ ችግር.....ምርኮኛ አያያዝ አይችልም!
<<ለማን ተናግረህ ነው?>> ብዬ ሳፈጥበት...አብሮት ሌክቸረር ለሆነ ሰቃይ ጓደኛው ብቻ
መናገሩን ነግሮ ይቅርታ ጠየቀኝ። እኔም ከተያዙ ቡኃላ መንፈራገጥ ጥቅም የለውም ብዬ
ተውኩት።
የግቢው አየር ባንድ ጊዜ ተገለበጠ። ሻማዬ የግቢው ቁጥር አንድ ተፈላጊ ወንድ ሆኖ ቁጭ
አለ። እኔ ደግሞ ስወጣ ስገባ የተረባ መለማመጃ ሆንኩ። አንዴ ወጣቶች ተወራርደው
አስገድደው ልብሴን ገልጠው፣ ታቱዬን ካዩብኝ ቡኃላ ከሀዘን የወጣሁበት ቀን ትዝ
አይለኝም።
ሻማዬ ሊጠብቀኝ ቀርቶ ቶሎ ቶሎ ሊያገኘኝ ራሱ ጥረት አያደርግም። እኔ ነኝ
የምደውልለት። እንዲያውም አልናገርም ብዬ እንጂ አልፎ አልፎ የግቢው ታዋቂ ሴቶች
ከቢሮው ሲወጡ አያለሁ። በአንድ ወቅት ሊነካኝ ከብዶት ሲንቀጠቀጥ የነበረ ሰው፤ ዛሬ
መዳፉ ላይ ሲያገኘኝ ጨብጦ ሊያፈርጠኝ ሲዳዳ ባዬው...ለመረዳት ከበደኝ።
የሆነ ቀን ጉዳዩን ጨራርሰን እንደተቀመጥን <<ሰሞኑን መድሀኒት ስትጠቀሚ አላይሽም!
ሌክቸረር ሆነ ብለሽ ልታረግዥብኝ ነውዴ?>> አለኝ። በዚች ንግግሩ ታሪኬን ቀዬረው።
ትምህርቴን አቋርጨ አዲስ ህይወት ጀመርኩ። ስሜንም ቀየርኩ። ታቱዬን ሙሉ ጥቁር
አድርጌ "ብላክ ሆል" ነው እያልኩ መንገር ጀመርኩ። ሰላም ያለው ህይወት ለመኖር የነበረኝ
አንድ አማራጭ ነበር። ሁሉንም ሰው ከህይወቴ አስወጥቼ ልጄን ማሳደግ። የዚያኔ እንደዛ
ባለኝ ሰዓት ፀባዩ ሲስተካከል እነግረዋለሁ እያልኩ ያረፈድኩባት ፅንስ ነበረችኝ።
አሁን አሁን ሳስበው ታሪኬ ረጅም ይመስላል እንጂ አጭር ነው። ይቺው ናት ውጣ ውረዴ!
ልጄን እስካሳድግ ድረስ ሁለት ጊዜ ብቻ ነው ከቤተሰቦቼ ጋር የተገናኘሁት። እነሱም
እምብዛም ሊያዩኝ አይፈልጉም። መላቀቅ ነው! ይቅሩብኝ ከነምላሳቸው! ምላስ ሽሽት ነው
ነው ኑሮዬ!
አልፎ አልፎ ስር እንዳይሰድ አድርጌ የወሲብ ግኑኝነት እጀምራለሁ። እነሱም ስለኔ ትንሽ
ማወቅ ሲጀምሩ ጥያቸው ዲዲዲዲዲዲ! በዚህ ርዕስ ላይ ከማወራ ይሻለኛል።
ልጄ በኔ መልክ ባባቷ ጭንቅላት በመውጣቷ ያገኛት ሁሉ ይወዳታል። እኔም በሷ
እየተፅናናሁ እኖራለሁ። በቃ።
ይሔን ሁሉ ቁጭ ብዬ የማስበው ዛሬ <<አባቴ ማነው?>> ብላ ጠይቃኝ ነው። ለመጀመሪያ
ጊዜ ሩጨ የማላመልጣት ሰው ገጠመችኝ። የመመለስ ግዴታ እንዳለብኝ አውቃለሁ። ግን
እንዴት ነው የአ'ምሮ በሽተኛ ሳላደርጋት ስለአባቷ ልነግራት የምችለው? ተረት ላድርገው
ይሆን? እምብዛም የማይንቁት...እምብዛም የማያደንቁት የ'ንደኔ አይነቷ ኖርማል ሰው
ህይወት እንዴት ነው የሚተረተው?
<<ተረት ተረት>>
<<የመሰረት>>
<<በድድሮሮሮሮ ጊዜ አንዲት ሔለን የምትባል ከብርጭቆዋ ጋር ጨለማ ክፍል ውስጥ
የምትኖር ልዕልት ነበረች>>
<<እእእሽ>>
<<ሁሌም ሌቦች ብርጭቆዬን ይሰርቁብኛል ብላ ስለምትሰጋ ጨለማው ያስፈራት ነበር።
ከዛ አንድ ቀን ምን ብታገኝ ጥሩ ነው?>>
<<ምን?>>
<<ሻማ! በጣም ደስ አላት። ሻማዋን አብርታ እያዬች ደስ አላት። ይቺ ሻማ እስካለች
አልሰጋም ስትል አሰበች። ሻማዋ ግን እጠፋለሁ ብላ ትሰጋ ነበር። ንፋስ በመጣ ቁጥር
ትንፋሿ ቁርጥ ቁርጥ ይላል። ልዕልቷም ሻማዋን ከንፋስ ለማስጣል ብላ አንድ የሞኝ ውሳኔ
ወሰነች!>>
<<ምን አደረገች?>>
<<በብርጭቆዋ ሸፈነቻት።>>
<<ከዛስ?>>
<<ከዛማ ሌባ ይገባል ብላ በር በሩን እያዬች ከኋላዋ ቃቃቃቃቃቃ የሚል ድምፅ ተሰማት።
ደንግጣ ስትዞር የምትሳሳላት ብርጭቋዋ ናት። ንፋስ መቋቋም አቅቷት ልትጠፋ የነበረችው
ሻማ በሙቀቷ ብርጭቆዋን ሰንጥቃባታለች። ልዕልቲቱ አዘነች። ውሀ አጣጯ ቢመጣም
ውሀ መጠጫ እንደሌላት እያሰበች አለቀሰች! አለቀሰች!..>> እያለ የሚቀጥል ተረት!

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Mickel Azmeraw
ያለፍከውን ያንን ፍርጃ ማን ያውቀዋል? ቢያውቀውስ ምን ሊጠቅም?
ከበስተኋላህ የጎመውን ዞረህ አትይ ያዝልሀል። ፊት ፊቱን ፊት ፊቱን ነው መጨበጥ ለመሻገር ለማሻገር ይሆንሀል።
ወጋገኑም ይቀርብሀል።

በል አሁን ሂድ ተንቀሳቀስ ቃሌ በድን ካልሰራሀው በጉልበትህ ካስጠኸው ነፍስ ከጥረትህ ተራ ወሬ ሆኖ እንዳይቀር.....ፊት ፊቱን ፊት ፊቱን ቀናው ላይ ነው ሰርክ ማተኮር።
.........................
ፎቶ: ደብረሊባኖስ / የፖርቱጋል ድልድይ/ 2014
© Ribka Sisay
@wegoch
@wegoch
@ribkiphoto
እንደሚሞት እያወቅሁ አክመዋለሁ(ክፍል ሁለት)
።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።


...."እሺ ምን?"

"ተነስ ሂድና ራስህን ግደል ብቻ በይኝ።ውለታሽን በሰማይ እመልሳለሁ።"

"ምን!?"

"ምነው?"

"ምን ማለት ነው ይሄ?የምለፋልህ ልገድልህ ነው እንዴ?"

"እንደምሞት እያወቅሽ ለምን ታክሚኛለሽ?ለምን ስቃዬን ዕድሜ ትሰጭዋለሽ?"ጥያቄዬን በከባድ ጥያቄ መለሰብኝ።

በተኛበት አትኩሬ አየሁትና እጆቹን ይዤ

"ዳንኤል ተስፋ አለህኮ!ትልቅ ተስፋ!ደሞዝህን ተቀብለህ ለእናትህ ያማራቸውን ልትገዛላቸው ትችላለህ....ለልጆችህ ያወጣኸውንም ስም ከልጆችህ ሌላ ማንም አይጠራበትም።እመነኝ ህይወትህ ያማረ ይሆናል።"የምናገረው ግን ከልቤ አልነበረም።እየተናገርኩ የማስበው አንድ ነገር ነው።እኔ በእርሱ ቦታ ሆኜ ሐኪሜ እነዚህን ቃላት ብትደረድርልኝ እየተጓዝኩበት ካለው የሞት መንገድ ወደሁዋላ የሚስብ የህይወት ብርሀን ይታየኛል ወይ የሚለውን...

"አንቺ የህልም ሰው ነሽ ዶክተር"አለኝ እጄን ከእጁ እያስለቀቀ።ራሴን ወቀስኩ...ምንድነው ያልኩት ቆይ?

"ዶክተር የሚለውን ማዕረግ ተወው...simply በስሜ ልትጠራኝ ትችላለህ ከፈለክ "

"ዶክተርነትሽን ሳይቀር እንድትጠይው አረኩሽ አይደል?"እንባው መንታ መንታ እየሆነ መጉረፍ ጀመረ።እጆቼን ሰድጄ እንባውን ላብስለት ስል ከመሀል ቀብ አርጎ ያዘኝና

"ተይ!እንዳታደርጊው!ቢያንስ እንዳለቅስ እንኳን ፍቀጂልኝ "

ዝምምምምምምምምም

በዝምታ ዐይኖቹን ከድኖ ሲተነፍስ ሳየው ፍርሀት ይወረኛል ።ዳግም ዐይኑን የማይገልጥ ይመስለኛል።

አንድ ቀን ከታካሚና አካሚነት ወጥተን ምሳ ልጋብዝህ ብዬ ቤቴ በስንት ልመናና ክርክር ተስማምቶልኝ ወሰድኩት።ከእናቴ ጋር አስተዋወቅሁትና በቅፅበት ተግባቡ።እኔን ረስተው የብዙ ዐመት በሚመስል ትውውቅ እየተሳሳቁ ሲጫወቱ ሳይ ምናለ ጌታ ሆይ ለዚህ ውብ ፍጡርህ የማይጠወልግ ተስፋን ብትቸረው ስል ለመንኩለት።

እናቴ የሰለጠነች ግን ደግሞ መሰረቷን የማትለቅ ዘመናዊ ሴት ናት።ሰዎችን የምትረዳበት(ጠብቆ ይነበብ) መንገድ ሁሌም እንዳስገረመኝ ነው።

"እእሺ ሴትዮ ቡናው አልፈላም?"ይለኛል ከፊትለፊቴ የተዘረጋውን ረከቦት እያየ።

"ተረጋጋ ምን ያጣድፍሀል?"

"ኦኦ!በሁዋላ ሰውየውንም ምን ያጣድፍሀል ልትይው ነው?"

"ሰውየው?የምን ሰውዬ?"

"ባልየውን ነዋ"

"አሄሄሄ...በደህና ጊዜ ቡና በዞረበት የማይዞረውን አጋጥሟት ነው እንጂማ ጊዜና ቡና ማፍላት የማይታረቁ ነገሮች ናቸው"ስትል እናቴ በአንዴ ፊቱ ልውጥውጥ ሲል ታወቀኝ።ለይስሙላ ፈገግ ብሎ

"ግዝሽ መታጠቢያ ቤቱ በየት በኩል ነው?"አለኝ ብድግ አለና...ገብቶኛል ሀሳቡ።ሊያለቅስ ፈልጎ ነው።አቅጣጫውን ጠቆምኩት።ከክፍሉ ከመውጣቱ እናቴ ላይ መጮህ አምሮኝ ነበር።እንዳይሰማኝ በለሆሳስ

"እምዬ ምን ነካሽ ምን ማድረግሽ ነው ቆይ?"

"ምን አረኩ ደግሞ?"አለችኝ ድሞፁዋን ቀንሳ

"እንዴት ባለትዳር እንደሆንኩ ትነግሪዋለሽ?"

"ምን?አያውቅም?ለምን አልነገርሽውም?"

"ምክንያት አለኝ"

"የምን ምክንያት ነው ሚጡ" እናቴ ሰው ፊት ካልሆንን ሚጡ ነው የምትለኝ።

"ለማስረዳት የሚከብድ ምክንያት....ዳ...ዳንኤል ፍቅር ይዞታል።"

"እና ቢይዘው?ጥሩ ነዋ!"

"አይ እማ!አልገባሽም ነገሩ...ከማን መሰለሽ የያዘው?ከ...ከኔ ነውኮ"ፈራ ተባ እያልኩ ዳንኤል እንዳይመጣ ዱካውን እየሰለልኩ ነበር የማወራው።እናቴ ፊቷ ተለዋወጠ።

"ሚጡ ግን ጤነኛ ነሽ?"

"ለመሆን እየሞከርኩ ነው"

"ባለትዳር ሆነሽ እንዴት ነው ከሌላ ከሚያፈቅርሽ ሰው ጋር ጤናማ ግንኙነት ውስጥ መቆየት የምትችይው?ለዚያውም ላንቺ ስሜት እንዳለው እያወቅሽ...እንዴት!?"

"እማ ተረጂኝ ይሄ የምሰጠው ህክምና አንዱ አካል ነው።"

"ቢገባሽ እየገደልሽው ነው።"

"አይደለም እማ።በሽታውን ሳይሆን እኔን እንዲያስብ...ለመኖር እንዲጓጓ እያረኩት ነው።"

"ምናይነት ውጥንቅጡ የወጣ ሂሳብ ነው ይሄ?የማይሆን ተስፋ በልቡ እየሞላሽ ሞቱን መራር ልታደርጊበት ነው?በሚያምር ጓደኝነት ቀኑን ማስዋብ እየተቻለ?"

"ብችል ደስ ባለኝ እምዬ" ስል ኮቴው ተሰማኝና ዝም አልኩ።ዐይኖቹ የቲማቲም ድልህ መስለዋል።ምን እያለ ይሆን ያለቀሰው??

ገና አልጨረስኩም ይቀጥላል።

በማዕዶት ያየህ

07/07/2014 ዓ.ም.

@wegoch
@wegoch
@paappii
እንደሚሞት እያወቅሁ አክመዋለሁ(ክፍል 3)
።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።


"ቡናችን ፈልቷል"አልኩ የውሸት ፈገግታ ተከናንቤ።

"ጥሩ!እስኪ ይቀመስ"አምዬ ነበረች።

ቡናውን ቀድቼ ስሰጠው ትኩር ብሎ አየኝ።ያ የምገባበት እንዲጠፋኝ የሚያደርገኝ አስተያየት።በቃ ትኩርርርር

እናቴ ነገረ ስራችንን ሁሉ እያጤነችው ነው ታውቆኛል።ቡናው አልቆ እየሸኘሁት መንገድ ላይ እንዲህ አለኝ...

"ለምን አልነገርሽኝም እንዳገባሽ?"

"ገናኮ ጋብቻው official አልሆነም።ሰርጉ ከወራት በሁዋላ ነው...plus ደግሞ መናገሩ አስፈላጊ ስላልመሰለኝ ነው።"

"እኔ ለምንድነው ምንም የማልደብቅሽ ታዲያ"

"ያው ሐኪምህ ስለሆንኩ ነዋ!"

"አዎ ግን የበሽታዬ ብቻ ሳትሆኝ የኑሮዬም የህይወቴም ሐኪም ስለሆንሽ ነው...እኔ ግን ላንቺ ተራ ታካሚ ነኝ መሰለኝ"

"እንደዛ ለማለት አይደለም እባክህ አታስጨንቀኝ ዳንኤል"

"በቃ ብዙ አትራቂ ዶክተር...ረከቦቱም እንደተዘረጋ ነው ።ነገ ሆስፒታል እንገናኝ"

"እሺ"

"እሺ"

በአየር ላይ እንኳን ስንብት ሳይሰጠኝ ሄደ።ወደቤት ተመለስኩ።

ዳንኤልን ማከም ከሐኪምነትም ያለፈ ሌላ ጥበብ ... ሌላ መላ...ሌላ ዘዴ ይጠይቃል።ለኔ ደግሞ ያንን ዘዴ መዘየድ ከባድ ነው።ለምናገረው ለእያንዳንዱ ተስፋ ያዘለ ንግግሬ ልቤን የሚሰብርበትና ዶክተርነቴን እንድረግመው የሚያደርግበት ከሞት የጨለመ የመልስ ምት አለው።በመሀል ደግሞ ዕውን ሊሆን የማይችል ስሜት ተሰማው...ፍቅር...ከኔ ከባለትዳሯ ሐኪሙ ፍቅር ያዘው።ነገረኝም...አሳየኝም።ቃል በቃል እንዲህ አለኝ።

"ለምን ትኖራለህ ቢሉኝ መልሴ ለእናቴ ስል አይደለም።ከዚህ በሁዋላ ምን እጠቅማታለሁ?የምኖረው ስለጊዜ ባለኝ ጠንካራ ፍቅር ነው የሚል ነው መልሴ።እሱ ስሜት ለመኖርና ነገን ለመናፈቅ ከበቂ በላይ አሳማኝ ምክንያት ነው ለኔ።ሁሌም ስተኛና ስነሳ የማፈቅራት ነፍስ እንዳለች አስባለሁ።እሷን ለማየት ስል ብቻ በሰላም አተኝተህ አንሳኝ ብዬ እፀልያለሁ።እሱ ይሰማኛል።ምክንያቱም የሱም የመኖሩም የመሞቱም ምክንያት ከራሱ በላይ እኛን ማፍቀሩ ነው።"
ይህንን ሲለኝ ወኔዬ ከዳኝ።

"ከወራት በሁዋላ ላገባ ዝግጅቴን ጨርሻለሁኮ ዳኒ"ልለው አሰብኩና ውስጤ ሲጠወልግ ሲሰማኝ አንደበቴን አስቆምኩት።በዚሁ ያኖረኛል በሚለው ስሜቱ እንኳን እስኪ ትንሽ በተስፋ ይኑር ብዬ ዝምታን መረጥኩ።ቢያንስ በነዚያ ቆርጠው በሚጥሉ ቃላቱ ልቤን አያቆስለውም ስል አሰብኩ።


በነጋታው በጣም በጠዋት ነበር ሆስፒታሉ ጊቢ የደረስኩት።ጠበቅሁት....የዘገየ መሰለኝና ሰዐቴን አየሁ።ጥቂት ደቂቃዎች ይቀራሉ።ግን ትዕግስት አጣሁ።ደቂቃዎቹ እንደምንም አለፉ....አልመጣም።ጭንቀት ወረረኝ።የእጅ ስልኬን አውጥቼ ልደውል ስሙን ስፈልግ ልቤ በሀይለኛው መምታት ጀመረ።ራሴን በስንት መከራ አረጋግቼ ደወልኩለት።ስልኩ አይነሳም...የት እንደምሄድ ጨነቀኝ።ከዚህ ቀደም ከሚመጣበት አንድ ሰዐት ዘገየ።በጥበቃዬ መሀል ሌላ ታካሚ መጣ።ቀኔን በሱ የመቅረት መርዶ መጀመር ግድ ሆነብኝ...

አላለቀም

በማዕዶት ያየህ

07/07/2014 ዓ.ም.

@wegoch
@wegoch
@wegoch
ከሰባት አመታት በፊት ነው፡፡ በወቅቱ የምሰራበት መስሪያቤት እኛ ክፍል አዲስ ጀማሪ
አካውንታንት ተቀጠረች፡፡
ስሟን ዘነጋሁት(ባስታውሰውም አልጠቅሰውም) ።
ውብ ነበረች!
ቅላቷ መቼስ ጸሐይን ያስንቃል። የአርመን ወይ የግሪክ ክልስ አይነት ውበት ታውቃላችሁ?
የሐበሻ ደምግባቱ ፤ ጥቁር ሐር ፀጉሩ ፤ ነጭ ጥርሱ አንዳለ ሆኖ ...የፈረንጅ ጉንጭና
አፍንጫ ተጨምሮበት በጆሮዎቿና በማጅራቷ በኩል ታክከው የሚወርዱት ጥቅልል
ፀጉሮቿ። ዓይኖቿ ነጭና ጥቁር ብቻ! እንደኛ ብዙ አይቶ ፣ አልቅሶ ደፍርሶ የማያውቅ ንፁህ
ዓይን።
የወርቅ ፍልቃቂ የመሰለች ። በዛ ላይ ንፁህ ነች። ነጫጭ ሸሚዞቿን በዘመን አመጣሽ
ጂንስ እና በክፍት ጫማ ታዘወትራለች። የእግሮቿ ጣቶች ከእኔ እጅ ጣቶች ይልቅ ያምራሉ።
ይለሰልሳሉ። በተረከዟ ውስጥ ደሟ ሲመላለስ ይታያል።
እኔማ "በዚህ እግር ነው ሃያ ሁለት አመት ሙሉ የተራመደችው ወይስ ቅያሪ አላት ?"
እላለሁ በሆዴ።
እሷ ቢሯችን ከገባች በኋላ የክፍላችን ጠረን ግን ተለወጠ። በጥሩ አይደለም! በመጥፎ!
ገማ! ቀረና! ሸተተ! ጨሰ !
"እፍፍፍፍ እፍፍፍፍፍ ምንድነው ክፍላችሁ" ይላሉ እንግዶች ።
መስኮቶች ይከፈታሉ፣ መጋረጃ ተገልጦ ይናፈሳል (እንዳሁን ማስክ የለ...በሻርፕ በሹራብ
ምናምን አፍንጫችንን እንይዛለን)
"አይጥ ሞታ ነው" ተባለ...ፋይል እየተነሳ ሼልፍ እየተንፏቀቀ ምንጣፍ እየተጎተተ ተፀዳ !
የመፀዳጃቤት ቱቦ ተጠረጠረ ... ማፅጃ ተገዛ፣ ተፈትቶ ተገጠመ ፣ ተፀዳዳ። ለውጥ የለም!
ጎረምሶቹ ሁሉ እንዲታጠቡ ማስጠንቀቂያ ተሰጠ ! ባለቱታ ባለ ቦቲ የቀን ሰራተኞች ሁሉ
ጉዳይ ቢኖራቸው እንኳ ወደ ቢሮ ዝር እንዳይሉ ተከለከሉ!
ምንም ለውጥ የለም ... ውሎ ሲያድር ምንጩ ተደረሰበት !
ምፅ ያቺ ቆንጆ
እንደሰራ አይገድል መቼስ .... ከሰውነቷ የሚመነጨው መጥፎ ጠረን ይገፈትራል። አይን
ሁሉ ይቆጠቁጣል። ጆሮ ጭውውውው ያደርጋል ። የስሜት ህዋስ ይጎዳል።
ቁንጅናዋንና ንፅህናዋን እያየን በዚህ ጠረን ማ ጠርጥሯት ?
አንድ ክፍል ለ7 ታጭቀን በዛ ላይ ግንቦት ነው አስቡት በቃ ... ጠዋት ተነስቼ ወደዛ ቢሮ
እንደምሄድ ሳስብ ያቅለሸልሸኝ ጀመር !
የስራ ከባቢው ተበላሸ!
አዲስ 'ቺክ' አገኘን ያሉ ወንድ ሰራተኞች በ"እናላምድሽ" ሰበብ ሻይ ቡና ሊጋብዙ ከሩቁ
ምራቃቸውን እየዋጡ ፣ ክንፋቸውን ዘርግተው ይመጡና አጠገቧ ሲደርሱ አፍንጫቸውን
ይዘው ያልፏታል
አለቃችን "ቼክ ለማስፈረምም ሆነ ለሌላ ጉዳይ እሷን ወደ ቢሮዬ አትላኩብኝ ፤ በመከራ
የዳንኩት ሳይነስ ተቀሰቀሰብኝ" አለ
መልኳን ረሳነው። እንደ ፀሐይ እያበራች አልትራ ቫዮሌት ጨረር ትለቅብን ያዘች። ስራዋ
ላይ ጥሩ ነበረች። ምን ዋጋ አለው የመስሪያ ቤቱ መነጋገሪያ መጠቋቆሚያ ሆነች። አብሯት
የሚሰራ የሚቀመጥ ጠፋ
በየኮሊደሩ ...
"አትታጠብም እንዴ ኤጭ?"
"ሴት ልጅ ደሞ እንደዚህ ስትገማ"
"እፍፍፍ" ይሏታል
ማን ቀርቦ ጠይቋት? በኋላ የክፍሉ ሰው ተመካክሮ "በቃ ይነገራት! የምታስተካክለው
ነገርም ካለ ታስተካክል" ተባለና
"በፆታም በእድሜም አንቺ ትቀርቢያሽ" ብለው መከረኛዋ እኔው ላይ ዕጣው ወደቀ
ምን ተብሎ ይነገራል በጌታ?
"ትሸቻለሽ?"
"ታጠቢ?"
"ችግርሽ ምንድነው ?"
አወይ መከራዬ ! ብቻ ቡና እንጠጣ ብዬ ይዣት ወጣሁ ... አጠገቧ የምሆንበትን ሰአትም
ለማሳጠር ....በምንም በምንም በምንም ብዬ ቶሎ አነሳሁባት ...
የኔ እናት ያ ፀሐይ መልኳ ከል ለበሰ፤ እንባዋ መቆሚያ አጣ
"አንቺም አልሽኝ?" አለች
"ሰው ሁሉ ነውኮ የሚያወራው ስላልነገርንሽ ነው እንጂ" አልኳት
"ሰው ንፅህና ይመስለዋል እኔ በየቀኑ ነው የምታጠበው፡፡ ያልሞከርኩት ህክምና የለም
የባህልም ፣ የዘመናዊም የቆዳ ነው ይሉኛል አለርት ሄድኩ መፍትሄ የለም። አንዱጋ አጥንት
ነው ይላሉ ...ሌላው የአንጀት ነው ይለኛልና .... የማህፀን ኢንፌክሽን እባላለሁ መድሐኒት
ተፈራረቀብኝ እንጂ መፍትሄ አልሰጡኝም፡፡ ምግብ ቀየርኩ ፣ ልብስ ጫማ ሳሙና
እየቀያየርኩ ሞከርኩ በመከራ ነው ተምሬ የጨረስኩት ። በየቀኑ እያለቀስኩ እንደዚህ ሰው
ሲነግረኝ እንጂ ለራሴ ደሞ አይታወቀኝም፡፡ ምን ልሁን? ምን ላድርግ? የት ልድረስ?"
እየዬ አለች በስማም እንደዚህ እያለቀሰች ደሞ ዓይኗ አይቀላም እንዴ?
ብቻ አባብዬ ፤ ጥቂት ዘለላ እንባ አብሬአት አንጠባጥቤ "እግዜር ያመጣውን ሰው አልችል
አይልም" ብዬ ፤ ሌላ ሕክምናም እንድትሞክር መክሬ ወደስራችን ተመለስን!
የክፍል ባልደረቦቼ የተልዕኮዬን ውጤት ለመስማት አሰፍስፈው ይጠብቁኛል።
"ነገርሻት?"
"እ?"
"ምን ሆኜ ነው አለች?"
ወዳ እንዳልሆነ ፤ የጤና ችግር መሆኑን ፤ ሳይፈርዱ እንዲራሩላት በየጠረጴዛቸው እየዞርኩ
በሹክሹክታ መከርኩ ። ዘከርኩ።
"ምፅ ምፅ ይቺን የመሰለች ልጅ" ተባለ ...
"እግዜር ይማራት" ተባለ ...
"እንትን ፀበል ፤ እንቶኔ ሐኪም" ተጠቆመ ...
ብቻ ያቺ ልጅ በእኛ መስሪያ ቤት ከ45 ቀናት የሙከራ ጊዜ በላይ አልቆየችም፡፡ ከዛ በኋላም
አግኝቻት አላውቅም ። መሰል ጠረንም ሸቶኝ አያውቅም።
ትናንትኮ ነው በመንገድ ሳልፍ ያ ሽታ ውልብ አላለብኝም?
ሰባት አመት ወደኋላ አንደረደረኝ ፤ መልኳ ድቅን አለብኝ ... በዓይኔ ፈለኳት በስነስርዓቱ
ቆሜ እያንዳንዱን ሰው በአይኔ መረመርኩ
የለችም ። እሷ አይደለችም ።

@wegoch
@wegoch
@paapppii

#Tayim_tsigereda_gonfa
እንደሚሞት እያወቅሁ አክመዋለሁ(ክፍል 4)
።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።።

ተስፋ አንዳንዴ መጥፎ ነው።ቀስ በቀስ ነው ውስጣችንን እየሸረሸረ ባዶ የሚያደርገው።ያ የመሸርሸር ሂደት ደግሞ ከምንም በላይ ይከብዳል።ልብ አንዴ ቆርጦ እርሙን እንዳያወጣ ወደ ሁዋላ እየጎተተ ነገ ብሩህ ይሆን ይሆናል እያለ የማይሆን መዋለል ውስጥ ይከታል።ነገ የተባለው ቀን ዛሬ ሆኖ ያ ብሩህ ነገር ባይመጣ እንኳን ሌላ ነገን ከማለም ወደሁዋላ እንዳንል ያደርገናል...እና ተስፋ አንዳንዴ ሕመም ነው።

እኔንም ከታካሚዎቼ በላይ በሽተኛ ያደረገኝ ያለፉትን 25 ቀናት በውስጤ ሲያቆጠቁጥ እየታወቀኝ ዝም ብዬ ያየሁት የዳንኤል የይመጣል ተስፋ ነበር።25 ቀናትን...600 ሰዓታትን...36,000 ደቂቃዎችን 2,160,000 ሴኮንዶችን ችዬ እንድጠብቅ ያደረገኝ ይሄው ተስፋ የማይቆርጠው ተስፋዬ ነበር።

በነዚህ 25 ቀናት ውስጥ በየቀኑ በትንሹ 30 ጊዜ ሳልደውልለት አልቀርም. ...ያለምንም ማጋነን የላክሁዋቸው የጽሁፍ መልዕክቶች ብቻቸውን የስልኩን memory card ሙሉ በሙሉ ሊቆጣጠሩት ይችላሉ።በጣም ብብብብብዙ ጊዜ "ቤቴን እይልኝ እስኪ...እናቴንም ላስተዋውቅሽ" ሲለኝ በስራ መደራረብ ምክንያት የቀረሁባቸውን ቀናት ረግሜአቸዋለሁ።

የት ብዬ ልፈልገው??በሱ መጥፋት ምክንያትኮ ያልተመኘሁት የጅል ምኞት የለም። የሆነ ወረርሽኝ በከተማው ገብቶ ለክትባት የሆነ ሰፈር ተመድቤ ሄጄ ምናል ከተከታቢው መሀል ባገኘው ብዬም ተመኝቻለሁ።ጭንቀቴ የሱ አለመምጣት ብቻ ቢሆን እንደምንም ራሴን ማደንደኑ ባላቃተኝ! ሰርጌ የቀረው 3 ሳምንት ብቻ ነው...21 ቀናት።ለዚህ ምክንያቷ ደግሞ እናቴ ናት።በዳንኤል መጥፋት ምክንያት እንደሆነ ባታውቅም የሰሞኑን መረበሼን አይታ ከ 2 ወር በሁዋላ የታቀደውን ሰርግ ከ 3 ሳምንታት በሁዋላ እንዲሆን ያስደረገችው እሷ ናት።የኔ ምስኪን እናት!በሰርጌ ወይን ጭንቀቴን ለቅልቃ ልትደፋልኝ አስባለች።ለኔ ግን የሰርጉ መቃረብ የባሰ ራስ ምታት ሆኖብኛል።ተቃውሜም ቀኑን ለማስረዘም የሚሰማኝ አጣሁ።ደከመኝ።

ዳንኤልን ካየሁት ዛሬ 28ኛ ቀኔ ነው።28 ቀንኮ ግን ብዙ ነው።በ28 ቀን ጊዜ ውስጥ አንዲት ሴት 2 ጊዜ ደመ-ፅጌ ልታይ ትችላለች።በ28 ቀናት ውስጥ አንድ ፅንስ ቅርፁን ይዞ በጥቂቱም ቢሆን ሰው ሊመስልም ይችላል።በ 28 ቀን ውስጥ አንድ ደሞዝተኛ 2 ኛ ደሞዙን ሊቀበል የሚችልበት ዕድልም አለ።በ 28 ቀናት ውስጥ ክርስቶስ ወርዶ "አንቺ ተስፈኛ ሐኪም ጊዜ ሆይ!ስለምን በጥበቃ ብዛት ትደክሚያለሽ?በዕውነቱ ዳንኤል አሁን ያለው ከሰማይ አባቱ ጎን አይደለምን?"ሊለኝም ይችላል።በ 28 ቀናት ውስጥ ሩሲያ ዩክሬንን ከምድረ ገፅ አጥፍታ ለታሪክ የማይመች ግፏን ልታስነግርም ትችላለች።በ 28 ቀን ውስጥ የህዳሴው ግድብ ለ 3ኛ ጊዜ ሊሞላም ይችላል።

እናም የቢሮዬ ጠረጴዛ ላይ አፍጥጬ በ28 ቀናት ውስጥ ምን ምን ነገሮችን ማሳካት እንደሚቻል ሳስብ ከበሩ አካባቢ የሆነ ሰው ጥላ ሲያርፍብኝ ታወቀኝና ቀና አልኩ።ለካ በ 28 ቀን ጊዜ ውስጥ እኔን በጥበቃ ያዛለኝ ዳንኤልም ሊመጣ ይችላል።ብዙ ቃላት ጉሮሮዬ ላይ ሲጣሉ ይታወቀኛል...'ዞር በል ከዚህ አንተ ደካማ ነህ...በፍፁም አንተ አሁን የሚሰማትን ስሜት ልትገልፀው አትችልም' የሚባባሉ ይመስለኛል ቃላቱ።በመሀል ድሉ ለዝምታ ሆነና ደንዝዤ ዝም አልኩ።ከፊት ለፊቴ እንደቆመ አምኜ ለመቀበል ሌላ 28 ቀናት የሚያስፈልጉኝ ይመስል ድምፁን እስከምሰማው ምንም አልተነፈስኩም።

"ዶክተር ጊዜ እንደምን ከርመሻል?"

አጠያየቁ ከከረምኩበት ሁኔታ አንፃር ቀለለብኝ።እንደ አምሳለ 'ከረምኩ በመከራ...እንባዬን ሳዘራ' ልበለው?

"እእእእእእ....አርክቴክት ዳንኤል" አልኩኝ በግርምት ተሞልቼ ከተቀመጥኩበት እየተነሳሁ።ቀረብ ብሎ ከፊቴ ቆመና በዚያ በሚያስደነብረው አስተያየቱ ትኩርርርር ብሎ አየኝ።

"እባክህ እንደዚህ አትየኝ ክቡር አርክቴክት"

"ትፈሪያለሽ እንዴ ክብርት ዶክተር?"

"ምን ሆነህ ነው 28 ቀን ሙሉ?"

"ኧ?ቀኑን ቆጠረሽው ነው?እኔኮ አላምንሽም!" ከልቡ ፈገግ አለ።

"Am not joking Dani...ምን አድርጌህ ነው ቆይ?"

"ህልሜን በከፊልም ቢሆን እያሳካሁ ነበር።ግን 28 ቀን በቂ አልሆነልኝም።የመጣሁት ተጨማሪ ዕድሜ ፈልጌ ነው።መድሀኒቴን ጨርሻለሁ"

"አልገባኝም"

"አስረዳሻለሁ።እንግዳ አረፍ በል እንኳን የማይባልበት ምናይነት ቢሮ ነው ይሄ?"አለና እየሳቀ ተቀመጠ።እኔም ለማብራሪያው ቸኩዬ ተቀመጥኩ።


ገና አልጨረስኩም ተረጋጉ!

በማዕዶት ያየህ

08/07/2014 ዓ.ም.

@wegoch
@wegoch
@tizur_12
እንደሚሞት እያወቅሁ አክመዋለሁ(ክፍል 5)
።።።።።።።።።።።።።።።።።

...."በዚህ 28 ቀን ውስጥ ምን ምን ሰራሁ መሰለሽ?ካንቺ ጋር በተለያየን በነጋታው ስልኬን ሸጬ ቢዝነስ ካርድ አሳተምኩ...ለደላሎች በየቦታው promotion እንዲሰሩልኝ ነገርኩ...ድሮ ፋዘር ከመሞቱ በፊት አላምጦ የጣላት ስልክ ነበረች ድምፁአ ብቻ የሚሰራ...እሷን ይዤ ሽር ጉድ ስል በ 5 ቀን ውስጥ 2 የስራ ውል ያዝኩ..."

"ኧረ ባክህ!"

"እኔ ልሙት!በማዕረግ graduate ማድረግ እንደዚህ ይጠቅመኛል ብዬ አስቤ አላቅም።ደሞ ሰው ምን ነክቶት ነው ዋጋ እንኳን ቀንሱልኝ ብሎ አይከራከርም እንዴ?መጀመሪያ የተዋዋልኩትን ባለሀብት ለባለ 2 ፎቅ የህንፃ ዲዛይኒንግ ስንት እንዳስከፈልኩት ገምቺ እስኪ..."

"እእእእእ...ኔንጃ...አላውቅም..80 ሺህ አካባቢ?"

"መች ትቀልጃለሽ?80?ብታምኚም ባታሜኚም 160 ሺህ ብር!"

"ምን?"

"ጊዜ ትሙት!"አለና እጄን መታው።

"ኧረ እዛው ራስህ ሙት! "

"እኔማ እሞታለሁ"ሲለኝ ንግግሬ መስመሩን እንደሳተ ታወቀኝ።ምን ማለት እንዳለብኝ ጠፋኝ።ያን ምትሀታዊ አስተያየቱን ተኮሰብኝ።ለአፍታ ዐይኑን ሳያርገበግብ ትኩርርርርር! የአይን መርገብገብ(blinking of eyes) ከቁጥጥራች ውጪ የሆነ ድርጊት(reflex action) እንደሆነ ነበር የተማርኩት...ሳይንሱ እዚህ ሰው ላይ አይሰራም ልበል?ዐይኖቹን እየተቆጣጠረ ነው የሚያርገበግባቸው።

"እሞታለሁ ስትልኮ አዝናለሁ ዳንኤል"

"እና ዳንኤል ደስ የሚለው ነው የሚመስልሽ?"

"ለምንድነው በንግግርህ የምትጎዳኝ"

"ልጎዳሽ ሳይሆን ልጠቅምሽ ነበር ሀሳቤ"

"እንዴት ነው በዚህ ልብ በሚያቆስል ንግግርህ ልትጠቅመኝ የምትችለው?"

"ልብሽ ቆስሎ ካልዳነ ደህና አትሆኝም።ምክንያቱም አለማቁሰል የሚቻልበት ምንም መንገድ የለም ምንም!...ይልቅ የጀመርኩትን ልጨርስ አታቋርጪኝ...ሰውየው ምንም ሳይከራከር 160 ሺህ ከፈለ ።በሁዋላ ስራው ያደከመኝን ድካም ሳየው ግን 200 ራሱ ሲያንሰኝ ነው...የ8 ቀን ጥሩ እንቅልፌን ነው በ160 የሸጥኩለት"

"ጉደኞች ናችሁ 160 ሺህ ማለትኮ የኔ የዐመታት ደሞዝ ነው።"

"ይሄ ይገርምሻል እንዴ?አራዳ ሁለቴ አይሸወድም ብዬ ሁለተኛውን ባለሀብት 190 ነው ያስከፈልኩት"

"በ28 ቀን ውስጥ 350 ሺህ ብር?በል ግማሹ የኔ ነው እንዳትቀብጥ"

"ግማሹ ቀርቶ የሩብ ሩብ ሩብ ራሱ የለም አሁን"

"እንዴ ያንን ሁሉ ብር ምናረከው? "

"ህልሜን ኖርኩበት"

"ማብራሪያ እባክህ..."

"የናቴን ቤት በደምብ አደስኩት...ከውስጥ እስከውጭ አደስኩት...ነጉራንጉሩን ሁሉ አፀዳሁት"

"ጎበዝ!ጀግና ነህ'ኮ ከልብህ!...ማርያም እናቴን ኮራሁብህ!"በሰማሁት ነገር እጅግ ከመደሰቴ የተነሳ ዘልዬ ላቅፈው ለጥቂት ነው የተመለስኩት።

"ኧረ እዛው በባልሽ ኩሪ ሆሆሆ...ሰርጉ ግን መቼ ነው?"

"ከ21 ቀን በሁዋላ"

"ማለት በ 27?አንቺ ፃድቅ ነሽ በቃ ዶክተር...ሰርግሽም በዕለተ ቀኑ ነው ደሲላል"ሲለኝ ርዕሱን ለማስቀየር

"እኔምልህ ክቡር አርክቴክት...ከ 350ው ሺህ ላይ ለኔ ስጦታ ለመግዛት የሚሆን አጠረህ?በጣም ትገርማለህ"

"ምን ያጣድፍሻል?ስጦታን ለመስጠት ትክክለኛውን ጊዜ የማውቅ ሰው ነኝ"

"እሱን አልጠራጠርም...እናስ እናትህ መቼስ በደስታ ሊያብዱ ደርሰዋል አይደል?"

"ሆሆሆይ!ኧረ እኔስ ያልቻልኩት የመንደሩን ምላስ ነው...ምንድነው አንቺ እንደዚህ መመቀን?አንድ እግዜርም ሰይጣንም አንቅረው የተፏት አሮጊት በቃ በጥብጣ ልትገለኝ!!ለካ ሞት ሲዘገይ የሰውን ፀባይ ያከፋል!ሃ....ሃ.....ሃ....."

"ሃ.....ሀ......ሃሃሃሃሃ ምን ብለው ነው የበጠበጡህ ቆይ?"

"ሂጅ አንቺ ደግሞ የሆነ በየሰው ልብ ልጎዝጎዝ 'ምትይው ጉድ አለሽ...የሆነ ወጣችሁን ልቅመስላችሁ የምትያት ነገር አለችሽ...አሁን የት አውቀሻት ነው አንቱ እምትያት?"

"እእእህህህ!አንተ ደግሞ ታበዛዋለህ!ያው አሮጊት ናቸው ስላልክ ነዋ!"

"አልወጣኝም!"

"እየሰማሁህ?"

"አሮጊት ናቸው አይደለም ያልኩት እኔ?"

"ታዲያ?"

"አሮጊት ናት ነው ያልኩት"

"ሂድ!ደነዝ ተች!"

"አሀሀሀሀ...ሀሀሀሀ"ከልቡ ሲስቅ ሳየው ለመጀመሪያ ጊዜ ነው ልበል!!ምነበር ይሄንን ከሚሊየን ዓመታት አንዴ በጠራራ ጨረቃ የሚመጣ ሳቅ ቀድቼ ባስቀምጠውና በከፋኝ ቁጥር እየሰማሁት ፈገግ ብል።ፈገግታው የመላዕክት ፈገግታ ይመስለኛል።'የመላዕክ ፈገግታ እንዴት ነው?' ቢሉኝ 'እንደዳንኤል ነዋ!'ብዬ በኩራት እንደምመልስ አስባለሁ።ልዩ ሰው ለመሆኑ ማስረጃ አቅርቢ ቢሉኝ ጠያቂው ራሱ እስኪታክተው ማስረጃ አዘንብለታለሁ።አሁን ዶክተርነቴን አንዳንንዴ እወደዋለሁ።ዳንኤልን ስላመጣልኝ...ደግሞም እጠላዋለሁ...የማክመው እንደሚሞት እያወቅሁ ስለሆነ።

ከስራ መልስ እናቴን ማስቸገር እንዳለብኝ እያሰብኩ ወደቤት ገባሁ።መጨነቄ ገብቷታል።

"ምን ሆነሻል?"

"ደህና አይደለሁም"

"እሱማ አይደለሽም ግልፅ ነው።እኔ ምን ሆንሽ ነው ጥያቄዬ"

"21 ቀን በጣም ትንሽ ነው እምዬ"

"ማለት?"

"ለሰርጌ ዝግጅት 21 ቀን አይበቃኝም"

"ይሄንን ጉዳይ አልተነጋገርንም ሚጡ?ባለቤትሽ ከጎንሽ መሆኑ ለዐዕምሮሽ ትንሽ እረፍት ይሆንልሻል...ሀሳብሽን ትተነፍሽለታለሽ"

"እኔ መች መተንፈሻው ቸገረኝ እምዬ?"

"እና ምንድነው የቸገረሽ?"

"ትንፋሹ"

"ኧ?"

"እምዬ ስሞት አፈር ስሆን..."

"ምንድነው?"

"3 ወር ብ......ቻ!"

"3 ወር??እንዴ ስዩምስ ምን ይላል ቆይ?"

(ስዩም ማለት ላገባው የተዘጋጀሁት(ተዘጋጅቻለሁ ለማለት ቢከብድም)እጮኛዬ ነው።እስራኤል ነው የሚኖረው።)

"እሱ ምንም አይልም"

"ግፍ አትዋይበታ ሚጥሻዬ!አያሳዝንሽም በሰው አገር አንቺ ና እስክትይው ነው'ኮ እሚጠብቀው. ...ባለፈው 2 ወር ብለሽ 2 ወር ጠበቀሽ...አሁን ደግሞ 3 ወር?ሚጥሻዬ ሌላ ሰው በሀሳብሽ ገባ እንዴ?"

"እኔ በሰው ሀሳብ ገባሁ እንጂ እምዬ"

"ማነው እሱ?"

"ታካሚዬ ነው"

"በቀደም ቡና የጋበውሽው ባልሆነ!ህክምናዬ እንደዚህ ነው ያልሽው?"

"አዎ"

"ሚጥሻዬ ምን ሆንሽብኝ?የሚጣፍጥ መርዝ ነውኮ የምትሆኝበት ለልጁ"

"የሚጣፍጥ መርዝ?"

"አዎ የሚጣፍጥ መርዝ"

"መች ቀመሰኝ እምዬ"

"ቁርጥ ያርግሽ አሁንም አንች ባለጌ...ሄሄሄሄሄሄ...."

"እምዬ ሙች...እሱኮ መቅመስ አይፈልግም...ማየት ነው ሚፈልገው"

"ሂጅ አንች!ምን ትላለች ይቺ!ሆሆሆሆሆ.....ሂሂሂሂሂሂሂሂ"እናቴ እስክታለቅስ ሳቀች።እኔም እምባዬን ሳቅሁት....ሳቄን አለቀስኩት።በህመሜ ውስጥም ቢሆን...በተመተረው ልቤም ቢሆን. ...ባልከዳኝ ጥርሴ ሳቅሁኝ።


አላለቀም አይዞአችሁ!

በማዕዶት ያየህ

10/07/2014 ዓ.ም.

@wegoch
@wegoch
@tizur_12
ከሞት የተረፈችበት እለት
_
ሥራ የጀመርኩት ቢሾፍቱ ንግድ ባንክ ነበር። ከእዚያም ቀበሌ 09፣ ገበያ ሰፈር ቤት
ተከራየሁ። ያከራየኝ ልጅ ሸገር የሚኖሩ የአክስቱን ቤት ነው የሚያስተዳድረው። በእድሜ
ብዙም ስለማንራራቅ ከአከራይና ተከራይ ይልቅ ጓደኛሞች ሆንን።
እሁድ እስከ 6 ሰዐት የመተኛት ልምድ አለኝ። ከባድ ስንፍና። ሰው በየመቅደሱ፣
በየአጥቢያው፣ አምላኩን ሲመሰግን ጥሌ የቤተክርስቲያን ድምጽ ማጉያ ሳይበግራት
ለሽሽ። ሰማይ ቤት ስሄድ ምደባዬን ያወቅኹ ይመስል።
ያን እሑድ ጠዋት በሬ 3 ሰዐት ላይ ተንኳኳ። እየተነጫነጭኩ እና እየተጨናበስኩ በሩን
ስከፍት በር ላይ የቆመው አከራዬ ማለቴ ጓደኛዬ ሸሜሳው ነው። (በነገራችን ላይ ለብዙ
ጊዜ ስሙ <ሸሜሳው> ይመስለኝ ነበር። አንድ ቀን ባንክ ገንዘብ ሊቀበል ሲመጣ ነው ስሙ
ሸምሱ ሊበን መሆኑን ያወቅኹት።)
<<ምንድነው በጠዋቱ ሸሜ?!>>
<<ቁርቁራ ማዘር ጋ ልሄድ ነው። እንዳይቀር ብላኸለች። በየአመቱ የምትደግሰው ድግስ
አለ>>
<<የምን ድግስ?>>
<<ሲስተር ከሞት ያተረፈችበት ቀን ነው። በየአመቱ ይደገሳል>>
እየተነጫነጭኩ ልብሴን ለብሼ በታክሲ እና በጋሪ የሸሜሳ እናት ቤት ደረስን። ድንኳን
ተጥሎበከባዱ ተደግሷል። ዘመድ አዝማድ ከሸገር እስከ ገጠር ተጠርቶ መጥቷል።
ይበላል። በልቶ የጠገበው ደግሞ ይጨፍራል።
እየተበላ፣ እየተጠጣ፣ እየተጨፈረ አመሸን። የሚገርም ጠላ ተጠምቋል። እኛም እሱን
እየዘመዘምን የባጥ የቆጡን ስናወራ አመሸን። ማታ ላይ በተደጋጋሚ እጠይቀዋለሁ ብዬ
ሳስብ የነበረውን ጥያቄ አነሳኹለት።
<<ሸሜ ሲስተር ምን ሆና ነው ከሞት የተረፈችው?!>>
<<ሲስተር ሸገር ነበር የምትማረው። የዛሬ 3 አመት በእዚህ ቀን በመኪና አደጋ አርፋለች፣
ምኒልክ ሆስፓታል መጥታችኹ ሬሳ ውሰዱ ተብሎ በቤት ስልክ ተደወለ። ሰፈሩ በለቅሶ
ተሞላ፤ ማዘር ጨርቋን ጣለች፣ በወቅቱ ሞባይል ስልክ ብዙ ሰው እጅ የለም። በቤት ስልክ
አዲስ አበባ የምትኖረው የአክስቴ ቤት ተደወለ። እዛም ለቅሶ ሆነ። ከጎረቤት ትልልቅ ሰዎች
ተመርጠው ሬሳ እንዲያመጡ ወደ አዲስ አበባ ተላኩ። እድር ታዝዞ ድንኳን ተተከለ፣
አግዳሚ ወንበሮች ተደረደሩ። ከገጠር ከከተማ ዘመድ አዝማድ እድርተኛ እየመጣ ለቅሶ
መድረስ እና መላቀስ ተጀመረ።
ቀኑ በሙሉ ሲለቀስ፣ ሴቶቹ ንፍሮ ሲቀቅሉ፣ ለእሬሳ መሸኛ ከብት ታርዶ ሲዘጋጅ መሸ። 12
ሰዐት ገደማ ሸገር የተላኩት ሰዎች የቤት ስልክ ላይ ደወሉ። <<ሬሳዋ ምኒልክ ሆስፒታል
የለም!>> አሉ። ሌላ ለቅሶ። እጅግ የመረረ ለቅሶ ተከተለ። እናቴ ለያዥ ለገናዥ አስቸገረች።
የሚይዛት ታጣ።
በእዚህ ጊዜ አንድ ተለቅ ያሉ የጎረቤት ሰው <<ለመሆኑ ልጅቷ ዘንድ ደውላችኹ
አጣርታችዃል?>> ሲሉ ጠየቁ።
<<ኮሌጅ ተማሪ ናት። እራሷ ስትደውል ነው የምናገኛት፣ ተከራይታ ነው የምትኖረው>>
ስንል መለስን።
<<ግድ የላችኹም። ይሄ ነገር ተንኮል ይሆናል። እስኪ እናቲቱን ተረጋጊ በሏት።>> አሉ።
ነገሩ በጣም አጓጓኝ። <<ከእዛስ?>>
<<ማታ ላይ ምኒልክ የሄዱ ሰዎች ባዶ እጃቸውን ተመለሱ። የነበረውን ለቅሶ ልነግርህ
አልችልም። ሽማግሌዎች እስኪነጋ ጠብቁ ብለው ተቆጡ። እኛም አልሞተች ይሆናል ብለን
ተስፋ ሰነቅን። በጠዋት ተነስተን አዲስአበባ ወደምትማርበት ኮሌጅ ሄድን። የተከራየችበትን
ቤት የሚያውቅ ስላልነበረ ነው ወደ ኮሌጁ የሄድነው።>>
<<ከእዛስ?>>
<<አራት ሰዐት ላይ ክላስ ልትገባ ሾር ብትን እያለች ስትመጣ ከወንድሜ ጋር ሮጠን
ተጠመጠምንባት። አቅፈናት ተላቀስን።
<<እማዬ ናት የሞተችው?!>> ብላ አብራን ማልቀስ ጀመረች።
<<አንቺ ነሽ የሞትሽው።>> አልናት።
<<እየቀለዳችኹብኝ ነው?!>>
ከእዚያ ከክላስ አስቀርተን እያዋከብን፣ የሆነውን እየነገርናት ወደ ቢሾፍቱ ይዘናት ተመለስን።
ነገሩ ሁሉ በህልሜ ውስጥ ያለኹ መስሎኝ ነበር። እርሷን ይዘን ሰፈር ስንደርስ እናቴ
በድንጋጤ ራሷን ሳተች። ሰው እንደ አዲስ ተላቀሰ። ባለማመን የሚዳብሷት፣ የሚነካኳት
ብዙ ነበሩ። እናቴ ውኀ ፈስሶባት ሩኋን ገዛች። ለእሬሳዋ ሽኝት የተደገሰው ወደ ፌሽታ ድግስ
ተቀየረ። ከበሮ ተፈልጎ ተዘፈነ። ለቀብሯ የመጣ ዘመድ አዝማድ ሲሳከር አደረ።>>
<<ማነው ሞተች ብሎ የደወለው?!>>
<<እስከዛሬ የምናውቀው ነገር የለም። ከተረጋጋን በኋላ ነው ቀኑ የፈረንጆች <አፕሪል ዘ
ፉል/April fool's day መሆኑን ያወቅነው። ሰው እንዴት በእዚህ ይቀልዳል? ይኸው ከእዛ
ቀን በኋላ ማዘር አፕሪል ዘ-ፉልን እንደ አመቱ ገብርኤል ደግሳ ታበላለች። እኛም እህታችን
ከሞት ያተረፈችበት እለት እያልን ለሰው እንነግራለን።>>

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Tilahun Girma ango
2024/09/22 23:28:33
Back to Top
HTML Embed Code: