Telegram Web Link
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

            #የካቲት ፳፪ (22) ቀን።

እንኳን የፋርስ ንጉሥ ልጅ በጸሎቱ ከነበረባት ጋኔን ለፈወሳት #ለኤጲስቆጶስ_ለአባ_ማሩና ለዕረፍቱ በዓል መታሰቢያና በከሀዲ በዲዮቅልጥያኖስ ዘመን #በፋርስ_አገር_ለተገደሉ_ሰማዕታት ለሥጋቸው ለፈለሰበት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በዚች ቀን በተጨማሪ ከሚታሰቡ፦ ከከበረ #ከአባ_ቡላና_ከሦስት_መቶ_ሰማንያ ሰማዕታት ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።

                            
#አባ_ማሩና፦ ኤጲስቆጶስ ማሩናንም ስለ ድንቆች ተአምራቶቹ ስለ ትሩፋቱና ስለ ጽድቁ የአኖርዮስና የአርቃድዎስ አባት ታላቁ ቴዎዶስዮስ ንጉሥ ላከው ከእርሱም ጋር እጅ መንሻ በመካከላቸው ስለ አለው ፍቅር ተላከ። ወደ ሳቦር ወደ ፋርስ ንጉሥም በደረሰ ጊዜ ታላቅ ክብርንም አከበረው በቤተ መንግሥቱም እልፍኝ ውስጥ አኖረው።

ይህ ቅዱስም የንጉሡ ልጅ ጋኔን አድሮበት እንደታመመች በሰማ ጊዜ የከበረ አባ ማሩና ብላቴናዪቱን ጠርቶ በፊቱ አቁሞ በላይዋ ጸለየ ጋኔኑም ከእርሷ ወጥቶ ዳነች ንጉሡም ልጁ እንደ ዳነች አይቶ እጅግ ደስ አለው የአባ ማሩናንም ፍቅርና አክብሮት ጨመረ። ከዚህም በኋላ አባ ማሩና በፋርስ አገር በሰማዕትነት ስለሞቱ የከበሩ ሰማዕታት ሥጋቸውን ስለ መሰብሰብ ከንጉሥ ዘንድ ፈለገ ንጉሡም የሰማዕታትን ሥጋቸውን ይሰብስቡ ዘንድ አዘዘ ያች ቤተ ክርስቲያንም በዚች ዕለት ከበረች። ዳግመኛም በታላቋ ከተማ ውስጥ በከበረ አባ ማሩና ስም ያማረች ቤተ ክርስቲያንን ሠሩ እርሷም ማረፊያ የተባለች ናት።

ከዚህም በኋላ ይህ አባት ወደ ንጉሥ ቴዎዶስዮስ ተመልሶ በሮሜ አገር ሁለት ዓመት ተቀመጠ የእነዚያ ሰማዕታት ቤተ ክርስቲያን በከበረችበት በዚች በየካቲት22 ዕለት ዐረፈ ከቤተ ክርስቲያኒቱም ክብር ጋር በዓሉንና መታሰቢያውን የሚከብሩበት ሆነ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የአባ ማሩና በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የየካቲት 22 ስንክሳር።

                            
"#ሰላም_ለማሩና_ሠናየ_ተልእኮ_ቀሲስ። ወዓዲ ካዕበ ኤጲቆጶስ። ቤተ ሰማዕታት ሐኒፆ በአገረ ፋርስ። በዕለተ ቀደሳ #በስመ_ኢየሱስ_ክርስቶስ። ተጸውዐ ዮም ለመርዓ ሐዳስ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የየካቲት_22

                            
#የዕለቱ_ምስባክ፦ "ዘይሰማዕ ግብር ሊተ ምሕረተከ በጽባሕ። እስመ ኪያከ ተወከልኩ እግዚኦ። ምርሐኒ እግዚኦ ፍኖተ እንተ ባቲ አሐውር"። መዝ 142፥8-9። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 12፥1-14፣ 1ኛ ጴጥ 1፥6-10 እና የሐዋ ሥራ 16፥16-19።  የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 13፥10-18። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።

@sigewe

https://www.tg-me.com/joinchat-AAAAAFGQ22bI0Ij80hYpFA

https://www.facebook.com/profile.php?id=100063896616886

https://www.facebook.com/profile.php?id=61552828743736&mibextid=ZbWKwL
††† እንኳን ለታላቁ ሐዋርያና ሰማዕት ቅዱስ ፖሊካርፐስ እና ቅዱስ አውሳብዮስ ሰማዕት ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!†††

††† ቅዱስ ፖሊካርፐስ †††

†††ቅዱስ ፖሊካርፐስ:-
*ከ70 እስከ 156 ዓ/ም የነበረ::
*ዮሐንስ ወንጌላዊ በራዕዩ ከመሰከረላቸው 7ቱ አብያተ ክርስቲያናት የአንዱ (የሰርምኔስ) ዻዻስ የነበረ::
*ከሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ቃል በቃል የተማረና ደቀ መዝሙሩ የነበረ አባት ነው::

ታላቁ አግናጥዮስ (ምጥው ለአንበሳ) የዚህ ቅዱስ ባልንጀራ ነበር:: ከ46 ዓመታት በላይ በፍፁም ትጋት ቤተ ክርስቲያንን አገልግሎ አረማውያን በ86 ዓመቱ በአደባባይ በእሳት አቃጥለው ገድለውታል:: አባቶቻችን "ሐዋርያዊ" ሲሉ ይጠሩታል::

††† ዳግመኛ በዚህ ዕለት በ1888 ዓ/ም በቅዱስ ጊዮርጊስ ምልጃና ረዳትነት አባቶቻችን አድዋ ላይ ጣልያንን ድል አድርገዋል:: ቅዱስ ጊዮርጊስን እና ደጉን ንጉሥ ዳግማዊ አፄ ምኒልክን እናስባቸው ዘንድ ይገባል::

††† ቅዱስ አውሳብዮስ ሰማዕት †††

በቤተ ክርስቲያን ስመ ጥር ከሆነ ቅዱሳን ሰማዕታት አንዱ ቅዱስ አውሳብዮስ ነው:: ተወልዶ ያደገው በምድረ አንጾኪያ (ሶርያ) ሲሆን ዘመኑም 3ኛው መቶ ክ/ዘ ነው:: አባቱ ታላቁ ሰማዕት ቅዱስ ፋሲለደስ ነው:: እናቱም ቡርክት ሶፍያ ትባላለች::

ሰማዕቱ ቅዱስ መቃርስ ትንሽ ወንድሙ መሆኑም ይታወቃል:: ቅዱሳን እነ ፊቅጦር : ገላውዴዎስ : ቴዎድሮስ : ዮስጦስ : አባዲር . . . ባልንጀሮቹ ሆነው ኑረዋል::

ቅዱስ አውሳብዮስ የቅዱስ ፋሲለደስ ፍሬ ነውና ጾምና ጸሎትን የሚያዘወትር ሆነ:: በቤተ መንግስት ውስጥ ስንት የተደላደለና የተቀማጠለ ነገር እያለ እርሱ ግን እንደ ቡሩክ አባቱ ንጽሕናን መረጠ:: የወርቅ ካባ ደርቦ ሲሰግዱ ማደር ምን ይደንቅ!

ያ ዘመን እጅግ ግሩም የሆኑ ቅዱሳን በቤተ መንግስት የታዩበት ነበር:: ቅዱስ አውሳብዮስ በምጽዋት : በጾምና ጸሎት የሚኖር ቢሆንም በየጊዜው ወደ ጦርነት ይላክ ነበር:: ምክንያቱም እርሱ ኃያል የጦር ሰው : የሠራዊቱም ሁሉ አለቃ ነውና:: በሔደበት ሁሉም በእግዚአብሔር ኃይል ድል ያደርግ ነበር::

አንድ ጊዜም ከፋርስ ቁዝ ሰዎች ጋር ጦርነት ውስጥ ገቡ:: ይህንን ጦርነት በበላይነት እንዲመሩ ቅዱሳን አውሳብዮስና ዮስጦስ በኑማርያኖስ (ንጉሡ ነው) ተሹመው ወደ ሠልፍ ገቡ::

በጦርነቱ ጐዳና ላይ ሳሉ ግን አንድ አታላይ ሰላይ በጠላት እጅ እንዲወድቁ አደረጋቸው:: የተማረኩና የታሠሩ ዮስጦስና ሠራዊቱ ሲሆኑ ቅዱስ አውሳብዮስ ይህን ሰምቶ አለቀሰ:: ወደ ፈጣሪውም እየተማጸነ ለመነ::

በዚህ ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ አረጋጋው:: ድል መንሳትንም ሰጥቶት አደጋ ጥሎ ባልንጀራውን ዮስጦስን አስፈታው:: ጠላቶቻቸውንም እያሳደዱ አዋረዷቸው:: "ወመጠውከኒ ዘባኖሙ ለጸርየ" እንዳለ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ::

ከዚህ ሠልፍ በሁዋላ ቅዱሳን አውሳብዮስና ዮስጦስ በድል አድራጊነት ወደ አንጾኪያ ሲመለሱ ግን አንጀትን የሚቆርጥ ዜና ደረሳቸው:: አምላከ አማልክት ክርስቶስ ተክዶ ጣዖታት (እነ አዽሎን : አርዳሚስ) እየተሰገደላቸውም ደረሱ:: ይህንን ያደረገ ደግሞ የሰይጣን ታናሹ የሆነ ርጉም ዲዮቅልጢያኖስ ነው::

ቅዱሳኑንም ለጣዖት ስገዱ ሲል በአደባባይ ጠየቃቸው:: ድፍረቱ ያናደደው ቅዱስ አውሳብዮስ ግን ሰይፉን መዞ ወደ ንጉሡ ተራመደ:: ያን ጊዜ ንጉሡ ሸሽቶ ሲያመልጥ መሣፍንቱን ሜዳ ላይ በተናቸው:: አባቱ ቅዱስ ፋሲለደስ ባይገለግለው ኖሮ ኃያል ነውና ባላተረፋቸው ነበር::

ከቀናት በሁዋላ ግን ቅዱስ አውሳብዮስ በጾምና ጸሎት ሰንብቶ ሰማዕት ለመሆን ልቡ ቆረጠ:: ቅዱስ ሚካኤልና አባቱ ፋሲለደስም በምክር አበረቱት:: እርሱም በአጭር ታጥቆ በከሐዲው ንጉሥ አደባባይ ላይ ቆመ::

"እኔ ክርስቲያን ነኝ:: ክርስቶስን አመልካለሁ:: ለእርሱም እገዛለሁ:: ጣዖታት ግን ድንጋዮቸ ናቸውና አይጠቅሙም:: የሚሰግድላቸውም የረከሠ ነው::" ሲል አሰምቶ ተናገረ:: ንጉሡ ዲዮቅልጢያኖስ እዚያው ሊገድለው ፈልጐ ነበር:: ቅዱሱ ተወዳጅ ሰው ነበርና ሁከት እንዳይነሳ አውሳብዮስ ወደ አፍሪቃ (ግብጽ) ሒዶ እንዲገደል ተወሰነበት::

በምድረ ግብጽም አረማውያን በእሳትም : በግርፋትም : በስለትም ብዙ አሰቃዩት:: ቅዱስ ሚካኤል ግን ገነትን አሳይቶ ከደዌው እየፈወሰ ተራዳው:: በመጨረሻም በዚህች ቀን ገድለውት አክሊለ ክብርን ተቀዳጅቷል::

††† አምላከ ቅዱሳን ሰማዕታት ጽናታቸውን አድሎ ከበረከታቸው ይክፈለን::

††† የካቲት 23 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ፖሊካርፐስ ሐዋርያዊ ሰማዕት (የሰርምኔስ ዻዻስ)
2.ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት (አባቶቻችንን አድዋ ላይ የረዳበት)
3.ቅዱስ አውሳብዮስ ሰማዕት (የቅዱስ ፋሲለደስ ልጅ)
4.ቅዱስ አውስግንዮስ ሰማዕት

††† ወርኀዊ በዓላት
1.ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት
2.ቅዱስ ሰሎሞን ንጉሠ እስራኤል
3.አባ ጢሞቴዎስ ገዳማዊ
4.አባ ሳሙኤል
5.አባ ስምዖን
6.አባ ገብርኤል

††† "በሰርምኔስም ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልዐክ እንዲህ ብለህ ጻፍ:- ሞቶ የነበረው: ሕያውም የሆነው: ፊተኛውና መጨረሻው እንዲህ ይላል:-
'መከራህንና ድህነትህን አውቃለሁ . . . እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን: የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ::" †††
(ራእይ 2:8)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
††† እንኳን ለጻድቁ አባታችን ቅዱስ አቡፋና እና ቅዱስ እንጦኒ ሐዲስ ሰማዕት ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† አባ አቡፋና †††

††† ታላቁ አባ አቡፋና፦
በምድረ ግብጽ ተጋድሏቸውን የፈፀሙ፣
በመዐልት አምስት መቶ ጊዜ በሌሊትም አምስት ጊዜ አቡነ ዘበሰማያትን ይጸልዩ የነበሩ፣
በአርባ ቀን አንድ ጊዜ ብቻ እህል ይቀምሱ የነበሩና ሙሉ ዘመናቸውን በበርሃ በታላቅ ጽሙና የፈፀሙ አባት ናቸው።

ጻድቁ በጣም የሚታወቁት ከማበጡ የተነሳ እጅግ ግዙፍ በነበረ እግራቸው ነው። ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ ስለ መድኃኔ ዓለም ፍቅር አልቀመጥም፤ አልተኛም ብለው ለአሥራ ስምንት ዓመታት በመቆማቸው ነው።

አሥራ ስምንት ዓመት የመቆማቸው ዜናስ እንደምን ነው ቢሉ፦
አንድ ቀን "እኔ ግን ከዚህ ዓለም የምለየው መቼ ይሆን?" ሲሉ አሰቡ። በእርግጥ ይህንን ሐሳብ ብዙ ሰዎች ሊያስቡት ይችላል። ሐሳቡ ጠቃሚም ያልተፈቀደም ነው።
፩. "ጠቃሚ ነው።" ያልኩት አንድ ሰው ሞት እንዳለ ካወቀ ወይም 'መቼ ነው የምሞተው' ብሎ ካሰበ ንስሐ ይገባል፤ ክፋትን ይተዋል ተብሎ ስለሚታመን ነው። ወገኔ ሁሉ እንደ አውሬ ሲባላ፣ ደም ሲያፈስ፣ ክፋትን ሲጐነጉን የሚውል "እሞት ባይ" ሳይሆን "እኖር ባይ" ሆኖ ነውና።
ግን ሞት በቅርቡ እንዳለ በኃያሉ አምላክ ፊት ራቁቱን ለፍርድ እንደሚቀርብ ለወገኔ ማን በነገረው!
፪. "ያልተፈቀደ ነው።" ያልኩት ደግሞ በሁለት ምክንያት ነው።
"ኢትበሉ ለጌሰም (ለነገ አትበሉ።)" የሚል አምላካዊ ቃል ስላለ።
ማቴ. ፮፥፴፬
ሰው (በተለይ ዓለማዊው) የሚሞትበትን ቀን ቢያውቅ አጭር ጊዜ ከሆነ ሽብር ጭንቀት ይበላዋል። ወዲህ ደግሞ ጊዜው ረዥም ቢሆን እንደ ሰብአ ትካት (ማለትም በኖኅ ዘመን እንደ ነበሩ ሰዎች) 'ብዙውን ልዝናናበት (ኃጢአት ልሥራበት')ና ንስሐ እገባለሁ።' ይላልና ነው።

በዚያውም ላይ በቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት ቅዱስ ሰውና የነቢያት አለቃ ቅዱስ ሙሴ የሞቱን ጊዜ ጠይቆ እጅግ መቸገሩን መጥቀሱ በራሱ በቂ ነው። ጌታ "ዓርብ ቀን ትሞታለህ።" ብሎት ለሁለት ዓመታት ዓርብ ዓርብ ሲገነዝ ሲፈታ ኑሯል።

በመጨረሻም ዓርብ ቀን ድንገት መልአከ ሞት መጥቶበታል። ስለዚህ "ወድልዋኒክሙ ንበሩ - ተዘጋጅታችሁ ኑሩ። መባላችንን አስበን ልንኖር ግድ ይለናል።
ማቴ. ፳፬፥፵፬

ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና ቅዱስ አቡፋና ይህንን የዕረፍታቸውን ነገር ሲያስቡ ቅዱስ መልአክ ተገልጦ "ተርፈከ አሠርቱ ወሰመንቱ - አሥራ ስምንት ቀርቶሃል።" አላቸው። እርሳቸውም "ጌታዬ አሥራ ስምንት ምን?" ሲሉ ቢጠይቁትም ሳይመልስላቸው ተሠወረ።

ከደቂቃ እስከ ኢዮቤልዩ ብዙ አሥራ ስምንቶች አሉ። እርሳቸው ግን "አሥራ ስምንት ቀን ነው!" ብለው ለጌታ ተሳሉ። ስዕለታቸውም "ከዚህ በኋላ አልቀመጥም።" የሚል ነው። እየጾሙ እየጸለዩ ለአሥራ ስምንት ቀናት ቆሙ። ሞት አልመጣም።

"አሥራ ስምንት ሱባኤ ይሆን!" ብለው አሥራ ስምንት ሱባኤ (መቶ ሃያ ስድስት ቀናት) ቆመው ጸለዩ። አሁንም ሞት አልመጣም። "አይ! አሥራ ስምንት ወር ሊሆን ይችላል።" ብለው ለአሥራ ስምንት ወራት (ለአንድ ዓመት ከስድስት ወር) ቆመው ተጉ። አሁንም ግን ሞት የውኃ ሽታ ሆኖ ቀረ።

ይህን ጊዜ ግን ወደ ፈጣሪ ለመኑ። "ጌታዬ! ያልከኝ ምን አሥራ ስምንት ነው?"
ቅዱስ መልአኩም መጥቶ "አቡፋና ሆይ! የቀረህ አሥራ ስምንት ዓመት ነውና ጽና።" ብሏቸው ተሰወረ። ልብ በሉልኝ "እስክሞት አልቀመጥም።" ብለው ተስለዋል።

ቅዱሱ ገዳማዊ በቃላቸው የሚገኙ እውነተኛ ክርስቲያን ነበሩና ለአሥራ ስምንት ዓመታት እንደተተከለ ምሰሶ ቆመው ጸለዩ፣ ጾሙ። እንዲህ ያሉትን ቅዱሳን ሊቃውንት፦
"ሰላም ለከ ጽኑዕ ከመ ዓምድ
ዘኢያንቀለቅሎ ሞገድ።"
(ማዕበለ ዓለም የማያናውጸው ብርቱ ምሰሶ ሆይ! ምስጋና ይገባሃል።) የሚሏቸው።

ስለ ቅዱሱ የተጻፈ አርኬም፦
"ሰላም ለቁመተ አቡፋና ዘአልቦ ኑታጌ
እስከ ተመሰለ እግሩ ከመ እግረ ነጌ።" ይላል። ከመቆም ብዛት አካላቸው ደቆ እግራቸው የዝሆን እግር እስኪመስል ወፍሮ ነበርና።

††† አባ አቡፋና በዘመናቸው ብዙ ተአምራትን ሠርተው በዚህች ቀን አርፈዋል።

††† ቅዱስ እንጦኒ ሐዲስ ሰማዕት †††

††† ቅዱስ እንጦኒ (Anthony) በትውልዱ ከሶርያ ዐረቦች ሲሆን በቀደመ ሕይወቱ ክርስቲያኖችን ያሳድድ፣ ካህናትን ይደበድብ፣ አብያተ ክርስቲያናትንም ያቃጥል ነበር። እግዚአብሔር በንስሐ ሲጠራው ግን ደግ፣ ጻድቅና ምርጥ ዕቃ ሆኖ ተገኘ። በመጨረሻም ከብዙ መከራ በኋላ ለሰማዕትነት በቅቷል።

††† አምላከ ቅዱሳን የወዳጆቹን ትጋት፣ ጽናት፣ ፍቅርና በረከት ያድለን። ከማስተዋልም አያጉድለን።

††† የካቲት ፳፭ ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
፩.ቅዱስ አባ አቡፋና ጻድቅ
፪.ቅዱስ እንጦኒ ሐዲስ ሰማዕት
፫.ቅዱሳን ሰማዕታት አውሳንዮስ፣ ፊልሞናና ሉቅያ ድንግል (የቅዱስ ጳውሎስ ሐዋርያ ደቀ መዛሙርት)
፬.ቅዱስ ቶና ዲያቆንና ሰማዕት
፭.ቅዱስ ሚናስ ዘሃገረ ቁስ

††† ወርኀዊ በዓላት
፩.ቅዱስ መርቆሬዎስ ሰማዕት
፪.ቅድስት ቴክላ ሐዋርያዊት
፫.ቅዱስ አበከረዙን ሰማዕት
፬.ቅዱስ ዱማድዮስ ሶርያዊ
፭.አቡነ አቢብ (አባ ቡላ)

††† "ኃይል የሰጠኝን ክርስቶስ ኢየሱስን ጌታችንን አመሰግናለሁ። አስቀድሞ ተሳዳቢና አሳዳጅ አንገላችም ምንም ብሆን ይህን አደረገልኝ። ነገር ግን ሳላውቅ ባለማመን ስላደረግሁት ምሕረትን አገኘሁ።" †††
(፩ጢሞ ፩፥፲፪-፲፫)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
†††እንኳን ለታላቁ ሊቅና ጻድቅ ቅዱስ አንስጣስዮስ እና አቡነ ዓምደ ሥላሴ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቅዱስ አንስጣስዮስ ሊቅ †††

††† ቅዱስ አንስጣስዮስ በ4ኛው ክ/ዘመን የተነሳ ሶርያዊ የነገረ መለኮት ሊቅ: ገዳማዊ ጻድቅና የመንበረ አንጾኪያ ሊቀ ዻዻሳት ነበር:: ቅዱሱ ርጉም አርዮስን ካወገዙ 318ቱ ቅዱሳን ሊቃውንት አንዱ ነው:: በወቅቱ ታላላቅ ሊቃነ ዻዻሳት ሱባኤውንና ጉባኤውን የመሩ ሲሆን አንዱ ይህ ቅዱስ ነው::

ከ 5 ዓመታት በሁዋላም ብዙ ድርሳናትን ጽፎ: ሐዋርያዊ አገልግሎቱን ፈጽሞ በ330 ዓ/ም አርፏል:: ያረፈው ግን አርዮሳውያን ባቀረቡት ክስ በሃሰት ተመስክሮበት በግፍ ተሰዶ ነው:: ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ስለ ውለታው የውዳሴ ድርሳን ጽፎለታል::

††† አቡነ ዓምደ ሥላሴ †††

††† እኒህ ታላቅ ጻድቅ ሐዋርያዊ አባት አቡነ ዓምደ ሥላሴ የትውልድ ሃገራቸው ጎጃም ሲሆን የተወለዱት በዚሁ ዕለት (የካቲት 27) ነው:: ጻድቁ በአጼ ሱስንዮስ (በ17ኛው መቶ ክ/ዘ) የነበሩ ድንቅ ሠሪ : ተአምረኛና ገዳማዊ አባት ናቸው::

የካቲት 16 ቀን መንኩሰው ወደ ተጋድሎ ገብተዋል:: በዋልድባ በነበራቸው ቆይታም እመቤቴ ኪዳነ ምሕረት የካቲት 16 ቀን እንድትከበር ማድረጋቸውም ይነገራል:: ጻድቁ በሌሎች ገዳማትም የነበሩ ሲሆን ዛሬም ድረስ ረድኤታቸው የሚደረግበት : ስማቸው የሚጠራበት ገዳም ግን ማኅበረ ሥላሴ ይባላል::

ገዳሙ የሚገኘው በሃገራችን ሰሜን ምዕራብ አቅጣጫ : በመተማ በርሃ ውስጥ ነው:: ይህንን ቅዱስ ገዳም የመሠረቱትም ራሳቸው አባ ዓምደ ሥላሴ ናቸው:: ገዳሙ ዛሬም ብዙ ምሑራንና መናንያን ያሉበት : በደህና ሁኔታም የሚገኝ ነው:: ግን በርሃውን የኔ ብጤ ደካማ ሰው የሚችለው አይደለም::

ስለ ጻድቁ ዓምደ ሥላሴ ከሚነገሩ ታሪኮች ቅድሚያውን የሚይዘው የተዋሕዶ ጠበቃነታቸው ነው:: በ1603 ዓ/ም ዼጥሮስ (ፔድሮ) ፓኤዝ የሚባል ካቶሊካዊ እሾህ ወደ ሃገራችን ገብቶ ነበርና ንጉሡን ሱስንዮስን አባብሎ ተዋሕዶን አስካዳቸው:: ነገሩ ውስጥ ለውስጥ ሲበስል ቆይቶ በ1609 ዓ/ም በመገለጡ እነ ራስ ዮልዮስ ለሃይማኖታቸው ጠዳ ላይ ተዋግተው ግንቦት 6 ቀን ተሰው::

ይህ ነገር ሲሰማ ወንድ ሴት : ትልቅ ትንሽ ሳይመረጥ በገጠሩም : በከተማውም : በገዳሙም ያሉት ሁሉ የተዋሕዶ ልጆች መንቀሳቀስ ጀመሩ:: 7 ዓመታት እንዲህ አልፈው በ1616 ዓ/ም ግጭቱ በይፋ ተጀመረ::

"ተዋሕዶን ካልካዳችሁ" በሚል በቀን እስከ 8,000 ሰው በሰይፍ ታረደ:: ይህን ያደረጉት ደግሞ አልፎንሱ ሜንዴዝ : ንጉሡ ሱስንዮስና ጀሌዎቻቸው ነበሩ::

በጊዜውም ከቤተ መንግሥት እነ ንግሥት ወልድ ሰዓላ (የሱስንዮስ ሚስት) : ከጻድቃን አበው ዘርዓ ቡሩክ ዘግሺ : ሐራ ድንግል ዘደራ : ምዕመነ ድንግል ዘጩጊ : ዓምደ ሥላሴ ዘማኅበረ ሥላሴ . . . ከቅዱሳት እነ ፍቅርተ ክርስቶስ : ወለተ ዼጥሮስ : ወለተ ዻውሎስ : እኅተ ዼጥሮስ . . . ለሃይማኖታቸው ተዋሕዶ ጥብቅና ቆመው ሕዝቡን አስተማሩ:: መከራም ተቀበሉ::

ብዙ ኢትዮዽያውያን የመከራ ጽዋን ተጐንጭተው ለክብር ከበቁ በሁዋላ የእግዚአብሔር ፍርድ ተገለጠ:: በጻድቃኑ እነ አባ ዓምደ ሥላሴ ሐዘን ንጉሡ ታመመ:: ምላሱ ተጐልጉሎ ወጣ::

በዚህ ጊዜ አቤቶ ፋሲለደስ ለአባ ዓምደ ሥላሴና ለሌሎቹ ቅዱሳን "አባቴን አድኑልኝ! ተዋሕዶም ትመለስ" አላቸው:: ጻድቁም ከባልንጀሮቻቸው ጋር ጸልየው ንጉሡን አዳኑት:: በፈንታውም ይህንን አሳወጁ::

††† ፋሲል ይንገሥ!
ሃይማኖት (ተዋሕዶ) ይመለስ!
የሮም ሃይማኖት ይፍለስ! †††

ከዚህ በሁዋላ በ1624 ዓ/ም ፋሲል ሲነግሥ አባ ዓምደ ሥላሴ ለገዳማቸው ብዙ ቦታ አስከልለው : በተጋድሎ ኑረው በዚህች ቀን ዐርፈዋል::

††† አምላከ ቅዱሳን በቀናችው እምነት ተዋሕዶ ሁላችንም እስከ ፍጻሜ ዘመናችን ያጽናን:: ከበረከተ ቅዱሳንም ይክፈለን::

††† የካቲት 27 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.አባ አንስጣስዮስ ርቱዓ ሃይማኖት (ዘአንጾኪያ)
2.አቡነ ዓምደ ሥላሴ

††† ወርኀዊ በዓላት
1.የጌታችንና አምላካችን መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ በዓለ ስቅለት
2.አቡነ መብዐ ፅዮን ጻድቅ
3.ቅዱስ መቃርስ (የመነኮሳት ሁሉ አለቃ)
4.ቅዱስ ፊቅጦር ሰማዕት
5.ቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ
6.ቅዱስ ገላውዴዎስ ሰማዕት (ንጉሠ ኢትዮዽያ)
7.ቅዱስ ቢፋሞን ጻድቅና ሰማዕት

††† "የተጠራችሁለት ለዚህ ነው:: ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሏልና:: እርሱም ኃጢአት አላደረገም:: ተንኮልም በአፉ አልተገኘበትም:: ሲሰድቡት መልሶ አልተሳደበም:: መከራንም ሲቀበል አልዛተም . . . እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ::" †††
(1ዼጥ. 2:21-25)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
Audio
""🛑 የዐቢይ ጾም መግቢያ ትምህርት ""

እንዴት እንጹም?

(መጋቢት 1 - 2016)

በዩቲዩብ ለምትፈልጉ👉https://youtu.be/3TJdP3s6PB8?si=6oGh5kG5IFTh0s46


ዝክረቅዱሳን ማኅበረ ቅዱስ ዳዊት

" ፍቅር ያጌብረኒ ከመ እንግር ዜናሆሙ ለቅዱሳን"::/የቅዱሳንን ዜና(ታሪክ) እንድመሰክር ፍቅር ያስገድደኛል::
       አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ /መጽሐፈ ምሥጢር

https://www.tg-me.com/zikirekdusn
✞ እንኩዋን ለታላቁ "የጌታ ጾም (ጾመ እግዚእ)" በሰላም አደረሳችሁ ✞

+*" ጾመ እግዚእ "*+

=>ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በአዋጅ ምዕመናን
እንዲጾሟቸው የሠራቻቸው 7 አጽዋማት አሏት:: "ጾም" ማለት "መከልከል" ነው:: የምንከለከለው ደግሞ ከኃጢአትና ከክፋት ሲሆን አንድም ሰውነትን ወደዚያ ከሚወስዱ አዝማደ መባልዕት (የምግብና የመጠጥ ዓይነቶች) መከልከልን ይመለከታል::

+"7ቱ" አጽዋማት:-
1.ዓቢይ ጾም
2.ጾመ ፍልሠታ
3.ጾመ ሐዋርያት
4.ጾመ ነቢያት
5.ጾመ ድኅነት
6.ጾመ ነነዌ እና
7.ጾመ ገሃድ ይሰኛሉ::

+በእነዚህ አጽዋማት ከዓቢይ ጾም በቀር እስከ 9 ሰዓት
ድረስ መጾም ይገባል:: ዓቢይ ጾም ግን የተለየ ሥርዓት
አለው:: ስለ ጾም ሲነሳ አስቀድሞ የሚመጣው ጥያቄ
አስፈላጊነቱ ነው:: "ጾም ለምን ያስፈልጋል?" ብሎ
ከመጠየቅ "ሃይማኖት ለምን ያስፈልጋል?" ብሎ
መጠየቁ ይቀላል::

+ምክንያቱም ከሃይማኖታዊ ትዕዛዛት ትልቁ በመሆኑ
እርሱን መቃወም ሃይማኖትንና አዛዡን እግዚአብሔርን
መቃወም ነውና:: እኛ ሃገር ላይ የተለመደች ክፉ ልማድ
አለች:: የከበደችንን ነገር "አያስፈልግም" በሚል
እንከራከራለን::

+ደግሞ ጾምን ለመሻር ጥቅስ የሚጠቅሱ ወገኖች
በጣም ይገርሙኛል:: ኃጢአትን ለመሥራት : ጾምንም
ለመሻር ጥቅስን መጥቀስ አያስፈልግም:: እኛ ግን
¤ከፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጀምሮ (ማቴ. 4:2)

¤አበው ቅዱሳን ጾመው (ዘዳ. 9:19, ነገ. 19:8, ሐዋ.
13:3, ቆሮ. 4:11) አሳይተውናልና እንደ አቅማችን
እንጾማለን::

+የጾሙ የመጀመሪያው ሳምንት (ዘወረደ) የሚጾመው
እስከ 12 ሰዓት ሲሆን ከቅድስት (ከ2ኛው ሳምንት) እስከ
ተጽኢኖ (የኒቆዲሞስ ዓርብ) ድረስ ደግሞ እስከ 11
ሰዓት ይጾማል::
በሰሙነ ሕማማት ግን የምንጾመው "እስከ ይሠርቅ
ኮከብ" (እስከ ምሽት 1 ሰዓት) ድረስ ይሆናል::

+ነገር ግን ሁሉም እንደ መጠኑ ነውና ከመምሕረ ንስሃ
ጋር ሊጨዋወቱት ይገባል:: በዓቢይ ጾም ለቻለ ቂጣ
በጨው እየበላ: ውሃ እየተጐነጨ ሊጾም ይገባል::
በእነዚህ 55 ቀናትም ከዕለተ ሆሳዕና በቀር ከበሮ
አይጐሰምም:: ጸናጽል አይጸነጸልም:: ተድላ ደስታም
አይደረግም::

+አብዝቶ መብላት : ሳቅ ማብዛትና ጌጥን ማብዛትም
እንዲሁ አይገባም:: ለቻለ ደግሞ በሌሊት ሰዓታቱን፡
በግህ ኪዳንና ስብሐተ ነግሁን : በመዓልት ቅዳሴውን :
በሰርክ (ምሽት) ደግሞ ምሕላውን ሊሳተፍ ይገባል::

+በእነዚህ 55 ቀናት ፈቃደ ሥጋ ሊደክም : ፈቃደ ነፍስ
ልትሰለጥን ግድ ነውና:: ከሌላው ጊዜ በተሻለ ወቅቱ
ምጽዋትና ጸሎት የሚደረግበት ነው:: በዚያውም ላይ
ነገሮችን እያመቻቹ በእነዚህ ዕለታት ቅዱስ ቃሉን
መስማት (ማንበብ) ይገባል:: በትዳር ውስጥ ላሉም
መኝታን መለየት ግድ ነው::

=>ከ7ቱ አጽዋማት አንዱ የሆነው ይህ ጾም=
1.ዐቢይ (ታላቁ) ጾም
2.የጌታ ጾም
3.ጾመ ሑዳድ
4.የድል ጾም
5.የካሳ ጾም
6.አርባ ጾም
7.የፍቅር ጾም . . .
በሚሉ መጠሪያዎችም ይታወቃል::

=>የጾሙ መግቢያ የመጀመሪያ ሳምንት ደግሞ=
1.ጾመ ሕርቃል
2.ጾመ በረከት ዘሐዋርያት
3.ሰሙነ ዘወረደም ይባላል::

=>ጾሙን የሰላም : የፍቅር : የምሕረት : የፀጋ :
የበረከት ያድርግልን:: ጾሞ ለማበርከትም ያብቃን፡፡

=>+"+ አሁንስ ይላል እግዚአብሔር በፍጹም ልባችሁ
በጾምም በልቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ:: ልባችሁን
እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ:: አምላካችሁም
እግዚአብሔር ቸርና መሐሪ: ቁጣው የዘገየ: ምሕረቱም የበዛ: ለክፋትም የተጸጸተ ነውና ወደ እርሱ ተመለሱ:: +"+ (ትን. ኢዩኤል 2:12)

✞ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ✞
††† እንኳን ለአባታችን ቅዱስ ቆዝሞስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቆዝሞስ ሊቀ ጳጳሳት †††

††† "ጳጳስ" ማለት "አባት - መሪ - እረኛ" ማለት ነው:: በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ በሐዲስ ኪዳን የመንፈሳዊ ስልጣን ደረጃዎች በጥቅሉ 3 ናቸው:: እነሱም ዲቁና: ቅስና: ጵጵስና ሲሆኑ በሥራቸው ወደ 9 ያህል ክፍሎች አላቸው:: ከእነዚህም ከፍተኛው ስልጣን ጵጵስና ነው::

ጵጵስና ማለት የክርስቶስን መንጋ እንደ ባለቤቱ አድርጐ መጠበቅ ማለት ነው:: ሥልጣኑ በምድር "ሸክም: ዕዳ" ሲሆን በሰማይ ግን "ክብር" ነው:: ማንም በሥጋው ላይ ካልጨከነ በቀር ጵጵስናን አይመኝም::

ቅዱስ ጳውሎስ "ሠናየ ግብረ ፈተወ - ማንም ጵጵስናን ቢመኝ መልካም ሥራን ተመኘ" (1ጢሞ. 3:1) ማለቱን ይዞ "ሹሙኝ" ማለት ወደ ማይጠፋ እሳት የሚያስጥል ከባድ ውሳኔ ነው:: ምክንያቱም አንድ ክርስቲያን የሚጠየቅ በራሱ ኃጢአት ሲሆን አንድ ካህን ደግሞ ስለ ልጆቹ ይጠየቃል:: የከፋው ግን የጳጳሱ ነው::

አንድ ጳጳስ ቢጾም ቢጸልይም እንኳ ለድኅነቱ በቂ አይደለም:: ምክንያቱም በመንበሩ ላይ ያስቀመጠው መንጋውን እንጂ ራሱን እንዲያድን አይደለምና:: ጌታ እንዳለ መልካም እረኛ "ይሜጡ ነፍሶ ቤዛ አባግኢሁ - መልካሙ እረኛ ስለ በጐቹ ቤዛ ራሱን አሳልፎ የሚሰጥ ነው::" (ዮሐ. 10) ስለዚህም ክህነት ( ጵጵስና) ሐዋርያዊ አገልግሎት ከባድም ኃላፊነት ነው::

አባቶቻችን ሐዋርያትና ተከታዮቻቸው ሐዋርያውያን ታላላቅ የጵጵስና መንበሮችን መሥርተው: ትምሕርቱን ከነ ወንበሩ አስተላልፈዋል:: ከእነዚህ መንበረ ጵጵስናዎች አራቱ የበላይ ናቸው::

እነዚህም የቅዱስ ጴጥሮሱ የሮም: የቅዱስ ዮሐንሱ የአንጾኪያ: የቅዱስ ማርቆሱ የእስክንድርያና የቅዱስ ጳውሎሱ የኤፌሶን መናብርት ናቸው::

እነዚህ መንበሮችም ከክርስቶስ ዕርገት እስከ 443 (451) ዓ/ም: ጉባኤ ኬልቄዶን ድረስ በአንድነት ቆይተው ተለያይተዋል:: ከእነዚህ መናብርት መካከል የእስክንድርያው (የግብጹ) እና የአንጾኪያው (የሶርያው) ዛሬም ድረስ በተዋሕዶ እምነት የጸኑ ናቸው::

የእኛ ቤተ ክርስቲያንም ሐዋርያዊት እንደ መሆኗ ሐዋርያትን መስለው: ሐዋርያትን አህለው የተነሱ አበው ጳጳሳትን በየጊዜው በበዓላት ታስባለች: ታከብራለች::

በተለይ ደግሞ የእስክንድርያና የአንጾኪያ በርካታ አባቶችን እናከብራለን:: እነርሱ ለቀናች ሃይማኖትና ለመንጋው ሲሉ ብዙ መከራን በአኮቴት ተቀብለዋልና:: ከእነዚህም መካከል አንዱ ቅዱስ ቆዝሞስ የእስክንድርያ (የግብጽ) 58ኛ ሊቀ ጳጳሳት የነበረ አባት ነው:: ዘመኑ እስልምና የሰለጠነበት ነበርና በዚያ ጊዜ እረኝነት (ጵጵስና) መመረጥ እንደ ዛሬው ዘመን ሠርግና ምላሽ አልነበረም:: በከሃዲዎች እሳትና ስለት መከራን ለመቀበል መወሰን እንጂ::

ከ6ኛው መቶ ክ/ዘመን በኋላ በዓለማችን ከተነሱ ሊቃነ ጳጳሳት ለግብጻውያኑ ቤተ ክርስቲያን ልዩ ቦታ አላት:: ምክንያቱም በወቅቱ በጎቻቸውን (ምዕመናንን) ለመጠበቅ ከግብጽ ከሊፋዎች የግፍ ጽዋዕን ጠጥተዋልና:: ከነዚህም አንዱ የእመቤታችን ፍቅር የበዛለትና በዚህ ቀን ያረፈው ቅዱስ ቆዝሞስ ነው::

††† አምላከ ቅዱሳን ሊቃውንት በጸሎታቸው እኛንም: ቤተ ክርስቲያናችንንም ከክፉ ጠላት ይጠብቅልን::

††† መጋቢት 3 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ አባ ቆዝሞስ (የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት)
2.አባ በርፎንዮስ ክቡር

††† ወርኀዊ በዓላት
1.በዓታ ለእግዝእትነ ማርያም ድንግል ወላዲተ አምላክ
2.ቅዱሳን ኢያቄም ወሐና
3.ቅዱሳን ሊቃነ ካህናት አበው (ዘካርያስና ስምዖን)
4.አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ
5.አቡነ ዜና ማርቆስ
6.አቡነ መድኃኒነ እግዚእ ዘደብረ በንኮል

††† "ነገር ግን ወንድሞች ሆይ! እናንተ የተማራችሁትን ትምህርት የሚቃወሙትን: መለያየትንና ማሰናከያን የሚያደርጉትን ሰዎች እንድትመለከቱ እለምናቹሃለሁ:: ከእነርሱ ዘንድ ፈቀቅ በሉ:: እንዲህ ያሉት ለገዛ ሆዳቸው እንጂ ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ አይገዙምና:: በመልካምና በሚያቆላምጥ ንግግርም ተንኮል የሌለባቸውን ሰዎች ልብ ያታልላሉ::" †††
(ሮሜ ፲፮፥፲፯)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
2024/09/24 21:26:44
Back to Top
HTML Embed Code: