Telegram Web Link
😂
ኮንዶሚኒየም መኖር ችግር ነው! ሁሉም ዶሮና በጉን በሩ ላይ አስሮ
ብሎካችንን ኤልፎራ አስመስሏታል። እኔም ትናንት ሚስቴ በግ ካልገዛህ
እያለች ስትነተርከኝ ጥቂት ብር ይዤ በግ ልገዛ ብወጣ አንድ ቀውላላ በግ
ነጋዴ ሁለት ፊታቸው ላይ ከባድ ድብርት የሚታይባቸውን ከሲታ በጎች ይዞ
ቆሞ አገኘሁና ጠጋ ብዬ
«ልትሸጣቸው ነው?» አልኩት
«እና ሐገር ላስጎበኛቸው ነው ካገሬ ይዣቸው የወጣሁት?» አለኝ
«እንደው ኩነኔ አይሆንም እነዚህን መግደል?» ስለው ፈጠን ብሎ
«አንቀህ ነው እንዴ ምትገድላቸው?» አለኝ
«አይ ያው በቢላም ቢሆን ...» ብዬ ሳልጨርስ
«ወንድሜ ካሳዘኑህ ውሰድና በጉዲፈቻ አሳድጋቸው» አለኝ
«እሺ ስንት ነች እቺ?» አልኩት ወደአንዷ እየጠቆምኩ
«በግ ታውቃለህ ማለት ነው። በጣም አስተዋይ በግ ነች እሷ» ብሎ
ጀርባዋን መታ መታ ሲያደርጋት ወደጎን ፍንግል አለችና አቧራዋን አራግፋ
ተነሳች።
«እኔ አስተውሎቷ ምን ይሰራልኛል ላስተምራት አይደለም እኮ ምወስዳት»
ስለው
«ሁለት ሺ ብር ክፈል» አለኝ
«ሁለት ሺ ብርማ አታወጣም»
«በርግጥ ላታወጣ ትችላለች ነገር ግን እኔ ሁለት ሺ ብር ነው
የሚያስፈልገኝ»
«ቀንስና ልውሰድልህ» አልኩት
«አይ ወዳጄ በጓን ግን አይተሃታል? ውስጠ ወይራ እኮ ነች። መፍዘዟን
አትይ። በዚያ ላይ በእንክብካቤ ነው ያደለብኳት»
«ጭራሽ ደልባ ነው እንዲህ የከሳችው?»
«አዎና! በርግጥ እኔ ስብእናዋ ላይ ነው የሰራሁት። በጥሩ ስነምግባር
ነው ያሳደግኋት» አለኝ ቆፍጠን ብሎ። ሳቄን ለመቆጣጠር እየሞከርኩ
«አንድ ሺ ብር ትሸጥልኛለ ...?» ብዬ ሳልጨርስ
«ውሰዳት!» አለኝ በደስታ ተሞልቶ።
ምነው ዝም ባልኩ ብዬ በይሉኝታ አንድ ሺ ብር ሰጥቼው በጓን ይዤ ልሄድ
ስል መራመድ አቅቷት በቀስታ ስታዘግም
«ቃሬዛ ቢኖርኮ ደግ ነበር» አለኝ ሰውዬው በጉን በሃዘን እየሸኘ።
ተበሳጭቼ ዝም ብዬው ስሄድ
«ወንድሜ እንደው ለነፍስ ትሆንሃለች መጀመሪያ የህክምና እርዳታ
አርግላት» አለኝ
መንገድ ላይ በጓን ያየ ሁሉ ከንፈሩን እየመጠጠ ያልፋል። አንዳንዱ እኔን
እያየ አንገቱን በሃዘን ይነቀንቃል። በግ ላርድ ሳይሆን እንደአብርሃም ልጄን
ልሰዋ ይዤ እየሄድኩ ነው ያስመሰሉት። ሽምቅቅ እንዳልኩ ቤት ደረስኩ።
ሚስቴ በጓን እንዳየቻት
«ምንድነው ይዘህብኝ የመጣኸው?» ብላ ጮኸች። በጩኸቷ ከኔ ይልቅ
የደነገጠችው በጓ ነች። አይኗን አስለምልማ መሬት ወደቀች! የመጀመሪያ
ደረጃ እርዳታ ላደርግላት ሞከርኩ። አልነቃ ስትለኝ በአፌ ትንፋሽ ልሰጣት
ሳጎነብስ ሚስቴ
«በዚህ አፍህ እኔ ከንፈር ጋር ድርሽ እንደማትል እወቀው!» ስትለኝ ቀና
ብዬ መጨረሻዋን ማየት ጀመርኩ ..
ውይይ! አረፈች! በጣም የሚያሳዝን ሁኔታ ነው የገጠመኝ ጎበዝ።
ለሚስቴ «ያ ሙታን አስነሳለሁ ሚለው ነብይ ጋር ይዘናት እንሂድ ይሆን?»
ስላት
«እሱ አክስቱ ሞታ ክፍለሐገር ሄዷል» አለችኝ። እሺ ምን ተሻለኝ ጓዶቼ?
«ቆይ ግን ...የግድ ስጋዋን ለመብላት እኛ ልንገድላት ይገባል እንዴ? ያው
ሞት ሞት ነው። በቢላም ሞተች በድንጋጤ ያው መሞቷ አይቀርም!» ስል
ሚስቴ ሶስት ግዜ አማትባ «በል አውጥተህ ጣል» አለች።
እኔ ግን ተስፋ አልቆረጥኩም! እቺን በግ እኮ ስጋዋን ፈልጌ ሳይሆን
እንደበግ እንድትተውን ነው የገዛኋት። አክተር ደሞ አይሞትም
ኦህህህህህ! ተመስገን!
ነቅታለች ጎዶች «እልልልል ...» (አሉ እትዬ ዘርፌ የቤት እቃ (ማማሰያ
ሳይቀር) እየሰረቀ ያሰለቻቸው ልጃቸው ሲታሰር)
እንዲህ ነው እንጂ በግ! ዝም ብሎ መሞት አለንዴ? እኛ ሳንፈቅድላትማ
አትሞታትም! አልኩ ለሚስቴ (አንዳንዴኮ እንደ አፍሪካ መሪዎች ሚያደርገኝ
ነገር አለ። ተመልሳ ሳትወድቅ ብሬክ ላርጋት።

© የሀገር ጥበብ

@Wegoch
@Wegoch
@Mahletzerihun
#not_polytricks_its_just_a_ወግ
...ትናንት ለአንድ ጉዳይ ወደ 6 ኪሎ ግቢ ሳመራ..በስንት ጊዜዬ አራት ኪሎን
ረገጥኳት..ከዛ በአይኔ ዙሪያ ገባውን ስቃኝ የቀድሞ ባሻ ወልዴ ችሎት
አደባባይ ገደማ ቤተሞግዚቱ በር ላይ ያለችውን peacock እንዳየው
ለሰፈሩ የእንግዳነት ስሜት ተሰማኝ...የዛ አካባቢ ድባብ ፈፅሞ መለወጡ
ገባኝ...ትንሽም አመታት ቢሆን የኖርኩባት እሪ በከንቱ ናፈቀችኝ...መከላከያ
ጋራዥ፣ ግንብ [ዝንብ] መደዳ፣ቱሪስት ጀርባ፣ ፣ሁለተኛ ፖሊስ ጣቢያ፣እሪ
በከንቱ ድልድይ፣በርጌስ ክሊኒክ፣ white house፣ ሠራተኛ ሠፈር፣ለ free
wifi ብርድ የጠጣሁበት ማዕከላዊ ስታቲክስ፣ ከፍ ብሎ ኢንሪኮ፣አሮጌ
ቄራ፣ ናፓሊዮን የሚባል ጓደኛዬ በፍቃዱ ሁሉም ሀሳቤ ላይ ለደቂቃ
ተመላለሱ.....ከዛ መለስ ብዬ ያቺን Giant peacock በተመስጦ
አየዃት..መግቢያው እጅግ አሸብርቋል....ምናልባትም አናቷ ላይ ለጌጥ
አምፖል የተሰካባት አነስተኛ የሳር ጎጆ ነገር ብትኖር የቃልቻ ደጅ ይመስል
ነበር...በራሴ ሀሳብ ፈገግ አልኩ...ከዛ ወዲያው አባባ ታምራት ትዝ
አለኝ...የት ገብቶ ይሆን እሱ ሰውዬ አልኩ? ያ ሁላ የአንድ ሰሞን ትሪኩ ትዝ
አለኝና በውስጤ ሳቅኩ...ምን አይነት ብልህ ሰው ቢሆን ነው እንደዛ
የተጫወተብን አልኩ ምን አይነት ገራገር እና ምስኪን ብንሆን ነው
አልኩ...ግን ወዲያው ምቀኝነታችን ትዝ ሲለኝ ሀሳቤን ቀየርኩ፣...በእውነቱ
አንዳንዴ የሰዎችን ድክመት እንደመጠቀም ረቂቅ ብልህነት የለም ...እና
አባባ ታምራትን በዚ ብልሀቱ አደንቀው ነበር ከልቤ...ለታዳሚዎቹ ክንፍ
እየተከልኩ ወደ አሜሪካ አስበርራችሁዋለው ይላቸው የነበረው ጨዋታ
ትዝ ሲለኝ መልሼ ፈገግ አልኩ...እሱን ተከትሎ ወዲያው ደሞ ብልፅግና
የሚለው ሀሳብ ከየት መጣ ሳልለው ድንገት ክስት አለልኝ
...ከ40 አመት በዃላ አለም ላይ 2 ሃያላን ሀገራት ይኖራሉ አንዷ
ኢትዮጵያ ትሆናለች!!...ማን ነበር ይሄን ያለው በውል ትዝ አይለኝም
...እና ዞሬ ዞሬ ከሀሳቤ መለስ ስል አብሮኝ ለነበረው ጓደኛዬ እንዲህ
አልኩት...ለምን እንደሆነ አላቅም ይሄን በርና የፒኮኮቹን ድባብ ምናምን
ስታይ የሆነ የቃልቻ ግቢ ነገር አይመስልህም ስለው ከተቀመጠበት በሳቅ
ወደቀ ...ምን እንዳሳቀው ግን ለማወቅ አልጓጓሁም...ከፈለጋቹ
እናንተው ጠይቁት

© Samson Ali

@wegoch
@wegoch
@Mahletzerihun
ልጅ ሆኜ _
ነፍሴን የዳርኩለት የልጅነት ሙሽራዬ እርሱ ነው ፤ ጧት ደጁ ልሄድ ሳስብ ሌሊቱ በቅጡ እስኪነጋ ልቤ ተሰቅሎ አሸልባለሁ ፤ ሊነጋጋ ሲል በርግጌ ተነስቼ ፊቴን አብሼ ብጣሽ ነጠላዬን አንገቴ ላይ አስሬ የሚያምር ንጋት ላይ የተኳለ ውበት የእርሱ ነው እያልኩኝ ፤ ወደቤቱ የማዘገም የማለዳ ወፍ ነበርኩ ።
ታዳጊ እያለሁ_ የሆነ ቀን እናቴ ሞተችብኝና ከሁሉ ነገር ስጣላ እርሱም አልቀረለትም ። መጋረጃ ጋርደው ያስቀመጡት ሳጥኗ ፊት በቸልታ እግሬን አጣጥፌ ተቀምጬ ካድኩት " የራስህን እናት ሞት ከማየት አንተ ቀድመኻት የሞትከው ራስ ወዳድ ብትሆን ነው..... እኔን ቁጭ አድርገኸኝ እናቴን ስለወሰድካት የሰጠኸኝ ህመም መቼም
የሚድንልኝ አይደለም ብዬ ፤ አቄምኩ አኮረፍኩ ። እና ከዚያ በኋላ መቃብሯን ላይ ስሄድ ያሳደገኝ ደጁን ትቼ በጓሮ እናቴ ጋር ደርሼ የምመለስ አኩራፊ ሆንኩኝ ስጎረምስ_ በእርሱ ምክንያት በሄሮድስ ትዕዛዝ ያለቁ ህፃናትን አስቤ የምበሳጭ ፣መስቀል ተሸክሞ ሲሄድ አግኝቶት ምን ያንቀረፍፍኻል ስላለው ብቻ ዘላለም መባዘንን ስለፈረደበት ከርታታው ይሁዲ የምብከነከን ፣ ብስጩ ሆንኩ ከዚያ_ አኩርፌ ተበሳጭቼ ከርሱ ተለይቼ ከደጁ ርቄ ፣ እየኖርኩ ባለሁበት ፣ ሌሊት ከእንቅልፌ ነቅቼ የምሰማው ምህላ አንጀቴን በናፍቆቱ የሚያንሰፈስኝ ፣ ፋሲካ ሲደርስ ህማማቱ ፀሎተ ሃሙስ ላይ እንግልቱ ነፍሴ ድረስ የሚሰማኝ ፤ ለስቅለቱ በኪራላይሶ መሃል ጎንበስ ቀና የምልለት ከክህደት ተመላሽ አማኝ ሆንኩኝ አሁን _ በቸልታ የተሞሉ ቀናቴ መሃል በልጅነቱ ስላደረጋቸው ታዓምራት አስባለሁ ። ቀራኒዮ ላይ ግራና ቀኙ የተሰቀሉ ወንበዴዎች ልጅ እያለ ከእናቱ ማርያም እና ከእጮኛዋ ዮሴፍ ጋር ሲሰደድ አግኝተውት ኋላ ላይ በግራ የተሰቀለው እንዝረፋቸው ሲል በቀኝ የተሰቀለው አይነውሃቸውን አይቶ እዝነት ልቡን ጎብኝቶት አንዝረፋቸው ብሎ ጭራሽ ጨቅላውን እንኮኮ አድርጎት ረጅም መንገድ ሸኝቷቸው ተሰናብቷቸው ሲሄድ የልብሱ ጠረን ተቀይሮ እርሱን እየጨመቀ ይሸጠው ስለነበር እንኮኮ ካለው ጌታው ወደ ልብሱ ስለተጋባ አልባስጥሮስ ሽቶ የማስብ ሆንኩ .... አለ አይደል " በዘረፋው ቀጥሎ መጨረሻው ቀራኒዮ ከሚሆን ሽቶውን እየጨመቀ አይሸጥም ነበር " እያልኩኝ ወይም ደግሞ በረሃ በስደት የደረሱባቸው የሄሮድስ ወታደሮች እንዳያዩዋቸው በእናቱ እቅፍ ሳለ ሰንጥቆት የተደበቁበትን ዛፍ ማን ቆርጦት ይሆን የምል ፤ ካልሆነም በአናጢነት ዘመኑ
የጠረበው ወንበር ላይ ማን ተቀመጠ? አልጋውስ ላይ ማን ፍቅር ሰራ? ምናምን
ብዬ የምጠይቅ ... እስከ ግራ መጋባቴ ርቄው እንኳን የሚናፍቀኝ ፣ እብሪተኛውን ልቤ በፍቅሩ የሚያንሰፈስፍ እየሱስ ልደቱ ነበር።

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Elssa Mulugeta
ምናገባቸው ቆይ! ስለኔ መክሳት መጥቆር መዘነጥ መጎሳቆል! እንዴ??

ጓዳቸው ውስጥ ያልፈቱት የራሳቸው ቋጠሮ ተከምሮ እያለ የምን የሰውን መፍታት ነው?
አላወራም ብዬ እንጅ ... የራሴን ጉዳይ አረረም ጣፈጠም ራሴው ልያዘው ስለሰው ምን አስፈተፈተኝ የራሴ ያረረው ድስት እያለልኝ የሰው ምን አማሰለኝ ብዬ እንጅ አናውቅም እንዴ? ስንት ድስት እንዳረረባቸው? ስንት ነገር ከህይወታቸው እንደተደፋባቸው?
ስንቱስ በየቤታቸው ጨለማ ታቅፈው ውጭ ውጭውን ብቻ ደምቀው እንደሚታዩ??

እንዴ በቃ ምን አገባሽ.... አጣው ነጣው አይደል? ምንሽ ተነካ እንች? ከቻልሽ ነይ አፅናኚኝ ወይ ደግፊኝ ካልቻልሽ አፍሽን ዝጊ! እንዴ???

ወደኩ አይደል? የጀመርኩት ስራ ህይወት ፍቅር ምናምን ሁሉ ገደል ገባብኝ አይደል? እና ምን ይጠበስ? ዳር ሆነህ ምን ወሬ አራገበህ? ምን በየቡናው ላይ ግዜ ማሳለፍያ አደረገህ? ምንስ መንገድ ላይ ስታየኝ አፍህን አስያዘህ? ለምን መጥተህ የምትረዳኝ ነገር ካለ አትጠይቀኝም ወይ አታወያየኝም? አለዚያ አፍህን ዝጋ! እንዴ? ሰው እንደራሱ ሆኖ መኖር አይችልም እንዴ? ጎበዝ!

መውደቁ ሳይሆን የሰው ምላስኮ ነው እየገደለን ያለው. ቢዝነስ ጀመረክ በውሀ ተበላህ..እንበል.... ከክስረትህ በላይ አላስቀምጥ የሚልህኮ የማያከትም ቡናቸውን እያንቃረሩ ወሬ የሚለቃቅሙ የወሬኞች ቀደዳ ነው.......
" የያዘችው ስራኮ በቂዋ ነበር ስትስገበገብ ነው እንጅ!ይበላት?"...." አሁን የኮራ የደራ ስራዋን ትታ ምን አንዘጠዘጣት...አወይ ሰው ? ስግብግብኮ ነው... አይ በቃኝን አለማወቅ ...ምፅ"...... ስራዬ ያስደስተኝ አያስደስተኝ ..... ማገኘው ገንዘብ ይብቃኝ አይብቃኝ ምን አባሽ የምታውቂው ነገር አለና ነው? ተራራው አናት ላይ ተሆኖና ተራራው ግርጌ ተሆኖ ከተማ እኩል ይታያል እን ዴ???

ጥቁርቁር ስትይ... ልብስሽ ላይሽ ላይ ሲውለበለብ... ምድረ አስመሳይ ከንፈር መጣጭ...ሁላ መላምቱን ያዝጎደጎደዋላ.... ከሰላምታ በኋላ ....." ምነው ከሳሽ? አመመሽ እንዴ? ከባልሽ ጋ ሰላም ናቹ?.. ምፅ አይዞሽ " ዞር ይልና ከቢጤው ጋ. ገጥሞ..... አርግዛኮ ነው?? ..... ቧሏልሽ ይደበድባታል አሉ ብታይ ...ባርያ በያት ምን ይች ሚስት ነሽ ቱ!...."
ኧረ በወላዲቱ! ምን የምታውቀው ነገር አለና ነው እንዲ የምትደሰኩረው? ከኔጋር የምትኖር አይመስልም እንዲ ስታወራ ለሚያይህ?
አንዱኮ ነው ( በለው! እዚው ጀመረችው እንዳትሉኝ እንጅ!!) ጎረቤቱ ቲቪ ይገዛል ከዛ ልጁ አላስቀምጥ ትለዋለች "አባ ቲቪ ግዛ? እነማሙሽ ተገዝቶላቸው የለ?" ሰውየው ከየት ያምጣ.... እንደምን ብሎ እቁብ ብድርም አድርጎ ገዛ!... ተወራ ስለአዲሱ ቲቪ! እንደጉድ!..... ከወራት ቡሀላ ጎረቤቱ ዲሽ ይገዛላችዋል... መቼም የልጅ ነግር ሁሌ አምጣ ነው ግዛ ነው.. ... ንዝንዝ!..... ሰውየው ጨነቀው...... ብድሩንኳ ሳይከፍል...... በስተመጨረሻ... ቲቪውን ሸጦ ዲሹን ግዝት! እና ምን ያርግ?? ልጁ በዚ ሚስቱ የሰፈሩን ሀሜት ሰምታ በዚ ስትነዘዝንዘው ምን ያድግ.??

ኧረ ተው ተው ተው ግን??


ደሞኮ ወረቱ ሲያልቅ አብረው ያሙኝ ይጣሉና እም! ያኔ ያወሯት እንድም ሳትቀር ጆሮዬ ትደርሳለች! የፈሷት ሳትቀር! አቤት ግን በቃ መበላላት ነው ስራችን? ምናለ ሁላችንም የየራሳችንን ድስት ብናማስል?

በቃ ከሳች አይደል.. እሰይ እንኳን ከሳች ከቻልኩ ምክንያቱን ጠይቄ ልረዳት ሞክራለው ካልሆነ ዝም! ዝምን ማን ገደለው?..... ከሰረ አይደል? እንኳን ከሰረ? የሚሰራ ሰው ይከስራል...መልሶ ያገኘዋል ምን እዚ ወሬ አራግባለው....

ኧረ ወገን! ተው መበላላቱ ይቅርን? ተው ተው ግን?


ተፃፈ by aggie

@wegoch
@wegoch
@paappii
ገ ' ና ነው


፡ እስካሁን "እስክቢርቶ ለምን ያገለግላል?" ብሎ የጠየቀኝ የለም እንጂ መልሴ የሚሆነው አንደኛ ስለሷ ለመፃፍ ፡ ሁለተኛ ስለሷ ለመፃፍ ፡ ሶስተኛ ስለሷ ለመፃፍ ነበር የሚሆነው። ነገር ግን ስለሷ ልፅፍ ብዕሬን ሳነሳ አቡጊዳ ያልተማረ መሀይም እሆናለው። ማለት ምፈልገውን ብዬ አላውቅም።
ገና ከበአላት ሁሉ ደስ የሚለኝ በአል ነበር የዛሬን አያርገውና ። ዛሬ ግን በአል የተባለ ነገር ያስጠላኛል። ለምን ብትሉኝ ለበአል ሰው ሁሉ ከቤት አይወጣም። እኔን ያስጨነቀኝ የሰው ከቤት አለመውጣት አይደለም። ከፈለገ ዝንት አለም ከቤት አይውጣ።የኔ ጉዳይ አይደለም። እኔን ያስጨነቀኝ ለበአል ከቤት ከማይወጡት መሀል የብዕሬ ንግስት አንዷ ስለሆነች ነው። ዛሬ ግን ፀሎት ሳላደርግ ፡ ስለት ሳልሳል ፀሎቴ የደረሰ ስለቴ የሰመረ ያክል ተሰማኝ። ምክንያቱ ደሞ የስልኬ መስታወት ላይ "ንግስቲቱ እየደወለች ነው" የሚል ምልክት እያየው ስለሆነ ነው።
"ሄሎ ቤኪ እንዴት ነህ ፤ እንኳን አደረሰህ ፤ ለነገሩ ቀድመኸኛል።"(ቀድሜ የእንኳን አደረሰሽ መልእክት ልኬላት ነበር)
ይገርማል እኔ ከደወለች እንዲ እላታለው ብዬ ለቀናት የማስበውን ነገር እሷ በሰከንዶች ውስት እንደ ቀላል ነገር ትናገራቸዋለች።
" እንኳን አብሮ አደረሰን በአል እንዴት ነው " አልኳት
" በአል ባክህ ይደብራል ፤ በአል በአል አልመስልሽ ብሎኛል" አለችኝ። በመሀል ከስልኩ ራቅ ብላ ስትስቅ እሰማታለው ፡ በምንና በማን እንደምትስቅ አላውቅም ነገር ግን ዝም ብዬ አብሬአት እስቃለው።
የኔን ወሬ አልጠበቀችም " እኔ ምልህ ቤኪ እዮብ ደውሎልኝ ' ቤተ ክርቲያን መርሀ ግብር አለ ነይ ' ብሎኛል አብረኸኝ አትሄድም?" አለችኝ። " ወደ ሞት እንኳን ቢሆን በደስታ እንደምሄድ ማን በነገረሽ " አልኩኝ በውስጤ። አፌ ግን የሚያወራው ሌላ ነበር " ስንት ሰአት ነው?" አልኳት። " ከሌሊቱ 9 ሰአት" ብትለኝ እንኳን እንደማልቀር እያወኩት ለምን ሰአት እንደምጠይቃት አልገባኝም። " ሰባት ሰአት ነው ያለኝ "አለችኝ። ሰአቴን አየሁት 4:30 ይላል የሰአቱ እርዝመት እያሰብኩኝ " በቃ ስቶጪ ደውይልኝ" አልኳት። " እሺ ቻው " አለችኝ። ቻው ከምትለኝ ዝም ብላ ጆሮዬ ላይ ብትዘጋብኝ በተሻለኝ ነበር። ሰአቱ እንደምንም እያዘገመ ደረሰ ተገናኘን። ከዚ ቡሀላ ቤ/ክ እስክንደርስ ድረስ ያወራነውን አልፅፈውም። ምክንያቱም ለሌላ ሰው ተራ ወሬ የሚመስል፤ ምንአልባትም ለሷም ጭምር ተራ ስለሚመስል ለኔ ግን ጥዑም የመላዕክትን ዝማሬ የምሰማ ያክል ይሰማኝ ነበር። ከአንደበቷ የሚወጡትን ቃላት ወድቀው እንዳይሰበሩ የምጠብቃቸው ይመስል አፍ አፏን እያየው እመሰጥ ነበር። እየሄድን ያለነው እግር መንገድ ዳገት ከመሆኑም በላይ የዘንድሮ ፀሀይ ተጨምራበት እያነደደችን ነው። በጣም ደክሟታል እኔም ደክሞኛል ድካሜ ግን ለኔ ያን ያህል ቦታ አልነበረውም። የሚታየኝ የሷ ድካም የሚሰማኝ የሷ የድካም ትንፋሽ ነበር ። ጀርባዬ እንደዛ ደክሞት እንኳን እሷን ለመሸከም ይጓጓ ነበር። አፌ ግን እንኳን ልሸከምሽ ሊላት አይዞሽ የሚል የማፅናኛ ቃል እንኳን አላወጣ አለ። በዚ ሰአት ስልጣኑና ችሎታው ቢኖረኝ አፌንና ልቤን ቦታ አቀያይራቸው ነበር። ለነገሩ ከበሮ በሰው እጅ ያምር ሲይዙት ያደናግር አይደል ሚባለው ልቤም ቢሆን የአፌን ቦታ ቢይዝ አንዲት ቃል ትንፍሽ የሚል አይመስለኝም። መንገዱ ያን ያህል እርቆ በምን ፍጥነት እንደደረስን አልገባኝም። ለምን ቶሎ ደረስን አላልኩም ፈጣሪ ነውና ፤ እንኳን ደረስንም አላልኩም ከሷ ጋር ሁኜ ምንም ነገር ማየትም መስማትም ስለማልፈልግ። ስንደርስ ፀሎት እየተደረገ ነበር ። ፀሎቱ እንዳለቀ ፕሮግራም ተጀመረ።ከገባን ጀምሮ እያወራን ስለነበር ከፕሮግራሙ ሁሉ የሰማችው (እኔ ምንም አልሰማሁም) አንዱን ብቻ ነበር። አንዷን ፕሮግራም እንኳን እንዳልሰማ ትከሻዬን ተደግፋ የኔን ጆሮ ሰርቃ ብቻዋን የእግዜርን ማዕድ ትኮሞኩማለች። እኔ ግን በዛ ሰአት ማስበው ' ትከሻዬ ይቆረቁራት ይሆን ' 'ከፍ ብዬባት ለአንገቷ አልተመቻትም ይሆን ' እያልኩ አስብ ነበር። የሷ አስተኛኘት ግን በጥጥ የተሰራ ትራስ ላይ የተኛች ነበር የሚመስለው። እንደተመቻት ሳውቅ ዘላለም ትከሻዬ ላይ ብታርፍ ብዬ ተመኘው። ብዙ ጊዜ ምኞቴ አይሳካልኝም ። ገና ከማሰቤ ትምርቱ አልቆ ከትከሻዬ ተነሳች። ተናድጃለው ነገር ግን በማን እንደተናደድኩ አላውቅም።
" በሷ ይሆን "
" አይ በሷማ አይሆንም ፤ ይሄን እንደጦር የሚዋጋ ትከሻህ ላይ ስለተንተራሰች እንደውም ልታመሰግናት ይገባል "
" ታዲያ በአስተማሪው ነው?"
"ስታስበው ይሄ አስተማሪ የማይደክመው ሮቦት ይመስልሀል"
" በቃ ጊዜው ነው ያናደደኝ "
" ሰውዬ ከጊዜ ጋር ባትጣላ ጥሩ ነው ፡ ደሞስ ለዚህ እራሱ ያበቃህ ጊዜው አይደል"
ጭንቅላቴ ውስጥ ሀሳቦች እርስ በርሳቸው እየተጋጩ እራስ ምታት አስያዙኝ። በሀሳቦች ተከብቤ ሳለ አንድ ሰው ደወለላት። አነሳችው ፡ አንስታው ያወራችውን በጠቅላላ ሰምቻለው ነገር ግን ለሚያየኝ ሀሳቤ ሁሉ ፕሮግራሙ ላይ ያለ ይመስል ነበር።የምታወራበት ሰአት እየጨመረ በሄደ ቁጥር ቅናት ይሁን ምን ውስጤን ይበላኝ ጀመር ። በዚ ቢበቃ እሰየው ብሎ ብሎ ካርድ ላከላት። " ቤኪዬ ካርድ ተላከልኝ ስንት ትራንስፈር ይደረግልህ?" አለችኝ እየሳቀች። እሷ በደግነት እንደሆነ አውቃለው ፤ ውስጤ ግን " ደሞ እሷን ማሳቁ አንሶ ጭራሽ የሱን ብር ልትቀበል ፡ ቢቻልህ ያለበት ሂደህ የፈላ ዘይት ፊቱ ላይ በደፋህበት " ይለኛል። ይህንን ንዴት ግን የኔ ፊት አያውቀውም። ዝም ብሎ በሳቀች ቁጥር አብሮ ይስቃል።

ገ ' ና ነው
የጌትነት ልጅ ፃፈ

@wegoch
@wegoch
@Mahletzerihun
"አሁን ምን ልታደርግ ነው?"
አልኩት... አንድ ....ብዙ የህይወት ጨለማዎችን እንዳሳለፈ ባገኘኝ ቁጥር የሚተርክልኝ ጓደኛዬን....... ከስንት አፈርድሜ መጋጥ ቡኋላ ተሳክቶልኝ ይኸው ሰው ሆኛለው ብሏል. ( ከሱ ሰምቼ ነው ይህንንም) በቅርቡ ነው የተዋወቅነው ባጋጣሚ!

"ሰው ልገዛ!"አላለኝም!!

ህም! ... በቃ ትንሽ ጨላ(money!) ስንጨብጥ ፈጣሪ የሆንን ነው የሚመስለን?............

ትንሽ ቆይቼ ግን ቆይ ይሄ ሰውዬ ምን ያህል መገፋት ደርሶበት ይሆን እንዲ የተናገረው? ብዬ አሰብኩ( ማለትም ያ ፈልጋል በርግጥ)


.........እውነት ግን ቆይ ወዴት እየሄድን ነው? ምን እያደረግንና ነው?

ሀብት ላለው ሰው አጎብዳጁ ብዙ ነው! ባለጠጋውንም እኮ እንዳያስተውል በሙገሳ ና በአጉል ክብር ገመድ አንቀን ገድለነው....
ሰውን በፍቅር እንጅ በገንዘብ እንደማይገዛ እንዳያስብ አደረግነው.

አሁን ይህ ሰው ምኑ ይፈረድበታል ቆይ?... ያኔ ነጫም ደሀ በነበረበት ግዜ የገፋው ሁላ አሁን ላይ እንኮኮ ሲለው ቢታየው ...ምን ይገርማል? ....ያኔ በቅጡ እንኲ ሰላምታ የማይሰጠው ማህበረሰብ ዛሬ ሲነጠፍለት ቢያልም ምኑ ይደንቃል? .....የገፋችው የህይወቱ ንግስት ካለችበት ቦታ ብረት ወደ ማግኔት እንደሚሳበው ስትመጣ ቢታየው ምኑ አጀብ ያሰኛል?...
ድሮ ብድር እንኳ የነፈጉት ሰዎች ዛሬ መንገድ ዳር ሲያዩት አከርካርያቸው እስኪቀነጠስ ተጉንብሰው ይዘይሩታል. ....... ምድር ላይ ያለ የተዛነፈ ስሌት ነው! ይሄ እንግዲ ...ምንም አያስደንቅም!

በተለይ በሴቶች ይብሳል.. ንፁ ልቡን መስዋት አድርጎ እያፈቀራት ... የሷ አይን ግን ከኪሱ ላይ ነው!(ሁሉም ማለቴ አይደለም በርግጥ) የአይናቸው ሞራ የተገፈፈላቸው ልባሞች አሉ. ችግሩ በዳበሳና በባትሪ ነው እንጅ የሚገኙት! ልቡ ባዶ ጋን ሆኖ ኪሱ ብቻ ይሙላ... ጉንዳኖች እንደሚወሩት የማር ጠብታ ግርርር!...... ከዛስ? ከዛማ.... ብሩ ሲያልቅ እብስ! .....ወዴት? ወደሌላው ልበ-ጎዶሎ ና ንዋየ-ሙሉ ተባዕት ነዋ!

ምን እሷ ብቻ ወንዱስ ቢሆን! ገንዘብን ቢያፈቅር አይደል ......እናቱ አይደለም አያቱ ከምታክል ሴት ጋር እሚዘለው? ኧረ እናንተዬ! .... ይህ ፍቅረነዋይ
አይናውጣ አድርጎን የለም እንዴ? እጅግ በጣም ተገርመሽ 'ምን ነክቶክ ነው ማሚን ከምታክል ሴት ጋር እምትዘለው?' ስትይው.....ፈገግ ብሎ ' እናቱ ቢዝነስ መሆኑን አታውቂም እንዴ?' ይልሻል!
ምን ትያለሽ ታድያ..... አግራሞትሽን ተከናንበሽ ጥርግ!

ከልክ ያለፈ ክብር መስጠት ለተቀባይ ትርፉ ልቡ በትዕቢት መሞላት ነው!

ጎበዝ! ገንዘብንኮ ሰርተነው ነው! ይህ እውነት እየተረሳ ሳሄድ አይቀርም....ወደፊት እንደውም ... አስደናቂ የአለም እውነታ ተብሎ "ገንዘብ የተሰራው በሰው ልጆች ነው!"ተብሎ መምጣቱ አይቀርም. ሁሉም ያነበበው ሰው አፉን በጁ ጭኖ ይደነቃል! ምን አለች በለኝ!

"ገንዘብ ገንዘብ ገንዘብ ያለው ያወጣ
ይስራ ያልሰራበት አገር እንድታድግ ሁሉም እንዲያልፍለት!"

ከምንመፃደቅበት...... ያገር ሴቶችን በግራ በቀኝ ከምናግበሰብስበት ........ በየመሸታ ቤቱ ገብተን አእምሮ ቢስ ና ለሆድ ኗሪ ጅብና አህያን ከምንጋብዝበት.........ለምን አንሰራበትም ቆይ? ሀብታም ተብዬው ቋጣሪ!(በኢንቨስትመንት እና በልማት ደረጃ ስንመጣ ማለት ነው) እጅህ ሊቆረጥ ነው የተባለ ይመስል ይሰበስባል! ለመደፋፋትስ? እንቡጥ ሴቶችን ለመግዛትስ?....ኪስን ወጥቆ መንደር ለመንደር ዲታ ነኝ ብሎ ለማስወራትስ አንደኛ!..... ድሀውም የባሰ ቋጣሪ! እንደውም በሱ ይብሳል!

" እንኳን ገንዘብ ሰውም ሲገላበጥ ነው የሚዋለደው!"

ላለው አንስገድ ወገን! እሱስ ኬት አባቱ ያመጣው ይመስልሀል? ከላይ ዘንቦለት? No........ ሰርቶ ነው አልያም ዘርፎ! ግፋቢል ወርሶ! እሱ ካገኘው እኔንስ ምን ገደበኝ? ያው ዝርፍያውን ማለቴ አይደለም.... ይህ ለችስታዎቹ ነው!

አንተ ደግሞ ዘርፈህም ይሁን ሰርተህ.... ወርሰህም ይሁን ሎተሪ ወቶልህ... ባለጠጋ የሆንከው..... አካፍል ...ስራበት... ለድድ አስጭዎች ስራ ፍጠርበት... የወደቁትን አንሳበት.... ካልሆነ ለኛ ስጠን... እንጅ አትኮፈስበት! ....ሰው ገዛበታለው አትበል.... ገንዘቤን ይጭነቀው አ..ት..በ..ልልልል!

እስከመቼ ድህነት ሚባለውን እከክ ታቅፈን እንዘልቀዋለን? ኧረ እንፋታው! እስቲ ይለፍልን እኛም ዘና እንበል.....በየቲቪያችን 'ዛሬ ኢትዮጵያ ለእገሌ ሀገር ይህም ያህል ብድር ሰጠች!' የሚለውን ዜና እንስማ! እስከመቼ ተበደረች! እስከመቼ ብድሯ ተሰረዘ! እስከመቼ አንገት መድፋት!

"አሥሬ ከመፍሳት አንዴ መቅዘን!" አለ መንጌ!

ይቅርብን እስቲ ለባላባት ማጎብደዱ! አጎብዳጅ ሲያጣ ሳይወድ በግዱ ወደስራ ይዞራታል............ለሥራ እናጎብድድ! እንካፈል.. እናካፍል... እንስራ....
(የሸክላውን እንስራ አይደለም ታድያ! እ!)

ተፃፈ by aggie

@wegoch
@wegoch
@wegoch
my very first superhero
{ ቀልጦ እንደሚበራ ሻማ ፤ መብራት በሌለው ከተማ }

ከድመት አፍንጫ በቀዘቀዘች ፤ አዲስ ነገሮች ከአለም እጅግ ዘግይተው በሚደርሱባት ትንሽዬ የገጠር ከተማ ውስጥ የምኖር የስድሰተኛ ክፍል ተማሪ ፤ ታዳጊ ልጅ ነበርኩ ። አንድ ቀን ሱቅ ተልኬ ስሄድ ባለሱቁ እየገነጠለ ስኳርና ቡና የሚጠቀልልበት መፅሃፍ ላይ አይኔ አረፈ። ከመፅሃፉ ላይ ጥቂት የማይባሉ
ገፆች ገንጥሎ ስኳር ምናምኑን ቢቸረችርበትም እንዲሰጠኝ ስጠይቀው በምትኩ ሌላ ወረቀት ማምጣት እንዳለብኝ ነገረኝ ። ቤት ተመልሼ የድሮ ደብተሮቼን ሰብስቤ አስረክቤ መፅሃፉን ተቀበልኩት። ያ መፅሃፍ የተክለፃዲቅ መኩሪያ 'ዐፄ ቴዎድሮስ እና የኢትዮጵያ ታሪክ" ነበር ።

{ ህይወት እንዳይሰለቸኝ ፤ ሲጨነቅ ሲጠበብልኝ}

በዛ ብዙ ነገር እንደነበረ በቀስታ በሚያዘግምበት ህይወት መኻል በታዳጊ
እድሜዬ የተደበቅኩበት ፤ ከቋራ እስከ ጋፋት ፣ ከሽርጌ እስከ መቅደላ ፣ ከዳሞት
እስከ ደንቢያ በምናቤ እንዳካልል ያደረገኝ የደጃዝማች ኃይሉ ወልደጊዮርጊስ እና የወ/ ሮ አልጣሽ ልጅ የመጀመሪያው ጀግናዬ ካሳ ሃይሉ ነው።

{ አየሁኝ ጥበብ ሰማሁኝ እውቀት ፣ ልናገር ልመስክር የዚህን ሰው ውበት፣ }

ያ በልጅነት ምናቤ በአንበሶቹ መሃል ሲንጎማለል የምስለው አፄ ቴዎድሮስ
የምርም ግርማው ብቻ ሳይሆን ተግባሩም ጀግንነት ነበር ማን አለ ከእርሱ ሌላ ? ኢትዮጵያን አንድ ለማድረግ የጣረ የለፋ የደከመ ' ሃገሬን' ሲል የራሱ ቤተመንግስት እንኳን ያልገነባ ? ማን አለ እንደርሱ ?ንጉስ ከመሆኑ በፊትም ቅጥ ና ስርአት የሌላቸው የዘመነ መሳፍንት ባላበቶች የሚቀማውን ገንዘብ ለገበሬዎች እያካፈለ ሞፈር እና ቀንበር እንዲገዙ የሚረዳ የሃበሻ ሮቢን ሁዱ? ማነው በዛ ዘመን ቁጭ ብሎ ከማዘዝ ይልቅ ራሱ ሰርቶ ህዝቡን የሚያሰራ ንጉስ የነበረ? (ማለት ለታይታ መጥረጊያ እንደሚይዙት እነ እንትና ሳይሆን ከልቡ የምሩን ) ሌላም ብዙ ብዙ ....

{ እየቀለጠ የበራልኝ ፣ እየሞተ ያኖረኝ }

እና ግን እግዜር ይሄን ታላቅ ሰው ከምን ጋር አስተላለፈው ? ከዘመን ጋር ለራሱ የሚበጀውን የማያውቅ ህዝብ መሃል ሃገሬን ከሌሎች በላይ ላድርግ ባለ
ስራችሁን ወጥራችሁ ታትራችሁ ስሩ ባለ ከዘመናቸው ብዙ ለራቀ ሃሳቡ ቀና መሆን ያቃታቸው እግራቸውን አጣምረው የሚውሉ ስራፈቶች ሁሉ ምቀኛ ሆነው
ተነሱበት እና ብርሃን ሆኗቸው ሳለ አቅልጠው ጨረሱት። ከውጪም ከእንግሊዝ ጋር የነበረው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በመቋረጡ ጦርነት መቅደላ ድረስ መጥቶ በመጨረሻ የምወደው ንጉስ የልጅነት ምናብ ጀግናዬ በክብር ወደቀ። እጄን አልሰጥም ብሎ በጀግንነት ሲዋደቅልን እኔና የሃገሬውን ሰው እርሱ ሞት ተጎንጭቶ እኛን በክብር አኖረን ።

{ የዘላለም አይደለም ወይ ፤የሰጠኝ ደስታ ከላይ }

ከጀግንነቱ ፣ ለኢትዮጵያ ካለው ፅኑ ፍቅሩ ባሻገር ዛሬ 202 ኛ አመቱ ሲከበር አንዴ ቀና ቢል ልነግረው ከምፈልጋቸው ነገሮች መካከል አንዱ " ልጅነቴን ውብ ስላደረክልኝ አመሰግናለሁ" ነው ።

{ እንደ መልከፀዴቅ ካህን ፣ ክህነቱ ከዘመን ዘመን }

ብዙ አመታት አልፈው ብዙ ነገስታት ተፈራርቀው ዛሬም እስከ ህልሞቹ እስከ አወዛጋቢነቱ እስከ ጀግንነቱ እስከ ሃዘኖቹ እጅግ የምናከብረው እና የምንወደው ንጉስ አፄ ቴዎድሮስ

@wegoch
@wegoch
@paappii

#elsa mulugeta
⛺️Camping Trip to #Ankober with #Sunsethiking!

📅camping Date :- Jan 23 - 24, 2021(tir 15 - 16, 2013)

🛫Departure:- - Piassa Tayitu Hotel

Departure Time - 2:00Am Local time 🚩

💵 contribution per person:- 1350 💰

🎉🎊Package 🎋🎊

🔵🚍 - Transportation
🔴⛺️- Tent, campfire &tea
⚫️🍝 - Traditional Roasted meat ( 🐏), Lunch and snaks🍟🍤
⚪️ Bottled water
🔵 Park entrance with Guide
🔴photograph 📷

NB.
🚫 Sanitizer & facemask mandatory!


for more join the
🔸channel @sunsethiking🍁
🔻📷 @sunsetphotography🍁

🎫 tickets available at
@Paappii ( +251922303747 )
ያለፈ ህይወትዋን ያየሁባት ይመስላል በሐፍረት አየችኝ። በዝግታ ንግግሯን
ቀጠለች፡- የህይወት ጣፋጭነትን ሳያዉቁ የሚሞቱ ሰዎች የሴትን ልጅ ስቃይ አይረዱትም። በተለየ በፈጣሪ ፍቃድ ነብሷን ለአንድ ሰዉ ሰጥታ በምድራዊ ህግጋት አስገዳጅነት ደግሞ ስጋዋን ለሌላ ወንድ የሰጠች ሴት ስቃይ አያዉቁትም። ይህ ስቃይ በሴቷ ደም እና እንባ ስለሚፃፍ ወንድ ሊያነበዉ አይችልም። ቢያነበዉም አይገባዉም። ቢገባዉም እንኳን በህመሟከመሳለቅ የተለየ ምላሽ አይኖረዉም። ይህ ማለቂያ አልባ የስቃይ ድራማ የሴት ልጅ ድክመት እና የወንድልጅ ብርታት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ የቀጠለ ነዉ። ብርቱዎች ደካሞችን በባርነት መያዝ እስኪያቆሙ ድረስ መቀጠሉ አይቀርም።በጨካኙ የሰዉ ልጅ ህግ እና በንፁሑ አፍቃሪ ልብ መካከል የሚደረግ ጦርነት ነዉ። ትናንት በዚያ የፍልሚያ ሜዳ ወድቄ ነበር ። ሆኖም ግን ብርታቴን አሰባስቤ የታሰርኩበትን ሰንሰለት በጠስኩት። ክንፎቼን ነፃ አዉጥቼ በከፍታ ወደሚገኝ ሰላም ና ፍቅር በረርኩኝ።


@wegoch
@wegoch
@paappii

#Madam Rose Hanie
ከዙኪ ገፅ ላይ የተወሰደ
አሜሪካን አገር ውስጥ ነው አሉ። ሰውዬው 7 ቢሊየን የአሜሪካን ዶላር ሎተሪ ይደርሰውና እንደደረሰው ሲነገረው በድንጋጤ እንዳይሞት በማሰብ ቤተሰቦቹ ሳይካትሪስት ቀጥረው እውነታውን ያለ ምንም ጉዳት እንዲቀበል ቅድመ ዝግጅት ያደርጋሉ። ሳይካትሪስቱ እንዴት ማሳመን እንዳለበት እቅድ አውጥቶ ሥራውን ይጀምርና ከሰውዬው ጋር በመነጋገር ተግባብተው በትንሽ ቀናት ውስጥ ጓደኛ መሆን ቻሉ። አንድ ቀን በጨዋታ መሀል ሳይካትሪስቱ ሰውየውን "7 ቢሊየን ዶላር ሎተሪ
ቢደርስህ ምን ታደርገዋለህ" ብሎ ጠየቀው። ሰውየው ቀለል አድርጎ ይመልሳል" 1 ቢሊየን ዶላር ላንተ ለወዳጄ እሰጥሃለው።" ሳይካትሪስቱ የሰውየውን ንግግር እንደሰማ ህይወቱ አለፈች።
…………
ከማሳመናችን በፊት እንመን
ከማዘጋጀታችን በፊት እንዘጋጅ
ከመምከራችን በፊት እንመከር።

@wegoch
@wegoch
@paappii
#Ab Bella 🖤
አሜን


የዘንድሮ ልጅ ግን በየትኛዋ ፀሀይ ነው ገላውን ታጥቦ የሚሞቀው? መቼም ዘንድሮ የተወለደ ልጅ በዚች ፀሀይ ሞቆ እንዴትም ፈረንጅ ቢመስል እንኳን አንድ ወር ሳይሞላው ያረረ ብረት ምጣድ እንደሚመስል አልጠራጠርም። አቤት ፀሀይ!!
ከቤት ወጥቼ የቀጠሮ ቦታዬ እስክደርስ ድረስ ከዛሬ ሁለት አመት በፊት የማሞካሻትን ፀሀይ፤ የማቆለማምጣትን ፀሀይ ፤ ለ'ናቴ ቁንጅና ተምሳሌት አረጋት የነበረችውን ፀሀይ እየረገምኳት፤ ፈጣሪዬንም ፀሀይን በመፍጠሩ እያማረርኩት የቀጠሮ ቦታዬ ደረስኩ። የሄድኩበት ቀጠሮ በጥቂት ደቂቃ ውስጥ አልቆ ያቋረጥኩትን ምሬት እየቀጠልኩ ፤ እንደ ፍሪጅ የሚቀዘቅዘውን ቤቴን ባይነ ህሊናዬ እየሳልኩ የቤቴን አቅጣጫ ተያያዝኩት።
መንገዴን በደመነፍስ እየተጓዝኩ ሳለ ድንገት አንድ ድምፅ አባነነኝ። "አባት" የሚል ድምፅ ሰምቻለው ነገር ግን አልዞርኩም። ብዙ ጊዜ ሰው የጠራኝ መስሎኝ እየዞሩኩ ብዙ ጊዜ የማርያም ብቅል እየፈጨው ነው ብዬ ተመልሻለው። በድጋሚ ሲጠራኝ ግን አንድ በጣም የማውቀው ሰው የጠራኝ ያህል ተሰማኝ። ፊቴን ሳላዞር እንባ ይተናነቀኝ ጀመር። በለሆሳስ አንገቴን አዞርኩኝ። አይኔ በፍጥነት ይርገበገባል ምክንያቱም አንድ ሰከንድ አይኔ መርገብገቡን ካቆመ እንባዬ ማቆሚያ አይኖረውም።
ያ የድምፁ ግርማ ሞገስ ሲቆጣ አይደለም ሲመክር ያስፈራ የነበረው፤ ያ ከትህትናው ብዛት 'አቤት ልጆቹ ታድለው በሁለት እናት ነውኮ ሚኖሩት ' እስከሚባል ድረስ ለሰው አዛኝ የነበረ ሰው፤ 'እንደሱ ልፋት እንደሱ ስራ ይሄም ሲያንስበት' እየተባለ በየሄደበት የሚሸለመው ሰው፤ ዛሬ በአንድ ቅፅበት ሁሉ ነገሩን ያጣ የሚመስል አንድ ሰው ፊት ለፊቴ ቆሟል። ከራስ ፀጉሩ እስከ እግር ጥፍሩ አየውት እየገላመጥኩት አልነበረም የማየው ነገር ገርሞኝ እንጂ።ፊቱ አልቀረ ፤ ቅንድቡ አልቀረ ፤ ያ'ይኖቹ ሽፋሽፍት እንኳን ሳይቀሩ መላ ሰውነቱ አቧራ የሸፈነው ከአለም ሁሉ ምስኪኑ ሰው ፊት ለፊቴ ቆሟል። "አባቴ ቡና ግዛልኝ?" አለኝ። ገንዘብ ምን ያህል ቀፋፊ እንደሆነ ተሰማኝ። የገንዘብ እጦት ለ አምስት ብር ቡና ሲባል ከታላቁ ክብር አንስቶ መሬት ይፈጠፍጣል። በአንድ ሰሞን ሰው ሁሉ ቡና ካልጋበዝኩክ እያለ ያስለመደውን ሱስ ለማስታገስ እኔን አባት እራሱን ንፋስ አንደፈለገ እንደሚያደርገው ፌስታል ቆጠረ። አንዲት ቃል ሳልተነፍስ እንባዬ ሲወርድ ታወቀኝ ።እንባዬ ጉንጬ ጋር እንደደረሰ ወዲያው በጆቼ ጠራርጌ " ና እንሂድ እገዛልሀለው " አልኩት። አይን አይኑን ማየት ስለፈለኩ ብሩን አልሰጠውትም። "እግዛቤር ይስጥልኝ" አለኝ አንገቱን እንዳቀረቀረ። ቡናውን ገና ሳልገዛለት እንደ ንጉስ አከበረኝ። ወደ ቡና መሸጫው እየሄድን እንኳን ካጠገቤ ሆኖ ሊራመድ አልደፈረም። እኔን እንደ አለቃ ፊት ፊት እየመራኝ እርሱ ግን እንደ ገረድ ከኋላዬ ይከተለኝ ነበር። ቡና ምታፈላዋ ጋር እንደደረስን " ቡና ቡና" አላት። የጠማው ቡና ሳይሆን ውሀ ነበር የሚመስለው።" ውይ ቀዝቅዟል ባይሆን ከቸኮልክ ሞቅ ላድርግልህ?" አለች "አይ ዝም ብለሽ ቅጂልኝ" ምን ያህል እየተንገበገበ እንደሆነ እያየች በድጋሚ "ቀዝቅዟል እኮ ነው ያልኩህ" አለችው። ዞር ብዬ አየት አረኩት አይኑ ይርገበገባል ፤ ሊያለቅስ ይሁን ሊመታት አልገባኝም። ገና አይኑን እንዳየች ሮጣ መታ ሲኒውን ጠረጴዛው ላይ ሳታስቀምጥ ቀዳችለት። እሱም ከ'ጇ ላይ ተቀብሎ(ቀምቶ) በአንድ ትንፋሽ ጭልጥ አረገው። የሲኒው ከንፈር ከከንፈሩ ሲላቀቅ ሰውነቱ አንዳች ነገር እንዳገኘ ይፈካ ጀመር። አጠገቡ መሆኔን ሲያውቅ ያ የማይቋረጥ ምስጋናውን ቀጠለ "አጊኝቶ ቀማጣት እመብርሀን ትሰውርህ ፣ የሰውን እጅ አያሳይህ ፤ አብልቶ ከመነከስ ይሰውርህ " አለኝ። ሂወቱን እየነገረኝ እንደሆነ ተሰማኝ። እንባዬም ከምርቃቶቹ እኩል ይፈስ ጀመር። ለመጀመሪያ ጊዜ ከልቤ ይህን ቃል አወጣውት
""""""'አሜን"""""""

የጌትነት ልጅ ፃፈ
@wegoch
@wegoch
@Mahletzerihun
እንደግመል ሽንት. . .
________________________
ጓደኛዬ ነው ያስታወሰኝ፤ "የኛ ነገር እንደግመል ሽንት ወደኋላ ሆነ" ብሎ።
የግመል ሽንት ለምን ወደኋላ ይፈሳል? ቸንቸሎው ትንሽ ስለሆነ ነው አሉ።
ግመሎች ሰው ካልረዳቸው በቀር ወሲብ ማድረግ አይችሉም ሲባል ሰምቻለሁ
(አይናለም የጠራሽ የለም!)። ከየት እንደመጣ ግን እንጃ። ሰው የግመል ፒምፕ ለመሆን ፈልጎ የፈጠረው ሰበብ ካልሆነ በቀር ውሸት ነው። ምክንያቱም ናሽናል ጂኦግራፊክ ላይ የሞንጎልያ የዱር ግመሎች ብሎ አይቻለሁ። በዚያ ላይ ደግሞ ሰው ግመልን ከማላመዱ በፊት ማን እያገናኛቸው ተዋለዱና እዚያ ደረሱ? እና ውሸት ነው። ያንን የሚያህል እንስሳ ቸንቸሎው እንዴት ትንሽ ሆነ? አንድ ታሪክ አውቃለሁ ስለሱ፣ እውነት እንደሆን አላውቅም። ፈጣሪ እንስሳትን ሁሉ ፈጥሮ ካበቃ በኋላ ነው ከያሉበት እንዲመጡ አስጠርቶ ቸንቸሎ ያደላቸው አሉ። መጀመሪያ የመጣው አህያ ነበር። First come, first served ተባለና የድሀ እግር የሚያህል ቸንቸሎ ተሰጠው። ቀጥሎ ፈረስ መጣ፣ እሱም ግድንግድ ቸንቸሎ ተሰጠው። እያለ እያለ ሰው መጣ፣ እሱም እስከዛሬ ድረስ ደስተኛ ስላልሆነ እየደበቀ የሚኖርበትን ያህል የተሰጠውን ወስዶ ሄደ። መጨረሻ ላይ በረሀ ለበረሀ ሲዞር የነበረው ግመል መጣ። ፈጣሪ እንስሶቹ ሁሉ የደረሳቸው መስሎት ነበር። ግመልን ሲያይ ደነገጠ። ግመል ጉዱን አላወቀም፣ ድርሻዬን አለ። ፈጣሪም "አይይይ ግመል፣ ምነው ዘገየህ? ካለቀ መጣህ፣ ይቺው ነች የቀረችው!" ብሎ መዳፉ ላይ ትንሽዬ ቸንቸሎ አሳየው።
ግመል ቀወጠው! "አመዳሞቹ እነአህያ ያንን የሚያካክል ወስደው ለኔ ይቺን፣
እንዴ አልፈልግም!" አለ። ፈጣሪም ሊያግባባው ሞከረ፣ "በቃ በረሀ ትዞር የለ፣ የውሃ ጥም መቻያ ሰጥሀለሁ፣ በሱ አካክሰው" ምናምን አለው። ግመል ገገመ። ተናዶ "ትልቅ ቸንቸሎ ነው የምፈልገው፣ ሌላ አልፈልግም" አለና ተናዶ ዞሮ ሊሄድ ሲል ፈጣሪ ተቆጣ።
"ና አንተ!" ግመል አልሰማም አለ። ዞሮ መሄድ ጀመረ። ይሄኔ ፈጣሪ ተናዶ "እናትህን!" አለና ትንሿን ቸንቸሎ ወረወረበት። ቸንቸሎዋም ሄዳ ቂጡ ጋር ተጣበቀች! እናም ሲሸና ወደኋላ ሆነ . . .
ወደኋላ . . . እንደግመል ሽንት . . .

@wegoch
@wegoch
@paappii
#Gemechu Merera Fana 🖤
#ይህ የሆነው ባለፈው ነበር;
አስቤዛዬ ሲሟጠጥብኝ ለመሸመት አመዴ ገበያ ወደተባለው ስፍራ ወረድኩኝ። ወደ ገበያ መውረድ ደስ ይለኛል። ቁምጣዬን ለብሼ ቆለጤን ከግራ ወደ ቀኝ እያማታሁ በገበያው መሀል እባዝነው ጀመር።

አንዲት አትክልት አሻጥር ባታሌ መሳይ እሴት ጋር ተጠጋሁ! ሻሽ አስራለች።
ቅልብልብ የሚል ዓይና ፣ ሰልካካ ሊባል የማይችል አፍንጫ አላት! ከንፈሮቿ
የተንጠለጠሉ ናቸው። አንገቷ ላይ ማህተም አለ። ማህተሙን ተከትዬ ስወርድ መስቀሏ በትልቅ ጡቶቿ
መሀል ተነክሯል! እኔ ልነከርልህ! የተጠጋጋ ያጡት ነው! ቡጉንች ያጡት አደለም አጋፋሪ ጎምላላ ያጡት ነው!
' አባቱ ምን ልታዘዝ ' ብላ ከጡት ላይ የዋለውን ዕይታዬን ደረመሰችብኝ። ለካ
በጡቷ አካባቢ ደፈጣ ሳካሂድ ደቂቃዎች ነጉደዋል! በውበት ዕይታ ግዜ ምንድነው ? የምሰጠኝን ነገርኳት። የግንባሬን አሳዛኝነት ተመልክታ ጥሩ ጥሩ አትክልት ከተተችልኝ! ' እሷ የለችም እንዴ ? ' አለችኝ። ማንም እንደሌለ ገበያ መውረድም ሙዴ እንደሆነ ነገርኳት። ስለ ትዳር አወራን። ለትዳር ጥሩ ምልከታ የላትም! ቀሽም ወንድ እንደበደላት ነገረችኝ። አንዲት ሴት ልጅ አላት! ይህን ሁሉ ስታወራኝ ለቂጤ በርጩማ አቀብላኝ ነበር። አቤት ድምጿ! አቤት አተራረኳ! አቤት ጨዋነት! ቀና ብዬ ገርመም ሳደርጋት በሰላሳዎቹ አጋማሽ ላይ የምትንቀዋለል ደርባባ ሴት ናት!
ጨዋነቷ የገነፈለብኝ ለዚህ ነው አልኩኝ።
ሌላም ግዜ መጥቼ እንደምሸምታት ቃልም ገብቼ ፣ ቁጥሬን ሰጥቼ ተለያየን!
ከስጋ ዘመዴ የምነጠል ያህል ተሰማኝ! የቋጠረችልኝን አስቤዛ አንጠልጥዬ ጋሪ
ላይ ተሳፈርኩኝ! ማታ ጋደም ብዬ የሀገሪቱን ፖለቲካዊ አካሄድ እያሰላሰልኩኝ! ስልኬ ጮኸች!
የማላውቀው ቁጥርም ነበር!
' አንተ ጨዋታዬ ይህን ያህል መስጦህ ነበር ? '
ቀን የሰማሁት ባለ-አስቤዛ ድምፅ ነበር!
' እንዴ እንዴት ? '
' ሂሳብ ሳሰጠኝ ሄድካ....'
' ወይኔ አዎ! ለምን ሳጠይቂኝ በናትሽ ? '
' ምን ችግር አለው መመለስህ አይቀር! ' አቤት ጨዋነት!
ከትንሽ ወጎች በኋላ ነገ ከስራ በኋላ ደውዬ እንደምሰጣት ነግሬአት ተሰነባበትን! ከአንድ ሸጎጥ ካለች የመንደር ግሮሰሪ ምሽት ላይ ደውዬ ጠራዃት! ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ውበት ደርባ ተሽሞንሙና መጣች! ደነገጥኩኝ! ድንጋጤዬን አይታ መሰለኝ ልክ እንደ ረዥም ወዳጅ በእቅፏ ከተተችኝ! ፍርሃቴ እንደ ብናኝ
ከላዬ ረገፈ! አምሽተን! ማለዳ ላይ ተስፈንጥሬ ተነስቼ ቁርስ አስቤዛዋን ያካተተ ዕንቁላል ስልስ ሰርቼላት በላች! ከልቧ ተደመመችብኝ! ሸኘዃት!
አሁንም ሂሳቧን ረሳሁትን ረሳችው!

@wegoch
@wegoch
@paappii

#noah
ወይዘንድሮ
(በእውቀቱ ስዩም)
.
ወይ ዘንድሮ- አለ ስንዝሮ- አንድ ዶላር በአምሳ ሁለት ብር ዘርዝሮ !እንደማመመጥ! የተሻለ ይመጣል ብለን ስንጠብቅ፤ አዲሱ የፈረንጆች አመት አዲስ የኮቪድ ጎረምሳ ፈቶ ለቆብናል ፤ በአምናውና በዘንድሮው ኮቪድ መካከል ያለው ልዩነት ምን ብየ ላስረዳችሁ? በልዩሃይል እና በሪፓብሊካን ጋርድ መካከል ያለው ያቅም ልዩነት እንደማለት ነው ፡፡
አምና ሁሉም ቻይና ላይ ነበር ጣቱን ብቻ ሳይሆን አንቴናውን እሚቀስረው! አሁን እያንዳንዱ አገር የራሱን ብራንድ ቫይረስ በማመንጨት ላይ ይገኛል ፡፡
ባለፈው ወዳጄ በየነ ዶክተሮች ምርመራ አድርገውለት
“ ኮቪድ አለብህ”ሲሉት ምን ብሎ መለሰ?
“ የእንግሊዙ ነው የደቡብ አፍሪካው?"
እኔን አይያዘኝ አልልም ! ከያዘኝ የኢትዮጵያው እንዲደደርሰኝ ፀልዩልኝ! አንዳንዴ ሲደብረኝ አዲሳበባ ወይም ማርቆስ ለሚኖር ጉዋደኛየ እደውላለሁ ፤
“ እንዴት ነው ኮቪድ? ”
“ እኔማን ትናንት ይዞ ለቀቀኝ “ ይለኛል
“ ፍቅር እንኩዋ ትንሽ ሳያሽ፥ ሳያከስል፥ ሳያከሳ አይለቅም ! እንዴት ዝምብሎ ይለቅሃል?”እላለሁ በቅናት ስሜት ፤
የሆነ ነገር ትዝ ይለኛል ፤ ድሮ መገናኛ ካልዲስ ካፌ ፊትለፊት ቆሜ የኮንሮባንድ ጫማ ስመርጥ የሆነ መዳፍ ትከሻየን ይነካኛል ፤ ዞር ስል አንድ ሰውየ “ኦ ይቅርታ ከማጅራትህ ሳይህ ከማውቀው ሰው ጋር ተመሳስለህብኝ ነው” ይለኝና ለጥቂት ሰከንዶች ይዞት የነበረውን ትከሻየን ይለቀዋል፤ ሸገር ያሉ ጉዋደኞቼ “ ኮቪድ ይዞ ለቅቀኝ ሲሉኝ “ ይሄ ነው ትዝ እሚለኝ!
እኔ ያለሁበት ከተማ የማስክ አነባብሮ ሁሉ ተጀምሩዋል ! በሰርጀሪው ማስክ ላይ ሌላ ከገበርዲን የተሰራ ማስክ ካልደረብሽ አገልግሎት አታገኝም ፤ ትንሽ ቆይተው፤ ኦክስጂን ራሱ በጉልኮስ መልክ የሚሰጡን ይመስለኛል ፤
ይህንና መሰል ጣጣዎችን ለመርሳት ዩቲውብ ላይ እጣዳለሁ ፤ዩቲውብ ለታታሪ ተመልካች መክፈል ቢጀምር እካሁን መኪና ብቻ ሳይሆን የራሴ መጠበቂያ ድሮን ሁሉ ይኖረኝ ነበር፤ ለመሆኑ ምንድነው እማየው? ፖለቲካ? ለእድሌም አላሳየው! ትናንት በርካታ ቆነጃጅት አንዱን አልባሌ ዘፋኝ ከበው ሲደንሱ አይቼ ዘና አልሁ ! ሌዲ ጋጋ የኢግዚቢሽን ማእከልን ድንኩዋን የሚያክል ቀሚስ በምትለብስበት ዘመን ያገራችብን ጉብሎች በከፊል መለመላ ሲቀውጡት አይቼ ተደነቅሁ ! በእኛ ጊዜ ክሊፕ በአይናፋር ሙድ ነበር እሚሰራው! አለማየሁ እሼቴ ኩኩ ሰብስቤን “ እንግዳየ ነሽ የኔ እንግዳ በበሩ ገብተሽ አረፍ በይ ጉዋዳ” ይላታል፤ እሱዋም እየተሽኮረመመች ያንኑ ትደግምለታለች! ግን ሁለቱም ጉዋዳ ለመግባት አይደፍሩም! ዘፈኑ ጀምረው እሚጨርሱት ከግቢ ውጭ ነው ፤ ዛሬ አስራ ምናምን ወይዛዝርት ሊሞዚን ውስጥ አንዱን ጎረምሳ ከበው ሲደንሱ አያለሁ! መብታቸው እንደሆነ ባምንም በዘፋኙ ላይ የተሰማኝን ቅናት የቀላቀለበት ንዴት መደበቅ አልቻልኩም ! እኔ እዚህ ተኮራምቼ ተቀምጨ የሰው አገር ብርድ እየጠጣሁ ፤ እንዴት ዋናው ሰብአ ሰገጥ ፤ ጨረቃ በመሳሰሉ ኮረዶች ይከበባል? በውነት ፌይር አይደለም!
የሆነ ቁምነገር ነገር ልጨምር! ብዙ ያገሬ ሰው በብልግና ነክ እንቶፈንቶ ቪድዮዎች ሲማረር አየዋለሁ ፤ የሚሻለው አለማየት ነው! እይታ በሌለበት እንዲህ አይነት ቪድዮዎች አይለመልሙም! ግን ያገሬ ሰው ባፉ እያማረረ ባይኑ ይቸክላል! ታድያ ገበያው ካለ ሸቀጡ ለምን አይኖርም?

@wegoch
@wegoch
ወሬ እና ሴት


እኔኮ ግርርርም የሚለኝ ወሬ ሲነሳ የሴቶች ስም ነፋስ እንደሚያነሳው ላስቲክ አብሮ መነሳቱ!

ወሬው ሲወራ እዛ እኛ ሰፈር እንዳለው የነ ጋሽ አለሙ ትልቅዬ ዲሽ ጆሮህን ዘርግተህ አትሰማ ይመስል!

እንደው ቆይ ቆይ ፍረዱኝማ!.....ያለወሬ ጠቅላላው የአለም ህዝብን ህልውና አስቡት ብትባሉ ይዋጥላችዋል???? በተለይ ሀበሻን?


ወሬኮ ለሀበሻ እስትንፋሱ ነው! ቡና እንጠጣው፣ እድሩ ፣ሰንበቴው ዋና ጥቅሙ ምን ሆነና! እኚ ደግሞ ዘመናዊዎቹ እነቴሌቪዥን እነማህበራዊ ሚዲያ የተፈጠሩት ለምን ሆነና? .... በዘመናዊ መልኩ አቀናብረው ያው ውሬ ለማስፋት ነው! እንደውም .......የሀበሻን ህዝብ 3ቱ መሰረታዊ ፍላጎቶች ምን ምንድን ናቸው በለህ ብትጠይቅ 1.ወሬ 2.ወሬ 3ኛም. ወሬ ብሎ ባይመልስ ከምላሴ ፀጉር ይነቀል!

ወሬ ህይወቱ በሆነ ማህበረሰብ ውስጥ እሷም ተዘርታ የፀደቀች አንዲት ሴትም ወሬ ወዳጅ ሆና መፈጠሯ ምንም አያስደንቅም!

እንደውም ባለፈው አንዱ የተቀነባበረ ወሬ ማሾለኪያ (ቲቪ) ሲል እንደሰማውት.... ለስለላ እና ለድርድር ስራ( ዲፕሎማሲ) ሴቶች ቁጥር አንድ ተመራጮች እየሆኑ መጥተዋል.

ባል ተብየውስ..... እዛ..... "ሴት በዛ ጎመን ጠነዛ!" ስትል ትውልና እዚ ደሞ ዞር ብለህ ማታ እራትህን ከምርጥ ቡናህ ጋር እያጣጣምክ ስለሰፈሩ ፣ስለሰዉ፣ ስለባቄላ ዋጋ፣ ስለውስላታዋ የሰፈርህ ሤት፣ ስለልክስክሱ የሰፈርህ ወንድ፣ ማን ተጣላ ማን፣ እርቅ አወረደ፣ ማን ሞተ፣ ማን ወለደ... ሚለውን የተጠራ መረጃ ምታገኘው ከሷው አይደል?

ወሬ እና ሴቶች እጅና ጓንት ባይሆኑ ኖሮ ይች ምድር እንዴት አስቀያሚ ትሆን ነበር ባካቹ!

ወሬውን ሴቶች ባያዳርሱት ኖሮ አፈታሪኮች እዛው ተቀብረው ቀርተው ዛሬ ለኛ ባልደረሱን ነበር! እሱን ተውትና የክርስቶስ ትንሳኤንም ባልሰማን ነበር.

በየቡናችን ላይ የምንፈተፍተው ምርጥ ጭብጥ አጥተን ቡናችን ባልደመቀ ነበር!

አንድን ሰፈር ሰፈር የሚያስብለው በውስጡ የሚንሸራሸረው የወሬ ብዛት ነው! (የሴቶች ህብረት አቋም!)

ወሬኛ ህዝብ ጤነኛ ህዝብ ነው! ብሏል በውቄ! እውነቱን ነው... እንደፈረንጆቹ ቤት ውስጥ ስልክ ሚባል ግድግዳ፣ እእ! ባቡር ውስጥ ወይ መኪና ውስጥ ጋዜጣ ወይ መፅሀፍ የሚባል ግንብ ከጎረቤት መከለያ አጥር በራሱ ላይ አጥሮ ሲቆይ ይኸው ድባቴ ሚባል በሽታ አጥቅቶት እርፍ!...... እኛ አገር ይህ ችግር ሲያልፍም እማይነካካበትን ምክንያት አስቀምጡ ብትባሉ ከሴቶች ውጭ ሌላ ምክንያት ከየት ታገኛላቹ? ለዚ ደሞ ሴቶች ምስጋና ይገባቸዋል!

ባለፈው አንዱ ፕሮፌሽናል ወሬኛ ጓደኛዬ(ጋዜጠኛው ማለቴ ነው) ምን አለኝ መሰላቹ...."ጋዜጠኞችና አክቲቪስቶች ይቀጡልን! ጥርሳችችን የነቀልንበትን ሙያ ሰረቁን!" በሚል መሪ ቃል ሴቶች አመፅ ሊያስነሱ ነው....አለኝ
..
....
ታድያስ! እውነት ነው! ከድሮ ጀምሮ ሲነቀፉበት ሲ ሰደቡበት እና ሱብጠለጠሉበት የነበረን ሙያ ሲነጠቁ ማየት አይደለም አመፅ ማስነሳት መንግስት ቢያስገለብጥ አያስደንቅም!

እንደውም...በአለማችን ላይ 7ቱንም ቀኖች 24 ሰዓት ሙሉ ያለማቋረጥ በማውራት ጊነስ ቡክ ላይ ላለመመዝገባችን እንደተግዳሮት አድርጌ የምቆጥረው ሲወራ አሥሠፍስፎ መስማት ሚወድ ግን አውሪውን ማያበረታታው ማህባሰባችን ነው! እንጂማ የት በደረስን! በተለይ ባሁኑ ሁሉም ሰው በወሬ Phdውን በያዘበት ዘመን!

ደግሞኮ ሴት ወሬኞች ከወንድ ወሬኞች የሚለያቸውና ሙያው ልክክ እንደሚልባቸው የሚያሳብቀው በደረቁ አለማራታቸው! ..... ወሬውን ማድመቅያ የተለያዩ ቃናንያላቸውን ድምፆች ፣ ግንነት ፣ የእጅና የፊት ትርኢቶች ካስፈለገም በወሬው መሀል የነበረን ጭፈራም ይሁን ድርጊት ጣል አድርገው ማውራታቸው ለወሬውም ጥፍጥና መጨነቃቸውም ለሙያውም ክብር እንዳላቸው ምርጥ ማሳያ ነው!

የማያምርበትን ሙያ በግድ ካላማረብኝ ብሎ ያለሙያው የሚወጠወጠው ወንዱ ወሬኛማ አይጣል ነው! ክሽን ያለች ወሬ ከሱ መጠበቅ ዘበት ነው! ግን ሲያወሩ ሴት ወሬኞችን ለሚያስንቁ ወንዶች እጅ ነሳለው!

ወሬ ለዘላለም ትኑ ር! ( የሴቶች ማህበር ዋና ዳይሬክተው የወይዘሮ አሰፉ ጥቅስ!)

By #magi

@wegoch
@wegoch
@paappii
ፕሮፋይሏ!

ስወዳትኮ....ውይ! ቃላት አይበቃኝም ለመግለፅ

ልክ የክርስቶስን ተዐምራት ምድር ብራና፤ ውቅያኖስ ደግሞ ቀለም ሆኖ ቢ ፃፍ እንኳ እንደማይበቃ እኔም እንደዛ ነው ምወዳት! ችግሩ እሷ አታውቅም። የልቤ ሁከት አፌጋ ሲደርስ 'አሀዱ ተብሏል ዝም በሉ' እንደተባሉ ምዕመናን ጭጭ! ይልብኛል

ታድያ በፌስቡክም በቴሌግራምም በቫይበርም በሁለም ጓደኛሞች ነን። አወራን ቢባል የሳምንት ምልልሳችን ተጨምቆ እንደምንም ግማሽ ገፅ ቢወጣው ነው። ብቸኛ መፅናኛዬ በየ5 ቀኑ የምትቀይረውን ፕሮፋይሏ ማየት ነው. ፌስቡክ ላይ ፎቶዋ ዝር ብሎ አያውቅም ለምን እንደሆነ እንጃ! ቫይነርም የሆነ ጥቅስ የያዘ ፎቶ ትሰካበታለች! ቴሌግራም ግን...

እሷ ስቃ ፣ እሷ ስታስብ፣ እሷ አኩርፋ። እሷ አዝና፣ ፀጉሯን በጎን ጎንጉናው፣ ጆሮ ጌጥ አድርጋ ፣ ሳታደርግ፣ ቆማ ፣ተቀምጣ፣ ተኝታም ሊሆን ይችላል.... ብቻ እስክትቀይር በጉጉት እየተበቅኩ ማየት ብቸኛ መፅናኛዬ ነው.

አንዳንዴም ከሷ ተውሼ የኔ ላይ ማድርግ ያምረኝና ደግሞ 'ምን አስበህ ነው አንተ?' ብላ ብትጠይቅኝ ምን ብዬ መልሳለው ለሚለው የራሴው ጥያቄ መልስ ሳጣለት ተወዋለው!

እንድ ቀን ግን እንደለመድኩት 5 ቀን ሞልቶት የፕሮፋይሏን መቀየር በጉጉት እየተጠባባኩ ሳለ... የሆነ የሚፍለቀለቅ የወንድ ምስል ላይ 'የኔ ልዩ' ተብሎ ተፅፎበት አየው..

እንዴ?? ንድድ አለኝ! ስልክህን ጣለው ጣለው አለኝ. መልሼ ግን ፎቶውን አጠናውት.....

ምን ይመስላል! ደግሞ አማረብኝ ብሎ መሳቁ.. ከመሳቁ በፊት ሄዶ የጉንጩን ስርጉድ አያስሞላም! ልትስመው ስትል ድንገት ሳታስበው ከንፈሯን አደናቅፎ ቢጥላትስ?

የሆነ አመዳም! እንደውም ያስታውቃል ሴቶች ሚለቀለቁትን አመድ እንደለመደ! በጤናው አይደለም ፊቱ እንዲ መስታወት የመሰለው! መጀመርያ ሄዶ ይታጠብላት... ባፍንጫዋ ስትተነፍስ ድንገት አመዱ ቦኖ ቢያፍናትስ ቆይ??

ደግሞ ጥርሱስ?? ይሄ ልጅ ቂም አለበት እንዴ?? አይኗን አሳውሮ ሊያስቀምጣት አሥቦ ሳይሆን አይቀርም እንዲ ጥርሱን ያነጣው! ይሄኔኮ እኔ ሙሉ ልብስ የምገዛበትን ገንዘብ አውጥቶ በጨረር ታጥቦ ይሆናል! አሁን እንደው ለሚወዱት ሰው ይህን ያህል መጨከን ምን ይሉታል! ቢመጣ ቢመጣ ባይን ይመጣል??? ጥርሳም!

አቤት አቤት አቤት! ደግሞ ፀጉሩም ተፈርዞልኛል! የህቱን ሻምፖ ቆይ ምን አስጨረሰው? ምናለ ትንሽ ብትጠቀምበት?
....
..........
ድንገት የልቤ ንግስት typing... ስትል አየዋት .....
ልቤ ልትቆም ምንም አልቀራት ነበር. እንኳንም ቶሎ replie አደረኩላት እንጂ 'አይተኸው ዝም ብለኸኛል' በሚል ሰበብ 1 ሁለት ቀን ባለመመለስ ትቀጣኝ ነበር.

"hi መሳይዬ"

"hey!"

በቀጥታ ስለፕሮፋይሏ ላለመጠየቅ ስለውሎዋ ስለጤናዋ ስጠይቅ ዳርዳር ስል ቆይቼ በስተመጨረሻ

"ppw ያምራል!" ብዬ ጀመርኩ

"እመሰግናለው! ናዝሬት ያለው የአጎቴ ልጅኮ ነው"

እኽኽኽኽ!
የሞት ፍርድ ተፈዶበት ምህረት የተደረገለ ሰው እንኳ እንዲ አይተነፍስም.

የሰደበው ልቤ መልሶ
' መጠርጠር ነበረብኝ... እንዲ ያማረው ለካ ዘመድሽ ሆኖ ነው..... ውይ ውይ ውይ! ሰው እንዲ ውበቱን ይደፋበታ........" አንጀቴ ቅቤ ጠጥቶ!

"መሆንም አለበት!"

........

....


Maggie ፃፈችው

@wegoch
@wegoch
@paappii
አንዳንዴ ... አንዳንዴ ብቻ እንደዚህ አስባለሁ። አሁን አይበለዉና የልብ ህመም እንደ ጉንፋን ሁሉንም ሰዉ የሚይዝ ቢሆን ሰዉ ለመጠላላት አቅም ያጠራቅም ነበር? ድንገት ከእንቅልፉ ሲነቃ የአይኖቹን ሽፋሽፍት መግለጥ ቢከብደዉ? ፤ እግርና እጆቹን ማዘዝ ቢሳነዉ? ፤ እየሞተ ይሁን እየነቃ ማወቅ እስኪያቅተዉ ቢሆን ከዛች ቅፅበታዊ መከራ ወጥቶ ሰዉ ይጠላል? እሺ ሰዉ መሃል ተሰብስቦ ደስ ብሎት በፌሽታ እየዘለለ ካለበት ቅፅበት ድንገት መሬት ላይ ተንሸራቶ ቢወድቅ? ፤ አንድ ብርጭቆ ዉሃ አንስቶ ወደ አፉ ማስጠጋት እየፈለገ ቢያቅተዉ? ፤ አንዳንዴ ያለሰዉ የፈለገበት መሄድ ባይችል? ከዚህ ሁሉ የደቂቃዎች ዉጥንቅጥ ሲነቃ ሰዉ ይጠላል? እንዴት አድርጎ?

@wegoch
@wegoch
@wegoch

#Ruth Habte Mariyam
ባሌ እንዳመነዘረብኝ ባወቅኩ ጊዜ እጅጉን ደስ አለኝ!! (ርዕስ ነው!!)

"ቦታችን በተለመደው ሰዓት እጠብቅሃለሁ:: አፈቅርሃለሁ!" የሚል መልዕክት ነው እንዲህ ያስቦረቀኝ!!

እሱ ጏዳ ቁርስ እያበሰለ የሚያማስለው የመጥበሻ ድምፅ ይሰማኛል:: ስልኩ መልእክት ሲቀበል ድምፅ አሰማ ያለወትሮዬ እጅ ጥሎኝ ስልኩን አነሳሁት::

አንደኛ የራሳቸው ቦታ አላቸው! እኔና እሱ የኛ የምንለው ቦታ ኖሮን አያውቅም!! ከቤታችን ውጪ

ሁለተኛ የተለመደ ሰዓት አላቸው:: እኔና እሱ ለምንም የተለመደም የተመደበም ሰዓት የለንም:: የልደት ቀኖቻችንን እንኳን እረስተነው አልፎ ... 'ለካ ትላንት ነበር' የምንባባልበት ጊዜ አለ::

ሶስተኛና ዋነኛው ታፈቅረዋለች::

ይሄ ሲሰላ ቀመሩ እሱም ከኔ በላይ ያፈቅራታል ማለት ነው!

ደስ ሲል .....

"ምን ተገኘ?" ይለኛል አስሬ የሰራልኝን ቁርስ እያጎረሰኝ

"ምነው?"

"በጣም ደስ ብሎሻል! ይሄን ፈገግታ ካየሁት የማላስታውሰውን ያህል የጊዜ ርዝመት ያህል ዘመን ሆኖ ነበርኮ!" አለኝ የተለመደ የተመጠነ ፈገግታውን እየፈገገ... ዝም አልኩ

እያመነዘርክብኝ እንደሆነ ሳውቅ ነው ደስ ያለኝ! ይባላል? አይባልማ!!
.
.
.
ሊወጣ ይለባብስ ጀመር::

"እሱን ሸሚዝ ቀይረው:: ቅዳሜ አይደል? ፈካ ያለ ነገር ልበስ.. ቆይ እኔ ልምረጥልህ!" ብዬው ቄንጠኛ ሸሚዝ እፈልግ ጀመር ... ተዝረክርኮ ሄዶ የባሌ አፍቃሪ ፍቅሯ እንዲቀንስ አልፈልግማ! ተውቦ ነው መሄድ ያለበት!!

አንዴ ፀጉሩን አንዴ ጫማውን ... ደሞ ኮሌታውን ሳስተካክልለት ግራ ተጋብቶ ያየኛል::

"ዛሬ በጣም ጥሩ ሙድ ላይ ነሽ!" ብሎኝ ከንፈሬን ስሞኝ ወጣ!!

ልፀልይ ሁሉ ቃጣኝ:: ግን እንዲህ ያለው ፀሎት ለእግዜር ነው ለሰይጣን የሚቀርበው?

"በምንዝርናው እንዲፀና አድርግልኝ! ደግሞ ደጋግሞ እንዲያመነዝር እርዳው!! "

እንዲህ ያለው ድርጊት አምላክን አይመለከትም! ለዲያቢሎስ የትብብር ውይም የድጋፍ ጥያቄ ላቅርብ? ያው እኔ ባልጠይቀውም ወጥሮ ማስመንዘር መደበኛ ስራው ነው ብዬ ነው::

የአስር ዓመት ትዳሬ ነውኮ..... የመጀመሪያው ትሁን? እንዳገባ ታውቅ ይሆን? ሄዶ ሲስማት የኔን ከንፈር ልቅላቂ እንደምትስም ታውቅ ይሆን? እቤቱ ሲገባ የሚያስኮንን አፍቃሪ መሆኑን ታውቅ ይሆን? ዛሬም ከ10 ዓመት በኃላ እያጎረሰኝ እንደምበላ ታውቅ ይሆን? ወይስ እሷምጋ ዝንፍ የማይል አስኮናኝ አፍቃሪ ይሆን?

"ውሎህ እንዴት ነበር?"

"ፍቅሬ ለ2 ሰዓት ብቻ ነውኮ የተለያየነው?" አለኝ ከሷጋ እንደመጣ

"እኮ ቢሆንስ "

" እሺ ቆንጆ ነበር!" አለኝ መገረም ሳይለየው

ተጣልተው ይሆን? ተጨቃጭቀው? ለምንድነው የተለየ ፊት የማያሳየው? ምን አይነቷ ናት? ለሁለት ሰዓት እያገኘችው እንዲስቅ ማድረግ ያቅታታል? ወይስ እሷም እንደኔ መፈቀር ደከማት?

ባጠገቡ ሳልፍ መቀመጫዬን ደለቅ አደረገኝ!! እህህህ በቀን ሁለት እሙሙ አይሰለቸውም? ወይስ እሷ አትሰጠውም? እሷ እንደእኔ ሚስት ስላልሆነች ግዴታ የለባትም ይሆን? ወይም እንደኔ በገዛ ሀጢያቷ ስላልታሰረች ካልመሰላት ታፆመዋለች?

እኔ ሳገባው ቄሱ በመከራውም በደስታውም ... በድህነቱም በሀብቱም ... ብለው ያስማሉኝ እንጂ መሳቢያው ውስጥ እንደሚያስቀምጠው ገንዘብ በፈለገ ጊዜ እየከፈተ የሚዘግነው ንብረት እንዲሆን እሙሙዬን ማስያዜን አላስታውስም! (መሀላው የማላውቀው ውስጠ ወይራ ይኖረው ይሆን? ታዲያ የሚስትነት ግዴታዬ እንደሆነ የማስበው ማን ምን ብሎኝ ነው? ዛሬ ይለፈኝ ካልኩት የበደልኩት የሚመስለኝ በየትኛው ህግ ነው?

አንድ ቀን .... ርቆ እንደህልም በሚታወሰኝ አንድ ቀን በሰራሁት በደል .... ራሴን በእዳ አስይዣለሁ!!

"ሁለተኛ ቂጤን እንዳትነካኝ!" አልኩት ኮስተር ብዬ

"እንዴ? ለምን?"

"የራሴው ቂጥ አይደል?"

"አዎ"

"እንደገና ደግሞ የራሴው ሰውነት ላይ አይደል ያለው? ራሴው አይደል የተሸከምኩት?"

"እንዴ ፍቅር ምን ሆነሻል?"

"ሌላ ደግሞ አንዳንድ አንዳንድ ጊዜ ተሸከምልኝ ብዬ አላስቸገርኩህም አይደል? ደሞም ቂጤን በማጣፍት የሚመለስ የተበደርኩት ብድርም የለብኝምኣ?"

"ምንድነው ጉዱ?"

"በነዚህ ከተስማማን በገዛ ቂጤ የማዘው እራሴው ነኝ! ደስ ባለህ ሰዓት እጅህን እየላክ በጥፊ እንድታላጋው አልፈቅድም!! አበቃሁ!!" ብዬው ማሳረጊያ የተለመደ ፈገግታ ፈገግ ብዬ ሄድኩ::

ይቀጥል ይሆናል!!

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
ባሌ እንዳመነዘረብኝ ባወቅኩ ጊዜ እጅጉን ደስ አለኝ!(የቀጠለ)

ሰይጣን ይሁን ራሴ ወይም ፈጣሪ ለሀጥያት በቀጠሩልኝ ቀን ከአለቃዬ ጋር ባለግኩ። ይኸው ነው ሀጥያቴ!

ጨው የሌለው አልጫ ወጥ አልጫ ወጥ የሚል ትዳር ውስጥ ፀጥ ለጥ ብዬ እንድቆይ ባለእዳ ያደረገኝ ሀጥያቴ ይኸው ነው!! ይኸው ነው ብዬ አቀለልኩት?

ካልጠፋ ቀን የዛን ቀን ስልኬ ባትሪ ጨርሶ ባሌ ሲደውል ስልኬ ዝግ ነበር። ካልጠፋ ቀን ስልኬ በዘጋ ቀን ስንት ቀን ባልተሰማኝ ያለፍኩት የአለቃዬ እጅ ሲነካኝ ንዝረቱን እንቢ ማለት አልቻልኩም። ካልጠፋ ቀን ባሌ የዛን ቀን ቢሮዬ ድረስ ዘለቀ። ምን የሚሏት ባላጊ ነኝ ግን? በዘመኔ ከባሌ ውጪ አንድ ሰው ብሞክር እሱንም የቢሮ ጠረጴዛ ላይ? እኔን ብሎ ባላጊ ! ቅሌቴ በዚህ አላበቃም።

ተያየን። ጠረጴዛው ላይ በግማሽ አካሌ ተጋድሜ ሰማይ የእኔን እግሮች ምሰሶ አድርጎ የቆመ ይመስል እግሮቼን ወደላይ ወጥሬ ሰድሬ አለቃዬ ከእግሮቼ መሃል ሆኖ ሲለፋ ባሌ በሩን ከፍቶ ሲገባ ተያየን። (አንባቢ ሆይ እዚህጋ ለምትስሉት ምስል እኔን ተጠያቂ እንዳታደርጉ:: ሁኔታውን በምስል ለመከሰት ታስቦ እንጂ አንባቢን ክፉ ለማሳሰብ ያልታሰበ!)

ለወትሮ ጨዋ ነበርኮ። ካልጠፋ ቀን የዛን ቀን ጨዋነቱን እረስቶ ሳያንኳኳ ዘው ይላል? አፌን ከፍቼ ብዙ ቆየሁ። ድንጋጤው ይሁን የአለቃዬ ልፋት ወይም ሁለቱም አፌም ተከፍቶ አይኔም ፈጦ ብዙ ሰከንዶች አለፉ!! ባሌ ቀስ ብሎ እንደገባ ሁሉ ቀስ ብሎ ወጣ! አለቃዬ በድንጋጤ የተጋለጠ ንብረቱን ለመሸፋፈን ይተረማመሳል። (ይሄ ደግሞ የሚስቱን ምጣድ በቂጡ ነው እንዴ የሚያስስላት? እሱ የበጨጨ ቀይ ፣ ቂጡ የብረት ምጣድ ቂጥ የሚመስለው!)

ከአንድ ሰዓት በላይ ቢሮዬ ተቀመጥኩ። ተጎለትኩ። የማስበውን አላውቅም። ወደቤት እንደማልሄድ አውቀዋለሁ። አይኑን አላየውም። ግን ወዴት ነው የምሄደውስ? ብቻ አላወቅኩትም። ቦርሳዬን አንስቼ ወጣሁ። ደርቄ ቆምኩ። ባሌ እየጠበቀኝ ነበር። ልክ ምንም እንዳላየ፣ ድሮ እንደሚያደርገው ሁሉ ዘሎ ከመኪናው ወርዶ በሩን ከፈተልኝ። ልሩጥ? መኪና ውስጥ ልግባ? ምን ላድርግ ደረቅኩ!

"ወደቤታችን እንሂድ አይደል?" አለኝ ቁጣም ፍቅርም ፣ ልስላሴም ምሬትም ባለው ድምፅ። አሁንም ምን እንደምለው ግራ ገባኝ። መሮጥ ፈለግኩ። ማምለጥ ! መሸሽ። ገብቶታል። አጠገቤ ደርሶ እጄን ያዝ አደረገው። ሲመጣ እያየሁት ደርሶ ሲነካኝ በረገግኩ። አብሬው ተራመድኩ።

"ስንት ጊዜያችሁ ነው?" አለኝ በፀጥታ ሲነዳ ከቆየ በኋላ

"ምኑ? ማለቴ? " ተንተባተብኩ

"ስታደርጉት የነበረውን ስታደርጉ ስንተኛ ጊዜያችሁ ነው?"

"የመጀመሪያችን"

"ትወጂዋለሽ? በፍቅር ትወጂዋለሽ? ከኔ በላይ ትወጂዋለሽ? "

"ኸረ አልወደውም!" እያልኩት ለምን አይሰድበኝም? ለምን አይጮህብኝም? ለምንድነው ምንም እንዳላደረግኩ ተረጋግቶ የሚጠይቀኝ? እያልኩ አስባለሁ ።

"ፍቅራችን ይህን ማለፍ አይችልም?" አለኝ። ዝም አልኩ።

"ይህን ማለፍ የሚችል ፍቅር የለንም?" አሁንም ዝም አልኩ።

"ይችላል። በደንብ ይችላል!!" ራሱ መለሰ። ድምፁ ውስጥ አማራጭ የለውም::

እቤት ስንገባ አፉ ከመለጎሙ ውጪ ከዛ ቀን በፊት ከሚያደርገው ምንም ዝንፍ ያላለ አመሻሽ አመሸን። አስፈራኝ! ብዙ ክፉ ሀሳብ አሰብኩ። ለዓመታት አቅፌው የተኛሁት ባሌ እንቅልፍ ሲወስደኝ ሲጥ አድርጎ የሚገድለኝ መሰለኝ። እያበድኩ መሰለኝ! ባልጌያለሁ አይደል? ቅድም ባሌ ስባልግ አይቶኝ የለ? ወይስ ቅዠት ነው?

ልክ አይደለማ! ሚስቱ ስትማግጥ በዓይኑ አይቶ ምንም እንዳልተፈጠረ መሆን ምኑ ነው ልክ? ንዴቱ ይቅር እንዴት አላስጠላውም? ለምን ብሎ እንዴት አይጠይቀኝም? ጭጭ አለ። እያጎረሰኝ እራት በላን!! ሶፋው ላይ እግሮቹ መሃል አስቀምጦ አቅፎኝ የጀመርነውን ተከታታይ ፊልም አየን! እሱ አየ እኔ ዓይኔ ቴሌቭዥኑ ላይ እየተንቀዋለለ ቅዠት እሰፍራለሁ::

ከቅሌቴ በፊት

እንደአብዛኛዋ ኢትዮዽያዊ ሴት ዮንቨርስቲ ጨርሼ እስክወጣ "ወንድ ልጅ ኡፉ ነው::" ተብዬ ነው ያደግኩት:: (ምኑጋ እንደሚፋጅ አልነገሩኝም) ይሄ ወንድ የሚሉት ፍጥረት ከአላማ የሚያስተጏጉል... ወደፊትሽን ሊቀጭ አሰፍስፎ የሚጠጋሽ አሰናካይ .... ከብልግና ውጪ ሀሳብ የሌለው ክፉ ፍጡር .... (እንደአላብዛኛዋ ሴት ያሉኝን አምኜ ወይም ፈርቼ ይሄን እርኩስ ፍጡር ስሸሽ አድጌ አላማሽ ነው ያሉኝን ትምህርቴን ተመረቅኩ)

ከዩንቨርስቲ ተመርቄ ስራ እንደጀመርኩ ያ ኡፉ ነው የተባልኩት ወንድ ድንገት በህይወቴ አንገብጋቢ ፍጥረት ሆኖ መጪ ሂያጅ "መቼ ነው የምታገቢው?" ይለኝ ገባ! እሱ በህይወቴ ስለሌለ ከህይወት ወሳኙ ክፍል እንዳመለጠኝ አይነት!!

ስሸሸው ኖሬ ኖሬ ስፈልገው ብቅል የሚል ያስመስሉታል!

እንደአብዛኛው ሀይማኖተኛ ቤተሰብ እንዳላት ኢትዮዽያዊ የባል መስፈርቱ "እግዜርን የሚፈራ" ተብሎ ተምሪያለሁ:: 100 ሺህ እግዜርን የሚፈራ ወንድ ቢኖር ከነዚህ መሃል የኔን ባል የምመርጥበትን መለኪያ አላስተማሩኝም:: ... ከመቶ ሺወቹ የተገኘው ... የቀደመ ... ወይም ይሄን ገፍታሪ መኮሳተሬን የደፈረ...

መጣ! እግዜርን የሚፈራ .... እጅግ ደግና መልካም! ጨዋ የጨዋ ዘር .... አወቅኩት! ለመድኩት!! ወደድኩት!!

"የተባረከ! መሬት የሆነ ወንድ! እድለኛ ነሽ" ተባልኩ::

ቤተክርስቲያን ቆሜ በህመሙም በድካሙም በፎከቱም ..... ላልለየው ብዬ ቃል ገባሁ:: ውብ ነበር:: የመጀመሪያዬ .... የመጨረሻዬ ... ህይወቴ .. ዓለሜ ... ተባባልን!! ኖርን ኖርን ኖርን ..... ሁለት ዓመት .....

የወደድኩት ባሌን ሳይሆን ትዳርን እንደሆነ ገባኝ ... እንዴት? አላችሁ? እሱን ላላገባችሁ እና ለፍሬሽ አግቢዎች አብራራለሁ ያገባችሁ (ቢያንስ 5 ዓመት የሆናችሁ) ገብቷችኃል::

"ልጅ እንውለድ አይደል ፍቅሬ? " አልኩኝ የሆነ ቀን

"ልጅ መውለድ እንደማልችል አልነገርኩሽም እንዴ?" አለኝ ልክ ውይ የላክሽኝን ቲማቲም ሳልገዛ ረስቼ መጣሁ እንደሚባለው ዓይነት ቅልልል አድርጎት .....

(በነገራችሁ ላይ አልጨረስንም)

@wegoch
@wegoch
@paappii

#Meri feleke
እሱ ስለ እሷ


ታሪክ አታሳጣኝ ብላ የምትፀልይ ይመስል የሚተረክ ማንነት አይጠፋትም።ትኖራለች፡ኖራለች።
ድንገት ነው የጠየኳት"ህይወት ውለታ እንድትውልልሽ ብትፈልጊ ምን ትጠይቂያታለሽ?"
"ፈጣሪዬ ብቻ ተስፋዬ እስኪሆን ድረስ በወጀቧ አስረድታ እንድታጠነክረኝ"አለችኝ።
ትገርመኛለች…ብርቱ ናት፤ፈሪም ናት፤ችኩል ናት፤ቀላል ናት።የአጠገቧን በቀረባት ሰዓት ለማድረግ ትቸኩላለች፤አታሳድርም…የዛሬ ልጅ ናት።በየቀኑ የተወለደች ይመስል ለዛሬዋ ህይወትን አትነፍግም።

እኔስ የትዝታ አድናቂ የነገ ናፋቂ ነኝ።ግን አንቃረንም።
"ነበር?ነበር ማን ነው …ንገረኛ…ትላንት የሚባል ቀን ነው?እኔ እስከዛሬ ትላንት በሚባሉ የዛሬ ጥርቅሞች ውስጥ እንደኖርኩ ማን ለነበር ተንታኞች በነገራቸው" በለስላሳ ዛቻዋ እንዲህ ትለኛለች።
…ያልተለመደውን የምትኖር ወይ የተለመደውን ባልተለመደ መንገድ የምታስኬድ ብዬ እንዳልፈርጃት ግራ ይገባኛል ግን በመደናገር ትገርመኛለች…ግን ቀላል ነች።ቀላል ተብለው የተተዉትን ስሜቶች ትኖራቸዋለች።

ለሷ ሁሌ ዛሬ ነው፤ዛሬም ሁሌ ነው።ያላት ይናፍቃታል…"ናፍቆትን ማነው በእርቀት ውስጥ ላለው ነገ የሰጠው"ትላለች።ዛሬን እየናፈቀች ትኖራለች።
አቅፋው የምተኛው ይናፍቃታል…ሸለብ ካረገኝ ትቀሰቅሰኝና "ናፈከኝ" ትለኛለች።
ስታወራ ድምፅህን መስማት አላለችኝም።ስታወራ የምታወጣቸውን ቃላት ግጥምጥም አድርጌ በአይምሮዬ እየሳልኩት ስታወራ ፈዝዤ ልይህ እንጂ።
የአምስቱን የስሜት ህዋሳት ስራ ማዋዋስ በሷ ነው ያየውት።ትንንሽ ከንፈሮቿን በፍጥነት ይያንቀሳቀሰች ሀሳቧን አራግፋ ስታበቃ ዝምምምም ትላለች።ዝምታዋ የንግግሯ ቅጥያ ነው፤ አይጎረብጥም።የዝምታዋ ውበት ያወራኝ ይመስል ዝምታዋን እንዳደምጠው ፍቃዴን ወስዳዋለች።
ቀጠለችና "ናፈከኝ" አለችኝ። "አንተን ማቀፍ እኮ አይደለም(ለግላጋ ፀጉሯን በእጆቿ እያጫወተች) አጠገቤ መሆንህን እየማግሁ ቅርበትህን ማሽተት አለችኝ"… መዳሰስን ስራ አስፈትታ። ኑሮዋን ታስተጋባለች…ተጋባብኝ መሰለኝ እኔም ያለቃላት የምትገልፃቸውን ማድመጥ ናፈቀኝ።ጆሮዬን ድርጊት ላስደምጠው ናፈቀኝ።

@wegoch
@wegoch
@paappii

#heaቨን
2024/09/29 17:31:55
Back to Top
HTML Embed Code: