Telegram Web Link
‹‹ሲስተርሊ- ብራዘርሊ››
(ከሕይወት እምሻው)
-----------------------
ከዶ/ር መረራ ኢንትሮዳክሽን ቱ አፍሪካን ፖሊቲካል ሲስተምስ ክላስ ስንወጣ ‹‹
ዛሬ ተሳክቶልኝ ኤፊን ላስተዋውቅሽ ነው›› አለኝ ክብሮም፡፡ ክብሮም፣ በእሱ ቤት ‹‹ንፁህ›› ጓደኛዬ ነው፡፡
(በነገራችን ላይ…ንፁህ ጓደኛ ሲባል ያስቀኛል፡፡ ወንድና ሴት ‹‹እሱ እኮ ንፁህ
ጓደኛዬ ነው…እሷ እኮ ንፁህ ጓደኛዬ ናት›› የሚባባሉት ወንድና ሴት ሆነው
ለፍቅርና ለድሪያ ስላልተፈላለጉ፣ ለስጋ ፍላጎታቸው እጅ ስላልሰጡ፣ ለ‹እንስሳዊ›
ስሜታቸው ባሪያ ስላልሆኑ ልዬ ፍጡር እንደሆኑ እንዲታወቅላቸው
ስለሚውተረተሩ ይመስለኛል፡፡ የጉብዝና አክሊል ድፉልን ለማለት ሲያሽቋልጡ
ይመስለኛል፡፡ አለ አይደል….‹‹ እዩንማ…እሷ ባለሽንቁር፣ እኔ ባለቃጭል
ብንሆንም መደራረግ አንፈልግም…በሌላ ነገር አንፈላለግም….ግንኙነታችን
ንጹህና ቅዱስ ነው….ልዩ ፍጡሮች አይደለንም? እንደነ ቀነነኒሳ ወርቅ ሜዳሊያ አይገባንም አይነት ነገር…)
እና ክብሮም በእሱ ቤት ንፁህ ጓደኛው ነኝ፡፡ ሰፊ ዳሌ፣ ትላልቅ ጡቶች
ቢኖሩኝም፣ የወር አበባ ባይም ከወንድ ጓደኞቹ ለይቶ የማያየኝ ጓደኛው፡፡
በእኔ የቀቢፀ ተስፋ ምስኪን ቤት ግን የወደፊት ባልና ሚስት ነን፡፡ በእኔ ቤት ግን
ኬቢ የምመካበት ባሌ፣ የምሳሳላቸው ልጆቼ አባት ነው፡፡ በህቡእ እወደዋለሁ፡፡
ኪቢዬ ኦክስጂኔ! ሳልነግረው አፈቅረዋለሁ፡፡ ‹‹በመጨረሻ ከኤፍሬም ጋር ልታስተዋውቀኝ ነው…?›› አልኩና መለስኩለት ፡፡ ‹‹እህ! ድሬ ሁለት አመት ውጣው ነው እንጂ ድሮ ነበር ማስተዋውቃችሁ፡፡ ትወጂዋለሽ….›› አለኝ ዘወትር በክፍሎች መሃከል ወደምንቀመጥባት ለእኛ
የተሰራች የምትመስለኝ የድንጋይ ወንበር ላይ ቀድሞኝ ሄዶ እየተቀመጠ፡፡
‹‹ትወጅዋለሽ›› አባባሉ ሌላውን ነገር ካለበት ሁኔታ ይለይ ነበር…የሆነ አፅንኦት… የሆነ ትኩረት ነበረው፡፡
ቁጭ ካልን በኋላ ትናንሽ አይኖቹን በትላልቅ አይኖቼ እያየሁ ‹‹ በአካል አንገናኝ እንጂ በዚህ ሁሉ አመት ወሬ ማውቀው ማውቀው ነው ሚመስለኝ….ለነገሩ ያንተ
ቤስት ፍሬንድ ከሆነ ምክንያት አለው….ላልውደው አልችልም›› አልኩት፡፡ ‹‹አሃሃ….ለነገሩ ልክ ነሽ…ኤፊ ከግምት በላይ አሪፍ ልጅ ነው…ትወጅዋለሽ…..›› ሶስት አረፍተነገር ሳንመላለስ ሁለት ጊዜ ‹‹ትወጅዋለሽ›› ፣ ያውም በ‹‹ እርግጠኛ ነኝ…አብራችሁ ትሆናላችሁ›› ስልት ማለቱ በእሱ ቤት ንፁህ ጓደኛ የመሆናችን አንዱ ማረጋገጫ ነው፡፡ አዲስ መረጃ ባይሆንም ልቤ እንደጎማ
ተነፈሰች፡፡ ግን ወሬ አላቆምኩም፡፡
‹‹ምነው ትወጅዋለሽ ትወጅዋለሽ አበዛህ? ልታጣብሰን አስበሃል እንዴ?›› አልኩና ፊቱን ለስሜት ለውጥ በሚመረምር አኳሃን አበክሬ ፈተሽኩ፡፡ ሲደነግጥ ወይ ሲያፍር፣ ወይ የደበቀው ነገር ሲታወቅበት እንደሚሆነው ቀይ ፊቱ አልደፈረሰም፡፡ ሲከፋ ወይ ቅር ሲሰኝ እንደሚሆነው አይኖቹ ይበልጥ አልጠበቡም፡፡ ያልተለወጠ ፊቱን እያየሁ መልሱን ሰማሁ፡፡ ‹‹እና ታዲያስ…ኤፊን አግኝተሽ ነው?›› አለኝ፡፡ ምንም ተስፋ የለኝም፡፡
፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥፥
የዚያኑ እለት ከሰአት ፤ በወሬ ከገነባሁት በአካል ከማላውቀው ኤፍሬም ጋር
ተዋወቅን፡:፡ ገና ለገና ኬቢን ስለምወደው…. ኤፍሬምን የመሰለ ልጅ በደብዛዛው ገልጬ፣ አገኘሁት ብዬ ማለፍ ፍትህ ማጓደል ነውና ዘርዝሬ ልንገራችሁ፡፡ ኤፍሬም ፣ ‹‹እስቲ አለሁ የሚል ወንድ ያንበርክከኝ›› ብላ በትእቢት ተወጥራ የመጣችን ሴት ባንዴ የሚያርበደብድ መልካና ቁመና አለው፡፡ እመኑኝ፤ የማያምር ነገር የለውም፡፡ አባቴ ይሙት፣ ጆሮዎቹ ሳይቀሩ ያምራሉ፡፡ የእግሮቹ ጣቶች እንኳን ያምራሉ ( ድሬ ለምዶበት ነው መሰለኝ በአዲስ አበባ
ብርድ ቄንጠኛ ነጠላ ጫማ አደርጎ ነው የመጣው) ፤ ቁርጭምጭሚቱ እንኳን
ያምራል (ከቁምጣ ረዘም፣ ከመደበኛ ሱሪ አጠር ያለ ‹‹ሚዲ›› ቱታ ነው የለበሰው)፡፡ ሰውነቱ ለሚበላው የሚጨነቅ፣ መንቀሳቀስ የሚወድ መሆኑን ይነግረኛል፡፡ ግን ደግሞ ሌት ተቀን ብረት እያነሳ በአንድ ደረት ላይ ሰላሳ ሶስት ቦታ ፈርጣማ ጡት አውጥቶ የመጠጥ ቤት ቦዲ ጋርድ ከሚመስል ሰው ጋር (በጣም የምጠላው ሰውነት…አቦ ቦርጭ ሁላ ይሻለኛል) የማይመሳሰል አይነት ነው፡፡ አለባበሱ ዘመነኛ፣ ወንዳወንድነቱ ግን የድሮ ነው፡፡ አለ አይደል…ስኪኒ ሱሪ አድርጎ መጥቶ ልክ ግሩም ኤርምያስ የአምባሳደርን ሱት ለብሶ ሲመጣ እንደሚሰራው ነው የሚሰራው…ሴት የሚያቅበጠብጥ ወንዳወንድነቱ ስኪኒ ከሚለብሱ ወንዶች የማይገኝ ህልም ነው፡፡ በዚያ ላይ ንፅህናው ያስገርመኛል….ሁሌም ልክ ከሻወር ሲወጣ ያገኛችሁት የሚመስል ንፅህና አለው…አባቴ ይሙት በልጅነቱ ንፍጥ ምናምን ተጠርጎለት ያደገ ሁሉ አይመስለም…ይህንኑ ልብሱን ለብሶ…ሽር ብትን ብሎ ከእናቱ ማህፀን
‹‹ወክ›› አድርጎ የወጣ እንጂ እንደሌሎቻችን በምጥ ተደናብሮ፣ አምርሮ እያለቀሰ…በምናምን ተሸፍኖ የተወለደ አይመስልም፡፡ ሲያወራ የረጋ፣ ግን ደግሞ ተጫዋችም ነው፡፡ ጋግርታምም አይደል፣ ቀለብላባም አይባል….ብቻ በሁሉ ነገሩ ምትሀታዊ በሆነ መልኩ በሁለት ሊያስጠሉ በሚችሉ ፅንፍ ማንነቶች መሃከል አማካይ ነጥብ ላይ በምቾት ተቀምጦ፣ እንደኔ ያለችውን ሴት ለማሳሳት ተሰርቶ የተዘጋጀ የምርጥ ወንድ ሰርቶ ማሳያ ነገር ሆነብኝ፡፡ እመኑኘ፣ ልጁ ትንሽ ፊት ቢሰጡት መነኩሴን አለማዊ የሚያደርግ፣ ጭምትን የሚያሳብድ ያልተለመደ አይነት መስህብ አለው፡፡ እንዲህ ያለን ወንድ፣ ያውም በገዛ ጓደኛው ‹‹አብራችሁ ሁኑ›› የሳምንታት ግፊት እየተገፉ እንዴት ብሎ መቋቋም ይቻላለል? እንዴትስ ብለው ለእንዲህ አይነቱ ሰው በሴት- ያውም በፍቅር እጦት በተጎሳቆለች የሴት ልብ- ላይረቱልት
ይቻላል? ህእ….ልወደው ነው እንዴ?

@wegoch
@wegoch
@paappii
‹‹ሲስተርሊ-ብራዘርሊ››
(ከሕይወት እምሻው)
ክፍል ሁለት
-----------------
ህእ….ልወደው ነው እንዴ? አዬ..በምን እድሌ? አይደለም፡፡ እስካሁን ያወራሁላችሁ ሁሉ ስለ ኤፍሬም አይኔ
ያየውን፣ አንጎሌ የመዘገበውን እንጂ አብላልቼ፣ ሳላስበው ለልቤ የነገርኩት፣
ልቤም ከእኔ የተቀበለውን የውደጂው ጥሪ ተቀብሎ ንዝንዙን የጀመረበት…ልክ
ኬቢን የወደድኩበት መንገድ የሚመስል አይደለም፡፡ (አያችሁ….አይንና አንጎል
ገለልተኞች ናቸው፡፡ ሊስት ይዘው ሰው የሚመዝኑ…ይሄ አሪፍ ነው ይሄ ይደብራል
የሚሉ……ልብ ግን …ልብ ግን አንዴ ከወደደ ወገንተኛ ነው….ዝርዝር ሳያወጣ… ምክንያት ሳይደረድር በቃ ወደድኩት ብሎ ግግም የሚል…ግድፈት የሚያይ አይን የሌለው…የሚያመዛዝን አንጎል የሌለው ደደብ ነገር ነው ልብ፡፡ …) አዎ ልጁ ድንቅ ነው፡፡ መልከ-መልካም ነው (በሰፊው እንዳየሁት…በሰፊው እንዳወራሁት) ጨዋ ነው (ለሳምንታት እንደቃረምኩት) ደስ ብዬዋለሁ ( በአስተማማኝ መረጃዎች ላይ ተመሰርቼ እንደገመትኩት) ግን ምን ያደርጋል…. ሺህ ጊዜ ቢያምር፣ የት አባቱን ያህል ቢያማልል፣ ለአመታት
ቢያነሆልል አንድ ነገር ግን ይጎድለዋል፡፡ ኬቢ አይደለም፡፡
--------------------
ይሄ በሆነ በወር ከምናምኑ በኬቢ ‹‹ሞክሪው›› ግፊት ተነድቼ፣ በኤፍሬም አሪፍነት እና ‹‹ወደድኩሽ›› ጉትጎታ ይሉኝታ ተይዤ፣ ኬቢን በልቤ ዙፋን አደላድዬ እንዳስቀመጥኩ፤ ከኤፍሬም ጋር ፍቅር የሚመስል ነገር ጀመርን፡፡
እዚህና እዚያ ቡና እና ማኪያቶ፡፡ ክትፎና ሽሮ….እዚህ እና እዚያ ሶቶ ተያይዞ
መሄድ….እንደ ፍቅረኛ ፊልም ገብቶ ፊልምና ፖፕ ኮርኑን ትቶ ከንፈርን መቃመስ፡፡ የከረረ ግንኙነት አልነበረም፡፡ ፍቅር አልሞካከረኝም፡፡ ከመሳሳም ያለፈ ነገር አላደረግንም፣ ያቺ አመፀኛ ልቤ መች ፈቅዳ፡፡ ከኤፍሬም ጋር ውለን ስንለያይ ቤት ስገባ አይናፍቀኝም፡፡ አጠገቤ ከሌለ ትዝ አይለኝም፡፡ ሳገኘው ግን አይከፋኝም፡፡ ለጥቂት ሳምንታት ይሄ ስሜት ምን እንደሆነ ውሉ ጠፋኝና ቤቴ ስገባ መስታወት ፊት ቆሜ ራሴን ‹‹ምናባሽ እያደረግሽ ነው?›› ብዬ መጠየቅ ጀመርኩ፡፡ እስከዛሬም ደፍሬ መጠየቅ አልፈለግኩም እንጂ መልሱ ሩቅ አልነበረም፡፡ ኬቢ ለኤፍሬም አንፀባራቂ ትሪ ላይ አድርጎ፣ አሳልፎ ከሰጠኝ በኋላ፣ በእሱ ፈንታ ከኤፍሬም ጋር ስውል…ጊዜዬን በሙሉ ስቀማው እስከዛሬ በዝቼ በመገኘቴ ምክንያት ታይቶት የማያውቀው ታላቅ ክፍተት ይፈጠራል ብዬ በማሰብ ነው፡፡ ከእጁ ስወጣ ከመዳብነት ወደ ወርቅነት እቀየራለሁ ብዬ ተስፋ በማድረግ ነው፡፡ እስከዛሬ አስተውሎት በማያውቅ ሁኔታ ይወደኝ እንደነበር…ይፈልገኝ እንደነበር የሚረዳበትን መልካም የቅናት አጋጣሚ እፈጥራለሁ ብዬ ነው፡፡ አላሳዝንም? አላሳዝንም፤ ምክንያቱም ከሳምንታት ቸልተኝነት እና ‹‹እንዴት ነው ተመቻቻሁ አይደል?›› የሚሉ ልብ ማቁሰሎች በኋላ ፤ እሰቲ ዞር ስል ዋጋዬ ከታየው ብዬ….ከቀኖቼ የሚበዙትን ለኤፍሬም ፍጆታ ማዋል ስጀምር፣ ከኤፍሬም ጋር ብቻ ወጣ ገባ ማለት ስጀምር፤ ኬቢ በጣም መደወል ጀመረ፡፡ ‹‹ ጠፋሽ…ላወራሽ ምፈልገው ጉዳይ አለ›› ብሎ እንደመለማመጥ ሁሉ ሰራው፡፡ በርትቼ ትንሽ ባንገላታው እወድ ነበር…ግን ያቺ ገለልተኝነት የማታውቅ…ላፈቀረችው ሰው የቀናት ጭካኔን የማትፈቅድ ስቱፒድ ልቤ እምቢ አለችኝ፡፡ ‹‹ሲሪየስ ትመስላለህ…ሰላም አይደለህም እንዴ ኪቢዬ?›› አልኩት አንዱን ቀን ካልተገናኘን ብሎ ሲወጥረኝ፡፡
‹‹እኔ ደህና ነኝ…ዛሬ እንገናኝ….›› አለ ጥድፍ ብሎ፡፡
‹‹ዛሬ?››
‹‹አዎ…ምነው….›
‹‹አይ ኤፊ ጋር ነኝ….››
‹‹ማለት ከእሱ በፊት ወይ በኋላ አግኚኛ!›› (ልጁ ብሶበታል….አርባራቱ ታቦቶች ፀሎቴን ሰምተው በእጄ ሊያስገቡት ይሆን…?) ‹‹አይ…ኬቢዬ ከስራ እንደወጣሁ አርሊ ሄጄ እዛው ላድር ነበር…›› የኤፍሬም ‹‹ ከከንፈር እንውረድ›› ጉትጎታ ቢበረታም፣ ‹‹እሺ በቃ ዝም ብለሽ ነይና እደሪ…አይ ስዌር አልነካሽም›› ልምምጥ የዘወትር ስንቄ ቢሆንም፤ ለኤፍሬም ከንፈሬን እንጂ ሌላ ነገር አልሰጠሁትም፡፡ አድሬ አላውቅም፡፡ የማደር አጭር እቅድም የለኝም፡፡ ኬቢን ለምን ‹‹ላድር ነው››› እንዳልኩት ጥንቅቄ አውቃለሁ፡፡ ያበጠው እንዲፈነዳ ነው፡፡ ኬቢ በሆዱ ያለውን ፍቅር (እሱ ባያውቀውም) ቶሎ እንዲወልደው ‹‹ከኤፍሪም ጋር እየተኛሁ ነው›› የሚል የምጥ መርፌ መውጋቴ ነው፡፡ ‹‹ላድር?›› ከልክ በላይ ጮኸ፡፡ (ሰምሯል ሃሳቤ ሰምሯል….ሆኗል ምኞቴ ሆኗል…..) ‹‹ምን ያስጮህሃል…?›› ‹‹ማደር ጀምራችኋል እንዴ….?›› (ለምንድነው እንደዚህ የሚጮኸው? ቀና…….? ተቃጠለ? እርር ድብን ብሎ አስረክቤ መጣሁ አስረክቤ ወርቅ አምባሬን ከእጄን እያለቀሰ መዝፈን ጀመረ….?) ‹‹ቦይፍሬንዴ መስሎኝ….›› አልኩ ትንሽ ወጠር ብዬ፡፡ ‹‹ቢሆንስ…ቢሆንስ…ገና በወር ከምናምን…ገና ምንም ሳታውቂው….›› ‹‹ምንም ሳታውቂው? አንተ አይደለህ እንዴ ላንቺ ከእሱ በላይ ሰው የለም ብለህ ስትገፋኝ የነበርከው….?ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ?›› (አሁን እኔም መጮህ ጀመርኩ፡፡ የከረመች ‹‹እንዴት ለጓደኛው አሳልፎ ይሰጠኛል›› ብስጭቴ እድል
አግኝታ ወጣች፡፡) ቀጥሎ ምን እንደሚል ለመገመት ስሞክር፣ ‹‹ይሄ በስልክ አይሆንም…ያለሽበት መጥቼ መነጋገር አለብን….ቀልዴን አይደለም…የት ነሽ?›› አለኝ፡፡ የት ነሽ ነው ያለኝ? (ፈንጠዚያ አለም ላይ ነኝ የኔ ኦክስጅን፡፡፡፡ ከደመና በላይ እየተንሳፈፍኩ በምንም በማንም የማልረበሽበት ውብ የፈንጠዚያ አለም ላይ ነኝ ኬብዬ ማለት አማረኝ፡፡)
በአካል አግኝቼው ሁሉ ነገር ሲፍረጠረጥ…እወድሻለሁ ሲለኝ…ለአመታት የጎመጀሁትን ከንፈሩን ሲሰጠኝ ፣ ለአመታት ያለምኩትን ፍቅር ሲያሳየኝ ታየኝና ሳላቅማማ ተስማምቼ አንዱ ካፌ ተገናኘን፡፡ ተረጋግቶ፣ በአመለጠችኝ….ከሌለ ተኛች ፀፀተ አለንጋ ተገርፎ፣ ….አንገቱን ደፍቶ
እና ያፈቀረ ወንድን የልብ ስብራት ይዞ ይጠብቀኛል ብዬ ነበር፡፡ ግን ቱግ እንዳለ
ነበር፡፡ ቀይ ፊቱ ደፍርሷል፡፡ አይኖቹ ይባስ ጠበዋል፡፡ የአሸናፊነት ስሜት ውስጥ እየዋኘሁ፣ እንደዋዛ ጉንጩን ሳም አደረግኩትና ተቀመጥኩ፡፡ (ከደቂቃዎች በኋላ እንደ ፍቅረኛ ከንፈሮቹን እንደምስም እያሰብኩ…ያውም ለመጀመሪያ ጊዜ…) መግቢያም ያልነበረው ወሬያቸን ከስልክ ጥሪው ቀጥታ ቀጠለ፡፡ ‹‹ለምንድነው አብራችሁ የምታድሩት?›› ብሎ ጀመረ፡፡ ሳቅኩ፡፡ በልቤ እያዘንኩለት..ግን ደግሞ….በዚያች የእሱ ባሪያ በሆነች ልቤ እየራራሁለት ሳቅኩ፡፡
(ተነካ እንዴ ይሄ ልጅ?) ‹‹እንዴ ምን ማለትህ ነው?››› ‹‹ምን ታደርጋላችሁ አብራችሁ ስታድሩ…..?›› ‹‹ኬቢዬ..ትላንት ነው እንዴ የተወለድከው?›› ብየ እንደገና ሳቅኩ፡፡‹‹ምእራፍ አትቀልጂ…ጥያቄዬን መልሺልኝ…›› ‹‹ያው አልጋው ላይ ካርታ እንጫወታለና…ሌላ ምን እናደርጋለን?!›› በማሾፍ መለስኩለት፡፡ ፊቱን እጆቹ ውስጥ ቀበረና ቀና ብሎ አየኝ፡፡ ተለዋጭ እና የተሻለ መልስ የሚጠብቅ ይመስላል፡፡ የጀመርኩትን መጨረስ አለብኝ፡፡ ያደፈረስኩትን ማጥራት አለብኝ፡፡ መቅናቱን እንዲናዘዝ፣ ማፍቀሩን ይፋ እንዲያወጣ መገፍተር አለብኝ፡፡ ‹ምን ይመስልሃል…?ዊ ፋክ….በቃ….!›› አልኩት፡፡ እንዲህ ስድ መሆኔን፣ ኬቢ ላይ እንዲህ መባለግ መቻሌን ማመን አቃተኝ፡፡ ግን ይሄ ግልብ መልስ ከልክ በላይ አንድዶት፣ ይሄንን ድብብቆሽ ቶሎ የሚያፈርስና ‹‹እወድሻለሁ›› የሚያስብለኝ፣ ለአመታት የጠበቅኩትን ልጅ በደቂቃዎች የሚሸልመኝ ስለመሰለኝ እንደዚያ አልኩ፡፡ ልቡ በተሰበረ ሰው አኳሃን አየኝ፡፡ እመኑኝ፤ አግኝቼዋለሁ፡፡

@wegoch
@paappii
ሲስተርሊ ብራዘርሊ
ከሕይወት እምሻው
ክፍል ሶስት
---------------
እንዲህ ስድ መሆኔን፣ ኬቢ ላይ እንዲህ መባለግ መቻሌን ማመን አቃተኝ፡፡ ግን
ይሄ ግልብ መልስ ከልክ በላይ አንድዶት፣ ይሄንን ድብብቆሽ ቶሎ የሚያፈርስና
‹‹እወድሻለሁ›› የሚያስብለኝ፣ ለአመታት የጠበቅኩትን ልጅ በደቂቃዎች
የሚሸልመኝ ስለመሰለኝ እንደዚያ አልኩ፡፡
ልቡ በተሰበረ ሰው አኳሃን አየኝ፡፡
እመኑኝ፤ አግኝቼዋለሁ፡፡ በድንገት ቀና አለና ‹‹ምእራፍዬ፣ በጣም አዝናለሁ…ይሄ ሁሉ የኔ ጥፋት ነው…አንቺ ምንም
አላረግሽም›› አለኝ፡፡
አላልኳችሁም? ኑዛዜው ተጀመረ….!
‹‹ምንድነው ጥፋትህ?›› አልኩት ቀስ ብዬ አይን አይኑን እያየሁ፡፡
‹‹የማፈቅራትን ልጅ በድድብናዬ ለሌላ አሳልፌ መስጠቴ፡፡ ጅልነቴ፡፡ ላንቺ ያለኝን
ፍቅር ለማወቅ ይህን ሁሉ ዘመን መፍጀቴ፡፡ ከሁሉ በላይ ግን አንቺን እንዲህ ማሰቃየቴ›› ሊለኝ ነው ብዬ ሳስብ…፡ ‹‹እኔ ነኝ ገፋፍቼ እዚህ ሁሉ ነገር ውስጥ የከተትኩሽ….ለማንኛውም…አሁን
እውነቱን ሳውቅ ነው በድፍረት ልንገርሽ ብዬ የመጣሁት›› ያው ነው፡፡ እኔ ቀጥታ የሚለኝን ነገር አሰብኩ እሱ ግን ዙሪያ ጥምጥሙን ጀመረ፡፡ ታግሼ ማስጨረስ አለብኝ፡፡
‹‹ምንድነው እውነቱ?›› አልኩኝ እንደመሽኮርመም እየሰራኝ፡፡
‹‹እሱ ኢት ኢዝ ኖት ኢምፖርታንት!››
‹‹ማለት…›› ‹‹በቃ እሱን እንተወው…ዋናው ነገር አንቺ ከኤፊ ጋር መሆን የለብሽም››
‹‹እኮ ለምን?››
‹‹በቃ አይሆንም አልኩሽ››
‹‹ምንድነው በቃ አይሆንም አልኩሽ ማለት…ድንገት ምን ተፈጠረ?›› በዙሪያ
ጥምጠሙ ትእግስቴ እያለቀ ጠየቅኩ፡፡
በረጅሙ ተነፈሰ፡፡ የደፈረሰ ፊቱ ይበልጥ እየደፈረሰ ‹‹በቃ….አንቺ ከእሱ ጋር
መሆነን የለብሽም›› አለ፡፡
‹‹ኬብ!›› አልኩት በንዴት ጮክ ብዬ
‹‹እ››
‹‹ቀንተህ ነው አይደል?››
ፊቱ ላይ ከፍተኛ ግራ መጋባት፣ መወናበድ አየሁ፡፡
‹‹ም…..ን?›› አለኝ እጅግ በደነገጠ ሰው ሁኔታ፡፡
‹‹ኢትስ ኦኬ…ንገረኝ…..››
‹‹ምንድነው ምነግርሽ?››
‹‹እውነቱን…››
‹‹ምንድነው እውነት የመሰለሽ?››
‹‹ቀንተህ ነው ወይ…..››
‹‹በማ…በማን ነው ምቀናው?››
‹‹በኤፊ….ከኔ ጋር ስለሆነ ….››
‹‹ምእራፍ አትዘባርቂ!››
‹‹ምን ማለት ነው አትዘባርቂ..?››
‹‹እንደሱ አይደለማ!››
‹‹እንዴት ነው ታዲያ?››
‹‹ምክንያቱ ምን ያደርግልሻል? በቃ እሱ ላንቺ አይሆንም ካልኩ አታምኚኝም?››
‹‹ትላንት ያለሱ ሰው አልተፈጠረም ያልከውን ሰው ዛሬ ከመሬት ተነስተህ ላንቺ አይሆንም ስትለኝ ለምንድነው ማምንህ? ይልቅ ዋናውን አውነት ንገረኝ….›› ‹‹ከመሬት ተነስቼ አይደለም!››
‹‹እና ከምን ተነሳህ….›
‹‹እሱን ዛሬ ላወራሽ አልፈልግም››
ነገሩ ሁሉ ሊማሊሞ ዳገት ሆነብኝ፡፡ ተዳከምኩ፡፡ ተናደድኩም፡፡
‹‹በቃ ልትነገረኝ ካልፈለግህ ተነስና ሂድ!›› አልኩት በመሰላቸት፡፡ ‹‹አልሄድም…ህጻን አትሁኚ…›› ‹‹ማነው ህጻኑ? እኔ? ማትሄድ ከሆነ እውነቱን ንገረኝ›…እኔ የምጠረጥረው፣ የማውቀው ነገር አለ፡፡ ከፈራህ ይሄው ልጀምርልህ….ምእራፍዬ…በል››
‹‹ምን? ምንድነው ምጠረጥሪው?››
‹‹ዝም ብለህ የምልህን በል….››
‹‹ሆሆ…ምን ሆነሻል?››
‹‹ምእራፍዬ በል››
ፊቱ ላይ የንዴት ሳቅ ተስሎ ዝም ብሎ አየኝ፡፡
‹‹በላ››
‹‹ምን?››
‹‹የምልህን ድገም….››
‹‹በናትሽ….››
‹‹አለዛ ሂድ….››
‹‹ወይ ጉድ….ምን አይነት ጨዋታ ነው? እሺ….ምን ልበል?..››
‹‹ምእራፍዬ….››
‹‹ምእራፍዬ…..››
‹‹እኔ ከኤፊ ጋር እንድሆኚ የማልፈልገው….››
ዝም አለ፡፡ ‹‹ኬቢ…ድገምልኝ….እኔ ከኤፊ ጋር እንድትሆኚ የማልፈልገው በል››
እያቅማማ ‹‹እኔ…ከኤፊ ጋር እንድትሆኚ የማልፈልገው›› አለ
የሚቀጥለውን አረፍተ ነገር ከአፌ አውጥቼ ድገመው ከማስባሌ በፊት በረጅሙ ተነፈስኩ፡፡ በጥልቀት አየሁት፡፡ ነገሮች ሊቀየሩ ነው፡፡ ሕይወቴ ሊቀየር ነው፡፡ በአዲስ የፍቅር ፀሃይ ፀዳል ልደምቅ ነው፡፡ አይኔን ጨፍኜ ታላቁን አረፍተነገር ከአፌ አወጣሁ፡፡
‹‹ራሴ ስለማፈቅርሽ ነው….››
አይኖቼ እንደተጨፈኑ ይሄ ሕይወቴን የሚቀይር አረፍተነገር በምወደው ልጅ
አንደበት እስኪወጣ ድረስ ልቤ አታሞ እየመታች፣ መላ ሰውነቴ ውሃም እሳትም
እየሆነ ጠበቅኩ፡፡
ሰከንዶች አልፈዋል፡፡
ፍፁም ፀጥታ፡፡
አይኖቼን ከፈትኩ፡፡
ፍጹም በድንጋጤ እና በሃዘን የደረቀ የኬብ ፊት ጠበቀኝ፡፡ ይሄን ፊቱን
አላውቀውም፡፡ ሁሉ ነገር እንዳበቃለት፣ አይሳሳቱት አይነት ስህተት መሳሳቴ ገባኝ፡፡ ስንት ደቂቃ በሚጎረብጥ ዝምታ እንዳሳለፍን አላውቅም ግን መጀመሪያ
የተናገረው እሱ ነበር፡፡ ‹‹እህህህህም…ምእራፍዬ…ኤፍሬም ካንቺ ጋር ከጀመረ በኋላ…ከአንድ ሁለት
ሴቶች ጋር ሲቃበጥ ስላየሁት ነው….ማለቴ….እኔው ራሴ ገፋፍቼ …አስግድጄ ከእሱ ጋር አድርጌሽ እንዲህ አይነት ነገር ሲሰራሸ ፀፀት ተሰምቶኝ ነው›› አለ፡፡ ሰምቼዋለሁ ግን መልስ የመስጠት ፍላጎትም አቅምም አልነበረኝም፡፡ በኤፍሬም ብልግና ልቤ ተሰብሮ አይደለም፡፡ እንኳን ከአንድ ሁለት ከሃያ ሁለት ሴት ጋር ሲዳራ ቢውልና ቢያድር ግድ የለኝም፡፡ምክንያቱም ልብ የሚሰበረው ልብን በሰጡት ሰው ብቻ ነው፡፡ ብዙ ስብራት የሚመጣው አብዝተው በሚያፈቅሩት ሰው ነው፡፡ እንደ ኤፍሬም አይነቱማ አልፎ ሂያጅ ነው፡፡ እኔ
በኤፍሬም እንደተጠቀምኩበት ቢጠቀምብኝም ምን ይገርማል? እኔ ኬቢን በሚመኝ አፌ በሽንገላ ከሳምኩት እሱ ደግሞ በዚያው አፉ ቢዋሸኝ ፍትህ
ተዛብቷል? አይመስለኝም እምባ ባዘሉ አይኖቼ አየዋለሁ፡፡ ‹‹ምእራፍዬ…አንቺ እኮ ለእኔ….ከእህትም በላይ ነሽ…..የምወዳት እህቴ ላይ
እንዲህ ያለ ነገር ሲያደርግ ዝም ማለት አልቻልኩም…ማለት….››
የምወዳት እህቴ፡፡ እህህህ፡፡
ሳላስበው አቋረጥኩት፡፡ ‹‹በፊት…በፊት ለእኔ እንዲዚህ አይነት ስሜት እንደማይሰማህ አውቅ ነበር…
ከኤፊ ጋር ከሆንን ጊዜ ጀምሮ ግን የቀናህ መስሎኝ ነበር….ማለት…ልክ እንደኔ ….ሳታውቀው የምታፈቅረኝ……››
የዝምታ ተራው የእሱ ሆነ፡፡ በሃዘን ያየኛል፡፡ ቀጠልኩ፡፡ ‹‹ግን እንደዛ አስበኸኝ አታውቅም አይደል…ይሄን ሁሉ አመት አንዲትም ጊዜ?›› አልኩት፡፡ መልሱን ማወቅ የማልፈልገውን ጥያቄ ለምን ጠየቅኩ? ወሽመጤ ተቆርጦ እንዲቆርጥልኝ? ላያዳግም ፍቅሩ እንዲወጣልኝ? አቀረቀረና ፣ ሳግ በሚመስል በታፈነ ድምጹ ‹‹እኔ..እኔ እንደ እህቴ ነው ማይሽ….በዚያ ላይ ደግሞ….››አለኝ፡፡:
በዚያ ላይ ደግሞ ነው ያለው?
‹‹በዚያ ላይ ደግሞ ምን?› አልኩት
‹‹ሳምሪን…ሳምሪን እንደምወዳት የምታውቂ መስሎኝ…..›› እንዳቀረቀረ፡፡
አረ ተው ኬቢ፡፡ የሞተ ሰው ይደበደባል? የደከመን ገድሎ ፉከራው ምንድነው
አለች ያቺ ጂጂ፡፡ ቀን ቢጥለኝ በወደቅኩበት በካልቾ ያጣድፈኝ?
ሳምሪን አውቃታለሁ፡፡ የእኔና ኬቢ የማስተርስ ክላስ ውስጥ ናት፡፡ እንኳን
እንደሚወዳት በስርአቱ አይቷት እንደሚያውቅ እንኳን አላውቅም፡፡ እኔ የማውቀው ቆንጆ ሴት እንደሚወድ ነበር፡፡ እኔ የማውቀው ሸንቃጣ ሴት
እንደምታቅበጠብጠው ነው፡፡ ቁንጅና ስለማይጎድለኝ ምንም ያህል ጊዜ ይፍጅ
አንድ ቀን አይኑ ውስጥ እንደምገባ አስብ ነበር፡፡ልክ እንደሚወደው ሸንቃጣ
ለመሆን ገመድም እራትም እዘል ነበር፡፡ ምስኪን ምእራፍ፡፡ ሳምሪን አሰብኳት፡፡ ያቺ ሁለመናዋ ከስብ የተሰራ የስብ ክምር…የሰው ጮማ፡፡ ከእኔ በምን በልጣ የማፈቅረው ልጅ ልብ ገባች? እንዴት መግቢያ ፈተናውን አልፋ ራሷን በልቡ ከንቲባነት አወጀች? ቀና ብዬ ላየው አልቻልኩም፡፡ የሃፍረቴ መጠን በኪሎ ቢመዘን አራት ግብዲያ የጭነት መርከቦች ችለው አይጭኑትም፡፡ እዚያው ከተቀመጥንበት
ሳያየኝ መ…….ጭ ብዬ ወደ ማርስ መሄድ ተመኘሁ፡፡ በቅርብ ጊዜ ሳይንቲስቶች ሰው በደንበኛው ሊኖርበት ይችላል ሲሉ ሰምቻለሁ፡፡ግን ሚሊዮን ሰው ቢኖርበት ምን ዋጋ አለው፡፡ ኬቢ አይኖርም፡፡

@wegoch
@wegoch
@paappii
👏👏ጠቅላይ ሚንስትሩ ተሸለሙ።👏👏
ዛሬ 30/01/12 ጠቅላይ ሚንስትሩ የኖቤል የሰላም ሽልማትን አሸነፉ። ኢትዮጵያና አፍሪካ አሸነፈች ተባለ። በዚህ ጊዜ ምን እንደ ተሰማቹህ አላውቅም እኔ ግን እኔ በሆንኩ ብዬ አሰብኩ (የብዙዎቻችን እንደምንል አምናለሁ)። ታድያ ቅናት መሆኑን ሳስብ እራሴን ታዘብኩ። የርሱ ደስታ የሁላችንም መሆኑን ለምን አላመንኩም። አንድ ሀሳብ ግን ቅናቴን አጠፋው፤ ጠቅላይ ሚንስትሩ ርዕሰ ብሔርነታቸው ለኢትዮጵያ ነው። በቦታው ላይ በመሆናቸው ብቻ ግን ይህን አላመጡትም ብዙ ሆነው ያለፉ አሉና። ቦታውን ሲያገኙ እራሳቸውን ከማገልገል በላይ ለሀገር በማደር እርሳቸውንም ሀገርንም ለማገልገል በመቻላቸው ነው እንጂ።
ሽልማቱ የሀገር ነው፤ ስንል ግን በየቦታቸው፣ በየወንበራቸው፣ የሚገባውን ነገር ለሰሩ ጭምር ነው። ሁላችሁም እንኳን ደስ ያላችሁ።
ጠቅላይ ሚንስትሩ ስለ 5 ሚልየኑ እራት ሲናገሩ ያልተባበራችሁን አይሳካም ያላችሁም አመለጣችሁ በሚል እንቁልልጭ ብለዋቸዋል። ዛሬ የተሰማኝ ያ ነው። የኔም ሽልማት ነው ብዬ እንዳላስብ፤ በአቅሜ፣ በቦታዬ የሰራሁት ስለሌለ ሸመመኝ። የሰራችሁ ግን ከጠቅላይ ሚንስትሩ እኩል እንኳን ደስ አላችሁ።
ለባለቤታችሁ ታማኝ ባሎችና ሚስቶች፤ ለሰፈር ሰላም የሆናችሁ አባቶችና እናቶች፤ ለመንጋችሁ የተጨነቃችሁ የሀይማኖት አባቶች፤ ለኔ ይድላኝ ያላላችሁ የፖለቲካ አካላት፤ በየመስሪያ ቤቱ ዐይን የሆናችሁ ሰራተኞች፤ ቤታችሁን የምትንከባከቡ እናቶች ሽልማቱ ይገባችኋል። በተቃራኒው ለቆማችሁ ደግሞ ከስራቹህ ልትመለሱ ልትቀኑ ይገባል። ምንም ያልሰራን ደግሞ መታጠቅ ይኖርብናል።
ሽልማቱ ግን ለሚገባቸውና ለኢትዮጵያ አንዴ ብቻ ተሰጠ።
መልካም ነገ።

@wegoch
ለሰንበቲታችሁ
💚

እግዚአብሔር በሚፈሩት በምሕረቱም በሚታመኑት ይደሰታል


፩ ሃሌ ሉያ። እግዚአብሔርን በመቅደሱ አመስግኑት፤ በኃይሉ ጠፈር አመስግኑት።


፪ በችሎቱ አመስግኑት፤ በታላቅነቱ ብዛት አመስግኑት።


፫ በመለከት ድምፅ አመስግኑት፤ በበገናና በመሰንቆ አመስግኑት።


፬ በከበሮና በዘፈን አመስግኑት፤ በአውታርና በእምቢልታ አመስግኑት።


፭ ድምፁ መልካም በሆነ ጸናጽል አመስግኑት፤ እልልታ ባለው ጸናጽል አመስግኑት።


፮ እስትንፋስ ያለው ሁሉ እግዚአብሔርን ያመስግን። ሃሌ ሉያ

መዝሙረ ዳዊት ምዕራፍ ፻፶


መልካም ሰንበቲት 💚

@wegoch
@wegoch
...አንዳንዴ በዙሪያህ ያለው ሰው ቢቃወምህም እውነትን መመስከር አለብህ። የሚቀየመኝም ካለ መቀየም ይችላል። አረንጓዴ፣ ቢጫ፣ ቀይ ሰንደቅ ግን የአንድ ድርጅት፣ የአንድ ብሔር ወይም የአንድ ሐይማኖት መለያ ብቻ የሆነ መለያችን አይደለችም። የባንዲራውን ቀለሞች እየተጠቀሙ "የኛ ብቻ ነው" ማለት ይቻላል፤ እውነታው ግን ሌላ ነው። ወደድንም ጠላንም እውነት ግን እውነት ናትና!
... ከጅምሩ እነዚህ ሦስት ደማቅ ቀለሞች ምንጫቸው ከላይ ከሳብዓይ ሰማይ ነው። ሰማያዊ ክቡር ማዕድናት ኢያስጴድ (አረንጓዴ እንቁ)፣ ዮጵ(ቢጫ እንቁ) ና ሰርዲኖን(ቀይ እንቁ) የተንጸባረቀ ታላቅ ምልክት (Revelation) ነው። እነዚህ ቀለማት በቅድሚያ ለኖህ የተገለጹ ናቸው። በኖህ ጊዜ ህዝበ-አዳም ሀጥያቱና ማፈንገጡ በዝቶ ስለነበር ኤሎሄም ዓለምን ሙሉ በሙሉ በውሀ አጥለቅልቆ የምድር ገፅ ላይ የነበሩትን ሰዎች በሙሉ አጠፋ፤ ኖህና ቤተሰቦቹ ሲቀሩ።
ኋላም መሬት ውሀዋን መጣ፣ ደርቃ የኖህ መርከብም ከኢትዮጽያ ግዙፍ የአራራት ተራሮች ደርሳ፣ ከየብስ ስትነካካ ለኖህ ቃልኪዳን ተገባለት። አምላክ ድጋሚ ዓለምን በውሀ ሙሉ ለሙሉ እንደማያጠፋ ቃል የገባውም ሰማይ ላይ ቀስተ-ደመናን ከጥግ እስከጥግ በመዘርጋት ነበር። ጎልተው የወጡት ህብረ-ቀለማትም ...
፩, አረንጓዴ-(ልምላሜ፣ ተፈጥሮ፣ ፀጋ፣ ሰላም፣ እርጋታ፣ ተመስጦ...)
፪, ቢጫ-(እምነት፣ ተስፋ፣ ራእይ፣ መንፈሳዊነት ጥበብ፣ ፍቅር፣ ርህራሄ፣ ምህረት...)
፫, ቀይ - (ደም፣ መሰዋእት፣ ነፃነት፣ በደም መተሳሰር፣ ሉዓላዊነት፣ አንድነት...) ነበሩ።
.
የኖህ፣ ከዚያም (በተለይ) የኩሽ ልጆች ይህንን የቃልኪዳናቸውን ምልክት ላይረሱ አከበሩት። የልጅ ልጆች እነ ኢትኤልም ይህንን ምልክት ከልባቸው አውታር አትመውት ዘለቁ።
ኋላ ግን ዲበ-ሰው እስያኤል(ራምሃይ፣ ዙልቀርኒን) እነዚህን ቀለማት በግዛቱ እያውለበለበ፣ ለዓለማት ከ2800 ዓመታት በፊት የባንዲራን ኮንሰፕት አስተዋውቋል። ጦርነቶች ሊዋጋ ሲሄድም ይሄን ባንዲራ እንዲያውለበልቡ ወታደሮቹን አዟል። በኋላም ሰንደቅ ኣላማ በሚል ስሙ የነገሰ ንጉሳችን ሰንደቅ ኣላማ ሲል ሰይሞ የሐገር ዳር ድንበር ሉዓላዊነት መለያ መሆኑን አውጇል። እናም ጥንታዊ ነገስታቶቻችን ከጅምሩም የቀስተ ደመና ቀለማትን ከፍ አድርገው አንፀባርቀዋል።
"በሰማዩ ላይ ቢታይ ቀለም
የሷ ነው እንጂ ሌላ አይደለም!" እንዲል ብላቴናው፤
ባንዲራ...አርማ...መለያ...መኩሪያና መታያ ነው። ቀስተ-ደመና በወጣ ቁጥር የቃልኪዳናችንን ህያውነት ያበስረናል።
ይህንን ዋጋውን ያወቁ እልፎች ባንዲራው ዝቅ እንዳይል ተዋድቀውለታል። ወታደሮች ደም አጥንት ከስክሰው አስከብረውታል። በዓድዋ ላይ የነፃነት ፋና ወጊ በመሆኑ ለእልፎች የተስፋ ስንቅ ሆኗል። በዚህ እልህ ተነሳስተው ነፃነታቸውን የተቀዳጁ የአፍሪካ ሃገራትም በድላቸው አጥቢያ ይህንን ባንዲራ ኮፒ በማድረግ የሃገራቸውን ሰንደቅ ቀርፀዋል።
ባንዲራው ከኛ አልፎ ወደ ሃያ ለሚሆኑ የአፍሪካ ሀገራት መለያም ሆኗል!
እንግዲህ ...
"እንኳን ሰማይ ላይ ባንዲራሽን አይቶ፥
ኢትዮጵያ ሲባል ማን ዝም ይላል ሰምቶ?"
እንዳለው ለዚህች ሰንደቅ ብዙዎች ብዙ ዋጋ ከፍለዋል። አማራ፣ ኦሮሞ፣ አፋር፣ ሶማሌ፣ ትግራዋይ፣ ጉራጌ ወዘተ... ሙስሊም፣ ኦርቶዶክስ ፣ ዋቄ ፈና፣ ፕሮቴስታን ወይ ካቶሊክ ሳይለይ ልጆቿ ለነዚህ ቀለማት ተዋድቀዋል። አትሌቶች ላባቸውን ጠብ አድርገው ሰንደቋን ከፍ አድርገውታል።
ምንም ቢደረግ ምንም ግን ጸጋው እልፍ ለሆነው ሰንደቅ አላማችን ቢያንስ እንጂ አይበዛበትም።
(ለሁላችሁም መልካም የባንዲራ ቀን)
(ዶ/ር ኤልያስ ገብሩ/ 02/02/12)

@wegoch
@wegoch
ለውብ ቀን
💚

ደስታ የገዛ ንብረትህ ነው!


ሰለምን የገዛ ንብረትህን ሰው እንዲሰጥህ ትጠብቃለህ?
ደስተኛ መሆን ከፈለክ ደስታህን ሌሎች ጋር መፈለጉን ትተህ እራስህ ውስጥ ፈልገው


መንስዔም መፈትሄም እኛ ውስጥ ነው።


ሸጋ ቀን?💚

@wegoch
@wegoch
@balmbaras
አዳምና ቃየን
Written by ከመሐመድ ነስሩ (ሶፎንስያስ አቢስ) “ጥቁር ሽታ” የአጭር
ልብወለድ መድበል የተወሰደ)



“ሔዋን…ሔዋን”
እንደ እባብ ወደ ጐጆው ውስጥ እየተሳበ ይጣራል፡፡
ሀሳብ ጓዙን ጠቅልሎ፣ ግሳንግሱን በእጁ አንጠልጥሎ፤ ልቡ ውስጥ ውሎ
ማደር ጀምሯል:: ሀሳቡ ምክንያት አልባ አልነበረም፡፡ ልጆቹ ከእናታቸው ጋር
በፍቅር ሲተሻሹ አየ፡፡ ሚስቱ ልጆቿን እያገላበጠች ስትስም (ልክ እሱ
መጀመሪያ እሷን ሲስማት እንደሆነው ልቧ ጥፍት እስኪል ስትስም)
እንክብካቤም ስታበዛባቸው (እግዜር እሱ የኤደን አትክልት ቦታን
እንዲንከባከብ ያሰበውን ያህል ስትንከባከብ) ስታሞላቅቅ ስታቀብጣቸው
(እነሱ በተከፉ ቅጽበት ዓለም ድምጥማጧ የሚጠፋ እስኪመስል
ስታቀብጣቸው) ቢመለከት ልጅ የመሆን ሃሳብ እንደ ወባ ትንኝ አንዴ ወግቶት
ተውሳኩን ትቶበት ሄደ፡፡
አወቀ፡፡ ከሁሉም በላይ የሆነ በደል መበደሉን ተረዳ፡፡ ለካ አባት የለውም፡፡ ለካ
እናት የለውም፡፡
አዳም ሆድ ባሰው፡፡ እንባው መጣበት:: ህፃን አልሆነም፡፡ ህፃንነትን ዘሎ ሰው
ሆነ፡፡ በእናቱ ጭን ላይ የራስ ቅሉን አሳርፎ፣ በደረቷ ላይ በትናንሽ ብርሃንማ
እጆቹ የሰኞ ማክሰኞ መጫወቻ የሚያሰምረውን ልጅን ቃየንን አየው:: ልጇን
በስስት እያየች አስሬ ግንባሩን እንደ ቤተ አምልኮ የምትስመውን ሚስቱን
ሔዋንን አያት:: የማያውቀው ልጅነት ናፈቀው፡፡ ጤግሮስ ወንዝ በውሃ
እንደሚሞላ ዐይኑ በእንባ ተሞላ፡፡
“ምን ሆነሃል?” አለችው ሔዋን
ዝም፡፡
“አዴክስ ምንድን ነው እሱ?!”
የማልቀስ ነፃነቱን ያጣው ህፃን ባለመሆኑ እንደሆነ ሲረዳ፣ ንዴት ውስጡ
ተቀጣጠለ፡፡
ድንጋይ እንደተወረወረበት ወፍ አፈፍ ብሎ ወደ ውጭ በረረ፡፡
“ሔዋን” ሌላ ጥሪ፡፡
መልስ አልሰጠችውም፡፡
ጭንቀቱን ሊያዋያት ፈልጐ ነበር፡፡
ጠፋች፡፡
ቃየን እጁን አፋትጐ፣ ጭቃውን እያራገፈ ገባ፡፡
አዳምም አለው፡-
“እናትህስ?”
“ወንዝ ወርዳለች”
“የት?”
“ኤፍራጥስ”
አዳም ፍለጋዋን ሊወጣ ሲል፣ ሔዋን ከሄደችበት ተመልሳ መጥታ ፊቱ
ተገተረች፡፡
“አዳምዬ!”
ሲያያት እንደ መደንገጥም! እንደ መደሰትም፣ እንደ መናደድም አለ፡፡ ራቆቷን
ነበረች፡፡ የጭንና ጭኗ መጋጠሚያ ግድም ቅጠል አገልድማለች፤ እንደ
ብስል ፓፓያ ለመብላት የምታጓጓ፣ እንደ አመሻሽ ወርቃማ ጀንበር
እንዳትወድቅ የምትሳሳ ሆናለች፡፡
አላት፡-
“የት ነበርሽ?”
ዐይኑ እሳት እየተፋ፤ ድምፁ ማዕበል ሆኖ እየተናወጠ፤ ዙሪያ ገባውን እየናጠ፡፡
“ሰውነቴን ልታጠብ ወንዝ ወርጄ ነበር”
የበረዳት ትመስላለች፤ እንደ ሐዋላ ወርቅ ንፁህ በሆኑት እጆቿ፣ እንደ ጨረቃ
ብርሃን ተቀብሎ ብርሃን የሚረጭ ገላዋን ታሻሽለች፡፡
“ታዲያ ራቆት መሆን ደግ ነውን?! እግዜአብሔር ከቆዳ የሰራልሽን ልብስሽን
አትለብሺም?!”
ሔዋን የትዝብት ሳቅ ስትስቅ አያት፡፡
“ምን ያስገለፍጥሻል?!”
እንደ ኪሩቤል ሰይፍ አስበርጋጊነትን ተላበሰ::
“ያለነው የሰው ዘሮች እኔ፣ አንተና ልጆቻችን ብቻ ነን፤ ማን ያይብኛል ብለህ
ነው?!”
“ሰይጣንስ ቢሆን?! መላዕክትስ ቢሆኑ?! ዕፅዋትስ ቢሆኑ?! ተራሮችና
ሸለቆዎችስ ቢሆኑ ለምን ያዩሻል?!ኧረ ልጆቻችንስ ቢሆኑ?!! ባንቺ ማንን
አምናለሁ?! ለራስሽ አንዲት ብቻ! ደግሞ ማን ያየኛል ብሎ ነገር!”
“ሆ…ሆ…ሆ…” ተሽኮረመመች፡፡
ሔዋን ደስ አላት፡፡ ገመዳም ሳቅ አሳየችው፤ አዳም ተጐተተ፡፡ ወፍራም ምራቅ
ዋጠ፡፡
ከምራቁ ጋር ሃሳቡን ዋጠ፡፡ (ሊነግራት የነበረውን ረሳ) ወደ ቃየን ዞር ብሎ
አለው፤
“በል ሂድና በሬዎቹን አስገባ”

- ሀ -
አቤል ከተወለደ እጅግ ቆየ፡፡ ቃየን እናትና አባቱ ጋር የነበረውን ተወዳጅነት
ከአቤል መወለድ በኋላ ካለው ጋር ማነፃፀር የጀመረው ግን በቅርብ ነው፡፡
እንደ ቤተሰባቸውና እንደ እግዜር ህላዌ እጅግ የተራራቀ ሆኖ አገኘው፡፡
የተፈጠረበት የስሜት ለውጥም ሔዋን ልጃገረድ ሳለችና ከአዳም ጋር
ከወደቀች ወዲህ ካሳየችው የማንነት አካላዊ ለውጥ ጋር የሚገዳደር ነበር፡፡
ሔዋን ከለግላጋነት ወደ እናትነት ተሻግራለች፡፡ ቃየንም ከደስተኝነት ወደ
ፀለምተኝነት ተዛወረ::
ያኔ እንደ ንጋት ጮራ ፀሐይ በሚሞቁ፣ እንደ በለስ ቅጠል በሚለሰልሱ የሔዋን
ክንዶች የሚታቀፈው እሱ ብቻ ነበር፡፡ (አዳም የኔ ነው ሲል ሰምቶት
አያውቅም!)
ያኔ…እናቱ የሱ፣ የግሉ፣ የብቻው ነበረች፡፡
ያኔ…አባቱ የሱ፣ የግሉ የብቻው ነበር፡፡
እናትና አባቱ ከላይ እንደወረደ መና ይሻሙበታል፡፡ እንደ መንግስተ ሰማይ
ተስፋ የደስታቸው ምንጭ የነበረው እሱ ነው፡፡ እሱ ብቻውን!
ሁለተኛው ልጅ መጣ፡፡ ቃየን ብርቅነቱ አለቀ፡፡ እንደ መልዓኩ ሳጥናዔል
ማዕረጉን ተነጠቀ፡፡ የተፋለሙበት የጦር አውድ ሳይከሰት ወንድሙ
የበላይነትን ወርሶ የድል አክሊል ተቀዳጀ፡፡ የፍቅር ዘውድ ጫነ፡፡

- 2 –
አዳም ወንድነቱን ካለዘበ በኋላ ከሔዋን ወጥቶ በሃሳብ እቅፍ ውስጥ ወደቀ፡፡
ልጁን ማባረሩ ተሰምቶት አይደለም፡፡ ሚስቴን አላስደሰትኳትም የሚል ስጋት
አድሮበት አይደለም፡፡ ሚስትና ልጆች ብቻ እንዳሉት ትዝ ብሎት ነው፡፡
የልጅነትን ውብ፣ ማራኪ ጨዋታዎች አልተጫወተም፤ ቅል ቅቤ ተቀብቶ
እንደሚብለጨለጭ …የሱ ፊት የልጅነት ወዝ ተቀብቶ አልተብለጨለጨም፤
እንደ ኤደን ሰማይ አልፈካም፡፡ እንደ ሐዋላ ሽቶ ውድ የሆነውን የህፃን አልባብ
ሽታ ሰውነቱ አመንጭቶ አያውቅም፡፡
በህፃን ከንፈሩ የእናቱን ጡት አልጠባም፤ የአባት ፍቅር አላገኘም፡፡
እንደ የዓለም ጅማሮዎቹ አምስት ቀናት ሳይኖረው ባለፈውና እንደ ምጽዓት ቀን
በማያውቀው ልጅነት ናፍቆት ተሰቃየ፡፡ እንደ እግዜር ባላያቸው፤ እንደ ነብያት
ባልተፈጠሩት እናትና አባቱ ፍቅር ትዝታ ተንገበገበ፡፡ ብልሀቷን ያውቃልና
ጭንቀቱን ለሚስቱ ሊያካፍል አሰበ፡፡
“ሔዋኔ” አላት፡፡
“ወ…ዬ”
ከየት እንደመጣ የማይታወቅ ዝምታ አፉ ላይ ተከመረ፡፡ በዝምታው ውስጥ
ብቅ ያለው ሀሳብ አስደነገጠው፡፡ ስነግራት እሷም ተመሳሳይ ቅሬታ
ብታሰማስ? የባሰ ሕይወት ልትጨልምብን አይደለም?!
“ም…ነ…ው?” አለችው፡፡
የመጀመሪያ ሀሳቡን ደመሰሰና “በጣም እወድሻለሁ” ብሎ ወደሷ ዞረ፡፡
“ይህን ቃል ካንተ እኩል እንደምወደው ታውቃለህ መቼም!” ቃሉን ያሰማትን
አፉን በአፏ ገጨችው፡፡
ቃየን ገበሬ ነበር፣ እንደ ገበሬነቱ ካመረተው ሰብል መስዋዕት አቀረበ፡፡ አቤል
እረኛ ነበር፤ እንደ እረኛነቱ ከሚጠብቃቸው በጐች አንድ ጠቦት ሰዋ፡፡ የአቤል
መስዋዕት እግዜርን ደስ አሰኘ፤ ሞገስም አሰጠው፡፡ የቃየል መስዋዕት ግን
አስከፋው፡፡ የአዳም የበኩር ልጅ ባሰበት፡፡ አቤል ከእናቱና አባቱ አልፎ
በእግዜሩ ዘንድም ወንበር ተሻማው፡፡ በገነ፡፡
ከኋላ የመጣ…
እንደ ጥንቱ ሊሆን አልቻለም፡፡ እንዴት ሆኖ ሊሆን ይችላል?! አባቱን አሰበ፤
የመጀመሪያው ወንድ ነው፡፡ እናቱን አሰበ፤ የመጀመሪያዋ ሴት ናት፡፡ አባቱ
የሁሉ አባት ነወ፡፡ እናቱ የሁሉ እናት ናት፡፡ መነሻ ነጥቦች፡-
ታናሽ ወንድሙን አሰበ፤ በፈጣሪ ዘንድ ሞገስን አግኝቷል፡፡ ባቀረበው
መስዋዕት ፈጣሪውን ደስ አሰኝቷልና የታሪክ መዛግብት አይዘነጉትም፡፡
“ቆይ እኔስ?”
ራሱን አሰበ፡፡ ምንም እንደሆነ ተሰማው፡፡ በእንግዴ ልጅና በእሱ መካከል
ያለው ልዩነት ጐልቶ አልታይህ አለው፡፡
የተጣለ ነው፤ በሁሉም የተረሳ ነው፡፡
“ለምን?!...ለምን?!”
ወደፊት የማይረሳ ሰው መሆን እንዳለበት ለራሱ ቃል ገባ፡፡ “የመጀመሪያው”
በሚል ቃል ከሚጀምር ሀረግ ቀጥሎ ስሙ እንደሚሰፍር እርግጠኛ ሆነ፡፡

- 3 –
አዳም አላረፈም፡፡ ሰይጣን መልኩን እየለዋወጠ ወደ እሱና ወደ ባለቤቱ
እንደተመላለሰ ሀሳብ ቅርፁን እየቀያየረ ወደ አዕምሮው ተመላለሰ፡፡
“ምን ባደርግ
ይሻላል?!”
ይህ ጥያቄ በምናብ ተራራ አስወጣው፤ ወንዝ አስዋኘው፡፡ ምርጫ
ስላልነበረው በመጨረሻ ለሚስቱ አማከረ፡፡
አለችው፡-
“ለምን ፈጣሪያችንን አትጠይቀውም?!”
“ይሻላል?”
“አዎ ጠይቀው፤ በሽታውን ያልተናገረ መድሀኒት አይገኝለትም፡፡”
ሔዋን ነፍስ ናት፤ አዳም አካል ነው፡፡ ጥንትም አሁንም እንዲሁ ነው፡፡ ስጋ
እንደ ነፍስ ስለማይታይ አናያትም፡፡
አዳም ከሷ ውጭ ህልውና የለሽ መሆኑን ያውቃልና “እሺ”! አለ፡፡
ወደ እግዜርም ሄደ፡፡
“ምን ነበር?!”
“እናት የለኝም፤ አባት የለኝም!”
“ማን ነው እንዲህ ያለህ?”
“አየሁ፤ ተረዳሁ?! አወቅሁ”
“ጥንትም ማወቃችሁን ያልፈለኩት ለዚሁ ነበር” እግዜር አለ፡፡
“ለማንኛውም አለህ፡፡”
“እንዴት?! ከየት?!”
“አባትህ እኔ ነኝ፡፡”
“እናቴስ?”
“መሬት፡፡”
አዳም ዝም አለ፡፡ መልሱ በደንብ የተዋጠለት አይመስልም፤ ፈልጐ ከመጣው
ነገር ጋር አልተዛመደለትም፡፡
ለማንኛውም ሁለተኛውን ጥያቄውን አቀረበ::
“ህፃን ሆኜ አልኖርኩም፤ ህፃንነትን ማየት እፈልግ ነበር!”
“ጥሩ!” አለ እግዜር፡-
“ትሆናለህ፡፡ ህፃንነትን ወደፊት ትኖረዋለህ፡፡”
አዳም እጅ ነስቶ ተመለሰ፡፡
ደስም፣ ቅርም እያለው፤ በግማሽ ደስታና በግማሽ መከፋት ታጅቦ ወደ ቤቱ
አዘገመ፡፡

- ሐ -
የመጨቆን ስሜትና የመጀመሪያው ገዳይ የመሰኘት ምኞት በቃየን ልብ
ውስጥ እንደ ሔዋን ጡቶች መንታ ሆነው በቀሉ፡፡ ወደ ማዕድ ቤት ገብቶ
የሔዋንን ሽንኩርት መክተፊያ ቢላዋ ድጉ ውስጥ ከሻጠ በኋላ ወንድሙን
አለው፡-
“ና ወጣ ብለን አየር እንቀበል!”
ወጡም፡፡

- 4 -
አዳም ቤት ሲደርስ፤ ሔዋን እንባዋን እየዘራች ነበር- የሰማይ ውሃ ቧንቧዎች
የተከፈቱ እስኪመስለው!
“ምንድን ነው?”
“ጉድ ሆንኩልህ አዳምዬ! ጉድ ሆንኩልህ!”
“እኮ ምን ሆንሽ?” እያቀፋት አላት፡፡
“ጉድ! ጉድ!”
“ኧረ ንገሪኝ ምንድነው?”
“ጉድኮ ነው…ጉድ! ጉድ!”
ግራ ገብቶት ወገቡን ይዞ መንጐራደድ ጀመረ፡፡ ዐይኑን ወዲያ ወዲህ እየጣለ
ተሽከረከረ:: ድንገት ዐይኑ ቃየን ላይ ወደቀ፡፡ ደረቱን ነፍቶ በርጩማ ላይ ቁጭ
ብሏል፡፡
“ልጄ፤ እናትህ ምንድነው የሆነችው?”
“እኔ እንጃ!”
“ወንድምህስ የት አለ?”
“እኔ ገበሬ እንጂ እረኛ ነኝን?!”
ወደ ሔዋን ተመለከተ፤ ወደ ቃየን ተመለከተ:: ምክንያቱ ገባው፡፡ አቤል በአየር
ፋንታ ሞት ተቀብሏል፡፡ አዳም በቆመበት እንደ ድንጋይ ደርቆ ቀረ፡፡

- 5 –
ከቀናት በኋላ ሀዘን ተቀምጠው ሳለ፣ ከሀዘኗ ሊያዘናጋት ሽቶ፤
“ህፃናንነትን ትኖረዋለህ ተባልኩኮ”
አላት፡፡
“እንዴት?”
“ለፈጣሪ ፍላጐቴን ስነግረው ወደ ፊት እንደምኖረው ቃል ገባልኝ፡፡”
ሔዋን እንደ ራሷ ፀጉር የረዘመ ሃሳብ፣ ረጅም ጉዞ አስጓዛት፡፡
“ይኸ ነገር?” አለችው፡፡
“የቱ?”
“ይኼ ህፃን የመሆን ነገር!”
“እ?”
“ከእርጅና በኋላ የሚመጣ ሳይሆን አይቀርም፡፡”
“ማለት?”
“ሌላ ስሙ መጃጀት መሆን አለበት፡፡ ቃል ከተገባልህ ህፃን የምትሆነው
ስትጃጅ መሆን አለበት፡፡”
“እኔ ምን አውቄ?” አለ አዳም - በዐይኑ ዐይኗን እየተመለከተ፤ በልቡ
በብልሃቷና በጥበቧ ረቂቅነት እየተደነቀ፤ በስሜቱ እሷን የሰጠውን ፈጣሪ
እየወደደ፡፡


ሸጋ ጁምኣ!!💚


#ምንጭ አዲስ አድማስ


@wegoch
@wegoch
@balmbaras
አንዳንድ ነገሮችን ማብራራት ይከብዳል!!
ገበሬው በአቅራቢያው ያለ ጃምቦ ቤት በቀን አረቄ በጃንቦ ይጨልጣል።
አንድ ሌላ የሚያውቀው ሰው ይመጣና ይጠይቀዋል
" በዚ የስራ እና የምርት ሰዓት ግን እዚ መጠጥ ቤት ምን ታደርጋለህ?"
ገበሬው ጭንቅላቱን እያወዛወዘ
"አንዳንድ ነገሮችን ማብራራት ይከብዳል።" ይላል።
ሰውዬው ወንበር ስቦ እየተቀመጠ ገበሬውን ይጠይቀዋል
"ወዳጄ ምን ሆነህ ነው ንገረኝ፣ሲያወሩት ይቀላል"
"እሺ ካልክ...!" ብሎ ገበሬው ይጀምራል
"እሄውልህ ዛሬ ጠዋት ተነስቼ ግብርና በብድር የሰጠንን ነጯን ላም እያለብኩ
ነበር። አንድ እቃ እንደሞላው ግራ እግሯን አንስታ የታለበውን በሙሉ ደፋችው"
"እሺ ግን ይሄ እኮ ታድያ ብዙ አያስከፋም ለዚህ ሁኔታም አይዳርግም "ይላል ሰውየው
"አንዳንድ ነገሮችን ማብራራት ይከብዳል።" ብሎ ገበሬው አሁንም ይተክዛል ...ጭማሪ አረቄም ያዛል።
"እሺ ከዛስ ምን ሆነ" ሰውየው አለሳልሶ ለማረጋጋት ይጠይቃል
ገበሬው እየጠጣ ንግግሩን ይቀጥላል
" ከዛ ያው ግራ እግሯን ከ አንዱ ቋሚ ጋር አሰርኩት"
"ከዛስ....?"
"ከዛማ ድጋሚ ተቀምጬ ማለብ ጀመርኩ....በሌላ እቃ ሞልቼ እንደጨረስኩ ቀኝ እግሯን አንስታ ድጋሚ የሞላውትን እቃ ደፋችው"
ሰውዬው ከት ብሎ ስቆ "እንዴ ድጋሚ?" ይለዋል
ገበሬው አሁንም
"አንዳንድ ነገሮችን ማብራራት ይከብዳል " ይለዋል።
"ከዛስ ምን አረክ?" ሰውዬው በጉጉት ይጠይቃል።
"ያው ከዛ በጣም ተማርሬ ቀኝ እግሯንም ከሌላ ቋሚ ጋር አስሬ ማለብ ጀመርኩ...የሚያሳዝነው ይቺ የተረገመች ላም ይሄኛውን በጥንቃቄ እንደጨረስኩ
በጭራዋ ደፋችው"
"ያሳዝናል በእውነቱ "አለ ሰውዬው ጭንቅላቱን እየነቀነቀ።
"አንዳንድ ነገሮችን ማብራራት ይከብዳል።" ብሎ ጭንቅላቱን በሃዘኔታ ይነቃንቃል አሁንም ገበሬው
"ከዛስ?" ሰውዬው የገበሬው ችግር መጨረሻው አጓጉቶታል
"ከዛማ ሌላ ገመድ ፈልጌ ስላጣው ቀበቶዬን ፈትቼ ጭራዋን አስሬ እንደጨረስኩ
ሱርዬ ወለቀ፣በዝች ቅጽበት ሚስቴም ወደውስጥ እየገባች ነበር"
"አንዳንድ ነገሮችን ማብራራት ይከብዳል።"😜
...
...
..
መልካም አርብ!
ምንጭ እንዳትሉኝ....
#Feven Asheber
@wegoch
@wegoch
@kaleab_1888
የብዙዎችን ልብ የነካው ህፃን
ከዚህ ፎቶ መማር ይኖርብናል።
ለተተኪው ትውልድ ይሄን ማውረስ ከንቱነት ነው።
ከፊቱ ላይ የሚታየው ፍርሀት ማየት ብቻ በቂ ነው።
ዘረኝነት ይቁም

@wegoch
@wegoch
‹‹ደስ ይላል››
(ሕይወት እምሻው)
መነሻ ሃሳብ፡ የGuy de Maupassant ‹‹Indiscretion››
---------------
ከደመና በላይ የሚያንሳፍፍ ፍቅር ላይ ነበሩ፡፡ እሱ፤ ለሴት አዲስ ባይሆንም፣ ለፍቅር እንግዳ ባይሆንም ለእንዲህ ያለች ሴት ግን አዲስ ነበር፡፡ ለእንዲህ ያለ ሁለመናን የሚያሽመደምድ ፍቅር ግን እንግዳ ነበር፡፡ እሷ፤ እሷ የወደደችው በአስቴር አወቀ ዘፈንና ና በሮማስ ፊልም ብቻ ወደምታውቀው አቅል የሚያስት የፍቅር አለም እጇን ይዞ ስለመራት ነበር፡ ለሁሉም ነገር የመጀመሪያዋ ነበር፡፡ ወጣትነቱ፣ ወንዳወንድነቱ፣ ዘመናይነቱ፣ ከገንዘብ ችግር አለመተዋወቁ እና ለወራት ከፍ እንጂ ዝቅ የማይለው እንክብካቤው በፍቅር ጠልፎ ጣላት፡፡
ለስምንት ወራት ሶቶ ተያይዘው፣ አንገት ላንገት ተቆላልፈው በየመንገዱ ሲሄዱ፣
እሳት እያነደዱ ሳንቲም በሚለምኑ የጎዳና ልጆች ስንት ጊዜ ‹‹አይለያችሁ››
ተባሉ? በአደባባይ፣ ያላንዳች እፍረትና ይሉኝታ ከንፈር ሲሻሙ ባዩ አዛውንትና ወግ አጥባቂ ወጣቶችስ ስንት ጊዜ ተረገሙ? በፍቅር ሲሻመኑ አድረው ስንቷን የማለዳ ፀሃይ አብረው ተቀበሉ? ቀኑን ሙሉ ሲዳሩ ውለው ስንቷንስ የምሽት ጀምበር አብረው ሸኙ? ስንቱንስ ምሽት አብረው ማንጋት እየጓጉ በሰቀቀን ተለያዩ? ስንቱን ጠዋት አንዳቸው አንዳቸውን በማሰብ ነቅተው- ትላንት እንዳልተያየ፣ መንፈቅ እንዳልተገናኘ ሰው ተነፋፍቀው በየአልጋቸው ውስጥ ተነፋረቁ?
ከደመና በላይ የሚያንሳፍፍ ፍቅር ውስጥ ነበሩ፡፡ ከተጋቡ በኋላ ግን ፍቅራቸው በፍጥነት ወደ መሬት መምዘግዘግ ጀመረ፡፡ በናፍቆትና በእረፍት አልባ መፈላለግ መሰቃየት አቆሙ፡፡ ያ ከሰማይ በላይ የሚያንሳፍፍ ፍቅራቸው በአሰልቺና ድግግሞሻም የትዳር ሕይወት ስለት መገዝገዝ ጀመረ፡፡ ከእንግዲህ እሱ ስለሷ፣ እሷም ስለእሱ እንደአዲስ የሚያውቁት፣ የሚደነቁበት ነገር አልነበረም፡፡ ያልተጠበቁ እና ‹‹ምነው ባላለቁ›› የሚባሉ ድንገቴ የፍቅር ጊዜያት ከኋላቸው እንጂ ከፊታቸው አልነበሩም፡፡ ያላዩና ያልነኩት የገላቸው አካል፣ ያላወቁት የእርስበርስ ምስጢር አልነበረም፡፡ የፍቅራቸው ግለት ፈፅሞ ባይበርድም መፋጀቱን ግን ካቆመ ሰንበትበት ብሎ ነበር፡፡ ግን ይሁን ብለው አልተዉትም፡፡ አዲሱን እጅ እጅ ኑሮ አሜን ብለው አልተቀበሉትም፡፡ ልትጠፋ ጭል ጭል የምትለውን የፍቅራቸውን ነበልባል ባገኟት አጋጣሚ ሊያራግቧት፣ ፈፅማ ከመጥፋት ሊታደጓት ላይ ታች ይላሉ፡፡ ዛሬም፤ ልክ እንደ ድሮው፣ እንደፍቅረኝነት ዘመናቸው ጨረቃ በነገሰችበት ምሽት
እጅ ለእጅ ተያይዘው ለእግር ጉዞ ይወጣሉ፡፡ ምን ያደርጋል! ጨረቃዋም
ጎዳናውም ሳይለወጡ ፤ ድሮ እጆቻቸውን በላብ እንደማይረጥቡ፣ ገላዎቻቸው
በድንገት ሲነካኩ ታላቅ መናወጥን እንደማይፈጥሩ፣ አይን ለአይን ሲገናኙ አለምን ሁሉ እንደማይረሱ፤ አሁን አሁን ከዚህ ሁሉ ጎልቶ የሚታያቸው የመንገዱ
አቧራማነት ነው፡፡ ምን ያደርጋል! የሲኖትራክ ጩኸት….የባጃጅ ኳኳታ…..የታክሲ ሰልፍ
ረብሻ….የሃይገር ሩጫ…..ደመና ላይ ለመንሳፈፍ ላይ ታች የሚሉትን ፍቅረኞች
ጎትተው ከመሬት ይፈጠፍጧቸዋል፡፡ ዛሬም፤ ያመለጣቸውን የፍቅር ጊዜ ለመመለስ ልክ እንደ ድሮው የሮማንስ
ፊልም ሊያዩ ይሰለፋሉ፡፡ ግን ምን ያደርጋል! ልክ ያኔ እንሱ የነበሩበት ቦታ
የሚገኙ አዳዲስ ጥንዶችን የማይበርድ የሚመስል ፍቅር ሲያዩ፣ አየር እንኳን
በማያስገባ ሁኔታ እርስ በርስ ተጣብቀው ሰልፉን ረስተው በሚቃበጡ አዲስ
ፍቅረኞች ከመቅናት ውጪ ያተረፉት አንዳችም ነገር የለም፡፡ ዛሬም፤ ያለፈውን ለመቅለብ የፍቅር ግጥሞችን ሊያዳምጡ የሚሄዱባቸው የግጥም ምሽቶች ፍቅራቸውን ከማስታወስና ከማደስ ይልቅ በፖለቲካ ጡዘትና በጨለምተንነት በተሞሉ ሟርተኛ ‹‹ወዮላችሁ›› ገጣሚዎች ፊታውራሪነት ይሄን እጅ እጅ የሚል ሕይወታቸውን የመኖር ፍላጎታቸውን ሳይቀር ይቀማሉ፡፡
ላንጋኖ ሲሄዱ ከድሮው የድሪያ ጉጉት ይልቅ ወበቁ ያስጨንቃቸዋል፡፡ ሰሜን ተራራ ሲጓዙ አንጀት የሚደርሰው ውርጭ በወፍራም ብርድልብስ መሃል ገብቶ ፍቅርን ከመደገስ ይልቅ ከሚንቀለቀል የምድጃ እሳት አጠገብ ተቀምጠው እንዲተክዙ ይገፋፋቸዋል፡፡ ይህም ሆኖ ግን ይዋደዳሉና ተስፋ አልቆረጡም፡፡ አንዱን ቀን ጠዋት ቅድስት ባሏን ደረጀን እንዲህ አለችው፡፡ ‹‹ደሬ...ዛሬ ማታ እራት ውጪ ትጋብዘኛለህ?››
‹‹እንዴ! በደስታ ነዋ!››
‹‹ማለቴ ደህና ቦታ››
››ድሮስ….›› ልትነግረው ያልፈለገችው ነገር ፊቷ ላይ እንዳለ ስለሚያስታውቅ ግር እያለው አያት፡፡ ቀጠለች፡፡ ‹‹የት መሰለህ መሄድ የምፈልገው…በቃ…ደህና ቦታ….ደህና ሰው ብቻ የሚሄድበት ቦታ….›› ደረጀ ፈገግ አለና፤ ‹‹ገብቶኛል…›› አላት፡፡ ‹‹አልገባህም ደሬ…ዛሬ…ዛሬ ስንወጣ…››
ተንተባተበች፡፡ ‹‹ምንድነው ሆዴ…?ንገሪኝ …ምን ፈልገሽ ነው….?›› ‹‹አይ ተወው….›› ‹‹ምኑን ነው የምተወው? ምስጢር ጀመርን እንዴ?›› ‹‹አይ….›› ‹‹ታዲያ ንገሪኛ…አይዞሽ…›› ‹‹የሆነ ፊልም ላይ ያየሁት ነው….ከተጋቡ መአት አመት የሆናቸው ካፕሎች ልክ እንደኛ….እንደኛ….እንደድሮው ለመሆን ብለው ምን አደረጉ መሰለህ….››
‹‹ምናረጉ?›› ጓጉቶ ጠየቃት፡፡ ‹‹ሴቷ ምን አለችው መሰለህe….ዛሬ ራት ስትወስደኝ መጋባታችንን….ሚሰትህ መሆኔን እርሳው….ገርልፍሬንድህ ነኝ…ያውም አዲስ ገርልፍሬንድ…ገና ምንም
ያላረግን…..አንተ ደግሞ አዲሱ ቦይፍሬንዴ….››› በድንገት ዝም አለች፡፡
‹‹እያዳመጥኩ ነው….›› አለ ደረጀ አይኑን ከሚስቱ ውብ አይኖች ሳያላቅቅ፡፡
‹‹እና….እኔንም ልክ አዲስ ገርልፍሬንድህ እንደሆንኩ ይዘኸኝ እንድትወጣ ብዬ
ነው….እ?...ገና ምንም አላረግንም…..አለ አይደል….አስበው ዛሬ ብዙ ነገር አቅደን…ለመጀመሪያ ጊዜ…..ግን አባዬ ካልፈቀደልኝ አብረን ላናድር ሁሉ እንችላለን….›› ደረጀ ባልጠበቀው ፍጥነትና አኳኃን ወንድነቱ ሲነቃቃ ተሰማው….‹‹እህ…እያዳመጥኩ ነው….›› አለ በተቀመጠበት እየተመቻቸ፡፡ ቅድስት ሁኔታውን አይታ ተበረታታችና አጠገቡ ቁጭ እያለች… ‹‹የምትወስደኝ ደግሞ መጋባታችንን የሚያውቁ ሰዎች የሌሉበት ጨለምለም ያለ ቦታ ነው…እ? ገባህ? ›› ‹‹ገባኝ……›› ቀኝ እጁ ካለፈቃዱ ተዘረጋና ወደ ቀኝ ጡቷ ተዘረጋ፡፡ ጨመቃቸው፡፡ቅድስት በፍጥነት ቀኝ እጁን ከጡቷ አላቀቀችና ጧ አድርጋ መታው፤ ‹‹ አንተ ለበኋላ ሴቭ አርገው…..›› አለችው፡፡
(ይቀጥላል- ክፍል ሁለት ነገ ይለጠፋል)
‹‹ደስ ይላል››
(ሕይወት እምሻው)
ክፍል ሁለት
-----------------
ማታ አንድ ሰአት አካባቢ ደረጀ የቅድስትን ቅዱስ ሃሳብ ይመጥናል ብሎ የመረጠው ዘመነኛ እና ደንገዝገዝ ያለ ሬስቶራንትና ባር ሄዱና ቪ አይ ፒ ክፍል ተደላድለው ተቀመጡ፡፡ ክፍሉ በትናንሽ ከሻማ ያልተሸለ ብርሃን በማይሰጡ ቀያይ የጠረጴዛ መብራቶች ብቻ ተሞልቷል፡፡ አራት ትላልቅና ወይንጠጅ ሶፋዎች፣ ሁለት ትላልቅ ጠረጴዛዎች እና መብራቶቹን የተሸከሙ ስድስት ትናንሽ የጎን ጠረጰዛዎች አሉት፡፡ መሬቱ ከጥግ እስከ ጥግ በቀይ ምንጣፍ ተሸፍኗል፡፡ ከነቅድስት ሌላ አንድ ወንድና ሴት ባንዱ ጥግ ሆነው ይነካካሉ፡፡ ገና ከመቀመጣቸው፤ መልከመልካም የሆነ አስተናጋጅ በርዝመቱ የድሮውን
አዲስ ዘመን ጋዜጣ የሚያስንቅ ሜኑ ይዞ መጣና ለደረጀ አቀብሎ ትእዛዝ
መጠበቅ ጀመረ፡፡ ‹‹ምን እንብላ የኔ ቆንጆ?›› አለ ደረጀ ሜኑውን አየት እንኳን ሳያደርግ ለቅድስት እያቀበለ፡፡ በፍጹም ትኩረት ያያታል፡፡ ‹‹አንተ ምረጥ የኔ ፍቅር….እኔ የማልበላው ፓስታ ብቻ ነው…አይስማማኝም…በዛ ላይ ያወፍረኛል…›› አለች በደብዛዛው ብርሃን አይኑን እያየች ላዩ ላይ ልጥፍ እያለች፡፡ ደረጀ መረጃውን እንዳዲስ ሰምቶ፣ የሚፈልገውን ምግብና የቤቱን ውድ ቮድካ እዝዞ ሲጨርስ አስተናጋጁ በተለይ ቅድስትን እያየ፤ ‹‹ደስ ትላላችሁ…›› አለና ሄደ፡፡ ተያዩ፡፡ ከስንት አመታት በኋላ ‹‹ደስ ትላላችሁ‹‹ መባላቸው የልባቸውን ዳንኪራ ጨምሮት በደስታ ተያዩ፡፡ እየተቅበጠበጡ በተራቡ አይኖቻቸው ተያዩ፡፡ እንዲህ ያለው መቅበጥበጥ ለተጋቡት ጥንዶች አዲስ ነበር፡፡ ይህ መንገበገብ- በመስገብገብ መተያየት- ሶሰት አመታት በትዳር ለኖሩ የተሰላቹ ባለትዳሮች እንግዳ ስሜት ነበር፡፡ ግን ደስ የሚያሰኝ እንግዳ ስሜት፡፡በመፈላለግ በሚተሻሹ እጆቻቸው ላይ ያሉት የጋብቻ ቀለበቶቻቸው በጨለማው
ውስጥ ሲያንፀባርቁ…እዚያ ጥግ- ሌላኛው ሶፋ ላይ ሆነው የሚቃበጡት ጥንዶች ቢያዩዋቸው ሁለቱም በየትዳራቸው ላይ የሚማግጡ ስዶች ናቸው የሚል ግምት መውሰዳቸው አይቀርም ነበር፡፡ ራት ሆዳቸው ጢቅ እስኪል በልተው ሊጨርሱ ሲሉ ደረጀ ሞቅ ብሎት፣ ቅድስት ደግሞ ፍፁም ሰክራ ነበር፡፡ አይኖቿ እየተጨናበሱ፣ ጉንጮቿ በስካር ግለት እየነደዱ፣
‹‹ደሬ….›› አለችው፡፡
‹‹ወዬ የኔ ፍቅር….››
‹‹እሰቲ ዛሬ አንድ ነገር ንገረኝ…››
‹‹ምን የኔ ፍቅር?›› ‹‹እ…ከኔ በፊት ከብዙ ሴቶች ጋር ወጥሃል አይደል…?›› ደረጀ ሞቅታው በንኖ ደነገጠ፡፡ ያልጠበቀው ጥያቄ ነበር፡፡ በዚህ ሰአት ገና ያላወጣኸኝ ገርልፍሬንድህ ብቻ ነኝ ላለችው የሰማኒያ ሚስቱ ከእሷ በፊት ስለነበር የፍቅር ገድሉ ይደብቃታል ወይስ ይጎርራል? ለምን ጠየቀችው? ሚስቱ የመጀመሪያው…ሁለተኛው..ሶስተኛው…አራተኛው ወይ አስረኛው እንዳልሆነች፣ ከእሷ በፊት ከብዙ ሴቶች ጋር ላይ ታች እንዳለ በዝርዝር ባይሆንም ታውቃለች፡፡ ስለዚህ እንዲህ ያለ ጥያቄ አትጠይቀውም፡፡ ስለዚህ የዚህ ጥያቄ ባለቤት አዲሷ ገርልፍሬንዱ እንጂ አሮጌዋ ሚሰቴ አይደለችም ብሎ ደመደመና ምን ልበላት ብሎ ሲያስብ፣ ‹‹በናትህ ንገረኝ›› አለችው ደረቱ ላይ ተለጥፋ፡፡ ደማቅ ቀይ ሊፒስቲኳ ሰማያዊ
ሸሚዙን እንዳይነካበት ሳትጠነቀቅ፡፡
ዝም አለ፡፡ ‹‹እ…በላ! ስንት ሴት አፍቅረሃል? ስንት ሴት ታውቃለህ?›› ደረጀ አዲስ የቀዳውን ሙሉ ብርጭቆ ቮድካ አንስቶ በረጅሙ ጠጣና ‹‹ማፍቀር…ማፍቀርና ማወቅ እኮ ይለያያል የኔ ቆንጆ›› አለ፡፡ ለሚሰቱም፣
ለገርልፍሬንዱም የሚሆን ችግር ውስጥ የማይከተው መልስ መስሎ ተሰምቶት
ነው እንዲህ ያላት፡፡ ‹‹ጅል…!እሱንማ አውቃለሁ….እሺ ስንት ሴቶች ታውቃለህ?›› ‹‹ማወቅ ማለት…መተዋወቅ ወይስ ልክ ባይብል እንደሚለው ማወቅ….›› ሳቀና
ፊቷን ከደረቱ አንስቶ እንደ ህፃን ልጅ በትከሻው ደግፎ ጠየቃት፡፡ ከንፈሮቿ
ለመሳም የጓጉ ይመስላሉ፡፡ ግን ለበኋላ ‹‹ሴቭ›› እያደረገው ነው፡፡ ‹‹ወሬኛ…ማወቅ ማወቅ ነው…በቃ እሺ ከኔ በፊት ስንት ሴት ስመሃል?...እ…በዚህ ከንፈር…›› የላይ እና የታችኛው ከንፈሩን እንደ ክራር ክሮች እየመታች፡፡
‹‹እኔንጃ….እንዴት ይሄን ላውቅ እችላለሁ?›› ‹‹እንዴ! ቆጥረኻቸው አታውቅም ማለት ነው? ›› ‹‹ለምን ብዬ እቆጥራለሁ?›› ‹‹ካልቆጠርካቸው ብዙ ናቸው ማለት ነው….›› ‹‹የኔ ቆንጆ…የድሮ ታሪኬን ታውቂ የለ….ሁሉን አውርተናል..ላንቺ የመጀመሪያሽ እንደሆንኩ አውቃለሁ ግን ሁሉን ነገር ነግሬሽ የለ?›› ‹‹ኖኖ…ደሬ ደሞ! አትሰግጥብኛ! ገና አሁን ነው የተዋወቅነው እኮ! …ገርልፍሬንድህ ነኝ….ምናይነቱ ነው? ይልቅ ዝም ብለህ አውራኝ….›› ደረጀ ሳቀ፡፡ ጨዋታዋ ገባው፡፡ መቅናት ፈልጋለች፡፡ በቅናት ተለኩሳ ገላው ላይ መብረድ ተመኝታለች፡፡ ‹‹ያው መቼስ ደህና ሰው ለማግኘት የግድ ከሰው ሰው መሄድ አይቀርም…ወንድ ልጅ ደሞ….›› ‹‹እና ብዙ ናቸው ማለት ነው?›› ‹‹ምናልባት…›› ‹‹ኦኬ...በግምት ስንት ይሆናሉ ?›› ‹‹የኔ ቆንጆ የእውነት አላውቅም…አንዱን አመት ትንሽ በሌላው አመት ደግሞ በዛ ይላሉ….›› ‹‹እሺ በአመት እንዲያው በአቬሬጅ ስንት ይሆናሉ?›› ‹‹እንጃ…ሃያ…ሰላሳ…አንዳንዴ ደግሞ ድርቅ ያጋጥማል…አምስት ወይ
ስድስት…›› ‹‹እንዴ! ታዲያ በአስራ ስምንት አመትህ ዘግይተህ ጀመርክ እንኳን ቢባል ….ያ እኮ ቢደመር ሰባ ሰማኒያ ሊሆኑ ነው!›› ‹‹እንጃ እንግዲህ ይሆናል….›› በኩራት ፈገግ አለ፡፡: ቅድስት በድንገት ከእቅፉ ወጣችና ‹‹አንተ! ደግሞ ትስቃለህ እንዴ? በጣም ያስጠላል!›› አለችው፡፡ ደነገጠ፡፡ ‹‹ምኑ ነው የሚያስጠላው?›› ‹‹ምኑ ነው የሚያስጠላው ይለኛል እንዴ? ከሰማኒያ ሴት ጋር መውጣት… መተኛት…አያስጠላም?›› የቤት፣ የጭቅጭቅ ድምፅዋ ተመልሶ መጣ፡፡ ደረጀ ግራ ተጋባ፡፡ ደረጀ ተበሳጨ፡፡ ይሄ ሁሉ ቲያትር…ይሄ ሁሉ ኪነት ተመልሶ ጨቅጫቃ ሚስት ለመሆን ነው? ‹‹ባክሽ….ሰባም ሰማኒያም.. አንድም ያው ነው….›› አለ፡፡ ስካሩ ቃላቶቹን ከአፉ ገፍትሮ እንዳወጣቸው እየተሰማው፡፡
‹‹አንድማ አይደለም!›› ቅድስት ጮኸች፡፡
ከፍ ብሎ ከሚሰማው የኬቲ ፔሪ ‹‹ሮር›› ሙዚቃም በላይ ስለጮኸች ጥግ ላይ
ያሉት ጥንዶች ወደነሱ አዩ፡፡ ‹‹አትጩሂ…ደግሞ እንዴት ነው አንድ የማይሆነው?›› አለ፡፡ ‹‹ ምክንያቱም…ካንዲት ሴት ጋር ብቻ ስትሆን ፍቅርም ይባረካል….የምር ትፋቀራለህ…እውነተኛ ፍቅር ይኖርሃል›› ‹‹ባክሽ አትመጻደቂ…›› ‹‹ ጭራሽ እኔን? ….ወንዶች ግን ከዚህ ሁሉ ሴት ጋር እንዴት እንደምትሆኑ አይገባኝም እንስሳነት ነው….›› ጭንቅላቷን የሚቀፍ ነገር እንዳየ፣ የሚመር ነገር እንደቀመሰ ሰው እያንቀጠቀጠች፡፡ ‹‹ስላልሞከርሽው ነው…ብታውቂው የአለም ጣእም ሁሉንም መቅመስ ነው….››
‹‹እ?›› ‹‹አንቺ አሁን ሁሌ ሽሮ ብቻ ብዩ ብትባይ ትበያለሽ? አትበይም!›› ‹‹ባክህ ዝም በል….እኔን ሽሮ ማድረግህ ነው አይደለም? ሁሉን የለመደ ሰው
አንድ ሲይዝ የሚሰለቸው ለዚህ ነው..አንተም ያው ነህ…ትቀፈኛለህ…ደሞ
ድፍረትህ! ›› አለች… ትናንሽ ልጆች የልጅ ጠብ ሲጣሉ…ሸላላላላ ፑቲካ ሲባባሉ ላለመነካካት ፈቀቅ ብለው እንደሚቀመጡ እየሸሸችው፡፡ ለአንዲት ምሽት እንኳን ሚስቱ እንጂ ገርልፍሬንዱ መሆን አለመቻሏ እየበላት…የከሸፈ ጨዋታዋ እያበሳጫት… ‹‹ከቀፈፍኩሽ ለምን አገባሽኝ? ለምንስ እንዲህ ያለ ጥያቄ በዛሬ ቀን ጠየቅሽኝ? ›› ‹‹ምክንያቱም…›› አለች መለስ ብላ እያየችው፡፡ እስክትጨርስ ጠበቃት፡፡ ዝም አለች፡፡ ‹‹ምክንያቱም ብሎ መልስ አለ?›› ቆጣ ብሎ ጠየቀ፡፡ ‹‹ቆይ ግን እኔ ምልህ…ምን ምን አይነት
ሴቶች ነበሩ ግን? አርቲስቶችባለቡቲኮች? ሹገር ማሚዎች? ›› ‹‹ከያይነቱ›› ‹‹ወይ ጉድ….! ያው መቼስ መጨረሻ ላይ ደግምግሞሹ ሳያሰለችህ አልቀረም…ለዚያ ነው ያገባኸው….›› ‹‹አይ…ለውጥ መች ይሰለቻል ብለሽ ነው….የሚሰለቸው ሁሌ አንድአይነት ነገር…ሁሌ አንድ አይነት ሰው ነው….›› እሱ መጠጡን ሲጋት እሷ ስካሯ የፈቀደላትን ያህል ማሰብ ጀመረች፡፡ ምን እያላት ነው? ሁሌ ሽሮ እንደመብላት ነሽ….ሰልችተሸኛል…ለውጥ እፈልጋለሁ…እንኳን እኔ ብዙ ያየሁት አንቺም መለዋወጥን ስለማታውቂ ብዙ ቀርቶብሻል…? ብርጭቆዋ ውስጥ የቀረችው ቦድካ ጨለጠችና፤ ‹‹ሽንት ቤት ሄጄ ልምጣ›› ብላ ሚዛኗን እንዳትስት እየተንገዳገደች ተነሳች፡፡ አልተከተላትም፡፡ ከክፍሉ ስትወጣ ከዚያ..ቅድም ››ደስ ትላላችሁ› ብሎ በአይሆኑ አኳሃን ካያት አስተናጋጅ ጋር በር ላይ ተገጣጠሙ፡፡ በስካሯም በፍላጎትዋም ልትወድቀበት ነበር፡፡ ልክ ተዘጋጅቶ ይጠብቃት እንደነበር ሁሉ ቅልብ አደረጋት፡፡ ‹‹ውይ…ሃይ…›› አለችና ደረቱን በሁለት እጆቿ ለመላቀቅ ሳይሆን ደረቱን ለመንካት በታለመ መልኩ ነካችው፡፡ ነካካቸው፡፡ ‹‹ሃ…ይ›› አለ ከጀርባዋ ባሏ እንዳልተከተላት በሚያረጋግጥ ሁኔታ አካባቢውን ቃኝቶ ሲያበቃ እየደገፋት፡፡ ‹‹ሽንት ቤቱ የቱ ጋር ነው የኔ ቆንጆ….›› አለች ድጋፉ ላይ እየተመቻቸች፡፡ ‹‹ነይ ልውሰድሽ….›› ከአስራ አምስት ደቂቃ በኋላ ከባሏ አጠገብ ሶፋ ላይ ከመቀመጧ ፈገግ አለችና ‹‹ደሬ…ልክ ነህ…ለውጥ አሪፍ ነው…ደስ ይላል…በጣም ደስ ይላል ›› አለች ተሞዥቆ ተሞዥቆ ሙሉ በሙሉ የለቀቀ ሊፕስቲኳን ለመተካት ከትንሽ ቦርሳዋ ሊፕስቲኳን እየፈለገች በዚያውም የቆንጅዬውን አስተናጋጅ ስልክ የያዘውን ቁራጭ ወረቀት ቀስ ብላ ቦርሳዋ እየከተተች፡፡

@wegoch
@wegoch
@paappii
ወዳጆቼ ለኢትዮጵያ የምታስቡ፣ ሰላምና አንድነትን የእውነት የምትሹ ከሆነ ብሔር፣ ሐይማኖት አልያም የሆነ አስተሳሰብ የሚያራምድን ስብስብ ነጥሎ የሚመታ ነቆራ፣ ስድብና የንቀት ቃላትን አቁሙ! (ቀልድም ቢሆን ይቅርባችሁ)
ብዙ ሺህ ተከታይ ያላቸው ሰዎች ሳይቀር የሌላን ማንነት የሚያንቋሽሽ ነገር ሲጽፉ እመለከታለሁኝ። የተንቋሸሸውና የተሰደበው አካል አጸፋውን ሲመልስ (በመሐሉም ሰው ሲጎዳ) ደግሞ ራሳቸው ከንፈር ለመምጠጥና ጥሩ ሰው መስለው ለመታየት ይሞክራሉ። ይህቺን ነፍ አይነት አመለካከትና ፍላጎት የሞላት ሐገር ሰላም ከፈለግን ግን ሌላውን እናክብር። የሚሳደቡና የጥላቻ ንግግርን የሚነዙ ሰዎችን በብሎክ እንሰናበታቸው። እባካችኹን በጣም አደገኛ ወቅት ላይ ደርሰናል። ሁላችንም የሌላውን እውነት በማንቋሸሽ የኛ ብቻ እንዲገዝፍ እንሻለን፤
ያ መሆን አይችልም። ለአማራው የምታስብ ከሆነ ኦሮሞን ከነ አመለካከቱ አክብር፣ ትግራዋዩን ከነ አመለካከቱ አክብር፣ ሌላውን ብሔር በሙሉ ከመስደብና ከማናናቅ ተቆጠብ! ለኦሮሞ የምታስብ ከሆነ ኣማራውን፣ ትግራዋዩን፣ ጉራጌውም፣ ወላይታውን፣ ሶማሌውን፣ ሲዳማውን፣ አፋሩን... ሁሉንም ከነ ባህሉና አመለካከቱ አክብረው። ጥቂቱ ስድብና ጥላቻን ቢዘራም ለብዙኃኑ ስትል ባላየ ባልሰማ እለፈው። አንተ/አንቺ ግን በግልህ ማንንም አታስቀይም። በኛ ተራ በሚመስሉ ስድቦችና ነቆራዎች ቂም ተረግዞ፣ ያ ቂም ተወልዶ ግጭት ሲነሳ የሚመጣው ፍጅት ብሔርና ድርጅት የማይለይ የህዝብ እልቂት ሊሆን እንደሚችል አርቀን እንመልከት።
#ንቁ
#StopHateSpeech
............. (ዶ/ር ኤልያስ ገብሩ አዕምሮ)
2024/09/27 09:37:28
Back to Top
HTML Embed Code: