Telegram Web Link
እውነት እብዱ ማነው?
(እውነተኛ ታሪክ)
#ክፍል አንድ

እነሆ… እውነት እብዱ ማን ነው…? ልክ የዛሬ ሶስት ዓመት በዕለተ ባለወልድ አጥቢያ (ሐምሌ 28 ለሐምሌ 29) ከሌቱ ስምንት ሰዓት ገደማ ጥቂት ቀሳውስት ለቅዳሴና ማህሌት ወደ ቤተክርስቲያኒቷ እየገቡ ሳለ አንደኛው ቄስ ከቅፅሩ ባሻገር የትኩስ ውልድ ሕጻን ልቅሶ ድምፅ ሰምቶ ቆም አለ፡፡ ‹‹ይሰማችኋል የሕጻን ልጅ ልቅሶ…›› አለ፡፡ ሌሎቹም ጆሮአቸውን ቀስረው ይሰማል የተባለውን ድምፅ ለመጋራት ቆም አሉ፡፡ እንዳለውም ወዲያው የሕጻን ድምጽ ልቅሶ በድጋሜ ሲሰማ እውነትም ከቤተክርስቲያኑ ቅፅር ጀርባ ከወደ መቃብር ቤቶቹ አካባቢ የሚሰማው ድምጽ በጉልህ የትኩስ ውልድ ሕጻን እንደሆነ አረጋገጡ። የሐምሌው ዝናብ እኝኝኝ… ማለቱን ከጀመረ ቆይቷል… ይበርዳል…!
ከየት ነው…? የማን ነው…? ተጥሎ ነው…? የምን ጉድ ነው…? ወዘተ የመሳሰሉ ጥያቄ እያመላለሱ ሳለ ከመሃከላቸው አንደኛው ትንግርቱን የሚፈታ መላ መታ፡፡ ‹‹እናንተ… ያቺ እብድ እኮ ነፍሰ-ጡር ነበረች… እሷ ወልዳ መሆን አለበት…›› አላቸው፡፡ ሌሎቹም የተሰጠውን መላምት ከግምት በላይ እርግጠኛ ሆነውበት ምንም ሳይነጋገሩ በጥቆማው ተግባብተው ድምጹ ወደሚሰማበት የቤተክርስቲያኑ ቅፅር ጀርባ እየተጣደፉ ዘለቁ፡፡ "ያቺ እብድ" የተባለችው ይቺ ሴት ግን ማን ናት…? መጀመሪያ እሷን በጥቂቱ ላስተዋውቃችሁ፡፡ ስሟ በሀገሬው ሕዝብ ዘንድ “እብዷ” ይባላል፡፡ በቃ ይሄ ነው መጠሪያዋ፡፡ ከጥቂት ዓመታት በፊት ምናልባትም ከሁለት ዓመት ገደማ በፊት ነው እዚህ ከተማ የተገኘችው፣ ወይም “አምጥተው የጣሏት” ይላሉ ነዋሪዎቹ፡፡ በነገራችን ላይ ለምን እንደሆነ ባይገባትም ከተማውን በደንብ የምታውቀው እህቴ እንደነገረችኝ ከሆነ ብዙ እብዶችን በመኪና እያመጡ እዚህ ከተማ መጣል የተለመደ ነገር ከሆነ ቆይቷል፡፡ “ለእብድ መኖሪያ የሚሆን ተመራጭ ከተማ…” የሚለው ግርምተ-ሃሳብ ውስጤ ተመላለሰ፡፡ አንዳች መልስ የማገኝለት ይመስል ሃሳቡ ለአፍታም ቢሆን ውስጤ መቆየቱ ለራሴ ፈገግ አሰኘኝና ተውኩት፡፡ ክረምት ይሁን በጋ፣ ቀን ይሁን ማታ፣ “እብዷ” እዚህ ከተማ ከታየችበት ቀን ጀምሮ እስካሁን እርቃኗን ነው የምትውለው፣ እርቃኗን ነው የምታድረው፡፡ አንዳንድ ደግ ሰዎች እንደምንም ብለው ልብስ ሲያለብሷት በደማቅ ፈገግታ ታጅባ ለጥቂት ደቂቃዎች ብቻ የለበሰችውን ልብስ እንደ አንዳች ትንግርት ዙሪያ ገባውን ትመለከተዋለች፡፡ ይገርማታል ያስቃታል…! ከዚያ ሰዎቹ ዘወር ካሉ በኋላ ወዲያው አውልቃ ትጥለውና የለመደችውን ነጻነት በድጋሜ ተጎናፅፋ መለ–መላዋን ትቀጥላለች፡፡ በየትኛውም ቋንቋ ቢያናግሯትና ቢጠይቋትም በጠያቂው ድምፅ ወይም ቋንቋ ወይም ንግግር ከመደመምና አጫ በረዶ የመሰለውን ጥርሷን ብልጭ እያደረገች ፈገግ ከማለት ውጪ መልስ የሚባል ነገር ሰጥታ አታውቅም፡፡ የማትናገረው በተፈጥሮዋ “መናገር የተሳናት” ሆና ይሁን ወይም “እብዷ” ካሰኛት
የአዕምሮ ጤና መታወክ የተነሳ አይታወቅም፡፡ በአጭሩ ከፈገግታ በቀር አትናገር አትጋገር አይነት ናት፡፡ “እብዷ” እዚህች ትንሽ የገጠር ከተማ ከመጣች ጀምሮ ሰው ተተናኩላ አታውቅም ይላሉ፡፡ የተወለደችበትን አካባቢ ወይም ነገደ-ቋንቋዋን የሚያውቅ የለም፡፡ የሚገምትም የለም፡፡ ቁመቷ ሎጋ፣ ቀለሟ ጥቁር የሚባል፣ ፀጉሯ ከርዳዳና አጭር፣ አፍንጫዋ ሰልከክ ያለ፣ ጥርሷ ድርድር ያለ ነጭ ነው፡፡ ይህ ነው ስጋዊ መገለጫዋ፡፡ ከዚህ ውጪ እሷ ማለት በቃ “እብዷ” ናት፡፡ እዚህች ትንሽ ከተማ “አምጥተው ከጣሏት” ጀምሮ እዚያችው ማርያም ቤተ ክርስቲያን ዙሪያ ገባ እየዋለች፣ በመረጠችው መቃብር ቤት እያደረች፣ ቀንም ሆነ ማታ እርቃኗን በመሆን በራሷ ዓለም መኖር ጀምራለች፡፡
አንድ ክፉ ቀን “ጤነኛ” የሚባል/የሚባሉ የሆነ አካባቢ ሰው/ሰዎች ነው/ናቸው
አሉ እስኪደፍራት/እስኪደፍሯት ድረስ…
በዚያም ሰበብ እስክትፀንስ ድረስ…
ለሐምሌ ባለወልድ አጥቢያ በድቅድቁ ጨለማ ራሷ ሽሏን እስከምትገላገል ድረስ…
÷÷÷
ቄሶቹ የሚሰሙትን የአራስ ሕጻን ልጅ ልቅሶ አቅጣጫ እየተከተሉ፣ ድምጹ ከሚመጣበት ቦታ አካባቢ ሲደርሱ እውነትም “እብዷ” እንደማንኛውም ውሎ
አዳሯ ሁሉ በዚያ በሐምሌ ጨለማ በሐምሌ ቁር… በሐምሌ ዝናብ… እርቃኗን በድቅድቁ ጨለማ ውስጥ ቆማለች፡፡ አይናቸውን አጥብበው በጣም ተጠግተው ሲመለከቷት ደግሞ ከደቂቃዎች በፊት እዚያው እመቃብር ቤቶች አካባቢ አምጣ የወለደቻትን ልጅ ለፈጣሪ መስዋዕትነት የምታቀርብ ይመስል፣ ሕጻኗን በአንድ እጇ ወደላይ ከፍ አድርጋ ይዛ እንደተለመደው ፈገግ ትላለች፡፡ የሕጻኗ እትብት ከሕጻኗ ሆድ ጀምሮ ወደታች እስከ እናትየው እግሮች መሃል ድረስ ይወዛወዛል፡፡ ከእናትየው መዳፍ ብዙም የማትተልቀው ሕጻን በዚያ ሐምሌ ቁር እና ዝናብ እየተቀጠቀጠች በእሪታ ትነዝራለች፡፡ [ቄሶቹ የፈጣሪን እና የቅዱሳንን ስም እየጠሩ ማማተባቸውና ማነብነባቸውን መገመት ቀላል ነው፡፡]
ቄሶቹ በወቅቱ ምን አስበው ይሁን መረጃው ባይኖርም፣ በወቅቱ የወሰኑት ውሳኔ ከቤተክርስቲያኗ ፊትለፊት የሚገኝ አንድ ግቢ አስገብተውና የግቢውን በር
ዘግተው መሄድ ነበር፡፡ ግቢው ደግሞ አንድ ደግ የአካባቢው ሰው ደካማ
አዛውንቶችን የሚያኖሩበትና የሚረዱበት ነው አሉ፡፡ ለማንኛውም ቄሶቹ እዚያ
ግቢ አስገብው ወደ ቅዳሴአቸው ሄደዋል፡፡ (እዚህ ጋር ቄሶቹ ያደረጉት ነገር መልካም ነው ብዬ ለማሰብ ተቸግሬአለሁ…)
÷÷÷
የሐምሌው ዝናብ ሌቱም አልበቃ ብሎት ንጋትም እንዲሁ ሲንዛዛ ስለ ነበር፣በግቢው ውስጥ የሚኖርና በጠዋት የተነሳ ማንም ሰው አልነበረም፡፡ ከጠዋቱ ወደ ሶስት ሰዓት ገደማ በግቢው ውስጥ ከሚኖሩት ተረጂ አዛውንቶች መካከል አንዳቸውን ለመጠየቅ መጀመሪያ ወደ ግቢው የዘለቀችው አንዲት ወጣት ልጅ
ነበረች፡፡ ልጅት ወደ ግቢው ስትገባ ዙሪያ ገባ ከሚገኙት ክፍሎች መካከል ከኩሽና
ያልተናነሰውና ክፍት ከነበረው አንደኛው ክፍል ደጃፍ ላይ "እብዷ" አንዳች በጭቃ ተጨማልቆ የተድበለበለ ነገር ይዛ ወደላይ እየወረወረችና እየቀለበች ስትጫወትበት ተመለከተች፡፡ ልጅት ያየችው ነገር ትንንሽ እጆችና እግሮች
ስላሉትና ከሆዱ ደግሞ አንዲት ትንሽዬ ቁራጭ የምትወዛወዝ ነገር ስላየች በጣም ደንግጣ ጩኸቷን አቀለጠችው፡፡
የተኛም ያልተኛም ከየቤቱ ወጥቶ ምን ሆንሽ ቢሏት…‹‹እብዷ… እብዷ… እብዷ…. የሆነ አውሬ መሰለኝ… የሆነ አውሬ ነገር ይዛ እየተጫወተችበት ነው…›› ብላ እየተንቀጠቀጠች በጣቷ ወደ “እብዷ”
ትጠቁማለች፡፡ ሰዎቹም እየተጣደፉ ቢጠጉ “እብዷ” አሁንም ፈገግታዋን እያጀበች ሌት በ8:00 ገደማ በወለደቻትና በጭቃ ስታንደባልላት ባደረችው ልጇ አሁንም ትጫወታለች፡፡ አሁን የሕጻኗ እትብት ከእናትየው ተለያይቶ ትንሽዬ የእትብት ቅሪት በሕጻኗ ሆድ ላይ ተንጠልጥላለች፡፡ ራሷ ነች አሉ በጥሳ የለየችው፡፡ በጭቃ ተለውሳ ከተጨማለቀችው ልጅ ምንም አይነት ድምፅ የለም፡፡ በግቢው የነበሩት ሰዎች ተረባርበው ልጅቷን ከእናትየው ነጥቀው መሬት ላይ አስተኝተው ይተረማመሳሉ፡፡
ግንባሯ ላይ ድፍት ያለው ፀጉሯ ፈረንጅ የሚያሰኛት… ከአንድ መዳፍ በላይ
የማትተልቅ አንዲት እፍኝ ሴት ሕጻን ልጅ ትኑር ትሙት ለማወቅ የሚሞክር
ጠፍቶ ሁሉም እርስበርሱ እንደተፈራራ የሆነች እራፊ ጨርቅ ላይ አስተኝተዋት
አሁንም ወዲህ ወዲያ ይዋዥቃሉ… ይጮሃሉ… ይንጫጫሉ… አንዱ ይገባል…
የሚያየውን ማመን አቅቶትና ዘግንኖት እየሮጠ ይወጣል… ሌላው የተፈጠረውን
ለመመልከት ወደ ግቢው እየሮጠ ይገባል… ሁሉም ወዲህ ወዲያ ይላል…
ዝናቡም እኝኝኝ… ይላል…
÷÷÷
አባዬ፣ አለወትሮዋ የጠዋቱ ብርድ እና ዝ
ናብ ከአልጋ አላላቅቅ ብሏት ተኝታለች። ሰዓቱን ስትመለከት ሶስት ሰዓት ገደማ ስለሆነ እንደምንም ብላ ተነስታ ወደ
ማርያም ቤተክርስቲያን ቅዳሴ ሳያልቅ ለመድረስ ተጣድፋለች። በዚያ ላይ
ከልጆቿ መካከል አራቱን የወለደችው በባለወልድ ቀን ስለሆነ ለባለወልድ የተለየ ስሜት አላት። "አዬ የኔ ጉድ፣ ለዛውም በባለወልድ ቀን እንዲህ ላርፍድ?" እያለች ነጠላዋን ተከናንባ ከወጣቷ ልጇ ሚሚ ጋር አውራ መንገዱን ተሻግረው ወደ ማርያም የሚያስገባውን መንገድ ሲጀምሩ ከአንድ ግቢ ውስጥ የሚጮኹ፣ የሚንጫጩ፣ የሚተራመሱ ሰዎች ሲመለከቱ በድንጋጤ እየተጣደፉ ወደ ውስጥ ሲዘልቁ ሁለቱም በአይናቸው ያዩትን ማመን አልቻሉም…
÷÷÷

ይቀጥላል

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Tilahun abebe
#ወግ_ብቻ

💚#ናፍቆትህ ናፍቆኛል. .
©ትዝታዬ
.
" . . . ወሰን አልባው ፍቅርሽ ፣ ጠብቆኝ
በስስት ፣ አድርጎኛልና መንገዴን እንዳልስት።

ለአንኳኳለት ሁሉ ልቤ አይከፈትም ፣
እንኳንስ አካሌ ሃሳቤ አይሸፍትም።. . . ..
. . . "

ይኼን ሙዚቃ እንደ ዛሬ ብቻዬን ሳልቆዝምበት በፊት………ጮክ ብለን ዘፍነነዋል . . . ተለጣጥፈን አዳምጠነዋል. . . ተገባብዘነዋል. . . ትዝታ ፅፈንበታል. . . . .

ያኔ ……

ጥር ከመግባቱ በፊት ሳውቀው. . .

"ምወደው ጫካ አለ" አለኝ የመጀመርያ የአብሮነት ምሳችንን እየበላን ነበር. . .

"ትወስደኛለህ "

"ከፈለግሽ ደስ ይለኛል "

ካለንበት ዕሮብ ለቀጣዩ ዕሮብ አቀድን. . .

ፍቅሩን አንዴ ነው የጠጣሁት ለዚህም ነው አሁንም እንደ አማልክት ምኖረው. . .

የዓለምን ምስጢር የገለጠልኝ እውነት ነበር. . . ሚሆነውም እሱ ነው. .

አስፈሪው ጫካውን ሲያሳየኝ አልፈራውም ፣ አልደነገጥኩም. . . . አልተጨነኩም. . . . ነፍሴ ስትዘል . . . ስታመሰግን አየዋት . . . ያኔ ነው ያፈቀረችው መሰለኝ . . አክብራው ስታጎነብስ አይቻታለው. . . ነፃነቷን ሰቷት ነበር እና. . . .

ከዛ ቀን በኃላ ከንፈናል . . . ያለሱ ሚታየኝ ውበት፣ የሚጣፍጠኝ ስም አጣው. . . በረርኩ . . ልቡ ውስጥ ፣ ነፍሱ ውስጥ ፣ አዕምሮው ውስጥ . . በፍቅር ፈቀደልኝ. . .

ለኔ ደክሞት ፣ሰንፎ አያውቅም. . . ያፈቅረኛል!!
ፍቅሩን መላው አካላቱ ይናገራሉ. . .


ሊመሽ ሲል ከመለያየታችን በፊት መንገድ ዳር ሻይ እንጠጣለን. . . እኔ ችፕስ ወዳለው . . . እሱ ጨጓራውን ያመዋል . . . ቢሆንም ይበላልኛል. . .ቦታውን ወዶት እኮ አደለም ሚቀመጥልኝ እኔ ስላልኩት ነው. . . .

ማይወደውን ፣ ማይፈልገውን ሁሉ ለኔ ፣ ለፍቅራችን ሲል ፈልጎት ነበር . .

* * *


ዛሬ…………

ደክሞት ፣ ደክሞኝ ጠፍተናል. . . የዘረጋነውን እውነት በመቆሳሰል ደብቀነዋል. . . ያቀፈኝ ክንዱ ተሰብስቦዋል ፣ ጥጉ ፣ ጥጌ ላይ ነኝ. . . ህልሞቻችን ከቀኖቻችን ጋር ተኳርፈዋል . . . የራሱ ልብ ውስጥ ፣ የራሴ ነፍስ ውስጥ ተወታትፈናል. . . . ደምኖብናል . . .

እራሴን ጠይቃለው " ፍቅራችን እውነት አበቃ ?"

ይቆጨኛል. . . ሚቆጨኝ ስለሌለ ሳይሆን ያልነገርኩት ስላለ ነው. . .

"ያልኖርኩልክ የቀረኝ ሂወት አለኝ. . . ያላሳየሁክ ያልሆንኩልክ እውነት አለኝ ፣ ውሃን ልወልድልህ ፈልጋለው ፣ እስከ እድሜዬ አመሻሽ አንተን ነው ምፈልገው ፣ እንደ ደነስናቸው ዳንሶች ፣ እንደነበሩን ፀሃይና ጨረቃ ፣እደተሳሙት ከንፈሮቻችን ፣ እደተራመድንባቸው ጓዳናዎች ፣ እዳለቀስንበት ምሽት ፣በጅብ እንደፈራንበት ቀን ፣ እንደ ደበደበን ዝናብ ፣ እዳቃጠለን ሀሩር ፣ እንደ ጉርሻችን ፣ እንደ ሰጠከኝ አበቦች . . ተው ትዝታ አንሁን . . " ልለው ፈልጋለው!

"ከአንተ ጋር የአንዲት ሰዓት ሐሴት ዘላለማዊ ውድ ቅርፅ ነው።. . . ፍቅራችን ከዘመናት በፊት የጠፋውን ማሙዝ እንዲሆን አልፈልግም. . . የሳትነውን መንገድ እንመለስበት፣ ኑርልኝ፣ ልኑርልህ ፣ ና ፣ ልምጣ " ልለው እፈልጋለው

. . . . ግን አልለውም

አንዳንድ እውነቶች መነገር አይፈልጉም ፣ ቁጭትን እየወለዱ ቢሆን እንኳን በመደበቅ ይፀናሉ. . .

ቢሆንም ናፍቆትህ ዝም ብሎ ይናፍቀኛል ፣ ናፍቆ ያሰኘኛል. . . እንዳልመጣም ፣ እንድመጣም
ይመክረኛል!!

/ትዝታ /


|❀:✧๑♡๑✧❀|

@wegoch
@wegoch
@wegoch
ወጣቱ ልጅ የመጀመሪያ ደረጀ ት/ቤት አስተማሪውን በሆነ ሰርግ ላይ ያየዋል። ሮጦ ሄዶ በትህትናና በአድናቆት ሰላም ካለው በኃላ አስተማሪውን "አስታወስከኝ ወይ?" አለው።አስተማሪውም ግራ በመጋባት ውስጥ ሆኖ "ይቅርታ አላስታውስህም እንዴት እንደተዋወቅን ልትነግረኝ ትችላለህ?" አለው፤ወጣቱም ልጅ እንዲህ እያለ ተረከለት "3ኛ ክፍል እያለን ያንተ ተማሪ ነበርኩ፤ታዲያ አንድ ቀን የክፍል ጓደኛዬን ቆንጆና ልዩ የሆነውን የእጅ ሰዓቱን ሰርቄበት ነበር።እሱም እያለቀሰ ሄዶ የእጅ ሰዓቱ እንደተሰረቀበት ላንተ ሄዶ ይናገራል፤አንተም መጥተህ ልትፈትሸን ሁላችንም ክፍል ውስጥ ያለን ልጆች አይናችንን ጨፍነን እጃችንን ከፍ አድርገን ፍታችንን ወዴ ግድግዳ ኣዙረን እንድንቆም አዘዝከን።በዛን ጊዜ እኔ የፍተሻውን ውጤት እያሰብኩ በጣም ተረበሽኩ፤የሚገባበትን አጠሁ።አስበው ሰዓቱ በኔ ኪስ ውስጥ ተገኝቶ ሁሉም ተማሪ ሌባ እያለ ስሰድበኝ፤ ግቢ ውስጥ መጠቋቆሚያ ሲሆን፤ከት/ቤት ተባርሬ ወላጅ አምጣ ስባልና ወላጆቼ ይሄን አሳፋሪ ድርግቴን ስሰሙ።በዚህ ጭንቅ ውስጥ እያለሁ የፍተሻው ተራ ደርሶ እጅህ ወደ ኪሴ ስገባና ሰዓቱን ቀስ አድርገህ ከኪሴ ስታወጣ ተሰመኝ፤በቃ መጥፎ ዜናው ልነገር ነው አለቀልኝ ብዬ ስጠባበቅ አንተ ግን ምንም ሳትል የመጨረሻው ልጅ እስክትደርስ ፍተሻውን ቀጠልክ።ፍተሻውም ስያልቅ አይናችሁን ግለጡና ወደየቦታችሁ ተመለሱ አልከን።እኔ ግን መልሰህ ታስቆመኛለህ ብዬ መቀመጡን ፈራሁ።በጣም የሚገርመው አንተ ሰዓቱን አውጥተህ ለባለቤቱ መለስክለት፤ግን ከማን ኪስ ውስጥ እንዳገኛህና ማን እንደሰረቀበት ምንም አልተናገርክም ነበር።በት/ቤት ቆይታዬም ምን እንደተፈጠራ ማንም አላወቀብኝም ነበር፤አንተም ምንም ብለሃኝ አታውቅም።እኔ ግን ስሜንና ክብሬን እንዳደንክና ስብዕናዬ እንደጠበክልኝ ዛሬም ድረስ አስታውስሃለው።አንተም ይሄን ታሪክ ቶሎ ትረሳለህ ብዬ አልገምትም አሁንስ አስታወስከኝ?" አለው።አስተማሪውም በመገረም ውስጥ ሆኖ "ትንሽ ትንሽ አስታውሳለው በማን ኪስ ውስጥ እንዳገኛሁ ግን አላስታውስም፤ ምክንያቱም እኔም ስፈትሻችሁ የነበረው አይኔን ጨፍኜ ነበር!!"አለው።

# NB በህይወታችን ለሚናከናውናቸው ነገሮች ሁሉ ጥበብ ያስፈልገናል።እንደ አስተማሪ እንደ ወላጅ እንደ መሪ...ወዘተ ለአንዳንድ ነገሮች አይናችንን መጨፈን አለብን ምክንያቱም ሁሉም ጥፋቶች በቅጣት ብቻ አይታረሙም!!!!

@wegoch
@wegoch
@paappii

#ግጥም አብዮት
መቼም ጊዜ የማያሳየን ጉድ የለም።
ዛሬ የ you tube ከርስ ውስጥ ገብቼ አንጀቱን ሳማስል ቆየሁ። ከሁሉም ከሁሉም ግርምቴን የወሰደው የ 90 ዎቹ ሙዚቃ ነበር ። ሙዚቀኛ አቤል ነይ ማታ ማታ የሚለውን ሙዚቃ መለስ ብላችሁ እዩት እስቲ?
አቤሎ ያደረገው ከርፋፋ ሱፍ አነስ ያለ ዩንቨርስቲ ተምረው ለመመረቅ የተዘጋጁ 5 ተማሪዎችን ጥንቅቅ አድርጎ ያስመርቅ ነበር😊 ... አቤት የሱፍ ግፍ! ጓዶች በ 90 ዎቹ ጊዜማ የሱፍ ጨርቅ ላይ ግፍ አቆይተናል። እዛ የሰራነው ግፍ ነው ዛሬ ሱፍ ልብስንም የሱፍ ቆሎንም ያስወደደብን 😭
ወደ አቤሎ ሱሪ አዘቅዝቄ ተመለከትኩ።
ሱፍ ዑመር ዋሻማ ምን ይሰፋል? እንዝርት ለምታክል ቅልጥም የደብረ ብርሀን ብርድ ልብስ የሚያህል ጨርቅ ሱሪ ገድግዶበታል።
ወያኔ ምሽግ ሳይሰራ የቀረው እሱ ሱሪ ውስጥ ብቻ ነበር 😜
ደግሞ ሁሌ ሁሌ የሚል የሀይልዬ ክሊፕ አለ። በሰዓቱ ብዙ እይታ አድርጎ የሰቀለው ቪድዮ ላይ የሚደንሱ ሴቶች ሁለቴ ራመድ.. .ሶስቴ ወደ ኋላ መለስ እያሉ ይጨፍራሉ ። ደግሞ አሰላለፋቸው የኮንሶ ወረዳ ካዘጋጃቸው እርከኖች ፈፅሞ አይለይም።
ወደ ሌላ ሙዚቃ ተሸበለልኩ።
አሸንፈን...አሸንፈን...በማራቶን 😃
ወይኔ ወንድሜ ጆሲ !
የራሱ ትልቀትና የሰውነቱ ቅጥነት የሚመጠጠውን ከረሜላ ቁጭ!
ጀላቲም እንደመምሰል ይላል ። ፈረንጆች ይሄን አይተው ኖሯል ለካ እናንተ ጠኔያሞች ብለው የሚሞሸልቁን።
ነይ በክረምት የሚለው የመስፍኔ ሙዚቃ ለጥቆ መጣ ። የዳሎል ጨው !
ጭው ያለ ፊት ... የኢትዮጵያን መከራ የተሸከመ ፊት...ጦርነት ፊት ። ንግድ ባንክ ፊት ... ከዚህ እስከዛ ፊት ...ከዛ እስከዚህ ፊት 😄 ይሄም ቢሆን ግን የእናት አሜሪካ ውለታ ን መዘንጋት የለብንም። የማክዶናንድ በርገር አጋርነትን መርሳት የለብንም። መስፍኔ እንደገና ተወለደ ! መስፍኔ እንደገና አበበ ። መስፍኔ ከጨው ፊት ወደ ፓሎኒ ኳስ ፊት ያሸጋገርክልን ጌታ ክሪሺና ምስጋናህን ውሰድ 🙏
ትንሽ ቆየት ያለ የፍቅራዲስ ሙዚቃ ደግሞ ዠመረ ። ብትን ጨርቋ ብትንትን ብሎ መሬት ላይ ፍስስ.. .ስጋ ያልያዘ ፀጉራም ፍየል ቁጭ! ዛሬ እድሜ ለጊዜ ይሁንና የፍቅርዬ ቻፓ ወንዱን ሁሉ እያማለለው ይገኛል /አበበ ብርሀኔ አፉ ይበለኝና ቻፓዋ ግን ይመስጣል! /
ቴዲ አፍሮን ብነካ ጀማው ይነክሰኛል እንጅ የሆነ ዳፍንታም መነጥር አድርጎ ለማን ልማሽ እያለ መሞዘቁን ላሽ ልል አልፈልግም። ለዛ ክሊፕ ሳይሆን ለብረት ቤት ብየዳ አገልግሎት ነበር ያ መነጥር መዋል የነበረበት ።
ከአፍታ በኋላ ቴድዮ ከተፍ አለች ። ጡት ከጣለ ሳምንት ያልሞላው ምስኪን ራፐር ። የጉራጌ ቶን ምናምን 😁 ክሊፑ ላይ ሲደንስ ሳየው እንደ ወፍ እንዳይበር እንዴት እንደፈራሁለት ብታዩ!
በሰው ይሄን ያህል ስቄ ከ አራት ዓመታት በፊት የተነሳሁትን የራሴን ፎቶ አየሁት ።
በዛን ጊዜ ሉሲን አገኘኋት ያለው አንትሮፖሎጂስት እኔ አይቶ መሆንማ አለበት !
እህል ከቀመሰ ዓመታት ያስቆጠረ ነብይ ይሄን ያህል አይሞግግም። ስማር ነበር ወይስ ተማሪዎችን ፉጨት ሳስተምር ነበር ? በሚል ጥያቄ ትንሽ እንደተወዛገብኩ.. . የመሰረት መብራቴ ድራማ ሰተት ብሎ ላፕቶፔ ስክሪን ላይ ተገሰጠ ። መሲ የኔ Philps ከጥንት እስከ ጠዋት አንድ አይነት ፊት።
አባቴ በጋን ቁልፍ ጠርቅሞ ሲጠቀምበት የኖረው Philips ካውያ ዛሬም ድረስ አዲስ መሆኑን አስቤ ፈገግ አልኩኝ።
አባዬ ካውያውን ዝም ብሎ ሲያየው ይቆይና አይ የድሮ እቃ! ይላል በግርምት ። በነገራችን ላይ እሷን ካውያ የነካ አይደለም የቁም ሳጥኗን ቁልፍ በእጁ የያዘ የቤተሰቡ አባልን አባዬ በርግጫ እንደ ኳስ ያነጥረው ነበር ። ቀልቃላዋ ታናሽ እህቴ ስንት ጊዜ በረንዳውን ተሻግራ የግቢው አበባ ላይ እንዳረፈች እኔ ብቻ ነኝ የማውቀው !
ሸሚዙን ጠረጴዛ ላይ ጥሎ ካውያውን ከወዲህ ወድያ ሲያንገላታው መሲዬ ን ያሰቃያት እየመሰለኝ በልቤ አዝንበት ነበር :)

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Mikael aschenaki
Forwarded from WORDS
"The secret of your future is hidden in your daily routine."

@words19
#የህልም ፍታት - ከአመታት ወደ ቀናት

ክተታችን ደርሶ እየመታነው እንገኛለን። አዲስ ነገርን አስበን ብዙ አስበን ሩቅ አልመን ያዘጋጀነውን አጣፍጠን የሰራነውን ማዕድ ብትቀምሱ ለብርዱም ኩታችሁን ደርባችሁ የኪነ-ጥበብ ማዕድ ላይ ብትቋደሱ እያልን ስንጋብዝ። ገጣሚው ቃሉን ሰድሮ ሙዚቀኛውም ዜማውን ወጥሮ የሰራውን ማዕድ ቅመሱልኝ ብሎ ስለተጣራ ሁላችሁም በጠራነው ክተት ተከታችሁ ነሀሴ 23 ፒያሳ በሚገኘው hi5 coffe house እንድትገኙ እንላለን። ያለን ቦታ ውስን በመሆኑ የእሽቅድምድም ጉዳይ እና ቀድሞ ብታ የማስያዙ ጉዳይ ይታሰብበት ልንል እንወዳለን። ኩታችሁን ደርባችሁ አልያ በሀገር ባህል ልብስ አሸብርቃችሁ ኑልን እኛም ጎንበስ ብለን እንቀበላለን።

ሁላችንም ግብዣውን እናድርስ
share
እውነት እብዱ ማነው?
ክፍል - ሁለት
(የመጨረሻ ክፍል)

አባዬ፣ አለወትሮዋ የጠዋቱ ብርድ እና ዝናብ ከአልጋ አላላቅቅ ብሏት ተኝታለች። ሰዓቱን
ስትመለከት ሶስት ሰዓት ገደማ ስለሆነ እንደምንም ብላ ተነስታ ወደ ማርያም ቤተክርስቲያን ቅዳሴ ሳያልቅ ለመድረስ ተጣድፋለች። በዚያ ላይ ከልጆቿ መካከል አራቱን የወለደችው በባለወልድ ቀን ስለሆነ ለባለወልድ የተለየ ስሜት አላት። "አዬ የኔ ጉድ፣ ለዛውም በባለወልድ ቀን እንዲህ ላርፍድ?" እያለች ነጠላዋን ተከናንባ ከወጣቷ ልጇ ሚሚ ጋር አውራ መንገዱን ተሻግረው ወደ ማርያም የሚያስገባውን መንገድ ሲጀምሩ ከአንድ ግቢ ውስጥ የሚጮኹ፣ የሚንጫጩ፣ የሚተራመሱ ሰዎች ሲመለከቱ በድንጋጤ እየተጣደፉ ወደ ውስጥ ሲዘልቁ ሁለቱም በአይናቸው ያዩትን ማመን አልቻሉም…በግቢው ውስጥ ያለው አብዛኛው ሰው ፈራ-ተባ ባለበት ወቅት አባዬ አለፍ ብላ የማትናገር የማትንቀሳቀሰዋን ሕጻን አንስታ በሕይወት ትኑር ትሙት ለማወቅ ትንፋሿን ለማዳመጥ ሞከረች። ከሌቱ ስምንት ሰዓት ጀምሮ እስከ ንጋቱ ሶስት ሰዓት ድረስ ለዘለቁት ሰባት ወይም ስምንት ሰዓታት ገደማ በዚያ አይነት ሁኔታ የቆየችው አራስ ልጅ አሁንም እስትንፋሷ አለ፡፡ በምን እንደተቆረጠ የማይታወቀው ቁራጭ እትብቷ አሁንም ሳይታሰር ጠልጠል እንዳለ ነው፡፡ አባዬ ሕጻኗን ለሚሚ ሰጥታ እየሮጠች ወደ ቤቷ ተመልሳ መጠራረጊያ እና ማቀፊያ የሚሆኑ ልብሶች ይዛ መጣች፡፡ ልጅቷን ሲጠራርጓት በጣም የገረማቸው ነገር ከጭቃ በቀረ ምንም አይነት ደም የቀላቀለ ነበር አልነበረባትም፡፡ ምናልባትም እናትየው ከወለደቻት በኋላ በዝናቡ ውስጥ መንገድ ላይ ዘለግ ላለ ጊዜ ይዛት ስለቆመች ዝናቡ አጥቧትም ሊሆን ይችላል፡፡ ያም ሆኖ ግን ጭቃዋ ሲጠራረግ ልቅም ያለች ቀይ ልጅ ብቅ አለች፡፡ ‹‹ፀጉሯ ግንባሯ ድረስ ድፍት ብሎ ቻይና ነበር እኮ የምትመስለው…›› ትላለች አባዬ ለኔ ባወራችኝ ጊዜ እንኳን ሶስት ዓመት ወደ ኋላ ተመልሳ በትዝታ፡፡ የግቢው ባለቤት፣ አባዬ እና ሚሚ ልጅቷን ከበው ምን እንደሚያደርጉ ለአፍታ መምከር ጀመሩ፡፡ ‹‹ለመንግስት እንስጣት ይሆን እንዴ…? ምን ይሻላል…? ምንስ እናድርግ…?›› ይላሉ
የግቢው ባለቤት፡፡ ‹‹አዪ ለመንግስት ብንሰጥስ ምን ይበጃታል ብለሽ ነው…? መጀመሪያ ግን ወደ ጤና ጣቢያ መውሰድ አለብን… ሌላውን በኋላ እናያለን…›› አሉ አባዬ ልባቸው የሚነግራቸው ሌላ መፍትሄ እንደሆነ በውስጣቸው እርግጠኛ ሆነው፡፡ መጀመሪያ ግን የልጅቷን ሕይወት ማትረፍ እንደሆነ ስለገባቸው ወደ ጤና ጣቢያ ለመውሰድ እየተሰናዱ፡፡ አባዬ በቃል አያውጡት እንጂ በልባቸው ያለውን አሳብ ምንም ሳይዘገይ ነበር ሚሚ ያቀበለችው፡፡ ይህ ሲሆን ሚሚ ነበረች የተጠራረገችውን ልጅ በማቀፊያ ይዛ የነበረችው፡፡ ‹‹አባዬ ይቺን ልጅማ ለማንም አንሰጥም… እኛው እናሳድጋታለን…›› አለች ፍጹም ፍርጥም ባለ እርግጠኝነት እና ስስት በእቅፏ ያለችውን አራስ ቁልቁል ትክ ብላ እያየች…‹‹ይሁን እኔም እንደሱ ነበር እያሰብኩ የነበረው… በይ ወደ ጤና ጣቢያ እንውሰዳት መጀመሪያ… በጣም ደክማለች…›› ብለው እየተጣደፉ ወደ ጤና ጣቢያ ሄዱ፡፡ ጤና ጣቢያ ደረሱ፡፡ ቁራጭ እትብቷም ተቋጠረ፡፡ ሙቀቷ 27 ዲግሪ ስለነበር በወቅቱ የነበረችው ሐኪም ወደ ማሞቂያ ክፍል እንድትገባ አደረገቻት፡፡ ሕጻኗ እየቆየች የበለጠ
ነፍስ እየዘራች ብትሄድም አንድም ጊዜ ስላልጠባች ጉዳት እየገጠማት ስለሆነ እነ አባዬ እብዷ ወዳለችበት ተመልሰው መጥተው እንዴት አድርገው እናትየውን አግባብተው በመውሰድ ልጅቷን እንድታጠባ ለማድረግ ከሰፈሩ ሰዎች ጋር ይመክራሉ፣ ይህ ሲሆን ተሲያት ሆኗል፡፡ የሚሚ ስልክ አቃጨለ፡፡ ሐኪሟ ነበረች… ‹‹ሐሎ አለች ሚሚ…›› ምናልባትም መጥፎ ዜና ልትነግራት የደወለች መስሏት እንደመደንገጥ ብላለች፡፡
‹‹ሐሎ… ምንድን ነው በዚያው የጠፋችሁት…እዚህ አምጥታችሁ ጥላችሁ የሄዳችሁትን
መጥታችሁ ውሰዱ እንጂ… ማን ላይ ጥላችሁ ለመሄድ አስባችሁ ነው…›› እያለች
አበሻቀጠቻት፡፡ ‹‹ስሚ የኔ እህት… እዚያ ጥለን የሄድነው ዕቃ አይደለም… የሰው ልጅ ነች እሺ…!?
እንዲህማ ልትናገሪ አትችዪም እሺ…! ለማንኛውም አሁን እንመጣለን ሌላ ትርፍ ነገር
አትናገሪ…›› ብላ እሷም አስታጠቀቻትና ወደ ጤና ጣቢያው ተመለሱ፡፡ እብዷም በዚህም በዚያም ተወስዳ ልጅቷን ባታጠባም ቢያንስ ኤች.አይ.ቪ እንድትመረመር ተደረገ፡፡ የፈጣሪ መልካምነት ማለቂያ አልነበረውምና እናትየው ከቫይረሱ ነፃ መሆኗን ሲያውቁ ለሁሉም ትልቅ እረፍት ነበር፡፡ ልጅቷን የማጥባቱ ነገር ግን የሚሆን ስላልሆነ
ከአመሻሹ 11፡00 ገደማ የፎርሙላ ዱቄት ወተት ተገዝቶና በጡጦ ተበጥብጦ ልጅት አፍ ላይ ሲደረግ በርሃብ ስትናጥ የነበረችው ሕጻን ወዲያው መጥባት ጀመረች፡፡ አባዬ ትልቅ
እረፍት እና ደስታ ተሰማት፡፡ የሚገባውን ጊዜ ወስደው፣ ልጅቷ በሙሉ ጤንነትና ጥንካሬ ላይ ስትሆን አባዬና ሚሚ ልጃቸውን ይዘው ወደ ቤታቸው ገቡ፡፡ ለአባዬ ትልቅ ትዝብት የነበረው ነገር እና እስካሁን ስታወራው እጅግ እየከነከናት ያለው ነገር አንዳንድ ሰዎች፣ የጤና ጣቢያዋን ሐኪም ጨምሮ የተናገሩት ነገር ተመሳሳይ እና እጅግ ኢሰብዓዊ የመሆኑ ነገር ነበር፡፡ ‹‹እንዲህ አይነቱ ልጅ ሲገኝስ ወስዶ ማሳደግ ነበር…! ግን ምን ዋጋ አለው… ሴት ሆነች እንጂ…! ወንድ ቢሆን ኖሮ ቢያንስ ቤት ይጠብቃል… ወይም ጥሩ እረኛ ይሆን ነበር… እያሉኝ እኔ ግን ልጄን ይዤ ስመጣ በጣም ነበር ደስ ያለኝ…›› ትላለች አባዬ አሁንም በጥልቅ ትዝብት የሰዎቹን ክፋት እየታዘበችና ወደኋላ እየተመለሰች፡፡ "ልጄ" ብላ ነው የምትጠራት። አባዬን ላስተዋውቃችሁ…?
አባዬ አክስቴ ነች… የእናቴ ታናሽ እህት… ከመንታ የማትተናነስ ቁርጥ እናቴን መሳይ…ከቁመና እስከ ፊት መልክ… ከድምጽ እስከ ውስጠ ስብዕና…! ላለፉት 14 ዓመታት አባዬን ባየሁ ቁጥር ስሜቱን ለማስተናገድ እጅግ ከባድ ነበር ለኔ፡፡ እናቴ ከሙታን ዓለም መጥታ የምታናግረኝ እስኪመስለኝ ድረስ ነበር መመሳሰላቸው… ድምጻቸው… ስብዕናቸው…እርጋታቸው… ጥርሳቸው… ጣቶቻቸው… ምኑ ቅጡ…!እናም አባዬን ለመጨረሻ ጊዜ ያየኋት ሌላኛዋ አክስቴ በሞተች ወቅት ለቀብር እዚያች ከተማ በሄድኩበት ጊዜ ነበር፡፡ እሱ ደግሞ ጊዜው ዘለግ እያለ ስለመጣ የሆነ ቀን ታላቅ እህቴን አብረን ሄደን እንደምንጠይቃት እንደዋዛ ቃል ገባሁላት፡፡ እህቴም የዋዛ አልነበረችም አውቃ ቀን አስቆረጠችኝ፡፡ እኔም ተስማማሁ፡፡ ቀኑ ደረሰና ከመጓዛችን በፊት ባለቤቴም የጉዞው ተሳታፊ እንደምትሆን አሳውቃን እጅግ ደስ የሚል ጉዞ አደረግን፡፡ አባዬን እና ሌላኛዋን አክስቴን እንዲሁም ዘመድ አዝማድን ከማየት እና ከመጠየቅ በዘለለ እንዲህ አይነት ተዓምረ ክስተት እመሰክራለሁ ብዬ ፍፁም አላሰብኩምም አልገመትኩምም ነበር፡፡ ቅዳሜ ተሲያት በኋላ ነበር የደረስነው፡፡ መምጣታችንን ቀድመን አሳውቀን ስለነበር ምንም ነገር ሳይጎድል ሁሉ ሙሉ ሆኖ ነበር የጠበቀን፡፡ ደስታው ልዩ ነበር፡፡ የአክስቶቼ ስስት የሚዘገን የሚታፈስ ነበር፡፡ እናቴን እያስታወሱ ለማለቃቀስ ሞከር አድርጓቸውም ነበር እኔ ኮምጨጭ ብዬ መለስኳቸው እንጂ፡፡ እነሱ እንደሁ እናቴን አንስተው ለማልቀስ ጥንጥዬ ነገር በቂያቸው ነች፡፡ በዛውም እንደ ወናፍ እስክወጠር ድረስ ‹ዘመድ ጠያቂና ቁምነገረኛ› መሆኔ ተደጋግሞ
ሲነገረኝ፣ ስመሰገን፣ አሁንም አሁንም ስመረቅ እንደ መነፋፋትም ቢጤ ሞክሮኝ ጎምለል ማለቴ አልቀረም፡፡ ቤቱ ውስጥ የአክሰቶቼ ልጆች፣ ጎረቤት፣ ተጨማሪ ዘመድ አዝማድ ውር ውር ይላል፡፡
ከሁሉም አይኔን የሳበችው ግን አንድ ጊዜ ‹እማዬ› አንድ ጊዜ ደግሞ ‹አባዬ› እያለች የምትጣራ እና ሙልቅቅ ብላ አባዬን አላንቀሳቅስና ከሰው አላስወራ የምትለው ሕጻን ልጅ ነበረች፡፡ ሕጻኗን የ3 ዓመት ልጅ ገደማ መሆኗን መገመት ከባድ አልነበረም። የሚገርመው ግን ከ10 ቀን በኋላ ልክ 3 ዓመት የሚሞላት ልጅ መሆኗ ነበር፡፡ እሷ ማለት ደግሞ ያቺው ከላይ የተረኩላችሁ ተዓምረ-እግዚአብሔር ናት… "ሚጡ" እንበላት ለወጋችን ያክል፡፡ አባዬ እናቴ በምትጠራኝ ስም ‹በልዬ› እያለች ነው የምትጠራኝ፡፡ ሌላኛዋ አክስቴ ደግሞ ‹ጥላሁን› ነው የምትለኝ፡፡ በውስጤ ጥያቄ እንዳለ የገባት የመሰላት አባዬ ከምሳ በኋላ ቡና እየጠጣን በጨዋታ መሃል…‹‹ይኸውልህ በልዬ በስተርጅና ይቺን የመሰለች ልጅ ወለድኩ…›› ብላ ወሬ ከመጀመሯ ተዓምሪቷ ሚጡ አሁንም አላስወራ አለቻትና ከወሬው አናጠበቻት፡፡ ወዲያውም ደግሞ ለጠየቃትም ላልጠየቃትም ስሟን እስከ አያቷ ድረስ ደጋግማ መጥራት ትይዛለች፡፡
‹‹ማነው ስምሽ አንቺ…›› ሲሏት…‹‹እኔ… ሚጡ… አቡሽ… አባባ…›› ትላለች አሁንም አሁንም የራሷንም፣ የአባቷንም፣ የአያቷንም ስም ሳታዛንፍ በልጅ አፍ በትንሹ ኩልትፍ እያለችና ፊደላቱን እየጠራች፡፡ በአባትነት የምትጠራው አቡሽ በጥቂት ዓመት የሚበልጠኝን የአባዬ የመጨረሻ ወንድ ልጅ ነው፣ በአያትነት ደግሞ የአባዬን ባል (የአቡሽን አባት)…! ግራ መጋባቴ ቀጥሏል፡፡ አቡሽ የሚኖረው አሜሪካ እንደሆነና ይቺ ልጅ ከመወለዷ ብዙ ዓመት በፊት አግብቶ ልጆች
እንደወለደም አውቃለሁ፡፡ ግራ ገባኝ፡፡ አባዬ ወደ ጓዳ ሄድ ስትል… እህቴ ላይ የጥያቄ ፊት ዘረገፍኩባት፡፡ ይህን ያወጋኋችሁን ታሪክ እህቴ ከሌላኛዋ አክስቴ ልጅ ጋር ሆነው ፈጠን ፈጠን እያሉ ተጋግዘው በአጭሩ ነገሩኝ፡፡ ግፋ ቢል ከአምስት ደቂቃ ባልበለጠ ጊዜ አጠናቀቁት፡፡
‹ይህንንማ ከራሷ ከአባዬ ሙሉ ዝርዝሩን ካልሰማሁ በቀር አይሆንም…› አልኩና ለምሽት የእራት ላይ ጨዋታ አቆየሁት፡፡ አላስቻለኝምና እራት ገና እራት መብላት እንደጀመርን አነሳሁላት…‹‹አባዬ… ምንድን ነው ቅድም እኮ ስለዚህች ሕጻን ልጅ እንዲህ እንዲህ አሉኝ… ኧረ
እንደው ሙሉውን ንገሪኝ አባይዬ…›› ብዬ ጀመርኩ፡፡ ‹‹አይ በልዬ… የሷ ነገርማ ተዓምር ነው፡፡ ይሄ እናንተ በምታነቡት መፅሐፍ ውስጥ ራሱ ቢፈለግ አይገኝም…!›› አለችና ጀመረች፡፡ ‹ይሄ የምታነቡት መፅሐፍ ውስጥ አይገኝም›
ማለቷ በልብ-ወለድ እንኳን የማይታሰብ ነው ለማለት ነው፡፡ የንጽጽሯ ጥልቀት የገባኝ ታሪኩን ከጨረሰችልኝ በኋላ ነበር፡፡ Stranger than fiction የሚልና በጣም ወድጄ የተመለከትኩትን አንድ የሆሊዉድ ፊልም አስታወሰኝ አገላለጿ፡፡ ድንቅ ነበር ንጽጽሩ…!ለታሪኩ ስክት ብሎ የሚገባ ጠቅላይ ዐረፍተ ነገር…!ከዚያም ቀስ እያለች እስከላይ ድረስ የነገርኳችሁን ተረከችልኝ፡፡ የሰሙት ሁሉ እንደ አዲስ አደመጡ፡፡ አንዳንዴም በየመሃሉ እየገቡ ጨማመሩበት፡፡ ባለቤቴ በተፈጥሮ ያላት ቦጅቧጃ ስብዕና ላይ እናትነት ተጨምሮበት ፊቷን ለመግለጽ በሚከብድ ስሜት አብራኝ አባዬ አፍ ላይ ተተክላለች፡፡ እኔም በየመሃሉ ለማመን የሚከብደኝን ነገር በጥያቄ ማጣደፌ አልቀረም፡፡ ደጋግሜ የምጠይቃት ግን እንዴት ከሌቱ ስምንት ሰዓት ጀምሮ እንደዚያ ሆና በሕይወት ተረፈች…? እንዴትስ እስከ ማታ 11፡00 ድረስ ጡት ሳትጠባ ልትተርፍ ቻለች…? እንዴትስ
እትብቷ በዚያ መልክ ተበጥሶ እና ሳይታሰር ተረፈች…? እናትየውስ እንዴት ተረፈች…? ማለቂያ አልነበረውም ጥያቄዬ፡፡ ‹‹አይ በልዬ እንደሚሉትማ እትብት በ30 ደቂቃ ወይም ቶሎ ተቆርጦ ካልተቋጠረ ልጅ ይሞታል ይባላል፡፡ በዚያ ላይ ብርዱ፣ ዝናቡ፣ ጡት አለመጥባቱ፣ እንደዛ በጭቃ እያድበለበለች ስትጫወትባት አድራ በሕይወት መትረፏ ሌላ ምን መልስ አለው በልዬ…የፈጣሪ ስራ ነው እንጂ! የእመቤቴ ማርያም ስራ ነው እንጂ! የባለወልድ ተዓምር ነው እንጂ በልዬ! የሚገድልም የሚያድንም አንድ ፈጣሪ እንጂ እንደ ሰው ግምትማ መች ትተርፍ ነበር…!» የሚል ነበር መልሷ። አባዬ ይህን ስትለኝ በወቅቱ አንቀጹ ትዝ ባይለኝም ድሮ መፅሐፍ ቅዱስ ላይ ያነበብኩት አንድ ጥቅስ ትዝ አለኝ፡፡
‹‹አሁንም እኔ ብቻዬን እኔ እንደ ሆንሁ፥ ከእኔም በቀር አምላክ እንደሌለ እዩ፤ እኔ እገድላለሁ፥ አድንማለሁ፤ እኔ እመታለሁ፥ እፈውስማለሁ፤ ከእጄም የሚያድን የለም።›› ዘዳግም ምዕ.32፣ ቁ.39፡፡ እውነትም ይህን ጥቅስ ከማመን ውጪ ሌላ ሰውኛ ማብራሪያ ለመስጠት ከባድ ነውና
እኔም በፈጣሪ የማያልቅ ተዓምር ተደምሜአለሁ፡፡ እኔ በማምነው መንገድ በፈጣሪ ላይ ያለኝን እምነቴንም ይበልጥ አጠናክሮታል፡፡ አባዬ ብዙ ካለችኝ በኋላ ታሪኩን እያጠቃለለች ነው፡፡ ‹‹እናልህ በልዬ… እቤት ከመጣን በኋላ አቡሽዬ ሲደውል ነገርኩት፡፡ ‹አቡሽዬ… ይኸውልህ
በስተርጅና ሴት ልጅ ወለድኩ› አልኩትና ታሪኩን ስነግረው እጅግ ተደስቶ ለየዘመዱ እየደወለ ‹አባዬ ልጅ ወልዳለችና እንኳን ማርያም ማረሽ በሏት…› እያለ ሰዉን ሁሉ ግራ አጋባው፡፡ ወዲያውም የሚያስፈልጋትን በሙሉ እሱ እንደሚያሟላ እና የአባትነት ኃላፊነቱን እንደሚወስድ ቃል ገብቶ ይኸውልህ ሚጡም በሱ ስም ትጠራለች… እሷም አባትሽ ማነው ስትባል አቡሽ ትላለች…›› አለችና ተነስታ ከፎቶ ማህደሯ ውስጥ ከልጅነቷ ከምሮ ያስነሳቻትን ፎቶዎች አምጥታ ሰጠችኝ፡፡ እየተቻኮልን እና እየተቀማማን ተመለከትነው፡፡ ገና የወር ዕድሜ ሳይሆናት ጀምሮ በየጊዜው የተነሳቻቸው ፎቶዎች ልዩ ናቸው፡፡ የአንድ ዓመት እና የሁለት ዓመት ልደቷ ሲከበር ድል ያለ ድግስ እንደነበረው መመስከር ይቻላል፡፡ ሁለት ፎቶዎች ትርፍ ቅጂ ስለነበራቸው አባዬን ለምኜ ፈቀደችልኝና ወሰድኳቸው፡፡ ከሁሉም ግን የልደት ፎቶዎቿ ይለያሉ…‹‹ይገርማል፣ በተለይ ለልደቶቿ ትልቅ ድግስ ነው ያደረግሽላት አባዬ…›› አልኩ፡፡ ‹‹እኔ አይደለሁም በልዬ… የሚገርምህ ልጅቷ ከዚህ ሁሉ ታሪኳ ቀጥሎ የሚገርመኝ በብዙ ነገር ዕድለኛ ነች፡፡›› አለችና በሁለቱ ልደቶቿ ወቅት ድግሱ እንዴት ሊያምርላት እንደቻለ የተከሰቱትን ድንገቴዎች አወራችኝ፡፡ ‹‹ይኸው አሁን ደግሞ ሶስተኛ ዓመት ልደቷ መጪው ባለወልድ ነው ከ11 ቀናት በኋላ፡፡ ነገር ግን ሚሚ መጪው ማክሰኞ ወደ አዲስ አበባ ስለምትሄድ ልደቷን ቀድመን እናክብር ብለን ነገ ልናከብርላት ወስነን ነበር፡፡ እኔም ቤት ባፈራው የሆነውን አደርጋለሁ ብዬ እንጂ በግ አርዳለሁ ብዬ አላሰብኩም ነበር፡፡ ይኸው ዕድለኛ ነች ብዬህ አልነበር… አምላክ ደግሞ ምንም የማታውቀውን አንተን በግ አስገዝቶ ላከላት… ታዲያ ከዚህ በላይ ዕድለኝነት
አለ…? ኧረ የሷስ ድንቅ ነው በልዬ…›› አለች፡፡
እንዳለችውም እኔ እጅ መንሻ ብዬ የወሰድኩላቸው በግ በነጋታው ዕለተ እሁድ ታርዶ፣ የልደት ግብዓቶች ሁሉ ተሟልተው ትልቅ ድግስ ሆኖ የሚጡ 3ኛ ዓመት ልደት በድምቀት
ተከበረ፡፡ ድንቅ እኛም እሁድን አድረን ሰኞ ወደ አዲስ አበባ ተመለስን…! ማክሰኞ ማታም ይህንን ታሪክ ማካፈል ጀመርን…!እነሆ ዛሬ ዕለተ ረቡዕም ለመደምደም እየተንደረደርን ነው…!
***
መውጪያ…
(እስቲ ደግሞ ጥቂት አብረን እንናደድ) እብዷን የደፈራት ሰው በአደባባይ የሚታወቅ ጤነኛ ሰው ነው መባሉን ስሰማ በመጀመሪያ የተሰማኝ ስሜት "ምናለ ፈጣሪ ያን የሚደፍራትን ሰው እጅ ከፍንጅ ቢያሲይዘኝ…" የሚል ነበር፡፡
‹‹እንዴት ነው ግን ከዚያስ በኋላ አንድ ሰው እንኳን ወይም የከተማው አስተዳደር ራሱ በግድም ቢሆን ወስዶ የወሊድ መቆጣጠሪያ የማያስደርግላት…! አሁንስ ቢሆን ምንድን ነው ዋስትናዋ በድጋሜ እንደማይደፍሯት?›› ብዬ ፈርጠም ብዬ ጠይቄ ነበር፡፡ አሁንም ያቺ ደግ አክስቴ ያደረገችውን ነገረችኝ፡፡ ‹‹አይ በልዬ… እሱማ ከዚያ በኋላ እንደምንም ብዬ ይሄ ክንድ ላይ የሚቀበረውን የ4 ዓመት የወሊድ መከላከያ አስደርጌላት ነበር፡፡ የሆነ ቀን ራሷ ቆፍራ አወጣችውና ጣለችው፡፡ ይኸው ይግረምህና… አሁንም ነፍጠ-ጡር ነች… ፈጣሪ የስራውን ይስጠው እንዲህ ያደረጋትን እንጂ ምን ይባላል…›› ብላ በቁጭት ተነፈሰች፡፡ እብዷ አሁንም ሁለተኛ ነፍሰ-ጡር ነች፡፡ ይህንን ስሰማ እንዴት እንደነዘረኝ የማውቀው እኔ ነኝ፡፡

"ጨርሰናል"

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Tilahun abebe
እስስት : ስትጎተትና : ስትቀያየር እንደምትጠላ : አታውቅም : አካሄዷም : ቢሆን ፥ አይኗ : ልቧን : ይመራዋል : እንጅ ልቧ : አይኗን : እንደሚከተለው : አታውቅም.....
ግንኮ : አይን : ያየውን : ለልብ : ካልነገረው : ልብም : አድምጦ : ካላመነበት : አይንን : ይከተለዋልን?

መቼም አንዴ ለጉዞ ፈጥሮኛልና መንገድም : እወድ የለ .....
በጉም : ላይ : እየተረማመድኩ : ሳለ ብቻዬን : አግዜሩን : አግኝቸው : ነበር : በምናባዊ : ፀዳል እንደምናስበው : አደለም : ኮስማና ነው።

እናተ : ሰዎች: ለምን : ትጠሉኛላችሁ : ስለምንስ ከክብሬ : ቁልቁል : አፈረጣችሁኝ : ማቅለላችሁ : ሳይቀር : ለሌሎች : መሳለቂያ : አረጋችሁኝ ፥ ከዙፋኔ እያለሁ : እንደሌለሁ : አበሸቀጣችሁኝ ለምን? ስለምንስ? ተጠራጣሪ : ሆናችሁ : በኔ ለምን? እንባ እንቅ እንባ እንቅ ,,,,,
እያረገው : ሶስት : የእንባ : ዘለላ :ከገፁ ፥ ሲረግፍ እየሁ።

እንባው ፥ ወደስቅለቱ : ትዝታ : እያላጋ : ወሰደን በስቅለቴ : ግዜ አንድ : ደንባራ : ወታደር : በጦር ጎኔን ሲወጋኝ : ህመሙን : አታውቅም : ይሁዳ : በከንፈሮቹ ሀሞት : ተጎንጭቶ : ጉንጨ : ላይ : ሲተፋብኝ : የተሰማኝን : አታውቅም : ጴጥሮስ : ሶስት : ግዜ : አንድ ለአብ አንድ ለወልድ አንድ ለመንፈስቅዱስ ለያንዳንዳችን : በአንድነት : የክህደትን : ኮሶ : ሲያግተን : ምሬቱን : አታውቅም።

40 ቀን 40 ለሊት ስፆም ሰይጣን በእባብ ተመስሎ ሲፈትነኝ የፈጠርኩትን መልሶ የኔ ሊያረጋቸው ሲደራደረኝ ቤተ መቅደሴን ሲሻቀጡበት እናቴን ከቁሻሻ መሀል ትቢያ እንደተደፋ ልቅላቂ ሲጠየፏት አታውቅም።

አዎ አታውቅም ........ እናት ሰዎች ህመሙን አታውቁም .........

የእግዜር እንባ ግን ምን አይነት ነው?

እኔም: ሆድ : ብሶኝ : የልቤን : ዘረገፍኩለት :ጌትዬ : በሁለት : አለም : ሰካር : ውስጥ: አየዳገርኩ: ለምን ዝም አልከኝ? አንተኮ: ብትታመምም : አምላክ ነህ የአምላክነትህ : ባህርይ ረቂቅ : ነው ያስችልሀል::

ግን ለምን ፈጠርከኝ? ማጥ: ረመጥ : ውስጥ : ከተትከኝ? እውነት አውጣኝ : ብዬ : ስለምንህ: ሳትሰማኝ : ቀርተህ ነው?
የህይወትስ ጣዕሙ በምን ይለካል ? በድን : አካልን አሸክመኸኝ : ለአመመታት : መክረሜን ዘንግተኸው ነውን?

እኔ : የነካሁት : ሁሉ : ርኩሰትን : እንዲላበስ : ሁሌ እንድሸሸግ : የምታረገኝ : ራሴን : በራሴው እንደ እፉኝን : ስውጥ አላሳዝንህምን?

የእናትህስ : ህመም : አንተን : ብቻ : የሚቆረቁርህ ይመስልሀል?
እሷኮ : አምጣ : አልወለደችህም : ደም : አልፈሰሳትም
ምነው_ቸሩ _መድሀኔ_አለም : የኔዋ : እናት: ወዝ ወዘናዋን : አጠንፍፋ : ባማጠች : የህመሟን ሲቃ ባስረቀረቀች : አኔን : ወልዳ : እንኳ_ማርያም : ማረችሽ ቢሏት : አንተው : የማርካት መሰለህ? በድኩም : አካሏ : ተንፏቃ : አፈር : ልሳ : ብትለምንህ : መች ምሬሻለው : አልካትና? የማርያም ልጅ...!!

አንተ : ብትፆም :ባህሪህ : ቅዱስ : ነህና : ይፈቅድልሀል እኛስ :አንጀታችን :ሲታለብ :ቆርቆሮ :ቤታችን :ውስጥ : በችጋር : ስንለበለብ :ዞር ብለህ : አይተኸናል : እንዴ?
ቅፅበታዊ : ደስታን : አሳይተህ : ዛላቂያዊ : ህመምን ከልባችን : የቸነከርከው : እውነት : ከሳዶርና ፣ አላዶር የሚተናነሱ : ይመስልሃልን?

ተው : እንጅ : ቤዛ ከሉ መድሀኔ አለም..... ተው እንጅ የማርያም ልጅ!!

ተስፋዬን : በምኞት : ደግፌ : ብጓዝ :ባንተ : አይደል የጨነገፈው : ማያዬ :መመልከቻ : አድማሴን : ባገኛት
ባንተም : አይደል : ያጣኃት? እንደኩታ : አይሽሞንሙነህ : ያለበስከኝ : ይህን :ማንነት አንተም አደል : የፈጠርከው ? ይኸው : እሷም /ወደመሸሹ አጋደለች....
እስቲ : ልወቀው : ጥፋቴን :ለምን : ግራ አርገህ ፈጠርከኝ?
ምን ትለኝ ይሆን? ምንስ ምላሽ ይኖርህ?

ግን ለምን አትወስደኝም? ኖሬ : የህይወት : ጣዕሙንስ በምን :ምላሴ : ላጣጥመው? ምላሴን : ቆርጠህብኝ ......ሳላጣጥመው : ኮመጠጠኝ።

ተፈጥሮ : ፊቱን : አጨፍግጎብኝ : ሳለ : ከነፍሴ የተጣባች : እንስትን : ወዳንተ : ልካኝ : ነበር። አንተ የምድርና ፣ የሰማይ : ጌታ : ሆይ : ቸኮሌት : ላክልኝ ብልሀለች።

ከጥሪው : መዝብ : ሳሟ :ሳይሰፍር : ወደኔ መታ የነበረችው : ማያዬን አወካት?

ለነገሩ : አንተ : ብታቅም : አላቅም :ከማለት : ወደኃላ አትልም...... ብቻ እሷ ታቅሀለች።

በቃና : ዘገሊላ :ግዜ : ውሀውን : ወይን : ጠጅ : አድገህ : ነበር : በሰው : ሰርግ : እንደዚ : የሆክ : በራህ : ሰርግ : እንዴት: ትሆን?
በስቅለትህ : ወቅት : ጎንህን : ሲወጉህ : ውሀ፣ ደም፣ ወተት : ፈሶህ ነበር ።

በመጀመሪያ :ቀን : ማያዬን : ሳገኛት : ውሀ ጠጥታ ነበር ።
በሁለተኛው : ቀን : ስንገናኝ : በተፈጥሮ : ደም እየፈሰሳት :ነበረ ።
በሶስተኛ : ቀን : ፈጣሪ : ቸኮሌት : በኔ : በኩል እንዲልክላት : ጠይቃኝ ነበር።

በቸኮሌት: ውስጥ : ወተቱን : ለማግኘት :ፈልጋለው ይሆናላ....


ቸኮሌቷን : አንድቀን : ይዤላት: እንምመጣ :ታውቅ ይሆን?

አታውመቅም.........

የእግዚአብሄርን : ልጅ : ሰርግ : አይቼ : ከድግሱ : በልቼ ጠጥቼ : መሞቴን : እንኳን : አታውቅም..........


አዎ አታውቅመም.....

አደራ
**ንገሩልኝ******

ሱራፌል ጌትነት (ሱራ ቢራቢሮ)

የግማሽ አለም ጣኦት

@wegoch
@wegoch
@wegoch
የተለየ ፍቅር አለ. በቃ ልዩ!... ይህ ፍቅር ሚመጣው ተስፋ ቆርጠህ ባለፈው ፍቅርህ ተደቁሰህ ሁለተኛ ላለመደቆስ ወስነህ ጥግህን ከያዝክ ቦሀላ ነው. መጀመርያ ቦታ አትሰጠውም ቀልድ ታደርገዋለህ ምክንያቱም ከጨዋታው ራስህን አግልለሀላ! ሲቀጥል እስቲ ልየው ብለህ በሶምሶማ የኧሯሯጥ ስልት ታስቀጥለዋለህ... መሀል ላይ የትላንት ቁ ስልህ ትዝ ይልህና ሶምሶማውን ወደ እርምጃ ትቀይረዋለህ. ውስጥህ ግን ይረበሻል.. እኔ ላይ ሆኖ የነበረውን እዚ ሰው ላይ እንደገምኩት ይሆንን? ብለህ... ከዛ ግን ህሊናህን አፍነህ ገድለህ ትረጋጋለህ. ያሰው ግን ሳይቀየር አንድ ቀለም ሆኖ ይቀጥላል. ወጣ ብለህ ትርዒቱን ስታይ እስስቱ ራስህ ሆነህ ታገኘዋለህ. ያሰው አሁንም ላንተ ደስታ ደፋ ቀና ይላል. እያስመሰለ ይሆንን? ደፍሬ ብገባ እጋጋጥ ይሆን? ወይስ ይህ ሰው የተሻለ ነው? እድል ልስጠው ይሆን እንዴ? ብለህ ብዙ ታወራርዳለህ? የዶ/ር እዮብ "የፍቅር ህይወት" ከሚለው መፅሀፍ ላይ ባገኘኸው መለኪያ ሁሉ ትለካዋለህ ከዛ ይመዝንብሀል.... "አይ ይሄ ነገር ይቅርብኝ" ብለህ ለደመነፍስህ እንዲወስን መሪውን ታቀብለዋለህ. ... ሁሉንም መንገድ መዝጋት ትጀምረህ... ትረሳዋልህ ሁላ... ማስተካከል የማይስማማው ጠማማ ትሆናለህ... ከብረት የጠነከረ ልብ ይኖርሀል... ያሰው ይጎዳል ስንት ለሊት ስንት ቀን ያነባል... በስተመጨረሻ "እያለቀስኩማ አልኖርም!" ብሎ የመንገዱን አቅጣጫ ይቀይራል. ድሮ ሲያደርግ የነበረውን ተቃራኒ እያቃረውም ቢሆን ያደርጋል.... ይሄኔ ነው ብረቱ ልብህ ወደ ቄጤማነት ሚለወጠው.... እሱ ያሳለፋት እያንዳንዷ ነገር በአስር ተባዝታ ትሰማሀለች.. የድሮ ህግህን ብትጠቀምም አይሰራልህ...... ተሸንፈሀላ! የድሮ ቁስልህ እንደገና ለመቁሰል ሙሉበሙሉ ይስማማል! ህመምህን ትወደዋለህ! በእብርክክህ እየዳኽክ የገፋኸውን ሰው ትፈልገዋለህ.... ልክ እንደ 'ህል ውሀ. አማራጭ የለህም ሄደህ ትናዘዛለህ! አበቃ! ያም ሰው አይጨክንም. "ለመቅረብ መራቅ!" ሚለን ህግ ተጠቅሞ ኖሮ ያንተን መመለስ ነበር ሚጠብቀማው ፈገግታውን እፊቱ ላይ ፍቅሩን እልቡ ላይ እንደእንጀራ አስፍቶ ይጠብቅሀል. አሁንማ ማን ይቻላቹ! አንድ ላይ ተበርራላቹ.....

ልዩ ፍቅር አለ ያላሰብከው ግዜ የሚመጣ... ህይወትህን ከስር መሰረቱ ጀምሮ በማር ሚለውስ ... ያለፈው ህይወቴ እንዴት እሬት ነበር ብልህ እንድትገረም የሚያደርግህ.... ግን ሳታስበው ሳትዘጋጅ እንዲው ስሜትህ ውርድ ባለበት ሰአት ይከሰትና ዋጋ ያስከፍልሀል.

#በMaggie
@getem
@getem
@paappii
ሻንጣው!
ድሮ አስረኛ ክፍል ተማሪ ሳለን ነፍሰ ቀጭኑ ኬሚስትሪ መምህራችን እንዲህ ሲሉ ጠየቁን ።
“ውሀ ከምን እና ከምን ንጥረ ነገሮች ነው የተፈጠረው ?”
ብዙ ተማሪዎች ይህችን ቀላል ጥያቄ ለመመለስ ተቅለበለብን ። መምህሩ ግን ከሁሉም ተማሪ ይልቅ
ትኩረታቸውን ስንሻው ላይ አድርገው እንዲመልስ አስገደዱት ።
ስንሻው ከእንቅልፉ የተነሳ ይመስል አይኑን አሻሽቶ ትንሽ ቆየና መምህሩ ጥያቄውን እንዲደግሙለት
ጠየቃቸው። /በነገራችን ላይ የስንሻው አባት ልጃቸው ትምህርት እንዳይገባው ተደግሞበታል ብለው
ስለሚያስቡ እሱን ይዘው ያልተንከራተቱበት ፀበል አልነበረም ። ኋላ ላይ ቢታክታቸው ጊዜ እርግፍ
አድርገው ተውት ! እርሱም ትምህርት አይንህን ላፈር ብሎ ማንበብ እና ማጥናቱን እርግፍ አድርጎ ተወው
/
"እኛ የምን ጠጣው ውሀ ከምንና ከምን ውህደት ተፈጠረ ? " ብለው ጥያቄውን ደገሙለት ።
ውሀ ልማት እና ቀበሌ ተዋህደው በገጠሙት የቧንቧ መስመር ነው የተፈጠረው ! ብሎ ሲመልስ ያልደነገጠ
ተማሪ አልነበረም ። ሁላችንም እያሾፈ ነው ብለን በትኩረት አየነው ።
እሱ እቴ !
ልቡ ደጭ እንኳ አላለም ! ሰው እንዴት ይሄን የሚያክል ተራራ ስህተት ሰርቶ ትንሽ ሀፍረት እንኳ
አይሸብበውም ?
“ስ ! ውይ ይቅርታ” አለን መልሶ .... በቃ ኦክሲጂንና ሀይድሮጂን ታውሰውት ነው ማለት ነው ብለን
ማስተካከያውን በጉጉት መጠባበቅ ያዝን ! ስንሻው እጅ አውጥቶ መልሶ ፣ የተሳሳተውን አውቆ ትክክለኛ
መልስ ከመለሰ ዘጠነኛው ሺህ አልፎ አስራ ዘጠነኛው ሺህ ገብቷል ማለት ነው በቃ !
ስንሻው ጉጉታችን ላይ በረዶውን ሊከለብስ
“ውሀ ልማት እና ሰሜን ሸዋ ዞን በመተባበር ነው 🙂“ ብሎ እርፍ አለው ።
ነፍሰ ቀጭኑ መምህራችን በንዴት ተነፋፍተው ነብር አከሉ ! አለ አይደል የቤት ውስጥ ድመት ስትቆጣ
እንዴት ነው ኩፍ የምትለው ?
መምህራችን ኩፍ አሉ ።
በስመአብ !
አስተማሪ ሲናደድ ለካ እንደዚህ ያስፈራል ?ከአስተማሪም ሁሉ ደግሞ ኬሚስትሪ አስተማሪ ሲናደድ በጣም ያስፈራል ። የሆነ ሰልፈሪክ አሲድ
ከላብራቶሪ አንስተው ፊቱ ላይ የሚከለብሱበት ሁሉ መሰለን ። የስንሻውና መምህራችህ መጨረሻ
የተዘጋው ዶሴ ሊሆን ነው ስንል ሰጋን !
“ተነስ !”
ስንሻው ተነሳ ። ደግሞ አነሳሱ እኮ እንደ ንጉስ ክቡር ዘበኛ ቀብረር ኮራ ብሎ ነው ። ግዳይ የጣለ ጀግና
የነብር ቆዳ ለብሶ ቢመጣ እንኳ መቼ ይሄን ያህል ይጀነናል ? ጅ ንን ን ን ቅብርርርርርርርርርርርር
ከሴሽን አንደኛ የሚወጣው ፍቅሩ የሚባለው ቸካይ ተማሪ እንኳ መምህር ሲያስነሳው አንገቱን ሰበር
ያደርጋል እኮ !
ስንሻው ተንጠራራ ........ ደረቱን ነፋ !
“እነ ሚካኤል ፣ እነ እዮብ እነ አቤል ኢንጅነር ወይ ዶክተር ሲሆኑ ሻንጣ ተሸካሚያቸው እንደምትሆን
አልጠራጠርም “ ብለው ሞራሉ ላይ ቀዝቃዛ ውሀቸውን ከለበሱበት ። በቃ ስንሻው ሊተነፍስ ነው አልን !
ደግሞ እኮ እንደፈራነው ከወራት በኋላ ስንሻው ማትሪክን ወደቀ ። እኛ ፈተናውን በጥሰን አለፍን ።
እኛ አስራ ሁለተኛ ክፍል አልፈን ለዩንቨርሲቲ ስንዘጋጅ ስንሻው የሆነ ትምህርት እንደከረሜላ አሽጎ የሚሸጥ
ኮሌጅ ዲፕሎማ መማር እንደጀመረ ሰማን ። አውቶቡስ ተራ አለመሄዱም የመምህሩ ትንቢት እውን
እንዳይሆን ስለሰጋ እንጂ የሱ መጨረሻ ከወያላነት ይዘላል ብሎ ማን ያስብ ነበር ?
ግቢ ሁለተኛ ዓመት ተማሪ ስንሆን ስንሻው ቀበሌ ስራ አጊንቶ መግባቱ ተነገረን ። ያኔ በሱ ሙድ ያልያዘ
አልነበረም ።
እንደውም አንድ ቀን ፍቅሩ የሚባለውቸካይ የነበረ ተማሪ ወደኔ ጠጋ ብሎ "ስንሻው በዚህ ከመሬት አልፎ
ማርስ የምትባል ፕላኔት ላይ እንኳ በማይገኝ ድድብናው ቀበሌ ስራ ማግኘቱም ተመስገን ነው ብሎ
ገለፈጠ ። "ስንሻው እኮ ቀን ስራ እንኳ ይበዛበታል ። እንደ ህንዶች ሰባቴ ቢፈጠር ሰባት ጊዜም ትምህርት
አይገባውም" አለኝ ቀጥሎ ።
ሁላችንም ጎበዝ ተብዬ ተማሪዎች ስንመረቅ ግን የነፍሰ ቀጭኑ ሰውዬ እርግማን ለስንሻው ምርቃት ሆኖ
እርፍ አለው ።
የከተማችን አስተዳደር ተመራቂ ተማሪዎች ተደራጅታችሁ ኮብልስቶን አንጥፉ ምናምን ብሎ በስብሰባ
ሰበብ ሲጀናጀነን ስንሻው ተከብሮ የከተማችን ከንቲባ ሆኖ ነበር ።
ጭራሽ እዛ አመዳችን ቡን ባለ ተመራቂ ተማሪዎች ፊት ቀርቦ ስለ ስራ ፈጠራ ሰፊ ማብራሪያ ሰጠን ።
አቤት የምላሱ ፍጥነት ! አቤት የቃላት ክሸናው ! አቤት የንግግሩ ስድርነት !መጥበሻ ሆኖ የተማሪውን ልብ አቀለጠው ። ከኔ ጎን ተቀምጣ የነበረችው ፀሀይ የምትባል ጓደኛችን
ዛሬውኑ ጀበና እና ስኒ ገዝቼ ስራ ካልጀመርኩ በሚል ሀሳብ ጦዛ ብንንን ብላ ጠፋች🤣
“ ኢንጅነር ነን ዶክተር ነን ብላችሁ አትኮፈሱ የጀበና ቡና ብታፈሉ ትችላላችሁ ። ለምሳሌ ሚካኤል እዮብ
አቤል በኢንጅነሪንግ እና ዶክትሬት ተመርቃችሁ ሰፈር ለሰፈር ከምታውደለድሉ የጀበና ቡና ብታፈሉ ምን
ችግር አለው ? ብሎ በምሳሌነት ጠቀሰን ። እኔ እንዳስተማረን ሳይሆን እንደ ሰደበን ቆጥሬው እሳት
እንደነካው ላስቲክ ተኮራመትሁኝ ።
አቤል ፣ እዮብ ፣ ሚኪ ምንም ጎበዝ ተማሪ ሆናችሁ ስታስጨንቁን ብትኖሩም አሁን ግን መጨረሻችሁ
እጣን እያጫጫሱ ሀላፊ አግዳሚውን መካደም ነው ማለቱም አይደለ ?
እዮቤ ጓደኛችን ፊቱ በርበሬ ሆኖ ቀላ !
አይ መንግስት የስራህን ይስጥህ ፤ አንድ የተከበርኩ ዶክተርን ለመንደር ስኩፒኒ አሳልፈህ ትሰጠኝ ? ብሎ
ክፉኛ ቆዘመ !
እኔም አነጋገሩ ትንሽ ሸንቆጥ ስላደረገኝ ከስብሰባው በሁላ ስንሻውን ለማናገር ከተቀመጥሁበት ተነስቼ
ተራመድኩኝ ።
ዛሬ ምንም ጉድ ይለይለታል !
በዛ ቢባል ከንቲባውን ገላመጥክ ተብዬ ብታሰርም አይደል ? የልጅነት ጓደኛዬ ስለሆነ ትንሽ ራሮት
ተሰምቶት ከሳምንት በኋላ ራሱም ሊያስፈታኝ ይችላል የሚል ድፍረት አደረብኝ ። ጀርባውን ተከትዬ
ተጠጋሁት ። በሰዓቱ ከየት መጣ ያልተባለ ጠባቂው በመዳፉ ጭብጦ አሽቀነጠረኝ ።
የጠባቂው መዳፍ ጎትቶ እዛው የተመረቅሁበት የዩንቨርስቲ ግቢ ሊዶለኝ ምን ቀረው ?
ቀና ብዬ አየሁት !
“ምን አጠፋሁ አለቃ?”
ፈርጣማው ጠባቂ በቁጣ ቱግ ብሎ እንዲህ አለኝ
“አንተ ምን አይነት ደፋር ነህ ባክህ ? ክቡር ከንቲባችንን ለመቅረብ አይደለም ሻንጣቸውን ለመሸከም
ብትመጣ እንኳ ማስፈቀድ ነበረብህ “
#ሚካኤል አስጨናቂ

@wegoch
@wegoch
@paappii
[ፀሃይ፣ ዝናብ፣ ክረምት፣ ጷግሜ፣ ልብ፣ አዕምሮ እና አግዳሚ ወንበር ]

ሁሉ በትውልዱ በዘመኑ ከግብሩ የሚስማማ ስም ቢሰጠው የኔና አብሮአደጎቼ ስም "አንጋጣጭ" ይሆን ነበር። በመስከረም ብራ ሰማይ ላይ በምሽት የፈሰሱ ከዋክብት ተኮልኩለን የሞቅን ነን። ብሩህ አይኖቻችን ዘበን ተሻግረውም በብዙ ማየት ያመጣው ሞራ
ሊጋርዳቸው ያልደፈረው በነዚያ ቀናት አሻቅበን ያየናቸው የክዋክብቱ ብሩህ ጨረርሮች ለብሌኖቻችን ዘብ ቆመው ነው። ልኬቱን እና ስፋቱን የማናውቀውን ጠፈር የኮከብ ስብስቦች አቀማመጥ በምናውቀው ሰፈራችን ልክ ሰፍረን የጅራታም ድመት ቅርፅ ይዘው የተሰደሩ ክዋክብት መጠን "ከዘይነብ ሱቅ እስከ ጊዮርጊስ መሳለሚያ ይሆናል።" እንላለን። እኔና አብሮ አደጎቼ አንጋጠን ያየናቸው ከዋክብት ተባብረው ያበጇትን ባለ ጅራት ድመት በምናብ ምድር አውርደን ከዘይነባ ሱቅ እስከ ጊዮርጊስ መሳለሚያ ቦታ ስናስይዛት ግርምት እንደ ጣፋጭ አውጥ ፍሬ በትንሽ አፋችን ወስጥ ወደ ነፍሳችን እየሰረገ "ወይኔ ትልቅ ናት በጣምም" እያልን ....የርቀቱ ስሌት ባይገባንም ፊልም ላይ የምናያቸው የፈረንጅ ልጆች መሸት ሲል በየጣራቸው ወጥተው ሌንሱን ስበው ሰማይ ከሚያስሱበት ቴሌስኮፕ አይኖቻችን የተሻለ እይታ ነበራቸው። ከማንጋጠጣችን ብዛት ከክዋክብቱ ጋር ትውውቅ ያለንና ትልቋን ኮከብ ፀሃይን ሰርክ እለት አጅበን ለመሸኘት የተቀባን ነበርን። ከቅዱሳን ታሪክና ገድሎች ውስጥ ሁሌ የሚደንቀኝ ደመናን እንደ ራይድ ታክሲ ጠርተው እዛ ሃጫ በረዶ የጥጥ ባዘቶ መሳይ ነገር ላይ ተደላድለው ከአንዱ ሃገር ወደ አንዱ ሃገር
የሚጓጓዙት ነገር ነው። የልጅነት ቀናት ከስአቶቻችን እንደዘንድሮው ፀሃይ ያልጠነከረችባቸው ነበሩ። የደጋ ሃገር ከሰአት ነፋስ በአንቀልባ የሚያባብለን አይነት ነን፤ፉጨቱ መሃልም እሹሩሩ አይጠፋም። ዛፎች እርሱን ተከትለው ጎንበስ ቀና ይላሉ። ብሩህ ሰማይ ላይ ነጭ ዳመናት ቅርፃቸውን እየቀያየሩ ያልፋሉ። ተፈጥሮ ከሁሉ የሚልቅ የራሷ ኪን አላት። ብዙዎቻችን በልጅነታችን ካሜራ እንዲኖረን እንመኝ የነበረው የደመናትን ቅርፅ እና ሰማይን ፎቶ ለማንሳት ነው። ከረብሻችን ፋታ ካገኘንባቸው የትምህርት ቀናት መካከል "በወንዝ መሃል የበቀለ ዛፍ ለምን ያ ሁሉ ውሃ ከብቦት ይደርቃል?" ብለን ብንብሰለሰልም ልጅነት ደጉ ስለመዓድናት እናውቅ ዘንድ ስላልፈቀደልን መልስ የለንም ነበር። ስለ ትነት እና ደመና የተማርን ቀን ያሉንን ሁሉ የማንቀበል ነበር እና መምህሩ ያሉን ላይ የራሳችንን እምነት ጨምረን "የወንዝ ውሃ
እፀዋትን ለማለምለም አልተባረከም ተንኖ ደመና ሆኖ እግዜር ዙፋን ስር ደርሶ ሲመጣ ዝናብ ሆኖ ተርከፍክፎ ምድራቱን ያለመልማል" ብለን አመንን። ጥርጣሪያችንን ሲያበረታ የሰው ልጅ ያን የበረከት ወቅት ክረምት እያለ ሲጠራው ሰማን። ክረምት የሰማይና ምድር ፍቅር ሲጦፍ መሬት ከእቶን ከሙቀቷ አገግማ፤ ለአዲስ ተስፋ
ለአዲስ አመት ተሰናድታ ራሷን አጥባ ደማቅ አረንጓዴ ፀአደ ቢጫ ተጎናፅፋ ለመስከረም ልትዳር ጷግሜ ላይ ስትሽሞነሞን እማኝ ሆነናል።
እያልን እያወደስናት"ጷግሜ አንቺን መሆን መታደል ነው፤ ትንሽ ሆኖ ብርቅ መሆንን ማን
ታደለ ከአንቺ ሌላ? በሩፋኤል ጠበል ታጅቦ ፍጥረት የሚፈነጭበት ማን ወር አለ ከአንቻ
ሌላ ? ጷግሜ የወር ቅመም በአምስት ቀናት ብዙ ግብር እልፍ ተግባር ምትሸክፊ ፣ለወቅቶቹ መሻገሪያ አንቺ...የአሮጌ አመት መደምደሚያ አንቺ.... ለአዲስ ዘመን ዋዜማ አንቺ የአዲስ ተስፋ መባቻ አንቺ ...ይሄን ሁሉ በጨቅላ እድሜ ማን ታደለ ካንቺ ሌላ" እየዘከርን ጷግሚትን....ህይወት አልፎ ሂያጁ ሁሉ ለተወሰነ ቆይታ አረፍ የሚልባት የመንገድ ዳር ወንበር ናት። በዚያም በጎዳናው የሚያዘግሙ ሁነቶች፣ የሚያልፉ ወቅታትን፤ የእይታችን አድማስ እስከ ቻለ ድረስ ማየት የቻልነውን ተፈጥሮ ሁሉ የምናይበት .....ወደ ጥንቱ ዞር ብለን ልጅነትን ጉርምስናን በስስት የምንቃኝበት ። ልጅነታችን እንደ ታላቁ ተቀማጭ መዝገቡ ዱባለ ትዝብትና ማሰላሰል የሞላው ባይሆንም እሳቢያችን ወሰን አልባ፤ ህልሞቻችን ክንፋም ነበሩና ካለ ከልካይ በነፃ ምናብ እና ሃሳብ ያለፍነው ያ ዘመን አካል ቢሆን ባለ ነጭ አዕምሮው ልጅነት ካለ አእምሮ የሚመስለው የለም። ወጣትነት እንዳያልቅ እየሰሰቱት እንዳይጠፋ የሚለኩሱት፤ ሊያነዱትም ሊያጠፉትም የሚያሳስብ ሻማ ነውና ስለ ተሰጡን ስለሰጠናቸው ስለ ሰበሩን ስለሰበርናቸው ልቦች ብለን ይህ ዘመን አካል ቢሆን ልብ እንለው ነበር። እና እኔና አብሮአደግቼ በያለንበት ዛሬም ጀንበር ለመሸኘት አመሻሽ ደጃፋችን ላይ ስንሰየም በለሆሰስ እንዲህ የምንል ይመስለኛል "እንደ ፀሃይ፣ እንደ ዝናብ፣እንደ ክረምት፣ እንደ ጷግሜ፣ እንደ ወንበር፣ እንደ አዕምሮ፣ እንደ ልብ ያለ የህይወት ንጥረ ነገር ምን አለ?? መኖር ግን እንዴት ነው የሚያምረው ?!"

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Elsa mulugeta
የሞባይል ስልኬ አቃጨለች። አዲስ ቁጥር ነው። አንስቼ ማዋራት ጀመርኩ ...
"ሄሎ ሚኪያስ"
"አቤት "
"አይናለም ነኝ " ...
"አይናለም....አይናለም....ይቅርታ እናት አላወኩሽም...."
"ምነው ከዛሬ ሶስት ዓመት በፊት ጋሽ ክንዱ ሽንሽን ግዛላት ያሉህ ...ልጅ "
ስ....ስ....ስ! የሶስት ዓመት ትዝታዬ ሰተት ብሎ ከአዕምሮዬ ጓዳ ተሰነቀረ!!
ድሮ ልበል እንጂ.. .
ያው ድሮ አንድ ሽማግሌ አከራይ ነበሩኝ። የጠዋቷ ጀንበር ከረር ከማለቷ በፊት በረንዳቸው ላይ ካለች ብርኩማ ዘንድ ተቀምጠው መዝሙረ ዳዊት ያነባንባሉ ። አይናቸው ግን ፈፅሞ የፀሎት መፅሀፉ ላይ አርፈው አይቆዩም። ሀላፊ አግዳሚው ላይ እንከን ማውጣት አይሰለቻቸውም። እንኳን ተከራዮቻቸው ስናልፍ አይደለም የበረንዳው መደገፊያ ላይ ያረፈች ቢንቢን ብብትሽን ታጠቢ ለማለት ሁሉ ይዳዳሉ 😃
ታድያ እኔም ስለሚደብሩኝ ብዙ ጊዜ ከአንጀት ያልሆነ ሰላምታ ወርውሬላቸው ቶሎ ከስራቸው አልፋለሁ።
ሚ......ኪ........ያ......ስ.. .... ምናምን የሚል ድምፀታቸው የሚሰማኝ ከርቀት ነው።
አንድ ቀን ግን አይኔን የማያጠራጥር ቅፅበት ላይ ጉድ አየሁ !
አይ ...አይ ! ያው ወጣት ስለሆንኩ መስሎኝ ነው ብዬ አለፍኩት ያን ቀን።
የዛን ቀን ክስተት ግን ተደግሞ አይኔ ድርጊቱ ላይ ሲጋጭ ሰልስትም አልፈጀ ። የቤት ሰራተኛቸው ን መቀመጫ በከዘራቸው ሲጎሽሙት እጅ ከፉ ያዝኳቸው :)
ሼባው ትንሽ ደንገጥ ብለው.. .
አይናለም ምናለ ይሄን ቀሚስሽን በውሀ ነገር ብታለቀልቂው? አሏት። (በሳቸው ቤት ማስቀየሳቸው ነው። የውቤ በረሀ አራዶች ባንሆንም የውቤ ግሮሰሪ አራዳ መሆናችንን ማን በነገራቸው !)
ጋሼ ቀጠሉ...
"አባይ የኛ.. .ተከዜ የኛ...ይሄ ማነው...እ...እህ ! (ትንሽ እንደ ሳይንቲስት ሌባ ጣታቸውን ግንባራቸው ላይ አኑረው ተብሰለሰሉና ደግሞ ...) አዎ ! ...ዠማ ወንዝም የኛ አይደል ? ...ቀሚስሽን እጠቢ..."
ይሁና አለች ጥልያን.. .ለዛን ቀንም ባልገባው አለፍኳቸው።
ሶስተኛ ጊዜ ይሄ ክፉ እግሬ ክፉ አጋጣሚ ላይ ሲጥለኝ ደግሞ ቤት ኪራይ ለመክፈል በራቸው ድረስ መሄድ !
ጋሼ ለአይናለም ጎንጎ ጫማ ገዝተው እሳቸው ተንበርክከው ሮማንቲክ እየሰሩ ሲያጠልቁላት.. .አየሁ። ቀና ብለው ደግሞ ከንፈርሽን ታልጎረስኩት ብለው ተገለገሉ። አይናለም ገፈተረቻቸው... አሸዋ ላይ እንደቆመ ጎጆ ቤት በጀርባቸው ተገነደሱ ። ድሮንስ መጥሀፉም ቢሆን ሀጥያተኛ አሸዋ ላይ የቆመ ዳስ ነው ይል የለምን ? ግንድስ!
አቤት የሽማግሌ ቅሌታም!
በጀርባቸው ከተንጋለሉበት እጄን ዘርግቼ አነሳኋቸው... ይሄን ያደረኩት ለጋሼ ውለታ አይደለም...ገበናቸውን ስላየው ቢያንስ በይሉኝታ የአንድ ወር የቤት ኪራይ ይተውልኛል ብዬ አስቤ ነበር። ደግሞ መተውም አለባቸው እንጂ!
አያድርገውና ይሄን ክስተት አይቼ ለባለቤታቸው እትዬ ፋንቱ ባቃጥርስ ?...አዎ መብቴ ነበር !
ጋሼ ለአይናለም ጎንጎ ጫማ ገዝተው እግሯን እያሻሹ አጠለቁላት ማለት ብቻ ነበር የሚጠበቅብኝ....እትዬ በዛ እንደ ኢትዮጵያ መከራ በገዘፈ ጀበናቸው ጋሼን ያጠልቁላቸው ነበር።/አናታቸው ላይ ፍርክስ/ :)
ጋሼ "ተባረክ...ይህች አይናለም እኮ መሬቱን አለቅጥ በላርጎ እያጠበችው አዳልጦ ጣለኝ" አሉኝ። እኔ ንግግራቸውን እንዲህ ተረጎምኩት ...አይናለም የረጨችው የውቦት ፆር አይኔን ጠንቁሎት ኑሮ ከንፈሯን ክፉኛ ተጎመዠው ። እርሱን አጉርሺኝ ሰላት እሷ ግን እንደ ቅሪላ ለግታ ቅሌት አጎረሰችኝ ! እንዳሉ ቆጠርኩት።
አይናለም አንገቷን ሰብራ ስራችን ቆማለች።
ጋሼ ከምስጋናው ለጥቀው ብሩን ተቀበሉኝ። ምንም ሼም የሚባል ነገር የለም።
ጭራሽ የሰፈሩን ዘጠኝ ህፃናት ጭርት ሊያሲዝ የሚችል ምራቅ የቀኝ እጅ ጣታቸው ላይ ለድፈው ገንዘቡን አበጥረው ቆጠሩት ።
"ስማ! "
"እኔን ነው ጋሼ ?"
"እህሳ እዚህ ተጎንህ የቆመ መንፈስ አለ ?"
"አቤት ጋሼ "
"እየው ኑሮ እሳት ሆኗል ልጄ። እንደው ለሙከራ ሊጥ አዘጋጅተህ ገበያ ደረስ ብለህ ብትመጣ በኑሮ እሳት ተለብልቦ ሊጡ ዳቦ ይሆናል።"
"እውነት? "
"ገብሬልን ልጄ! ... እንደውም የዳቦው ገፅ እንደ ጋናዊ ከንፈር ም ሊጠቁር ይችላል"
"ይሁና! "
"አይ ምን ይሁና ነው ? ቤት ኪራይ ጨምር !"
ጭራሽ የጋሼን ገበና በሸሸግሁ ቤት ኪራይ ጨምር ?
"ጋሼ "
"አቤት ልጄ "
"እትዬ የሉም ?"
"ምነው ለምን ፈለካት ?"
"ጎንጎ ጫማ ለአይናለም እርሶ ስለገዙላት እሳቸው ደግሞ ሽንሽን ቀሚስ እንዲገዙላት ልንገራቸው ብዬ ነው"
ጋሼ ቆሌያቸው ሲገፈፍ ይታወቀኛል።
ቅዱስ ገብርኤል መብረቁን የሰደደ መሰላቸው።
ሳቁ....ሳቃቸው የውሸት ነው።
"ቂ......ቂ..... ቂ ....
አይ ልጄ ጎበዝ ተጫዋች እኮ ነህ። ደግሞ ቅን አሳቢ ነህ እሙት! ..."
"አይደል ?"
"ገብሬልን ስልህ! " ጋሼ ቀጠሉ ...
"ግን ያው ከአንድ ቤት ሁለት ወጭ ከሚወጣ ያሁኗን የቤት ኪራይ ልመልስህና ባይሆን ሽንሽኑን አንተ ግዛላት! "
ገንዘቤ ተመለሰ። ነቄ ለነቄ እንጠጣ አረቄ ።
"ውይ አስታወስኩሽ አይንዬ !"
"ምነው ሚኪያሴ ሽንሽኔን ሳትገዛ ሰፈር ቀየርክሳ ? የሰው አደራ ውጦ ዝም ግን አያስተዛዝብም 😃

@getem
@getem
@paappii
#ሚካኤል አስጨናቂ
አምስተኛ ክፍል ተማሪዎች ሳለን አንድ ተዓምር ክፍላችን ውስጥ ተፈጠረ። መነሻው ከየት እንደሆነ ያልታወቀ ሰላቢ አጠሬራ ለኤደን ደረሳት ። ኤደን እናቷ እንደሞተችባት ነገር ስቅስቅ ብላ አለቀሰች። ሰለስቱ ያልወጣ ትኩስ ለቅሶ ።
የለቅሶው ምንጭ የሆነ ሰይጣን ፈልፈላ I love you የሚል ፅሁፍ ፅፎ በእረፍት ሰዓት ደብተሯ ማህፀን ውስጥ በመሸጎጡ ነው😊
መቀመጫውን በቅጡ ካልጠረገ...ጡት ከጣለ ሰባት ዓመታት ካልቆጠረ ፈላ I love you የሚል ፅሁፍ ጡት እንኳ በቅጡ ላላጎጠጎጠች ሴት ሲላክ አይከብድም ወይ?
ከሁላችንም በእድሜ ከፍ የሚለው ነፍሰ ቀጭኑ አለቃችን ማሙሽ እንደ ሀይለስላሴ አንበሳ አጓራ!
በቃ የዛ ክፍል ወንዶች አለቀልን !
አንዲት ሰላቢ የኤደን ጓደኛ ደግሞ እጅግ አስደንጋጭ ሀሳብ አፈለቀች ።
ያቺ ልጅ ጁንታ ናት !
የሁሉም የዚህ ክፍል ወንዶች እጅ ፅሁፍ ይፈተሸ ተባለ። እኔን ጨምሮ የብዙ ወንዶች ልብ አታሞዋን ደለቀች። ልቤ ጎንደር መሸታ ቤት ገባች። ድም.. ..ድም.. .ድው.. .ድው.. .ድብልቅ!
የኋላ ወንበር የሚቀመጠው አቡላ ፅሁፉን ፅፎ እንዲያሳይ በጓድ ማሙሽ ተፈረደበት ።
I love you ብሎ ፃፈ። የእናቱ አጋዥ መልዓክ ቅዱስ ገብርኤል ከጉድ አወጣው ።
አለቃችን ለጥቆ ወደ እስጢፎ ቀጠለ።
እስጢፎ ገና ትምህርት በተጀመረ ሁለተኛው ክፍለ ጊዜ የጮርናቄ ሽታ የሚያስመንነው ወመኔ ነው። የብርሀኑ ይሁን የጨለማው ጌታ ከመዓት አወጣው።
ወደ ቦጌ ተቀጠለ።
ቦጌ እናቱ ጠላ ለመጥመቅ የሚያዘጋጁትን ቀለጦ ድምጥማጡን በማውጣት ፈላው ሁሉ ያደነቀው ጉደኛ ልጅ ነው። እንዴት እንዳለፈ እንጃ! ብቻ እሱም አይደለም ተባለ ።
ቀጣዩ እርምጃ ወደ ቸካዩ ተማሪ እዮቤ ቀጠለ ። እዮቤ እንዴት በዚህ ተልካሻ ነገር እጠረጠራለሁ ብሎ ትንሽ ከተነፋረቀ በኋላ I love you ብሎ ጣፈ ። ፅሁፉን ትኩር ብሎ ማሙሽ ካየ በኋላ ይቅርታ ጠየቀው። ከእዮቤ በፊት የፃፈ ጀማ ማንም ይቅርታ ግን አልተባለም።
ማሙሽ የኪዳነምህረት አገልጋይ የነበረው ዳንኤልን ባላየ ላሽ አለው ። የዛ ሁሉ ታቦት ጌታ በረቂቅ ጥበቡ ይሄን ጉድ አሻገረው ።
ማሙሽ ቀጥሎ ጴጥሮስ የሚባል ጴንጤ ልጅን አፃፈው ። የፓስተሮች ጌታ መንጥቆ አወጣው ።
የዛች የኡቃቢያም ልጅ ደጀኑም ጣፈ ። የእናቱ ቆሪጥ ከዚህ ጉድ ሰወረው ።
ከጎኔ የነበረው አህመድ ሽንቱ ጭርቅ አለ ። ካኪ ሱሪው በሰበሰ።
I Love you ብሎ ጣፈ ። አላህ ደጉ አላህ መሀሪው የት ሄዶ ?
ከዚህ መዓት ስውር :)
ቀጥሎ ማሙሽ ወደኔ ተምዘገዘገ ። በቃ እኔ ጋር እስኪደርስ ያለውን moment የሆረር ፊልም በሉት ። ሳጥናኤል ከነ ጀለሶቹ የቀረበኝ መሰለኝ ።
እግዚኦ በዛ ላይ አስተያየቱ !
ግልምጫው ብቻ ገሀነም ዶለኝ :)
እውነቱን ለመናገር እኔ በዛን ጊዜ ተረት እየፃፍኩ ለክፍል ልጆች አቀርብላቸው ነበር እንጅ የሴት ልጅ መሻት ተልቤ ዘልቆም አያውቅ!
ደግሞ ያስጠረጠረኝ ነገር የፍቅር ተረት ማብዛቴ ነበር።
እኔን ብሎ ደራሲ...እኔን ብሎ ሮማንቲክ ...እኔን ብሎ ተራኪ !
እነሱን ላዝናና በጣርኩኝ ...ተጠረጠርኩኝ (ይሄ ነገር ገጠመ መሰለኝ 😃)
በቃ ያለኝ አማራጭ ከትክክለኛ ፅሁፌ ውጬ ነገሩን አንጋዶ መፃፍ ብቻ ነው።
I.. ..LAVI YAOU ብዬ ጣፍኩኝ። እንጃ ብቻ ቃላቱን ማሳሳቴ ከጉድ ያወጣኝ መሰለኝ።
ማሙሽ መንኮራኩር እንደሚያመጥቅ ሳይንቲስት ጥሁፌን ለደቂቃዎች ትኩር ብሎ ከዛ በአጭር ወረቀት ከተፃፈ ደብዳቤ ጋር አነፃፀረ ።
አነፃፅሮ.. . ከክፍል ወጣ ።
ከዛ በኋላ የማስታውሰው ብቸኛ ነገር ቢኖር መምህር ሀንዴቦ የሀረር ቄሮን የሚያህል ዱላ ይዘው መምጣታቸውን ነው።
እንደ ጀት ፈጥነው ስሬ ተገተሩ ።
አንተ ? ነው ያሉኝ.. .
አንተ !
እንደ ወረብ ከበሮ ተደለቅሁኝ :)
አቤት ሼም !
አቤት ውርደት!
የክፍል ተማሪዎች ግልምጫ እሳት ሆኖ ለበለበኝ። ገና በእረፍት ሰዓት "ዬዩ....ዬዪ " ምናምን የሚሉ ነቆራዎች አሉብኝ።
ተዟዙሬ.. .እንደ ኳስ ከተለጋሁ በኋላ መምህራችን አንድ ሰቅጣጭ ቃል አወጡ።
ነገ ወላጅ ይዘህ ና !
በጀርባዬ ልወድቅ ምን ቀረኝ! ነፍሴ...ልቤ...አንጀቴና ጉበቴ እኩል ሸኑ ።
ስንት ጉድ ተፈጥሮ ካለቀ በኋላ ግን ያን ደብዳቤ የፃፈው ዳቆኑ ዳንኤል እንደሆነ ተደረሰበት። ነገሩ ስለተረሳ ብዙም አልተካበደበትም።
ከዛ በኋላ ኤደን የምትባለውን ልጅ ባየኋት ቁጥር ትደብረኛለች :)

@getem
@getem
@paappii

@Mikael aschenaki
ሥዕልን ለማሳል በ +251984740577
ወይም @gebriel_19 ላይ ፎቶ በመላክ በ ተመጣጣኝ ዋጋ ማዘዝ ይችላሉ!
#ሥዕል_ብቻ የቴሌግራም ገፅ


@seiloch
@seiloch
አንዳንዴ በሽምግልና የማያልቅ ነገር አለ። በፍርድ ቤትም ለመፍታት የሚቸገር። ተፈጥሮ
ከሽምግልናም ከፍርድ ቤት በላይ ወሳኝ የሚሆንበት።
:
ባልና ሚስት በሽምግልና መስማማት አቅቷቸው ፍርድ ቤት ሄዱ። ፍርድ ቤት ሃብታቸውን
እኩል እንዲካፈሉ ተወስኖ ተስማሙ። በጋብቻ ውስጥ ያፈሯቸውን ሶስት ልጆቻቸው ግን
እንዴት እንደሚካፈሉ መፍትሔ ጠፋ።
ባልና ሚስት ተመካከሩና ተጨማሪ አንድ ዓመት አብሮው በመኖር በሚቀጥለው ዓመት
አንድ ልጅ ጨምረው ከዛ በኃላ ለመለያየት ተስማሙ።
:
ቀጣይ ዓመት ደርሶ ፍርድ ቤት ሲመጡ ሚስት መንታ ወልዳ ቀረበቸ። አምስት ልጆች
ሆኑ።
በድጋሚ አንድ ዓመት አብረው ኖረው በቀጣይ ዓመት አንድ ልጅ ወልደው ለመመለስ
ተስማምተው ሄዱ።

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Abinet Addis
ዘመቻ አልሄድክም ለምትሉኝ ጓዶች ቤቴ ውስጥ የገጠመኝን ትግል ታውቁታላችሁ ወይ?

ወንድ ልጅ ማሳደግ ማለት በጁንታ መያዝ መሆኑንስ ታርፉታላችሁ?

ባባ እንደ ጌታቸው ረዳ ቦርጭ የገዘፈውን ኩባያ ወረወረው ! ... ደግሞ እኮ የአወራወሩ ሀይል ! ... ጁንታ ያስወነጨፈው ከባድ መሳሪያ የአከራዬ አናት ላይ መዓት ሆኖ ወረደ 🙂

ኡኡ ነው ያሉት 

አጋነንክ አትበሉኝና እሪ.....ሪ.... ብለው ግቢውን ደበለቁት ።

በዛ ላይ ያ መከረኛ CNN ህወሀት አዲስ አበባን ከቦታል ብሎ አሳምኖዋቸዋል። 

ሰላማዊ ዜጋ ላይ መድፍ አሉ ባለቤታቸው።

በዛ ላይ የኩባያው መሰበር ። ከዚህች ቀን ቀደም ምን ከሚያክል ብፌ ላይ ወድቆ እኮ ጭራሽ አዲስ ሆኖ ነው የተነሳው 🤔

በዛች ቅፅበት ግን ፍርክሽ አለ ...ቡም !

ያቺ እኔ ከተከራየሁበት ክፍል የተከራየችው የሺ ደግሞ ጩኸቱ ላይ ሌላ የራሷን ታለንት አከለችበት ። እማዬ ድረሱልኝ! 

አቤት ለአከራይ ማሽቃበጥ

ደግነቱ "ኸረ ለኔም አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ይድረስልኝ" ብለው ኩም አደረጓት ።

ደግሞ ያ የእንጀራ በወጥ ታጋይ ባሏም ቆመጥ ይዞ ወጣና እንደ ደህና የባህል ሙዚቃ ጨፋሪ ፎከረ !

ከበላይ ሆኜ በቁምጣው ስር የሚታይ ታፋውን ቃኘሁት ። ሰማኸኝ በለው ማረኝ!

ሲኦል ያሉ ፍጥረታት ላይ መከራ ለመጨመር በሚመስል አረጋገጥ ነው በዛ ሞፈር እግሩ ምድሪቷ ላይ የሚንጎማለለው። 
ምድር ወዮ ብላ ያለቀሰች ይመስለኛል ወትሮም ራመድ ራመድ ሲል ...

የግቢው መሰረት ተናጋ ! 

የአንድ ዓመት ከምናምን ወር ህፃን አልቆጣው ነገር ሆኖብኝ "እንዴ ባባ ?" የሚል ደንጋጣ ጥያቄዬን ሰነዘርኩኝ። አሁን ይሄ ጥያቄ የኒኬል መደቀኛ ያስወረውራል ወይ? 🙂

ኪችልችልችልችል.. .

ሰማኸኝ በለው (ውይ ያማነው ከበደ ) ፉከራውን ጥሎ በረረ ... 

አቤት ግዙፍ ሰው ባሏ በካልቾ እንደጠለዛት የሴት ሲሮጥ.. .

እማምዬ አለ ።

"ሰላማዊ ዜጋ ላይ ቦንብ ?" ብለው ለጠቁ ማዘር 🙂

እሺ ኒኬሉ ደግሞ ጣሪያው ላይ ጮሆ ቢያበቃ ምናለበት?

ሴራሚኩ ላይ ወርዶ ተቅጨለጨለ ።

ይህን ጊዜ ጋሼ ደምግፊታቸው ሶፋ ላይ ጥሏቸው ይሆናል መቼም !

ቂጭልልልልልልል ቀጭ....

ደቂቃዎች ሲያልፉ ከየትኛውም ክፍል ድምፅ ጠፋ ። ባባን ይዤው ወደሳሎን ወረወርኩና ወደ መሬት ተንደረደርኩ ።

አቶ ከበደ (ሰምን መቼም መልዓክ ያወጣዋል አይደል የሚባለው ?)...ለደቂቃዎች በመስኮት ሲያተኩር ቆይቶ የኔን መምጣት ሲመለከት ተስፈንጥሮ ወጣ ።

አወጣጡ ደግሞ እንደ ዱር አንበሳ እየተንጎማለለ እኮ ነው። ... የሆነ ነብር ገድሎ ቆዳውን ለምስክር ለብሶ የመጣ ጀብደኛ እኮ ነው የሚመስል ።

ሳቀ ...

"ሃሃሃ..... ማዘር የመጨረሻዋን ሳቅ የምንስቃት እኛ ነን አላልኩም ? አይዞን ተረጋጉ ኒኬል ነው 🙂

ከደቂቃዎች በኋላ ጋሼ ስክም ስክም እያሉ መጡ ።

"አሁንስ በዛ ! ከነገ ጀምሮ ቤቴን..."

ማንም አከራይ ተከራዩን እንዳያስወጣ የሚለውን አዋጅ ለማሳየት ስልኬን መዳበስ ጀመርኩኝ 😋

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Mikael aschenaki
አለ አይደል አንዳንዴ?... ማለት አበዛለው!.......ውስብስብ..... ብናገር ሰው ሊረዳው የማችለው ቢረዳውም ፈራጅ ይሆናል ብዬ ላሰብኩት ነገር...... የምመርጠውም የሚመጣልኝም ቃል ቢኖር አለ አይደል አንዳንዴ? የሚል ነው...... ብዙ ማስበውና የምደሰትበት ነገር አለኛ!..... ለሰሚ የሚያስገርም አይነት ለምን የሚል ጥያቄ የሚጭር አይነት.....እና እኔ ቀለል አድርግና.....ህመሙን ሀሴቱን ለራሴ በመተው
መናገር ሲከብደኝ አለ አይደል እላለው!
አዋ አለ አይደል አንዳንዴ ... ተንደርድረሽ እቀፊው እቀፊው ይለኛል .... ለምንስ ቶሎ ምንስ
ቢፈጠር ሌላ አለም ውስጥ ካስገባሽ ክንዱ ትነጠያለሽ ይላል አካሌ........ ቀን ማታ ናፍቆቴ
ነው ይኸው ደሞ ሁሉንም ሳልናገር ትቼው አለአይደል ልል ነው....ቀርቦም እርቆም የሚናፈቅ
ሰው ነው! .. አለ አይደል አንዳንዴ .........እንዝላልነትም ሲጨመርበት ናፍቆት ይበረታል መሰለኝ አይኖቻችን በተገጣጠሙ ጊዜ አንገቴን ሰበር .... ወይም ዘወር ማድረግ ስራዬ ነው....እወዳቸዋለው እፈራቸዋለሁም ........ከአፍህ ተቃራኒ እንዳይሆኑብኝ ይሆን? አሊያም
ተመሳሳይ ሆኖ ብርቱነታቸውን እኔ ላይ እንዳያረጋግጡ? ....... ወይም ደግሞ የእኔን ዐይኖች ጓደኛህ እንዳይሆኑ ሰግቼ....... ደካማነቴን እንዳያሳብቁብኝ ፈርቼ...... አቃጣሪ እንዳይሆኑብኝ እና እያንዳንዷን ሀሳቤን ሹክ እንዳይሉህ ለማምለጥ...... እሸሻቸዋለው...... በየትኛው ምክንያት እንደሆነ ባይገባኝም ላያቸው፣ በጥልቀት ልመረምራቸው ፈልጌ እተወዋለሁ ........

አትኩረህ እንዳታየኝ ደግሞ ስስ ነህ ፈራሀለሁ!...

@wegoch
@wegich
@paappii
#Muna Abduselam Mu
2024/09/23 12:14:46
Back to Top
HTML Embed Code: