Telegram Web Link
የደብረ መድኃኒት ዐቢየ እግዚእ ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ወቅዱስ መርቆሬዎስ የአለቃ ወልደ አብ የመጻሕፍት ት/ቤት ግንባታ ፕሮጀክት  ተመረቀ ፡፡
     
በማኅበረ ቅዱሳን አስተባባሪነት በሀገር ውስጥና ከሀገር ዉጭ በሚገኙ በጎ አድራጊ ምእመናን የገንዘብ ድጋፍ የተሠራው  በማእከላዊ ጎንደር ሀ/ስብከት  የደብረ መድኃኒት ዐቢየ እግዚእ ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ወቅዱስ መርቆሬዎስ የአለቃ ወልደ አብ የመጻሕፍት ት/ቤት ግንባታ ፕሮጀክት  ብፁእ አቡነ ዮሐንስ የማእከላዊ ጎንደር ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁእ አቡነ ሰላማ የምእራብ ጎንደር ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ምእመን በተገኙበት ኅዳር 16 ቀን 2016 ዓ.ም በታላቅ ድምቀት ተመርቋል፤
   
በምርቃቱ መርሐግብር ላይ ንግግር ያደረጉት  የማኅበረ ቅዱሳን ም/ሰብሳቢ አቶ ግዛቸው ሲሳይ  የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለማስቀጠልና ተተኪ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን ለማፍራት አብነት ት/ቤቶችን ማጠናከርና እንደዚህ ዓይነት አብነት ት/ቤቶች በተለያዩ አካባቢዎች ማስፍፍትና ማጠናከር እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል፡፡
በተመሳሳይ የፕሮጀክቱን  የትግበራ ሪፖርት ያቀረቡት የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊ ዲ/ን አንድነት ተፈራ  አብነት ት/ቤቱ  ባጋጠመው ከፍተኛ የሆነ የተማሪዎች ማደሪያና መማሪያ ችግር ምክንያት   ደቀ መዛሙርቱ ለተለያየ ችግር በመጋለጣቸው  ተስፋ በመቁረጥ ከጉባኤ ቤቱ  እየለቀቁ በመሄዳቸው   የጉባኤ ቤቱ ህልውና አደጋ ላይ ወድቆ እንደነበር አስታውሰው ይህን ችግር በዘላቂነት ለመፍታትና ተተኪ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያንን ለማፍራት ዓላማ አድርጎ መሠራቱን ገልጸዋል፡፡ ጉባኤ ቤቱ 4 ወለል ያለው ሕንጻ ሲሆን 110 ተማሪዎችን የሚያስተናግድ የተማሪዎች ማደሪያ ፣ የመምህራን ቤት፣ 100 ተማሪዎችን በአንድ ጊዜ ማስተማር የሚያስችል መማሪያ ( ጉባኤ ቤት) ፣የሥልጠና ማእከል ፣ ቤተ መጻሕፍት ፣ መመገቢያና ማብሰያ፣  መጸዳጃ ቤት እንዲሁም ለአገልግሎት አስፈላጊ የሆኑ ቁሳቁሶች የተሟሉለት መሆኑን ም/ዋና ጸሐፊው በሪፖርታቸው ገልጸዋል፡፡

የማእከላዊ ጎንደር ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁእ አቡነ ዮሐንስ የጉባኤ ቤቱ መገንባት እንዳስደሰታቸው በመግለጽ ደቀ መዛሙርቱ ትምህርታቸውን በንቃት እንዲከታተሉ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በተያያዘ ዜና ጉባኤ ቤቱ ሲያስተምራቸው የቆዩ 24 የመጻሕፍት መምህራንና በጉባኤ ቤቱ የተጻፈ ሰሎሞን ወሲራክ አንድምታ ትርጓሜ መጽሐፍ በዕለቱ አስመርቋል፡፡

ዘጋቢ ፡- ቴዎድሮስ አይቸው
                ጎንደር ፡፡
የደብረ ሐዊ ቅዱስ ያሬድ አንድነት ገዳም የገቢ ማስገኛ ሕንጻ ግንባታ ፕሮጀክት  ተጀመረ።
 
በማኅበረ ቅዱሳን አስተባባሪነት በደባርቅ ከተማ የሚገነባው የደብረ ሐዊ ቅዱስ ያሬድ አንድነት ገዳም ሁለገብ የገቢ ማስገኛ ሕንጻ ግንባታ ፕሮጀክት ኅዳር 15 ቀን 2016 ዓ.ም  የገዳሙ አባቶች፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የአካባቢው ምእመናንና ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት የጸሎተ ወንጌል መርሐ ግብር በማከናወን የቁፋሮ ሥራው በይፋ ተጀምሯል።

የሰሜን ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ  ዲ/ን ሸጋው ውቤ ፕሮጀክቱ  በከተማችን መተግበሩ ለገዳሙ ከሚያስገኘው ጥቅምና መንፈሳዊ አስተዋጽኦ ባሻገር ለቱሪዝም ዘርፉ፣ ለማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ  ጉዳዮች ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያስገኝ መሆኑን በፕሮጀክቱ ማስጀመሪያ መርሐ ግብር ላይ ገልጸዋል፡፡

የገዳሙን ኢኮኖሚያዊ አቅም በዘላቂነት ማጠናከር የፕሮጀክቱ ዋና ዓላማ መሆኑን በመግለጽ ፕሮጀክቱ  በታቀደለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ  የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊ ዲ/ን አንድነት ተፈራ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።

ጥቅምት 11 ቀን 2016 ዓ.ም "ስምከ ሕያው ቅዱስ ያሬድ" በሚል መሪ ቃል በሚሊኒየም አዳራሽ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ማካሄዱም ይታወሳል ።

ዘጋቢ ፡- ቴዎድሮስ አይቸው
             ደባርቅ ፡፡
ደባርቅ ማእከል የማኅበረ ቅዱሳን 52ኛ ማእከል በመሆን አገልግሎት መስጠት ጀመረ።

ማኅበረ ቅዱሳን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣውን የአገልግሎት ስፋት የሚመጥን መዋቅር ለመዘርጋት ከፍተኛ ጥረት እያደረገ ይገኛል። በተለይ የሀገረ ስብከት መቀመጫ ቦታዎች ላይ የቤተ ክርስቲያንን እና የማኅበሩን ተልእኮ ማስፈጸም የሚችሉ ማእከላትን በማቋቋም ደረጃ በከፍተኛ ትኩረት እየተንቀሳቀሰ ይገኛል።

በ1994 ዓ.ም የተቋቋመው የደባርቅ ወረዳ ማእከል ለ21 ዓመታት ያክል በጎንደር ማእከል ሥር በመሆን የማኅበረ ቅዱሳንን አገልግሎት ሲያከናውን ቆይቷል።ወረዳ ማእከሉ የሚገኝበት አካባቢ በርካታ የታሪካዊ እና መንፈሳዊ ቦታዎች የሚገኙ በመሆኑ እና ከ2011 ዓ.ም መጨረሻ ጀምሮ ደግሞ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ውሳኔ መሠረት  በአዲስ አደረጃጀት የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በሚል በመዋቀሩ ወረዳ ማእከሉን ወደ ማእከል እንዲያድግ ተደርጓል።

በዚህም መሠረት ኅዳር 16 ቀን 2016 ዓ.ም የደባርቅ ማእከል የማኅበሩ 52ኛ ማእከል በመሆን ምሥረታውን ያከናወን ሲሆን በዕለቱ የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊ ዲ/ን አንድነት ተፈራን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በተገኙበት የምሠረታ መርሐ ግብሩ ተከናውኗል።

ማእከሉ የተለያዩ አድባራት እና ገዳማትን እንዲሁም የአብነት ትምህርት ቤቶችን በውስጡ ይዟል። በተጨማሪም አዲስ የሚሠራው የደብረ ሐዊ ቅዱስ ያሬድ አንድነት ገዳም የገቢ ማስገኛ ሕንጻ ፕሮጀክት በዚህ ማእከል ውስጥ የሚገኝ መሆኑ ይታወቃል።

የቴሌግራም ቻናላችንን ይቀላቀሉ


https://www.tg-me.com/mahibere_kidusan
2024/09/30 22:19:08
Back to Top
HTML Embed Code: