Telegram Web Link
"ትንሽ ቦታ"

ስሜታዊ ሆኖ ለተናገረን ፣ ሊረዳን ፈልጎ ለሳተ ፣ ኑሮ አስክሮት ለገፋን ፣ ንዴት ገፍቶት ላጠፋ ፣ ግዜ አጣሁ ብሎ ላልጎበኘን ፣ ስናሸንፍ ላላጨበጨበ፣ ስንወድቅ ላላነሳን ፣ ስናስብለት ላልተረዳን ፣ ማደጋችንን ላላየ ፦

"ትንሽ ቦታ ለይቅርታ" አኑረናል

አማረልን ብለን ላሳዘንን ፣ አጉል ተስፋ ለሰጠነው ፣ ውድቀት ላይ ለሳቅነው ፣ ብልግናን ላጎላናው ፣ ድድብናን ላነፈስነው ፣ ማድረግ ችለን ላላደረግነው ፣ ችለን ለተጣመምነው ።

ለራሳችን ይቅርታ አደርገናል...

ቺርስ ለአዲስ ዘመን
ቺርስ ለተስፋችን
ቺርስ🙏.


By Adhanom Mitiku

@wegoch
@wegoch
@paappii
ሌሶቶ

በዝግታ የሚራመዱ ሰዎች ሃገር (Kingdom of the mountains ይላሉ ራሳቸውን ሲያቆላምጡ)
ከፍ ካለ ተራራማ ሃገር ስለመጣሁ "Kingdom of the slow walkers" እላቸዋለሁ እኔ ደግሞ።

ማሴሩ ተራሮች መሃል የከተመች ከተማ ።
ፀጥ ያለች
የተረጋጋች
ወከባ የማይታይባት።

እግረኞቿና አሽከርካሪዎቿ ብንሮጥም የትም አንደርስም የሚሉ ይመስላሉ።

በጠራራ ፀሃይ ብርድልብስ እና ቦት ያደረገ በግ ነጂ ከጂፕ ነጂ ጋር የሚተላለፍባት፣

ደረቅ፣ ነፋሻማና ቀዝቃዛ
(መዘዞ፣ መሃል ሜዳ ወዘተን የምታስታውስ)፣

ሁሉንም ሱቆቿን 12 ሰአት ላይ ዘግታ ወደ ቤቷ የምትከተት፣

በአንዱ የተራራ ጫፍ ትልቅ ነጭ መስቀል የሰቀለች፣ በዚህም አዲግራትን የምታስታውስ።

ባገሬ መስከረም መጋቢትን የመሰለ ደረቅ ወቅት ላይ ተገኘሁ።
እዚህ የክፍል ማሞቂያ 25 ላይ ይደረጋል ከቅዝቃዜ ለመሸሽ (እንደ ኳታር ባለ ሃገር ደግሞ ማቀዝቀዣ 25 ላይ የሚደረገው ከውጪው ሙቀት ለመሸሽ ነው።)

2800 ሜትር አናት ላይ አድጌ 1600 ሜትራቸውን ማድነቅ አልቻልኩም። በመጓዝ ብዛት የገባኝ ተራራ ለብዙ የአፍሪካ ሃገራት ብርቅ መሆኑ ነው /ደብረሲናን፣ ደሴን፣ አሰላን፣ አርሲ ቀርሳን፣ አዲስአበባን ላየ ሰው ማሴሩ የጉብታ ከተማ ነው/።

የዚህ ሃገር ሰዎች ንጉሳቸውን ይወድዳሉ።
ወይም የሚወዱ ይመስላሉ።

ከባድ ባለስልጣን የተባለው ብርድልብስ ለብሶ ስብሰባ ሊመጣ ይችላል።

ሁሉም በሚባል ሁኔታ ክብ ባርኔጣ ያደርጋሉ።

ዶላር ወደ ሌሶቶ ሎቲ መቀየር ፈልገን ካረፍንበት ሆቴል ፊትለፊት ወዳለ ካፌ ነገር መሩን። ሃበሾች ተሰብስበው ያወራሉ። የካፌውም ባለቤት፣ ዶላር ቀያሪውም የኛው ሰዎች ናቸው። ባልተለመደ ሁኔታ እዚህ የሚኖረው ሃበሻ አብዛኛው Expat ነው። የ አፍሪካ ህብረት፣ የ UN ሰራተኛ ወይንም በፕሮጀክቶች የተቀጠረ ሃኪምና ኢንጂነር።

" አንድ የሃበሻ ሬስቶራንት አለ ለበአል እዚያ እንወስዳችኋለን" አሉን።

ድሮ ድሮ የበአል መንገድ ያማርረኝ ነበርና
አንድ ቀን እናቴን
"መንገድ አማረረኝ የበአል ሰሞን ልቅርና በአዘቦት ቀን እየመጣሁ ልጠይቅሽ?" አልኳት።
መለሰች
" ስንት በአል የምናከብር ይመስልሃል ከዚህ በኋላ? ስሞት ትቀራለህ አትቸኩል።"

ዛሬ የአደይ አበባ፣ የበአል ግርግር፣ የመስከረም ምልክት አንዱም በማይታይበት ከተማ ሆኜ ንግግሯን አስታወስኩ።
እንቁጣጣሽ ሲያመልጠኝ ሁለተኛዬ ነው (የዛሬ አመት በጦርነት ምክንያት መንገድ በመዘጋቱ፣ ዘንድሮ በስራ)። ስንት እንቁጣጣሽ እንደቀረኝ ባላውቅም፣ ለኔ ለራሴ የበአል ጉጉቱ ባይኖረኝም ከቤተሰቤ ጋር(ከምወዳቸውም ሁሉ ጋር) የሚኖረኝ ጊዜ የተገደበ ነውና አለመገኘቴ አስደበረኝ።

የመንገዱ ሰልፍና ምሬት፣ የበአል ገበያ፣ የበአል ዘፈኖች፣ የእናቴንና እህቴን ቤት ውስጥ ወዲያ ወዲህ ማለት፣ የአባቴን ደጁን ለእርድ ማስተካከል፣ የወንድሜን ለቅዳሴ ለመሄድ መዘጋጀት፣ አልፌ የምሄድባቸውን አረንጓዴና አበባ የለበሱ ሜዳዎችና ተራሮች እናፍቃለሁ።

ከቤተክርስቲያን መልስ ስለምንበላው ጥብስ፣ ከፋዘር ጋር ተጋግዘን ስለምንገፈው በግ፣ በደምብ ስለማላውቃቸው ጎረቤቶች፣ ስለ ብዙ የስልክ ጥሪዎችና መልዕክቶች፣ ስለ ድፎ ዳቦ፣ ስለ ቡና አስባለሁ።

እዚህ ያለው ቡና በጣም ቢቀጥንብኝ ከኢትዮጲያ መሆኔን አውቃ "ሰላም ነው?" ያለችኝን አስተናጋጅ ፈልጌ ጠራሁ።
"This coffee is too weak I need somthing strong"
"Our coffee is not like yours".

የጀበና እጣቢ የሚመስል ነገር እየጠጣሁ አለሁ። ሆድ ለባሰው ....

ከበአል ድባብ ያላመለጠኝ ብቸኛ ነገር የፌስቡክ ፖስትና የቴሌግራም ስቶሪ ነውና ....

ሁላችሁንም እንኳን አደረሳችሁ።
መልካም አዲስ አመት።

ወንድማችሁ ነኝ ከጉብታዎች አናት ማሴሩ።

By haileleul Aph

@wegoch
@wegoch
@paappii
«ካባዬ»
(ከለእርቃን ሩብ ጉዳይ መፅሐፍ)

ክፍል አንድ

------------
ይሄንን ኮንዶሚኒየም ቤት ለማግኘት ከሦስት ወር በላይ ተንከራትቻለሁ።

ኪራይ ነው።
ዛሬ ዛሬ አዲስአበባ ላይ ፍላጎትንም፣ አቅምንም አጣጥሞ የሚገኝ የኪራይ ቤት
ማግኘት ሕልም ነው። እኔ ደግሞ የብር ችግር እንደሌለበት ሰው ስመርጥ ዐይን
የለኝም። ሀብታም ስላልሆንኩ ጠባብ ቤት መኖር ይፈረድብኝ፣ ግን ጠባብም
የተግማማም መሆን አለበት?



የለበትም።
ለዚህ ነው ይህንን አራተኛ ፎቅ ላይ የሚገኝ በጣም ጠባብ ግን ንጹህና ሰላማዊ
ስቱዲዮ ኮንዶሚኒየምለማግኘት ሦስት ወራት የፈጀብኝ። ከንጽሕናው ፀጥታው፣
አራተኛ ፎቅ ጥግ ላይ ክትት ብሎ መገኘቱ ማረከኝና ተከራየሁት።


ግን ይሄ ታሪክ ስለ ተከራየሁት ስቱዲዮ ኮንዶሚኒየም አይደለም።
ስለንጽሕናውና ስለፀጥታውም አይደለም። ስለሰፈሩ ከተማ መሀል መገኘትም
አይደለም። ስለ አዲሷ ጎረቤቴ እትዬ እማዋይሽ ነው።


ታኅሳስ ላይ ቤቱን ቀለም አስቀብቼ፣ እቃዎቼን ሸክፌ ገባሁ።


በገባሁ ዕለት ነው እትዬ እማዋይሽን ያገኘኋት እና የተዋወቅኳት።

ቅዳሜ ነበር። ከቀኑ ዘጠኝ ሰዐት ይሆናል።

እሷ፣ ፎቁን እያረፈች እንደወጣች በሚያስታውቅ ሁኔታ ትንፋሽዋ ቁርጥ ቁርጥ እያለና እያለከለከች በሬ አጠገብ የሚገኘው በሯ ጋር የቤቷን ቁልፍ እያንቀጫቀጨች ስትደርስ፣ እኔ ደግሞ ውስጥ ያለውን እስካስተካክል ውጪ የተውኳቸውን ኮተቶቼን ወደ ቤት ለማስገባት ስወጣ ነው፣ ፊት ለፊት የተገጣጠምነው።

እንዳየኋት የተሰማኝ ነገር ያለቦታዋ የምትገኝ ሰው መምሰሏ ነበር።

በዕድሜ ስልሳ ቤት ትሆናለች።

ነገር ግን ሙሉ በሙሉ የሸበተው ጸጉሯ ብዙ ጊዜ ዕድሜያቸው የሄደ ሰዎች ላይ እንደማየው ስስና እንክብካቤ ያጣ አልነበረም። ዘንፋላና በሥነ-ሥርአት የተተኮሰ ነበር። አለባበሷ አሁንም በእሷ ዕድሜ ያሉ ሴቶች እንደሚዘወትሩት ሰፊ ልብስ ላይ ሌላ ሰፊ ልብስ፣ ግራጫ ቀለም ላይ ቡናማ፣ ወፍራም ሹራብ ላይ ወፍራም የአንገት ልብስ ዓይነት አልነበረም።
ደልደል ያለና ውብ ሰውነት አላት።

በልኳ ግን ሳይጠብ የተሰፋ ቆንጆና ደማቅ ቢጫ ቀሚስ፣ አጠር ካለ ሰማያዊ ክፍት ሹራብ ጋር ለብሳለች። ተረከዙ አጭር፣ ፊቱ ሹል ጥቁር ጫማ አድርጋለች። የምታምር ትንሽዬ ቡናማ ቦርሳ አንግታለች።

ደርባባ ነች። ዘንጣለች።

“እንዴት ዋልሽ ልጄ?” ስትለኝ ነው ዕድሜዋን ከዝነጣዋ ያስታረቅኩት።

“ደህና ይመስገን” አልኩኝ ፈጠን ብዬ።

“ጎረቤትሽ ነኝ… እንኳን ደህና መጣሽ… እማዋይሽ እባላለሁ”
“አመሰግናለሁ… ኤደን እባላለሁ” መለስኩላት።
“ሳናግዝሽ ገባሽ… አሁን ምን ልርዳሽ?” አለች ዐይኖቿን ተመሳቅለው
የተኮለኮሉት ውጪ የተዘረገፉ እቃዎች ላይ አሳርፋ።

“ግዴለም ብዙ አይደለም ጨርሻለሁ” አልኩ አሁንም ፈጥን ብዬ።

“በይ ስትረጋጊ ቤቴ ነይና ቡና ጠጪ” አፈር አልኩና፣

“አይ…. እሱ እንኳን ሌላ ቀን” አልኩ። እያግደረደረችኝ ከሆነ መግደርደሬ ነበር።

“ኖንሴንስ… እያግደረደርኩሽ አይደለም… ጎረቤት መተዋወቅ አለበት። ቡና
ማፍላቴ ስለማይቀር እቃሽን ቦታ ቦታ አስይዢና እንጠጣለን”

አሁን ጥያቄ አልነበረም።

ትልቅ ሰውም ስለሆነች፣ ጥያቄም ስላልነበር ምርጫ አጥቼ እሺ አልኳት።
ዐሥራ አንድ ሰዐት ገደማ ላይ የብረት በሬ ተንኳኳች።

እማዋይሽ ነበረች።

“ነያ ቡናው ደርሷል” አለችኝ።

በሬን ቆልፌ ተከትያት ቤቷ ገባሁ።

ቤቷ፣ አዲስ በተቆላ የቡና ጠረንና ለአፍንጫ በሚጥም ዕጣን ጭስ ተጨናንቃ
ተቀበለችኝ።

ረከቦትና ስኒዎቹን በዐይኔ ብፈልግ የሉም። ዕጣን ማጨሻውን ለማግኘት ብሞክር
አልቻልኩም።

ከመቀመጤ፣ “ዛሬ ገብተሽ መቼስ ምግብ አልሠራሽም” ብላ ምን የመሰለ
ፍርፍር አበላችኝ።

ጎንደር ያለችውን ባለሙያ እናቴን አስታወሰኝ።

(ይቀጥላል)

By Hiwot Emishaw


@wegoch
@wegoch
@paappii
< "እናርግ" አለኝ እኮ፣ ያ ውሻ >

ምናለበት እሺ ብትዪው ? ምትወጂው ከሆነ ስሜቱ ለጋራ ነው ፣ አይደለም እንዴ?

< አንተ ሐይሚን አርገሀታል? ንገረኝ። >

"አድርገሀታል" ማለት? ምን አደረኳት? "

< ሒይ ! እያወክ አትገግም። >

"በድተሀታል ወይ ? ማለት ፈልገሽ ከሆነ ፣ በድቻታለሁ። ብድትድት ነው ያረኳት። ካንቺ ጓደኞች ያልበዳሁት የለም። "

< እህ ? ውሻ! ውሻ ነህ ።>

አዎ ነኝ ! ዉው ዉው ኣዉዉዉዉዉ ። ሀያትንም በድቻታለሁ።

ሀያት ነች ያስተዋወቀችን። ሀያት የጥቁር ቆንጆ ፣ እንደ እሳት ቅልብልብ ፈጣን ውልብልብ እጅግ ብልህና በትምህርትም ጎበዝ ተማሪ የነበረች ናት። ኤለመንተሪ ከሀያት ጋር ስንማር ጥያቄ ና መልስ ውድድር እኔና እሷ ከፍላችንን እየወከልን ዞረናል። ሀይስኩል እንደገባን ሀያት ናት ከዚህችኛዋ አለም ጋር ያስተዋወቀችን። ከአስረኛ ክፍል በሁዋላ ሀያት የት እንደገባች አናውቅም። እኔና አለም ግን አስር አመት ሆነን። በጓደኝነት። ንፁህ የሚባለው አይነት ጓደኝነት።

*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*

አለም

< ወዬ >

" አለም የሚል ስም ይዘሽ እንዴት መንፈሳዊት አማኝ ሆንሽ ? "

< አንተማ ለይቶልሀል። >

ሁሌም ከፍቅረኞቿ ምትለያየው የወሲብ ጥያቄ ሲያቀርቡላት ነው። እሷ "ከጋብቻ በሁዋላ" ትላቸዋለች። እነሱ ጥለዋት ሲሄዱ መጥታ እኔ ላይ ታለቅስብኛለች። ይበዳኛል ብላ ሰግታ አታውቅም።

እኔ ብበዳሽስ ? እላታለሁ።

ሁሌም < ሐይሚን አርገሀታል? እስካሁን ስንት ሴት አወጣህ? > ትለኛለች።

"ስንቷን ሴት ስንት ስንት ጊዜ እንዳወጣሁ ልንገርሽ ? ሐይሚን ...ሐያትን ደሞ እእእ ?"

< ኡህ! አንተስ ባልገሀል >

ትለኛለች።

*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*

በስጋ እናትም አባትም። ቤተሰቦቿ አሳዳጊዎቿ ናቸው። እና እኛ። እኛ ማለት እኔና ሌላ ማላውቃቸው ጓደኞቿ።

< አንተ ቤተሰብ ስላለህ እድለኛ ነህ > ትለኛለች።

" እኔ ቤተሰብ እዳ ነው " እላታለሁ።

*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*

ያኔ ሐያት ከእሷ ጋር ካስተዋወቀችን ማግስት ወደኔ ክላስ እየተጎተተች መጣች። ፀይም ነበረች ግን አመዳም። ፀጉሯ ረጅም ነው፣ ግን ደረቅ ነው። ጥቁር ሻርፕ አንገቷ ላይ ጣል ታደርጋለች ፣ ለምን እንደምታደርግ አይገባኝም። እናም ያግባባን ብቸኛ ነገር እኔ ብልህ እንደሆንኩ ማሠቧ ና እሷ ብርቱ ስለሆነች ከእሷ ጋር እንደምስማማ ስለምታስብ ነው።

እኔስ ? እኔ ትምህርት ላይ እየቀነስኩ አሪፍ መስሎ መታየት ላይ እየበረታሁ ነበረ። ቀንደኛ ቀልደኛ ሚባሉት ተማሪዎችን ጎራ ተቀላቀልኩ። ሁሉም ጓደኞቼ ድንግል ሆነው ሳሉ ቀድሜ ገርልፍሬንድ ያዝኩ፣ ቆንጆ ሴት፣ ከሌላ ክፍል፣ ሐይማኖትን ። በርግጥ ኤለመንተሪ እያለሁ የሔርሜላን አንገት ስሜያለሁ። ከነሱ መፍጠኔ ለእኔ አይገርመኝም።

እና ይህቺ አለም < ትምሕርትህ ይበጅሀል። እሷን ተዋት። ገና ልጅ ነህ። ደግሞም ቆንጆ አይደለችም።> ትለኝ ነበረ።

ግን ሁለታችንም በእድሜ እኩያሞች ነን። እሷን መካሪ እኔን ተመካሪ ያደረገን እሷን ለይቶ የመከራት ኑሮ ነው።

ኑሮ ያስተማራትን ትምህርት በደንብ ይዛዋለች። ፈተናውንም አልፋዋለች። አሁን ዘናጭ ነች። ፀይም መልኳም ፀጉሯም ወዝ ኖሮታል። ለስራ ሌላ ሀገር የሄደች ጊዜ ገንዘብ እኔ አበድራት ነበረ። ሁለት ጊዜ ሌባ ሙልጭ አድርጎ ዘርፏታል። አሁን እኔ ገንዘብ ሲቸግረኝ ከእሷ ነው የምበደረው። የወር ገቢዋ ከእኔ የወር ደመወዝ አስር እጥፍ ነው።

*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*_*

አስረኛ ክፍል ተዋወቅን ፣ አስር አመት አብረን አሳለፍን ። አሁን ልታገባ ነው። ሰርጓ በቅርብ ነው።

<አንተ መቼ ነው ምታገባው ? >

ብዙ ፍቅረኞች አሉኝ ። የቷን ላግባ?

< ባለጌ

ሐይሚን አሁን ብታገኛትስ ? >

አስር አመት ሙሉ ሐይሚን ያልረሳሻት ለምንድን ነው ?

< ሐይሚን አይደለም ያልረሳሁት። ያንን የግቢውን ቆንጆ፣ ብልህና ትንሽዬ ልጅን ልረሳው ያልቻልኩት። የአስራስድስት አመቱን ያንን ናሁ መሆን እፈልግ ነበር። አሁን ላይ ግን እዚህ ሆነን ደግሜ እሱ ራሱን ሆኖ ማየት እመኛለሁ >

" እመኚኝ። እኔ ምንም ከስሬ አላውቅም። እናም የራሴን መንገድ አገኛለሁ። ሚስትም አገባለሁ።

አንቺ ትንሽ ቀደም ብለሽ ሒጂ። አግቢ። እኔ ባንቺ መንገድ አልሄድምና። መልካም መንገድ። መልካም ጋብቻ።

ለባልሽ የምነግረው ነገር አለኝ ፦ " እሷን እቅፌ ላይ ለብዙ ቀን እንዳሳደርኳትና ከእሷ ገላ ላይ የወሰድኩት ምንም ነገር እንደሌለ ነው።

ስላልፈለኩ። ወይ ፈልጌ ስላልቻልኩ። ወይ ችዬም ታማኝ ሆኜ ይሆናል።

እኔ ባለቤቷ ነኝ። አሁን አንተ ባሏ ልትሆን ነው። ይትባረክ"


By Nahu senay

@wegoch
@wegoch
@paappii
የሄደበትን የመጨረሻ ቀን አስባለሁ።

ኩራቱን ተገፎ ሀፍረትን ተከናንቦ እርቃኑን እንደቆመ ሠው ዐይኔን ሽሽት አንገቱን ደፍቶ መሬት መሬት እያየ "እሜትዬ በድዬሻለሁ…" ያለበትን ቃና እሰማለሁ። ምህረት ፍለጋ ለይቅርታ አልመጣም ነበር። አንዳንድ ሀጥያቶች ስርየት የላቸውም፤ ስለአንዳንድ በደሎቻችን ከራሳችንም እርቅ አይኖረንም። ለዋለው ክህደት ይቅርን አልፈለገምና የኔ ይቅር ማለት ትርጉም አልነበረውም። የኔ ምህረት መስጠት ኩራትና ክብሩን ከወደቀበት ሊያነሳለት አቅም አልነበረውም። አንገቱን ደፍቶ በገባበት በር አንገቱን ደፍቶ ሲወጣ ቃል አልወጣኝም። አልተከተልኩትም በዐይኔ አልሸኘሁትም። ልቤ መመለሱን ቢሻ ከበደሉ ሊያልቀው ግን አልተቻለውም። በሰው ለውጦሻል ተይው ይሂድ አለ፡፡ ተውኩት፣ ሄደ…አልተመለሠም ።

ዘመናቶቼ መኸል ግን እጠብቀው ነበር። አንዱን ቀን ይመጣል ብዬ በር በሩን አማትሬያለሁ። ወሬውን ፍለጋ ጆሮዎቼ እልፍ ጊዜ ቆመው የደጁን ድምፅ ሲቃርሙ ኖረዋል። ብዙ ጠብቀዋል፤ ለማንም ሳልነግር በደሉን ውጫለሁ። ባሻዬ ከዳኝ ሳልል ይቅር ብዬ ነበር። ፍለጋ ባልወጣ የት ሄደ ባልል በልቤ በእየዕለቱ 'አንተ ትሻላለህ፤ ተመለስ ግድ የለም' እል ነበር።

እወደው ነበር፤ ኩራት በሸበበው ፈገግታ ቢደበቅም ቅሉ ሳየው ልቤ የፈካ ቀለምን ትፈነጥቅ ነበር። እንደነዛ የመጀመሪያ ቀናት ጠጁን እየተጎነጨ ጓዳውን ሲያማትር በዐይኑ ሲፈልገኝ ትንሿ ልቤ በመጋረጃ ተከልላ እያየች ትደልቅ እንደነበረው፤ እንዲያ…እንዲያ እወደው ነበር። እነዛ ጊዜ ሸምኗቸው ጋቢ ሆነው የለበሳቸው የጥጥ ማጎች ስለሱ እያሠብኩ ሳሾራቸው፤ ተበጥሰው እንደተንከባለሉ ስንት ወድቀው ስንት እንደተነሱ፤ ስንት እንዝርት እንደሰበሩ አያውቅም፤ አልነገርኩትም ለፍቅር ሰነፍ ነበርኩ ።

By Beza Wit

@wegoch
@wegoch
@paappii
አገባሁ...ወለድኩ...ደገምኩ...ሠለስኩ:: እሱን እያፈቀርኩ ከወንድሙ ሦስት ልጆች ወለድኩ:: እሱን እየተመኘው ወንድሙን አገባሁ:: ካሳለፍናቸው 3 የUniversity ጓደኝነት አመታት በኃላ እንደተመረቅን ነበር ላገኘው እንደምፈልግና ብቻውን እንዲመጣ የነገርኩት ገና ተደላድሎ ከመቀመጡ ነው " አፈቅርሀለው" ያልኩት ::ሳቀ በሀይል ሳቀ
"አንቺ ያምሻል እንዴ ለቁም ነገር ነው ምፈልግህ ስትይኝኮ ምን ሆነች ብዬ ስንት ነገር ነው ጥዬ የመጣሁት ትቀልጃለሻ አንቺ ሆሆ " አየሁት .. እነዛ መጀመሪያ ካየዋቸው ቅፅበት ጀምሮ ራሴን ያሳጡኝን አይኖቹን ትኩር ብዬ አየዋቸው ::ሚያረገው እየጠፋው ሁሌ እንደሚጠራኝ
" ቃሊ የምርሽን ነው እንዴ "
"አዎ አፈቅርሀለው" ፊቱን በአንዴ ወደ ግራ የተገባ ፊት ቀይሮ " ከመቼ ጀምሮ ቃሊ?"
"ከመጀመሪያው የሁለተኛ አመት የትምርት ቀናችን ከማክሰኞ ከመስከረም 22 ጀምሮ" ደነገጠ " ቃሊ please አታሹፊብኝ " ፊቱ ሲቀላ እየታወቀኝ መጣ
"ምንም እንድትለኝ አይደለም ብንጋባ ብታፈቅረኝ ምንምን በደስታ ልሞትብህ ስለምችል አላቅም ግን እህቴ ነሽ ምናምን እንዳትለኝ ደሞ" መንተባተብ ጀመርኩ ::
"ቃሊ"
"ወዬ" ልቤ በፍጥነት ስትመታ ይታወቀኛል
"ኤላኮ ያፈቅርሻል" ፊቱ ማላቀውን እሱን ሆነብኝ..ውስጤ ሲፈረከስ ተሰማኝ ኤላ ማለት? ኤላ የሱ ወንድም? ማለት መንታ ወንድሙ ኤላ ? ኤላ ጓደኛዬ? ኤላ ኤላ ውስጤ ተተራመሰ.....በመልክም በአመልም ምንም አለመመሣሠላቸው ሲገርመኝ ነበር ሶስቱን የጓደኝነት አመታት ያሳለፍነው :: ሁሌም አብረን ነበርን እሱም..ኤላም...እኔም :: በሁለት መንታ ወንድማማቾች መሀል ያለው ብቸኛ ጓደኛቸው በመሆኔ ጊቢ ውስጥ እንደኔ ደስተኛ ሰውም የነበረ መኖሩን እኔንጃ እኔን መሀል አርገው ሲተራረቡ መስማት...ሲበሻሸቁ...አንዳቸው እንዳቸው ላይ ሲቀልዱ ...እጄን የኔው ተፈቃሪ እንደቀልድ በቦክስ ሲመታኝ ኤላ ሲቆጣው...ተሸክመውኝ ሲሯሯጡ ላየን 3 መንታዎች እንጂ ማልዛመዳቸው መሆኔን ማንም አይጠረጥርም አንዳንዶቹ ደሞ የማንኛው ናት እንደሚሉም አቃለው :: የጊቢው ሴቶች ደሞ ኤላን ይወዱት ስለነበር እንዳጣብሳቸው ሚወተውቱት እኔን ነው ኤላ ግን ወይ ፍንክች ስለሚል ማጣበሱ አልተሳካልኝም ነበር :: ሲፈጥረኝ ከሴት አትዋደጂ ያለኝ ይመስል ከልጅነቴ ጀምሮ ሴት ጓደኛ ኖሮኝ አያውቅም ጊቢ ገብቼም የመጀመሪያውን freshman አመት ከማንም ጋር አልግባባም ነበር ከዛ ግን ሁለተኛ አመት ላይ ምንማረውን ትምርት መርጠን ስንመደብ እነሱን አገኘው ለዛም ነበር በጓደኝነታችን ደስተኛ የነበርኩት :: ከ6ኪሎ ጊቢ በታች ያሉ ማሚ ቤቶች ሄደን ምሳ ስንበላ በእጄ ከአንድ ጉርሻ በላይ ስጎርስ አላስታውስም በሁለቱ የፉክክር ጉርሻ ነበር ጠግቤ ምነሣው በዛ ላይ ሳየው ገና ልቤ የደነገጠለት ልጅ ጓደኛ ሆኜ ስስቅ መዋል ..ደስታ ማለት እኔ ነበርኩ:: "ጉድና ጅራት ወደ ኃላ ነው" አሉ....ያን ቀን "ኤላኮ ያፈቅርሻል " ሲለኝ ጉሮሮዬም ልቤም አይምሮዬም ደረቀብኝ ጎኔ ያለውን ግማሽ ኮካ አንስቼ ጨለጥኩት ::
"ኤላ የቱ" አይኖቼ ሲፈጡ ይታወቀኛል
"ቃሊ ኤላ የኛ ነዋ "ፊቱ የማላቀው ቋንቋ ፅሁፍ ሆነብኝ አየዋለው አይገባኝም ::
"ከመቼ ጀምሮ?" እሱ እንዳለኝ እኔም አልኩት ማወቄ ይቀይረው ያለ ነገር ይመስል
"ካየሽ ቀን ጀምሮ ቃሊ ትዝ ይልሻል class እንደጀመርን ካፌ አጊኝተንሽ ብቻሽን ከምትበዪ ከኛ ጋር ምሳ አብረን እንብላ ብዬሽ አብረሽን የዋልሽ ቀን " እንዴት እረሳዋለው ያን ቀን በአይን ካፈቀርኩት ሰውጋር አምላክ አገናኘኝ ብዬ በደስታ ስፈነድቅ ነበር የነጋው :: ፀጥ ብዬ ሳየው ወሬውን ቀጠለ "ያን ቀን ማለት ኤላ ካላስተዋወከኝ ብሎ ሲለምነኝ ነበር ታውቂያለሽ ቃሊ ኤላን ከማህፀን ጀምሮ ሳውቀው ከአፉ ወቶ ሚያውቀው የሴት ስም ያንቺ ብቻ ነበር :: ቃሊ ኤላ አንቺን ስለማግባት ካንቺ ስለመውለድ ብቻ ነውኮ ሚያልመው ደሞ እሱም ከዛሬ ነገ እነግራታለው እያለ ነውኮ የተመረቅነው ቃሊ ኤላን ያዢው ወንድሜ እስከነፍሱ የሚያፈቅራት ሴት ታፈቅረኛለች ብሎ ማሰቡ ለኔም በሽታ ነው ቃሊ ደና ዋይ ኤላን ያዢው" ብሎኝ ነበር በተቀመጥኩበት ጥሎኝ የሄደው "ኤላን ያዢው" ይሄን ነበር ያለኝ :: .....እኔም ኤላን በእጄ በልቤ እሱን ይዤ ይኸው ሶስተኛ ልጃችንን ወለድን:: .....ኤላ ህልሙን ኖረ እሺ እኔስ?? የሱ ህልም ማስፈጸሚያ ልሆን ነበር የተፈጠርኩት? ያፈቀሩትን ስለማግኘት ኤላ ያሟላው እኔ ያጎደልኩት መስፈርትስ ምን ነበር??? ልጆቼስ አጎታቸውን በልቤ አግብቼ እንደምኖር ያወቁ እንደሆነ እንዴት ይዳኙኝ ይሆን ? እንጃ....ሁሉም ያፈቀረውን አያገባም..ልክ እንደኔ::


By ቃል_ኪዳን


@wegoch
@wegoch
@paappii
God,have mercy! This woman is so obsessed with her life. With her home and her family.

በጠዋት ትነሳለች ቁርስ ትሰራለች ቤተሰቦቿን ታበላለች ታጠጣለች መጥገባቸውን ታረጋግጣለች ከዛም ወደየሚሄዱበት ትሸኛቸዋለች። ቀጥላ ወደቤቷ ጽዳት ፣ ወደእንጀራ ጋገራ ፣ ምሳ ማሰናዳት ወዘተ.... አቤት ያላት ፅናት! ለጉድ ነው! ቤት ጠርጋ ወልውላ አጫጭሳ ልብሶች አጥባ እቃዎቹ ታጥበው ደርቀው በየቦታቸው ተደርድረው።
ወጡ ችክን ብሎ ተሰርቶ፣ ቡናው ትክን ብሎ ፈልቶ እጣኑ እየጤሰ ምሳ 'ሳት ይደርሳል። በር በሩን እያየች የቤተሰቧን መምጣት ትጠብቃለች ሲመጡላት በሚገባ ታስተናግዳቸዋለች።

በፈገግታ እና በምግብ ከፈወሰቻቸው በኋላ መልሰው ወደየሩጫቸው! "አመሠግናለሁ"ን እንኳን ሳትጠብቅ በሳቅ በፈገግታ ሸኝታ ወደቤቷ! የተበላበትን የተጠጣበትን እቃ አጥባ፣ የተዝረከረከውን ቤት አበጃጅታ ስታበቃ ደግሞ ለእራት ዝግጅት ጉድ-ጉድታዋን ትጀምራለች። ጣፋጭ ምግብ አብስላ፣ ሙቅ ሾርባ ሰርታ ቤቷን አሟሙቃ ትጠብቃለች። ወዳሞቀችው ጎጆ ይሰበሰባሉ ከእጇ ፍሬም ይበላሉ።

ይሔ ብቻ አይደለም she is psychiatrist ,she is economist, she is event organizer, she is expert in negotiation and an incredible socialist!

ይህች ሴት እናቴ ናት❤️

ምኞትሽ ምንድነው ብባል " እንደሷ መሆን" እላለው።


By Magi

@wegoch
@wegoch
@paappii
2024/09/21 12:30:52
Back to Top
HTML Embed Code: