Telegram Web Link
አግዚአብሔር ዝም ሲል አቅቶት አይደለም፡፡ እርሱ ዝም ሲል የእኛ ነገር ሰልችቶት አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ዝም ሲል ረስቶንም አይደለም፡፡ ሰው ይረሳል እርሱ ግን በነገሩ ሁሉ ታማኝ ነውና አይረሳም፡፡

በዝምታ ውስጥ መሰራት አለ። በዝምታው ውስጥም መልስም አለ፡፡
Daniel:
እንኩዋን ለኃያል "መሥፍነ እሥራኤል ቅዱስ ጌዴዎን" እና "ማርያም እህተ ሙሴ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ኃያል ጌዴዎን "*+

=>እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን: 22ቱን ሥነ ፍጥረትን ፈጥሮ አዳምን ገዢ አደረገው:: አክሎም በነፍስ ሕያው አድርጐ: በመንፈስ ቅዱስ አክብሮ: ነቢይና ካህን አድርጐ: ካንዲት ዕፀ በለስ በቀር በፍጥረት ሁሉ ላይ አሰለጠነው::

+አባታችን አዳም ግን ስሕተት አግኝቶት ከገነት ወጣ:: መከራና ፍዳም አገኘው:: በሁዋላም ለ100 ዓመት አልቅሶ ንስሃ ገባ:: ጌታም ንስሃውን ተቀብሎ "ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ" የሚል ተስፋ ድህነትን ሰጠው::

+ስለዚህም ምክንያት ለ5,500 ዓመታት ትንቢት ሲነገር: ሱባኤ ወደ ታች ሲቆጠር: ምሳሌም ሲመሰል ኖረ:: ከደግ ፍጥረት አዳም እስከ ኖኅ ድረስ: የሴት ልጆች እግዚአብሔርን በንጽሕና ሁነው በደብር ቅዱስ አመለኩ::

+ትንሽ ቆይተው ግን ስለተቀላቀሉ ከቃየን ልጆች ጋር በማየ ድምሳሴ ጠፉ:: በጻድቅ ሰው ኖኅ የተጀመረው ትውልድም እግዚአብሔርን ለመዘንጋት ጊዜ አልፈጀበትም:: ነገር ግን ከሴም ዘር ቅንና ጻድቅ ሰው አብርሃም ተገኘ::

+ከእርሱም ይስሐቅ: ከዚያም ያዕቆብ (ደጋጉ) ተገኙ:: ያዕቆብም "እሥራኤል" ተብሎ: በልጆቹ "ሕዝበ እግዚአብሔር" የተባለ ነገድ ተመሠረተ:: በተስፋይቱ ምድር በከነዓን እንዳይኖሩም ረሃብ ምድረ ግብጽ አወረዳቸው::

+በዚያም ለ215 ዓመታት በጭንቅ የባርነትን ሕይወትን አሳለፉ:: እግዚአብሔርም ስለ ወዳጁ አብርሃም ሲል እሥራኤልን አሰባቸው:: የዋሕና ጻድቅ ሰው ሙሴን አስነስቶ እሥራኤልን ከግብጽ ባርነት አዳናቸው::

+ይኸውም በጸናች እጅ: በበረታችም ክንድ: በ9 መቅሰፍት: በ10ኛ ሞተ በኩር: በ11ኛ ስጥመት ግብጻውያንን አጥፍቶ ነው:: በየመንገዱም ጠላቶቻቸውን እየተበቀለላቸው ነው:: ከዚህ ዘመን ጀምሮም እሥራኤል በመሳፍንትና በካህናት የሚተዳደሩ ሆኑ::

+አስቀድሞ ሙሴ በምስፍና: አሮን በክህነት መሯቸው:: ቀጥሎም በቅዱስ ሙሴ ኢያሱ: በአሮን አልዓዛር ተተኩ:: እንዲህ እንዲህ እያለም ከኃያል ሰው ጌዴዎን ደረሱ:: ይኸውም ከዓለም ፍጥረት 4,151 ዓመታት በሁዋላ መሆኑ ነው::

+በጊዜው እሥራኤል ጣዖትን እያመለኩ እግዚአብሕርን ስላሳዘኑት ለጠላቶቻቸው አሳልፎ ይሰጣቸው ነበር:: የአካባቢው መንግስታት እነ አሞን: አማሌቅ: ኢሎፍሊ ስንኩዋ ያኔ ዛሬም ቢሆን እንደምትመለከቱት ዶሮና ጥሬ ናቸው::

+ከክርስቶስ ልደት 1,349 ዓመታት በፊትም በእሥራኤል ላይ ምድያማውያን (ይህቺ ሃገር የኢትዮዽያ ግዛት ነበረች ይባላል) በጠላትነት ተነስተውባቸው ተጨነቁ::

+አምላካችን እግዚአብሔርም ሊያድናቸው ወዶ መልአኩን ወደ ጌዴዎን ላከው:: ቅዱስ መልአክም ወደ እርሱ ቀርቦ "ኃያል የእግአብሔር ሰው" ሲል ጠራው:: ጌዴዎን ግን "ባሮች ስንሆን ምን ኃይል አለን!" ሲል መለሰለት::

+መልአኩም "እግዚአብሔር ካንተ ጋር ነውና ሒድ! እሥራኤልን ከምድያም እጅ አድናቸው" አለው:: ጌዴዎን ምልልሱን ቀጠለ:: "እግዚአብሔር ከእኔ ጋር መሆኑን በምን አውቃለሁ?" ሲል ጠየቀው::

+ጌዴዎን ይህንን ያለው ፈጣሪውን ተጠራጥሮት አይደለም:: ይልቁኑ ጥበበ እግዚአብሔር ይገለጥ ዘንድና በሁዋለኛው ዘመን የሚፈጸመውን ምሥጢረ ሥጋዌ ሊያስረዳ እንጂ::

+መልአኩም መስፍኑ የሰዋውን መስዋዕት አሳረገለት:: ቀጥሎም ጌዴዎን "ጸምር (ብዝት ጨርቅ) ልዘርጋ:: ጠል (ዝናብ) በጸምሩ ላይ ይውረድ:: ዳር ዳሩ ግን ይቡስ (ደረቅ) ይሁን" አለ:: በጠዋትም እንዳለው ሆኖ አገኘው::

+በጸምሩ ላይ የወረደውን ጠል ጨምቆ በመንቀል ሞልቶ ቢጠጣው ሰማያዊ ኃይል ወረደለት:: ጥያቄውን አሁንም ቀጠለ:: "ጌታ ሆይ! እንደ ገናም ነገሩ ይቀየርልኝ:: ጠል በጸምሩ ላይ አይውረድ:: ዳር ዳሩ ግን ይውረድበት" አለ::

+እንዳለውም ሆነ:: ይህ ሁሉ ምሳሌ ነው:: ለጊዜው ጸምር የእሥራኤል: ጠል የረድኤት: ምድር የአህዛብ ምሳሌ ነው:: ጠል በጸምር እንጂ በምድር ላይ እንዳልወረደ ረድኤተ እግዚአብሔር ለእሥራኤል እንጂ ለአሕዛብ ያለ መደረጉ ምሳሌ ነው::

+አንድም ምሳሌውን ይለውጧል:: ጠል የሚለውን ብቻ እንቀይረውና ጠል የመቅሰፍት ምሳሌ: በ2ኛው ጠል በምድር ላይ እንጂ በጸምር ላይ እንዳልወረደ: መቅሰፍቱም እሥራኤልን ትቶ በአሕዛብ ላይ ወርዷልና:: ( ይህ ጊዜአዊ ምሥጢሩ ነው:: )

+አማናዊ ምሥጢሩ ግን ወደ ሐዲስ ኪዳን ያመጣናል:: ጸምር የእመቤታችን: ጠል የጌታ ምሳሌ:: ጠል በጸምር እንጂ በምድር ላይ አለመውረዱ ጌታ ከድንግል ማርያም ብቻ መወለዱን ያሳያል::

+በ2ኛው ምሳሌ ደግሞ ጠል የፍዳ: የመርገም ምሳሌ ይሆናል:: ጠል በምድር ላይ እንጂ በጸምር ላይ አለመውረዱ ድንግል ማርያም ፍዳ መርገም የሌለባት ንጽሕት መሆኗን ያሳያል::

+ይህ ሁሉ የተደረገለት ጌዴዎንም በወገኖቹ መካከል አዋጅ አስነግሮ 32ሺ ሠራዊትን ሰበሰበ:: ግን እግዚአብሔር የእሥራኤላውያንን ክፋት (ማለትም በራሳችን ኃይል አሸነፍን) እንደሚሉ ያውቃልና "የፈራ ይመለስ በል" አለው::

+22ሺ ሠራዊት ፈርቶ ተመለሰ:: ምክንያቱም የምድያም ሠራዊት ከ100ሺ በላይ ነበርና:: አሁንም "10ሺው ብዙ ነው:: ወደ ወንዝ አውርደህ ለያቸው" አለው:: ጌዴዎንም ወደ ወንዝ አውርዶ "ውሃ ጠጡ" አላቸው::

+ከ10ሺው 300ው በእጃቸው እየጠለፉ ሲጠጡ 9,700 ያህል ሰራዊት ግን ተጐንብሰው በአፋቸው ጠጡ:: በዚህም "ሌሎቹን (የተጐነበሱትን) አስመልሰህ በ300ው ተዋጋ" ተባለ::

+እርሱም 300ውን ተከታዮቹን ይዞ: መለከትና መብራት በሸክላ ይዞ በምድያም ሠራዊት አካባቢ አደረ:: በዚያች ሌሊትም ጌዴዎንና ሠራዊቱ በምድያም መካከል ገብተው እንስራቸውን ሰበሩ::

+መለከቱንም ነፉ:: እንደ አንበሳም "ኃይል ዘእግዚአብሔር: ኩዊናት ዘጌዴዎን - ኃይልን ከእግዚአብሔር: ጦርን ከጌዴዎን" እያሉ ገጠሙ::

+በድንጋጤ የተመቱት ምድያማውያንም እርስ በርሳቸው ተዋግተው በአንድ ሌሊት ብቻ 102,000 ሠራዊት አለቀባቸው:: ቀሪዎቹም ወገኖቻቸው አፈሩ:: እሥራኤል ግን በፈጣሪያቸው ኃይል ተፈሩ:: ጌዴዎንም ለ40 ዓመታት እሥራኤልን አስተዳድሮ በዚህች ቀን ዐርፏል:: (መሣ. 6:1---8:35)

+"+ ማርያም እህተ ሙሴ +"+

=>ይህች እናት የሊቀ ነቢያት ቅዱስ ሙሴና የሊቀ ካህናቱ ቅዱስ አሮን ትልቅ እህት ስትሆን ወላጆቿ እንበረምና ዮካብድ ይባላሉ:: እሥራኤል ከግብጽ ባርነት እንዲወጡ የእርሷን ያህል አስተዋጽኦ ያደረገች ሴት የለችም::

+ከመነሻውም ቅዱስ ሙሴን የጠበቀች: በሕግ በሥርዓት እንዲያድግ ከእናቱ ጋር ያገናኘች: ወገኖቿ ከግብጽ ሲወጡም ሴቶችን የመራች እናት ናት:: ወንድሞቿን ሙሴንና አሮንንም ታገለገላቸው ነበር:: በተለይ እግዚአብሔር ባሕረ ኤርትራን የብስ ሲያደርጋት ከበሮን አንስታ "ንሴብሖ ለእግዚአብሔር" ብላ ፈጣሪዋን አመስግናለች:: (ዘጸ. 15:20)

+አንድ ጊዜም "ኢትዮዽያዊቷን ሲፓራን ለምን አገባህ" በሚል ስለ ተናገረችው እግዚአብሔር ተቆጥቶ በለምጽ መቷታል:: (ዘኁ. 12:1) ቆይቶም በቅዱሱ ምልጃ ምሯታል:: ማርያም በመንገድ ሳሉ: ወደ ርስት ሳይደርሱ ዐርፋ ተቀብራለች:: (ዘኁ. 20:1)

=>አምላከ ኃያላን መንፈሳዊ ኃይልን ልኮ ጠላትን ያድክምልን:: ከወዳጆቹ በረከትም ይክፈለን::

=>ታሕሳስ 16 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ጌዴዎን ኃያል
2.ማርያም እህተ ሙሴ
=>ወርኀዊ በዓላት
1.ኪዳነ ምሕረት (የሰባቱ ኪዳናት ማሕተም)
2.ቅድስት ኤልሳቤጥ (የመጥምቁ ዮሐንስ እናት)
3.ቅዱስ ገብረ ማርያም ጻድቅ ንጉሠ ኢትዮዽያ
4.ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌሉ ዘወርቅ
5.ቅዱስ አኖሬዎስ ጻድቅ
6.አባ ዳንኤል ገዳማዊ
7.አባ አቡናፍር ገዳማዊ

=>+"+ እንግዲህ ምን እላለሁ? ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ: ስለ ሶምሶንም: ስለ ዮፍታሔም: ስለ ዳዊትና ስለ ሳሙኤልም: ስለ ነቢያትም እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛልና:: እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ:: ጽድቅንም አደረጉ . . . +"+ (ዕብ. 11:32)

   <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
Daniel:
  እንኩዋን ለታላቁ ጻድቅ "ቅዱስ ሉቃስ ዘዓምድ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ቅዱስ ሉቃስ ዘዓምድ "*+

=>"ዘዓምድ" በሚል ስም ከሚታወቁ የቤተ ክርስቲያን አበው መካከል 4ቱ ቅድሚያውን ይይዛሉ:: እነዚህም:-
*ቅዱስ ስምዖን ዘዓምድ:
*ቅዱስ አጋቶን ዘዓምድ:
*ቅዱስ ዳንኤል ዘዓምድ: እና
*ቅዱስ ሉቃስ ዘዓምድ ናቸው::

+"ዘዓምድ" የሚለውን ቃል ምሥራቃውያን በልሳናቸው "THE STYLITE" ይሉታል:: የእኛው ቃል ደግሞ ከግዕዝ የተወረሰ ነውና በቁሙ ቢተረጐም "የምሰሶው" የሚል ትርጉምን ይይዛል:: ይህም በ2 ምክንያቶች ነው::

+አንደኛው ቅዱሳኑ ተጋድሏቸውን የፈጸሙት ከረዥም ምሰሶ ላይ ወጥተው በመጸለይ ስለሆነ ነው:: ሌላኛው ምክንያት ደግሞ እነዚህ አባቶች በዘመኑ ለነበሩ ምዕመናንና መነኮሳት አጽናኝ: አስተማሪ: መሪና ፈዋሽ በመሆናቸውና እንደ ምሰሶ ተተክለው ሳይነቃነቁ በመጸለያቸው ነው::

+ልክ ከዓለም ሃገራት ብዙ ስውራንን እና ቅዱሳን ነገሥታትን በመያዝ ሃገራችን ቀዳሚ እንደ ሆነችው ሁሉ ምሰሶ ላይ ወጥተው የሚጋደሉ ቅዱሳንም ሶርያውያንና ምሥራቃውያን ናቸው:: በዚህ ዕለትም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የታላቁን ቅዱስ ዘዓምድ ሉቃስን በዓል ታከብራለችና ከዜና ሕይወቱ ለበረከት ጥቂት እንካፈል::

+ቅዱስ ሉቃስ ተወልዶ ያደገው በፋርስ (በአሁኗ ኢራን) ሲሆን ዘመኑም ዘመነ ጻድቃን (ከ3ኛው እስከ 6ኛው ክ/ዘመን ድረስ) እንደ ሆነ ይታመናል:: ዛሬን አያድርገውና በጊዜው በጣም ብዙ: በዚያም ላይ ጽኑዕ የሆኑ ክርስቲያኖች በሃገሪቱ ነበሩ::

+በወቅቱ በየሥፍራው ዜና ቅዱሳን ሰፍቶ ነበርና ብዙዎቹ ወደ ምናኔ እየሔዱ ገዳማትን አጨናንቀው ነበር:: መንፈሳዊ ቅንዓት የሚያቃጥላቸው ክርስቲያኖችም ብዙ ነበሩ::

+ቅዱስ ሉቃስ ከልጅነቱ መሠረቱ ክርስትና ነው:: ልጅ ሳለም ሃይማኖቱን በሚገባ አውቁዋል:: ወጣት በሆነ ጊዜ ሠርቶ መብላት ሃይማኖታዊ ግዴታም ነውና ሥራ ፍለጋ ወጣ::

+በጊዜው ደግሞ በቀላሉ የሚገኝ ሥራ የሠራዊት አባል ወይም በዘመኑ ልሳን "ወታደር" መሆን ነበርና ሒዶ ገባ:: ውትድርና የኃጢአት ሥራ አይደለም:: ሃገርን: ዳርን: ድንበርን እየጠበቁ ራስን መስዋእት ማድረግ ነውና::

+ነገር ግን አንዳንዶቻችን የማይገባ ሥራ ስንሠራበት: ለእኛም ለወገንም የማይበጅ ድርጊት ስንፈጽም ይታያል:: ለዚህ ደግሞ እግዚአብሔር በምድርም ሆነ በሰማይ ይፈርዳልና ሁላችንም በተሠማራንበት ሙያ ሁሉ እንደሚገባ ልንኖር ግድ ይለናል:: የአባቶች ሕይወት እንዲህ ነበርና::

+ቅዱስ ሉቃስም ወታደር (ጭፍራ) ነው:: ግን ደግሞ ክርስቲያን ነው:: በ2ቱም ማንነቶቹ የሚጠበቁበትን እየተወጣ: የወጣትነት ስሜቱን በፈጣሪው ኃይል እየገታ: ራሱን ለእግዚአብሔር እያስገዛ ቀጠለ::

+እንደሚታወቀው ሰው በሥራው መጠን ክፍያው (ደሞዙ) እና ማዕረጉ (ሥልጣኑ) ከፍ እያለ መሔዱ አይቀርም:: ምንም እንኩዋ ብዙ እንዲህ ዓይነት ተግባራት በዘመናችን ቀዝቃዞች ቢሆኑም:: የሠራውን ትቶ ላልሠራው መሸለም በክርስትናው ዓለም ትልቅ ስህተት ነው::

+ምናልባትም ይሔው ገርሞት ይመስለኛል:-
"ሃገሬ ኢትዮዽያ ሞኝ ነሽ ተላላ::
የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ::" ሲል የሃገራችን ሕዝብ የተቀኘው::

+ቅዱስ ሉቃስም እንደ ሥራው መጠን ከፍ እያለ ሒዶ የፋርስ ሠራዊት ሃቤ ምዕት (የመቶ አለቃ) ለመሆን በቃ::

+ቅዱስ ሉቃስ የጦር መሪነት ስራውን እያከናወነ ጐን ለጐን ለፈጣሪው ይገዛ መጻሕፍትን ያነብ ነበር:: በተለይ ዜና ቅዱሳን ዕለት ዕለት ይስበው ነበርና ልቡናው ወደ ፍቅረ ክርስቶስ ተመሰጠ:: ይህችን ዓለም ትቷት ሊሔድም ተመኘ::

+በጐ ምኞትን የሚፈጽም ጌታም ልቡን አበርትቶለት ከዓለማዊ ንብረቱ አንድም ነገርን ሳያስከትል: ሹመቱንም ትቶ በርሃ ገባ:: በዚያም በረድዕ ሥርዓት የአባቶች ደቀ መዝሙር ሆነ:: አዛዥነትን ትቶ ታዛዥ: ተገልጋይነትን ትቶ አገልጋይ ሆነ::

+ትሕትናውንና ትጋቱን የተመለከቱ አበውም ወደ ምንኩስና ማዕረግ ከፍ አደረጉት:: አሁንም ታጥቆ አገልግሎቱን ቀጠለ:: እውቀቱን: ማስተዋሉንና ቅድስናውን ያዩ አባቶች በጐ እረኛ እንደሚሆን ስላወቁም ቅስናን ሾሙት::

+ከዚህ በሁዋላ ግን ቅዱስ ሉቃስ የተጋድሎውን ደረጃ ከፍ አደረገ:: በመጀመሪያ ጾሙን ከአንድ ቀን ወደ 3 ቀን አሸጋገረ:: ትንሽ ቆይቶ ግን ጾሙ 7 ቀን ሆነ:: ምን ጊዜም እህልን የሚቀምሰው በዕለተ ሰንበት (እሑድ) ብቻ ሆነ::

+ሁልጊዜም በዕለተ ሰንበት ቅዳሴን ይቀድሳል:: ለእርሱ ሥጋ ወደሙን ተቀብሎ ለሌሎቹ ያቀብላል:: ከዚያም ወደ በዓቱ ሒዶ አንዲት ዻኩሲማን ይመገባል:: "ዻኩሲማን" አባቶች በቀደመ ልሳን "የዳቦ ለከት" ይሉታል:: በዘመኑ ልሳን "ትንሽ የዳቦ ቁራጭ" እንደ ማለት ነው::

+ከዚህ ጐንም ወገቡን በሰንሰለት ታጥቆ በፍጹም መንፈሱ ይጸልይና ይሰግድ ነበር:: በዚህ ተጋድሎ ላይ ሳለም በታላቁ አባ አጋቶን ሕይወት መቅናትን ቀና:: በአንደበት ከሚወጣ ኃጢአት ይጠበቅ ዘንድም ሙልሙል ድንጋይ አዘጋጅቶ ጐረሰው::

+ያ ድንጋይ የሚወጣው በሳምንት አንዴ: ለሥጋ ወደሙና ለቁርባን ብቻ ነበር:: ማንም ምንም ቢያደርገውም ሆነ ቢናገረው ምንም አይመልስም:: ይህም ተጋድሎ "አርምሞና ትዕግስት" ይባላል::

+አርምሞ (ዝምታ) አንደበትን መቀደስ ሲሆን ትዕግስት ደግሞ ልብን ጸጥ አድርጐ መቀደስ ነው:: 2ቱ ጸጥ ካሉ ሰውነትም ከኃጢአት ማዕበል ጸጥ ይላልና:: የክብር ባለቤት መድኃኒታችን ክርስቶስም በመዋዕለ ስብከቱ ማርያምን "ኃርየት መክፈልተ ሠናየ - በጐ እድልን መረጠች" ያላት ስለዚህ ሃብቷ እንደ ሆነ መተርጉማን አትተዋል:: (ሉቃ. 10, ቅዳሴ ማርያም)

+ቅዱስ ሉቃስ በዚህ ሕይወቱ ለ3 ዓመታት ቆየ:: በሁዋላ አምላክ ቅዱስ መልአኩን ልኮ ወደ ቁስጥንጥንያ መራው:: የብርሃን መስቀል እየመራውም ወደ ምሥራቅ ተጉዋዘ::

+በዚያም እስከ ዛሬ ድረስ የሚታወቅበትን ተጋድሎ ጀመረ:: ከቁስጥንጥንያ ከተማ አቅራቢያ አንድ ምሰሶ አግኝቶ በላዩ ላይ ወጣ:: በዚያም ከእርሱ በፊት የነበሩ ቅዱሳን አባ ስምዖንና አባ አጋቶን ዘዓምድ እንዳደረጉት ያደርግ ጀመር::

+በምሰሶው ላይ መቀመጥ ስለ ማይቻል ትልቁና የመጀመሪያው ገድል ያለ ዕረፍት መቆም ነው:: በተረፈ ግን ለአካባቢው ምዕመናን መሪ: አስተማሪ ነበር:: ዝናውን እየሰሙ ሰዎች ከተለያየ አሕጉር ይመጡ ነበር::

+ያላመኑትን በስብከቱ ማሳመን: ያመኑትንም በምክሩ ማጽናትን ቀጠለ:: እርሱ አስተምሮት የማይለወጥ አልነበረም:: ምክንያቱም ምሉዓ መንፈስ ቅዱስ (መንፈስ ቅዱስ የመላበት) ነውና አጋንንት በሥፍራው አይቆሙምና::

+በጊዜውም ዻዻሳቱም: ካህናቱም: ሕዝቡም: መሣፍንቱም ይወዱት ነበር:: ቢያዝኑ አጽናኝ: ቢታመሙ ፈዋሽ: ከፈጣሪ ቢጣሉ አስታራቂ ነበርና:: እንዲህ ባለ ተጋድሎ ቅዱስ ሉቃስ ለ45 ዓመታት በምሰሶው ላይ ቆየ:: ስለዚህ እስከ ዛሬም ድረስ "ዘዓምድ" (THE STYLITE) እየተባለ ይጠራል::

+እግዚአብሔር ሊያሳርፈው በፈለገ ጊዜም ደቀ መዝሙሩን ጠርቶ ወደ ከተማ ላከው:: መልእክቱን የሰሙት የቁስጥንጥንያ ከተማ መሣፍንት: ዻዻሳት: ሕዝቡና ካህናቱ እየተሯሯጡ ቢመጡ ታኅሳስ 15 ቀን በፍቅር ዐርፎ አገኙ::

+እያዘኑ በታላቅ ለቅሶና ዝማሬ ወደ ቁስጥንጥንያ አደረሱት:: በዚያም በክብር በዚህች ቀን ከአበው መቃብር ቀበሩት::

<< ዛሬም ድረስ በአካባቢው ክቡር አባት ነው !! >>
=>አምላከ ቅዱስ ሉቃስ መካሪ: ዘካሪ አባቶችን አያሳጣን:: ከቅዱሱ በረከትም

ያሳትፈን::

=>ታሕሳስ 17 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ሉቃስ ዘዓምድ
2.ቅዱስ ናትናኤል ጻማዊ
3.ቅዱስ ማርቆስ

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ እስጢፋኖስ ሊቀ ዲያቆናት (ወቀዳሜ ሰማዕት)
2.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ወልደ ዘብዴዎስ)
3.ቅዱሳን አበው መክሲሞስና ዱማቴዎስ
4.አባ ገሪማ ዘመደራ
5.አባ ዸላሞን ፈላሢ
6.አባ ለትጹን የዋህ
7.ቅዱስ ኤዺፋንዮስ ሊቅ
8.ቅድስት ወለተ ዼጥሮስ

=>+"+ ጻድቅ እንደ ዘንባባ ያፈራል::
እንደ ሊባኖስ ዝግባም ያድጋል::
በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ተተክለዋል::
በአምላካችንም አደባባይ ውስጥ ይበቅላሉ::
ያን ጊዜ በለመለመ ሽምግልና ያፈራሉ::
ደስተኞችም ሆነው ይኖራሉ:: +"+ (መዝ. 91:12)

   <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
Daniel:
እንኩዋን ለቅዱሳን "ሐዋርያት ቶማስ ወቲቶ" እና "አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ "*+

=>ከ12ቱ ቅዱሳን ሐዋርያት አንዱ የሆነው ቅዱስ ቶማስ ብዙ መከራን በማሳለፉና የጌታችንን ጐን በመዳሰሱ ይታወቃል::

+ቅዱስ ቶማስ እንደ ሌሎቹ ሐዋርያት በእሥራኤል ተወልዶ በዚያውም በሥርዓተ ኦሪት አድጐ ገና በወጣትነቱ የሰዱቃውያንን ማሕበር ተቀላቅሏል:: ሰዱቃውያን ሰው ከሞተ በሁዋላ አይነሳም (አልቦ ትንሳኤ ሙታን) የሚሉ ናቸው:: መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማስተማር ሲጀምር ግን ቅዱስ ቶማስ ከነበረበት ማሕበር ወጥቶ ጌታችንን ተከተለ:: ጌታችንም ከ12ቱ ሐዋርያት አንዱ ይሆን ዘንድ ሾመው:: የቀደመ ስሙ "ዲዲሞስ" ሲሆን ጌታችን "ቶማስ" ብሎታል::

+ቅዱስ ቶማስ ጌታ አልዓዛርን ለማስነሳት በሔደ ጊዜ ሌሎች ሐዋርያት ጌታን "አይሁድ ይገድሉሃል ቅር" ሲሉት እርሱ ግን "እንሒድና አብረን እንሙት" ሲል ፍቅሩን አሳይቷል:: (ዮሐ. 11:16)

+ጌታችን ትንሳኤውን ለደቀ መዛሙርቱ በገለጠ ጊዜ ያልነበረው ቶማስ ካላየሁ አላምንም አለ:: ምክንያቱም:-

1.ለጌታችን ከነበረው ፍቅር የተነሳ እውነት አልመስልህ ቢለው::

2.አንድም "ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሳኤውን አየን እያሉ ሲያስተምሩ እኔ ግን ሰማሁ ብየ ማስተማሬ ነው" ብሎ በማሰቡ ነበር::

+ለጊዜው ጌታ ተገልጾ ቢገስጸው "እግዚእየ ወአምላኪየ (ጌታየና አምላኬ)" ብሎ ፍጹም ሃይማኖቱን ገልጿል:: ለፍጻሜው ግን የጌታችንን ጎን (መለኮትን) ይዳስስ ዘንድ ባለቤቱ እንዳደለው ያጠይቃል:: መለኮትን የዳሰሰች ይሕቺ ቅድስት እጁ ዛሬም ድረስ ሕያው ናት::

+ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው ሐገረ ስብከት ሲከፋፈሉ ለቅዱስ ቶማስ ሕንድና በዙሪያዋ ያሉ ሃገራት ደረሱት::

+ከዚህ በሁዋላ ነው እንግዲህ ዘርዝረን የማንጨርሰውን ተጋድሎ የፈጸመው:: ቅዱሱ በነበረው ፍጹም ትጋት አባቶቻችን "ዘአሠርገዋ ለብሔረ ሕንደኬ (ሕንድን በወንጌል ያስጌጣት)" ሲሉ ያከብሩታል::

+ቅዱስ ቶማስ ንጉሥ ሉክዮስንና የሃገሩን ሕዝብ ለማሳመን በችንካር መሬት ላይ ወጥረው ቆዳውን ገፈውታል:: ቆዳውንም እንደ ገና ሰፍተው: አሸዋ ሞልተው አሸክመውታል:: በየመንገዱ የተገፈፈ ገላውን ጨው ቢቀቡት በጎች መጥተው ግጠው በልተውታል:: በዚሕ ምክንያት:-
"ኩሉ የአኪ እንዘ የአኪ ዘመኑ::
አባግዒሁ ለቶማስ እስመ አራዊተ ኮኑ::" ብለዋል ሊቃውንቱ::

+በሁዋላ ግን ከፎቅ ወድቃ የሞተችውን የንጉሡን ሚስት በተገፈፈ ቆዳው በማዳኑ ሁሉም አምነው ተጠምቀዋል::

+ቅዱሱ ሐዋርያ ልክ እንደ ቅዱስ ዻውሎስ አንዳንዴ በፈሊጥ: ሌላ ጊዜም በመከራ ለወንጌልና ለቤተ ክርስቲያን ተጋድሏል:: ያለ ማቁዋረጥም ከሕንድ እስከ ሃገራችን ኢትዮዽያ ድረስ ለ38 ዓመታት ወንጌልን ሰብኩዋል:: በመጨረሻም በ72 ዓ/ም በሰማዕትነት አርፏል:: መቃብሩና ቅድስት እጁ ዛሬ ድረስ ሕንድ ውስጥ አሉ:: ከኘሮቴስታንቶች በቀር መላው ዓለም ያከብረዋል:: ዛሬ የቅዱሱ ሐዋርያ በዓለ ፍልሠቱ ነው::

+*" ቅዱስ ቲቶ ሐዋርያ "*+

=>የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዝሙር ቅዱስ ቲቶ ከ72ቱ አርድእት አንዱ ሲሆን በተወሰነ መንገድም ቢሆን የተዘነጋ ሐዋርያ አይደለም:: በተለይ ደግሞ ቅዱስ ዻውሎስ ከጻፋቸው 14 መልእክታት መካከል አንዷ የተላከችው ለዚህ ቅዱስ በመሆኗ ታሪኩ እንኩዋ ባይነገር ስሙ አይረሳም:: ቅዱስ ዻውሎስም በመልዕእክታቱ በጐ ስሙን እየደጋገመ ያነሳዋል::

=>ለመሆኑ ሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ ማን ነው?

+ቅዱስ #ቲቶ የተወለደው በ1ኛው መቶ ክ/ዘ እስያ ውስጥ ቀርጤስ በምትባል ከተማ ነው::

+መዳን በእውቀት ይመስላቸው ስለ ነበር የአካባቢው ሰዎች የግሪክን ፍልስፍና ጠንክረው ይማሩ ነበር:: ቅዱስ ቲቶም በወጣትነቱ ወደ ት/ቤት ገብቶ የግሪክን ፍልሥፍናና የዮናናውያንን ጥበበ ሥጋ ተማረ:: በጥቂት ጊዜም የሁሉ የበላይ ሆነ::

+ቅዱሱ ምክንያቱን ሳያውቀው ለእኔ ቢጤዎች ያበላ: ያጠጣ: ይንከባከባቸውም ነበር:: እግዚአብሔር ግን የዚህ ቅን ሰው በጐነቱ እንዲሁ እንዲቀር አልወደደምና አንድ ቀን በራዕይ ተገለጠለት::

+በራዕይም አንድ ምንነቱን ያልተረዳው ነገር "ቲቶ ሆይ! ስለ ነፍስህ ድኅነት ተጋደል:: ይህ ዓለም ኃላፊ ነው" ሲለው ሰማ:: ከእንቅልፉ ነቅቶ በእጅጉ ደነገጠ:: የሚያደርገውንም አጣ:: ያናገራቸው ሁሉ ምንም ሊገባቸው አልቻለም::

+ድንገት ግን በዚያ ሰሞን ከወደ ኢየሩሳሌም አዲስ ዜና ተሰማ:: "ክርስቶስ የሚሉት ኢየሱስ: እርሱም የባሕርይ አምላክ የሆነ ወደ ምድር ወርዶ: ስለ እግዚአብሔር መንግስትም እየሰበከ ነው" ሲሉ ለቲቶ ነገሩት::

+"ሌላስ ምን አያችሁ?" አላቸው:: "በእጆቹ ድውያን ይፈወሳሉ: ሙታን ይነሳሉ: እውራን ያያሉ: ለምጻሞች ይነጻሉ: ሌሎች ብዙ ተአምራትም እየተደረጉ ነው" አሉት:: የወቅቱ የሃገረ አክራጥስ መኮንን ፈላስፋ ነበርና ስለ ክርስቶስ ሲሰማ ሊመራመር ወደደ::

+"ብልህ ጥበበኛ ሰው ፈልጉልኝ" ብሎ ተከታዮችን ቢልካቸው ከቲቶ የተሻለ በአካባቢው አልነበረምና እርሱኑ አመጡት:: መኮንኑ ቲቶን "ነገሩ ትክክል ወይም ስሕተት መሆኑን በጥልቅ መርምረህ ምላሽ አምጣልኝ" ብሎ ላከው::

+ቅዱስ ቲቶም ፈጥኖ ተነስቶ ወደ ኢየሩሳሌም ገሰገሰ:: ወደ ከተማዋ እንደገባም ጌታችንን አፈላልጐ አገኘው::

1.ጌታችን ክርስቶስ በሥልጣነ ቃሉ ደዌያትን ሲያርቅ: አጋንንትን ሲያሳድዳቸው ተመልክቶ ይህ ሥራ የፍጡር እንዳልሆነ ተረዳ::

2.ጌታችን የሚያስተምረው ትምሕርት ከግሪክ ፍልሥፍና እጅግ ርቆና መጥቆ አገኘው:: ጌታ በጣዕመ ቃሉ የሚያስተምረው ሰማያዊ: በዚያ ላይ ዘለዓለማዊ የሆነ ትምሕርት ነው:: በራዕይ "ስለ ነፍስህ ተጋደል" ያለው ምሥጢር አሁን ተተረጐመለት::

+በዚህ ምክንያትም ጊዜ አላጠፋም:: ወዲያውኑ አምኖ ተከታዩ ሆነ:: ጌታም ከ72ቱ አርድእት ደመረው:: የአክራጥስ መኮንን "ምነው ዘገየህ?" ቢለው ያየውን ሁሉ ጽፎ: እንደማይመለስም አክሎ ደብዳቤ ላከለት::

+ከዚህ በሁዋላ ቅዱስ ቲቶ ከጌታችን እግር ለ3 ዓመታት ተምሮ: በበዓለ ሃምሳ መንፈስ ቅዱስን ተቀብሎ: በመላው እስያ ወንጌልን ሰብኩዋል:: ቅዱስ ዻውሎስ ባመነ ጊዜ ደግሞ የእርሱ ደቀ መዝሙር ሆኖ ለ25 ዓመታት አስተምሯል::

+ቅዱስ ዻውሎስ ሰማዕት ከሆነ በሁዋላ ደግሞ ወደ አክራጥስ ተመልሶ: ሕዝቡን አሳምኖና አጥምቆ: ቤተ ክርስቲያንን አንጿል:: ዕድሜው በደረሰ ጊዜም መምሕራንን: ካህናትን ሹሞላቸው: ባርኩዋቸውም ዐርፏል:: ዛሬ የቅዱሱ ሐዋርያ በዓለ ፍልሠቱ ነው::

+*" አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን "*+

=>ቅዱሱ በትውልዳቸው ግሪካዊ ቢሆኑም ሶርያ አካባቢ እንዳደጉ ይታመናል:: በቀደመ ስማቸው ፍሬምናጦስ የሚባሉት አቡነ ሰላማ ወደ ኢትዮዽያ የመጡት በአደጋ ምክንያት ቢመስልም ውስጡ ግን ፈቃደ እግዚአብሔር ነበረበት::

+በድንበር ጠባቂዎች ከባልንጀራቸው ኤዴስዮስ ጋር ተይዘው ወደ አክሱም የመጡት በንጉሥ ታዜር (አይዛና) እና በሚስቱ ሶፍያ (አሕየዋ) ዘመን ነው:: ጊዜው በውል ባይታወቅም በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው::
+ፍሬምናጦስ ምንም የመጡበት ዓላማ ስብከተ ወንጌል ባይሆንም በአክሱም ቤተ መንግስት አካባቢ ይሰብኩ ነበር:: ያን ጊዜ በጃንደረባው ቅዱስ ባኮስ የተቀጣጠለው የክርስትና ችቦ ውስጥ ውስጡን በሃገሪቱ ነበረና ፍሬምናጦስ አልተቸገሩም:: በተለይ ኢዛናና ሳይዛናን ከልጅነት ስላስተማሯቸው ነገሮች የተሳኩ ሆኑ::+ንጉሥ ታዜር እንደ ሞተ2ቱ ሕጻናት በመንበሩ ተቀመጡ:: ፍሬምናጦስንም ወደ ግብፅ ዻዻስና ጥምቀት ከመጻሕፍት ጋር እንዲያመጣላቸው ላኩ:: ሐዋርያዊ ቅዱስ አትናቴዎስም ፍሬምናጦስን "ሰላማ" ብሎ ሰይሞ: በዽዽስና: በንዋየ ቅድሳትና በመጻሕፍት ሸልሞ መለሳቸው::

+አቡነ ሰላማ ወደ ኢትዮዽያ እንደተመለሱ ከነገሥታቱ ጀምረው ለሕዝቡ ጥምቀትን አደሉ:: ኢዛናና ሳይዛናም አብርሃ እና አጽብሃ ተብለው ስማቸው ተደነገለ:: ከዚያ በሁዋላ ድንቅ በሚሆን አገልግሎት ነገሥታቱ: ዻዻሱ ሰላማና ሊቀ ካህናቱ እንበረም ለክርስትና መስፋፋት በጋራ ሠርተዋል::

=>የአቡነ ሰላማ ትሩፋቶች:-
1.ዽዽስናና ክህነትን ከእውነተኛ ምንጭ አምተዋል::
2.ክርስትናና ጥምቀትን በሃገራችን አስፋፍተዋል::
3.ቅዱሳት መጻሕፍትን ከውጭ ልሳኖች ተርጉመዋል::

4.ገዳማዊ ሕይወትን ጀምረዋል::
5.አብያተ ክርስቲያናትን አንጸዋል::
6.ግዕዝ ቁዋንቁዋን አሻሽለዋል::
ሀ.ከግራ ወደ ቀኝ እንዲፃፍ
ለ.እርባታ እንዲኖረው
ሐ.ከ"አበገደ" ወደ "ሀለሐመ" ቀይረዋል::

+ባላቸው ንጹሕ የቅድስና ሕይወት ለሕዝቡ ምሳሌ ሆነዋ:: "ወበእንተዝ ተሰይመ ከሳቴ ብርሃን" እንዲል በነዚህ ምክንያቶች "ከሣቴ ብርሃን" (ብርሃንን የገለጠ) ሲባሉ ይኖራሉ:: በመጨረሻም ከመልካሙ ገድል በሁዋላ በ352 ዓ/ም ዐርፈው ተቀብረዋል:: ቅዱሱ ለሃገራችን ዻዻስ ሆነው የተሾሙት በዚህች ዕለት ነው::

=>አምላከ አበው ቅዱሳን በመጽናታቸው ያጽናን:: ከበረከታቸውም ያድለንና።


ታሕሳስ 18 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ (ፍልሠቱ)
2.ቅዱስ ቲቶ ሐዋርያ (ፍልሠቱ)
3.አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን
4.ቅዱስ ፊልሞና ባሕታዊ
5.ቅዱስ ኢርቅላ

=>ወርሐዊ በዓላት
1.አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ረባን
2.አቡነ አኖሬዎስ ዓቢይ
3.ማር ያዕቆብ ግብጻዊ
4.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ከ72ቱ)
5.ቅዱስ ፊልዾስ ሐዋርያ (ከ12ቱ)

=>+"+ የእግዚአብሔር ባሪያና የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የሆነ ዻውሎስ . . . መድኃኒታችን እግዚአብሔር እንዳዘዘ: ለእኔ አደራ በተሰጠኝ ስብከት ቃሉን ገለጠ: በሃይማኖት ኅብረት እውነተኛ ለሚሆን ልጄ ቲቶ::
ከእግዚአብሔርም አብ: ከመድኃኒታችንም ከጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ምሕረት: ሰላምም ይሁን:: +"+ (ቲቶ. 1:1)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
Forwarded from ሊdia
⚡️መጪዉን ትልቅ የ ልደት በዓል መታሰቢያ ምክንያት በማድረግ ለ አንድ በጎ አድራጎት ተቋም የ ስጦታ ማሰባሰብ እያረግን እንገኛለን። ስጦታዉ የሚሆነዉ በ አይነት ብቻ ሲሆን፣

🩸በ ዚህኛዉ ዙር ሞዴስ ይሆናል።
    ስጦታዉን የምንቀበለዉ በ አይነት ብቻ ነዉ። አንድ ሰዉ እንዲሰጥ ሚጠበቀዉ ሞዴስ ብዛት በቤተሰብ ቁጥር እንዲሆን እንመክራለን።
📌አድራሻ ፡ ያሉበት መተን ወይም አቅራቢያዎ ባለን ሰዉ እንቀበላለን።
📌 0900611328


መልካም በአል!
†† እንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል: ቅዱስ ዮሐንስ ዘቡርልስ እና አቡነ ስነ ኢየሱስ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት †††

††† በቤተ ክርስቲያን ክቡር ከሆኑ ሊቃነ መላእክት አንዱ የሆነው ቅዱስ ገብርኤል ብዙ የክብር ስሞች አሉት:: በተለይ ግን:-
*ሊቀ አርባብ:
*መጋቤ ሐዲስ:
*መልአከ ሰላም:
*ብሥራታዊ:
*ዖፍ አርያማዊ:
*ፍሡሐ ገጽ:
*ቤዛዊ መልአክ:
*ዘአልቦ ሙስና . . . እየተባለ ይጠራል::

በብሉይ ኪዳንም ሆነ በሐዲስ ኪዳን ስሙ በብዛት ተጠቅሷል:: ስለ ረዳትነቱና አማላጅነቱም ቤተ ክርስቲያን በስሙ ታቦት ቀርጻ: መቅደስ አንጻ በሥርዓት ክብሩን ትገልጻለች::

ከእነዚህም አንዱ ሠለስቱ ደቂቅን እንዳዳነ የሚታሰብበት አንዱ በዓሉ ዛሬ ነው::
"ለዝንቱ ዜናዊ መልአከ ኃይል::
በዛቲ ዕለት ከመ ይትገበር በዓል::
መምሕራን አዘዙ ወሠርዑ በቃል::" እንዲል:: (አርኬ)

ንጉሡ ከምርኮ ወጣቶች ለቤተ መንግስት ሲመርጥ ሦስቱ ቅዱሳንና ዳንኤል ተመርጠው የምቾት ሕይወት ተዘጋጅቶላቸው ነበር:: ነገር ግን በምግብና በአምልኮ ከአሕዛብ ጋር መተባበርን አልፈለጉምና ምርጫቸው ጾምና ጸሎት ከቆሎ ጋር ሆነ::

ምንም እንኳ በቤተ መንግስት ውስጥ ቢኖሩ: ምንም የነገሥታት ልጆች ቢሆኑ ለእነርሱ ከእግዚአብሔር ፍቅር የተሻለ አልነበረምና በጥሬ ቆሎ ተወስነው ኖሩ::

አምላካቸው ከሃሊ ነውና በውበትም ሆነ በጥበብ በባቢሎን ምድር ከነርሱ የሚደርስ አልተገኘም:: ንጉሡም በባቢሎንና በአውራጃዋ ላይ ሾማቸው:: ስማቸውንም በአማልክቱ ስም ሲድራቅ: ሚሳቅና አብደናጐ አላቸው::

ከነገር ሁሉ በኋላ አሕዛብ ቀንተውባቸዋልና የክፋት አዋጅን አሳወጁ:: ናቡከደነጾር 60 ክንድ ቁመት ያለውን የወርቅ ምስል አቁሞ ስገዱ ቢላቸው አይሆንም በማለታቸው ተቃጥለው እንዲሞቱ እሳት ተፈረደባቸው:: ነበልባሉ ከጉድጓዱ ወደ ላይ 49 ክንድ ቢነድም ቅንጣት ያህል ፍርሃት አልጎበኛቸውም::

ወደ እሳቱም ሲጥሏቸው መልዐከ አድኅኖ ቅዱስ ገብርኤል ደርሶ አዳናቸው:: ከሆነው ነገር የተነሳ አሕዛብ አፈሩ:: ናቡከደነጾር ግን ከዙፋኑ ተነስቶ የቅዱሳኑን አምላክ እግዚአብሔርን ባረከ::

ቅዱሳኑን ያዳነ ቅዱስ መልአክ እኛንም ያድነን ዘንድ እንደ አባቶቻችን
"አድኅነኒ ዘአድኃንኮሙ በአክናፊከ ምንትው::
አመ ውስተ እሳት ተወድዩ ሠለስቱ እደው::" እያልን እንለምነው:: (መልክዐ ገብርኤል)

††† ቅዱስ ዮሐንስ ዘቡርልስ †††

††† ይህ ቅዱስ አባት ስም አጠራሩ የከበረ ነው:: ሊቅም: ጻድቅም: ጳጳስም: ገዳማዊም ነው:: ከሁሉም በላይ ግን ዛሬም ድረስ ቤተ ክርስቲያን በተድላ ለምትጠቀምባቸው መጻሕፍት (ስንክሳር: ግጻዌ እና ሃይማኖተ አበው) መሠረትን የጣለ ቅዱስ ሰው ነው::

ቅዱስ ዮሐንስ በትውልዱ ግብጻዊ ሲሆን ጊዜውም 5ኛው መቶ ክ/ዘ ነው:: ወላጆቹ ክርስቲያኖች: በዚያውም ላይ ሞልቶ የተረፋቸው ባለ ጠጐች ነበሩ:: እንደ ሕጉ ወጣት እስኪሆንና ራሱን እስኪችል ድረስ አሳደጉት::

ከዚያ ግን ድንገት አባቱና እናቱ ተከታትለው ዐረፉ:: ከቁጥር የበዛ ሃብትን የግሉ ያደረገው ቅዱስ ዮሐንስ ምን እንደሚያደርግበት ጨነቀው:: አንድ ትልቅ ነገር ግን ከማይሆን ጐዳና ጠበቀው::

ወላጆቹ ሁሌም መዝገብን በሰማያት ያገኙ ዘንድ ለነዳያን ይራሩ ነበርና ይህንኑ ለመቀጠል ወሰነ:: መልካም ፍሬ ከመልካም ዛፍ ነውና (ማቴ. 7:16) ወላጅ ለልጁ ማውረስ ያለበት ምድራዊ ሃብትን ሳይሆን በጐ ሕሊናን ነው:: ሳይሠሩ ያገኙት ሃብት ብዙዎችን አጥፍቷቸዋል::

ለዛም ይመስላል ዛሬ አንዳንዶቻችን በቤተሰቦቻችን ሃብት ከእኛ አልፈን ትውልዱን እየገደልንበት ያለው:: ለዚህ ደግሞ እግዚአብሔር ንስሃ ካልገባን ይመጣብናል:: መቅረዛችን (ሕይወታችንም) ከእኛ ላይ ይወስዳል::

ፍርድ የሚሆነው በክፉው ትውልድ ላይ ብቻ አይደለም:: ይህንን ትውልድ በፈጠርነውና መልካሙን መንገድ ባልመራነው በሁላችንም ላይ እንጂ:: (ራዕ. 2:5)

ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና ቅዱስ ዮሐንስ በወላጆቹ ሃብት የእንግዶች ማረፊያ የሚሆኑ ቤቶችን አንጾ ነዳያንን ይንከባከብ ገባ:: ሙሉውን ቀን ለነዳያን ሲራራ ይውላል:: አመሻሽ ላይ እንግዶችን ተቀብሎ: አብልቶ ያሳርፋል::

ከዚያም ፈጣሪውን ያመሰግናል:: በእንዲህ ያለ ሕይወት ዘመናትን ካሳለፈ በኋላ አንድ እንግዳ መነኮስ ወደ ቤቱ መጣ:: አስተናግዶት ሲጨዋወቱ አደሩ:: ሌሊት ላይ ግን ስለ ምንኩስና ሕይወትና ስለ ክብሩ ነግሮት ነበርና ልቡ ተመሰጠ::

መነኮሱን ከሸኘው በኋላም ይመንን ዘንድ ቆረጠ:: ነዳያንን ሰብስቦ ሃብቱን አካፈላቸው:: ከዚያም ወደ ገዳመ አስቄጥስ ሒዶ የታላቁ አባ ዳንኤል ደቀ መዝሙር ሆነ:: በትሕትና ለአባቶች እየታዘዘ ከቆየ በኋላ በጭንቅ ደዌ ተያዘ:: ሰይጣን በቅንዓት ገርፎት ነበርና::

እርሱ ግን በደዌው ምክንያት ለዓመታት መሬት ላይ ወድቆ ቢቆይም ፈጣሪውን ፈጽሞ ያመሰግን ነበር:: እግዚአብሔር ደግሞ በፈውስና በኃይል አስነሳው::

በጊዜው የቡርልስ ጳጳስ ዐርፎ ነበርና አባት ፍለጋ ወደ አስቄጥስ ገዳም መጥተው ነበር:: መንፈስ ቅዱስ መርጦታልና አበው ቅዱስ ዮሐንስ ጳጳስ ይሆን ዘንድ አስገደዱት:: እርሱም የፈጣሪ ፈቃድ መሆኑን ስላወቀ ሔደ::

በዚያም (በሃገረ ቡርልስ) ታላቁን ገድል ተጋደለ:: ወደ ከተማዋ ሲገባ ብዙ ነገሮች ከሚገባው ሥርዓት የወጡ ነበሩ:: ብዙ ሰው የእግዚአብሔርን ድምጽ ከመስማት ይልቅ ባላስፈላጊ ነገሮች ላይ ተጠምዶ ነበርና መንጋውን ያድን ዘንድ ተጋ::

ሳይሆኑ "ባሕታዊ": "አጥማቂ" ነን እያሉ ሕዝቡን የሚያሳስቱ ተኩላዎችንም አስወገደ:: ለሕዝቡ አጉል ሕልም: ሟርትን የሚያስተምሩትን ገሠጸ:: አንመለስም ያሉ መናፍቃንን እሳት ከሰማይ ወርዳ በላቻቸው::

ቅዱስ ዮሐንስ ከቅድስናው ብዛት ዘወትር ሲቀድስ መድኃኒታችንንና አእላፍ መላእክትን ያይ ነበር:: ከከዊነ እሳት ማዕረግ በመድረሱም አካሉ በመፈተት ሰዓት እንደ እሳት ይነድ ነበር:: እንባውም እንደ ውኃ ይፈስ ነበር::

ቅዱስ ዮሐንስ ከዚህ ጐን ዛሬም ድረስ የሚታወቅበትን ታላቅ ሥራም ሠርቷል:: መንፈስ ቅዱስ አነሳስቷቸው ቅዱሱና የሃገረ አትሪብ ጳጳስ የነበረው ሊቁ አባ ሚካኤል መጽሐፈ ስንክሳርን : መጽሐፈ ግጻዌንና ሃይማኖተ አበውን ለመጀመሪያ ጊዜ አዘጋጅተዋል::

"ስንክሳር" የቅዱሳንና የፈጣሪን ነገር በየዕለቱ የሚዘግብ መጽሐፍ ሲሆን "ግጻዌ" የየዕለቱን በዓላት ከምስባክና ምንባባት ጋር አስማምቶ የያዘ መጽሐፍ ነው:: "ሃይማኖተ አበው" ደግሞ የዶግማ መጽሐፍ ሆኖ ከሐዋርያት እስከ ሊቃውንት ድረስ የጻፉትን የያዘ ነው:: ሦስቱን የሚያመሳስላቸው "ስብስብ / እስትጉቡዕ / Collection" መሆናቸው ነው::

ቅዱሱ ዮሐንስ በሃገረ ቡርልስ በከፍተኛ ድካም ይህንን ፈጽሞ በዚህች ቀን ዐርፏል::

††† አቡነ ስነ ኢየሱስ ጻድቅ †††

††† ጻድቁ በመካከለኛው (የብርሃን) ዘመን የነበሩ ኢትዮጵያዊ::
*ከምድረ ሽዋ ወደ ታች አርማጭሆ የሔዱ መናኝ:
*ጭው ባለ በርሃ ለቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ ገዳምን ያነጹ አባት:
*ብዙ አርድእትን ያፈሩ መናኝ:
*ብዙ ተአምራትን የሠሩና ወንጌልን ያስተማሩ መነኮስ ናቸው::
በደመናም ይጫኑ ነበር:: ገዳማቸውም (ታች አርማጭሆ: ከሳንጃ ከተማ የ3 ሰዓት መንገድ ይወስዳል) ድንቅና ባለ ብዙ ቃል ኪዳን ነው:: መልአከ ሞት መስከረም 1 ቀን ቢመጣ "የቅዱስ ገብርኤልን በዓል ሳላከብርአይሆንም" ብለው ለ3 ወራት በበራቸው አቁመውታል:: ታኅሣሥ 19 ቀንም ዐርፈዋል::

††† አምላከ ቅዱሳን በመልአኩ ረድኤት ጠብቆ ለጻድቃኑ በረከት ያብቃን::

††† ታኅሣሥ 19 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት
2.ቅዱስ ዮሐንስ ዘቡርልስ
3.አቡነ ስነ ኢየሱስ ጻድቅ

††† ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት
2.አቡነ ዓቢየ እግዚእ ጻድቅ
3.አቡነ ዮሴፍ ብርሃነ ዓለም
4.ቅዱስ ይምርሐነ ክርስቶስ

††† ". . . በአምላኬም በእግዚአብሔር ፊት ስለ ተቀደሰው ስለ አምላኬ ተራራ ስለምን: ገናም በጸሎት ስናገር አስቀድሜ በራእይ አይቼው የነበረው ሰው ገብርኤል እነሆ እየበረረ መጣ:: በማታም መሥዋዕት ጊዜ ዳሰሰኝ:: አስተማረኝም . . ." †††
(ዳን. ፱፥፳)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
2024/09/30 16:32:01
Back to Top
HTML Embed Code: