Telegram Web Link
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
ታኅሣሥ 15-የእኔ ቢጤ የነበሩትና ጽድቃቸውን ማንም ሳያውቅባቸው የኖሩት ጻዱቁ አባ ቆራይ ዕረፍታቸው ነው፡፡
+ በአንዲት ምሰሶ ላይ ወጥተው ከዚያ ሳይወርዱ በላይዋ ላይ ሆነው ታላቅ ተጋድሎን እየተጋደሉ 45 ዓመት የኖሩት አቡነ ሉቃስ ዘዓምድ ዕረፍታቸው ነው፡፡
+ በከሃዲው ንጉሥ ድርጣድስ አማካኝነት በጥልቅ ጉድጓድ ውስጥ በተጣሉበት በዚያው ለ15 ዓመታት በመኖር ደም ያለማፍሰስ ሰማዕት የሆኑት የአርማንያው አቡነ ጎርጎርዮስ ዕረፍታቸው ነው፡፡

የእኔ ቢጤው አባ ቆራይ፡- እጅና እግር የሌላቸውና የእኔ ቢጤ የነበሩት ጽድቃቸውን ማንም ሳያውቅባቸው የኖሩት አባ ቆራይ ጻድቅ መሆናቸው ካረፉ በኋላ ነው የታወቀው፡፡ ገዳማቸው ትግራይ ተንቤን ውስጥ ይገኛል፡፡ ቅዱሱ በዐፄ ልብነ ድንግል ዘመነ መንግሥት በትግራይ ተንቤን አውራጃ አዲ ራእሶት-የራሶች (የታላላቅ ሰዎች አገር) በሚባለው ቦታ የእግርና የእጅ ጣቶች የሌሏቸው አባ ቆራይ ወንበር በምትመስል ድንጋይ ላይ ተቀምጠው ተገለጡ፡፡ አንድ የአካባቢው ሰው በመንገድ ሲያልፍ አባ ቆራይ ድንጋይ ላይ ተቀምጠው ጸሎት ሲያደርጉ አያቸውና በሁኔታው ተገርሞ ወደ እርሳቸው ጠጋ ብሎ ስማቸውንና የመጡበትን አገር ጠየቃቸው፡፡ እርሳቸውም ‹‹ስሜ አባ ቆራይ ይባላል፣ አገር ግን የለኝም›› አሉት፡፡ እርሱም እባክዎን ወደ መንደር እንሂድና የጸሎትና ቤት ሠርተንልዎት በዚያ ይቀመጡ›› አላቸው፡፡ አባ ቆራይ ግን ‹‹ማረፊያዬ ይህቺ ናት፣ ከዚህች ሥፍራ አልነሣም›› አሉት፡፡ አባ ቆራይም በዚያው እንደተቀመጡ ዝናቸው በሁሉ ዘንድ ተሰማና ሰዎች መጥተው በተቀመጡበት ድንጋይ ዙሪያ ጎጆ ቀለሱላቸው፡፡
ከዚህም በኋላ መንደርተኞቹ በየተራ በምግብ ሊረዷቸው ዕጣ ተጣጥለው ወደየቤታቸወ ሄዱ፡፡ በመጀመሪያ ተራ የደረሰው ሰው ከአንድ ሰዓት በኋላ ምግብ ይዞ ቢመለስ የአባ ቆራይ ጎጆ በብርሃን ተሞልታ አገኘ፡፡ ወደ ጎጆዋም ሲጠጋ ነበልባሉ እየፈጀው አላስቀርበው አለ፡፡ እርሱም በድንጋጤ ወደ መንደሩ ተመልሶ ለአካባቢው ሰው ነግሮ ሁሉም ተሰብስበው መጡ፡፡ መንደርተኛውም ካህናትን ይዘው ብዙ የምሕላ ጸሎትና እግዚኦታ ካደረሱ በኋላ እግዚአብሔር ወደ ጎጆዋ እንዲገቡ ፈቀደላቸውና ገቡ፡፡ ነገር ግን አባ ቆራይን በሕይወት አላገኟቸውም፡፡ አስክሬናቸውን ብርሃን ከቦት አገኙት፡፡ ከአስክሬናቸው አጠገብ ‹‹የአባ ቆራይን አስክሬን ከዚህች ጎጆ ውስጥ እንድትቀብሩት፤ ወደ ሌላ ቦታ ወይም ቤተ ክርስቲያን ወስደን እንቀብራለን ብላችሁ እንዳታስቡ፡፡ ነገሩን በድፍረት ብትፈጽሙት በሀገሩ ላይ እግዚአብሔርን ቁጣ ታመጣላችሁ›› የሚል ትእዛዝ በብራና ተጽፎ ተገኘ፡፡ በዚሁ ትእዛዝ መሠረት የአሀሩ ሕዝብ ተሰብስቦ አባ ቆራይን ታኅሣሥ 15 ቀን እዚያው ቀበሯቸው፡፡

ከጥቂት ዘመናት በኋላ ባልና ሚስት የሆኑ ሰዎች መቆመም ሆነ መራመድ የማይችል ድውይ ልጃቸውን ይዘው ወደ ጸበል ሲሄዱ መሸባቸውና በአካባቢው ማደሪያ ሲፈልጉ የአባ ቆራይ ጎጆ ክፍት ሆኖ ታያቸውና ልጃቸውን ይዘው ሄደው ገቡ፡፡ ድውይ ልጃቸውን በአባ ቆራይ መቃብር ላይ ቢያስተኙት የኤልሳዕን አጥንት እንደነካውና ፈጥኖ እንደተነሣው ሙት ይህ ድውይ ልጅም በአባ ቆራይ መቃብር ላይ እንዳረፈ ወዲያው አፈፍ ብሎ በመነሣት እንደ እንቦሳ ጥጃ መዝለል ጀመረ፡፡ ወላጆቹም እልልታቸውን አቀለጡት፡፡ ወላጆቹም በነጋ ጊዜ ወደ መንደርተኛው ሄደውየተደረገላቸውን ተአምር ተናገሩ፡፡ ከዚያም ጊዜ ጀምሮ የአባ ቆራይ በዓል በአካባቢውና አጎራባች ቦታዎች ሁሉ ዘንድ መከበር ጀመረ፡፡ የእረፍታቸውም በዓል ታኅሣሥ 15 ቀን ሆነ፡፡
አባ ቆራይ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ለይተው እንደ ቅዱስ አልዓዛር (ሉቃ 16፡19-35) ለዚህ ዓለም ውዳቂ መስለው ለታላቅ ክብር የበቁ ጻድቅ አባት ናቸው፡፡ ዛሬም ልብሳቸውንና አካላቸውን ብቻ እያየን የምንንቃቸው ሰዎች እንደ አባ ቆራይ ያሉ ቅዱሳን ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ከልዑል እግዚአብሔር በቀር ማንም ማንንም የሚያውቅ የለም።
የአባ ቆራይ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን!
+ + +

አቡነ ጎርጎርዮስ ዘአርማንያ፡- የአርማንያው ሊቀ ጳጳሳት አቡነ ጎርጎርዮስ በንጉሡ ድርጣድስ ዘመን ሰማዕትነትን የተቀበሉ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ ንጉሡም ዕጣን ሊያሳርግ ወደ ጣዖት ቤቱ ሲገባ አቡነ ጎርጎርዮስን ጠርቶ ለአማልክት ዕጣን አሳርጉ አላቸው፡፡ እሳቸውም ትእዛዙን አልፈጽምም ባሉት ጊዜ እጅግ ጽኑ በሆኑ በተለያዩ ሥቃዮች አሠቃያቸው፡፡
ንጉሡም ብዙ ካሠቃያቸው በኋላ ጥልቅ ጉድጓድ አስቆፍሮ በዚያ ውስጥ ጣላቸው፡፡ አባታችንም በዚያ ጥልቅ ጉድጓድ እንደተጣሉ ለ15 ዓመታት ኖሩ፡፡ ስለምግባቸውም እግዚአብሔር አንዲት እናትን አዘዘላቸው፡፡ በንጉሡ አዳራሽ አቅራቢያም የምትኖረው ይህች ሴት በእግዚአብሔር ታዝዛ እንጀራን እየጋገረች ወደ ጉድጓዱ ትጥልላቸው ነበር፡፡ ከእርሷም በቀር አባታችን በሕይወት መኖራቸውን የሚያውቅ ሰው የለም፡፡ እንዲህም እያደረገች 15 ዓመት ኖራለች፡፡

ንጉሡ ድርጣድስም ቅድስት አርሴማን ማግባት ፈልጎ ሳለ ፈጽሞ እምቢ ብትለው በእርሷ ምክንያት ብዙ ደናግል ሴቶችን ገደለ፡፡ ሰይጣን በልቡ ያደረበት ይህ ንጉሥ ድርጣድስም ደናግሎቹን እና ቅድስት አርሴማን በብዙ ሥቃይ ከገደላቸው በኋላ ሥጋቸውን በተራራ ላይ ጥሎት ነበር፡፡ ነገር ግን ምንም ሳይሆን በጌታችን ጥበቃ ኖረ፡፡ የቅድስት አርሴማንም ውበቷን እያሰበ ስላስገደላት የሚጸጸት ሆነ፡፡ ወገኖቹም ‹‹ከሀዘንህ ታርፍ ዘንድ ወደ ጫካ ሄደን አውሬ አድን›› አሉት፡፡ ንጉሡም በፈረሱ ተቀምጦ ወደ ጫካ ወጣ፡፡ ነገር ግን ሰይጣን ተዋሃደውና በእነ ቅድስት አርሴማና በአቡነ ጎርጎርዮስ ላይ በሠራው ግፍ እግዚአብሔር የተፈጥሮ መልኩን ቀይሮት እንደ እሪያ አደረገው፡፡
ንጉሡ ድርጣድስ ወደ እሪያነት ከተለወጠ በኋላ ያገኘውን ሁሉ የሚናከስ ሆነ፡፡ በቤተ መንግሥቱም ባሉ ሰዎች ላይ ሰይጣን አደረባቸውና ታላቅ ጭንቅ ሆነ፡፡ የንጉሡም እኅት በሌሊት ‹‹ጎርጎርዮስን ከጉድጓድ ካላወጣችሁት በቀር አትድኑም›› የሚል ራእይ አየችና ለወገኖቿ ነግረቻቸው፡፡ የሞተ መስሏቸው ስለነበር ይህን ሲሰሙ እጅግ ደነገጡና ሄደው ቅዱስ ጎርጎርዮስን 15 ዓመት ተጥሎ ከኖረበት ጉድጓድ ውስጥ በገመድ ጎትተው አወጡትና አክብረው ወሰዱት፡፡ እርሱም የደናግሉን ሥጋ ወዴት እንዳደረሱት ሲጠይቅ በተራራው ላይ እንዳለ ነግረውት ሄዶ ሲያየው ምንም ሳይነካው በደህና አገኘው፡፡ አንሥቶም ባማሩ ቦታዎች አኖራቸው፡፡ ሰይጣን ያደረባቸውን የቤተ መንግሥቱንም ሰዎች ፈወሳቸው፡፡ ስለ ንጉሡም ወደ አውሬነት መለወጥ ነግረውት እንዲፈውሰው ለመኑት፡፡
አቡነ ጎርጎርዮስም ወደ ንጉሡ ሄደው በእሪያነቱ ሳለ ‹‹ብፈውስህና ባድንህ ከክፉ ሥራህ ትመለሳለህ? በእውነተኛው አምላክ በኢየሱስ ክርስቶስ ታምናለህ?›› አሉት፡፡ እሪያ የነበረው ንጉሥም ‹‹አዎ›› ቢላቸው ጸሎት አድርገው ፈውሱት፡፡ አእምሮውና የቀድሞው መልኩም ተመለሰለት፡፡ ነገር ግን አቡነ ጎርጎርዮስ ንጉሡ ዳግመኛ እንዳይታበይ በማለት ከእግሩ ላይ የእሪያ ጥፍር አስቀሩለት፡፡ የቤተ መንግሥንም ሰዎች ሁሉ ከፈወሳቸው በኋላ 8 ቀን እንዲጾሙ አዘዛቸው፡፡ ሃይማኖትንም አስተምሮ ሥርዓት ሠራላቸው፡፡ እርሱም ክህነት አልነበረውምና ወደ ሮሜው ንጉሥ ወደ አኖሬዎስና ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ መልአክት ላኩና ጳጳስ ይላኩላችሁ አላቸው፡፡ የሮሙ ሊቀ ጳጳሳትም ጎርጎርዮስን ሾሞ ላከላቸው፡፡ ንጉሡ አኖሬዎስም በዚህ ተደሰተ፡፡ ጎርጎርዮስም ተሹሞ ከመጣ በኋላ ሁሉንም አጠመቃቸው፡፡
አርማንያም በቅዱስ ጎርጎርዮስ ትምህርት በክርስትና የምትታወቅ አገር ሆነች፡፡ እርሱም በእመቤታችን ስም ቤተ ክርስቲያን ሠርቶላቸው በመልካም መንገድ አገልግሎአቸው ታኅሣሥ 15 ቀን በሰላም ዐርፏል፡፡ መስከረም 19 ደግሞ ከጉድጓድ የወጣበት ዕለት ነው፡፡ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን!
+ + +

አቡነ ሉቃስ ዘዓምድ፡- ሀገሩ ፋርስ ሲሆን በመቶ የንጉሡ ጭፍራ ላይ መኰንን ሆኖ ተሹሞ ነበር፡፡ በኋላም ሹመቱን ትቶ ገዳም ገብቶ መነኮሰ፡፡ በምሥራቅ ካሉ ገዳማት ውስጥ በአንዱ ገብቶ ብዙ ዘመን ሲጋደል ኖረ፡፡ ልብሱንም የብረት ልብስ በማድረግ እስከ 6 ቀን የሚጾም ሆነ፡፡ ከዚህም በኋላ ከዓምድ ላይ ወጥቶ በዚያ ላይ ሦስት ዓመት ለጸሎት ቆመ፡፡ የታዘዘ መልአክም መጥቶ ከዚያ ዓምድ ላይ እንዲወርድ ነግሮት በብርሃን መስቀል እየመራው ወስዶ አንድ ገዳም አደረሰው፡፡ በዚያም ብዙ ተአምራት እያደረገ ኖረ፡፡

ከዚህም በኋላ አቡነ ሉቃስ አርምሞ ያዘ፡፡ ከቶ እንዳይናገርም በአፉ ውስጥ ድንጋይ ነክሶ ያዘ፡፡ አሁንም መልአኩ ወደ ቍስጥንጥንያ ዳርቻ ቦታ ይዞት እየመራ ወስዶት በዚያም አንዲት ምሰሶ ላይ ወጥቶ ታላቅ ተጋድሎን እየተጋደለ በላይዋ ላይ 45 ዓመት ኖረ፡፡ በዚያም አስደናቂ ተአምራትን እያደረገ ብዙዎችን በመፈወስና ወንጌልን በማስተማር ብዙ ደከመ፡፡ ታኅሣሥ 15 ቀን ካረፈ በኋላ ሊቀ ጳጳሳቱና ካህናቱ መጥተው በክብር ወደ ቍስጥንጥንያ ከተማ ወሰዱት፡፡ በዚህም ጊዜ በድውያን ላይ ታላቅ ፈውስ ሆነ፡፡ የአባ ሉቃስ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን!
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
ታኅሣሥ 16-የደብረ ድማኅ ታላቁ ጻድቅ አቡነ መርቆሬዎስ ዕረፍታቸው ነው።
+ እናታችን ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ በስሚዛ ሰንሰል እንጨት በአይጥ ሀረግ በነጠላ ማገር ቤተ ክርስቲያኗን በዕለተ ዐርብ ጠዋት ጀምራ ማታ በአንድ ቀን የጨረሰችበት ዕለት ነው።

+ መስፍነ እሥራኤል ቅዱስ ጌዴዎን ዕረፍቱ ነው፡፡
+ የሙሴ እኅት ማርያም ዓመታዊ መታሰቢያ በዓሏ ነው፡፡

አቡነ መርቆሬዎስ ዘደብረ ድማኅ፦ ወላጆቻቸው ካህኑ ቶማስ ስምዖን እና ሰሎሜ እግዚአብሔርን የሚያገለግሉ ቅዱሳን ስለነበሩ በየወሩም ዝክረ ቅዱስ ሰማዕት መርቆሬዎስ (ፒሉፓዴር) እያደረጉ ሲኖሩ በእለተ ቀኑ ተኣምር ስለተደረገላቸው የልጃቸውን ስም መርቆሬዎስ ብለው ሰየሙት፡፡ አቡነ መርቆሬዎስ ከተወለዱበት ጊዜ ጀምሮ ሲያሳዩት የነበው ተግባራት ሁሉ የትልቅ ሰው እንጂ የአንድ ሕፃን ጠባይ ስላልሆነ ወላጆቻቸው በአንክሮ ያስተውሉ ነበር፡፡

አቡነ መርቆሬዎስም ፊደል በመቁጠር የጀመሩት መንፈሳዊ ትምህርት 22 ዓመት ሲሞላቸው የብሉይ ኪዳንና የሐዲስ ኪዳን እንዲሁም የሁሉም መጻሕፍት ምሥጢር ተገለጠላቸው፡፡ ከአቡነ ኤዎስጣቴዎስ ደግሞ በ33 ዓመታቸው በደብረ ሸማና እያሉ ምንኵስናን እና አስኬማን መላእክትን ተቀበሉ፡፡ ከዚህኽም በኋለ አቡነ መርቆሬዎስ ለረጅም ጊዜ በምናኔ ኖረው ወንጌልን በመስበክና ክርስትናን በማስፋፋት ወደ ተለያዩ ሀገሮች እየተዘዋወሩ እያስተማሩ በርካታ ተኣምራትንም እያደረጉ ለ67 ዓመታት ያህል በታላቅ ተጋድሎ ኖሩ፡፡

አቡነ መርቆሬዎስ የመንፈስ አባታቸው የሆኑት አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ወደ ኤርትራ ሀገር እንደሚሔዱ በመንፈስ ቅዱስ ዐውቀው በራቂት የምትባል ቦታ ላይ ኹለቱ ቅዱሳን ተገናኙ፡፡ ኹለቱም ቅዱሳን አብረው ወንጌል እየሰበኩ ማይምነ ሲደርሱ ግን ሕዝቡን ከእግዚአብሔር ሕግ ርቆ በኀጢአት ወድቆ አገኙት፤ በዚያ ያሉ ክፉዎች ሰዎችም በሰይጣን ምክር ተመርተው አባቶቻችን ተኝተውባት የነበረችውን ጎጆ በእሳት አቃጠሏት። ቅዱሳኑ አቡነ መርቆሬዎስና አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ግን በዛ እሳት ሳይነኩ በእግዚአብሔር ተኣምር ዳኑ፡፡ ከዚኽም በኋላ እነዚህ ቅዱሳን አባቶች በአሁኑ ደብረ ደናግል ደብረ ድማኅ በሚባለው ቦታ ላይ ሱባኤ ገብተው አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ለሰባት ዓመት፣ አቡነ መርቆሬዎስ ደግሞ ለአራት ዓመት ባእት አበጅተው በጽኑ ተጋድሎ ኖሩ፡፡ ከሰባት ዓመት ሱባኤ በኋላ ከእግዚአብሔር ባዘዛቸውና ራእይ ባዩት መሠረት አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ወደ አርማንያ እንዲሔድ ሲነገራቸው አቡነ መርቆሬዎስን ደግሞ አንዲት ወፍ እየመራቻቸው ዛሬ ላይ በስማቸው ወደሚጠራው ታላቁ ገዳም ደብረ ድማኅ አደረሰቻቸው፡፡

አቡነ መርቆሬዎስም ቦታዋን እንዳዩአት ‹‹ይህቺ ለዘለዓለም ማረፊያየ ናት›› አሉ፡፡ የክብር ባለቤት መድኀኔዓለምም በአካል ተገልጦላቸው መጥቶ በአራቱ ማዕዘን ባረከላቸው፡፡ በዚህ ቦታ ላይ ይኖሩ የነበሩት ሰዎችም አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ወደ አርማንያ እንደሚሔዱ ሲሰሙ ‹‹የእናንተ ረድኤት እንዲሆንልን ቀድሳችሁ አቊርቡን›› ሲሏቸው ሁለቱ ቅዱሳን በጋራ ጥር 18 ቀን ቅዳሴ ቀድሰው ሕዝቡን አቊርበዋል፡፡ አቡነ መርቆሬዎስም አባታቸውን አቡነ ኤዎስጣቴዎስን ተከትለው ኹለቱም እስከ ሱዳን ድረስ ሔደው ወንጌልን በመስበክ ሰፊ ሐዋርያዊ አገልግሎት ሰጥተዋል፡፡ ከዚኽም በኋላ በግብፅ ተሻግረው አርማንያ ደርሰው ወደ ኢየሩሳሌም በመሔድ ቅዱሳት መካናትን ተሳልመዋል፡፡ ከዚያም አቡነ መርቆሬዎስ ወደ ገዳም ተመልሰው ሲመጡ ዉጡሕ በተባለ
ቦታ ላይ በኣት አጽንተው ሱባኤ ያዙ፡፡ እርሳቸውም በዕለተ ዐርብ መጋቢት 12 ቀን የቅዱስ ሚካኤል በዓል ዕለት በኣታቸው ውስጥ እየጸለዩ ሳሉ ድንገት ቁመቱ 170 ክንድ ጎኑ ደግሞ 9 ክንድ ከስንዝር የሚሆን ሰይጣን ከነጭፍሮቹ በውስጡ ያደረበት ታላቅ ዘንዶ ይውጣቸው ዘንድ መጣ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ከእርሳቸው ጋር ስለነበር ጸሎታቸውን ሰምቶ ቅዱስ ሚካኤልን ላከላቸው፡፡ መልአኩም ድል የሚያደርጉበትን መስቀል ሰጣቸው፡፡ ጻድቁም ከመልአኩ በተቀበሉት ቅዱስ መስቀል በሥላሴ ስም ቢያማትቡበት ዘንዶው ተሰንጥቆ በውስጡ አድረውበት የነበሩት አጋንንትከዘንዶው ወጥተው ሮጠው ሊያመልጡ ሲሉ አባታችን አወገዟቸው፡፡ ዘንድውንም ወስደው ዱበና በሚባል በረሓ ውስጥ ጣሉት፡፡

ጻድቁም ዘንዶውን ስለገደሉላቸው ለአካባቢው ሰዎችም ሆነ ለፍጥረታት ሁሉ ሰላምና ዕረፍት ሆነላቸው፡፡ ይኽንንም መሠረት በማድረግ በየአመቱ መጋቢት 12 ቀን መነኰሳት
አባቶች ከገዳም ታቦት ይዘው ወደዚህ ቦታ በመሔድ ይቀድሳሉ፣ በዓሉንም ያከብራሉ፡፡ በወቅቱ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል የሰጣቸው ረጅም መስቀልም እስከ አሁን ድረስ የተለያየ ተኣምራት እያደረገ በገዳሙ ይገኛል፡፡

አቡነ መርቆሬዎስ ከብዙ ተጋድሎ በኋላ ‹‹ሥጋየ የሚያርፍበትን ቦታ ግለጽልኝ›› ብለው ወደ እግዚአብሔር ቢጸልዩ በአሁኑ ጊዜ ቅዱስ ዐፅማቸው በክብር ያረፈበት ገዳም ደብረ ድማኅ እንደሆነ ገለጸላቸው፡፡ በ1340 ዓ.ም ስድስት መቶ መነኰሳትና ሦስት መቶ መነኰሳያይት ወደ አባታችን መጥተው መንኵሰዋል፡፡ አቡነ መርቆሬዎስም ሥርዐተ ምንኵስና ሠርተው ገዳም ገድመው ልጆቻቸውን በቅድስና ሲጠብቁ ኖሩ፡፡

አቡነ መርቆሬዎስ ገዳማቸው ሳሉ በአርማንያ ሀገር የአቡነ ኤዎስጣቴዎስ የዕረፍታቸው ነገር በራእይ ስለተገለጠላቸው ከ25 መነኰሳት ጋር ወደ አርማንያ ሔዱ፡፡ ነገር ግን
ለመርከብ የሚከፍሉት ገንዘብ ስላልነበራቸው አስቀድመው ከአባታቸው ጋር በአጽፋቸው የተሻገሩትን ባሕር በደመና ተጭነው በማለፍ አርማንያ ሀገር ደርሰው አቡነ ኤዎስጣቴዎስን አገኟቸው፡፡ ኹለቱም ቅዱሳን ሲነጋገሩ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ‹‹…ምሰሶ ተሰበረ›› አሉ፡፡ አቡነ
መርቆሬዎስም ‹‹ምሰሶው ምንድነው?›› ብለው ሲጠቋቸው ‹‹የኢትዮጵያው ንጉሥ ዓምደ ጽዮን ሞተ›› አሏቸው፡፡ አቡነ ኤዎስጣቴዎስም እንደተናገሩት በዚያን ጊዜ ንጉሡ በኢትዮጵያ ምድር እንደ ሞተ ተረጋገጠ፡፡ ከዚኽም በኋላ አቡነ መርቆሬዎስ አባታቸው አቡነ ኤዎስጣቴዎስን አሟሙተው ማለትም ገንዘው ቀብረው ወደ ገዳማቸው ሲመለሱ ዳግመኛም ታናሽ ወንድማቸው አቡነ አብሳዲም ዐርፈው ስለደረሱ እጅግ አዘኑ፡፡

አቡነ መርቆሬዎስ ከአርማንያ ተመልሰው ሲመጡ ተኸላ የሚባል ቦታ ደዳም መሥርተው ዐሥር ዓመታት ኖረዋል፡፡ ቅዱስ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ወደ አርማንያ ሲሔዱ ‹‹እንደ እኔ ሁናቸው›› ብለው የእጅ መስቀላቸውን የሰጡት ለአቡነ አብሳዲ ነበር፡፡ ከአቡነ አብሳዲ ዕረፍት በኋላ የገዳሙን ኀላፊነት የተረከቡት አቡነ መርቆሬዎስ ሆኑ፡፡ በአቡነ መርቆሬዎስ ገዳም በደብረ ድማኅ አበ ምኔት ሆነው የተሾሙት አባቶች ሁሉ በዚህ መንበር ነው የሚሾሙት፡፡

አቡነ መርቆሬዎስ ተጋድሏቸውን ፈጽመው ዕድሜያቸውም እየገፉ ሔዶ 130 ዓመት ሲደርሱ ለልጆቻቸው መሪ ይሆኑ ዘንድ በእርሳቸው ምትክ አባ ገብር ኄርን ሾሙላቸው፡፡ የክብር ባለቤት ጌታችንም ተገልጦላቸው ታላቅ ቃልኪዳን ከገባላቸው በኋላ ተኅሣሥ 16 ቀን 1411 ዓ.ም በ130 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሥጋ ሞት ተለዩ፡፡
ደብረ ድማኅ አቡነ መርቆሬዎስ ገዳም ከጥንታዊ ገዳማት ውስጥ አንዱ ነው፡፡ ገዳሙዳሙ ታላቅ የምናኔ ቦታ ከመሆኑም ባሻገር በርካታ ሊቃውንት የሚወጡበት ነው፡፡ የትርጓሜ መጻሕፍት፣ የብሉይና ሐዲስ፣ የቅኔ፣ የምዕራፍ፣ የጾመ ድጓ እና የመዝገበ ቅዳሴ መምህራን ከዚህ ገዳም ታጥተው አያውቁም፡፡ በደቡብ ዞን ዓረዛ ቆላ ሠራየ በሚባል ቦታ የሚገኝ ሲሆን ከአስመራ 102 ኪ.ሜ ርቀት ላይ እንዲሁም ከባሕር ወለል በላይ 2075 ሜትር ከፍታ ላይ የሚገኝ ታላቅ ገዳም ነው፡፡ ገዳሙን አቡነ መርቆሬዎስ የመሠረቱት በ1340 ዓ.ም ነው፡፡

ገዳሙ በጣም በተለየ ሁኔታ የሚታወቅበት ነገር እምነቱ ነጭ መሆኑ ነው፡፡ ይኽም የሆነው በጻድቁ ልመናና ቃልኪዳን ነው፡፡ ይኸውም አቡነ መርቆሬዎስ፣ አቡነ አብዲሳና አቡነ ፊልጶስ ሦስቱ አንድ ላይ ሆነው ጉዳዕ በተባለ አከባቢ ደብረ ድማኅ ገዳም ሮራ ተራራ ላይ ሆነው የየራሳቸውን ምኞት ሲጸልዩ አቡነ ፊልጶስ ስለሚያርፉባት ገዳም ጸለዩ፤ አቡነ አብዲሳም ልጆቻቸው ይበዙ ዘንድ ሲጸልዩ አቡነ መርቆሬዎስ ደግሞ ‹‹…እኔ የምኖርባትን ገዳም ነጭ፣ የልጆቼንም ኅሊናቸው እንደ ነጭ ንጹሕ አድርግልኝ›› ብለው ጸለዩ፡፡ እግዚአብሔር አምላክም እንደየጸሎታቸው ለሦስቱም ቅዱሳን ሰጣቸው፡፡ በዚኽም መሠረት የአቡነ መርቆሬዎስ እምነታቸው ነጭ አፈር ሆነ፤ ይኽም እምነታቸው ለሁሉም ዓይነት
ሕማም በጣም ፈዋሽ ሲሆን በተለይም ለአጋንንት በሽታዎችና ለነቀርሳ የታወቀ መድኀኒት ነው፡፡ የገዳሙ አባቶች ይኽን አስደናቂና ፈዋሽ እምነት ከአንድ ቦታ ላይ ቆፍረው እያወጡ ለሚመጣው ሕዝብ ሁሉ ሲያድሉ ከ600 አመታት በላይ ቢሆናቸውም በጣም በሚያስገርም መልኩ እምነቱ ተቆፍሮ የሚወጣበት ቦታ አንድ ስንዝር ያህል እንኳን ወደታች አለመጎድጎዱ ነው፡፡ በተለይም በየዓመቱ በጻድቁ የዕረፍታቸው ዕለት ታኅሣሥ 16 ቀን በጣም ብዙ ሕዝብ ለክብረ በዓሉ ወደ ገዳሙ እየሔደ እምነቱን ከአባቶች በብዛት እየተቀበለ ቢመለስም ተቆፍሮ የሚወጣበት ቦታ ምንም ሳይጎድል ከዓመት እስከ ዓመት ያው ነው፡፡

እኛም በ2011 ዓ.ም በጉዞአችን ወቅት ወደዚህ ተኣምረኛ ገዳም በአዳር መርሐ ግብር ሔደን ለመሳለምና የአቡነ መርቆሬዎስን ነጭና ፈዋሽ እምነት ከገዳሙ አባቶች ለመቀበል እግዚአብሔር ፈቅዶልናል፡፡ በቤተ መቅደሱ ውስጥ የእነ አቡነ ተክለ ሃይማኖትንና የእነ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራን ሥዕላት ጨምሮ አስደናቂ የሆኑ በጣም ጥንታውያን ቅዱሳት ሥዕላት በብዛት ይገኛሉ፡፡ ከዚሁ ገዳም አጠገብ የአቡነ ኤዎስጣቴዎስ ቤተ ክርስቲያንም ይገኛል፡፡

የአቡነ መርቆሬዎስ ጸሎታቸው በረከታቸው ከሁላችን ከሕዝበ ክርስትያን ጋር ይሁን አሜን፡፡ በጸሎታቸው ኀይል የተዋሕዶ ሃይማኖት ጠላቶቻችንን ያጥፉልን፣ ሀገራችንን ሰላም ያድርጉልን!
✞ ✞ ✞

ታኅሣሥ 16 በዚኽች ቀን ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ በስሚዛ ሰንሰል እንጨት በአይጥ ሀረግ በነጠላ ማገር ቤተ ክርስቲያኗን በዕለተ ዓርብ ጠዋት ጀምራ ማታ በአንድ ቀን የጨረሰችበት ዕለት ነው። ይኽችም ቤተክርስቲያኗ በታኅሣሥ 16 በዕለተ እሑድ ቅዳሴ ቤቱ ሲከብር በቍርባን ጊዜ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከድንግል ማርያምና ከእልፍ አእላፋት መላእክት ጋር ወርዶ ቤተ መቅደሱን ሲባርክ መቅደሱ በ፬ቱ መዓዘን ለጌታችን እንደሰገደ ዛሬም ድረስ የሚታይ ነው።

እናታችን ፍቅርተ ክርስቶስ ወይም እመ ምዑዝ በጎንደር ክፍለ ሀገር በደራ ፎገራ አንበሳሜ በሚባለው ቦታ የአብርሃምና የሣራ ምግባር ካላቸው ከአባቷ ከላባ ከእናቷ ከወንጌላዊት ጌታችን በተወለደበት ዕለት ታኅሣሥ 29 ቀን በታዘዘ መልአክ አብሳሪነት ተወለደች፡፡ በተወለደችም ጊዜ በእግሯ ቆማ ‹‹በማኅየዊ ቸርነትህ ከጨለማ ወደ ብርሃን ላወጣኸኝ ለአብ
ምስጋና ለወልድ ምስጋና ለመንፈስ ቅዱስም ምስጋና ይገባል›› ብላ አምላኳን አመስግናለች፡፡ ቤተሰቦቿ ያገኙዋት በስዕለት ሲሆን ስመ ክርስትናዋም ማርያም ጸዳለ ተባለ፡፡ ፍቅርተ ክርስቶስ የሚለው የቆብ (የምንኩስና) ስሟ ነው፡፡ ዕድሜዋ ለትምህርት እንደደረሰ እግዚአብሔር የላከው አንድ ደገኛ መነኩሴ ወደ እርሷ በመሄድ የዳዊትን መዝሙር፣ የብሉያትና የሐዲሳት መጻሕፍትንና የቤተክርስቲያንን ትምህርት ሁሉ በሚገባ አስተምሯታል፡፡እናታችን ፍቅርተ ክርስቶስ በነበረችበት ዘመን ዐፄ ሱስንዮስ ‹‹ሁለት ባሕርይ››
የሚለውን የረከሰ የሮማውያንን ሃይማኖት የአገራችን ሕዝዝ ሁሉ እንዲያምን በማወጁ ምክንያት በሀገራችን ከፍተኛ የሆነ የሃይማኖት ግጭት ስለተነሣና ከ8ሺህ በላይ ክርስቲያኖች በግፍ ተጨፍጭፈው ሲያልቁ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ከእነ አቡነ ስምዖንና ከሌሎችም ቅዱሳንና ቅዱሳት ጋር ተሰልፋ
ሰማዕትነትን ተቀብላ ለሃይማኖቷ መስክር ሆናለች፡፡ ባለቤቷ ዘርዐ ክርስቶስም በሰማዕትነት ዐርፎ ሰባት አክሊላት ወርደውለታል፡፡ዐፄ ሱስንዮስ ለፖለቲካዊ ጥቅም ብሎ የረከሰች የሮማውያንን ሃይማኖት በአገራችን ላይ እንዳወጀ ሊቀ ጳጳሱ አቡነ ስምዖን ካህናትንና ክርስቲያን ልጆቻቸውን አነሳስተው እያስተማሩና እያጠነከሩ እያለ በጦር ተወግተው
በሰማዕትነት ዐረፉ፡፡ ሊቀ ጳጳሱ አቡነ ስምዖንም በሰማዕትነት ከማረፋቸው በፊት ግን እነ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስን፣ ቅድስት ወለተ ጴጥሮስን፣ ቅድስት አካለ ክርስቶስን፣ ቅድስት እመ ወተትንና ሌሎቹንም ቅዱሳንና ቅዱሳት አነሳስተው ባራ
ሄደው ንጉሡን መክረውታል፣ ገሥጸውታል፡፡ ንጉሡ ግን ከፍተኛ ፖሊቲካዊ ጥቅም እንደሚያገኝ ሮማውያን ቃል ገብተውለት ስለነበር ቅዱሳን አባቶችና ቅዱሳት እናቶች አብዝተው ቢመክሩትም ከክህደቱ ሊመለስ አልቻለም፡፡ ይልቁንም ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስን የሃይማኖቷን ጽናት ስላየ ሥጋዋ እየተቆረሰ መሬት ላይ እስኪወድቅ ድረስ በብረት በትር አጥብቆ ያስገርፋት ጀመር፡፡ በመጨረሻም ምድር እየሰወረቻት ለመግረፍ የማይመቻቸው ቢሆን ከሌሎቹ ሰማዕታት ጋር አንገቷን በሰይፍ አስቆርጦታል፡፡ በዚህም ጊዜ ፍጹም ጨለማ ሆኖ ምድርም ተነዋወጠች፡፡ ስምንት ሺህ አሥር ቅዱሳንም በሰማዕትነት ዐረፉ፡፡ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስን አንገቷን በሰይፍ ቢቆርጧትና በሞት ብታርፍም ነገር ግን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ገነትንና ሲኦልን አሳይቶ 14 ቀን በሰማያዊት ኢየሩሳሌም ከተቀመጠች በኋላ እንደገና እንደተኛ ወይም ከእንቅልፉ እንደሚነቃ ሰው ከሞት አስነሥቶ ወደ ቦታዋ መለሳት፡፡ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤልም ከሞት ካስነሣት በኋላ እናታችን ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ መናኒ ሆና በየገዳሙና በየአድባራቱ እየሔደች ዓለምን ስትዞር ያቀናቻቸው ብዙ ገዳማት አሉ፡፡ ለምሳሌ ከተሰዓቱ ቅዱሳን አንዱ በሆኑት በአባ ጉባ ተመሥርታ በግራኝ ወረራ ጠፍታ የነበረችውን ራማ ኪዳነምሕረት አንድነት ገዳምን አቅንታ የወንድና የሴት ገዳም ብላ ሥርዓት ሠርታለች፡፡ ወደ ኢየሩሳሌምም በመሄድ ላይ ሳለች በመንገድ ሰውን የሚበሉ ፍጡሮች ወደሚኖሩበት አካባቢ ስትደርስ 60 የሚሆኑ አገልጋዮቿን ለመብላት ይዘው ሳር ቅጠል እንዲበሉ በማድረግ ዐይናቸውን በጉጠት በማውጣት 4 ወራት በጨለማ ቤት ውስጥ ዘጉባቸው፡፡ ሰይጣንንም ያመልኩ ነበርና ከ4 ወራት በኋላም በዓል አድርገው ለመብላት ከእሳት ውስጥ ጨመሯቸው፣ ነገር ግን ጌታችን በቸርነቱ ጠብቋቸዋልና እነ ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስን ምንም አልሆኑም፡፡ ያንጊዜም ሰው በላዎቹ ‹‹እናንተ ሰዎች ምንድን ናችሁ?›› ብለው ጠየቋቸው፡፡ ቅድስት እናታችን ፍቅርተ ክርስቶስም ክርስቲያን መሆናቸውንና እነርሱ የሥላሴ ሕንፃ የሆነውን የሰውን ልጅ መብላት እንደሌለባቸው ብታስተምራቸው ‹‹ምን እንበላለን?›› አሏት፡፡ እርሷም ከራማ
ኪዳነ ምሕረት ስትነሳ የእህል ዘርን ለአገልጋዮቿ አሰይዛ ስለነበር ከዚያ ስንዴ ወስዳ ዘራችው፡፡ ስንዴውም በአንድ ቀን ብቻ ተዘርቶ በቅሎ፣ታጭዶ፣ ደርቆ፣ ተፈጭቶ ለምግብነት በቅቷል፡፡ ቅድስት እናታችንም ቀምሳ ስታቀምሳቸው እንደማር እንደወተት የሚጣፍጥ ሆኖላቸው በደስታ ተመግበውታል፡፡ ከዚያም እንደዚህ እያደረጉ እየሠሩ እንዲበሉ አስተምራ
አስጠምቃቸው ስድስት አብያተ ክርስቲያናትን አሠርታላቸዋለች፡፡ ወንጌልን፣ስንክሳርን፣ ሃይማኖተ አበውን፣ ግንዘትን፣ መዝሙረ ዳዊትን፣ አርጋኖንን ሁሉ በእጇ ጽፋ አስቀመጠችላቸው፡፡ እናታችን ፍቅርተ ክርስቶስ ምን ያህል የከበረች ‹‹ሐዋሪያዊት›› እንደሆነች ከዚህ ልብ ይሏል፡፡
የብርሃን እናቱ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ተገልጣላት በልጇ ምክንያት ስለደረሱባት ሀዘኖች አውርታላታለች፡፡የፈለገችውንም እንድታደርግበት በእጇ ያለውን መስቀል ለፍቅርተ ክርስቶስ
ሰጥታታለች፡፡ በዚህም መስቀል እናታችን ፍቅርተ ክርስቶስ ባሕር ከፍላ ደቀ መዛሙርቶቿን አሻግራለች፡፡ የአባታችን የቅዱስ ኤዎስጣቴዎስን ገድል በማንበብና በመልአኩ ቅዱስ ሚካኤል እርዳታ ባህሩን በአጽፏ ተሻግራ ወደ ሀገረ ናግራን ሄዳለች፡፡ እንዲሁም በበትረ መስቀሏም እንደ ዘርዐ ቡሩክ ከባሕር ውስጥ የሠጠሙ የደቀ መዛሙርቶቿን መጻሕፍት ምንም ሳይሆኑ ማውጣት ችላለች፡፡ እናታችን በሁሉም ሀገር እየዞረች ቅዱሳት መካናትን ትሳለም ነበር፡፡በደብረ ዳሞም ሄዳ ‹‹ሴቶች መውጣት አይችሉም›› ቢሏት በሀዘን ስታለቅስ
መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል በሥውር ወስዶ ከዓምባው ላይ አውጥቶ ከቤተ መቅደሱ አድርሷታል፣ አቡነ አረጋዊም ተገልጸውላት ባርከዋታል፡፡ በዚያም ሥጋ ወደሙን በእጃቸው ተቀብላለች፡፡ እናታችን ወደ ኢየሩሳሌምም ሄዳ ቅዱሳት
መካናትን እየተሳለመች ለ7 ዓመታት ቆይታለች፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም በዓምደ ብርሃን እየመራት ተመልሳ ወደ ሀገራችን መጥታ በድጋሚ ከሱስንዮስ ጋር ተሟግታለች፡፡ ሙታንንም እያስነሳች እንዲመሰክሩለት ብታደርግም እርሱ ግን ከጥፋቱና ከክህደቱ ሊመለስ አልቻለም፡፡ ነገር ግን እናታችን ፍቅርተ ክርስቶስ የተለያዩ ተአምራትን በማድረግ መልእክቷንም በንስር አሞራ አድርጋ እየላከች ትመክረው ነበር፡፡በአንድም ወቅት በሀገራችን የእህል መታጣት ሆነና ቅድስት እናታችን ዘወትር እንደምታደርገው የኪዳምሕረትን ዝክር ልታደርግ ብላ ዝክሩን የምታደርግበት እህል አጣች፡፡ ደናግል ልጆቿንም ጠርታ ትንሽ ዱቄት እንዲያመጡላት ነግራቸው አመጡላት፡፡ በዚያችም ትንሽ ዱቄት ላይ ጸሎት አድርጋ ከጨረሰች በኋላ ‹ወደ ቦታው መልሱት› አለቻቸው፡፡ በማግስቱም እንስራው ጋኑ ሁሉ በዱቄት ተሞልቶ
አግኝተውታል፡፡ ቅድስት እናታችንና ልጆቿም የየካቲት ኪዳነ ምሕረትን በዓል በታላቅ ደስታ አክብረዋል፡፡መልአኩም እናታችንን ከቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም መልሶ ወደ ኢትዮጵያ
ካመጣት በኋላ ዛሬ ገዳሟ ካለበት ቦታ ስትደርስ ከቦታዋ ላይ ዓምደ ብርሃን ተተክሎ በቀስተ ደማና ተከቦ አይታ ‹‹ይህች ቦታ ምንታምር›› ብላ ጠራቻት፡፡በመድኃኔዓለምም ትእዛዝ የቅድስት ኪዳነ ምሕረትን ቤተ ክርስቲያን በአንዲት ቀን ብቻ ሠርታለች፡፡ ቦታዋ ዛሬም ድረስ ‹ምንታምር› እየተባለች የምትጠራ ሲሆን ቅድስት እናታችን ፍቅርተ ክርስቶስ የሠራቻት በስሚዛ (በሰንሰል) እንጨት፣በአይጥ ሐረግ፣ በነጠላ ማገር አድርጋ የግድግዳ ቤተ መቅደስ በአንዲት ቀን
ብቻ ሠርታ በታኅሣሥ 16 ቀን በዕለተ እሁድ ቅዳሴ ቤቷን አክብራለች፡፡ በዚህም ጊዜ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤልና ቅዱስ መሲፋይል በክንፋቸው አፈር ከኢየሩሳሌም አምጥተው በቦታዋ ላይ ቀላቅለውበታል፡፡ ጌታችንም ከብርሃን እናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም ጋር ለፍቅርተ ክርስቶስ ተገልጦላት ቦታዋን ባርኮላት እስከዕለተ ምፅዓትም ድረስ እንደማትፈርስ ቃልኪዳን ገብቶላታል፡፡
ለምሳሌ በአንድ ወቅት ከባድ የእሳት ቃጠሎ ተነስቶ ጫካውን ሁሉ ሲያቃጥል ከቤተክርስያኗ ላይ ግን ለምልክት ያህል ጫፏ ላይ ያለችውን የሰጎን እንቁላል ብቻ አቃጥሎ ቤተ መቅደሷን አልፎ ሄዶ ጫካውን ሁሉ አቃጥሏል፡፡እናታችን ፍቅርተ ክርስቶስ በአንዲት ቀን ብቻ በተአምራት የሠራቻት ቤተ ክርስቲያኗ ተሠርታ ባለቀች ጊዜ ጌታችን ለእናታችን ተገልጦላታል፡፡ ጌታችንም በተገለጠላት ጊዜ ቤተ ክርስቲያኗ በአራቱም አቅጣጫ ለጌታችን ሰግዳለች፡፡ዛሬም ድረስ ቤተ ክርስቲያኗ በአራቱም አቅጣጫ ሆነው ሲመለከቷት በተቃራኒው አቅጣጫ እየሰገደች ትታያለች፡፡ በምሥራቅ አቅጣጫ ሆነው ቢያዩዋት ወደ ምዕራብ ሰግዳ ትታያለች፤ በምዕራብም ሆነው ቢያዩዋት ወደ ምሥራቅ ሰግዳ ትታያለች፡፡ በሰሜን አቅጣጫ ሆነው ቢያዩዋት ወደ ደቡብ ሰግዳ ትታያለች፤ በደቡብም ሆነው ቢያዩዋት ወደ ሰሜን ሰግዳ ትያለች፡፡እናታችን ፍቅርተ ክርስቶስ በተሰጣት ቃልኪዳን መሠረት በገዳሟም ውስጥ መርዘኛ እባብም ቢሆን ሰውን ወይም እንስሳትን ቢነድፍ መርዙ ምንም
አይጎዳም፡፡ እንዲሁም ጌታችን ገዳሟን ኢአማንያን
እንደማይረግጧት ቃልኪዳን ሰጥቷታል፡፡ ለምሳሌ የጣሊያን ጦር በሀገራችን የተለያዩ ገዳማትን እያጠፋ መነኮሳትን እየገደለ ከፍተኛ ጥፋት ባደረሰበት ወቅት ይህችንም ገዳም ለማጥፋትና መነኮሳቶቹንም ለመግደል መጥቶ ነበር፡፡
መነኮሳቶቹም ይህን ሰምተው ለሰማዕትነት ተዘጋጅተው ጠበቁ ነገር ግን የጦር አዛዡና ሠራዊቱ የገዳሟን ክልል አልፈው መግባት አልቻሉም፣ የገዳሟ ክልል ላይ ሲደርሱ በተአምራት እግራቸው ተሳስሮ መቆም መቀመጥ ሳይችሉ
ቀርተዋል፡፡ የጦር አዛዡም ‹‹ክርስቶስ ከዚች ገዳም አለ›› ብሎ ሃምሳ ጠገራ ብር ሰጥቶ ወደመጣበት ተመልሷል፡፡
መድኃኔዓለም ክርስቶስ በዚህች ገዳም ላይ ለቅድስት እናታችን ድንቅ ድንቅ ቃልኪዳን ከሰጣት በኋላ እናታችን ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ በየካቲት 29 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፋለች፡፡ በሥጋዋም ላይ ታላቅ የብርሃን አምድ ተተክሎ የታየ ሲሆን እንደፀሐይም ከጠዋት እስከ ማታ ያበራ ነበር፡፡ በመካነ መቃብሯም ላይ እስከ አርባ ቀን ድረስ ብርሃን ተተክሎ ታይቷል፡፡የእናታችን የቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ረድኤት በረከቷ ይደርብን በጸሎቷ ይማረን!
+ + +

መስፍነ እሥራኤል ቅዱስ ጌዴዎን፡- አባታችን አዳም በሰይጣን ተንኮልና ፈተና ወድቆ ከገነት ከወጣ በኋላ ብዙ መከራና ፍዳ አግኝቶታል፡፡ ለ100 ዓመት ያህል አልቅሶ ንስሓ ቢገባ ይቅር ባይ እግዚአብሔርም ንስሓውን ተቀብሎት ‹‹ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ›› የሚል የድኅነት ተስፋ ሰጠው፡፡
ስለዚህም አባታችን አዳም ለ5,500 ዓመታት ትንቢት ሲነገር ሱባኤ ወደ ታች ሲቆጠር ምሳሌም ሲመሰል ኖረ፡፡ ከደግ ፍጥረት አዳም እስከ ኖኅ ድረስ የሴም ልጆች እግዚአብሔርን በንጽሕና ሁነው በደብር ቅዱስ አመለኩ፡፡ ትንሽ ቆይተው ግን ከቃየን ልጆች ጋር ስለተቀላቀሉ በማየ ድምሳሴ አብረው ጠፉ፡፡ ነገር ግን ከሴም ዘር ቅንና ጻድቅ ሰው አብርሃም ተገኘ፡፡ ከእርሱም ቀጥሎ ደጋጎቹ ይስሐቅና ያዕቆብ ተገኙ፡፡ ያዕቆብም ‹‹እሥራኤል›› ተብሎ በልጆቹ ‹‹ሕዝበ እግዚአብሔር›› የተባለ ነገድ ተመሠረተ፡፡ በተስፋይቱ ምድር በከነዓን እንዳይኖሩም ረሀብ ምድረ ግብጽ አወረዳቸው፡፡ በዚያም ለ215 ዓመታት በጭንቅ የባርነትን ሕይወትን አሳለፉ፡፡ እግዚአብሔርም ስለወዳጁ ስለአብርሃም ሲል እሥራኤልን አስቧቸዋልና የዋሕ ጻድቅ ሰው ሙሴን አስነሥቶ እስራኤልን ከግብጽ ባርነት አዳናቸው፡፡
ይኸውም በጸናች እጅ በበረታችም ክንድ፣ በ9 መቅሰፍት፣ በ10ኛ ሞተ በኩር፣ በ11ኛ ስጥመት ግብጻውያንን አጥፍቶ ነው፡፡ ከዚህ ዘመን ጀምሮ እስራኤል በመሳፍንትና በካህናት የሚተዳደሩ ሆኑ፡፡ አስቀድሞ ሙሴ በምስፍና፣ አሮን በክህነት መሯቸው፡፡ ቀጥሎም በቅዱስ ሙሴ ኢያሱ፣ በአሮን አልዓዛር ተተኩ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያለም ከኃያል ሰው ጌዴዎን ደረሱ፡፡ ይኸውም ከዓለም ፍጥረት 4,151 ዓመታት በኋላ መሆኑ ነው፡፡ በጊዜው እስራኤል ጣዖትን እያመለኩ እግዚአብሕርን ስላሳዘኑት ለጠላቶቻቸው አሳልፎ ይሰጣቸው ነበር፡፡
የአካባቢው መንግስታት እነ አሞን፣ አማሌቅ፣ ኢሎፍሊ ከጥንት ጀምሮ እርስ በእርሳቸው ጠላቶች ናቸው፡፡ ከክርስቶስ ልደት 1,349 ዓመታት በፊት በእስራኤል ላይ ምድያማውያን በጠላትነት ተነስተውባቸው ተጨነቁ፡፡ አምላካችን እግዚአብሔርም ሊያድናቸው ወዶ መልአኩን ወደ ጌዴዎን ላከው፡፡ ቅዱሱ መልአክም ወደ እርሱ ቀርቦ ‹‹ኃያል የእግአብሔር ሰው ሆየ! ›› ሲል ጠራው፡፡ ጌዴዎን ግን ‹‹ባሮች ስንሆን ምን ኃይል አለን?›› ብሎ መለሰለት፡፡ መልአኩም ‹‹እግዚአብሔር ካንተ ጋር ነውና ሒድ፣ እስራኤልን ከምድያም እጅ አድናቸው›› አለው፡፡ ጌዴዎንም ምልልሱን በመቀጠል ‹‹እግዚአብሔር ከእኔ ጋር መሆኑን በምን አውቃለሁ?›› ሲል ጠየቀው፡፡ ጌዴዎን ይህንን ያለው ፈጣሪውን ተጠራጥሮት አይደለም ይልቁንም ጥበበ እግዚአብሔር ይገለጥ ዘንድና በኋለኛው ዘመን የሚፈጸመውን ምሥጢረ ሥጋዌ ሊያስረዳ እንጂ፡፡ መልአኩም መስፍኑ የሠዋውን መሥዋዕት አሳረገለት፡፡ ቀጥሎም ጌዴዎን ‹‹ጸምር (ብዝት ጨርቅ) ልዘርጋ፣ ጠል (ዝናብ) በጸምሩ ላይ ይውረድ፡፡ ዳር ዳሩ ግን ደረቅ ይሁን›› አለ፡፡ በጠዋትም እንዳለው ሆኖ አገኘው፡፡ በጸምሩ ላይ የወረደውን ጠል ጨምቆ በመንቀል ሞልቶ ቢጠጣው ሰማያዊ ኃይል ወረደለት፡፡ ጥያቄውን አሁንም ቀጠለና ‹‹ጌታ ሆይ! እንደገና ነገሩ ይቀየርና ጠል በጸምሩ ላይ አይውረድ፣ ዳር ዳሩ ግን ይውረድበት›› አለ፡፡ እንዳለውም ሆነለት፡፡ ይኽም ምሳሌ ነው፡፡ ለጊዜው ጸምር የእስራኤል፣ ጠል የረድኤት፣ ምድር የአህዛብ ምሳሌ ነው፡፡ ጠል በጸምር ላይ እንጂ በምድር ላይ እንዳልወረደ ረድኤተ እግዚአብሔር ለእሥራኤል እንጂ ለአሕዛብ ያለ መደረጉ ምሳሌ ነው፡፡ አንድም ምሳሌውን ይለውጧል፡፡ ጠል የሚለውን ብቻ እንቀይረውና ጠል የመቅሰፍት ምሳሌ፣ በ2ኛው ጠል በምድር ላይ እንጂ በጸምር ላይ እንዳልወረደ መቅሰፍቱም እሥራኤልን ትቶ በአሕዛብ ላይ ወርዷልና ነው፡፡ ይህ ግን ጊዜአዊ ምሥጢሩ ነው፡፡ አማናዊ ምሥጢሩ ግን ወደ ሐዲስ ኪዳን ያመጣናል፡፡ ጸምር የእመቤታችን፣ ጠል የጌታች ምሳሌ ናቸው፡፡ ጠል ጸምር እንጂ በምድር ላይ አለመውረዱ ጌታችን ከድንግል ማርያም ብቻ መወለዱን ያሳያል፡፡ በ2ኛው ምሳሌ ደግሞ ጠል የፍዳ፣ የመርገም ምሳሌ ይሆናል፡፡ ጠል በምድር ላይ እንጂ በጸምር ላይ አለመውረዱ ድንግል ማርያም ፍዳ መርገም የሌለባት ንጽሕት መሆኗን ያሳያል፡፡ ይኽ ሁሉ የተደረገለት ጌዴዎንም በወገኖቹ መካከል አዋጅ አስነግሮ 32ሺ ሠራዊትን ሰበሰበ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የእሥራኤላውያንን ክፋት ማለትም በራሳችን ኃይል አሸነፍን እንደሚሉ ያውቃልና ‹‹የፈራ ይመለስ በል›› አለው፡፡ በዚህም ጊዜ 22ሺ ሠራዊት ፈርቶ ተመለሰ፡፡ ምክንያቱም የምድያም ሠራዊት ከ100ሺ በላይ ነበርና ነው፡፡ አሁንም እግዚአብሔር ጌድዮንን ‹‹10ሺው ብዙ ነው፣ ወደ ወንዝ አውርደህ ለያቸው›› አለው፡፡ ጌዴዎንም ወደ ወንዝ አውርዶ ‹‹ውሃ ጠጡ›› አላቸው፡፡ ከ10ሺው 300ው በእጃቸው እየጠለፉ ሲጠጡ 9,700 ያህል ሠራዊት ግን ተጐንብሰው በአፋቸው ጠጡ፡፡ በዚህም ‹‹ሌሎቹን (የተጐነበሱትን) መልሳቸውና በ300ው ብቻ ተዋጋ›› ተባለ፡፡ ጌድዮንም 300ውን ተከታዮቹን ይዞ መለከትና መብራት በሸክላ ይዞ በምድያም ሠራዊት አካባቢ አደረ፡፡ በዚያች ሌሊትም ጌዴዎንና ሠራዊቱ በምድያም መካከል ገብተው እንስራቸውን ሰበሩ፡፡ መለከቱንም ነፉ፡፡ እንደ አንበሳም ‹‹ኃይልን ከእግዚአብሔር ጦርን ከጌዴዎን›› እያሉ ገጠሙ፡፡ በድንጋጤ የተመቱት ምድያማውያንም እርስ በርሳቸው ተዋግተው በአንድ ሌሊት ብቻ 102,000 ሠራዊት አለቀባቸው፡፡ መኳንንቶቻቸውንና ነገሥታቶቻቸውንም ገደሏቸው፡፡ ቀሪዎቹም ወገኖቻቸው አፈሩ፡፡ እሥራኤል ግን በፈጣሪያቸው ኃይል ተፈሩ፡፡ ጌዴዎንም ለ40 ዓመታት እሥራኤልን አስተዳድሮ ታኅሣሥ 16 ቀን ዐርፏል፡፡
+ + +
ማርያም እህተ ሙሴ:- ይህች እናት የሊቀ ነቢያት ቅዱስ ሙሴና የሊቀ ካህናቱ ቅዱስ አሮን ትልቅ እህት ስትሆን ወላጆቿ እንበረምና ዮካብድ ይባላሉ፡፡ እሥራኤል ከግብጽ ባርነት እንዲወጡ የእርሷን ያህል አስተዋጽኦ ያደረገች ሴት የለችም፡፡ ከመነሻውም ቅዱስ ሙሴን የጠበቀች፣ በሕግ በሥርዓት እንዲያድግ ከእናቱ ጋር ያገናኘች፣ ወገኖቿ ከግብጽ ሲወጡም ሴቶችን የመራች እናት ናት፡፡ ወንድሞቿን ሙሴንና አሮንንም ታገለገላቸው ነበር፡፡ በተለይ እግዚአብሔር ባሕረ ኤርትራን የብስ ሲያደርጋት ከበሮን አንሥታ ‹‹ንሴብሖ ለእግዚአብሔር›› ብላ ፈጣሪዋን አመስግናለች፡፡ ዘጸ 15፡20፡፡
ሙሴ ኢትዮዽያዊቷን በማግባቱ እኅቱ ማርያም ‹‹ኢትዮዽያዊቷን ሲፓራን ለምን አገባህ? ›› ብላ ስለተናገረችው እግዚአብሔር ተቆጥቶ ለምጽ መቷታል፡፡ ዘኁ 12፡1፡፡ ቆይቶም በቅዱሱ ምልጃ ምሯታል፡፡ ማርያም እስራኤል በመንገድ ላይ ሳሉ ወደ ርስት ሳይደርሱ ዐርፋ ተቀብራለች፡፡ ዘኁ 20፡1፡፡
" ጸበለ ጸዐዳ-ነጩ እምነት! "
ይኽ በደብረ ደብረ ድማኅ የሚገኘው የአቡነ መርቆሬዎስ ነጭ እምነት እጅግ ፈዋሽ ለመሆኑ እኔም ብዙ ተኣምር አይቼበታለሁ። ገዳሙ በጣም በተለየ ሁኔታ የሚታወቀው በዚሁ ነጭ እምነቱ ነው፡፡ ይኽም የሆነው በጻድቁ ልመናና ቃልኪዳን ነው፡፡ ይኸውም አቡነ መርቆሬዎስ፣ አቡነ አብዲሳና አቡነ ፊልጶስ ሦስቱ አንድ ላይ ሆነው ጉዳዕ በተባለ አከባቢ ደብረ ድማኅ ገዳም ሮራ ተራራ ላይ ሆነው የየራሳቸውን ምኞት ሲጸልዩ አቡነ ፊልጶስ ስለሚያርፉባት ገዳም ጸለዩ፤ አቡነ አብዲሳም ልጆቻቸው ይበዙ ዘንድ ሲጸልዩ አቡነ መርቆሬዎስ ደግሞ ‹‹…እኔ የምኖርባትን ገዳም ነጭ፣ የልጆቼንም ኅሊናቸው እንደ ነጭ ንጹሕ አድርግልኝ›› ብለው ጸለዩ፡፡ እግዚአብሔር አምላክም እንደየጸሎታቸው ለሦስቱም ቅዱሳን ሰጣቸው፡፡ በዚኽም መሠረት የአቡነ መርቆሬዎስ እምነታቸው ነጭ አፈር ሆነ፤ ይኽም እምነታቸው ለሁሉም ዓይነት ሕማም በጣም ፈዋሽ ሲሆን በተለይም ለአጋንንት በሽታዎችና ለነቀርሳ የታወቀ መድኀኒት ነው፡፡ የገዳሙ አባቶች ይኽን አስደናቂና ፈዋሽ እምነት ከአንድ ቦታ ላይ ቆፍረው እያወጡ ለሚመጣው ሕዝብ ሁሉ ሲያድሉ ከ600 አመታት በላይ ቢሆናቸውም በጣም በሚያስገርም መልኩ እምነቱ ተቆፍሮ የሚወጣበት ቦታ አንድ ስንዝር ያህል እንኳን ወደታች አለመጎድጎዱ ነው፡፡ በተለይም በየዓመቱ በጻድቁ የዕረፍታቸው ዕለት ታኅሣሥ 16 ቀን በጣም ብዙ ሕዝብ ለክብረ በዓሉ ወደ ገዳሙ እየሔደ እምነቱን ከአባቶች በብዛት እየተቀበለ ቢመለስም ተቆፍሮ የሚወጣበት ቦታ ምንም ሳይጎድል ከዓመት እስከ ዓመት ያው ነው፡፡

ጻድቁ ለአገልግሎት ወደ ሌላ ቦታ ሔደው ተመልሰው ሲመጡ ዉጡሕ በተባለ ቦታ ላይ በኣት አጽንተው ሱባኤ ያዙ፡፡ እርሳቸውም በዕለተ ዐርብ መጋቢት 12 ቀን የቅዱስ ሚካኤል በዓል ዕለት በኣታቸው ውስጥ እየጸለዩ ሳሉ ድንገት ቁመቱ 170 ክንድ ጎኑ ደግሞ 9 ክንድ ከስንዝር የሚሆን ሰይጣን ከነጭፍሮቹ በውስጡ ያደረበት ታላቅ ዘንዶ ይውጣቸው ዘንድ መጣ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ከእርሳቸው ጋር ስለነበር ጸሎታቸውን ሰምቶ ቅዱስ ሚካኤልን ላከላቸው፡፡ መልአኩም ድል የሚያደርጉበትን መስቀል ሰጣቸው፡፡ ጻድቁም ከመልአኩ በተቀበሉት ቅዱስ መስቀል በሥላሴ ስም ቢያማትቡበት ዘንዶው ተሰንጥቆ በውስጡ አድረውበት የነበሩት አጋንንትከዘንዶው ወጥተው ሮጠው ሊያመልጡ ሲሉ አባታችን አወገዟቸው፡፡ ዘንድውንም ወስደው ዱበና በሚባል በረሓ ውስጥ ጣሉት፡፡

ጻድቁም ዘንዶውን ስለገደሉላቸው ለአካባቢው ሰዎችም ሆነ ለፍጥረታት ሁሉ ሰላምና ዕረፍት ሆነላቸው፡፡ ይኽንንም መሠረት በማድረግ በየአመቱ መጋቢት 12 ቀን መነኰሳት
አባቶች ከገዳም ታቦት ይዘው ወደዚህ ቦታ በመሔድ ይቀድሳሉ፣ በዓሉንም ያከብራሉ፡፡ በወቅቱ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል የሰጣቸው ረጅም መስቀልም እስከ አሁን ድረስ የተለያየ ተኣምራት እያደረገ በገዳሙ ይገኛል፡፡

የአቡነ መርቆሬዎስ ጸሎታቸው በረከታቸው ከሁላችን ሕዝበ ክርስትያን ጋር ይሁን።
✞ ✞ ✞

(ለ3ኛ ጊዜ በተከፈተው አዲስ ቻናል በኩልም በጽሑፍና በድምፅ ይከታተሉ።)
https://www.tg-me.com/kegedilatandebet27217
እንኩዋን ለታላቁ ጻድቅ "ቅዱስ ሉቃስ ዘዓምድ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ቅዱስ ሉቃስ ዘዓምድ "*+

=>"ዘዓምድ" በሚል ስም ከሚታወቁ የቤተ ክርስቲያን አበው መካከል 4ቱ ቅድሚያውን ይይዛሉ:: እነዚህም:-
*ቅዱስ ስምዖን ዘዓምድ:
*ቅዱስ አጋቶን ዘዓምድ:
*ቅዱስ ዳንኤል ዘዓምድ: እና
*ቅዱስ ሉቃስ ዘዓምድ ናቸው::

+"ዘዓምድ" የሚለውን ቃል ምሥራቃውያን በልሳናቸው "THE STYLITE" ይሉታል:: የእኛው ቃል ደግሞ ከግዕዝ የተወረሰ ነውና በቁሙ ቢተረጐም "የምሰሶው" የሚል ትርጉምን ይይዛል:: ይህም በ2 ምክንያቶች ነው::

+አንደኛው ቅዱሳኑ ተጋድሏቸውን የፈጸሙት ከረዥም ምሰሶ ላይ ወጥተው በመጸለይ ስለሆነ ነው:: ሌላኛው ምክንያት ደግሞ እነዚህ አባቶች በዘመኑ ለነበሩ ምዕመናንና መነኮሳት አጽናኝ: አስተማሪ: መሪና ፈዋሽ በመሆናቸውና እንደ ምሰሶ ተተክለው ሳይነቃነቁ በመጸለያቸው ነው::

+ልክ ከዓለም ሃገራት ብዙ ስውራንን እና ቅዱሳን ነገሥታትን በመያዝ ሃገራችን ቀዳሚ እንደ ሆነችው ሁሉ ምሰሶ ላይ ወጥተው የሚጋደሉ ቅዱሳንም ሶርያውያንና ምሥራቃውያን ናቸው:: በዚህ ዕለትም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የታላቁን ቅዱስ ዘዓምድ ሉቃስን በዓል ታከብራለችና ከዜና ሕይወቱ ለበረከት ጥቂት እንካፈል::

+ቅዱስ ሉቃስ ተወልዶ ያደገው በፋርስ (በአሁኗ ኢራን) ሲሆን ዘመኑም ዘመነ ጻድቃን (ከ3ኛው እስከ 6ኛው ክ/ዘመን ድረስ) እንደ ሆነ ይታመናል:: ዛሬን አያድርገውና በጊዜው በጣም ብዙ: በዚያም ላይ ጽኑዕ የሆኑ ክርስቲያኖች በሃገሪቱ ነበሩ::

+በወቅቱ በየሥፍራው ዜና ቅዱሳን ሰፍቶ ነበርና ብዙዎቹ ወደ ምናኔ እየሔዱ ገዳማትን አጨናንቀው ነበር:: መንፈሳዊ ቅንዓት የሚያቃጥላቸው ክርስቲያኖችም ብዙ ነበሩ::

+ቅዱስ ሉቃስ ከልጅነቱ መሠረቱ ክርስትና ነው:: ልጅ ሳለም ሃይማኖቱን በሚገባ አውቁዋል:: ወጣት በሆነ ጊዜ ሠርቶ መብላት ሃይማኖታዊ ግዴታም ነውና ሥራ ፍለጋ ወጣ::

+በጊዜው ደግሞ በቀላሉ የሚገኝ ሥራ የሠራዊት አባል ወይም በዘመኑ ልሳን "ወታደር" መሆን ነበርና ሒዶ ገባ:: ውትድርና የኃጢአት ሥራ አይደለም:: ሃገርን: ዳርን: ድንበርን እየጠበቁ ራስን መስዋእት ማድረግ ነውና::

+ነገር ግን አንዳንዶቻችን የማይገባ ሥራ ስንሠራበት: ለእኛም ለወገንም የማይበጅ ድርጊት ስንፈጽም ይታያል:: ለዚህ ደግሞ እግዚአብሔር በምድርም ሆነ በሰማይ ይፈርዳልና ሁላችንም በተሠማራንበት ሙያ ሁሉ እንደሚገባ ልንኖር ግድ ይለናል:: የአባቶች ሕይወት እንዲህ ነበርና::

+ቅዱስ ሉቃስም ወታደር (ጭፍራ) ነው:: ግን ደግሞ ክርስቲያን ነው:: በ2ቱም ማንነቶቹ የሚጠበቁበትን እየተወጣ: የወጣትነት ስሜቱን በፈጣሪው ኃይል እየገታ: ራሱን ለእግዚአብሔር እያስገዛ ቀጠለ::

+እንደሚታወቀው ሰው በሥራው መጠን ክፍያው (ደሞዙ) እና ማዕረጉ (ሥልጣኑ) ከፍ እያለ መሔዱ አይቀርም:: ምንም እንኩዋ ብዙ እንዲህ ዓይነት ተግባራት በዘመናችን ቀዝቃዞች ቢሆኑም:: የሠራውን ትቶ ላልሠራው መሸለም በክርስትናው ዓለም ትልቅ ስህተት ነው::

+ምናልባትም ይሔው ገርሞት ይመስለኛል:-
"ሃገሬ ኢትዮዽያ ሞኝ ነሽ ተላላ::
የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ::" ሲል የሃገራችን ሕዝብ የተቀኘው::

+ቅዱስ ሉቃስም እንደ ሥራው መጠን ከፍ እያለ ሒዶ የፋርስ ሠራዊት ሃቤ ምዕት (የመቶ አለቃ) ለመሆን በቃ::

+ቅዱስ ሉቃስ የጦር መሪነት ስራውን እያከናወነ ጐን ለጐን ለፈጣሪው ይገዛ መጻሕፍትን ያነብ ነበር:: በተለይ ዜና ቅዱሳን ዕለት ዕለት ይስበው ነበርና ልቡናው ወደ ፍቅረ ክርስቶስ ተመሰጠ:: ይህችን ዓለም ትቷት ሊሔድም ተመኘ::

+በጐ ምኞትን የሚፈጽም ጌታም ልቡን አበርትቶለት ከዓለማዊ ንብረቱ አንድም ነገርን ሳያስከትል: ሹመቱንም ትቶ በርሃ ገባ:: በዚያም በረድዕ ሥርዓት የአባቶች ደቀ መዝሙር ሆነ:: አዛዥነትን ትቶ ታዛዥ: ተገልጋይነትን ትቶ አገልጋይ ሆነ::

+ትሕትናውንና ትጋቱን የተመለከቱ አበውም ወደ ምንኩስና ማዕረግ ከፍ አደረጉት:: አሁንም ታጥቆ አገልግሎቱን ቀጠለ:: እውቀቱን: ማስተዋሉንና ቅድስናውን ያዩ አባቶች በጐ እረኛ እንደሚሆን ስላወቁም ቅስናን ሾሙት::

+ከዚህ በሁዋላ ግን ቅዱስ ሉቃስ የተጋድሎውን ደረጃ ከፍ አደረገ:: በመጀመሪያ ጾሙን ከአንድ ቀን ወደ 3 ቀን አሸጋገረ:: ትንሽ ቆይቶ ግን ጾሙ 7 ቀን ሆነ:: ምን ጊዜም እህልን የሚቀምሰው በዕለተ ሰንበት (እሑድ) ብቻ ሆነ::

+ሁልጊዜም በዕለተ ሰንበት ቅዳሴን ይቀድሳል:: ለእርሱ ሥጋ ወደሙን ተቀብሎ ለሌሎቹ ያቀብላል:: ከዚያም ወደ በዓቱ ሒዶ አንዲት ዻኩሲማን ይመገባል:: "ዻኩሲማን" አባቶች በቀደመ ልሳን "የዳቦ ለከት" ይሉታል:: በዘመኑ ልሳን "ትንሽ የዳቦ ቁራጭ" እንደ ማለት ነው::

+ከዚህ ጐንም ወገቡን በሰንሰለት ታጥቆ በፍጹም መንፈሱ ይጸልይና ይሰግድ ነበር:: በዚህ ተጋድሎ ላይ ሳለም በታላቁ አባ አጋቶን ሕይወት መቅናትን ቀና:: በአንደበት ከሚወጣ ኃጢአት ይጠበቅ ዘንድም ሙልሙል ድንጋይ አዘጋጅቶ ጐረሰው::

+ያ ድንጋይ የሚወጣው በሳምንት አንዴ: ለሥጋ ወደሙና ለቁርባን ብቻ ነበር:: ማንም ምንም ቢያደርገውም ሆነ ቢናገረው ምንም አይመልስም:: ይህም ተጋድሎ "አርምሞና ትዕግስት" ይባላል::

+አርምሞ (ዝምታ) አንደበትን መቀደስ ሲሆን ትዕግስት ደግሞ ልብን ጸጥ አድርጐ መቀደስ ነው:: 2ቱ ጸጥ ካሉ ሰውነትም ከኃጢአት ማዕበል ጸጥ ይላልና:: የክብር ባለቤት መድኃኒታችን ክርስቶስም በመዋዕለ ስብከቱ ማርያምን "ኃርየት መክፈልተ ሠናየ - በጐ እድልን መረጠች" ያላት ስለዚህ ሃብቷ እንደ ሆነ መተርጉማን አትተዋል:: (ሉቃ. 10, ቅዳሴ ማርያም)

+ቅዱስ ሉቃስ በዚህ ሕይወቱ ለ3 ዓመታት ቆየ:: በሁዋላ አምላክ ቅዱስ መልአኩን ልኮ ወደ ቁስጥንጥንያ መራው:: የብርሃን መስቀል እየመራውም ወደ ምሥራቅ ተጉዋዘ::

+በዚያም እስከ ዛሬ ድረስ የሚታወቅበትን ተጋድሎ ጀመረ:: ከቁስጥንጥንያ ከተማ አቅራቢያ አንድ ምሰሶ አግኝቶ በላዩ ላይ ወጣ:: በዚያም ከእርሱ በፊት የነበሩ ቅዱሳን አባ ስምዖንና አባ አጋቶን ዘዓምድ እንዳደረጉት ያደርግ ጀመር::

+በምሰሶው ላይ መቀመጥ ስለ ማይቻል ትልቁና የመጀመሪያው ገድል ያለ ዕረፍት መቆም ነው:: በተረፈ ግን ለአካባቢው ምዕመናን መሪ: አስተማሪ ነበር:: ዝናውን እየሰሙ ሰዎች ከተለያየ አሕጉር ይመጡ ነበር::

+ያላመኑትን በስብከቱ ማሳመን: ያመኑትንም በምክሩ ማጽናትን ቀጠለ:: እርሱ አስተምሮት የማይለወጥ አልነበረም:: ምክንያቱም ምሉዓ መንፈስ ቅዱስ (መንፈስ ቅዱስ የመላበት) ነውና አጋንንት በሥፍራው አይቆሙምና::

+በጊዜውም ዻዻሳቱም: ካህናቱም: ሕዝቡም: መሣፍንቱም ይወዱት ነበር:: ቢያዝኑ አጽናኝ: ቢታመሙ ፈዋሽ: ከፈጣሪ ቢጣሉ አስታራቂ ነበርና:: እንዲህ ባለ ተጋድሎ ቅዱስ ሉቃስ ለ45 ዓመታት በምሰሶው ላይ ቆየ:: ስለዚህ እስከ ዛሬም ድረስ "ዘዓምድ" (THE STYLITE) እየተባለ ይጠራል::

+እግዚአብሔር ሊያሳርፈው በፈለገ ጊዜም ደቀ መዝሙሩን ጠርቶ ወደ ከተማ ላከው:: መልእክቱን የሰሙት የቁስጥንጥንያ ከተማ መሣፍንት: ዻዻሳት: ሕዝቡና ካህናቱ እየተሯሯጡ ቢመጡ ታኅሳስ 15 ቀን በፍቅር ዐርፎ አገኙ::

+እያዘኑ በታላቅ ለቅሶና ዝማሬ ወደ ቁስጥንጥንያ አደረሱት:: በዚያም በክብር በዚህች ቀን ከአበው መቃብር ቀበሩት::
<< ዛሬም ድረስ በአካባቢው ክቡር አባት ነው !! >>

=>አምላከ ቅዱስ ሉቃስ መካሪ: ዘካሪ አባቶችን አያሳጣን:: ከቅዱሱ በረከትም

ያሳትፈን::

=>ታሕሳስ 17 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ሉቃስ ዘዓምድ
2.ቅዱስ ናትናኤል ጻማዊ
3.ቅዱስ ማርቆስ

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ እስጢፋኖስ ሊቀ ዲያቆናት (ወቀዳሜ ሰማዕት)
2.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ወልደ ዘብዴዎስ)
3.ቅዱሳን አበው መክሲሞስና ዱማቴዎስ
4.አባ ገሪማ ዘመደራ
5.አባ ዸላሞን ፈላሢ
6.አባ ለትጹን የዋህ
7.ቅዱስ ኤዺፋንዮስ ሊቅ
8.ቅድስት ወለተ ዼጥሮስ

=>+"+ ጻድቅ እንደ ዘንባባ ያፈራል::
እንደ ሊባኖስ ዝግባም ያድጋል::
በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ተተክለዋል::
በአምላካችንም አደባባይ ውስጥ ይበቅላሉ::
ያን ጊዜ በለመለመ ሽምግልና ያፈራሉ::
ደስተኞችም ሆነው ይኖራሉ:: +"+ (መዝ. 91:12)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
††† እንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል: ቅዱስ ዮሐንስ ዘቡርልስ እና አቡነ ስነ ኢየሱስ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት †††

††† በቤተ ክርስቲያን ክቡር ከሆኑ ሊቃነ መላእክት አንዱ የሆነው ቅዱስ ገብርኤል ብዙ የክብር ስሞች አሉት:: በተለይ ግን:-
*ሊቀ አርባብ:
*መጋቤ ሐዲስ:
*መልአከ ሰላም:
*ብሥራታዊ:
*ዖፍ አርያማዊ:
*ፍሡሐ ገጽ:
*ቤዛዊ መልአክ:
*ዘአልቦ ሙስና . . . እየተባለ ይጠራል::

በብሉይ ኪዳንም ሆነ በሐዲስ ኪዳን ስሙ በብዛት ተጠቅሷል:: ስለ ረዳትነቱና አማላጅነቱም ቤተ ክርስቲያን በስሙ ታቦት ቀርጻ: መቅደስ አንጻ በሥርዓት ክብሩን ትገልጻለች::

ከእነዚህም አንዱ ሠለስቱ ደቂቅን እንዳዳነ የሚታሰብበት አንዱ በዓሉ ዛሬ ነው::
"ለዝንቱ ዜናዊ መልአከ ኃይል::
በዛቲ ዕለት ከመ ይትገበር በዓል::
መምሕራን አዘዙ ወሠርዑ በቃል::" እንዲል:: (አርኬ)

ንጉሡ ከምርኮ ወጣቶች ለቤተ መንግስት ሲመርጥ ሦስቱ ቅዱሳንና ዳንኤል ተመርጠው የምቾት ሕይወት ተዘጋጅቶላቸው ነበር:: ነገር ግን በምግብና በአምልኮ ከአሕዛብ ጋር መተባበርን አልፈለጉምና ምርጫቸው ጾምና ጸሎት ከቆሎ ጋር ሆነ::

ምንም እንኳ በቤተ መንግስት ውስጥ ቢኖሩ: ምንም የነገሥታት ልጆች ቢሆኑ ለእነርሱ ከእግዚአብሔር ፍቅር የተሻለ አልነበረምና በጥሬ ቆሎ ተወስነው ኖሩ::

አምላካቸው ከሃሊ ነውና በውበትም ሆነ በጥበብ በባቢሎን ምድር ከነርሱ የሚደርስ አልተገኘም:: ንጉሡም በባቢሎንና በአውራጃዋ ላይ ሾማቸው:: ስማቸውንም በአማልክቱ ስም ሲድራቅ: ሚሳቅና አብደናጐ አላቸው::

ከነገር ሁሉ በኋላ አሕዛብ ቀንተውባቸዋልና የክፋት አዋጅን አሳወጁ:: ናቡከደነጾር 60 ክንድ ቁመት ያለውን የወርቅ ምስል አቁሞ ስገዱ ቢላቸው አይሆንም በማለታቸው ተቃጥለው እንዲሞቱ እሳት ተፈረደባቸው:: ነበልባሉ ከጉድጓዱ ወደ ላይ 49 ክንድ ቢነድም ቅንጣት ያህል ፍርሃት አልጎበኛቸውም::

ወደ እሳቱም ሲጥሏቸው መልዐከ አድኅኖ ቅዱስ ገብርኤል ደርሶ አዳናቸው:: ከሆነው ነገር የተነሳ አሕዛብ አፈሩ:: ናቡከደነጾር ግን ከዙፋኑ ተነስቶ የቅዱሳኑን አምላክ እግዚአብሔርን ባረከ::

ቅዱሳኑን ያዳነ ቅዱስ መልአክ እኛንም ያድነን ዘንድ እንደ አባቶቻችን
"አድኅነኒ ዘአድኃንኮሙ በአክናፊከ ምንትው::
አመ ውስተ እሳት ተወድዩ ሠለስቱ እደው::" እያልን እንለምነው:: (መልክዐ ገብርኤል)

††† ቅዱስ ዮሐንስ ዘቡርልስ †††

††† ይህ ቅዱስ አባት ስም አጠራሩ የከበረ ነው:: ሊቅም: ጻድቅም: ጳጳስም: ገዳማዊም ነው:: ከሁሉም በላይ ግን ዛሬም ድረስ ቤተ ክርስቲያን በተድላ ለምትጠቀምባቸው መጻሕፍት (ስንክሳር: ግጻዌ እና ሃይማኖተ አበው) መሠረትን የጣለ ቅዱስ ሰው ነው::

ቅዱስ ዮሐንስ በትውልዱ ግብጻዊ ሲሆን ጊዜውም 5ኛው መቶ ክ/ዘ ነው:: ወላጆቹ ክርስቲያኖች: በዚያውም ላይ ሞልቶ የተረፋቸው ባለ ጠጐች ነበሩ:: እንደ ሕጉ ወጣት እስኪሆንና ራሱን እስኪችል ድረስ አሳደጉት::

ከዚያ ግን ድንገት አባቱና እናቱ ተከታትለው ዐረፉ:: ከቁጥር የበዛ ሃብትን የግሉ ያደረገው ቅዱስ ዮሐንስ ምን እንደሚያደርግበት ጨነቀው:: አንድ ትልቅ ነገር ግን ከማይሆን ጐዳና ጠበቀው::

ወላጆቹ ሁሌም መዝገብን በሰማያት ያገኙ ዘንድ ለነዳያን ይራሩ ነበርና ይህንኑ ለመቀጠል ወሰነ:: መልካም ፍሬ ከመልካም ዛፍ ነውና (ማቴ. 7:16) ወላጅ ለልጁ ማውረስ ያለበት ምድራዊ ሃብትን ሳይሆን በጐ ሕሊናን ነው:: ሳይሠሩ ያገኙት ሃብት ብዙዎችን አጥፍቷቸዋል::

ለዛም ይመስላል ዛሬ አንዳንዶቻችን በቤተሰቦቻችን ሃብት ከእኛ አልፈን ትውልዱን እየገደልንበት ያለው:: ለዚህ ደግሞ እግዚአብሔር ንስሃ ካልገባን ይመጣብናል:: መቅረዛችን (ሕይወታችንም) ከእኛ ላይ ይወስዳል::

ፍርድ የሚሆነው በክፉው ትውልድ ላይ ብቻ አይደለም:: ይህንን ትውልድ በፈጠርነውና መልካሙን መንገድ ባልመራነው በሁላችንም ላይ እንጂ:: (ራዕ. 2:5)

ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና ቅዱስ ዮሐንስ በወላጆቹ ሃብት የእንግዶች ማረፊያ የሚሆኑ ቤቶችን አንጾ ነዳያንን ይንከባከብ ገባ:: ሙሉውን ቀን ለነዳያን ሲራራ ይውላል:: አመሻሽ ላይ እንግዶችን ተቀብሎ: አብልቶ ያሳርፋል::

ከዚያም ፈጣሪውን ያመሰግናል:: በእንዲህ ያለ ሕይወት ዘመናትን ካሳለፈ በኋላ አንድ እንግዳ መነኮስ ወደ ቤቱ መጣ:: አስተናግዶት ሲጨዋወቱ አደሩ:: ሌሊት ላይ ግን ስለ ምንኩስና ሕይወትና ስለ ክብሩ ነግሮት ነበርና ልቡ ተመሰጠ::

መነኮሱን ከሸኘው በኋላም ይመንን ዘንድ ቆረጠ:: ነዳያንን ሰብስቦ ሃብቱን አካፈላቸው:: ከዚያም ወደ ገዳመ አስቄጥስ ሒዶ የታላቁ አባ ዳንኤል ደቀ መዝሙር ሆነ:: በትሕትና ለአባቶች እየታዘዘ ከቆየ በኋላ በጭንቅ ደዌ ተያዘ:: ሰይጣን በቅንዓት ገርፎት ነበርና::

እርሱ ግን በደዌው ምክንያት ለዓመታት መሬት ላይ ወድቆ ቢቆይም ፈጣሪውን ፈጽሞ ያመሰግን ነበር:: እግዚአብሔር ደግሞ በፈውስና በኃይል አስነሳው::

በጊዜው የቡርልስ ጳጳስ ዐርፎ ነበርና አባት ፍለጋ ወደ አስቄጥስ ገዳም መጥተው ነበር:: መንፈስ ቅዱስ መርጦታልና አበው ቅዱስ ዮሐንስ ጳጳስ ይሆን ዘንድ አስገደዱት:: እርሱም የፈጣሪ ፈቃድ መሆኑን ስላወቀ ሔደ::

በዚያም (በሃገረ ቡርልስ) ታላቁን ገድል ተጋደለ:: ወደ ከተማዋ ሲገባ ብዙ ነገሮች ከሚገባው ሥርዓት የወጡ ነበሩ:: ብዙ ሰው የእግዚአብሔርን ድምጽ ከመስማት ይልቅ ባላስፈላጊ ነገሮች ላይ ተጠምዶ ነበርና መንጋውን ያድን ዘንድ ተጋ::

ሳይሆኑ "ባሕታዊ": "አጥማቂ" ነን እያሉ ሕዝቡን የሚያሳስቱ ተኩላዎችንም አስወገደ:: ለሕዝቡ አጉል ሕልም: ሟርትን የሚያስተምሩትን ገሠጸ:: አንመለስም ያሉ መናፍቃንን እሳት ከሰማይ ወርዳ በላቻቸው::

ቅዱስ ዮሐንስ ከቅድስናው ብዛት ዘወትር ሲቀድስ መድኃኒታችንንና አእላፍ መላእክትን ያይ ነበር:: ከከዊነ እሳት ማዕረግ በመድረሱም አካሉ በመፈተት ሰዓት እንደ እሳት ይነድ ነበር:: እንባውም እንደ ውኃ ይፈስ ነበር::

ቅዱስ ዮሐንስ ከዚህ ጐን ዛሬም ድረስ የሚታወቅበትን ታላቅ ሥራም ሠርቷል:: መንፈስ ቅዱስ አነሳስቷቸው ቅዱሱና የሃገረ አትሪብ ጳጳስ የነበረው ሊቁ አባ ሚካኤል መጽሐፈ ስንክሳርን : መጽሐፈ ግጻዌንና ሃይማኖተ አበውን ለመጀመሪያ ጊዜ አዘጋጅተዋል::

"ስንክሳር" የቅዱሳንና የፈጣሪን ነገር በየዕለቱ የሚዘግብ መጽሐፍ ሲሆን "ግጻዌ" የየዕለቱን በዓላት ከምስባክና ምንባባት ጋር አስማምቶ የያዘ መጽሐፍ ነው:: "ሃይማኖተ አበው" ደግሞ የዶግማ መጽሐፍ ሆኖ ከሐዋርያት እስከ ሊቃውንት ድረስ የጻፉትን የያዘ ነው:: ሦስቱን የሚያመሳስላቸው "ስብስብ / እስትጉቡዕ / Collection" መሆናቸው ነው::

ቅዱሱ ዮሐንስ በሃገረ ቡርልስ በከፍተኛ ድካም ይህንን ፈጽሞ በዚህች ቀን ዐርፏል::

††† አቡነ ስነ ኢየሱስ ጻድቅ †††

††† ጻድቁ በመካከለኛው (የብርሃን) ዘመን የነበሩ ኢትዮጵያዊ::
*ከምድረ ሽዋ ወደ ታች አርማጭሆ የሔዱ መናኝ:
*ጭው ባለ በርሃ ለቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ ገዳምን ያነጹ አባት:
*ብዙ አርድእትን ያፈሩ መናኝ:
*ብዙ ተአምራትን የሠሩና ወንጌልን ያስተማሩ መነኮስ ናቸው::
2024/10/01 17:31:25
Back to Top
HTML Embed Code: