Telegram Web Link
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነሐሴ_30_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ዕብራውያን 11
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
³² እንግዲህ ምን እላለሁ? ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ ስለ ሶምሶንም ስለ ዮፍታሔም ስለ ዳዊትና ስለ ሳሙኤልም ስለ ነቢያትም እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛልና።
³³ እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፥ ጽድቅን አደረጉ፥ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፥
³⁴ የአንበሶችን አፍ ዘጉ፥ የእሳትን ኃይል አጠፉ፥ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፥ ከድካማቸው በረቱ፥ በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ፥ የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ።
³⁵ ሴቶች ሙታናቸውን በትንሣኤ ተቀበሉ፤ ሌሎችም መዳንን ሳይቀበሉ የሚበልጠውን ትንሣኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤
³⁶ ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤
³⁷ በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤
³⁸ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና በምድር ጕድጓድ ተቅበዘበዙ።
³⁹-⁴⁰ እነዚህም ሁሉ በእምነታቸው ተመስክሮላቸው ሳሉ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አላገኙም፥ ያለ እኛ ፍጹማን እንዳይሆኑ እግዚአብሔር ስለ እኛ አንዳች የሚበልጥ ነገርን አስቀድሞ አይቶ ነበርና።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ይሁዳ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁷ እናንተ ግን፥ ወዳጆች ሆይ፥ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያት ቀድሞ የተነገረውን ቃል አስቡ፤
¹⁸ እነርሱ፦ በመጨረሻው ዘመን በኃጢአተኝነት እንደ ገዛ ምኞታቸው እየሄዱ ዘባቾች ይሆናሉ ብለዋችኋልና።
¹⁹ እነዚህ የሚያለያዩ ሥጋውያንም የሆኑ መንፈስም የሌላቸው ሰዎች ናቸው።
²⁰ እናንተ ግን፥ ወዳጆች ሆይ፥ ከሁሉ ይልቅ በተቀደሰ ሃይማኖታችሁ ራሳችሁን ለማነጽ እየተጋችሁ በመንፈስ ቅዱስም እየጸለያችሁ፥
²¹ ወደ ዘላለም ሕይወት የሚወስደውን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ምሕረት ስትጠባበቁ በእግዚአብሔር ፍቅር ራሳችሁን ጠብቁ።
²² አንዳንዶች ተከራካሪዎችንም ውቀሱ፥ አንዳንዶችንም ከእሳት ነጥቃችሁ አድኑ፥
²³ አንዳንዶችንም በሥጋ የረከሰውን ልብስ እንኳ እየጠላችሁ በፍርሃት ማሩ።
²⁴ ሳትሰናከሉም እንዲጠብቃችሁ፥ በክብሩም ፊት በደስታ ነውር የሌላችሁ አድርጎ እንዲያቆማችሁ ለሚችለው
²⁵ ብቻውን ለሆነ አምላክና መድኃኒታችን ከዘመን ሁሉ በፊት አሁንም እስከ ዘላለምም ድረስ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ክብርና ግርማ ኃይልም ሥልጣንም ይሁን፤ አሜን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹² በዚያን ጊዜ ደብረ ዘይት ከሚባለው ተራራ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ፥ እርሱም ከኢየሩሳሌም የሰንበት መንገድ ያህል የራቀ ነው።
¹³ በገቡም ጊዜ ወደሚኖሩበት ሰገነት ወጡ፥ ጴጥሮስና ዮሐንስም፥ ያዕቆብም፥ እንድርያስም፥ ፊልጶስም፥ ቶማስም፥ በርተሎሜዎስም፥ ማቴዎስም፥ የእልፍዮስ ልጅ ያዕቆብም፥ ቀናተኛ የሚባለው ስምዖንም፥ የያዕቆብ ልጅ ይሁዳም።
¹⁴ እነዚህ ሁሉ ከሴቶችና ከኢየሱስ እናት ከማርያም ከወንድሞቹም ጋር በአንድ ልብ ሆነው ለጸሎት ይተጉ ነበር።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_30_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"መንክር ተላህያ ለባሕር። መንክርሰ እግዚአብሔር በአርያሙ። ስምዐ ዚአከ እሙን፡ፈድፋደ"። መዝ 92፥4-5 ወይም መዝ 100፥6-7።
"ከብዙ ውኆች ድምፅ ከባሕርም ታላቅ ሞገድ ይልቅ እግዚአብሔር በከፍታው ድንቅ ነው። ምስክርህ እጅግ የታመነ ነው፤ አቤቱ፥ እስከ ረጅም ዘመን ድረስ ለቤትህ ቅድስና ይገባል"። መዝ 92፥4-5
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_30_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሉቃስ 24
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹³ እነሆም፥ ከእነርሱ ሁለቱ በዚያ ቀን ከኢየሩሳሌም ስድሳ ምዕራፍ ያህል ወደሚርቅ ኤማሁስ ወደሚባል መንደር ይሄዱ ነበር፤
¹⁴ ስለዚህም ስለ ሆነው ነገር ሁሉ እርስ በርሳቸው ይነጋገሩ ነበር።
¹⁵ ሲነጋገሩና ሲመራመሩም፥ ኢየሱስ ራሱ ቀርቦ ከእነርሱ ጋር ይሄድ ነበር፤
¹⁶ ነገር ግን እንዳያውቁት ዓይናቸው ተይዞ ነበር።
¹⁷ እርሱም፦ እየጠወለጋችሁ ስትሄዱ፥ እርስ በርሳችሁ የምትነጋገሩአቸው እነዚህ ነገሮች ምንድር ናቸው? አላቸው።
¹⁸ ቀለዮጳ የሚባልም አንዱ መልሶ፦ አንተ በኢየሩሳሌም እንግዳ ሆነህ ለብቻህ ትኖራለህን? በእነዚህ ቀኖች በዚያ የሆነውን ነገር አታውቅምን? አለው።
¹⁹ እርሱም፦ ይህ ምንድር ነው? አላቸው። እነርሱም እንዲህ አሉት፦ በእግዚአብሔርና በሕዝቡ ሁሉ ፊት በሥራና በቃል ብርቱ ነቢይ ስለ ነበረው ስለ ናዝሬቱ ስለ ኢየሱስ፤
²⁰ እርሱንም የካህናት አለቆችና መኳንንቶቻችን ለሞት ፍርድ እንዴት አሳልፈው እንደ ሰጡትና እንደ ሰቀሉት ነው።
²¹ እኛ ግን እስራኤልን እንዲቤዥ ያለው እርሱ እንደ ሆነ ተስፋ አድርገን ነበር፤ ደግሞም ከዚህ ሁሉ ጋር ይህ ከሆነ ዛሬ ሦስተኛው ቀን ነው።
²² ደግሞም ከእኛ ውስጥ ማልደው ከመቃብሩ ዘንድ የነበሩት አንዳንድ ሴቶች አስገረሙን፤
²³ ሥጋውንም ባጡ ጊዜ፦ ሕያው ነው የሚሉ የመላእክትን ራእይ ደግሞ አየን ሲሉ መጥተው ነበር።
²⁴ ከእኛም ጋር ከነበሩት ወደ መቃብር ሄደው ሴቶች እንደ ተናገሩት ሆኖ አገኙት፥ እርሱን ግን አላዩትም።
²⁵ እርሱም፦ እናንተ የማታስተውሉ፥ ነቢያትም የተናገሩትን ሁሉ ልባችሁ ከማመን የዘገየ፤
²⁶ ክርስቶስ ይህን መከራ ይቀበል ዘንድና ወደ ክብሩ ይገባ ዘንድ ይገባው የለምን? አላቸው።
²⁷ ከሙሴና ከነቢያት ሁሉ ጀምሮ ስለ እርሱ በመጻሕፍት ሁሉ የተጻፈውን ተረጐመላቸው።
²⁸ ወደሚሄዱበትም መንደር ቀረቡ፥ እርሱም ሩቅ የሚሄድ መሰላቸው።
²⁹ እነርሱ፦ ከእኛ ጋር እደር፥ ማታ ቀርቦአልና ቀኑም ሊመሽ ጀምሮአል ብለው ግድ አሉት፤ ከእነርሱም ጋር ሊያድር ገባ።
³⁰ ከእነርሱም ጋር በማዕድ ተቀምጦ ሳለ እንጀራውን አንሥቶ ባረከው፥ ቈርሶም ሰጣቸው፤
³¹ ዓይናቸውም ተከፈተ፥ አወቁትም፤ እርሱም ከእነርሱ ተሰወረ።
³² እርስ በርሳቸውም፦ በመንገድ ሲናገረን መጻሕፍትንም ሲከፍትልን ልባችን ይቃጠልብን አልነበረምን? ተባባሉ።

ወይም

ማርቆስ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ የእግዚአብሔር ልጅ የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል መጀመሪያ።
²-³ እነሆ፥ መንገድህን የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ የጌታን መንገድ አዘጋጁ ጥርጊያውንም አቅኑ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ ተብሎ በነቢዩ በኢሳይያስ እንደ ተጻፈ፥
⁴ ዮሐንስ በምድረ በዳ እያጠመቀ የንስሐንም ጥምቀት ለኃጢአት ስርየት እየሰበከ መጣ።
⁵ የይሁዳም አገር ሁሉ የኢየሩሳሌምም ሰዎች ሁሉ ወደ እርሱ ይወጡ ነበር፥ ኃጢአታቸውንም እየተናዘዙ በዮርዳኖስ ወንዝ ከእርሱ ይጠመቁ ነበር።
⁶ ዮሐንስም የግመል ጠጉር ለብሶ በወገቡ ጠፍር ይታጠቅ አንበጣና የበረሀ ማርም ይበላ ነበር።
⁷ ተጎንብሼ የጫማውን ጠፍር መፍታት የማይገባኝ ከእኔ የሚበረታ በኋላዬ ይመጣል።
⁸ እኔ በውኃ አጠመቅኋችሁ እርሱ ግን በመንፈስ ቅዱስ ያጠምቃችኋል እያለ ይሰብክ ነበር።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #ቅዱሳን_ሐዋርያት_ቅዳሴ ነው። መልካም የነቢዩ ቅዱስ ሚልክያስ የዕረፍት በዓልና የሐዋርያው ቅዱስ እንድርያስ የመታሰቢያ ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነቢዩ_ሚልክያስ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

“ሚልክያስ” ማለት “መልአክ፣ ሐዋርያ፣ መልእክተኛ” ማለት ነው፡፡ ጥር ፰ ቀን የሚነበበው ስንክሳር እንደሚያስረዳው ነቢዩ ሚልክያስ የተወለደው ሕዝቡ ከፄዋዌ (ከምርኮ) ከተመለሱ በኋላ ነው፡፡ ከሕፃንነቱ አንሥቶም የ #እግዚአብሔርን መንገድ የሚወድ ነበር፡፡ ሕዝቡም ይኽን አካኼዱን አይተው እጅግ ያከብሩት ነበር፡፡ ይኽን መልካምነቱንም አይተው “ከ #እግዚአብሔር የተላከ ነው” ሲሉ ስሙን ሚልክያስ ብለው ጠሩት፡፡

ነቢዩ ሚልክያስ ከጸሐፍት ነቢያት የመጨረሻው ነቢይ ነው፡፡ ከሐጌና ከዘካርያስ በኋላም በነቢይነት አገልግሏል፡፡ ከ፬፻፶-፬፻ ቅ.ል.ክ. ላይ እንደነበረም ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ ዕዝራና ነህሚያ ቤተ አይሁድን በሚስተካክሉበት ጊዜ ሚልክያስም ተባባሪያቸው ነበር፡፡

➛በነቢዩ ዙረያ የነበረው ነባራዊ ኹኔታ

➛በምርኮ የነበሩት አይሁድ በ፭፻፴፰ ቅ.ል.ክ. ላይ ከምርኮ ወደ አገራቸው መመለስ እንደሚችሉ ሲነገራቸው ከኹለት ቡድን ተከፍለዋል፡፡ አንደኛውና የሚበዛው ቡድን ወደ ተስፋይቱ ምድር መመለስን ያልወደደና በባቢሎን አገር በሀብትና ንብረት የተደራጀ ነው፡፡ ይኼ ቡድን ምንም እንኳን በባዕድ አገር የሚኖር ቢኾንም ባርነቱ የተመቸው ይኽንንም ዓለም የወደደ ነው፡፡ ይኼ ቡድን #እግዚአብሔር ለአባቶቹ የገባውን ቃል ኪዳን ለመካፈል ያልፈለገ ቡድን ነው፡፡ በሕገ ኦሪቱ መሠረት #እግዚአብሔርን እያመለከ ለመኖር ያልፈቀደ ቡድን ነው፡፡

➛ኹለተኛውና የሚያንሰው ቡድን ደግሞ ወደ ተስፋይቱ ምድር የተመለሰው ነው፡፡ ይኼ ቡድን ከምርኮ ሲመጣ የኢሩሳሌምን አጥር፣ ቤተ መቅደሱን ለመሥራት፤ እንዲኹም የቀድሞውን አምልኮተ #እግዚአብሔር ለመመለስ ነበር፡፡ ነገር ግን ከእነዚኽም መካከል ቤታቸውን ለመሸላለም “የ #እግዚአብሔር ቤት የሚሠራበት ዘመን ገና ነው” የሚሉ ነበሩ፡፡ አኹንም ከእነዚኽ ከተመለሱት ቅሪቶች መካከል ምንም እንኳን ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን ቢያከናውኑም አካኼዳቸው ግን ከልብ አልነበረም፡፡ መሥዋዕታቸው የቃየን መሥዋዕት ነበር፡፡ ሲዠምር “የ #እግዚአብሔር ማዕድ አስናዋሪ ነው” ይላሉ፡፡ በፊቱ የተዘጋጀ እኽሉም “አባር የመታው እንክርዳድ ነው” ይላሉ፡፡ እነርሱም ለመሥዋዕት ዕውሩን አንካሳውን እንስሳ ያመጣሉ /፩፡፰/፡፡

#ነቢዩ_ሚልክያስ የተላከበት ምክንያትም ይኽን አካኼዳቸውን እንዲያስተካክሉ ለማሳሰብ ነበር፡፡
#ነቢዩ_ሚልክያስ በነገሥታቱ ዘመን እንደነበረው ዓይነት ስብከት አልሰበከም፤ የባዕድ አምለኮ ዐፀዶችን እንዲያፈርሱም አልተናገረም፡፡ ልክ እንደ ዕዝራ ወደ አገራቸው እንዲመለሱ አላሳሰባቸውም፤ ልክ እንደ ነህምያም የኢየሩሳሌምን አጥር ቅጥር እንዲሠሩ አላሳሰባቸውም፡፡ ወደ ውሳጣዊ ሕይወታቸው ዘልቆ በቅድስና ከ #እግዚአብሔር ጋር ኅብረት እንዲኖራቸው አሳሰባቸው እንጂ፡፡ #እግዚአብሔር በእውነትና በመንፈስ የሚያመልኩት አምላክ ነውና ከምንም በፊት ውሳጣዊ ማንነታቸውን ወደ አገራቸው ወደ ሰማይ እንዲመልሱ፣ የነፍሳቸው የኢየሩሳሌምን አጥር ቅጥር እንዲሠሩ ነበር ያሳሰባቸው፡፡

#ትንቢተ_ሚልክያስ

ትንቢተ ሚልክያስ እጅግ መሳጭና የ #እግዚአብሔር ፍቅር እንደምን ጥልቅ እንደኾነ የምናነብበት መጽሐፍ ነው፡፡ #እግዚአብሔር የሰው ልጆችን በሙሉ ያለማዳለት ይወዳል፡፡ #እግዚአብሔር ሲወድ አንዱን በመጥላት ሌላውንም በመውደድ አይደለም፡፡ ያለ ማዳላት ኹላችንም ይወደናል እንጂ፡፡ ሰዎች በ #እግዚአብሔር ዘንድ የተጠሉ የሚኾኑት ከራሳቸው ክፋት የተነሣ ነው፡፡ ሕጉንና ትእዛዙን ሳያከብሩ ሲቀሩ #እግዚአብሔር አይቀበላቸውም፡፡ አፍአዊ በኾነ አምልኮ #እግዚአብሔርን መቅረብ ወደ ሕይወትም መጋበዝ አይቻልምና እነዚኽ ሰዎች በ #እግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነት የሌላቸው ይኾናሉ፡፡ በትንቢተ ሚልክያስ የምናገኘው አንዱ አንኳር ነጥብ ይኸው ነው /፩፡፪-፭/፡፡

ነቢዩ ሚልክያስም ለዚኹ ኹሉ ችግር መፍትሔው አንድና አንድ ብቻ እንደኾነ ይሰብካል፤ ይኽ ከ #እግዚአብሔር የተቀበለውንም መልእክት ለሕዝቡ ያስተላልፋል፡፡ “ወደ እኔ ተመለሱ፤ እኔም ወደ እናንተ እመለሳለኹ ይላል የሠራዊት #ጌታ_እግዚአብሔር” በማለት /፫፡፯/፡፡ ይኽ ለሰው ኹሉ የተከፈተ በር ነው፡፡ የእኛ ደንዳናነት ካልኾነ በስተቀር ይኽን የድኅነት በር መዝጋት የሚችል አካል የለም፡፡ እንኳንስ ፍጡር ይቅርና #እግዚአብሔርም ቢኾን ስለማይችል ሳይኾን ከታላቅ ፍቅሩ የተነሣ ይኽን በር በማንም ሰው ፊት አይዘጋውም፡፡ #እግዚአብሔርስ እርሱ እንዳይገባ የዘጋንበትን በር እንድንከፍትለት ያንኳኳል እንጂ አይዘጋውም፡፡ “ወድጃችኋለኹ ይላል የሠራዊት ጌታ #እግዚአብሔር” /፩፡፪/፡፡

ትንቢተ ሚልክያስን ገና ማንበብ ስንዠምር ከምርኮ የተመለሰው ሕዝብ አንድን ነገር ጠብቆ እንደመጣ እንገነዘባለን፡፡ ሕዝቡ አፍአዊ የኾነ በረከትን ሽቶ እንደ ነበር እንረዳለን፡፡ ከዚኽ በፊት ነቢያቱ ስለ መሲሑ የተናገሩት ኹሉ በጊዜአቸው የሚፈጸም መስሎአቸው እንደ ነበር እናስተውላለን፡፡ የዳዊት ድንኳን እንደገና በዘመናቸው እንደምትሠራ፥ ፈርሶና ተዳክሞ የነበረው መንግሥታቸውም እንደገና አንሰራርቶ በዓለም ላይ ገናና መንግሥት እንደሚኾን ገምተው እንደ ነበር እንረዳለን፡፡ እነርሱ እንዳሰቡት አፍአዊ የኾነ ነገር ሳይፈጸም ሲቀር ግን ግርምት ይዞአቸው #እግዚአብሔርን፡- “በምን ወደድኸን?” እንዳሉት እናነባለን /፩፡፪/፡፡ እንዲኽ ዓይነት የግርምትና የመደነቅ ንግግርም በብዙ ቦታ ላይ ሲናገሩት እናገኛቸዋለን፡፡ “ስምኽን ያቃለልነው በምንድነው?” /፩፡፮/፤ “ያረከስንኽ በምንድነው?” /፩፡፯/፤ “ያታከትነው በምንድነው?” /፪፡፲፯/፤ “የምንመለሰው በምንድነው?” /፫፡፯/፤ “የሰረቅንኽ በምንድነው?” /፫፡፰/፤ “በአንተ ላይ ድፍረት የተናገርነው በምንድነው?” /፫፡፲፫/፤ “ትእዛዙንስ በመጠበቅ በሠራዊት #ጌታ#እግዚአብሔር ፊት ኀዘንተኞች ኾነን በመኼድ ምን ይረባናል?” /፫፡፲፬/ እንዲል፡፡ #እግዚአብሔር ግን እነዚኽ ሰዎች ምድራዊውን ሳይኾን ሰማያዊውን፣ ጊዜአዊውን ሳይኾን ዘለዓለማዊውን፣ አፍአዊውን ሳይኾን ውሳጣዊውን፣ ብልና ዝገት የሚያገኘውን ሳይኾን በሰማያዊው መዝገብ የተቀመጠውን እንዲሹ ይጠራቸዋል፡፡ ነውረኛ መሥዋዕትን እያቀረቡ #እግዚአብሔርን ከመሸንገል ተመልሰው /፩፡፲፬/፣ የግፍ ሥራቸውን በልብስ መክደንን ትተው /፪፡፲፮/፣ “ክፉን የሚያደርግ ኹሉ በ #እግዚአብሔር ዘንድ መልካም ነው” ፥ እንዲኹም “የፍርድ አምላክ ወዴት አለ?” /፪፡፲፯/፣ “የሚታበዩትን ሰዎች ብፁዐን እንላቸዋለን” እያሉ /፫፡፲፭/ እግዚአብሔርን ከመፈታተን ተመልሰው ስሙን እንዲፈሩና የክፋት በረዶአቸው በጽድቅ ፀሐዩ እንዲቀልጥላቸው፥ በሕይወትም እንዲኖሩ ይጠራቸዋል /፬/።

በአጠቃላይ መጽሐፉ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡- “በመንፈሱ በውስጥ ሰውነታችሁ በኃይል እንድትጠነክሩ፥ ክርስቶስም በልባችሁ በእምነት እንዲኖር፥ … የእናንተ ሥርና መሠረት በፍቅር ይጸና ዘንድ፥ ከቅዱሳን ኹሉ ጋር ስፋቱና ርዝመቱ ከፍታውም ጥልቀቱም ምን ያኽል መኾኑን ለማስተዋል፥ ከመታወቅም የሚያልፈውን የ #ክርስቶስን ፍቅር ለማወቅ ትበረቱ ዘንድ …” እንዳለው /ኤፌ.፫፡፲፮-፲፱/ #እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ያለው ፍቅር እንደምን ጥልቅ እንደኾነ፣ የመንግሥተ ሰማያትን ደጅ የሚከፍት የተትረፈረፈው የ #እግዚአብሔር ጸጋ ለሰው ልጆች እንደምን ብዙ እንደኾነ፣ ከአፍአ ሳይኾን ከልቡ የተመለሰ ሰው ምን እንደሚያገኝ የሚያስረዳ ድንቅ መጽሐፍ ነው፡፡ ድኅነትን
የምትሻ ነፍስ መልስ የምታገኝበት ግሩም መጽሐፍ ነው፡፡ በውስጡም በዘመነ ሐዲስ ስለሚቀርበው ቊርባን /፩/፣ ስለ ጋብቻ ምንነት /፪/፣ እንዲኹም ስለ አስራት አሰጣጥ /፫/ በጥልቀት ያስተምራል፡፡

መጽሐፉን እንደሚከተለው መክፈል እንችላለን፡-
1. ምዕራፍ አንድን ስናነብ፥ ምንም እንኳን #እግዚአብሔር አባታቸው መኾኑን ቢያውቁም፣ ምንም እንኳን #እግዚአብሔር #ጌታ እንደኾነ ቢረዱም በገቢር ግን የአባትነትም ኾነ እንደ ጌትነቱ የመፈራት ክብርን አለመስጠታቸው ይገልጣል፡፡ ነውረኛ የኾነ መሥዋዕትን በማቅረባቸው የ #እግዚአብሔርን ስም እንዴት እንደናቁት ያሳያል፡፡ በሌላ አገላለጽ የእምነትና የምግባር አንድነትን የሚያስረዳ እውነተኛና ተቀባይነት ያለው አምልኮ ምን እንደሚመስል የሚያረዳ ነው፡፡
2. ምዕራፍ ኹለትን ስንመለከት ደግሞ የካህናቱን ኢሞራላዊነት ይናገራል፡፡ በዚኽ ድርጊታቸውም የ (እግዚአብሔርን ኪዳን እንዴት እንዳፈረሱት ለበረከት የኾነውም እንደምን ለመርገም እንዳደረጉት ያስረዳል፡፡

3. ምዕራፍ ሦስትና አራት ላይ #እግዚአብሔር እንደሚመጣና ሕዝቡንም ኾነ ቤተ መቅደሱን እንደሚቀድስ ይናገራል፡፡ ምዕራፍ ሦስት ላይ በመዠመሪያ ምጽአቱ ላይ ክብር ይግባውና #ጌታችንና_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሕዝቡን (ቤተ መቅደሱን) በገዛ ደሙ ለመዋጀት እንደሚመጣና ሕዝቡም እርሱን ለመቀበል በገቢር እንዲመለሱ ሲጠይቅ በምዕራፍ አራት ላይ ደግሞ የጽድቅ ፀሐይ የተባለው #ጌታችንና_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ጨለማ የተባለውን ክፋት ከሰው ልጆች ለማራቅ እንደሚመጣ ይናገራል፡፡ በዚያ አንጻርም በሕያዋንና በሙታን ላይ ዳግም ለመፍረድ እንደሚመጣ ይገልጣል፡፡

እኛስ ከዚኽ ምን እንማራለን?
© #እግዚአብሔርን በከንፈራችን ሳይኾን በገቢር እንደምንወደው መግለጥ እንዳለብን፤ ንጹሕ መሥዋዕትም ይኸው እንደኾነ /፩/፤
© እንዲኽ ካልኾነ ግን ብንጦምም፣ ብንጽልይም፣ ብንመጸውትም፣ ቤተ ክርስቲያን ብንመላለስም፣ መባ ብናቀርብም መሥዋዕታችን ኹሉ ፋንድያ እንደኾነ /፪፡፫/፤
© ምንም ያኽል ኃጢአተኞች ብንኾንም ልንመለስ እንደሚገባን /፫፡፯/፤ እርሱም ከየትኛውም ዓይነት ኃጢአታችን እንደሚያነጻን፤ የእርሱ ገንዘብ እንደምንኾንና አንድ ሰው የሚያገለግለው ልጁን እንደሚምረው የሠራዊት #ጌታ_እግዚአብሔርም እንደሚምረን /፫፡፲፯/፤
© እንዲኽ ከተመለስን በኋላ የጽድቅ ፀሐይ #ክርስቶስ ላይጠልቅ በሕይወታችን ላይ አብርቶ እንደሚኖር እንማራለን፡፡

…ተመስጦ…
ቸርና ቅዱስ #እግዚአብሔር ሆይ! በሕይወታችን እጅግ ጐስቋሎች ኾነን ስምኽን ብናቃልለውም ደካሞች ነንና በከንፈራችን ብቻ ሳይኾን በገቢርም እንድናውቅኽ እንድናመልክኽም እርዳን፡፡ ሊቀ ካህናችን #ኢየሱስ_ክርስቶስ ሆይ! እውነተኛ ካህናት እንድንኾን እርዳን፡፡ አባቶቻችን ካህናት ቅዱስ ሥጋኽና ክቡር ደምኽን ለምእመናን ለኹላችንም ሲያቀብሉ እኛም በክህነታችን ቁራሽ ዳቦና ኩባያ ውኃ ለድኾች መስጠት እንድንለማመድ እርዳን፡፡ የጽድቅ ፀሐይ #ኢየሱስ_ክርስቶስ ሆይ! ቅድስናኽ እኛን ቢቀድሰን እንጂ ኃጢታችን አንተን አያረክስኽምና በእኛ ዘንድ እደር፡፡ በኹለንተናችን ላይም አብራ፡፡ ጨለማን ከእኛ ዘንድ አስወግድልን፡፡ ለዘለዓለሙ አሜን!!!
#ጳጒሜን_1

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የተባረከ የጳጒሜን ወር ባተ። በዚህች ቀን ጳጒሜን አንድ #ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቅ የታሰረበት፣ የወንጌላዊ የቅዱስ #ዮሐንስ ረድእ #የዑቲኮስ_ሐዋርያና #ቀሲስ_አባ_ብሶይ የእረፍታቸው መታሰቢያ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቅ

ጳጒሜን አንድ ቀን በዚህች ዕለት ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ወደ እሥር ቤት ገብቷል። ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ፦ ንጉሡ ሔሮድስ የወንድሙን የፊልጶስን ሚስት ሔሮድያዳን በማግባቱና በመሰል ክፋቶቹ ቅዱስ ዮሐንስ ይገስጸው ነበር። ቅዱስ ዮሐንስ "መምሕር ወመገስጽ ዘኢያደሉ ለገጽ" "ፊት አይቶ የማያዳላ" ነውና ገሰጸው።

ሔሮድስ ቅዱሱን ይፈራው ያከብረውም ነበር። በኋላ ግን ፈቃደ ሥጋው ስላየለበት በተለይ ደግሞ ከሰባት ቀናት በኋላ ልደቱን ሲያከብር እንዳይረብሸው በመስጋት በዚህች ቀን በወታደሮቹ አስይዞ እሥር ቤት ውስጥ
ጥሎታል። ለሰባት ቀናት በጨለማ ውስጥ አሥሮ መስከረም 2 ቀን አስቆርጦታል።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዑቲኮስ_ሐዋርያ

በዚህች ቀን የወንጌላዊ ዮሐንስ ረድእ ሐዋርያና ሰማዕት የከበረ ዑቲኮስ አረፈ ።

ይህም ቅዱስ ወንጌላዊ ዮሐንስን ሲያገለግለውና ሲታዘዘው ኖረ። ከዚያም ከሐዋርያ ጳውሎስ ጋራ ሔደ እርሱም የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ስም እንዲሰብክ አዘዘው በአረማውያንና በዮናናውያንም መካከል ሰበከ። የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስንም ወደማወቅ ብዙዎችን መለሳቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው።

የጣዖታት ቤቶችን አፍርሶ አብያተ ክርስቲያናትን ሠራ። ከከሀድያንም ብዙ መከራ ደረሰበት መታሠርና ብዙ ቀኖች ግርፋቶችን በመቀበል፤ የ #እግዚአብሔርም መልአክ ወደ እሥር ቤት ከምግብ ጋር መጥቶ ይመግበዋል።

ከዚህም በኋላ ከእሳት ውስጥ ጣሉት እሳቱም ከቶ አልነካውም ሁለተኛም ለአንበሶች ጣሉት እነርሱም እንደ በጎች ሆኑለት። ከዚህም በኋላ ወደቍስጥንጥንያ ሀገር ሔደ። ሲሔድም የ #እግዚአብሔር መልአክ ይመራውና ያጸናናው ነበር ተጋድሎውንም ፈጽሞ በበጎ ሽምግልና ወደ እግዚአብሔር ሔደ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቀሲስ_ብሶይ_ሰማዕት

በዚችም ቀን የአባ ሖር ወንድም ቀሲስ ብሶይ በሰማዕትነት ሞተ። ይህም ቅዱስ ከአንፆኪያ አገር ክብር ካላቸው ወገኖች ውስጥ ነው ስለ ዕውቀቱና ስለ ሃይማኖቱ ጽናት ቅስና ተሾመ።

ወንድሙ አባ ሖርና እናቱ ወደ ግብጽ አገር ሔደው በሰማዕትነት ከሞቱ በኋላ እርሱም ተነሥቶ ወደ እስክንድርያ ሥጋቸውን ያይ ዘንድ ሔደ። ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች ሰጠ ከሦስት እንጀራና ከሚመረጐዛት ከአንዲት የሰኔል በትር በቀር ምንም አልያዘም ነበር።

ወደ እስክንድርያ አገርም በደረሰ ጊዜ የዘመዶቹ በድን ወዳለበት ሰዎች መርተው አደረሱት የእናቱንና የወንድሙንም ሥጋ በአየ ጊዜ ከእርሳቸው ስለ መለየቱ መሪር ልቅሶን አለቀሰ። ከዚህም በኋላ ወደ መኰንኑ ሒዶ በፊቱ ቁሞ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ።

ለመኰንኑም የአባ ሖር ወንድም እንደሆነ ነገሩት መኰንኑም ታላቅ የደንጊያ ምሰሶ በሆዱ ላይ እንዲአቆሙበት አዘዘ ይህንንም በአደረጉበት ጊዜ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ውስጥ ሰጠ።

ከዚህም በኋላ ደግሞ ሥጋውን ከወንድሙና ከእናቱ ሥጋ ደግሞ ቍጥራቸው ሰማንያ ስምንት ከሆነ ከሌሎች ሰማዕታት ሥጋ ጋር በአንድነት ያቃጥሉ ዘንድ መኰንኑ አዘዘ ወደ እሳት በጨመሩአቸውም ጊዜ ከቶ እሳቱ አልነካቸውም።

ምዕመናን ሰዎችም መጥተው የከበሩ የአባ ሖርንና የወንድሙ የአባ ብሶይን የእናታቸውንም ሥጋ ወሰዱ። ሀገሯ ዲብቅያ የሚባል የቅድስት ዳሞንንም ሥጋ፣ ሀገሩ በረሞን የሚባል የቅዱስ ቢማኮስንም ሥጋ፣ ጡልያ ከሚባል አገር የመጣ የውርሱኑፋን ሥጋም፣ አብስላሲ ወደሚባል አገር እስከሚያደርሷቸው በመርከብ ጫኗቸው። የስደቱ ወራት እስከሚፈጸም አክብረው ወስደው በመልካም ቦታ አኖሩዋቸው።

ከዚህም በኋላ አብያተ ክርስቲያን ተሠርቶላቸው ሥጋቸውን በውስጣቸው አኖሩ ከእርሳቸውም ተአምራት ተገለጡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆኑ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእኒህ ቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጳጉሜን_1#ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ጳጒሜ_1_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ፊልጵስዩስ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹² ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ይህ የደረሰብኝ በእውነት ወንጌልን ለማስፋት እንደ ሆነ ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ።
¹³ ስለዚህም እስራቴ ስለ ክርስቶስ እንዲሆን በንጉሥ ዘበኞች ሁሉና በሌሎች ሁሉ ዘንድ ተገልጦአል፥
¹⁴ በጌታም ካሉት ወንድሞች የሚበዙት ስለ እስራቴ ታምነው የእግዚአብሔርን ቃል እንዲነግሩ ያለ ፍርሃት ከፊት ይልቅ ይደፍራሉ።
¹⁵ አንዳንዶች ከቅንአትና ከክርክር እንኳ ሌሎች ግን ከበጎ ፈቃድ የተነሣ ክርስቶስን ይሰብኩታል፤
¹⁶ እነዚህ ወንጌልን መመከቻ ለማድረግ እንደ ተሾምሁ አውቀው በፍቅር ይሰብካሉ፥
¹⁷ እነዚያ ግን በእስራቴ ላይ መከራን ሊያመጡብኝ መስሎአቸው፥ ለወገናቸው የሚጠቅም ፈልገው በቅን አሳብ ሳይሆኑ ስለ ክርስቶስ ያወራሉ።
¹⁸ ምን አለ? ቢሆንም በሁሉ ጎዳና፥ በማመካኘት ቢሆን ወይም በቅንነት ቢሆን፥ ክርስቶስ ይሰበካል ስለዚህም ደስ ብሎኛል።
¹⁹ ወደ ፊትም ደግሞ ደስ ይለኛል፤ ይህ በጸሎታችሁና በኢየሱስ ክርስቶስ መንፈስ መሰጠት ለመዳኔ እንዲሆንልኝ አውቃለሁና፥
²⁰ ይህ ናፍቆቴ ተስፋዬም ነውና፤ በአንድ ነገር እንኳ አላፍርም ነገር ግን በሕይወት ብኖር ወይም ብሞት፥ ክርስቶስ በግልጥነት ሁሉ እንደ ወትሮው አሁን ደግሞ በስጋዬ ይከብራል።
²¹ ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ፥ ሞትም ጥቅም ነውና።
²² ነገር ግን በስጋ መኖር ለእኔ የሥራ ፍሬ ቢሆን፥ ምን እንድመርጥ ኣላስታውቅም።
²³ በእነዚህም በሁለቱ እጨነቃለሁ፤ ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፥ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና፤
²⁴ ነገር ግን በሥጋ መኖሬ ስለ እናንተ እጅግ የሚያስፈልግ ነው።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ዮሐንስ 5
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ ክርስቶስ ነው ብሎ በኢየሱስ የሚያምን ሁሉ ከእግዚአብሔር ተወልዶአል፥ ወላጁንም የሚወድ ሁሉ ከእርሱ የተወለደውን ደግሞ ይወዳል።
² እግዚአብሔርን ስንወድ ትእዛዛቱንም ስናደርግ የእግዚአብሔርን ልጆች እንድንወድ በዚህ እናውቃለን።
³ ትእዛዛቱን ልንጠብቅ የእግዚአብሔር ፍቅር ይህ ነውና፤ ትእዛዛቱም ከባዶች አይደሉም።
⁴ ከእግዚአብሔር የተወለደ ሁሉ ዓለምን ያሸንፋልና፤ ዓለምንም የሚያሸንፈው እምነታችን ነው።
⁵ ኢየሱስም የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ ከሚያምን በቀር ዓለምን የሚያሸንፍ ማን ነው?
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 18
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²¹ ነገር ግን ሲሰናበታቸው፦ የሚመጣውን በዓል በኢየሩሳሌም አደርግ ዘንድ ይገባኛል እግዚአብሔር ቢፈቅድ ግን ወደ እናንተ ደግሞ እመለሳለሁ አላቸው። ከኤፌሶንም በመርከብ ተነሣ።
²² ወደ ቂሣርያም በደረሰ ጊዜ ወጥቶ ለቤተ ክርስቲያን ሰላምታ ከሰጠ በኋላ ወደ አንጾኪያ ወረደ።
²³ ጥቂት ቀንም ቆይቶ ወጣ፥ ደቀ መዛሙርትንም ሁሉ እያጸና በገላትያ አገርና በፍርግያ በተራ አለፈ።
²⁴ በወገኑም የእስክንድርያ ሰው የሆነ ነገር አዋቂ የነበረ አጵሎስ የሚሉት አንድ አይሁዳዊ ሰው ወደ ኤፌሶን ወረደ፤ እርሱም በመጻሕፍት እውቀት የበረታ ነበረ።
²⁵ እርሱ የጌታን መንገድ የተማረ ነበረ፥ የዮሐንስንም ጥምቀት ብቻ አውቆ በመንፈስ ሲቃጠል ስለ ኢየሱስ ይናገርና በትክክል ያስተምር ነበር።
²⁶ እርሱም በምኵራብ ገልጦ ይናገር ጀመር። ጵርስቅላና አቂላም በሰሙት ጊዜ፥ ወስደው የእግዚአብሔርን መንገድ ከፊት ይልቅ በትክክል ገለጡለት።
²⁷ እርሱም ወደ አካይያ ማለፍ በፈቀደ ጊዜ፥ ወንድሞቹ አጸናኑት፥ ይቀበሉትም ዘንድ ወደ ደቀ መዛሙርት ጻፉለት፤ በደረሰም ጊዜ አምነው የነበሩትን በጸጋ እጅግ ይጠቅማቸው ነበር፤
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጳጒሜ_1_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"እስመ ጽድቀ ወምጽዋተ ያበድር እግዚአብሔር። እግዚአብሔር ይሁብ ክብረ ወሞገሰ። እግዚአብሔር ኢያስተፄንሶሙ እምበረከቱ ለእለ የሐውሩ በየዋሃት"። መዝ 83፥11።
“እግዚአብሔር አምላክ ምሕረትንና እውነትን ስለ ወደደ፥ ሞገስንና ክብርን ይሰጣል፤ እግዚአብሔር በቅንነት የሚሄዱትን ከመልካም ነገር አያሳጣቸውም።” መዝ 83፥11።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጳጒሜ_1_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ማቴዎስ 14
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ በዚያ ዘመን የአራተኛው ክፍል ገዥ ሄሮድስ የኢየሱስን ዝና ሰማ፥
² ለሎሌዎቹም፦ ይህ መጥምቁ ዮሐንስ ነው፤ እርሱ ከሙታን ተነሥቶአል፥ ስለዚህም ኃይል በእርሱ ይደረጋል አለ።
³ ሄሮድስ በወንድሙ በፊልጶስ ሚስት በሄሮድያዳ ምክንያት ዮሐንስን አስይዞ አሳስሮት በወህኒ አኑሮት ነበርና፤
⁴ ዮሐንስ፦ እርስዋ ለአንተ ትሆን ዘንድ አልተፈቀደም ይለው ነበርና።
⁵ ሊገድለውም ወዶ ሳለ፥ ሕዝቡ እንደ ነቢይ ስለ አዩት ፈራቸው።
⁶ ነገር ግን ሄሮድስ የተወለደበት ቀን በሆነ ጊዜ፥ የሄሮድያዳ ልጅ በመካከላቸው ዘፈነች ሄሮድስንም ደስ አሰኘችው፤
⁷ ስለዚህም የምትለምነውን ሁሉ እንዲሰጣት በመሐላ ተስፋ አደረገላት።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #ቅዱስ_ዮሐንስ_ወልደ_ነጎድጓድ ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችን ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ጾመ_ዮዲት

ዮዲት በናቡከደነጾር ዘመነ መንግሥት ትኖር የነበረች ባሏ የሞተባትና በንጽሕና ተጠብቃ፣ በጸሎትና በሕገ እግዚአብሔር የምትኖር ሴት ነበረች፡፡ በዚያን ጊዜ ንጉሡ ሥልጣኑን መከታ በማድረግ የእግዚአብሔርን ሕዝብ በግድ እያስገደደ እጅ መንሻ ይቀበል ነበር፡፡ የመንግሥቱን ትእዛዝ ያልተቀበለውንም እየገደለ፣ ጭፍሮቹ ኃያልነቱንና ገናናነቱን በዓዋጅ በጦር አዛዦች ጭምር እያሳወጀ፣ በርካታ የጦር ሠራዊቶችን አሰልፎ ከአይሁድ ከተማ ገባ፡፡ በዚያም ነዋሪዎችን በማስፈራራት የመንግሥቱን ትእዛዝ ያልተቀበሉትን ሁሉ እያሳደደ ስላስጨነቃቸው ማቅ ለብሰው፣ አመድ ነስንሰውና ድንጋይ ተንተርሰው ወደ ፈጣሪያቸው በመጮህ መለመን ጀመሩ። በጭካኔ የተሞላው የጦር አበጋዙ ሆሎፎርኒስም ይበልጥ እጅግ እንዲሰቃዩ ውኃ የሚቀዱበትን ስፍራ ተቆጣጠረው፤ በግዴታ ማርኮም እጅ እንዲሰጡ እንዳደረጋቸው በመጽሐፈ ዮዲት ላይ ተጽፏል፡፡ በአካባቢው ይኖር የነበረ ዖዝያን የተባለ አንድ ሰው የአባቶቻቸው አምላክ ጸሎታቸውን እንዲሰማቸው ለአምስት ቀናት በትዕግሥት ይጾሙና ይጸልዩ ዘንድ ሕዝቡን መከራቸው፤ እነርሱም በትዕግሥት ሊጠብቁ ተስማሙ፡፡ (ዮዲ. ፪፥፪)

የእስራኤል ልጆች የናቡከደነጾርን ጦር ብንችል ተዋግተን እንረታለን፤ ካልሆነም እጅ እንሰጣለን በማለት ይመካከሩ ጀመር። ሆኖም ዮዲት #እግዚአብሔርን የምትፈራ ብቸኛዋ ሴት እርሷ ነበረችና ምክክራቸውን ስትሰማ ለምን «እግዚአብሔር ያድነናል አትሉም» ብላ ገሠጸቻቸው፡፡ ማቅ በመልበስ፣ አመድ በመነስነስና ድንጋይ በመንተራስም ሱባኤ ገባች። በሦስተኛው ቀንም #እግዚአብሔር አምላክ ሕዝቧን የምታድንበትን ጥበብ ገለጸላት፤ ዮዲትም #እግዚአብሔር የሰጣትን ውበት ተጠቅማ ሕዝቧን ከጥፋት የምትታደግበትን ጥበብ ተረዳች። (ዮዲት ፯፥፲)

የክት ልብሷን ለብሳ፣ ሽቱ ተቀብታና ተውባ የጠላት ሠራዊት ወዳሉበት የጦር ሰፈር በድፍረት አመራች፡፡ ሠራዊቱም ውበቷን አይተው እጅግ በመደነቅ «ይህችስ ለአለቃችን ትገባለች» ተባብለው ከጦር መሪያቸው ዘንድ ወሰዷት። እርሷም ቀድማ ማምለጫ መንገድ አዘጋጅታ ነበርና ወደ አዛዡ ከገባች በኋላ «ክቡር ጌታዬ ሆይ ርስት ተወስዶብኛል፤ እንድትመልስልኝ አስቀድሜ ደጅ ልጠና መጥቻለውና ርዳኝ፤ ትብብርህ አይለየኝ» አለችው፡፡ በስሜት ፈረስ ታውሮ የነበረው የሠራዊቶቹ አዛዥም የጠየቀችውን እንደሚፈጽምላት ቃል ገባላት። ባማረ ድንኳን እንዲያስቀምጧት ሎሌዎቹን አዘዘ። ዮዲትም የተሰጣትን ጥበብ ተጠቅማ፣ መውጣት ስትፈልግ የምትወጣበትን እና የምትገባበትን ዕድል በ

#እግዚአብሔር አጋዥነት ዐወቀች፡፡ ከቀናት በኃላ የጦር አበጋዙ ለሠራዊቱ የምሳ ግብዣ አዘጋጅቶ ዮዲትን ከጎኑ አስቀመጣት፤ ከበሉና ከጠጡ በኋላም ሁሉን ሰው አስወጣ፤ እልፍኙን በመዝጋት ከእርሷ ጋር ብቻውን ሆነ፤ ነገር ግን እንቅልፍ ጣለው፡፡ እርሷም ወደ አምላኳ ጸለየች፤ ፈጣሪዋ እንዲረዳትም አጥብቃ ለመነች። በኋላም ከራስጌው ሰይፍ አንስታ አንገቱን ቀላችው፤ በድኑንም ከመሬት ጣለችው። የሆሎፎርኒስን ሞት ሠራዊቱ ሲሰሙ አውራ እንደሌለው ንብ ተበተኑ፤ ከፊሎቹ ሞቱ። እስራኤላውያንም ከሞት ተርፈው በ #እግዚአብሔር ኃይል ድል አደረጉ፤ በደስታም ፈጣሪያቸውን አመሰገኑ። (ዮዲት ፰፥፪)

ይህ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ታሪክ የሚያስረዳን ዮዲት ጠላቶቿን ድል ያደረገችው በጾምና በጸሎት እንደሆነ ነው፡፡ ለእኛም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ምንም እንኳ ወርኃ ጳጉሜን የፈቃድ ጾም ቢሆንም በሀገራችን የተጋረጠውን ችግር እናልፍ ዘንድ በፈቃደኝነት እንጾማለን። #እግዚአብሔር አምላካችን ለሁላችንም ጥበብ ሰጥቶናል። ይህም ችግሮችን ሁሉ የምንፈታበት መንገድ ነው። በዚህም የዓመተ መሸጋገሪያና የክረምቱ ወር ማብቂያ በመሆኑ ዕለተ ምጽአት ስለሚታሰብበት በየዓመቱ በጳጉሜ ወር ከሌሊት ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን ተገኝተን ጠበል በመጠመቅ፣ በማስቀደስና በመጸለይ እንዲሁም ሥጋ ወደሙን በመቀበል ልናሳልፍ ይገባል። ዕለተ ምጽአትም ከዚህ ዓለም ወደ ወዲያኛው ዓለም መሸጋገሪያችን ነውና በቀኙ እንቆም ዘንድ እንጾማለን፡፡ የሚመጣውን አዲስ ዘመንም በንጽሕና ለመቀበል ስላለፈው ዓመት ኃጢአታችን ንስሓ የምንገባበት ጾምም ነው።

ከተጋረጠብን ችግር « #እግዚአብሔር ያድነናል» በማለት ልክ እንደ ዮዲት ሱባኤ ገብተን፣ ማቅ ለብሰን፣ አመድ ነስንሰንና ድንጋይ ተንተርሰን አብዝተን ልንጾምና ልንጸልይ ይገባል፡፡ ሊለያየን፣ ሊነጣጥለን፣ ሊበታትነን እና ሊገድለን ካሰበው እንዲሁም ፍቅርን፣ መተሳሰብንና አንድነትን ሊነፍገን ከቃጣው ጠላትና ሃይማኖታችንን ሊያስተወን ከሚመጣ ፀረ ሃይማኖት እንድናለን። ስለዚህ ከፊታችን ያለችውን አምስቱን የጳጉሜን ቀን በፍቅር፣ በአንድነትና በሃይማኖት ጸንተን፣ ጾመን፣ ጸልየን ለዘመነ ማቴዎስ እንድንደርስ #እግዚአብሔር አምላካችን ይርዳን፤ አሜን።

#ወስብሐት_ለእግዚአብሔር
+++ #ልብስህን_ማን_ወሰደው? +++

በአንድ ወቅት "አባ ሰራብዮን" ወደ እስክንድርያ በሄደ ጊዜ፣ በገበያም ስፍራ አንድ ከልብስ የተራቆተ ነዳይ አገኘ፡፡ ለራሱም ‹ይህ ደሃ ሰው ታርዞ መነኩሴ የተባልኩ እኔ እንዴት ለብሼ እታያለሁ? በእውነት ይህ ‹ታርዤ አልብሳችሁኛልና› ብሎ የተናገረው ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ አይደለምን? በዚህ ብርድ እየተሰቃየ ነው እኮ!› ብሎ ፈጥኖ የገዛ ልብሱን ከራሱ በማውለቅ ይለብስ ዘንድ ለዚያ ደሃ ሰጠው፡፡ ከዚያም በእጁ ያለውን መጽሐፍ ቅዱስ እንደያዘ እርቃኑን በጎዳናው ዳር ተቀመጠ፡፡ እርሱን የሚያውቀው አንድ የከተማው ባለጠጋ ሰው አባ ሰራብዮን ባለበት ሥፍራ ሲያልፍ ተመልክቶት ወደ እርሱ ቀረበና ‹አባ ሰራብዮን ሆይ ልብስህን ማን ወሰደው?› ሲል ጠየቀው፡፡ ቅዱሱም በእጁ ወደ ያዘው መጽሐፍ ቅዱስ እየጠቆመ ‹ልብሴን የወሰደው ይህ ነው!› አለው፡፡ ያም ባለጠጋ አዲስ ልብስ ገዝቶ አለበሰው። ከዚህም በኋላ አባ ሰራብዮን ከእርሱ እንደ ተለየ በመንገድ ሲሄድ ዕዳውን መክፈል ባለመቻሉ እያንገላቱ ወደ ወኅኒ ቤት የሚወስዱትን አንድ ሰው ተመለከተ፡፡ እርሱም የያዘውን መጽሐፍ ቅዱስ ፈጥኖ በመሸጥ የዚያን ሰው ዕዳ ከፍሎ ነጻ አደረገው፡፡ ይህንንም አድርጎ ጉዞውን ሲጀምር እንደ ገና ሌላ የታረዘ ነዳይ ሲለምን ተመለከተ። አባ ሰራብዮንም እንደ ቀድሞው የለበሰውን ልብስ አውልቆ ለነዳዩ በመስጠት እርሱ እርቃኑን ወደ በአቱ ተመለሰ፡፡ ደቀ መዛሙርቱም መምህራቸውን እርቃኑን ባዩት ጊዜ ደንግጠው ‹መምህር! ልብስህ ወዴት አለ?› ብለው ጠየቁት፡፡ እርሱም ‹መጸወትኩት› አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም መልሰው ‹እኛን የምታጽናናበት መጽሐፍ ቅዱስህስ አባታችን?› ሲሉ ደግመው ጠየቁት፡፡ አባ ሰራብዮንም ‹በእጄ የነበረው መጽሐፍ ቅዱስ ሁል ጊዜ ‹ሂድ ያለህን ሽጠህ ለድሆች ስጥ› ይለኛል፤ ስለዚህ ያለኝ እርሱ ነበር እርሱንም ሸጥኩት› አላቸው፡፡

ምንጭ :–Paradise of the monks, P 89

ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እንደሚናገረው ምጽዋት የፊት መብራት ናት፡፡ አንድ ሰው በጨለማ ሲጓዝ ከኋላው መብራት ቢያበሩለትም እንኳ ከፊቱ የሚቀድመው የገዛ የአካሉ ጥላ እንቅፋት እየሆነበት ይጥለዋል፡፡ ወደ ፊት ያለውን መንገድ አጥርቶ እያየ ያለ ስጋት ለመሄድ እንዲችል የግድ የፊት መብራት ያስፈልገዋል፡፡ ጾም ፣ጸሎት እና ሌሎች መንፈሳዊ ትሩፋት እንደ ኋላ መብራት ናቸው፡፡ የፊት መብራት የተሰኘች ምጽዋት ካልታከለችባቸው እነዚህ ብቻቸውን ዋጋን አያሰጡንም፡፡ ከምጽዋት በላይ ታላቅ ነገር እንደሌለ ልንረዳ ይገባል፡፡ ዓለም ሁሉ ከነበረበት የበደል ዕዳ የዳነው ቸር እረኛ በሆነው በመድኃኔ ዓለም በአካሉ ምጽዋትነት (በሥጋው በደሙ መሰጠት) ነውና!!!
#ጳጒሜን_2

#ቅዱስ_ቲቶ_ሐዋርያ

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጳጒሜን ሁለት በዚህች ቀን ሐዋርያ ጳውሎስ መልእክት የጻፈለት የከበረ ሐዋርያ ቲቶ አረፈ። የዚህም ቅዱስ ትውልዱ ቀርጤስ ከሚባል አገር ነው። እርሱም ለዮናናውያን ወገን ለሆነ ለአገረ ገዥው እኅት ልጅዋ ነው።

ከታናሽነቱም የዮናናውያንን ትምህርትና ፍልስፍና ተምሮ እጅግ አዋቂ ሆነ በጠባዩም ቅን ሥራው ያማረ ለድኆችና ለችግረኞች መራራት የሚወድ ነው። ከሌሊቶችም በአንዲቱ ቲቶ ሆይ ስለ ነፍስህ ድህነት ተጋደል ይህ ዓለም አይጠቅምህምና የሚለውን በሕልሙ አየ። ከእንቅልፉም በነቃ ጊዜ ደነገጠ ምን እንደሚሠራም አላወቀም።

ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት የ #መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ትምህርት በተሰማ ጊዜ ብዙዎች ሰዎችም ተአምራቱን እርስበርሳቸው ተነጋገሩ የአክራጥስ መኰንንም ሰምቶ አደነቀ ዕውነት እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ወይም የሥራይ እንደሆነ ሊያውቅ ሽቶ የሚልከው ብልህ ሰው ፈለገ የእኅቱንም ልጅ ቲቶንን መረጠው ከእርሱ የሚሻል የለምና። ሲልከውም ታላቅና ጥልቅ የሆነ ምርመራ እንዲመረምር አዘዘው።

ቲቶም ከይሁዳ ምድር በደረሰ ጊዜ የ #መድኃኒታችንን ድንቆች የሆኑ ተአምራቶቹን አየ ሕይወትነት ያላቸው ትምህርቶቹንም ሰማ። ከዮናናውያንም በትምህርታቸውና በሥራቸው መካከል ታላቅ የሆነ መራራቅን አግኝቶ የዮናናውያን ሃይማኖታቸው የቀናች እንዳልሆነች ለይቶ ዐወቀ።

ከዚህም በኋላ በክብር ባለቤት በ #ጌታችን_ኢየሱስ አመነ፤ ደቀ መዝሙሩም ሁኖ ተከተለው። ወደ እናቱ ወንድም ወደ አገረ ገዥውም መልእክትን ላከ የክብር ባለቤት #ጌታ_ኢየሱስ_ክርስቶስ የሚያስተምረውና የሚሠራው ዕውነት እንደሆነ ነገረው።

#ጌታችንም ከሰባ ሁለቱ ደቀ መዛሙርቱ ውስጥ የተቆጠረ አደረገው ከዕርገቱም በኋላ ከሐዋርያት ጋር የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተቀብሎ ከእሳቸው ጋር በሀገሮች ሁሉ ዙሮ አስተማረ። #ጌታችንም ጳውሎስን ጠርቶ ሐዋርያው በአደረገው ጊዜ ያን ጊዜ ሐዋርያ ጳውሎስን ተከተለው በብዙ አገሮችም ወንጌልን ሰበከ።

የከበረ ጳውሎስም በሮሜ ከተማ ምስክር ሆኖ ከሞተ በኋላ ቅዱስ ቲቶ ወደ ሀገረ አክራጥስ ተመለሰ ቤተ ክርስቲያንም ሠርቶ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው በዙሪያቸው ላሉ አገሮችም እንዲሁ አደረገ።

ከዚህም በኋላ ሐዋርያዊ አገልግሎቱን ፈጽሞ ወደ ወደደው #እግዚአብሔር ሔደ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ቲቶ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጳጒሜን_2)
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ጳጒሜ_2_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ቲቶ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹-² የእግዚአብሔር ባሪያና የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የሆነ ጳውሎስ፥ በእግዚአብሔር ለተመረጡት እምነት እንዲሆንላቸው በዘላለምም ሕይወት ተስፋ እንደ አምልኮት ያለውን እውነት እንዲያውቁ የተላከ፤ ስለዚህም ሕይወት የማይዋሽ እግዚአብሔር ከዘላለም ዘመናት በፊት ተስፋ ሰጠ፥
³ በዘመኑም ጊዜ፥ መድኃኒታችን እግዚአብሔር እንዳዘዘ፥ ለእኔ አደራ በተሰጠኝ ስብከት ቃሉን ገለጠ፤
⁴ በሃይማኖት ኅብረት እውነተኛ ልጄ ለሚሆን ለቲቶ፤ ከእግዚአብሔር አብ ከመድኃኒታችንም ከጌታ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ምሕረት ሰላምም ይሁን።
⁵ ስለዚህ ምክንያት የቀረውን እንድታደራጅ በየከተማውም፥ እኔ አንተን እንዳዘዝሁ፥ ሽማግሌዎችን እንድትሾም በቀርጤስ ተውሁህ፤
⁶ የማይነቀፍና የአንዲት ሚስት ባል የሚሆን፥ የሚያምኑም ልጆች ያሉት፥ ስለ መዳራትም ወይም ስለ አለመታዘዝ የማይከሰስ ማንም ቢኖር፥ ሹመው።
⁷ ኤጲስ ቆጶስ፥ እንደ እግዚአብሔር መጋቢ፥ የማይነቀፍ ሊሆን ይገባዋልና፤ የማይኮራ፥ የማይቆጣ፥ የማይሰክር፥ የማይጨቃጨቅ፥ ነውረኛ ረብ የማይወድ፥
⁸ ነገር ግን እንግዳ ተቀባይ፥ በጎ የሆነውን ነገር የሚወድ፥ ጠንቃቃ፥ ጻድቅ፥ ቅዱስ፥ ራሱን የሚገዛ ይሁን፤
⁹ ሕይወት በሚገኝበት ትምህርት ደግሞ ሊመክር ተቃዋሚዎቹንም ሊወቅስ ይችል ዘንድ፥ እንደተማረው በታመነ ቃል ይጽና።
¹⁰ የማይታዘዙና ከንቱ የሚናገሩ የሚያታልሉ ይልቁንም ከተገረዙት ወገን የሚሆኑ ብዙ ናቸውና፤
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
2ኛ ጴጥሮስ 3
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁷ አሁን ያሉ ሰማያትና ምድር ግን እግዚአብሔርን የማያመልኩት ሰዎች እስከሚጠፉበት እስከ ፍርድ ቀን ድረስ ተጠብቀው በዚያ ቃል ለእሳት ቀርተዋል።
⁸ እናንተ ግን ወዳጆች ሆይ፥ በጌታ ዘንድ አንድ ቀን እንደ ሺህ ዓመት፥ ሺህ ዓመትም እንደ አንድ ቀን እንደ ሆነ ይህን አንድ ነገር አትርሱ።
⁹ ለአንዳንዶች የሚዘገይ እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም፥ ነገር ግን ሁሉ ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም እንዳይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሣል።
¹⁰ የጌታው ቀን ግን እንደ ሌባ ሆኖ ይመጣል፤ በዚያም ቀን ሰማያት በታላቅ ድምፅ ያልፋሉ፥ የሰማይም ፍጥረት በትልቅ ትኵሳት ይቀልጣል፥ ምድርም በእርስዋም ላይ የተደረገው ሁሉ ይቃጠላል።
¹¹-¹² ይህ ሁሉ እንዲህ የሚቀልጥ ከሆነ፥ የእግዚአብሔርን ቀን መምጣት እየጠበቃችሁና እያስቸኰላችሁ፥ በቅዱስ ኑሮ እግዚአብሔርንም በመምሰል እንደ ምን ልትሆኑ ይገባችኋል? ስለዚያ ቀን ሰማያት ተቃጥለው ይቀልጣሉ የሰማይም ፍጥረት በትልቅ ትኵሳት ይፈታል፤
¹³ ነገር ግን ጽድቅ የሚኖርባትን አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደ ተስፋ ቃሉ እንጠብቃለን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 4
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
³¹ ከጸለዩም በኋላ ተሰብስበው የነበሩበት ስፍራ ተናወጠ፥ በሁሉም መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው፥ የእግዚአብሔርንም ቃል በግልጥ ተናገሩ።
³² ያመኑትም ሕዝብ አንድ ልብ አንዲትም ነፍስ ነበሩአቸው፥ ገንዘባቸውም ሁሉ በአንድነት ነበረ እንጂ ካለው አንድ ነገር ስንኳ የራሱ እንደ ሆነ ማንም አልተናገረም።
³³ ሐዋርያትም የጌታን የኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ በታላቅ ኃይል ይመሰክሩ ነበር፤ በሁሉም ላይ ታላቅ ጸጋ ነበረባቸው።
³⁴ በመካከላቸው አንድ ስንኳ ችግረኛ አልነበረምና፤ መሬት ወይም ቤት ያላቸው ሁሉ እየሸጡ የተሸጠውን ዋጋ ያመጡ ነበርና፥
³⁵ በሐዋርያትም እግር አጠገብ ያኖሩ ነበር፤ ማናቸውም እንደሚፈልግ መጠን ለእያንዳንዱ ያካፍሉት ነበር።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጳጒሜ_2_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ቀዳሚሃ ለጥበብ ፈሪሃ እግዚአብሔር። ምክር ሠናይት ለኵሉ ዘይገብራ። ወስብሐቲሁኒ ይነብር ለዓለም"። መዝ 110፥10።
“የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፥ ለሚያደርጓትም ሁሉ ደኅና ማስተዋል አላቸው፤ ምስጋናውም ለዘላለም ይኖራል።” መዝ 110፥10።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ጳጒሜ_2_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሉቃስ 10
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ ከዚህም በኋላ ጌታ ሌሎቹን ሰብዓ ሾመ፥ ሁለት ሁለትም አድርጎ እርሱ ሊሄድበት ወዳለው ከተማና ስፍራ ሁሉ በፊቱ ላካቸው።
² አላቸውም፦ መከሩስ ብዙ ነው፥ ሠራተኞች ግን ጥቂቶች ናቸው፤ እንግዲህ የመከሩን ጌታ ለመከሩ ሠራተኞች እንዲልክ ለምኑት።
³ ሂዱ፤ እነሆ፥ እንደ በጎች በተኵላዎች መካከል እልካችኋለሁ።
⁴ ኮረጆም ከረጢትም ጫማም አትያዙ፤ በመንገድም ለማንም እጅ አትንሡ።
⁵ ወደምትገቡበት ቤት ሁሉ አስቀድማችሁ፦ ሰላም ለዚህ ቤት ይሁን በሉ።
⁶ በዚያም የሰላም ልጅ ቢኖር፥ ሰላማችሁ ያድርበታል፤ አለዚያም ይመለስላችኋል።
⁷ በዚያም ቤት ከእነርሱ ዘንድ ካለው እየበላችሁና እየጠጣችሁ ተቀመጡ፤ ለሠራተኛ ደመወዙ ይገባዋልና። ከቤት ወደ ቤት አትተላለፉ።
⁸ ወደምትገቡባትም ከተማ ሁሉ ቢቀበሉአችሁ፥ ያቀረቡላችሁን ብሉ፤
⁹ በእርስዋም ያሉትን ድውዮችን ፈውሱና፦ የእግዚአብሔር መንግሥት ወደ እናንተ ቀረበች በሉአቸው።
¹⁰ ነገር ግን ወደምትገቡባት ከተማ ሁሉ ባይቀበሉአችሁ፥ ወደ አደባባይዋ ወጥታችሁ፦
¹¹ ከከተማችሁ የተጣበቀብንን ትቢያ እንኳን እናራግፍላችኋለን፤ የእግዚአብሔር መንግሥት ግን ወደ እናንተ እንደ ቀረበች ይህን እወቁ በሉ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #ቅዱሳን_ሐዋርያት_ቅዳሴ ነው። መልካም የሐዋርያው የቅዱስ ቲቶ የዕረፍት በዓልና የጾም፣ የጸሎትና የምሕላ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ጳጒሜን_3

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ጳጒሜን ሦስት በዚህች ዕለት የሰዎች ሁሉ ጸሎት የሚያርግባት #ርኅወተ_ሰማይ ትባላለች፣
የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ #ቅዱስ_ሩፋኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው፣ ለእግዚአብሔር ልጅ ምሳሌው የሆነ #የካህኑ_መልከጼዴቅ መታሰቢያው ነው፣ የኢትዮጵያ ንጉሥ መልካም ስም አጠራር ያለው #ቅዱስ_ዘርዐ_ያዕቆብ አረፈ፣ ሰንዱን ከሚባል አገር #ቅዱስ_ሰራጵዮን አረፈ፣ አቡነ ቀጸላ ጊዮርጊስ ዕረፍታቸው ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ርኅወተ_ሰማይ

ጳጒሜን ሦስት በዚህች ዕለት የሰዎች ሁሉ ጸሎት የሚያርግባት፣ አራተኛው መጋቢ ኮከብ የሚያልፍባት፣ ለሰው ልጆች ከፈጣሪያቸው ጸጋ በረከት የሚሰጥባት ዕለት ስለሆነች ርኅወተ ሰማይ (ሰማይ የሚከፈትባት) ቀን ትባላለች።

አሁን በሰማይ መዘጋት መከፈት ኑሮበት አይደለም። የሰው ልጆችን ልመና ቅዱሳን መላእክት ያለ ከልካይ የሚያሳርጉበት አንድም ቅዱስ ሩፋኤል የዓመቱን የጸሎት መዝገብ የሚከፍትበት ቀን ስለሆነ እንዲህ ተባለ እንጂ።

እመቤታችን #ድንግል_ማርያም ለአጼ ናዖድ እንደ ነገረቻቸው በዚህች ዕለት ሁሉም ቅዱሳን ስለሚታሰቡ፣ የ #እግዚአብሔር የምሕረት መዝገቡ ስለሚከፈት፣ ዕለቷን ክብርት ያሰኛታል። በቅዱስ ሩፋኤል አበጋዝነት (መሪነት) በዚህች ዕለት ለዓመት የሚበቃ ምሕረት ይገኛል።

ስለዚህም አባቶቻችን በዚህች ሌሊት ሦስት መቶ ስልሳ አምስት አቡነ ዘበሰማያትን ሲጸልዩ ያድራሉ። በሌላ ወገን ደግሞ የጌታ ዳግም ምጽዓቱ መታሰቢያ እንደ መሆኗ ትልቅ ትኩረትም ይሰጣታል። ቸሩ #ጌታችን ከተከፈተች ገነት ከተነጠፈች ዕረፍት ሁላችንንም ያድርሰን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሩፋኤል_ሊቀ_መላእክት

በዚህች ቀን የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ የሩፋኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው። እርሱም ከመላእክት አለቆች ሦስተኛ የሆነ ነው። ደግሞም ከእስክንድርያ ውጭ በደሴት የታነፀች ቤተ ክርስቲያኑ በከበረ ሊቀ ጳጳሳት ቴዎፍሎስ ዘመን በውስጧ ተአምር የተገለጸባት የከበረችበት ነው።

ይህም እንዲህ ነው ሀብታም ሴት ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስ መጥታ ሳለ ከእርሷ ጋርም ብዙ ሰው ነበረ። ከባሏም የወረሰችው ብዙ ገንዘብ አላት በሊቀ ጳጳሳቱ ቤት አንጻር ያለውን ኮረብታ አስቆፈረችው በጥቅምት ወር ዐሥራ ስምንት ቀን እንደጻፍን የወርቅ መዝገብ ተገለጠ።

በዚያም ወርቅ ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናትን አነፀ ከእርሳቸውም አንዲቱ የመላእክት አለቃ በሆነ በከበረ መልአክ ሩፋኤል በስሙ የታነፀች ይህች ናት። ሥራዋንም በፈጸመ ጊዜ እንደዛሬው በዚች ቀን አከበራት።

ብዙ ምእመናንም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጸች ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና። የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው። ወደ ክብር ባለቤት #እግዚአብሔርም በከበረ መልአክ ሩፋኤል ስም ጮኹ ያን ጊዜ ይህ የከበረ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ እንዲህ አለው እግዚአብሔር አዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጽ ጸጥ ብለህ ቁም። አንበሪውም ጸጥ ብሎ ቆመ አልታወከም በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆነ።

ይቺም ቤተ ክርስቲያን እስላሞች እስከተነሡበት ዘመን ኖረች ከዚህም በኋላ ሁለተኛ ያ አንበሪ ተናወጸ ደሴቲቱም በላይዋ ከሚኖሩ ብዙ ሕዝብ ጋራ ሠጠመች።

#ዳግመኛም የቊስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስ ጻድቅ ለሆነ ንጉሥ አኖሬዎስ ተናገረ። እንዲህም አለው ንጉሥ ሆይ እኛ ወዳንተ ልንመጣ በመርከብ እንደተሳፈርን ዕወቅ በጒዞ ላይ ሳለንም በቀዳሚት ሰንበት ቀን በደሴት ውስጥ ታናሽ ቤተ ክርስቲያን አየን ወደ ወደቡም ደርሰን በዕለተ እሑድ ሥጋውን ደሙን እንቀበል ዘንድ ወደርሷ ሔድን።

ለዚያች ቤተ ክርስቲያንም በጐኗ ታናሽ ገዳም አገኘን በውስጧም ወንድሞች መነኰሳት አሉ በክብር ባለቤት ጌታችንም ፈቃድ ወደ ርሳቸው ደረስን ። መነኰሳቱንም በቀደሙ አባቶች ዘመን የተጻፈ አሮጌ መጽሐፍ በእናንተ ዘንድ እንዳለ እጽናናበት ዘንድ እርሱን ሰጡኝ አልኳቸው። እንዲህም ብለው መለሱልኝ እኛ ትርጓሜያቸውን የማናውቀው መጻሕፍቶች በዕቃ ቤት አሉ። እኔም አያቸው ዘንድ ወደዚህ አምጡልኝ አልኳቸው። በአመጡአቸውም ጊዜ መረመርኳቸው #ጌታችንም በደቀ መዛሙርቱ ፊት ያደረጋቸውን ኃይሎችና ድንቆች ተአምራቶችን ስለ ሰማይና ምድርም ጥንተ ተፈጥሮ አገኘሁ።

ሁለተኛም ስመረምር ስለ ሰባቱ ሊቃነ መላእክት ሹመትና መዐርግ አባቶቻችን ንጹሐን ሐዋርያት የጻፉትን አገኘሁ ይኸውም #ጌታችን በደብረ ዘይት ከእሳቸው ጋራ እያለ የመለኮቱን ምሥጢር በገለጠላቸው ጊዜ። ሐዋርያትም እንዲህ ብለው እንደለመኑት #ጌታችንና ፈጣሪያችን ሆይ የከበረ የሩፋኤልን ክብሩን ታስረዳን ዘንድ እንለምንሃለን በየትኛው ዕለት በየትኛው ወር ሾምከው።

ከባልንጀሮቹ የመላእክት አለቆችም ትክክል ነውን የበዓሉን መታሰቢያ ያደርጉ ዘንድ በዓለም ውስጥ ስለርሱ እንድናስተምር እርሱም በመከራቸው ጊዜ ይረዳቸው ዘንድ በአማላጅነቱም በአንተ ዘንድ ይቅርታን ያገኙ ዘንድ።

ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ አዘዘና ከሦስተኛው ሰማይ ሦስቱ የመላእክት አለቆች ሚካኤል፣ ገብርኤልና ሩፋኤል መጡ በታላቅ ደስታም ለክብር ባለቤት ለ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሰገዱ። #ጌታችንም ሩፋኤልን እንዲህ አለው የክብርህን ገናናነት የባልንጀሮችህንም ልዕልናቸውን እንዲያውቁ ለሐዋርያት ንገራቸው።

ያን ጊዜም ለ #ጌታችን ሰገደ ይነግራቸውም ዘንድ ጀመረ እንዲህም አላቸው ደገኛው የመላእክት አለቃ ሚካኤል ለሁሉም መላእክት አለቃቸው ነው ስሙም ይቅር ባይ ይባላል።

ሁለተኛም የመላእክት አለቃ ገብርኤል የስሙ ትርጓሜ አገልጋይም ጌታም የሆነ የዓለሙ ሁሉ እመቤት የሆነች አምላክን የወለደች ቅድስት #ድንግል_ማርያምን ያበሠራት ነው። የእኔም ስሜ ሩፋኤል ነው ይህም ደስ የሚያሰኝ ቸር መሐሪ ቅን የዋህ ማለት ነው እኔም ኃጢአተኞችን በ #እግዚአብሔር ዘንድ አልከሳቸውም ከኃጢአታቸው በንስሓ እስኪመለሱ ስለ ቅንነቴ በእነርሱ ላይ እታገሣለሁ እንጂ።

በሃያ ሦስቱ የመላእክት ነገድ ሠራዊት ላይ #እግዚአብሔር የሾመኝ እኔ ሩፋኤል ነኝ #እግዚአብሔር አብን ይቅር ባይ ልጁን አጽናኝና አዳኝ የሆነ #መንፈስ_ቅዱስን እናመሰግነው ዘንድ።

በደብረ ጽዮን በሚደረገው የሺህ ዓመት ተድላ ደስታ የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ የክብር ጽዋን በሚሰጣቸው ጊዜ ለቅዱሳኖቹ በጎ ነገርን እንድሰጣቸው #እግዚአብሔር ያዘዘኝ ሩፋኤል እኔ ነኝ። ደግሞም በዚች ቀን ከዕፀ ሕይወት ዐጽቅ ወስጄ ለተመረጡ ክርስቲያኖች በእጄ እንድሰጣቸው #እግዚአብሔር ያዘዘኝ ሩፋኤል እኔ ነኝ።

የሰማያት መዛግብትም ከእጄ በታች ተጠብቀው የሚኖሩ እኔ ሩፋኤል ነኝ። እኔም #እግዚአብሔር እንዳዘዘኝ እከፍታቸዋለሁ እዘጋቸዋለሁም።

በምድር ሰው ለባልንጀራው ስለ ስሜ በጎ ነገር ቢያደርግ እኔ በመከራው በችግሩ ረዳዋለሁ ወይም የሹመቴን ነገር የሚጽፍ ወይም ከቅዱሳን ጋራ ስሜን የሚያስብ ወይም በስሜ ለቊርባን የሚሆነውን የሚሰጥ ወይም በበዓሌ ቀን ምጽዋትን የሚሰጥ ይኸውም #እግዚአብሔር በሊቃነ መላእክት ክብር የሾመኝና ያከበረኝ ጳጕሚን ሦስት ቀን ነው። ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት እስከማስገባው በብርሃን ሠረገላ እኔ እሸከመዋለሁ በምድር ላይ ከቶ እንደርሱ ያለ የማይገኝ መዐዛው እጅግ ጣፋጭ በሆነ ሽቱ ነፍሶቻቸው እርሱን በማሽተት ደስ እንዲላቸው አደርጋለሁ።
ሐዋርያት ሆይ በ #እግዚአብሔር ፊት እስከምትቆሙ እጠብቃችሁ ዘንድ ከእኔ ርዳታን ሹ። የዚህ የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሩፋኤል ተአምራቶቹ ብዙ ናቸው ስለእኛ ይማልድ ዘንድ የበዓሉን መታሰቢያ ልናደርግ ይገባናል።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_መልከጼዴቅ

በዚህችም ቀን ለ #እግዚአብሔር ልጅ ምሳሌው የሆነ የመልከጼዴቅ መታሰቢያው ነው። መልከጼዴቅም ዐሥራ አምስት ዓመት በሆነው ጊዜ ከአዳም ሥጋ ጋር እንዲልከውና በምድር መካከል እንዲያኖረው #እግዚአብሔር ኖኅን አዘዘው እርሷም ቀራንዮ ናት። የዓለም #መድኃኒት_ክርስቶስም መጥቶ በዚያ እንደሚሠዋ አዳምንም ከልጆቹ ሁሉ ጋር እንደሚያድነው አመለከተው።

ከዚህም በኋላ በአባቱ በኖኅ ትእዛዝ ሤም መልከጼዴቅን በሥውር ወሰደው የ #እግዚብሔርም መልአክ እየመራቸው ሔደው ወደ ቀራንዮ ተራራም አደረሳቸው መልከጼዴቅም ክህነትን ተሾመ። ዐሥራ ሁለት ደንጊያዎችንም ወስዶ መሠዊያ ሠራ ከሰማይ የወረደለትንም ኅብስትና ወይን መሠዊያ በሠራቸው ደንጊያዎች ላይ መሥዋዕትን አሳረገ።

ምግቡንም መላእክት ያመጡለታል ልብሱም ዳባ ነው በአባታችን አዳም ሥጋ ዘንድ ሲያገለግል ኖረ። አብርሃምም ከጦርነት ነገሥታትን ድል አድርጎ በተመለሰ ጊዜ ኅብስትንና ወይንን አቀረበለት አብርሃምም ከገንዘቡ ሁሉ ከዐሥር አንድ ሰጠው እርሱ ካህንም ንጉሥም ሁኖ ተሹሟልና።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አፄ_ዘርዓ_ያዕቆብ_ጻድቁ

በዚህችም ቀን የኢትዮጵያ ንጉሥ መልካም ስም አጠራር ያለው ዘርዐ ያዕቆብ አረፈ። ዘርዐ ያዕቆብ ብሎ ስሙን መልአክ ነው ያወጣለት፡፡ ሲወለድም ብርሃን ቤቱን ሞለቶት ታይቷል፡፡ ግማደ መስቀሉን ከአባቱ ከዐፄ ዳዊት ተረክቦ በማስመጣት በግሸን አስቀምጦታል፡፡ ንግሥቲቱ የዐፄ ዳዊት ሚስት የጻድቁን የደብረ ቢዘኑን የአቡነ ፊሊጶስን እግራቸውን አጥባቸው ስትጨርስ የእግራቸውን እጣቢ ከጠጣችው በኃላ የእምነቷን ጽናትና ጥልቀት አይተው ጻድቁ ባደረባቸው መንፈስ ቅዱስ ትንቢትን በመናገር "ከማኅፀንሽ ፍሬ ታላቅ ጻድቅ ልጅ ይወጣል" ብለው ትንቢት ነገሯት፡፡ በትንቢታቸውም መሠረት ታላቁ ጻድቅ ንጉሥ ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ተወልዱ፡፡

ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ለሀገራችንም ሆነ ለቤተ ክርስቲያናችን ታላቅ ውለታ ውለዋል፡፡ ጣዖት አምልኮን ከሃገራችን ለማጥፋት ብዙ ሺህ ካህናትን አሰልጥነው በመላ አገራችን አሰማርተዋል፡፡ የኑፋቄ ችግሮችን ለመቅረፍ ጉባኤያትን አዘጋጅተዋል፡፡ ተአምረ ማርያምን ጨምሮ ከ11 ያላነሱ መጻሕፍትን በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ደርሰው ለአገልግሎት አብቅተዋል፡፡ ብዙ መጻሕፍትን ከውጪ አስመጥተው አስተርጉመዋል፡፡ ሰው ሁሉ ለእመ ብርሃንና ለቅዱስ መስቀሉ ፍቅር እንዲገዛ ጥረት አድርገዋል፡፡ እመቤታችንን በፍጹም ልባቸው ከመውደዳቸው የተነሳ ዛሬም ድረስ በሃገራችን #ድንግል_ማርያም "የዘርዓ ያዕቆብ እመቤት" እየተባለች ትጠራለች፡፡ ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን አንጸው ብዙ ሥርዓቶችም በሊቃውንት እንዲሠሩ አድርገው ሌሎች ብዙ በጐ ተግባራትንም ፈጽሞ በዚህች ዕለት በሰላም ዐርፈዋል፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሰራጵዮን_ዘሰንዱን

በዚህችም ቀን ሰንዱን ከሚባል አገር ቅዱስ ሰራጵዮን አረፈ። ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትን ትርጓሜያቸውንም ተማረ የዚህንም ዓለም ገንዘብ ሁሉ ትቶ ወደ አረሚ አገር ሔደ ራሱንም በሃያ ብር ሸጦ ማገልገል ጀመረ የሽያጩንም ዋጋ ጠበቀው። እንጀራ ሳይበላ ውኃ ሳይጠጣ ከስሕተታቸው ይመልሳቸው ዘንድ ሁል ጊዜ ወደ #እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር።

ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት በሆነ በ #ክርስቶስ አሳመናቸው ሕግንና ሥርዓትንም ሁሉ አስተማራቸው ከዚህም በኋላ ስለርሳቸው ራሱን ባሪያ አድርጎ እንደሸጠ እንጂ እርሱ ባሪያ እንዳልሆነ ነገራቸው ሽያጩንም ለድኆች እንዲሰጡት ሰጣቸው።

ከዚህም በኋላ መንካያውያን ወደሚባሉ ሕዝቦች ሒዶ ለነርሱም ራሱን ሸጠ የክብር ባለቤት ወደሆነ #ክርስቶስ እምነት እስከመለሳቸው ድረስ ተገዛላቸው። ከዚህም በኋላ ደግሞ ወደ ሮሜ አገር ሒዶ በሰላም እስከ አረፈ ድረስ በጾምና በጸሎት እየተጋደለ ኖረ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_ቀፀላ_ጊዮርጊስ

ትውልዳቸው አገው ሲሆን ከብዙ ጽኑ ተጋድሎአቸው በኋላ እንደ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ስድስት ክንፍ የተሰጣቸው ታላቅ አባት ናቸው። አቡነ ቀፀላ ጊዮርጊስ በ16ኛው መ/ክ/ዘ የነበሩ ሲሆን ታላቁን ቀብጽያ አንድነት ገዳምን የመሠረቱት ናቸው። ጻድቁ በመጀመሪያ የአባ አሞኒን ገዳም ለመገደም ወደ ትግራይ ቀብጽያ ሲሄዱ በእግዚአብሔር ታዘው የአቡነ አሞፅን ገዳም በሰማዕቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ ስም መሠረቱ። ገዳሙም "ቀብጽያ አሞፅ ወቀፀላ ጊዮርጊስ አንድነት ገዳም" ተባለ።

አቡነ ቀፀላ ጊዮርጊስ 200 ተከታይ መነኰሳትን አስከትለው ሌሎች 6 አስደናቂ ገዳማትን ገድመዋል። ገዳማቱም ማይወኒ ቅዱስ ሚካኤል፣ ውጅግ ቅዱስ መርቆሬዎስ፣ ጅል ውኃ ቅዱስ ማርቆስ፣ ዶቅላኮ አርባእቱ እንስሳ፣ አንጓ ቅድስት ማርያም እና ድቁል ማርያም ይባላሉ።

ጻድቁ ስድስት ክንፍ እስኪሰጣቸው ድረስ ብዙ ተጋድሎ ያደረጉት በቀብጽያ ገዳም ነው። ዕረፍታቸውም ጳጒሜን 3 ቀን ነው። በዘንዶዎች የሚጠበቀው ይህ አስደናቂ ገዳም በብዙ መልኩ ከሌሎች ገዳማት የተለየ ነው። የገዳሙን አፈር ቅዱሳን መላእክት ናቸው ከገነት ያመጡት። ጌታችን 12 እልፍ መላእክቱን ልኮ ከገነት አፈር አምጥተው በዝናብ አምሳል በቀብጽያ ገዳም ላይ እንዲነሰንሱት አዟቸዋል።

ገዳሙን የተሳለመ ሰው ኢየሩሳሌም በጎልጎታን እንደተሳለመ የሚቆጠርለት ሲሆን በገዳሙ ውስጥ የተቀበረ ሰው ወቀሳ የለበትም። ከአካሉም ላይ ፀጉሩን ወይም ጥፍሩን ቆርጦ በገዳሙ ክልል ውስጥ የቀበረ ሰው ቢኖር መልአከ ሞትን ፈጽሞ እንደማያይና ገዳሙ የሚገኝበት አካባቢ በእግር ለመጓዝ አስቸጋሪ ቢሆንም ቦታውን የረገጠ እስከ 15 ትውልድ ምሕረትን እንደሚያገኝ ጌታችን በቃል ኪዳን አጽንቶታል።

ቀብጽያ ገዳምን ለየት የሚያደርገው ነገር ቢኖር ፈዋሹ ጠበል ከጻድቁ አቡነ አሞፅ መቃነ መቃብር ሥር የሚፈልቅ መሆኑ ነው፡፡ ከዋሻው ሥር የተንጠባጠበው ጠበል ወደ ጠንካራ ዐለትነት የሚቀየር ሲሆን እርሱን ለእምነት የተጠቀሙበት ሰዎች ከተለያዩ በሽታዎች ተፈውሰዋል፡፡ በቅርቡም ከ6 ዓመት በፊት በዚህ እምነት የተሻሸች አንዲት ሴት ከዘመኑና መድኃኒት ካልተገኘለት ከHIV በሽታና ከመካንነቷ ተፈውሳ ልጅ ወልዳለች፡፡ ይህ አስደናቂ ቀብጽያ ገዳም ፍልፍል ዋሻ ቤተ መቅደስ ቢሆንም ከጊዜና ብዛት ጉዳት ስለደረሰበትና የሚያድሰው አካል ስላላገኘ በአሁኑ ወቅት ሌላ አዲስ ቤተ መቅደስ እየታነጸ ይገኛል፡፡

በቀብጽያ ገዳም ውስጥ 336 ዓመት የሆነው የወይራ ዛፍ የሚገኝ ሲሆን በቅርቡ ስውራን የሆኑ ቅዱሳን ሦስት ጊዜ ደወል ሲደውሉበት ተሰምቷል፡፡ ገዳሙን አቡነ ቀፀላ ጊዮርጊስ ይገድሙት እንጂ በቦታው ላይ አቡነ አሞፅ አስቀድመው መቶ ዓመት በታላቅ ተጋድሎ ኖረውበታል። አቡነ አሞፅ ትውልዳቸው ሸዋ ሲሆን የመነኰሱት ደብረ ሊባኖስ በአቡነ ዮሐንስ ከማ እጅ ነው፡፡ አቡነ ዮሐንስ ከማ በመልአክ ታዘው 10 መነኰሳት 500 ሕዝብ ተከትሏቸው ወደ ትግራይ ሲሄዱ ሳምረ ወረዳ ላይ ሲደርሱ ሕዝቡ ቢራብ ዋርካ ዕለቱን አብቅለው ባርከው መግበውታል፣ ውኃም አፍልቀው አጠጥተውታል፡፡ ከዚኽም በኋላ የበቁትንና ቅዱሳን የሆኑትን ዓሥሩን መነኰሳት ገዳም እንዲገድሙ ወደተለያዩ ቦታዎች ላኳቸው፡፡ ከእነዚኽም ዓሥር ቅዱሳን መነኰሳት መካከል አቡነ አሞፅ አንዱ ናቸው፡፡ እርሳቸውም
ጽላተ ማርያምን ይዘው በቅዱሳን መላእክት ታጥራ ወደምትገኘው ምድረ ቀብጽያ መጥተው መቶ ዓመት በታላቅ ተጋድሎ ኖሩ።

አቡነ አሞፅ ሰቆቃወ ድንግል የሚባለውን የእመቤታችን መከራ የሚተርከውን ድንቅ ድርሰት ሙሉውን ክፍል በብራና ላይ በሥዕል ገልጸው በክብር አስቀምጠውታል፡፡ ከሰማይ የወረደላቸው የወርቅ መስቀላቸውም በገዳሙ ይገኛል፡፡

አቡነ አሞፅ በ1592 ግንቦት 26 አርብ ቀን ሲያርፉ ጌታችን ከድንግል እናቱ ጋር ተገልጾላቸው ከላይ ያየናቸውን አስደናቂ ቃልኪዳኖች ከሰጣቸው በኋላ ነፍሳቸውን እመቤታችን አቅፋ አሳረገቻቸው፡፡ ዐፅማቸው ያረፈበትን መካነ መቃብር ታላላቅ ዘንዶዎች ይጠብቁታል፡፡ ጠበላቸውም የፈለቀው ከመቃብራቸው ሥር ነው፡፡ ቦታው በስውራን ስለሚገለገል የከበሮ ድምፅ የሚሰማ ሲሆን የእጣንም ሽታ ይሸታል፡፡ ከአባታች ከአቡነ ቀፀላ ጊዮርጊስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸውም ይማረን!።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በመልአኩና በቅዱሳኑ አማላጅነት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ጳጉሜን_3#ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ እና #ከገድላት_አንደበት)
2024/09/21 11:28:28
Back to Top
HTML Embed Code: