Telegram Web Link
ምክር ለወዳጅ

🔴 በወጣትነት ሁሉም ነገር ትክክል ነው ከሚል መመሪያ ውጣ ፤ ሁሉንም ካላየሁ አላምንም አትበል ። ሰምቶ ማመን ፣ ከተጎዱት መማር አስተዋይነት መሆኑን አትርሳ ። የሰማንያ ዓመት ዕውቀትን ለመገብየት ግድ ሰማንያ ዓመት መኖር የለብህም ። ሰማንያ ዓመት ከኖሩት በትሕትና መጠየቅ ይገባሃል ።

📕ምክርን ብትሰማ በነጻ ትማራለህ ። ምክርን አልሰማ ብትል ግን በዋጋ እንደምትማር እወቀው ። በዋጋ መማር ግን አድካሚ ደግሞም የሚያስመርር ነው ። ብልህ ከሆንህ በሰው ከደረሰው ትማራለህ ፣ ሞኝ ከሆንህ ግን በራስህ ሲደርስ ትማራለህ ።

📘 የታየህን አሳይ ፣ ያልታየህን አጥራው ። በደንብ ያልተረዳኸውን አታስተምረው። ያልቀመስከውን ለሰው አትጋብዝ ። የሰማኸውን ሁሉ አትመን ። ያየኸውን ሁሉ ስጡኝ ፣ የተናገርከውን ሁሉ ፈፅሙ አትበል ። የሰጠኽውን እርሳ እንጂ አታውራ። ፍፃሜውን ሳታይ ምስጋና አታብዛ ። ቀኑ ሳይመሽ ቀኑ ጥሩ ነው አትበል ።

📘ዓይንህ የፊቱን ቢያይ ልብህ የኋላውን ያስብ ። ነገ ላይ እንድትደርስ የትናንቱን አትርሳ ። የምትሄድበት እናዳይጠፋህ የመጣህበትን አትዘንጋ ።

🔴የአባቶችህን መልካም ሥራ አብነት አድርግ ። ካሳለፉት ሕይወት ተማር እንጂ አወዳሽና ወቃሽ አትሁን ። ሌሎች መሆን ያለባቸውን ስታውቅ አንተ መሆን ያለብህ እንዳይጠፋህ ተጠንቀቅ ። ደግሞም አንተም በታሪክ ፊት መሆንህን እወቀው ።

🔵 ክፋት አይሙቅህ ፣ መልካም ነገርም ብርድ ብርድ አይበልህ ። ለክፋት አቅም ካለህ ለበጎ ነገርም አቅም አለህና ተግባርህ የምርጫ ውጤት ነውና አስብበት ።

📕 ገንዘብ የሚመልሰው የገንዘብን ጥያቄ ብቻ ነውና ሁሉንም ነገር ገንዘብ ያስገኝልኛል ብለህ አታስብ ። ላለው አትሩጥ ፣ ምጽዋትህና ተግባርህ በአቅምህ መጠን ይሁን እንጂ ከአቅምህ አትነስ ። ድሃም ሆነህ ተበድረህ ስጦታ አትስጥ ። በጣም ካልቸገረህ ለቅንጦት አትበደር ። ያንተን ድርሻ ከጨረስህ ያልተጨረሰ የሌሎችን ድርሻ ፈፅምላቸው ።

💎 ለሀብታም አትሳቅ ፣ የደሀ ጉልበት አይለፍብህ ፣ ያለ ሰው ሰው አልሆንክምና ሰው አትጥላ ፣ የወጣህበትን መሰላል አትገፍትር ፣ ለመውረድም ያስፈልግሃልና ፣ ያየኽውን ሴት ሁሉ የመውደድ ጠባይህ ካለቀቀህ ትዳር አትያዝ ፣ ካልጋበዙህ በቀር አማካሪ አትሁን ፣ ባልጠሩህ ሥፍራ አቤት አትበል ፣ ካልሾሙህ መሪ አትሁን ፣ ጉድለት በሌለበት ቦታ ጊዜህን አታባክን ፣ የሰው ፊት ጥገኛ ሁነህ ሲስቁልህ የምትስቅ ሲቆጡህ የምታለቅስ አትሁን ፣ ነገርህን በልክ ፣ ቃልህን በጣዕም ፣ ድምፅህን በዝግታ ፈፅመው ።

🔵እውር እንዳይሉህ ያልታየኽን አያለሁ አትበል ። ጨካኝ እንዳይሉህ ያልተሰማህን ጩኸት እሰማለሁ አትበል ። ንፉግ እንዳይሉህ ያለ አቅምህ እረዳለሁ አትበል ። ነገር አይገባውም እንዳይሉህ ያልገባህን እንደገባህ አድርገህ አትለፍ ። አንድ በጎ ዕውቀት ሳትጨብጥ የዋልክበትን ቀን እንደ ኖርክበት አትቁጠረው ፣ ስለዚህ መፅሐፍትን አንብብ ፣ አዋቂዎችን ጠይቅ ፣ ሁሉን ሳትንቅ ስማ ።

🔵 ሥልጣን ሲሰጥህ መሪ እንጂ አለቃ አትሁን ፤ ከፊት እየቀደምህ አስከትል እንጂ ከኋላ ሆነህ አትቅደም ።

🔴 በዓላማ ኑር ፤ እንቅፋቶች የሚያጸኑህ እንጂ ተግባርህን የሚያስተውህ አይሁኑ ። ሕይወት ትምህርት ቤት መሆኑና ባለማወቅ ብዙ ትህምርቶች እንዳያመልጡህ ተጠንቀቅ ።
:
📕 የመከራ ቀን ወዳጆችህን አትርሳ ፤ የዛሬ ሰው ብቻ አትሁን ፤ የትላንቱንም አስብ ፤ አንገት የተፈጠረው ዞሮ ለማየት ነውና ።

🔵ዓለም ዋዣቂ ናት ። ከፍና ዝቅ ስትል አትደናገጥ ፤ ፀሐይ ዝናብን ተከትላ ትፈነጥቃለች ። ከመከፋትም በኋላ ትልቅ መፅናናት ይሆናል ። ከሌሊት በኋላም ሌሊት አይመጣም ። ከሀዘን በኋላ ደስታ ይሆናልና በርታ!

🔴 መነቀፍን አትፍራ ፤ ነቀፋህን ግን አጥራው ፤ ስለ ሀሰት ሳይሆን ስለ እውነት ተገፋ ፤ ሌሎችን ውደድ ፍቅር ስጦታ እንጂ ብድር አይደለምና አልወደዱኝም ብለህ በአበዳሪዎች አንቀጽ አትካሰስ ፤ የገባህን አድርግ የዚህ ዓለም ሰው ሲወድህም ሲጠላህም ባለማወቅ ነው ። ብዙዎች ስለወደዱህ ይወድሃል ፤ ብዙዎች ስለጠሉህ ይጠላሃል ።

🔵 ሁልጊዜ የበላዮችህን አትመልከት ፤ የበታቾችህንም ተመልከት ። ለድምፅ አልባዎች ጩህላቸው ፣ ለተጠቁት ተሟገትላቸው ። እውነት እውነት በማለትህ የምታጣው ሀሰተኛ ወዳጅህን ብቻ ነው ። እውነት እውነት በማለትህ የምታተርፈው ግን እውነተኛ ወዳጅን ነው ።

🛑ደጋፊዎች ተከታዮች አይደሉም ። ሰዎች ስለደገፉህም የያዝኩት እውነት ነው ብለህ መንቻካ አትሁን ፤ ምናልባት ዛሬ የሚጮሁልህ ዛሬን ሊረሱብህ ሊሆን ይችላልና ። ሲያለቅሱልህም ቃልህ ማርኳቸው ሳይሆን የሞተ ዘመዳቸው ትዝ ብሏቸው ሊሆን ይችላልና አለቀሱ ብለህ ንግግርህን ድንበር አታሳጣው ። እውነትንም በደጋፊ ብዛት እንዳትመዝናት ተጠንቀቅ ።

🔴ለእውነታ እንጂ ለይሉኝታ አትኑር ፤ ያን ስልህ የምትኖርበት ሕዝብና ባሕል ከእውነት ጋር እስካልተጋጨ መጋፋት የለብህም። ሠዎች የሚቀበሉህ ባሕላቸውን ስታውቅና ስታከብርላቸው ነው ።

🔵ልጅነት የለሰለሰ መሬት ፣ ወጣትነት የአዝመራ ዘመን ፣ ሽምግልና ደግሞ የአጨዳ ዘመን መሆኑን አስተውል ። በሽምግልናህ የምታጭደው የወጣትነትህን አዝመራ ነውና ዛሬ ለምትዘራው ተጠንቀቅ ።

📍 የሰዎችን ያለማወቅ አግዝ ፤ ዕውቀትህ ባላወቁት ላይ እንድትኮራና እንድትፈርድ አያድርግህ የአዋቂ ኩሩ ቁጥሩ ካላዋቂዎች ነውና ማወቅ ባለዕዳነት እንዳይሆን አላዋቂዎችን እርዳቸው ።

🔵 ዛሬ የመዝራት ዘመንህ ነገ መከርህ ነውና በእምነት እውነትን ዝራ ፤ በምታውቀው ቦታ ላይ አገልጋይ በማታውቀው መልካም ተግባር ላይ ደጀን ሁን ፤ በቦታህ መምህር ያለቦታህ ተማሪ ሁን ፤ ክብሩ እንዳይቀንስብህ ከዕቃ ትምክህት ፣ ከዕውቀት ሙግት ራቅ ።

🔴ሁሉን ወሬ ላውራ አትበል ፣ የደበቁህን ምስጢር አታውጣጣ ፣ የሰማኽውን ወሬና የተገለጠልህን ምስጢር ምን መፍትሔ ሰጠኸውና ? ያየህውን ሥራ ሁሉ እሰራለሁ የሰማኸውን ትምህርት ሁሉ እማራለሁ አትበል ። ይህ የተሰወረው የቅንዓት ጠባይ ነውና ሁሉን ልያዝ ማለትም ዝንጉ አድረጎ እንዳያስቀርህ ሁሉም ውስጥ ልኑር አትበል ።

🔵ቆንጆዎች ቁንጅናቸው ሁሉን የሚተካ እየመሰላቸው ከዕውቀትና ከትሕትና ይርቃሉ ። ሁሉንም ሰው በመልካቸው የሚማርኩት ስለሚመስላቸው ኩሩና ተንኮለኞች ይሆናሉ ። አንተ ግን ቆንጆ ወዳጅን እንጂ ቆንጆ ቁመናን አትሻ ፤ ቆንጆ ትዳርን እንጂ ቆንጆ ሴትን አትመኝ ፤ የላይ ነገር ከንቱና ኀላፊ ነውና በሚፈርስ አካል ፣ ኑሮ በሚለውጠው መልክ አትደለል ።

🛑እወድሃለሁ ብለህ የምትናገረውን ቃል ውለታ አታድርገው ፣ መውደድህን የምትናገረው እንወድሃለን እንዲሉህ አይሁን ፣ ሠላም ያለው አፍቃሪ የራሱን ፍቅር ያለ ምክንያት መፈፀም የሚችል ብቻ እንደሆነ እወቅ ። መወደድህን ለመስማት አትጠብቅ ።

🌀የሰዎችን ያለማወቅ አግዝ ፤ ዕውቀትህ ባላወቁት ላይ እንድትኮራና እንድትፈርድ አያድርግህ የአዋቂ ኩሩ ቁጥሩ ካላዋቂዎች ነውና ማወቅ ባለዕዳነት እንዳይሆን አላዋቂዎችን እርዳቸው ።

🛑ዛሬ የመዝራት ዘመንህ ነገ መከርህ ነውና በእምነት እውነትን ዝራ ፤ በምታውቀው ቦታ ላይ አገልጋይ በማታውቀው መልካም ተግባር ላይ ደጀን ሁን ፤ በቦታህ መምህር ያለቦታህ ተማሪ ሁን።

        ውብ አዳር ❤️

@Ethiohumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
💫"የምትጓዝበት መንገድ ወደ ጥሩ አሊያም ወደ መጥፎ የሚመራው አንተን እንጂ ተመልካችህን አይደለም፤የምትለብሠው ልብስ የሚያሞቀውም ሆነ የሚያበርደው አንተኑ እንጂ የሚያይህን አይደለም፤የምትበላው ምግብ የሚጣፍጠው ወይም የሚመረው አንተን እንጂ ሌላውን አይደለም።

💫ብዙ ውጫዊ ነገሮች አስደሳች ቢሆኑም ከጊዜ ጋር የተሳሰሩና ሃላፊ ናቸው። ዛሬ ያስደሰተን ጓደኛ ነገ ላይኖር ይችላል ዛሬ ያጌጥንበት ውበት ነገ ይረግፋል፤ ዛሬ የተመካንበት አስተሳሰብ ነገ በቆመበት አይጸናም። ከውጪ የምናገኘው ማንኛውም አይነት ደስታ በመጣበት እግሩ ጥሎን መሄዱ አይቀርም። ከዛም አልፎ ዋጋ ያስከፍለናል። ከጊዜ ጋር የማይለዋወጥ ደስታን ለማግኘት ብቸኛ መፍትሄው ደስታና ሰላምን በውስጣችን መፈለግ ነው። እንደ ኩሬ ውሃ ያነሰች፤ እንደ ኩራዝ መብራት የቀጨጨች፤ እንደ ሰናፍጭ ቅንጣት የደቀቀችም ብትሆንም እንኳን ውስጣዊ ደስታን በልባችን መትከል ነው። ይህ ነው ማንም ሊነካውና ሊደፍረው የማይገባው ስፍራ።

በርግጠኝነት ለሰው ብለን የምንይዘው ማንነት፤ ለኛ በልክ እንዳልተሰፋ ልብስ አያምርብንም፤ ቀላሉ መፍትሄ እራሳችንን መሆን እና፤ መክሊታችንን መኖር ነው። በዚህ ስፍራ ውስጥ ሙሉ ነን፤ እውነተኛ እኛነታችን የሚታየው በዚህ ስፍራ ነው። ወደ ውስጣችን ዘልቀን በዚህ ስፍራ ላይ ቆመን ህይወታችንን ብናየው፤ እንደምናስበው ደካማ አይደለንም፤ የሚጎድለን ብዙ አይደለም፤ ከምንም በላይ በፈጠረን ፈጣሪ አይን ውስጥ ውብና ንጹህ ነን። ታዲያ ከዚህ በላይ ምን አለ? ደስታና ሰላማችን በሰው እጅ ፤ ፍርድና ቅጣታችን በሰው ወንበር ፈጽሞ አይሁን.!!

ውብ ምሽትን ተመኘን❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
💡ደግነትን ፣ ርህራሄን ፣ አዛኝነት ፣ ቅንነት እና በጎ አሳቢነት በተፈጥሮ ለሰው ልጅ የተቸረ ነው።

📍ከትሕትና የበለጠ መልካም ነገር የለም። የደካማነት መገለጫ አይደለም።
የዋህነት ደካማነት ሳይሆን የለስስት የመኖር ችሎታ ነው፣ ደግነት የመልካም ሰው የህይወት መምርያ ነው። ደጎች የፍቅር ልብ ያላቸው፣የሰው ችግር የሚገባቸው ።ከራሳቸው ሰውን የሚስቀድሙ ፣በሰው ላይ የማይፈርዱ ና ሩህረሩህ ናቸው ።ውስጣቸው ከክፋት የጠራ ብዙ ደስታ ና ፍቅር የሚገኝባቸው ጥበበኞች ናቸው።

📍ሰው በውስጡ በመልካም እና ሰናይ ምግባራት የተሞላ ፍጥረት ነው።
እኩይ ተግባር ግን የልምምድ ወጫዊ ተፅእኖ ተግባር ነው።በውጫዊ ተጽእኖ ሳይደናቀፉ እና ሳይቀየሩ ይህን የተፈጥሮ ጸጋ መጠቀም ደግሞ ታላቅነት ነው ሰብአዊነት ነው አርቆ አሳቢነት ነው አስተዋይነት ነው።

🔺በአስተዋይነት ከተጓዝን ደስታ ፣ ፍቅር ፣ እርካታ እና ነጻነት ደግሞ የህይወት ሽልማት ናቸው።

           ውብ አዳር ❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
ትላንት አልፏል ስለዚህ ሞቷል።
እከሌ ህይወቱ አለፈ ስንል፡ ሞተ ከአሁን ቡሃላ እዚ ምድር ላይ አይኖርም እያልን ነው። በተመሳሳይ ሁኔታ ትላንት አልፏል (አለፈ) ስንል ሞቷል በህይወታችንም ዋጋ የለውም እያልን ነው። ነገ ደሞ ሚስጥር ነው ካልደረስንበት አናውቀውም።እንዲሁም ነገ ስጦታ ነው ካልተሰጠን አንደርስበትም።ዛሬ ግን በእጃችን ላይ ነው። ስለዚህ ስለ ትላንት በማሰብ ስለነገም በመጨነቅ ዛሬን አናበላሽዉ። ትልቅ ጥበብ ዛሬን መኖር ነው ከዛሬም ደሞ አሁን። ወዳጄ ትላንት ስላሳለፍከው ነገም ስለምትሆነው አትጨነቅ። ነገን ስትደርስበት ህይወት እራሷ ትገልፅልሀለች።

💎የህይወት ትልቁ ስጦታ በህይወት
መኖር ነው። ትዳር የምትመሰርተው ሀብት ንብረት የምታፈራው በህይወት ስላለክ ነው። ህይወት ደግሞ የሚኖሯት እንጂ የሚመልስዋት ጥያቄ ፣የሚፈቷት እንቆቅልሽ አይደለችም።የሆነው ሁሉ መሆን የኖረበት ነው ፣ የሚሆነውም መሆን ያለበት ነው። ለምን ሆነ ? ህይወት ምንድነች ? የመሳሰሉትን በመጠየቅ እራስህን አታድክም። የህይወት ጥያቄዎች ሁሉ መልስ ያለው እራስዋ ህይወት ውስጥ እንጂ አይምሮህ ውስጥ አይደለም።

⌛️አንተ ያስከፋህን ነገር አይደለህም ፡አንተ ያስደሰተህንም ነገር አይደለህም አንተ የሁለቱም መውረጃ ቦይ ነህ የሚያስደስትህም የሚያስከፋህም ነገር በአንተ ውስጥ ያልፉል አንተግን ሁለቱንም አይደለህም። ይህ የህይወት ህግ ነው።

🕰ከ24 ሰአት ውስጥ 12ቱ ብርሀን 12ቱ ጨለማ ነው፣1አመትም በጋና ክረምት ነው ። አየህ በህይወት ብርሀንና ጨለማ በጋና ክረምትም ይፈራረቃሉ።ባንተም በተመሳሳይ መልኩ ማግኘትና ማጣት ፣ማዘንና መደሰት ይፈራረቃሉ ይህ ይሆን ዘንድ ግድ ነው ። በሌላው ከሆነው ይልቅ ባንተ ብቻ የሆነ ምንም የለም። ካንተ በፊትም አሁን በሚኖሩትም የሆነ ነው አንተ ላይም እየሆነ ያለዉ። የሚሟሽ የሚከለስ እንጂ አዲስ መከራ የለም። ፀደይ፣ መኸር፣በልግ እያሉ ወቅቶች እንደሚፈራረቁ ስሜቶችም አንተ ላይ ይፈራረቃሉ።ንዴት ፣ ቁጣ ፣ መረጋጋት፣ መስከን እያሉ ማለት ነው። አስታዉስ አንተ ግን ስሜቶችህን አይደለህም አንተ ከዛ በላይ ነህ።

💎ሰለዚህ ህይወት ምንድናት እያልክ አትጨነቅ ።እስዋ የህፃን ልጅ ሳቅና ለቅሶ፣ የወጣት ድንፋታ ፣የሽማግሌ ስክነት፣ አለቶች ከውሀ ጋር ሲጋጩ የሚያሰሙት ድምፅ፣ ንፋስ የሚያወዛውዘው ቅጠል ይህ ሁሉ ናት። አንተ ግን የህይወትን ሚስጥር በቃላት ለመግለፅ በመሞከር እና ስለትላንት በማሰብ እንዲሁም ስለነገ በመጨነቅ ዛሬን ታበላሻለህ።እውነት ዛሬ ነው! ። ስለዚህ ዛሬን ኑር !

ውብ አሁን❤️

@Ethiohumanity
@Ethiohumanity

@Ethiohumanitybot
❤️ጉንዳኖች ውሀ ሲሻገሩ አይተህ ታውቅ ከሆነ በውሃው ላይ ተያይዘው ተያይዘው ይቆማሉ። ጉንዳኖች ተያይዘው በወንዝ ላይ በሚሰሩበት መንገድ ሌሎች ብዙ ጉንዳኖች ይሻገራሉ። ተያይዘዉ ይሻገራሉ። ተደጋግፈው አስፈሪውን ወንዝ ይሻገሩታል። ባይያያዙና ባይደጋገፉ ግን አይቻላቸውም። አንዲት ጠብታ ዝናብ ለአንድ ጉንዳን ውቅያኖስ ብትሆንም ብዙ ጉንዳኖች አንድ ላይ ከተያያዙ ግን ውቅያኖስ መሻገር ይችላሉ።.

❤️ያንተ መኖር ለሌሎችም አንድ ቀን ለሌላ ከለላ ይሆናል።ያንተ መቆም አንድ ቀን ሌሎችን ከመውደቅ ይታደጋል ። ያንተ መኖር ላንተ ብቻ ሳይሆን ለሌሎችም አስፈላጊ ነው።ስትኖር ለራስህ ብቻ ሳይሆን ሌላን ታሳቢ ማድረግም የግድ ነው ። ሕይወት ልክ እንደ ሰንሰለት እርስ በእርስ ተያይዘው የሚያዘግሙባት የትብብር መድረክ ናት ።

❤️አኗኗራችን ነፃና ውብ መሆን ይችላል ፣ከጉብዝና ይልቅ ደግነትና ሩህሩህነት ያስፈልገናል ያለነዚህ ብቃቶች ሕይወት ቀውስ ውስጥ ትሆንና ሁሉንም እናጣለን። ይህንን ሕይወት ነፃ ውብ የተሻለ የማድረግ ኃይል አላችሁ አዲስ ስለሆነ ዓለም, ቀና ለሆነ ዓለም, የመስራት ዕድል ለሰው ስለሚሰጥ ዓለም እንልፋ ! ለወጣቱ መፃኢ ተስፋ ለአዛውንቱ እፎይታና ዕረፍትን ስለሚሰጥ ዓለም እንልፋ ጥላቻና አለመቻቻልን ለመጣል ምክንያት ስለሆነች ዓለም እንልፋ , ልፋታችን ለመልካም ብቻ ይሆን ዘንድ እንልፋ።

             ውብ አሁን❤️
@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
💡የሁላችንም ጥንካሬ ያለው በተመቻቸው ስፍራ ሳይሆን ሁኔታዎች ፈር ሲለቁ ጨለማ ሲከበንና ህይወት መውጫ የሌላት መስላ ስታስጨንቀን በምንወስነው ውሳኔ ውስጥ ነው። የማንነታችን ትርጉም የሚለካው ነን ብለን የምናስበው ማንነታችን ፈተና ሲገጥመው በምንወስደው እርምጃ ነው። እራሳችንን የፍቅር ጥግ አርገን የምንይ ከሆነ የፍቅር ጥግ መሆናችንን የሚረጋገጠው ጥላቻ ግድ የሚሆንበት ቦታ ላይ የፍቅርን ፀዳል መልቀቅ ስንችል ነው። የይቅርታ ሰው መሆናችን የሚታወቀው ይቅርታ ለማረግ በሚያስቸግርበት ሁኔታ ላይ ይቅር ማለት ስንችል ነው።ምክንያቱም ነን ብለን የምናስበው ሁሉ ያልሆነው ነገር ሲመጣ ይፈተናልና። እናም በምትፈተንበት ሰዓት የምታረገው ትልቁ ነገር ትልቁ መሸጋገርያህ ይሆናል።

🕯ታድያ ፍቅር ስትሆን ጥላቻ መሀል ትሄዳለህ። ህይወት ስትሆን ሞት መሀል ትራመዳለህ። ሰላም ስትሆን ጦርነት መሀል እራስህን ታገኛለህ። ደግ ስትሆን ክፋት ይከብሀል። እና ይሄ ሁሉ የሚሆነው ነኝ ብለህ የምታስበውን ብርሀን ነኝ ብለህ የምታስበውን ፍቅር ነኝ ብለህ የምታስበውን መልካምነት ታረጋግጥ ዘንድ ነው። " እኔ መልካም ሆኜ ሳለው ለምን መከራ በኔ ላይ ፀና" ብለህ ምታዝን ከሆነ አላማውን ስተሀል። ማንም ክፉ የለምና።ሁሉም ደግ ሁሉም ቸር ሁሉም ፍፁም ነውና። ነገር ግን አንዳንዱ ሁኔታው ሲናወጥ ማንነቱ መርሳቱ ነው። ስልጣን ፤ ገንዘብ፤ ረሀብ ፤ ጥጋብ ፤ ድህነት . . . ወዘተ ማንነትን የማስረሳት ችሎታ አላቸውና። ታድያ ሚሰርቅ ስታይ ሌባ ባለመሆንህ እራስህን እንደ ፃዲቅ አትቁጠር። ምክንያቱም የሌባው ቦታ ላይ ብትሆን እራስህ ያንን ነገር ላለማረግህ ምንም ዋስትና የለህምና። ስንቶች በተናገሩ ባወገዙት በጠሉት ነገር እራሳቸው ገብተውበት አይተናልና።

💡ፍጥረት ሁሉ ፍፁም መሆኑን ተረዳ። ፍፁም ያልሆነ ሁኔታ እንጂ ፍፁም ያልሆነ ሰው የለም። ሁሉም ሰው ክፍቶብህ ከታየህ ከመራገም ይልቅ ነኝ ብለህ ምታስበውን መልካምነት ሁን። ጥላቻ ሲከብህ ነኝ ብለህ ምታስበውን ፍቅር ሁን። ይሄን መሆን ካልቻልክ ግን ሁሌም ቢሆን ማንነትህን ሳታውቅ ትኖራለህ። እራስን መካድ የፈጠረን መካድ ነው። ውብ እና ድንቅ ሆነህ ከተፈጠርክ ውብ ና ድንቅ ሆነህ መኖር ብቸኛው አማራጭህ ነው። ውብ ና ድንቅ ሆኖ የተፈጠረው ደግሞ አንተ ብቻ ሳትሆን ሁሉም ነውና መንገዱን የሳተ ሰው ሲጎዳህ ከመርገም ይልቅ ወደ ውብነቱ ወደ መልካምነቱ የሚመለስበትን ብርሀን አብራበት።

ውብ አዳር❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
ሕይወት እንደ ማዕበል ሲሆን!

🌊አንዳንድ ጊዜ ሕይወት እንደ ማዕበል ነው፡፡ በሰላም ይሄዱ የነበሩ ነገሮች ልክ የተመካከሩ ይመስል በአንድ ላይ ይናጋሉ፡፡ የሁኔታዎች አልሳካ ማለት፣ ድንገተኛ ወጪዎች፣ የገንዘብ እጥረት፣ የጉዳዮች መጥመም፣ የሰዎች ክህደት፣ ስጋትን የሚፈጥሩ ሁኔታዎች መከሰት፣ የጤንነት መቃወስን የሚጠቁሙ ምልክቶች . . . ልክ እንደ ማዕበል በአንድ ላይ ይመጣሉ፡፡

🌊ስለዚህም መወገድ የሚችለውን ችግር በማስወገድ፣ የማይወገደውን ችግር ደግሞ ችግሩ የሚያስከትለውን መጨናነቅ ከእኛ በማስወገድ ነው የምናሸንፈው፡፡

🌊ችግር ካልተወገደ በስተቀር የተሳካ ሕይወት እንደሌለህ ስታስብ፣ ዘወትር የማይለወጥ ነገርን ስትታገል ትኖራህ፣ ሁል ጊዜ “ለምን?” በሚል ጥያቄ ውስጥ ትኖራህ፣ ተስፋ ቢስነት ይጫጫንሃል፣ እንዲሁም ሁሉም ሰው ከችግር ነጻና ደስተኛ፣ አንተ ብቻ ችግረኛ እንደሆንክ በማሰብ ድብርት ውስጥ ትገባለህ፡፡

🌪በተቃራኒ ግን የችግሩ ማዕበል ባይይረጋጋም አንተ ስትረጋጋ መነጫነጭን ታቆማለህ፣ የፈጠራ ብቃትህ ይወጣል፣ አዳዲስ መንገዶን ትቀዳለህ፣ ችግሩን ጠንካራ ለመሆን ትጠቀምበታለህ፣ ከችግሩ ባሻገር አልፈህ ከሄድክ በኋላ ለብዙዎች ደጋፊ ትሆናለህ፡፡

🌪ይህ የተለመደ የሕይወት አካል የሆነ ክስተት በእኛም ላይ ሲደርስ መረጋጋት ወሳኝ ነው፡፡ ማዕበል ይመጣል፣ ልክ እንደመጣ ደግሞ ይሄዳል፡፡ ነፋስ ከየት እንደመጣ ሳናውቀው ወደ እኛ ይነፍሳል፣ ወደየት እንደሚሄድ ሳናውቀው ደግሞ ወደሌላ ቦታ ይነፍሳል፡፡

ተንጋግቶ የመጣው ተንጋግቶ ይሄዳል፣
የችግሩ ማዕበል ባይረጋጋም አንተ ግን ተረጋጋ!!

ዶ/ር እዮብ ማሞ

መልካም እንቅልፍ❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
በዓሉ ግርማ እድር የለውም ፣ እቁብ የለውም ፣ ማኅበረ የለውም። ስለ ነገ አይጨነቅም። “ መስከረም በዓሉ ግርማ ” የነገረችኝም ይህንኑ ነው ፣ 'በዓሉ አሁንን ነው የሚኖረው። እሱ ብቻ ሳይሆን መሪ ወንድ ገፀባሕርያቱ የአሁን ሰው ናቸው። ኦሮማይ ውስጥ የምናነበው ፀጋዬ ኃይለማርያም የሚናገረው ነገር በዓሉን የሚገልጸው ሆኖ አግኝቼዋለሁ።
እንዳለጌታ ከበደ

📍ስለ ሕይወት እቅድ የለኝም ከመኖር ሌላ:: የሕይወት ግቡ እራሱ መኖር ነው::
ይህችም ውድ የሆነች ትንሽ ቁራሽ ሕይወት እንደአብርሃም ቤት የለኝ፣ እንደሙሴም መቃብሬ ሳይታወቅ መኖር፣ መጻፍ ፣ ሕይወትን በተስፋ ወደፊት እየኖርኩና ወደኋላም እያስተዋልኩ ስለ ኑሮ ቀርቶ ስለምጽፈው ልብወለድም ቢሆን እቅድ አላወጣም።
📖ደራሲው

📍« ስለሞት አስቤ አላውቅም። የሙያዬ ባህርይ ፣ ያለምንም ሥጋትና ጭንቀት በማያቋርጥ አሁን ሁኔታ ውስጥ የመኖር ልማድ አሳድሮብኛል። ስለ ወደፊቱ ለምን ይታሰባል ?” ትኩስ ዜና ፣ ትኩስ ሕይወት ! ሞት ለእኔ ምኔም አልነበረም ፣ ሆንም አያውቅም። ትኩስ ዜና ከማጣት ፣ አበቦችን ካለማየትና የቆንጆ ሴት እጅን ለመንካት ካለመቻል የበለጠ ስቃይና መለየት ምን ይኖራል ?” ሞት ትርጉም ሰጥቶኝ አያውቅም . . . እውን ነገር አሁን ብቻ ነው። አሁን አለሁ ፣ ደህና ነኝ ፣ እተነፍሳለሁ ፣ ውብ ኮከቦች እቆጥራለሁ ፣ ይበቃል።
📖 ኦሮማይ

በዓሉ ግርማ

ውብ አዳር ❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
🌞ጨርሶ አይጨልምም። ፀሐይ ስትጠልቅ፣ ጨረቃና ከዋክብት ይወጣሉ። ዘጠኝ በሮች ሲዘጉ አንዱ ይከፈታል። ዘጠኝ ወዳጆች ሲሄዱ አንዱ ይተርፋል። ፀሐይ ባትጠልቅ ጨረቃ አትታይም። ፈተና ካልመጣም የማናውቃቸው ሰዎች አሉ። ፈተናው የሚሰጠን የመጨረሻ ውጤት የቅርብ ያልነው ሩቅ፣ የሩቅ ያልነው የቅርብ መሆኑን ነው።

🌗ሁሌም ቢሆን ጥቁር ብቻ መስሎ ከሚታይህ ቀን ጀርባ የታዘለ ደማቅ ብርሃን አለ ሊገፈትሩህ ከበረቱ እልፍ ክንዶች ኋላ ሊያቀኑህ የቆሙ ልስልስ መዳፎች አሉ አንሸራትተው ከሚደፉህ ሃሳቦች ባሻገር በተስፋ ሞልተው የሚያቆሙህ ቅን ሀሳቦች ተሰልፈዋል ያላየኸው ነገ ብዙ አዲስ የህይወት ገፆችን ይዞ ይጠብቅሃል ካጎነበስክበት ቀና ትላለህ ሀዘንህ በሳቅ ይተካል ጉስቁልናህን ወዝ ይሽረዋል ይህ እንዲሆን ግን ነገን ጠብቀው ፣ ተስፋ አትቁረጥ ነገ ያንተ ሲሆን ብቻ አሸናፊ ነህ::

🌖ፀሐይ ስትጠልቅ ያልጠበቅናቸው ጨረቃና ከዋክብት ይወጣሉ። የማታ ብርሃኖች ዙሪያውን በደንብ ባያሳዩንም ለእግራችን መርገጫ ያሳዩናል። ሰማዩን በውበት ይገልጡልናል። የብርሃንን ዋጋ እንድናስብና እንድንሰስት ያደርጉናል። እንደ ፀሐይ እርግጠኛ የሆንባቸው ወዳጆች ድንገት ሊጠልቁ ይችላሉ። ያልጠበቅናቸው ደግሞ ብቅ ይላሉ። ጨርሶ አይጨልምምና።

🌕“ፀሐይ ስለ መጥለቋ ከተማረርክ ፣ ከዋክብትም ይሰወሩብሃል” ይባላል። ቢወጡም አታያቸውም ማለት ነው። ምሬት ዓይንን ያጨልማልና። "ከምንማረርባቸው ነገሮች ይልቅ..ልናመሰግንባቸው የሚገባን ብዙ ነገሮች አሉ።ሁሉም በግዜው ውብ ሆኖ መደረጉ አይቀርምና ፣ ለሆነልህ፣ ላለሆነልህ፣ ላለህ፣ ለሌለህ ዘወትር አመስግን ሁሌም ቢሆን ፈጣሪ ሁሉን በግዜው ውብ አድርጎ መስራት፣ ማከናወን ያውቅበታልና።

ውብ አሁን❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
🎄በመላው ዓለም ለምትኖሩ የክርስትና እመነት ተከታይ እህት ወንድሞቻችን እንኳን ለእየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል በሰላም አደረሳችሁ አደረሰን።

💛በአሉ የሰላም የፍቅርና የደስታ ይሁንልን🎄

❤️🏑 መልካም የገና  በአል 🏑


@ETHIOHUMANITY
@ETHIOHUMANITY
💎የሚዋኝ ይኖራል !!

መዋኘት የሚችል ሰው በውሃ ላይ የመንሳፈፍ ጥበቡን በደንብ ያውቀዋል። ውሃ ላይ ለመንሳፈፍ ጠንካራ መሆንን አይጠይቅም። ይልቅ ውሃ ደግ ሆኖ ከመስመጥ የሚታደገን ፈታ ብለን ስንጫወትለት ብቻ ነው። ውሃ ግትር ሰው አይወድም፤ እጅ እና እግሩን ከማያፍታታ ግትር ጋር ውሃ ልጫወት አይልም። በጉልበት እንሳፈፋለው ለሚል ሰውም ውሃ እርህራሄ የለውም

🌊አለን ዋትስ የተባለ አንድ ምሁር በአንድ ወቅት እንዲህ ሲል ሰምቸው ነበር " እምነት ልክ እንደዋና ነው። ዋናተኛ ከውሃው ላይ ለመንሳፈፍ ከፈለገ፤ እጁን ዘርጋ አድርጎ በነጻነት በውሃው ላይ ይወራጫል እንጂ፤ ላለመስመጥ ሲል ዉሃውን ልጨብጥ አይልም። ውሃውን ልጨብጥ ብሎ ግትር የሚል ሰው እጣ ፋንታው መስመጥ ብቻ ነው፤ በውሃ ላይ ለመንሳፈፍ ምንም ነገር መጨበጥ የለብንም ፤ ዋና መዋኘት እና ህይወትን መኖር በጣም ተመሳሳይነት አላቸው"

💎ብዙዏቻችን በህይወት ባህር ውስጥ የምንሰምጠው፤ ከኑሮ ጋር በቀላሉ መንሳፈፍን ስላለመድን ነው። እርግጥም ኑሮ እንደዋና ፈታ ብለው የሚኖሩት ባህር ነው። ግትር መሆን ውሃውን ለመጨበጥ እንደመሞከር ይሆናል። በህይወታችን ወስጥ በእኛ ቁጥጥር ስር የሆኑ ነገሮች አሉ፤ ሌሎች ከእኛ ቁጥጥር ውጪ የሆኑ ደግሞ እጅግ ብዙ ነገሮች ይኖራሉ። በኑሮ ውስጥ መስመጥ የሚከሰተው ታዲያ፤ ከእኛ ቁጥጥር ወጪ የሆኑ ነገሮች ላይ ግትርነታችንን ለማሳየት ስንሞክር ነው። መለወጥ የማንችለውን ነገር በጉልበት ለመለወጥ ስንሞክር፤ የመዋኘት ጥበቡ ጠፍቶናል ማለት ነው።

🌊አንድ ዋናተኛ ከሆዱ እየተሳበ እጅ እና እግሩን እያወራጨ ወደፊት ካልሄደም የመስመጥ እድሉ ሰፊ ነው። ኑሮም ላይ እንደዛው ትላንት ከቆምንበት ቦታ ካልተንቀሳቀስን፤ ውሃ ላይ እንደመቆም ይከብደናል። የሚገርመው የህይወት ሚስጢር በየተፈጥሮ ገንባር ላይ ተጽፎ መገኘቱ ነው፤ እርግጥ ነው ሶስተኛ አይን ኖሮት ላስተዋለው ሰው ብቻ የሚገለጥ ሚስጢር ነው።

💎ሌላው ብዙዏቻችን የሚያሰምጠን ዋነኛው ምክንያት ለለውጥ ያለን አመለካከት ነው። አሁንም ከግትረነት ጋር የተያያዘ ነው። ህይወት ወደድንም ጠላንም ባልታሰቡ ስጦታዎች የተሞላች ነች። እንደ ዋናተኛው በእምነት ፈታ ብለን ካልተንሳፈፍን በፍጹም ከለውጥ ጋር ተግባብተን ለመኖር አይቻለንም።

አቤል ብርሀኑ

ውብ ምሽት❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
🌗ሕይወት ከሁሉም ነገር በፊት የነበረች ናት ። ቆነጃጅት ምድር ላይ ከመወለዳቸው በፊት ቁንጅና ነበረች። ስለ እውነት ከመነገሩ ቀድማ እውነት ነበረች።

ሕይዎት በዝምታችን ውስጥ ታዜማለች ፣ በእንቅልፋችን ውስጥ ታልማለች። በዝቅታ በወደቅንበት ጊዜ እንኳን ቢሆን ሕይወት ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ትቀመጣለች። እኛ ስናለቅስ እርሷ በቀኑ ላይ ፈገግ ትልበታለች። የእሥራት ሰንሰለታችንን በምንጎትትበት ወቅት እርሷ ነፃ ናት።

🌗ብዙ ጊዜ ሕይወትን እንማራለን። ሆኖም ግን መራራና ጨለማ እኞው እንጂ እርሷ አይደለችም። ሕይዎትን ባዶ ናት እንላለን። ሆኖም ግን ነብሳችን በምድረበዳ የተቅበዘበዘችና ስለራሷ ብቻ እያሰበች መሆኗን ልብ አንልም

ሕይዎት ትልቅ ከፍ ያለችና ሩቅም ናት። ሰፊው የእይታ አድማሳችሁ እግሯ ስር አይደርስም ፣ ሆኖም ደግሞ ቅርብ ናት ፣ እስትንፋሳችሁ ከእርሱ ልብ ባይጠጋም የጥላችሁ ጥላ ግን ፊቷ ላይ ያርፋል። የጩኸታችሁ ማስተጋባት ለእርሷ እንደ መኸርና ፀደይ ንፋስ ነው።

🌗እንደ ነብሳችሁ ሁሉ ሕይወት ሕይወት ደግሞ ድብቅና ስውር ናት። ሕይወት ስትናገር ሁሉም ነፍሶች ቃላት ይሆናሉ ፣ ሕይዎት ስትናገር የከናፍራችሁ ፈገግታና የአይኖቻችሁ እንባ ሳይቀር ድምፆች ይሆናሉ። ሕይወት ስታዜም መስማት የማይችል ሲቀር ጆሮ ይሰጣታል ፣ ሕይወት ስትራመድ አይነስውራን እጆቿን ይዘው በአድናቆት ይከተሏታል።

📖 ( The Prophet )
ካህሊል ጂብራን

ውብ ምሽት❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
ምክር ለወዳጅ

📗ምክር ብትሰማ በነፃ ትማራለህ።ምክርን አልሰማ ብትል ግን በዋጋ እንደምትማር እወቀው።በዋጋ መማር ግን አድካሚ ደግሞም የሚያስመርር ነው።ብልህ ከሆንህ በሰው ከደረሰው ትማራለህ ሞኝ ከሆንህ ግን በራስህ ሲደርስ ትማራለህ።

📒በአመት የካብከውን በዕለት የምትንደው በቁጣህ ነውና አትቆጣ።ቁጣ አውቀህ እንዳላወቀ ለፍተህ እንዳለፋ የሚያደርግ በመልካም መሰረት ላይ የአገዳ ቤት የሚሰራ ነው።በገዛ እጅህ ዋጋህን እንዳታሳንሰው ቁጣህን ያዘው።

📕በወጣትነት ሁሉም ነገር ትክክል ነው ከሚል መመሪያ ውጣ።ሁሉንም ካላየሁ አላምንም አትበል።ሰምቶ ማመን ከተጎዱት መማር አስተዋይነት መሆኑን አትርሳ።የሰማንያ አመት እውቀትን ለመገብየት ግድ ሰማንያ አመት መኖር የለብህም።ሰማንያ አመት ከኖሩት በትህትና መጠየቅ ይገባሀል።

📗አይንህ የፊቱን ቢያይ ልብህ የኋላውን ያስብ።ነገ እንድትደርስ የትላንቱን አትርሳ።የምትሔድበት እንዳይጠፋህ የመጣህበትን አትዘንጋ።

📗ክፍት አይሙቅህ መልካም ነገርም ብርድ ብርድ አይበልህ።ለክፋት አቅም ካለህ ለበጎ ነገርም አቅም አለህና።ተግባርህ የምርጫህ ውጤት ነውና አስብበት።ክፋ ሰርተህ እንቅልፍ ሲወስድህ ሰይፍ ላይ መተኛትህን እወቅ።

📒ማግኘት ማጣት የኑሮ ተራ እንጂ አደጋ አይደለም።የተቀበልከው ያንተ ያልነበረውን ነው የተወሰደብህም ያንተ ያልሆነውን ነውና አታንጎራጉር።

📕ስትጠግብ የምትራብ ስትራብ የምትጠግብ አይመስልህም።ነገር ግን ሁሉም ይለወጣል።ዛሬ ያለኸው በጨለማው ከሆነ ቀጥሎ ብርሃን ነውና ደስ ይበልህ።ዛሬ ያለኸው በብርሃን ከሆነ ቀጥሎ እንዳይጨልምብህ ተጠንቅቀህ ያዘው።በመከራ ውስጥ ካለው ሰው በድሎት ውስጥ ላለው ቀጥሎ አስፈሪ መሆኑን አስብ።በእውነት ጥጋብህ እንዳለፈ ረሀብህም እንደሚያልፍ እመን።

📕የትላንትናውን ምሽት ስትይዝ አይነጋም ብለህ ሳይሆን ብርሃንን ተስፋ አድርገህ ነው።ከሌሊት ቀጥሎ ሌሊት አይመጣም።ከሌሊት ቀጥሎ ቀን ይሆናል።እንዲሁም ከዛሬ መከፍትህና ሀዘንህ በሀላ ታላቅ መፀጰናናት ይሆናል።

📗ሁሉም የራሱ ትግል አለውና እንደ እገሌ ምነው ባደረገኝ አትበል።ትዕግስት ስጠኝ ብለህ ለምን እንጂ።በዚህ አለም ላይ የሚታዘንለት እንጂ የሚቀናበት ሰው የለምና።

📒እገሌ ይናገርልኝ እገሌ መልስ ይስጥልኝ ከሚል ጥገኝነት ተላቀቅ።ጥቂትም ቢሆን በማታውቀው ሙያ ሰራተኞችን ተማምነህ ስራ አትጀምር።ስልጣን ሲሰጡህ መሪ እንጂ አለቃ አትሁን።ከፊት እየቀደምህ አስከትል እንጂ ከሀላ ሆነህ አትቅደም።

📕የመከራ ቀን ወዳጆችህን አትርሳ።የዛሬ ሰው ብቻ አትሁን።የትላንቱንም አስብ።አንገት የተፈጠረው ዞሮ ለማየት ነውና።

📗ታሪክን በጣም ወቃሽ አትሁን።አንተም በታሪክ ፊት ነህና ተጠንቀቅ።ያለፋት ተመልሰው መጥተው ያበላሹትን ማበጀት አይችሉም።አንተ ግን እድል አለህና እወቅበት።ታሪኬ እንዲያምር ብለህ አስመሳይ ፃድቅ አትሁን።ዛሬ በቅንነት የምትሰራው ግን ለታሪክህ ይተርፋል።ስራህን ስራ እንጂ ለስምህ አትኑር።አለም እንደ እቅድህ አይደለምና።

📒ሰዎች ሁሉ እንደ እኔ ካላሰቡ ብለህ አትጥላቸው።ሰው ላንተ ፈቃድ የተፈጠረ አይደለም።ደግሞም ነፃ ፈቃድ ያለው ፍጡር ነው።ነፃ ፈቃዱን እያከበርክለት ወደ እውነት ምራው።ከጠባብ ድንኳንህ ውጣ።

📕ዛሬ ዋሽተህ ማምለጡ ድል ይመስልሀል።የታወቀብህ ቀን ግን በውሸትህ ያመነህ ሰው በእውነትህ ግን አያምንህምና አትዋሽ።ውሸታምና አመንዝራ ተለውጠው እንኳ ቶሎ የሚያምናቸው አያገኙምና ከውሸት እራቅ።

📕እጅግ ግልፅነት እብድ ያደርጋል።እጅግ ዝምታም ወዳጅ ያሳጣልና ንግግርህና ዝምታህ በቦታው ሲሆን ውበት ይሆናል።

📕የእኔ መናገር ምን ይለውጣል?ብለህም ስህተትን አትለፍ።የእኔ አስተዋጵኦ ምን ይጠቅማል?ብለህም ስጦታህን አትጠፍ።

አሸናፊ መኮንን

ውብ አዳር❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
7⃣ ዐይን-ገላጭ የጃፓኖች የሕይወት ጭብጥ!

1⃣ IKIGAI

፨ በሕይወት ውስጥ ዓላማህን ድረስበት።
፨ ሰርክ ማለዳ የመንቃትህን ምክንያት እወቅ።
፨ አስፈላጊነትህን (ለዓለም)፣ ጥንካሬህን፣ ዝንባሌህን የተወዳጀ የሆነ ነገር አስስ። ይሄ ነው ለሕይወትህ ትርጉም የሚሰጣት።

2⃣ SHIKITA GA NAI

፨ መለወጥ የማይቻልህን ነገር ተወው፣ ልቀቀው።
፨ ካንተ ቁጥጥር ውጪ አንዳንድ ነገሮች መኖራቸውን እና ያም ያለ መሆኑን ተረዳ። ሂድ እና መቀየር በምትችለው ነገር ላይ ትኩረት አድርግ።

3⃣ WABI-SABI

፨ በጎዶሎነት ውስጥ ሠላምን አግኝ።
፨ ራስህ እና ሌሎችን ጨምሮ በሕይወት ውስጥ ምንም ነገር ፍፁም አለመሆኑን ተገንዘብ።
፨ ለእንከን-የለሽነት ከመትጋት ይልቅ ሕይወትን ልዩ በሚያደርጋት ጎዶሎነት ውስጥ ደስታን አጣጥም።

4⃣ GAMAN

፨ በፈታኝ ጊዝያቶች ክብርህን ጠብቅ።
፨ ፈተና ውስጥ እንኳ ብትሆን የሥሜት-ብስለትህን እና ራስ-ገዝነትህን አሳይ።
፨ ታጋሽ፣ ፅኑ፣ ተረጂ ለመሆን እንዳትዘነጋ።

5⃣ OUBAITIORI

፨ ራስህን ከማንም ጋር እንዳታወዳድር።
፨ ሁሉም የተለየ ጊዜ-ቤት እና ልዩ ጎዳና አለው።
፨ ራስህን በሌላው ለመለካት ከመሞከር ይልቅ በራስህ መሻሻሎች ብቻ ማተኮርህ አስፈላጊ ነው።

6⃣ KAIZEN

፨ ሰርክ በሁሉም የሕይወትህ ክፍል ውስጥ መሻሻሎችን ፈልግ!
፨ ጥቃቅን ለውጦች እንኳ መጠራቀም ችለው በጊዜ ሂደት ውስጥ ግዙፍ ለውጥ ያመጣሉ።

7⃣ SHU-HA-RI

"ተማሪዎቹ ሲዘጋጁ መምህሩ ይገኛል። ተማሪው የምር ዝግጁ ሲሆን ግን መምህሩ ይሰወራል።"
―Teo Te Ching

👉 (እንዴት) ስለመማር እና በዘዴው ስለመጠበብ ማወቂያ መንገድ ነው። ከዕውቀቱ ለመድረስ ሶስት ደረጃዎች አሉት።

፨ SHU: የአንዱን አዋቂ (master) ትምህርት በመከታተል መሰረቶቹን መቅሰም!
፨ HA: ከአዋቂው የተቀሰመውን ትምህርት ከሙክረት በማዋሃድ የተግባር ልምምድ መጀመር።
፨ RI: ይሄ ደረጃ የሚያጠነጥነው ፈጠራዎች ላይ እና ትምህርቶቹን በተለያዩ መስኮች የመተግበር ችሎታ ላይ ነው።

ውብ ቅዳሜ❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
2024/09/27 11:24:09
Back to Top
HTML Embed Code: