Telegram Web Link
ይጠብቃቹሃል" አላቸው:: እነርሱም ደስ እያላቸው
በፍጥነት ወደ
አክሚም ወጡ::በዚያ ሰሞን የጌና ጾም ተፈጽሞ
የአክሚም ክርስቲያኖች ለበዓለ ልደት ዝግጅት ሲያደርጉ
በጠላት ሠራዊት
ተከበቡ::ይህ ሠራዊት የተላከው ከርጉም
ዲዮቅልጢያኖስ ሲሆን መሪው ደግሞ አርያኖስ ነው::
ዋናው ተልዕኮው
ክርስቲያኖችን ለጣዖት ማሰገድ: እንቢ ካሉ ደግሞ
መግደል ነው:: ክርስቲያኖቹ መከበባቸውን እያወቁ
አልፈሩም:: ታኅሳስ
29 ቀንም ሁሉም የከተማዋ ክርስቲያኖች ወደ ቤተ
ክርስቲያን ተሰበሰቡ::በዚያም ሊቀ ዻዻሱ ሥርዓተ ቅዳሴን
አደረሱ::

ሁሉም
በተመስጦ ይጸልዩ ነበርና የክብር ባለቤት ክርስቶስ
በገሃድ ተገለጠላቸው:: በዓይናቸው እያዩም ሥጋ ወደሙን
አቀበላቸው::
ቅዳሴው ሲጠናቀቅ ግን አርያኖስና ሠራዊቱ ደርሰው
ሁሉንም ክርስቲያኖች ያዛቸው::

+ክርስቶስን ክደው ከመገደል እንዲድኑ ተጠየቁ:: እነርሱ
ግን በአንድ ድምጽ "አይሆንም" አሉ:: በዚያን ጊዜ
ወታደሮቹ
በክርስቲያኖች አንገት ላይ በሰይፍ ይጫወቱ ያዙ::በተራ
አሰልፈው ዻዻሱን: ካህናቱን: ዲያቆናቱን:
አንባቢዎችን:መሣፍንቱን ሳይጨምር ከ16,000 በላይ
ክርስቲያኖች ደማቸው ፈሰሰ:: የቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር
ሞልቶ ደም
ወደ ውጭ 20 ክንድ ያህል ፈሰሰ::

በክርስቲያኖች ላይ
ግፍ ተፈጸመ::አካባቢውም ያለ ወሬ ነጋሪ ቀረ:: ግድያው
ለ3
ቀናት ቀጥሎ ጥር 1 አንድ ቀን ቅዱሳን ዲዮስቆሮስና
ሰከላብዮስ ሲገደሉ ተጠናቀቀ::

✞አምላከ ሰማዕታት ፍቅረ ሃይማኖታቸውን ያሳድርብን::
ከበረከታቸውም ይክፈለን::

✞ጥር 1 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ እስጢፋኖስ ቀዳሜ ሰማዕት (ሊቀ ዲያቆናት)
2.ቅዱሳን ሰማዕታተ አክሚም
3.ቅዱሳን ዲዮስቆሮስ ወሰከላብዮስ
4.ቅዱስ ለውንድዮስ ሰማዕት
5.አባ መቃርስ ሊቀ ዻዻሳት

 በ 01 የሚከበሩ ወርኀዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ልደታ ለማርያም ድንግል እግዝእትነ
2.ቅዱሳን ኢያቄም ወሐና
3.ቅዱስ ራጉኤል ሊቀ መላዕክት
4.ቅዱስ በርተሎሜዎስ ሐዋርያ
5.ቅዱስ ሚልኪ ትሩፈ ምግባር

✞እስጢፋኖስም ጸጋንና ኃይልን ተሞልቶ በሕዝቡ መካከል
ድንቅንና ታላቅ ምልክትን ያደርግ ነበር . . . አንዳንዶቹ
ተነስተው
እስጢፋኖስን ይከራከሩት ነበር:: ይናገርበት የነበረውንም
ጥበብና መንፈስ ይቃወሙ ዘንድ አልቻሉም:: በዚያን ጊዜ
በሙሴ
ላይ: በእግዚአብሔርም ላይ የስድብን ነገር ሲናገር
ሰምተነዋል የሚሉ ሰዎችን አስነሱ . . . በሸንጐም
የተቀመጡት ሁሉ
ትኩር
ብለው ሲመለከቱት እንደ መልአክ ፊት ሆኖ ፊቱን አዩት::
(ሐዋ. 6:8-15)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
#የሰማዕታተ_አክሚም በስንት ቀን ይታሰባሉ
Anonymous Quiz
15%
ታሕሳስ 30
56%
ጥር 1
12%
ታሕሳስ 29
18%
ሁሉም
እንኳን ለጻድቅ ሰው "ቅዱስ አቤል" እና "ቅዱስ ቴዎናስ ሊቅ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

("አቤል" ማለት በስዕሉ ከፊት ያለው ወጣት ነው)

+*" ቅዱስ አቤል ጻድቅ "*+

=>እግዚአብሔር አዳምን በ7 ሃብታት አክብሮ በገነት ቢያኖረው "አትብላ" የተባለውን ዕፀ በለስ በላ:: በዚህም ከፈጣሪው ተጣልቶ: በሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ: በርደተ መቃብር ርደተ ገሃነም ተፈረደበት:: በሁዋላ ግን ንስሃ ስለ ገባ "ከ5 ቀን ተኩል (5,500 ዘመን) በሁዋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ" የሚል ቃል ኪዳንን ሰጠው::

+አዳምና ሔዋን ከገነት ከወጡ በሁዋላ ወዲያው ሕገ ሰብሳብን (የወንድና የሴት ሥርዓትን) አልፈጸሙም:: ይልቁኑ ለ14 ኢዮቤልዩ (ለ100 (98) ዓመታት) ንስሃ ገቡ: አለቀሱ እንጂ::

+አለቃቀሳቸውም እንደኛ በቤተ ፈት ልማድ ሳይሆን "እግዚአብሔርን ያህል ጌታ: ገነትን ታህል ቦታ በበደላችን አጣን" እያሉ ነበር:: "አልቦቱ ለአዳም ካልዕ ሕሊና ዘእንበለ ብካይ ላዕለ ኃጢአቱ" እንዲል:: (መቅድመ ወንጌል)

+እውነትን እንነጋገር ከተባለ እኛ ለወላጆቻችን አዳምና ሔዋን ተገቢውን ክብር እየሰጠናቸው አይደለም:: አንደበቱን የከፈተ "አስተማሪ" ሁሉ ኃጢአታቸውን እንጂ ክብራቸውን ሲናገር ሰምቼ አላውቅም:: ሌላው ይቅርና ማንም ሰው "ቅዱስ አዳምና ቅድስት ሔዋን" ብሎ ሲጠራቸው ገጥሞኝ አያውቅም::

+የሚገርመው ደግሞ እኛ እልፍ አእላፍ ኃጢአትን ተሸክመን እነርሱን ስለ አንዲቷ ኃጢአታቸው ስንወቅሳቸው መዋላችን ነው:: በእነርሱ ምክንያት ገነት ብትዘጋ: ዳግመኛ የተከፈተችው በፍጹም እንባና ንስሃቸው ነው::

+"ፍቅር ሰሐቦ ለወልድ ኃያል እመንበሩ ወአብጽሖ እስከ ለሞት" (ቅዳሴ ማርያም) እንዲል:: ጌታን ለሰውነት: ለሞት ያበቃው ፍቅረ አዳም መሆኑን ልንዘነጋ አይገባም::

+በዚያውም ላይ አባታችን ቅዱስ አዳም:-
*በኩረ ኩሉ ፍጥረት
*በኩረ ነቢያት አበው
*በኩረ ሐዋርያት ወአርድእት
*በኩረ ጻድቃን ወሰማዕት
*በኩረ ደናግል ወመነኮሳት የሆነ ደግ ፍጥረት ነው:: ስለዚህም ቅዱሳን አዳምና ሔዋንን ልናከብራቸው በእጅጉ ይገባናል::

+ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና ቅዱሳኑ አዳምና ሔዋን ንስሃቸውን ፈጽመው: ተስፋ ድኅነት ከተሰጣቸው በሁዋላ አብረው አደሩ:: በዚያች ሌሊትም ቃየንና ኤልዩድ (ሉድ) ተጸነሱ: በጊዜውም ተወለዱ::

+አሁንም ድጋሚ አብረው ቢያድሩ ቅዱስ አቤልና መንትያው አቅሌማ ተጸንሰው ተወለዱ:: ዓለምም በጊዜው እነዚ 6 ሰዎች ይኖሩባት ነበር:: ምንም እንኩዋ እናታችን ቅድስት ሔዋን ብዙ መንትያዎችን ብትወልድም "ብዙ ተባዙ: ምድርንም ሙሉአት" ያለው የጌታ ቃል ይፈጸም ዘንድ ልጆቻቸውን ማጋባት ነበረባቸው::

+የመጀመሪያው የልጆች ጋብቻም በአቤልና በኤልዩድ: እንዲሁም በቃየንና በአቅሌማ መካከል እንዲሆን ተወሰነ:: አባታችን ቅዱስ አዳም ደግ ነቢይ ነውና ለማራራቅ ሲል ይህንን አደረገ:: ነገር ግን በውሳኔው እንደማይስማማ ቃየን ተናገረ::

+ምክንያቱ ደግሞ የአቤል መንትያ መልኩዋ የኔ ብጤ በመሆኗና የእርሱ መንትያ ኤልዩድ ግን እናቷን ቅድስት ሔዋንን የምትመስል ቆንዦ ስለ ነበረች "እኔ መንትያየን ነው የማገባ" የሚል ነበር::

+አቤል ግን የቱንም ቢሉት ከወላጆቹና ከፈጣሪው ትዕዛዝ የማይወጣ ደግ ሰው ነበር:: በጊዜውም መላእክት ባስተማሩት መሠረት ቅዱስ ሰው አዳም ለልጆቹ እርሻንና እንስሳት እርባታን አስተምሯቸው ነበርና ቃየን በግብርና: አቤል ደግሞ በበግ እረኝነት (እርባታ) ይኖሩ ነበር::

+ቅዱስ ሰው አቤል በቅንነቱና በታዛዥነቱ መንፈሰ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ሆነለት:: ሁሌም ስንጠራው "ጻድቅ" ብለን ነው:: ከጻድቃነ ብሊት (ብሉይ) አንዱ ሲሆን የዚህች ዓለም የመጀመሪያው ሟችና ሰማዕት ለመሆንም በቅቷል::

+በሴት ልጅ መልክ ምክንያት በዚህች ዓለም ጥላቻ "ሀ" ብሎ ጀመረ:: ምንም ሳያደርገው ቃየን ወንድሙ አቤልን ጠላው:: የጥላቻ አባቷ ዲያብሎስ ነውና የእርሱ ዘመድ ሆነ::

+ነገሮች ያላማሩት ቅዱሱ አባታቸው ግን በጐ መፍትሔ ሊሆናቸው: የቀናውንም ሥርዓት ሊያስተምራቸው "ለእግዚአብሔር መስዋዕትን አቅርቡ:: እግዚአብሔር መስዋዕቱን የተቀበለለት ኤልዩድን ያገባል" አላቸው:: "እሺ" ብለው መካነ ምስዋዕ አዘጋጁ::

+አቤል ከንጹሕ ልቡ እንዲህ አሰበ:: "እግዚአብሔር ንጹሐ ባሕርይ ነውና ንጹሕ ነገርን ይወዳል" አለ:: በዚህም ቀንዱ ያልከረከረውን: ጥፍሩ ያልዘረዘረውን: ጠጉሩ ያላረረውን: የ1 ዓመት ነውር የሌለበትን ጠቦት አቀረበ::

+ቃየን ደግሞ ከክፉ ልቡ እንዲህ አሰበ:: "እግዚአብሔር አይበላ: አይጠጣ:: ጥሩ ነገር ብሰጠውስ ምን ያደርገዋል" ብሎ ዋግ የመታውን: ነቀዝ የበላውን እሕል (ሥርናይ) አቀረበ:: እዚህ ላይ አንድ ነገርን ልብ እንበል::

+እግዚአብሔር እንደ ሰው አይበላም: አይጠጣም:: ይህ እውነት ነው:: ግን እግዚአብሔር የአቤልን መስዋዕት የተቀበለው በጉን ፈልጐ: ወይ አቤል ቆንጆዋን ሴት እንዲያገባ አይደለም:: ምክንያቱም አቤል እንደሚገደልና በድንግልናው እንደሚሰዋ እርሱ ያውቃልና::

+ይልቁኑ እግዚአብሔርን የሚያስደስተው የስጦታው ምንነት ሳይሆን የሰጭው ማንነት ነውና እኛ ክርዳድ ሆነን ለእግዚአብሔር ስንዴ ልናቀርብለት አንችልም:: ምክንያቱም እግዚአብሔር ከእኛ ምንም ነገርን አይሻም:: ሰማይና ምድር: ፍጥረታት በሙሉ የእርሱ ናቸውና::

+ንጹሐ ባሕርይ ጌታ ከእኛ አንዲት ነገርን ብቻ ይሻል:: ይህቺም በንጹሕ ልቡና የምትቀርብ ንጹሕ አምልኮ ናት:: በዚህም የምንጠቀመው እኛ እንጂ እርሱ አይደለም::

+2ቱ ወንድማማቾች መስዋዕትን ሲያቀርቡለትም "ወነጸረ እግዚአብሔር ላዕለ አቤል ወላዕለ መስዋዕቱ" እንዲል እግዚአብለሔር ቃየንና መስዋዕቱን ትቶ መጀመሪያ ወደ አቤል: ቀጥሎም ወደ መስዋዕቱ ተመለከተ:: ማለትም አቤልና መስዋዕቱን ወደዳቸው::

+በዚህ ምክንያትም ቃየን ተበሳጨ:: ክፋትን እያሰበ ሲመላለስም ሰይጣን ተገናኝቶ ክፉውን መከረው:: በቁራ ተመስሎ ነፍሰ ገዳይነትን አስተማረው:: በዚህም ወደ ምድረ በዳ ወስዶ በድንጋይ ጭንቅላቱን መትቶ ገድሎት ሔደ::

+በዚህ ምክንያትም አቤል "በኩረ ምውታን - የመጀመሪያው ሟች" ተባለ:: "የዋሕ" የተባለበትም ምሥጢሩ ቂም እንደ ያዘበት: ክፋትን እንዳሰበበት እያወቀ እንደ በግ ተከትሎት መሔዱ ነው::

+ስለዚህም ነገር ለመድኃኒታችን ክርስቶስ ምሳሌው ሆነ:: አባ ሕርያቆስም እመቤታችንን ሲያመሰግናት "የውሃቱ ለአቤል ዘተቀትለ በአመጻ-በአመጻ የተገደለ የአቤል የውሃቱ: የየዋህነቱን ዋጋ የምታሰጭው አንቺ ነሽ" ብሏል::

+ቅዱስ አቤል ከተገደለ ከ28 ዓመታት በሁዋላ ነፍሱ ገነትን ተሳልማለች:: ስለ ቅዱሱ ግፍም እግዚአብሔር የቃየንን ዘሮች በጥፋት ውሃ ደምስሷቸዋል::

+"+ ቅዱስ ቴዎናስ ሊቀ ዻዻሳት +"+

=>ይህ ቅዱስ ሰው ተወልዶ ያደገው በእስክንድርያ (ግብጽ) ሲሆን ዘመኑም 3ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: እርሱ ትምሕርተ ቤተ ክርስቲያንን ተምሮ ጸጋው ቢበዛለት ከምዕመንነት ወደ ዲቁና: ከዲቁና ወደ ቅስና ማዕርግ ተሸጋገረ::
+ቀጥሎም ለታላቅ ሃላፊነት ተመረጠ:: አባ መክሲሞስ ባረፈ ጊዜ የግብጽ 16ኛ ፓትርያርክ ሆነ:: ግን ኃላፊነቱ ሠርግና ምላሽ (የተመቸ) አልነበረም:: ምክንያቱም እርሱ ሊቀ ዻዻሳት ሲሆን ዘመነ ሰማዕታት በመጀመሩ ክርስቲያኖች ተሰደዱ: ተጨፈጨፉ::+አብያተ ክርስቲያናትም ተቃጥለው አለቁ:: በዚሀ ጊዜ ቅዱስ ቴዎናስ እየዞረ ሕዝቡን ያጸና ነበር:: በተለይም የእመቤታችንን ቤተ ክርስቲያን አንጾ ለሕዝቡ ያቆርብ: ያስተምር ነበር::

+በዘመነ ሲመቱ ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ዼጥሮስን ጨምሮ ብዙ አርድእትን አፍርቷል:: ሥልጣነ እግዚአብሔር ጋርዶት ስለ ነበር አገልግሎቱን ፈጽሞ በዚህ ቀን ዐርፏል::

=>የጻድቅ ሰው አቤል አምላከ የውሃቱን ይስጠን:: የዋሃንን ያብዛልን:: ከበረከቱም ይክፈለን::

=>ጥር 2 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ አቤል ጻድቅ
2.ቅዱስ ቴዎናስ ሊቀ ዻዻሳት
3.ቅዱስ አላኒቆስ ሰማዕት
4.ቅድስት ሳቤላ ነቢዪት
5.ቅዳሴ ቤታ ለድንግል (በደብረ አባ ሲኖዳ)

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ታዴዎስ ሐዋርያ
2.ቅዱስ ኢዮብ ጻድቅ ተአጋሲ
3.ቅዱስ አባ ዻውሊ ገዳማዊ (ታላቁ)
4.ቅዱስ ዮሐንስ ነቢይ (መጥምቀ መለኮት)
5.ሊቁ አባ ሕርያቆስ
6.ቅዱስ ሳዊሮስ ዘአንጾኪያ

=>+"+ እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ: የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው . . . አቤል ከቃየን ይልቅ የሚበልጥን መስዋዕት ለእግዚአብሔር በእምነት አቀረበ:: በዚህም እግዚአብሔር ስለ ስጦታው ሲመሰክር እርሱ ጻድቅ እንደ ሆነ ተመሰከረለት:: ሞቶም ሳለ በመስዋዕቱ እስከ አሁን ይናገራል:: +"+ (ዕብ. 11:1)

    <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
እንኩዋን ለቅዱሳን "ሕጻናተ ቤተ ልሔም" እና "አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ሕጻናተ ቤተ ልሔም "*+

=>በሮሙ ቄሣር በአውግስጦስ ዘመን ሰው ሁሉ ይቆጠር ዘንድ አዋጅ ወጥቷልና እመ ብርሃን ማርያም ከቅዱሳኑ ዘመዶቿ ዮሴፍና ሰሎሜ ጋር ወደ አባቷ ዳዊት ከተማ ወደ ቤተ ልሔም ሔደች::

+በዚያም ሳሉ የምትወልድበት ጊዜ ቢደርስ በፍጹም ድንግልና እንደ ጸነሰችው ሁሉ በፍጹም ድንግልና ወለደችው:: (ኢሳ. 7:14, ሕዝ. 44:1) ተፈትሖም አላገኛትም:: ልማደ አንስትም አልጐበኛትም:: ምጥም አልነበረባትም::

+በጊዜውም በምሥራቅ የፋርስ: የባቢሎንና የሳባ ነገሥት አስቀድሞ ከበለዓም: በሁዋላም ከዠረደሸት በተረዱት መሠረት ኮከቡን በማየታቸው ታጥቀው ተነሱ::

+ከምሥራቅ አፍሪቃና ከእስያም በተመሳሳይ ኮከቡን በማየታቸው 12 ነገሥታት በየግላቸው 10 10 ሺህ ሠራዊትን እየያዙ ድንግልንና ንጉሥ ልጇን ፍለጋ ወጡ::

+12ቱ ነገሥታት ከነ ሠራዊታቸው ሲሔዱ ስንቃቸው በማለቁ 9 ነገሥታት ተስፋ ቆርጠው ተመለሱ:: 3ቱ ግን በፍጹም ጥብዓት ከ30ሺ ሠራዊት ጋር በኮከብ እየተመሩ ኢየሩሳሌም ደረሱ::

+እነዚህም መሊኩ የኢትዮዽያ (የሳባ ንጉሥ ተወራጅ): በዲዳስፋና መኑሲያ (ማንቱሲማር) ደግሞ የፋርስና የባቢሎን ነገሥታት ናቸው:: ወደ ኢየሩሳሌም ሲደርሱም ሔሮድስና ሠራዊቱ ታወኩ::

+እነርሱ ግን የቤተ ልሔምን ዜና ከጠየቁ በሁዋላ በጐል ድንግል ማርያምን: ክርስቶስን: ዮሴፍና ሰሎሜን አገኙ:: ለ2 ዓመታት እነርሱን ፍለጋ ደክመዋል: ተንከራተዋልና ደስታቸው ወሰን አጣ::

+በእመቤታችንና በልጇ ፊት በደስታ ዘለሉ:: "አንፈርዓጹ ሰብአ ሰገል" እንዲል:: ወርቁን: እጣኑንና ከርቤውንም ገብረው በግንባራቸው በፊቱ ሰገዱ:: 3 ጊዜ እየወጡ እየገቡ ቢመለከቱት በኪነ ጥበቡ አንዴ እንደ ሕጻን: በ2ኛው እንደ ወጣት: በ3ኛው እንደ አረጋዊ ሆኖ ታይቷቸው ፈጽመው አድንቀዋል::

+ወደ ሃገራቸው ሲመለሱም "ወአስነቀቶሙ ሕብስተ ሰገም" እንዲል የገብስ ዳቦ ጋግራ ድንግል ሰጠቻቸው:: እነርሱም ይህንን እየተመገቡ የ2 ዓመቱን መንገድ በ40 ቀን ሲጨርሱት ዳቦው ግን ያ ሁሉ ሺህ ሰው ተመግቦት አላለቀም:: ተአምራትንም ሠርቷል::

+ሰብአ ሰገል ቅዱስ መልአክ እንደ ነገራቸው በሔሮድስ ዘንድ ሳይሆን በሌላ ጐዳና ተጉዘው ሃገራቸውን መግባታቸውን ንጉሡ ሰማ:: እንደ ዘበቱበት ሲያውቅም የሚያደርገው ጠፍቶበት ወደ ቤቱ ገባ::

+በሕሊናው የሚመላለሰውም አንድ ነገር ብቻ ነበር:: የአይሁድ ንጉሥ የተባለውን (እርሱስ የሰማይና የምድር ሁሉ ንጉሥ ነው) እንዴት ሊያጠፋው እንደሚችል ያስብ ነበር:: በዚያች ሰዓትም ሰይጣን በሰው ተመስሎ ወደ እርሱ ቀረበ::

+ሕጻኑን እንዴት ሊገድለው እንደሚችል ነግሮት: በዓለም ታይቶ የማይታወቀውን ጭካኔ አስተማረው:: ርጉም ሔሮድስም ሠራዊቱን ጠርቶ "አዋጅ ንገሩልኝ" አላቸው::

+እነርሱም "በቤተ ልሔምና በአውራጃዋ: በይሁዳም የምትገኙ እናቶች:- አውግስጦስ ቄሣር ሕጻናትን በማርና በወተት አሳድገህ ለሹመት አብቃልኝ: ለእናቶቻቸውም ወርቅና ብር ስጥልኝ ስላለ 2 ዓመትና ከዚያ በታች የሆናቸውን ሕጻናት ሁሉ አምጡ" እያሉ አዋጁን ነገሩ::

+የቤተ ልሔምና የአካባቢዋ እናቶችም ያላቸው አንድም: ሁለትም እየያዙ: የሌላቸው ደግሞ እየተዋሱ ወደ ሔሮድስ ዘንድ ይዘዋቸው መጡ:: ያን ጊዜ አውሬው ሔሮድስ እናቶችን በአንድ ቦታ እንዲታጐሩ አድርጐ ሕጻናቱን በወታደሮቹ አሳፍሶ ወደ ተራራ አወጣቸው::

+በሥፍራውም ተወዳዳሪ በሌለው ጭካኔ 1,200 ወታደሮቹን አሰልፎ ሕጻናቱን አሳረዳቸው:: ሰይፍ የበላቸው የቤተ ልሔም ሕጻናት ቁጥርም 144,000 ሆነ::

+የሕጻናቱ ደም ከተራራው እንደ ጐርፍ ወረደ:: የእናቶች የጡት ወተትም በመሬት ላይ ይፈስ ነበርና ተቀላቀለ:: የቤተ ልሔም እናቶች አንጀታቸው በእጥፉ ተቆረጠ:: ታላቅ ሰቆቃም አካቢውን ሞላው:: ዋይታም ሆነ::

+ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ እንዳለው ነቢዩ ኤርምያስ የተናገረው ትንቢት ተፈጸመ:: "ራሔል ስለ ልጆቿ አለቀሰች:: የሉምና መጽናናት አልቻለችም" (ማቴ. 2:18, ኤር. 31:15)

+ሰይጣን ግን አላማው እንዳልተሳካና ድንግልና አምላክ ልጇ መሸሻቸውን ሲያውቅ ይህንኑ ለሔሮድስ ሹክ አለው:: ስለዚህም ንግሥተ አርያም ድንግል ማርያምና ወልደ አምላክ ልጇ በስደት ለ3 ዓመት ከ6 ወር ተንገላቱ::

+እንደ ገናም ክፉ ሰዎች መጥተው ለሔሮድስ አሉት:- "አንተ የምትሻው በዘካርያስ ቤት አለና ግደለው::"
ሔሮድስም ወታደሮቹን ልኮ: ሕጻኑን ቅዱስ ዮሐንስን ቢያጣው ደጉን ነቢይ: አረጋዊ ዘካርያስን በቤተ መቅደስ መካከል ገድሎታል::

+በጊዜው የሚፈርድ እግዚአብሔርም ስለ ሕጻናቱ ደም ተበቅሎ ሔሮድስን አጠፋው:: ወደ እመቀ እመቃትም አወረደው:: 144 ሺው ንጹሐን ሕጻናት ግን ስልጣነ ሰማይ ተሰጣቸው:: ከእነርሱ በቀር ማንም በማያውቀው ምሥጢርና ዜማ ፈጣሪያቸውን ይሠልሱትና ይቀድሱት ዘንድም አደላቸው:: (ራዕ. 14:1)

+አባ ሕርያቆስ በሐዳፌ ነፍስ ድርሰቱ "ያስምዓነ ቃለ መሰናቁት ዘሕጻናት-የሕጻናትን የመሰንቆ ድምጽ ያሰማን" እንዳለ:: (ቅዳሴ ማርያም)

+እነዚህ 144 ሺህ ንጹሐን ሕጻናት ዛሬ በሰማይ ለምዕመናን ምሕረትን: ለጨካኞች ፍርድን ይለምናሉ:: በፍርድ ቀንም በጌታ ፊት በክብር ቅንዋቶቹን ይዘው ይመጣሉ::

<< ክብራቸው ታላቅ ነውና ለቅዱሳን ሕጻናት ምስጋና ይሁን !! >>

+*" አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ "*+

=>በሃገራችን እጅግ ዝነኛ ከሆኑ ቅዱሳን አንዱ አባ ሊባኖስ ናቸው:: እርሳቸው እንደ ተስዓቱ (ዘጠኙ) ቅዱሳንና አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ሁሉ ከውጪ ሃገር የመጡ ናቸው::

+የነበሩበት ዘመንም 5ኛው መቶ ክ/ዘመን መጨረሻና 6ኛው መቶ ክ/ዘመን ውስጥ ነው:: ጻድቁ አባ ሊባኖስን "አባ መጣዕ" እያሉ መጥራት የተለመደ ነው:: "መጣዕ" ማለት ኤርትራ ውስጥ የሚገኝና ጻድቁ በተጋድሏቸው የቀደሱት ቦታ ነው:: ጥንተ ታሪካቸውስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-

+አባ ሊባኖስ ትውልዳቸው ከሮም ታላላቅ ሰዎች ነው:: አባታቸው አብርሃም: እናታቸው ደግሞ ንግሥት ይባላሉ:: በብሥራተ መልአክ ተጸንሰው ስለ ተወለዱ ስማቸውም በዚያው "ሊባኖስ" ተብሏል::

+"ሊባኖስ" እመ ብርሃን የተወለደችበት ቅዱስ ሥፍራ ሲሆን በጥሬ ትርጉሙ "ደጋ" ማለት ነው:: ምሥጢራዊ ትርጉሙ ግን ለጻድቅነት ያገለግላል:: አባ ሊባኖስ በሃገራቸው ሮም ከወላጆቻቸው ጋር አድገው ለአካለ መጠን ሲደርሱ ከወደ ቁስጥንጥንያ ሸጋ ብላቴና አጭተው አጋቧቸው::

+ወጣቱ አባ ሊባኖስ ግን ማታ "ወደ ጫጉላ አልገባም" ብለው እንቢ አሉ:: ለዚያች ሌሊት ብቻ ከአባታቸው ጋር እንዲያድሩ ተፈቀደላቸው:: መጻሕፍትን የተማሩ ነበሩና በሌሊት ምን እንደሚያደርጉ ሲያወጡ: ሲያወርዱ ቅዱስ መልአክ ከሰማይ ወርዶ 3 ጊዜ "ሊባኖስ" ብሎ ጠራቸው::

+"እነሆኝ ጌታየ!" ቢሉት ከአባታቸው ጐን ነጥሎ እያጫወተ ሳይታወቃቸው ከሮም ግብጽ (ገዳመ ዳውናስ) አደረሳቸው::

+በጊዜው ታላቁ ኮከብ ቅዱስ ዻኩሚስ ነበር:: አባ ሊባኖስን አስተምሮ አመነኮሳቸው: በዓትም ለየላቸው:: በዚያ ለተወሰነ ጊዜ እንደቆዩም ቅዱሱ መልአክ መጥቶ "ለዘለዓለም መጠሪያህ በዚያ ነውና ወደ ኢትዮዽያ ሒድ" አላቸው::
+እየመራም ከግብጽ አክሱም አደረሳቸው:: አባ ሊባኖስም በዚያ በዓት ወቅረው ይጸልዩ ጀመር:: ጥቂት ቆይተውም ለስብከተ ወንጌል ተሰማሩ:: በተለይ በ6ኛው መቶ ክ/ዘመን በስብከት ከአክሱምሸዋ (ግራርያ) ደርሰዋል::

+ተመልሰው ወደ አክሱም ሔደው: ጸበልን አፍልቀው ነበርና ድውያንን ፈወሱ:: ሙትን አስነሱ:: በዚህ የቀኑት የአካባቢው ሰዎች ግን "ምትሐተኛ ነህ" ብለው አባረሯቸው:: ጻድቁም ዶርቃ በምትባል ቦታ ለ3 ዓመት ሲኖሩ በአክሱም ዝናብ አልዘንብ አለ::

+ጥፋታቸው የገባቸው የአክሱም ካህናት ወደ ጻድቁ ሔደው "ይማሩን" ቢሏቸው ዘንቦላቸዋል:: አባ ሊባኖስ ግን ወደ ሽዋ ተመልሰው በደብረ አስቦ ለመኖር ቢሞክሩ አልተሳካም:: ስሙ የአንተ: ማደሪያነቱ ግን የቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ነውና ወደ "መጣዕ" ሒድ አላቸው መልአኩ::

+እርሳቸውም ወደ መጣዕ (ኤርትራ) ወርደው ታላቅ ገዳም አነጹ:: ጸበሎችን አፈለቁ:: ብዙ አርድእትንም አፈሩ:: በዚያም በቅድስናና በገቢረ ተአምራት ኑረው ጥር 3 ቀን በ140 ዓመታቸው ዐርፈዋል:: የላሊበላውን ቤተ አባ ሊባኖስን ጨምሮ በርካታ አብያተ መቃድስ በሃገራችን አሏቸው::

=>የሕጻናቱና የጻድቁ አምላክ እኛን ይማረን:: ከበረከታቸውም ያሣትፈን::

=>ጥር 3 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1."144 ሺ" ቅዱሳን ሕጻናት
2.አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ
3.አባ አሞን መስተጋድል

=>ወርኀዊ በዓላት
1.በዓታ ለእግዝእትነ ማርያም ድንግል
2.ቅዱሳን ኢያቄም ወሐና
3.ቅዱሳን ካህናት (ዘካርያስና ስምዖን)
4.አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ
5.አቡነ ዜና ማርቆስ
6.ቅዱስ ቄርሎስ ዓምደ ሃይማኖት
7.አቡነ መድኃኒነ እግዚእ ጻድቅ

=>+"+ አየሁም: እነሆም በጉ በጽዮን ተራራ ቆሞ ነበር:: ከእርሱም ጋር ስሙና የአባቱ ስም: የመንፈስ ቅዱስም ስም በግምባራቸው የተጻፈላቸው መቶ አርባ አራት ሺህ ነበሩ . . . ደርዳሪዎችም በገና እንደ ሚደረድሩ ያለ ድምጽ ሰማሁ:: በዙፋኑም ፊት: በአራቱም እንስሶችና በሊቃውንቱ ፊት አዲስ ምስጋና አመሰገኑ:: ከምድርም ከተዋጁት ከመቶ አርባ አራት ሺህ በቀር ያን ቅኔ ሊማር ለማንም አልተቻለውም:: ከሴቶች ጋር ያልረከሱ እነዚህ ናቸው:: ድንግሎች ናቸውና:: +"+ (ራዕ. 14:1)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞

++ እንኩዋን ለፍቁረ እግዚእ ዮሐንስ ሐዋርያ: ወልደ ነጐድጉዋድ ዓመታዊ የፍልሠት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ++

++ ቅዱስ ዮሐንስ ፍቁረ እግዚእ ++

=>አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቅዱስ ወንጌሉ እንደነገረን በመንግስተ ሰማያት ታላቁ ሰው ወንጌላዊው ዮሐንስ ነው:: ቅዱሱ ሐዋርያ ከዘብዴዎስና ከማርያም ባውፍልያ ተወልዶ: በገሊላ አካባቢ አድጐ: ገና በወጣትነቱ መድኃኔ ዓለምን ተከትሎታል::

+ቅዱስ ዮሐንስ ከሐዋርያት ቀድሞ ጌታን ከመከተሉ ባሻገር በምንም ምክንያት ከጐኑ አይጠፋም ነበር:: ስለ ንጽሕናውና በጐ የፍቅር ሕሊናው ሕጻን ሳለ በወንድሞቹ ሐዋርያት ዘንድ ሞገሱ ከፍ ያለ ነው:: ጌታችንን እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ በመከተሉ ድንግል እመቤታችንን ተቀብሏል::

+ከእርሷ ጋር ለ15 ዓመታት ቢቀመጥ መዝገበ ምሥጢር ሆነ:: ስንኩዋን ከሰው ልጆች ይቅርና ከልዑላኑ መላዕክትም ማዕረጉ ከፍ አለ:: ሰው ቢበቃ መላእክትን ሊያይ ይቻለዋል:: ቅዱስ ዮሐንስን ግን መላእክት ሊያዩት ይከብዳቸዋል:: ከፍጥረት ወገን ከእመ ብርሃን ቀጥሎ ክቡር እርሱ ነው::

+ቅዱስ ዮሐንስ በታናሽ እስያ ለ7ቱ አብያተ ክርስቲያናት መስበኩ ይታሰባል:: ቅዱሱ ከጌታችን ዕርገት በሁዋላ ለ70 ዓመታት በዚህ ምድር ሲኖር አብዛኛውን ጊዜውን ያሳለፈው በኤፌሶን አካባቢ ነው:: ሕዝቡን ወደ ክርስትና ለማምጣት በአፍም በመጽሐፍም ደክሟል::

+3 መልዕክታት: ራዕዩንና ወንጌልን ጽፎላቸዋል:: ሕይወትን ስለ ሰበከላቸው በፈንታው ብዙ አሰቃይተውታል:: ከእሳት እስከ ስለት: እስከ መጋዝም በስተእርጅና ደርሶበታል:: እርሱ ግን በትእግስቱ ገንዘብ አድርጉዋቸዋል::

+" ቅዱሱ በኤፌሶን "+

=>ይህቺ ኤፌሶን የሚሏት ሃገር መገኛዋ በቀድሞው ታናሽ እስያ (አሁን ቱርክ አካባቢ) ሲሆን ብዙ ሐዋርያት አስተምረውባታል:: ያም ሆኖ የሚፈለገውን ያህል ለውጥ ያመጣች አልነበረችምና ቅዱስ ዮሐንስ ሊሔድ ተነሳ::

+ከደቀ መዛሙርቱ መካከልም ቅዱስ አብሮኮሮስን (ከ72ቱ አርድእት አንዱ ነው) አስከትሎ እየጸለዩ በመርከብ ላይ ተሳፈሩ:: ሐዋርያት አበው መከረኞች ናቸውና ማዕበል ተነሳባቸው:: በጥቂት አፍታም መርከባቸው በማዕበሉ ተበታተነች::

+ቅዱስ አብሮኮሮስ በስባሪ ላይ ተሳፍሮ ወደ አንዲት ደሴት ደረሰ:: ግን ከንጹሑ መምሕሩ ቅዱስ ዮሐንስ ተለይቷልና አለቀሰ:: ፍቁረ እግዚእ ግን ያለ ምግብና ውሃ ማዕበለ ባሕር እያማታው ለ40 ቀናት ቆየ::

+እርሱ በፈጣሪው ፍቅር የተመሰጠ ነበርና አለመመገቡ አልጐዳውም:: በ40ኛው ቀን ግን ደቀ መዝሙሩ ወዳለበት ደሴት ማዕበሉ አደረሰው:: 2ቱ ቅዱሳን ተፈላልገው ተገናኙ:: እጅግም ደስ ብሏቸው ፈጣሪን አመሰገኑ::

+አምላካቸው ወደዚህች ደሴት ያመጣቸው በጥበቡ ነውና ሲዘዋወሩ 2 ነገርን አስተዋሉ:: 1ኛ የደሴቷ ሁሉም ነዋሪ የሚያመልኩት ጣዖትን ነው:: 2ኛ አብዛኞቹ ልዑላን (የቤተ መንግስት ውላጆች) ናቸው:: ሮምና የሚሏት አንዲት ሴት ደግሞ እነዚህን ሁሉ እየመገበች ታስተዳድራለች::

+ቅዱሳኑ በቦታው በቀጥታ ትምሕርተ ወንጌልን ቢናገሩ እንደ ማይቀበሏቸው ስለ ተረዱ ሌላ ፈሊጥን አሰቡ:: እንዳሰቡትም ወደ እመቤት ሮምና ቤት ሒደው በባርነት ተቀጠሩ::

+ለእርሷም "ድሮ የአባትሽ ባሮች የነበርን ሰዎች ነን" ስላሏት 2ቱን ቅዱሳን እሳት አንዳጅና ገንዳ አጣቢ አደረገቻቸው:: ለሰማይ ለምድሩ የከበዱ እነዚህ ቅዱሳን የካዱትን ይመልሱ ዘንድ በባርነት ግፍን ተቀበሉ:: የመከር (የማሳመኛ) ጊዜ ሲደርስም አንዳች አጋጣሚ ተፈጠረ::

+ቅዱሳኑ ዮሐንስና አብሮኮሮስ ወደ መታጠቢያ ቤቱ ሲገቡ ሰይጣን በውስጥ ኖሮ ደንግጧልና እወጣለሁ ብሎ ሲሮጥ የንጉሡን ልጅ ረግጦ ገደለው:: ሮምናና የአካባቢው ሰዎች ከበው ሲላቀሱ ቅዱሳኑ ቀረቡ::

+ሮምና ግን በቁጣ "ልትሣለቁ ነው የመጣችሁ?" በሚል ቅዱስ ዮሐንስን በጥፊ መታችው:: መላእክት እንኩዋ ቀና ብለው ሊያዩት የሚከብዳቸው ሐዋርያ ይህንን ታገሰ:: በጥፊ ወደ መታችው ሴት ቀረብ ብሎም "አትዘኚ! ልጁ ይነሳል" አላትና ጸለየ::

+ወደ ሞተውም ቀረብ ብሎ በጌታችን ስም አስነሳው:: በዚህ ጊዜም ሮምናን ጨምሮ በሥፍራው የነበሩ ሰዎች ለቅዱስ ዮሐንስ ሰገዱ:: እርሱ ግን ሁሉንም አስነስቶ ትምሕርተ ሃይማኖትን: ፍቅረ ክርስቶስን ሰበከላቸው::

+በስመ ሥላሴ አጥምቆ: ካህናትን ሹሞ: ቤተ ክርስቲያንም አንጾላቸው ወጥቷል:: በሁዋላም ለሮምናና ለደሴቷ ሰዎች ክታብ (መልዕክትን) ጽፎላቸዋል:: ይህች መልዕክት ዛሬ 2ኛዋ የዮሐንስ መልዕክት ተብላ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ትታወቃለች::

+ቅዱስ ዮሐንስ ቀጥሎ የተጉዋዘው ወደ ኤፌሶን ነው:: በዚህች ከተማ የምትመለክ አርጤምስ (አርጢሞስ) የሚሏት ጣዖት ነበረች:: አርጤምስ ማለት መልክ የነበራት ትዕቢተኛ ሴት ስትሆን አስማተኛ ባሏ ነው እንድትመለክ ያደረጋት::

+ቅዱስ ዻውሎስ ብዙ ምዕመናን ከእርሷ እንዲርቁ ማድረግ ችሏል:: ጨርሶ ያጠፋት ግን ቅዱስ ዮሐንስ ነው:: በቦታውም ብዙ ግፍ ደርሶበት: በርካታ ተአምራትን አድርጉዋል:: ቤተ ጣዖቱንም በተአምራት አፍርሶታል::

+" የፍቅር ሐዋርያ "+

=>ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ዮሐንስን 'የፍቅር ሐዋርያ' ትለዋለች:: ለ70 ዘመናት በቆየ ስብከቱ ስለ ፍቅር ብዙ አስተምሯል:: ፍቅርንም በተግባር አስተምሯል:: በየደቂቃውም "ደቂቅየ ተፋቀሩ በበይናቲክሙ - ልጆቼ ሆይ! እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ" እያለ ይሰብክ ነበር::

+በተለይ ደግሞ ከፈጣሪው ክርስቶስ ጋር የነበረው ፍቅር ፍጹም የተለየ ነበር:: በዚህ ምክንያትም ጌታ ባረገ ጊዜ እንዲህ ብሎታል:- "ለፍጡር ከሚገለጥ ምሥጢር ከአንተ የምሠውረው የለኝም" ብሎታል::

+ቀጥሎም በንጹሕ አፉ ስሞታል:: ሊቁ:-
"ሰላም ለአፉከ ለዮሐንስ ዘሰዓሞ:
ንጽሐ ኅሊናሁ ወልቡ ለዐይነ ፍትወትከ ሶበ አደሞ" እንዳለው:: (መልክዐ ኢየሱስ)

=>ቅዱስ ዮሐንስ ከእመቤታችንም ጋር ልዩ ፍቅር ነበረው:: እርሷ እንደ ልጇ ስትወደው: እርሱ ደግሞ እንደ እናቱ ልቡ እስኪነድ ድረስ ይወዳት ነበር:: እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ ተከትሎ ያገኛት እመቤቱ ናትና::

+ከዚያ ሁሉ ጸጋና ማዕረግ የመድረሱ ምሥጢርም ድንግል ናት:: ለ15 ዓመታት በጽላሎተ ረድኤቷ (በረዳትነቷ ጥላ) ተደግፎ አብሯት ሲኖር ብዙ ተምሯል:: ከመላእክትም በላይ ከብሯል:: ከንጽሕናዋ በረከትም ተካፍሏል::

+ስለ ድንግል ማርያምም "ነገረ ማርያም" የሚል ድርሰት ሲኖረው "የሰኔ ጐልጐታንም" የጻፈው እርሱ ነው::

+ድንግል ባረፈችበት ቀንም ልክ እንደ ልጇ ክርስቶስ እርሷም ስማው: ታቅፋው ዐርፋለች:: ሊቃውንቱ ለዚህ አይደል በንጹሕ ከንፈሮቿ መሳምን (መባረክን) ሲሹ:-
"በከመ ሰዓምኪ ርዕሰ ዮሐንስ ቀዳሚ:
ስዒሞትየ ማርያም ድግሚ" ያሉት::

+ታላቁ ቅዱስ ሐዋርያ ዕድሜው 90 ዓመት በሆነው ጊዜ በዚህች ዕለት ተሰውሯል:: ከዚያ አስቀድሞም የዓለምን ፍጻሜ ተመልክቷል:: ዛሬ ያለበትን የየሚያውቅ ቸር ፈጣሪው ነው::

=>እናት ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ዮሐንስን ስትጠራው እንዲሕ ነው:-
*ወንጌላዊ
*ሐዋርያ
*ሰማዕት ዘእንበለ ደም
*አቡቀለምሲስ (ምሥጢራትን ያየ)
*ታኦሎጐስ (ነባቤ መለኮት)
*ወልደ ነጐድጉዋድ
*ደቀ መለኮት ወምሥጢር
*ፍቁረ እግዚእ
*ርዕሰ ደናግል (የደናግል አለቃ)
*ቁጹረ ገጽ
*ዘረፈቀ ውስተ ሕጽኑ ለኢየሱስ (ከጌታ ጎን የሚቀመጥ)
*ንስር ሠራሪ*ልዑለ ስብከት
*ምድራዊው መልዐክ
*ዓምደ ብርሐን
*ሐዋርያ ትንቢት
*ቀርነ ቤተ ክርስቲያን
*ኮከበ ከዋክብት

=>በቅዱስ ዮሐንስ ላይ ያደረ የእመቤታችን ድንግል ማርያምና የአንድ ልጇ ፍቅር በእኛም ላይ ይደር::

=>ቅዱስ ዮሐንስን የወደደ ጌታ በፍቅሩ ይጠግነን:: ከእናቱ ፍቅር አድርሶ በሐዋርያው በረከት ያስጊጠን::

=>ጥር 4 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ዮሐንስ ሐዋርያ
(ፍቁረ እግዚእ)
2.አባ ናርዶስ ጻድቅ (ዘደብረ ቢዘን)
3.ቅዱስ ጊዮርጊስ
4.ቅዱስ ማርቴና

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ
2.ቅዱስ እንድርያስ ሐዋርያ
3.ቅድስት ሶፍያ ሰማዕት
4.ቅዱስ ዮሐንስ ዘሐራቅሊ (ሰማዕት)

=>+"+ በጌታ ኢየሱስ መስቀል አጠገብ እናቱ: የእናቱም እህት: የቀለዮዻም ሚስት ማርያም: መግደላዊትም ማርያም ቆመው ነበር:: ጌታ ኢየሱስም እናቱን: ይወደው የነበረውንም ደቀ መዝሙር በአጠገቡ ቆሞ ባየ ጊዜ እናቱን 'አንቺ ሆይ! እነሆ ልጅሽ' አላት:: ከዚህ በሁዋላ ደቀ መዝሙሩን 'እናትህ እነሁዋት' አለው:: ከዚህም ሰዓት ጀምሮ ደቀ መዝሙሩ ወደ ቤቱ ወሰዳት:: +"+ (ዮሐ. 19:25)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
እንኳን ለቅዱስ "ማቴዎስ ነዳይ" እና "ቅዱስ አውስግንዮስ አረጋዊ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ቅዱስ አባ ማቴዎስ "*+

=>ቅዱሱ አባት በቤተ ክርስቲያናችን ስመ ጥር ነው:: በተለይ ትርጉዋሜ ወንጌል ላይ እንደ አብነት ሲጠቀስ የተአምረ ማርያምን ሥርዓት በማዘጋጀቱ የበዓላት መቅድመ ተአምር ላይ ስሙ አለ:: ቅዱሱ ለእመቤታችን በነበረው ፍቅር ድንግል ብዙ ጊዜ ትገለጥለት ነበርና::

+ቅዱስ ማቴዎስ ግብጻዊ አባት ሲሆን የነበረው በመካከለኛው ዘመን ውስጥ (ማለትም በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን) ነው:: በቤቱም መልካም ወላጆችና ያዕቆብ የሚባል ወንድምም ነበረው::

+እንዲያውም አንዴ እናቱ ቅዱሱን ጸንሳ ሳለች የበቁ አበው ሆዷን እጅ ነስተው "ቅዱስ ፍሬ በማኅጸንሽ ውስጥ አለ" እንዳሏት ይነገራል:: ቅዱስ ማቴዎስ በልጅነቱ ወደ እግዚአብሔር ከመገስገስ: ቅዱስ ቃሉን ከመማር በዘለለ ሌላ ሃሳብ አልነበረበትም::

+ወጣት ሲሆንም ወላጆቹ ተከታትለው በማረፋቸው ከወንድሙ ያዕቆብ ጋር ለብቻቸው ቀሩ:: ብዙ የወላጆቹ ሃብት ቢኖርም ቅዱስ ማቴዎስ ስለ መካፈል አላሰበም:: ከለበሳት ጨርቅ በቀር ምንም ሳይይዝ ወደ በርሃ ገሰገሰ::

+ሊመነኩስ ወዶ የደብረ ቅዱስ አቡፋናን አበው ቢጠይቃቸው "አይሆንም" አሉት:: ምክንያቱም በጊዜው ወንድሙን ያውቁት ስለ ነበር እየመጣ እንዳያውካቸው "አስፈቅድ" ማለታቸው ነበር:: ቅዱስ ማቴዎስ ግን ወደ ሌላ ገዳም ሔዶ አለቀሰ::

+አባቶችም ወደ ወንድሙ ሔደው ስለ ማለዱት ፈቀደለት:: ስለዚህም በደብረ አቡፋና መነኮሰ:: ትንሽ ቆይቶ ግን ወንድሙ ያዕቆብ "ለወንድሜ ያልሆነች ዓለም ለእኔም አትረባኝም" ብሎ: በርሃ ገብቶ በቅቶ ዐርፏል::

+ቅዱስ ማቴዎስም በገዳሙ በፍቅርና በመታዘዝ ሲያገለግል ዜና ትጋቱ ተሰማ:: ይህንን ከሰሙት ዻዻሳት አንዱ አባ ዼጥሮስ ያለ ፈቃዱ ከገዳም አስወጥቶ በመንበረ ዽዽስናው ረዳት አደረገው:: እርሱ ግን አንገቱን አቀርቅሮ ተጋድሎውን በጾምና በጸሎት ቀጠለ::

+ነገር ግን ሰይጣን በሴቶች አድሮ ፈተነው:: በጣም አዝኖ ዻዻሱን "አሰናብተኝ" አለው:: "እንቢ" ቢለው የክብር ልብሱን (የዻዻሱን) አውጥቶ በመቀስ ብጥስጥስ አደረገውና በዻዻሱ ፊት አኖረለት::

+ፈጽሞ የተበሳጨው ዻዻሱም በየቀኑ 300 እንዲሰግድ: ወደ ቤት እንዳይጠለልና ሌሎች ቀኖናዎችን ቅጣት ሰጥቶ ወደ በርሃ አሳደደው:: ቅዱስ ማቴዎስም መሻቱ ይህቺው ነበረችና ደስ እያለው ሔደ::

+ለ2 ዓመታትም የቀኑ ሐሩር: የሌሊቱ ቁር እየተፈራረቀበት ቅጣቱን በመፈጸሙ የፍትሐት ደብዳቤ ተላከለት:: አንድ ቀን ግን በገዳሙ የነበረ አንድ የበቃ አባት ክብረ ማቴዎስ ተገልጦለት "የብዙዎች አባት ትሆናለህ" አለው::

+ውዳሴ ከንቱን ፈጽሞ የሚጠላት ቅዱሱ ግን አዘነ:: ሰዎች እያከበሩት ስለተቸገረም ገዳሙን ለቀቀ:: በሔደበት ገዳምም ድንቅ ነገሮቹን እያዩ ሲያከብሩት በአንድ ገዳም የማይቀመጥ ሆነ:: ከአንዱ ወደ ሌላውም ይሔድ ነበረ::

+ቅዱስ ማቴዎስ ከዻዻሱ ዘንድ እያለ ቅስናን ሹሞት ነበርና በገዳማት ይቀድሳል:: ከብቃቱም የተነሳ በቅዳሴ ሰዓት ማሕበረ መላእክትን ያያቸው ነበር:: መድኃኒታችን ክርስቶስም ሕጻን መስሎ ከፊቱ ይቀመጥ ነበር:: ስለዚህ ነገርም ዕንባው እንደ ዥረት ውሃ ይፈስ ነበር:: እየቀደሰም ተመስጦ (ተደሞ) ይመጣበት ነበር::

+ዘወትር የፈጣሪውን ጌትነት እያደነቀ ይመራመር ነበርና አንዴ ቀና ቢል 7ቱ ሰማያት ተከፈቱለት:: እግዚአብሔርንም ከጽርሐ አርያም (7ኛው ሰማይ) ከፍ ብሎ አየው:: ደንግጦ ዝቅ ቢል ደግሞ ከጥልቁ በታች ተመለከተው::

+በዚህ ጊዜ "ይህን ያሳየኸኝ ጌታየ እኔ ማነኝ!" ሲል አለቀሰ:: ሁሌ ዐርብም ሕማማተ ክርስቶስን: በተለይ መድኃኒታችን መቸንከሩን እያሰበ ረጅም ችንካርን በጉልበቱ ውስጥ ይከት ነበር:: ለቀናት ስለማያወጣውም ደሙ ፈሶ አካሉ መልኩ ይቀይር ነበር::

+እንዲህ ካሉ የቅድስናና የተጋድሎ ዓመታት በሁዋላም ሌላ ጥሪ ከፈጣሪው መጣለት:: አበው በጸሎት ላይ ሳለ መጥተው አሠሩት:: "ምን አደረኩዋችሁ አባቶቼ?" ቢላቸው የግብጽ ፓትርያርክ ነህ ከዚህ በሁዋላ" አሉት:: ቢለምናቸውም እንቢ አሉት::

+"እንግዲያውስ" ብሎ: ምላሱን አውጥቶ: በመቀስ ቆርጦ ጣላት:: መናገር የማይችል ሰው ክህነት አይሾምምና:: (እንዲህ ነበር አበው ሥልጣንን የሚሸሿት) ነገር ግን እመቤታችን ከሰማይ ወርዳ "ወዳጄ! ነገሩ የልጄ ፈቃድ ስለ ሆነ እሺ በላቸው" ብላ አዲስ ምላስን ሰጠችው::

+የግብጽ 87ኛ ሊቀ ዻዻሳት ሆኖ ሥርዓተ ሲመቱ ሲፈጸም የወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ራሱ በዚያ ነበረችና ክንፍ አውጥታ: በራ ቅዱስ ማቴዎስን ስትስመው ሁሉም አዩ:: ከሰማይም ማሕበረ መላእክት "አክዮስ-ይገባዋል" ብለው ሲጮሁ ተሰማ::

+ቅዱስ ማቴዎስ ምንም ፓትርያርክ ቢሆንም ለትምሕርት: ለቅዳሴና መሰል ነገሮች ካልሆነ ከበዓቱ አይወጣም ነበር:: ገንዘብ የሌለው: ጥሩ ልብስ የማይለብስ ነበርና "ነዳዩ" እየተባለ እስካሁን ይጠራል::

+በዘመነ ዽዽስናው ብዙ ተግባራትን ሲከውን ዋኖቹ ግን የእመቤታችን ተአምር በሥርዓት እንዲነበብ ማድረጉ ቀድሞ ይጠቀሳል:: በተረፈም የጌታችን ግማደ መስቀሉ ወደ ኢትዮዽያ እንዲመጣም ትልቅ አስተዋጽኦን አድርጉዋል::

+በተሰጠው የትንቢት ሃብትም ወደ ፊት የሚፈጸሙ ነገሮችን ተመልክቷል:: የተናገራቸውም ሁሉ ተፈጽመዋል:: በመጨረሻው ግን ያሰቃየው የነበረው የወቅቱ የግብጽ ከሊፋ (ክፉ ሰው) አስጠርቶ አካሉ እስኪደቅ ድረስ ገረፈው::

+ቅዱስ ማቴዎስም ወደ እመቤታችን ጮኸ:: ድንግልም ወርዳ አጽናናችውና "አሳርፍሃለሁ" አለችው:: ሕዝቡን ተሰናብቶም በዚህች ቀን ዐርፏል::

+*" ቅዱስ አውስግንዮስ አረጋዊ "*+

=>ይህ ቅዱስ ሽማግሌ በሃይማኖቱ ጽናት: በምግባሩ ብዛት ለወጣቶች አብነት መሆን የቻለ አባት ነው:: በብዛት የሚታወቀው በሰማዕትነቱ ቢሆንም በቅዱስ ሰውነቱ በርካታ መልካም ነገሮችን ሠርቷል::

+በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን መነሻ አካባቢ (ዘመነ ሰማዕታት ሊጠናቀቅ ሲል ማለት ነው) የቅዱስ ቆስጠንጢኖስ (የንጉሡ) ወታደር ሁኖ ተቀጠረ:: ንጉሡ ወደ መክስምያኖስ ለጦርነት ሲሔድ በሰማይ ላይ መስቀልና "ኒኮስጣጣን" የሚል ጽሑፍን ተመልክቷል::

+ሁሉም ሰው ለመተርጐም ሲፈራ ወጣቱ አውስግንዮስ ግን በድፍረት ለንጉሡ ክብረ መስቀልንና ትርጉሙን አስረዳ:: በቅዱሱ ንጉሥ ሥርም በወታደርነት ለ20 ዓመታት አገለገለ::

+ከዚያም ሥጋዊ ተግባሩን ትቶ በጾምና በጸሎት: ሰዎችንም በማስታረቅ: በማስተማርም ተወሰነ:: ፈጣሪ ጸጋውን አብዝቶለትም ዕድሜው 110 ዓመት ደረሰ::

+በጊዜውም የነበረው ከሃዲው ዑልያኖስ "ሰዎችን አስታርቀሃልና ክርስቶስን አምልከሃል" በሚል በዚህች ቀን አንገቱን አሰይፎታል:: ዑልያኖስን ደግሞ ቅዱስ መርቆሬዎስ ተበቅሎታል::

=>አምላከ ቅዱሳን ስለ አባቶቻችን ሲል ይማረን:: ከበረከታቸውም ይክፈለን::

=>ጥር 5 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ አባ ማቴዎስ
2.ቅዱስ አውስግንዮስ አረጋዊ (ሰማዕት)
3.ቅድስት እስክንድርያ
4.ቅድስት አውስያ ሰማዕት

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ዼጥሮስ ሊቀ ሐዋርያት
2.ቅዱስ ዻውሎስ ብርሃነ ዓለም
3.አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ
4.ቅዱስ ዮሐኒ ኢትዮዽያዊ
5.ቅዱስ አሞኒ ዘናሒሶ
6.ቅድስት አውጋንያ (ሰማዕትና ጻድቅ)
2024/09/25 19:28:50
Back to Top
HTML Embed Code: