Telegram Web Link
ለውብ ቀን
💚
ውብ ቀናችንን አሀዱ ብለን በካህሊል ጂብራን ስንጀምር በሰጠን የጥበብ ቱሩፋት ስንቋደስ…



☞ ሊቀኑብኝ ወይም ሊጠሉኝ የሚችሉ ከበታቼ ያሉት ብቻ ናቸው፡፡
ከማንም ሰው የበለጥኩ ስላልሆንኩ ቀንቶብኝም ሆነ ጠልቶኝ የሚያውቅ የለም፡፡


እኔን ማሞገስ ወይም ማውገዝ የሚችሉት ከበላዬ ያሉት ብቻ ናቸው፡፡


ከማንም ያነስኩ ስላልሁንኩ አሞግሶኝም ሆነ አውግዞኝ የሚያውቅ የለም፡፡



የሰው ልጅ ምን እንደ መልአክ መናገር/መስበክ ቢችል የሚኖረው ግን እንደ ሰው ነው



ኩሩ መሆን ማለት ከምትፈልገው በታች መውሰድ ማለት ነው



ፍቅር የመለያያ ሠዓቱ እስኪደርስ ድረስ የራሱን ጥልቀት አይረዳም


ውብ ቀን!

@wegoch
@wegoch
ለምሽታችን
💚

“ከመናገርህ በፊት አስብ፤ ከማሰብህ በፊት አንብብ”
ይላል ደራሲው ፍራን ሊዊዝ የንባብን ጠቀሜታ ሲያመሣጥር። ያነበበ ሰው ሲያስብ
ነገሮችን በጥልቀት የማየት እድል ይኖረዋል የሚል ሀሳብም ያጋራናል።


የሕይወትን ምስጢር ለመፈተሽ፣ ዕውቀት ለመጨመር መፍትሄው ማንበብ ነው፣ ንባብ
በራስ የመተማመን ስሜትህን እንደሚጨምርልህና እውቀትህን እንደሚያሰፋልህ
የሚታወቅ ነው።


አንድ ጊዜ ሳነብ ያገኘውሁት ጋሽ ስብሀትን እንዲህ ብሎ ይጠይቀዋል “ጋሽ ስብሐት
የመጽሐፍት ንባብ ለምን ይጠቅማል? እስኪ ይህን ጉዳይ አስረዳን?” አለው።


ጋሽ ስብሐት ሲመልስ፤ “ይህን ቀሽም ጥያቄህን ወዲያ ተውና ይልቅ አንድ ታሪክ
ላጫውትህ…” ብሎ ወግ ጀመረ።


የስብሐት ወግ ያተኮረው ሰር ዋልተር ስኮት ስለተባለ ሰው ነበር። ይህ ሰው በዚህች ምድር
ላይ ሲኖር አብዛኛውን ጊዜውን ከመፃሕፍት ጋር አሳልፏል። ዋልተር ስኮት በዓለም ላይ
የተፃፉ ታሪኮችን ሁሉ ሲያነብ ሲመራመር የኖረ ሰው ነው። እርሱ ያልኖረበትን፣ ከወዲያኛው
ዓለም የነበረውን የሰው ልጅ ታሪክ አንብቦ፣ እርሱ ያለበትን ገሀድ ዓለም በመፃህፍቱ
አማካይነት አይቶ፣ መጪውንም ዘመን ተረድቶ ይህችን ዓለም የሚሰናበትበት የመጨረሻዋ
ሰዓት ደረሰች።


ታዲያ በዚህች ሰዓት ቄስና ሽማግሌ ጠርቶ ኑዛዜ ውስጥ አልገባም። ይልቅ ወደ ቤተ-
መፅህፍቴ ውሰዱኝ አለ። እዚያም በዊልቸር ወሰዱት። መፃህፍቶቹን አያቸው።
አመሰገናቸው። ውስጤ እንዳይጐድል አደረጋችሁኝ፣ ሰብእናዬን ሞላችሁት፣ እናም
ሳልሳቀቅ ወደ ሌላው ዓለም ደግሞ ልጓዝ ነው። እዚህ ሙሉ ሠው ስለነበርኩ እዚያ ጐድዬ
የምታይበት ምክንያት የለም። ችርስ ብሏቸው ነው የተሰናበታቸው።
በመሆኑም ንባብ ፈታኝ ሊሆንብህ ቢችልም እንኳ ከማንበብ ወደ ኋላ አትበል!


“ከመናገርህ በፊት አስብ፤ ከማሰብህ በፊት አንብብ”

ሸጋ ምሽት!💚

@wegoch
@wegoch
@balmbaras
ለውብ ቀን
💚


የሰው ልጅ ሁሉ አንድ ነው። ልዩነት የሚመጣው በዕውቀትና በብልጠት ነው። በድፍረቱም
ሆነ በጉልበቱ የሚመካ ይጠፋል። ዕውቀትን የሙጥኝ ያለ ግን ይኖራል።


ኢ-ደመነፍሳዊ ዕውቀት አይወረስም። በደም ወይም በዘር አይተላለፍም። የዚህ ጥሩ
ማስተላለፊያው መጽሐፍ ነው።


የዶክተር ፈቃደ አዘዘን ግጥም የንባብ መንፈስ መጥፋቱን በግጥሙ ላይ እንዲህ
ይገልፀዋል።


ይጮኻል ደራሲ
……………..
ይጮኻል ከያኒ፤
ግን ማን አዳምጦ?
ኧረ ማንስ ሰምቶ?
ሁሉም እጆሮው ላይ በሆዱ ተኝቶ፡፡
አንድ ጣሳ አረቄ ፤አንድ በርሜል ጠላ
ጠጃጠጅ አምቡላ
ከአስራአስር ክትፎ ጋር፣አስር ኪሎ ሥጋ
ቢጎምድ ቢሰለቅጥ ቢቸልስ ቢለጋ
ይመርጣል ዘመኑ፤
ጥበብ ለሱ ምኑ?
ድርሰትና ግጥም ፣ኧረ ምን ለከርሱ
ለባዳ ኀሊናው ለባዳ መንፈሱ

ሸጋ ጁምአ!💚

@wegoch
@wegoch
ምናባዊ ካፒታል

ከእግር ጥፍራቸው እስከ ራስ ጸጉራቸው በዕዳ ባህር የተዘፈቁ ነዋሪዎች የሚኖሩባት
አንዲት ከተማ ነበረች። ኑሯቸውን የሚገፉት በመበዳደር ነው። ከዕለታት አንድ ቀን የሆነ
ሐብታም ቱሪስት የመኝታ አልጋ ለመያዝ በዚህች ከተማ ውስጥ ወደሚገኝ ሆቴል አመራ።
የእንግዳ መቀበያ ጠረጴዛው ላይ አንድ መቶ ዶላር አስቀምጦ የተሻለ የመኝታ ክፍል
ለመምረጥ ወደ ፎቁ ወጣ።
.
.
ይህን መልካም አጋጣሚ የተመለከተው የሆቴሉ ባለቤት ከጠረጴዛው ላይ የተቀመጠውን
አንድ መቶ ዶላር አንስቶ በፍጥነት በአቅራቢያው ከሚገኝ የሉኳንዳ ነጋዴ ዘንድ በመሄድ
የነበረበትን እዳ ከፈለ። ልኳንዳ ነጋዴው በደስታ ጮቤ ረገጠ። በሳቅ ተፍለቀለቀ። ልኳንዳ
ነጋዴውም የቀንድ ከብት ሻጭ ወደሆነ ደንበኛው በማምራት የነበረበትን እዳ ከፈለ። የቀንድ
ከብት ሻጩም በአቅራቢያው ካለ የእንስሳት መኖ አቅራቢ ነጋዴ ላይ የነበረበትን ዕዳ በሙሉ
ከፈለ። የመኖ አቅራቢ ነጋዴው በተራው መኖውን ከሩቅ አካባቢ ለሚያመጣለት የጭነት
መኪና ሾፌር የነበረበትን ዕዳ ከፍሎ ተገላገለ። የጭነት መኪናው ሾፌር መግቢያችን ላይ
ከላይ የገለጽነው የሆቴል ባለቤት ዘንድ አመራ። መኖውን ጭኖ ሲመጣ ጎኑን ለማሳረፍ ሲል
በዱቤ ይጠቅመበት የነበረውን የአልጋ ኪራይ ለሆቴሉ ባለቤት ወዲያው ከፈለ። ያቺ መቶ
ዶላር ተሽከርክራ ፍዳውን ከበላች በኋላ ወደ መጀመሪያ ቦታዋ በአማን ተመለሰች።
ሐብታሙ ቱሪስት ከፎቁ ላይ ከመውረዱ በፊት የሆቴሉ ባለቤት ተመልሳ በእጁ የገባችውን
መቶ ዶላር የነበረችበት የእንግዳ መቀበያ ጠረጴዛ ላይ አስቀመጣት።
.
.
ሐብታሙ ቱሪስት የመኝታ ክፍሎቹ ሁኔታ አልተመቸውም። መቶ ዶላሩን ተቀብሎ ከተማዋን
ለቆ ወጣ። የዚያች ከተማ ነዋሪዎች ዕዳቸውን እርስ በርስ ከመክፈል ውጭ አንድም ትርፍ
የሚባል የላቸውም። ሁሉም እዳቸውን ከፈሉ ፤ መቶ ዶሏሯም ወደ ባለቤቷ ተመለሰች።
አሜሪካም የዓለምን ኢኮኖሚ የምትዘውረው እንዲህ እያደረገች ነው።

(( መሀመድ አህመድ ))

@wegoch
@wegoch
@balmbaras
ለውብ ቀን!
💚

የእውነት ዓይኖች የታደለው ባለቅኔ

#ከበደ ደበሌ ሮቢ


በሩቅ ምሥራቅ የአያሌ ሺህ ዘመናት የማርሻል አርት ጥበብና በዘመናዊው ዓለም
አስተሣሰብ የመምህር ከፍ ያለው ደረጃ MASTER ነው፡፡
በሠው ልጆች ታሪክ ውስጥ ከተከሰቱ ጥቂት ታላላቅ ማስተሮች ኢትዮጵያዊው ነገር አዋቂ
ሠሎሞን ደሬሳ አንዱ ነው፡፡ ሠሎሞን ድንቅ መካርም ነው፤ ፍንትው ያለ የእውነት ዓይን
(The eyes of Truth) ያለው ታላቅ ባለቅኔ ደራሢና ጋዜጠኛ፤ አሠላሣይና ፈላሥፋ፤
ሀሣበ ትጉህና ልበ ብሩህ…
የበራለት (Enlightend የሆነ) ልዕለ ሠብ ነው፡፡ ዛሬም የሠባ አምሥት ዓመት አዛውንት
ሆኖም የዘላለም ተማሪ፤ በነቢበ ነፍሥ በንቃት በተገኘበት እያንዳንዱ ቅፅበት ወደ ልቡ
የመጣው ወደ ዓይንና ጆሮው የገባው ነገር ሁሉ እርሱ የሚማርበት፤ የዘላለም ተማሪ
እንዲሆን የተደረገበት ክሥተት ነው፡፡ አእምሮው ንቃቱ፣ (ነቢበ ነፍሱ) ያስባል ያውቃል፤
በደመ ነፍሱ (Instinct) ያውቃል፤ መንፈሡ ደግሞ ከሁሉም የበለጠ ያውቃል፡፡

የእንቅልፎቹ የሸለብታ ሠዓታት ለሌሎች በማውራት ወይ በማስረዳት የተጠመደባቸው
ቅፅበቶች በነቢበ ነፍሥ በንቃት ያልተገኘባቸው ወቅቶች ናቸው፡፡ መናገር ስትጀምሩ
ማሠባችሁ ይቆማል ይላል ተወዳጁ መምህር ካህሊል ጂብራን፡፡ ከሃሣቦቻችሁ ጋር
መስማማት ሲያቅታችሁ መናገር ትጀምራላችሁ … ከዛሬ ሃምሣ ዓመት በፊት ግድም
ሠሎሞን በታላቁ ኢትዮጵያዊ ሠዓሊ ፕሮፌሠር እስክንድር በጐሥያን ሥዕሎችና በሠዓሊው
ጥበባዊ ሠብዕና ላይ ያቀረበውን ሂሣዊ ትንታኔ የሚያህል የተባ የሠላ የበራ ያማረ …
ጥበባዊ ሂሥ በመላ ህይወቴ በጭራሽ አይቼ አላውቅም፡፡

በእርግጥ ልክ ቭላድሚር ኤሊየች ኡልያኖቭ እንዳለው፡- እኛ ከአባቶቻችን የበለጠ
እንዋጋለን፤ ልጆቻችን ደግሞ ከእኛ የበለጠ ይዋጋሉ …፡፡ ይሄን ውጊያ ወደ ጥበብ ውበት
ወደ እውቀት ጉልበት ከወሠድነው ሁል ጊዜ በቀድሞዎቹ ትውልዶች ውስጥ ካየናቸው
ኃያላት ይልቅ በመጪዎቹ ትውልዶች ውስጥ የምናያቸው ታላላቅ ሠዎች ይበልጣሉ … እንደ
ማለት፤ ከትናንት ይልቅ ዛሬ ከዛሬ ይልቅ ነገ የተሻለ ሠው የተሻለ ልሂቅ ይመጣል፡፡ በአሁኑም
ሆነ በመጪው ኢትዮጵያዊ ትውልድ ውስጥ ትጉህና ብሩህ የእውነትና የፍቅር ዓይኖች
ያላቸው ታላላቅ ኃያሢያን እንደሚመጡ ወይ እንደሚኖሩ ቅንጣት አልጠራጠርም፡፡ ሠሎሞን
ፅፎት ፕሮፌሰር ተስፋዬ ገሠሠ በኢትዮጵያ ራዲዮ ያነበበውን በእውነትና በውበት፣
በሥላትና ከፍ ባለ እውቀት የተኳለውን ጥበባዊ ሂስ ያደመጥኩት የዛሬ አሥራ አራት ዓመት
በ1990 ዓ.ም ነው፡፡ ፅሁፉ በራዲዮ በቀጥታ ለህዝብ የተለቀቀው በ1952 ዓ.ም
የሠሎሞን የመጀመሪያ መፅሀፍ ከመታተሙ አሥራ አንድ ዓመት ቀደም ብሎ ሲሆን ያኔ
ሠሎሞን የሃያ አራት ወይም የሃያ አምሥት ዓመት ወጣት ቢሆን ነው፡፡
ሠሎሞን የእውነት ዓይኖች ብቻ ሣይሆን የእውነት ፍቅርም (Love of Truth) የታደለ፣
እጅግ ከፍ ያለ ክቡር ሠብዕና ያለው ሠው ነው፡፡ በኦሮምኛ፡- ጃለለ ዱጋ [የእውነት ፍቅር
(Love of Truth)] የሚል ሀረግ (Phrase) እንዳለ አውቃለሁ፡፡ ሠሎሞን ሲወለድ ከፍ
ያለና ለየት ያለ ሠብዕናው ከእውነት ፍቅር ጋር አብሮ ተወለደ፡፡ … ዋጋው ከጠቢቡ እውቀት
እንኳ እንደተሠወረ … ይላል ፐርሺያዊው የአምላክ ክብር ባሃኡላኽ.. ከፍ ያለውን የሠው ልጅ
ሠብዕና ታላቅነት ሲገልፅ፡፡ እንደ ባሃኡላህ አቀራረብ ጠቢቡ እግዚአብሔር ነው፤ ዋጋው
ከጠቢቡ እውቀት እንኳ የተሠወረው ደግም ሠሎሞን፡፡ ከማስደነቁ ብዛት የተነሣ፡፡ ጃለለ
ዱጋን በሠማሁበት ምሽት፡- “ተሠቀለ ቢሉኝ ሞፈሩ ነው ብዬ ተሠቀለ ቢሉኝ ቀንበሩ ነው
ብዬ … ለካስ በላይ ኖሯል ትልቁ ሠውዬ” የሚል የአማርኛ ዘፈን ሠምቻለሁ፡፡

ችግኝ ቶሎ ብሎ እንዲያድግ በየማለዳው እየተነሣህ ሥሮቹ ከተንሠራፋበት የምድር ገፅ
እስኪነቀነቅ ድረስ ቅርንጫፎቹን ይዘህ ሽቅብ አትጐትተውም፤ እያንዳንዱ ነገር ለማደግ
የራሱ ሂደት አለው …” የሚል አስተሳሰብ ያለው ሠሎሞን፤ ከሺህ ዘመናትና ከብዙ መቶ
ዓመታት በፊት አክሡምና ላሊበላን የሚያህሉ የሥነ ህንፃ ትንግርቶች በታነፁበት አገር ላይ
ከነዚያ ድንቅና ብርቅ የሥነ ህንፃ ጥበባት ርዝራዥ ውርስ ከማየት ይልቅ ማገራቸው የረገፈ
ደሣሣ ጐጆዎች ማየቱ በህይወቱ ከሚያስገርሙት ክስተቶች አንዱ እንደሆነ ይናገራል፡፡
ሠሎሞን በዚህ በዛሬው ዘመን ያ ጭርንቁስ ዝተት ቡትቶ እየተገፈፈ የረገፈ ማገር የዛገ
ቆርቆሮ እየፈረሠ ሥፍር ቁጥር የሌላቸው በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ውብና ያማሩ ህንፃዎች
በመላው ኢትዮጵያ በተገነቡበትና በመገንባት ላይ እያሉ ባለበት ወቅት ወደ ትውልድ አገሩ
ቢመጣና ቢያይ በመደነቅ የሚደነግጥ በመደሰት የሚነካ ይመስለኛል፡፡ ከዚህ አንፃር እኔን
ግርም የሚለኝ ደግሞ በሠው ልጆች የሥነ ህንፃ ጥበብና የሌሎች ጥበባት ታሪክና አሁንታ
ውስጥ እፁብ ላሊበላን የሚያህል ከቶም ያለመገኘቱ ነው፤ እፁብ እለዋለሁ ቅዱስ
ላሊበላን፡፡ የህንዱ ታጅመሃል፣ የግብፅ ፒራሚዶች፣ የቻይና ግንብ፣ የፓሪስ ሎቭሬ …
የማያህሉህ እፁብ ላሊበላ፤ አንተ የሠራኸውን ድንቅ ማን ሠራ? ፡፡
“በማናቸውም የኢትዮጵያ ሁኔታ ውስጥ በኢትዮጵያ ጉዳይ ሲወስኑ የኖሩት አማርኛ
ኦሮምኛና ትግሪኛ ተናጋሪዎች ናቸው … ይሄ ግን ጥጋብ ይመስለኛል፡፡ ኢትዮጵያ የብዙ
ብሄሮችና ህዝቦች አገር ነች” የሚለው ሠሎሞን፤ በዚህ በዛሬው ዘመን ወደ አገሩ ቢመጣ
በብዙው ይደነቃል እላለሁ፡፡ አንድ ነጭ አሜሪካዊ ፈረንጅ ደራሢ ከጥቂት ዓመታት በፊት
በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አውደ ሰብ ላይ ስለ ሠሎሞን ሲናገር፡- በ”ፍቅር የምወድዳት
ፍቅረኛዬ በተጣላችኝና በተለያየን ጊዜ ነው ከሠሎሞን ጋር የተገናኘነው … አለ፤ ሠሎሞን
ከፍቅረኛህ ጋር በመለየትህ ምክንያት የተሠማህ ሥሜት በማናቸውም ጊዜ (አዘቦት)
የሚገኝ ወይ የሚሰማህ አይደለም ስለዚህ ይሄንን ሥሜት ተጠቀምበት፤ መቼውንም ሊገኝ
የማይችለውን ይሄንን ስሜት እንደ ደራሢ ተቀበለው፤ አሁን ይሄንን ስትነግረኝ በዚህ ስሜት
ሣቢያ ያለህበትን State of Mind (የአእምሮ ሁናቴ) ሌላ ጊዜ ልታገኘው ስለማትችል
በዚህ State of Mind የአንድ ደራሢ አዲስና ብርቅ የፈጠራ ሃሣብ ብቅ ይበል …”
በማለት እንደመከረው አውስቷል፡፡
በጠጠሮችና በእሾሆች መሃከል እረፍት መገቻዋን አገኘች የሚለውን የፖል ኤሊዬዘር
የፈረንሣይኛ አባባል በመጀመሪያ ገፁ የያዘው የሠሎሞን የበኩር ሥራ የሆነው የግጥምና
የቅኔያት ስብስብ፡- “ልጅነት አርባ ተኩል ግጥሞች” በሚል ርዕስ የታተመው በእኛ በ1963
ዓ.ም ከአርባ አንድ ዓመታት በፊት ነው፡፡ በዚያን ጊዜ ሠሎሞን የሠላሣ አራት ዓመት ብስል
ወጣት ነው፡፡ በመፅሀፉ መግቢያ የአራት ገፆች ሽፋን የተሠጠው “እሽቅድምድም” ብቻውን
እንኳ ትልቅ ሃሣብ ያለው አንድ ደጐስ ያለ መፅሀፍ ይወጣዋል፡፡ የመጀመሪያ ሥራው
ከታተመ ከሠላሣ ዓመታት በኋላ ለህትመት ያሠናዳውን የግጥምና የቅኔ ስብስብ “ወለሎ”
ርዕሥ፡- ብሥለት ብሎት ነበር፤ ይሁንና ደርሶ ቀንድ መንከስ እንዳይሆንብኝ ብሎ “ዘበት
እልፊቱ” በማለት በእኛ በ1990ዎቹ መጀመሪያ ላይ ለፍሬ አበቃው፡፡ በዚህን ወቅት
ሠሎሞን ዕድሜው ስድሳዎቹ መጀመሪያ አካባቢ ነበር፡፡ በግጥም አፃፃፍ ስልቱም እንደ
አስተሳሰቡ መርሆና የግል ፍልስፍናው ሁሉ፡- ሠሎሞን የራሱ ጌታ ነው፡፡
ግጥሞቹ በይዘታቸውም ሆነ በአቀራረባቸው ለየት ያሉ ናቸው፡፡ “ክቡር ኢትዮጵያውያን”
የሚለውን ግጥሙን እንደ ምሣሌ ብንወስድ፡-

ክቡር ኢትዮጵያውያን
ቂንጥር ይቆርጣሉ
ቂንጥር ይሰፋሉ
ግን ቂንጥር ማለት ያፍራሉ
በ”ልጅ
ነት አርባ ተኩል ግጥሞች”፡- ላይ ደግሞ፤ “ገድለሽኝ ነበረ” … ይለናል፡፡
ገድለሽኝ ነበረ አምናና ካቻምና
ተመልሼ መጣሁ ቂም አልይዝምና
ሠሎሞን፡- በ1920ዎቹ አጋማሽ ግድም በምዕራብ ኦሮሚያ ወለጋ ውስጥ ጩታ በተባለች
ሥፍራ ነው የተወለደው፡፡ የአራት ዓመት ህፃን ሲሆን ከወለጋ ጩታ ወደ አዲስ አበባ መጣ፡፡
ጋሼ ሥብሀት ደግሞ በአሥር ዓመቱ ከትግራይ አድዋ ርባገረድ በትሬንታ ኳትሮ ወደ አዲስ
አበባ፡፡ የኢትዮጵያ እምብርት በሆነችው ርዕሠ መዲና ላይ ተገናኙ፡፡
ፈረንሳይ አገር ኤክሣን ፕሮቫንስ በምትባል ትንሽዬ ከተማ ወደሚገኝ ዩኒቨርሲቲ ከጋሼ
ስብሀት ጋር ለትምህርት ሲላኩ፡- ጋሼ ስብሀት መፅሀፍ መፃፍ ጀመረ፡- ትኩሳትን፤ሠሎሞን
እንደ ልብ ያገኛቸውን የተለያዩ መፃህፍትን በትጋት ማንበብ ጀመረ፡፡
መምህር ሆነ ሠሎሞን ፡- MASTER የፈረንጅ የቅኔ (POETRY) ሊቃውንትንና
ተመራማሪዎችን ማስተማር የጀመረው ገና የመጀመሪያ ዲግሪውን ሳያገኝ አሜሪካን አገር
ሜኒሶታ ሜኒአፖሊስ ውስጥ ነው፡፡
ከፈረንሳይ አገር ኤክሳን ፕሮቫንስ ትንሽዬ አውሮጳውዊት ከተማ ወደ ሰሜን አሜሪካ USA
ከሄደ በኋላ መጀመሪያ መሥራት የጀመረው ሥጋ ቤት ውስጥ ነበር፡፡ ሥጋ ቤት ውስጥ
ሲሰራ ቆይቶ ለቅጽበት የማይናጠብ የሥጋ ሽታ ሲሰለቸው ሥራውን ጥሎ ወጣ፡፡ የሠሎሞን
የመጨረሻውና ሶስተኛው መጽሐፍ ርዕሱ “ስንብት” እንደሚሰኝ እርሱ ራሱ አስቀድሞ
ተናግሮታል፡፡ ልጅነት፤ ብስለት (ዘበት እልፊቱ) እና ስንብት የውዱ ኢትዮጵያዊ ባለቅኔ
የብርሃን ጭረት (የብርሃን ልቃቂት)ሠሎሞን በሶስት ጣቶች የተነካ መምህር ነው፤
በእግዚአብሔር ጣት በኢትዮጵያ ጣት እና በወለጋ (በኦሮሞ) ጣት፡፡ ኦሮምኛ የሌለበት
የሠለሞን ነገር ምንም የለም፡፡ ኢትዮጵያ የሌለችበት የሠሎሞን ሥራ አንዳች የለም፤
የእግዚአብሔር ክብር ብርሃን ያልፈነጠቀበት ጽሑፍና ንግግርም እንደዚሁ፡፡ በሥራዎቹ ሁሉ
እነዚህን ጣቶች ታያለህ፡፡ ሠሎሞን ቤተሰቡ ጭምር ከአባትየው ከብላታ ደሬሣ ጀምሮ
ምሁራን ልሂቃን (ኤሊት) እና ሊቃውንት ናቸው፡፡ ከወለጋ ጩታ ገበሬ ቤተሰብ የወጡ ወላጅ
እናቱ የሰማንያ ዓመት ባልቴት ሆነው ያማረ ቤተ መፃሕፍት አላቸው፡፡ ብላታ ደሬሣ በመላው
ኢትዮጵያ የታወቁ ነገር አዋቂ ልሂቅ ናቸው፡፡ ጋሼ ስብሃት ብላታን ሲገልፃቸው በሁሉም ዘርፍ
የበቃ ዕውቀት ያላቸው “All rounded ይላቸዋል፡፡ ሰሎሞንን መጠጥ መጠጣት ያስተውት
የሱፊዎች የጠዳና የነፃ ምግባር መሆኑን የልብ ወዳጄ ተፈሪ መኮንን ከበደ (ተ.መ.ከ)
አጫውቶኛል፡፡ ሱፊዎች እግዚሃርን በጣም አታስቸግሩት የሚሉ ከእሥልምና ሱናና ሻይት
Sects ውስጥ ብቅ ያሉ የሃይማኖት ክፍል ናቸው፤ እግዚአብሔርን ካለ ነቢይም ካለ
አማላጅም ካለ መልዕክተኛም በቀጥታ (በብርሃን መንፈስ) ማናገር (መገናኘት) ይቻላል
ይላሉ፡፡ ሠሎሞንን በአካል ባገኘው ምንም አልጠይቀውም፤ ዐይኖቹን ብቻ ማየት ነው
የምፈልገው፡፡ ዓይኖቹ ውስጥ እግዚብሔርን በብርሃን ክብር አገኘዋለሁ፡፡ ይሄ ጽሑፍ
ኢትዮጵያንና የኢትዮጵያን ህዝቦች ከሚወድድ አንድ ኢትዮጵያዊ ለሠሎሞን እና ለጥበብ
ቤተሰቦች እንደተፃፈ ይቆጠርልኝ፡፡

ሸጋ ቀን!💚

@wegoch
@wegoch
@balmbaras
ለውብ ቀን!
💚

ሰበብ
Written by ደረጀ በላይነህ


ጧት፤ ቡና ጠጥቶ ሊወጣ ሲል፣ የመጨረሻውን ስኒ ቡና
ስታቀብለው፤ ‹‹ዋ! ዛሬም ደግሞ ባዶ እጅህን ናና - ትገባታለህ!...” ያለችው
ድምፅ ሲከተለው ነበር የዋለው፡።
እየሳቀ፤ ‹‹ዛሬ እንኳን የምትወጃትን ይዤ ከተፍ ነው፡፡”
‹‹ይ-ታ-ያ-ላ!››
ሽሙጧ ገብቶታል፤ ከያዘች አትለቅም፤ ምክንያት አታውቅም፡። ስራ ቀዝቅዟል፣
ገበያ የለም… ቢሏት አይገባትም፡፡ ወልዶም ቢሆን ያምጣ ነው!
እናትዋም፤ አባትዋን እንዲህ፤ እያስጨነቁ፣ የፈቀዱትን ያስደርጉ እንደነበር
ብዙ ቀን አልጋቸው ላይ ነግራዋለች፡፡ ቢሆንም፤ ሀሳቡን ፈልቅቆ መስማት
አልቻለም፡፡ ጉያዋ ሆኖ፤ እውነት ማሰብም ሆነ መናገር አይቻልም፡፡ እሷ፤ ጉያዋ
ውስጥ እሾክ ይጠወልጋል፣ ብረት ይቀልጣል፤ ወርቅ ይነጥራል፡፡
ድሮ ድሮ - ወርቅ ነኝ ብሎ ያስብ ነበር፡። እንዳልሆነ ያወቀው፡፡ ትዳር ውስጥ
ከገባ በኋላ ነው፡፡ የአቻምየለሽ ገላ ምድርን ያስረሳል፣ ገነትን ያስገፋል፡፡
አንዳንዴ ወንድ ሁሉ እንደኔ ይሆን? ብሎ ይጠይቃል::
አንድ ቀን ሠፈራቸው ያለው ከመጽሐፍ የማይላቀቅ ልጅ፤ “የወንድ ልጅ
ገነቱም ሲኦሉም? ያው ሴት ናት” ብሎታል፡፡ ድሮም የሪሲያው ደራሲ “ሞቼ -
ሞቼ የሬሳ ሳጥን ውስጥ፣ ገብቼ፣ የክዳኑ ምስማር ካልተመታ፣ ስለ ሴት
አልናገርም፤ ብሏል ዓለምን ይለዋል፡፡
አንዳንዴ፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ ይደሰታል:: ‹‹አሁን አቻምየለሽ ባትኖር ዓለምን
እንዴት አውቃለሁ” የመኖር ጣዕም የት ይገባኛል? … የት አድርሳ
እንደምትመልሰኝ እኔስ ትርጉሙን ከየት አመጣለሁ?››… ይላል፡፡ ሲላትም
ለብልባ ታቃጥለዋለች፣ እንባውን አውጥቶ እንዲያለቅስ ታደርገዋለች፡፡
ዛሬም፤ ድምጽዋ እየተከተለው ከሄደ በኋላ የሚችለውን ሁሉ ሲጥር ዋለ፡፡
ሥራ የለም፣ ገንዘብ መበደር ፈልጎ ወደ ጓደኛው ሲደውል፣ ጓደኛው ከከተማ
ወጥቷል፡፡ የታባቱ ሄዶ ነው! ይችላል፡፡
ያኔ - ሳይከስር በፊት፣ ያኔ ሱቁ ሙሉ ሳለ፣ ጣጣ አልነበረውም፡፡ ለሁሉም ነገር
ብሩን መዥርጦ ያወጣ ነበር፡፡ በኋላ መንግስት በግብሩም - በምኑም እያለ
አደቀቀው፡፡ የደርጉ ዘመን ወኔ አልለቅ ብሎት ሲታገል፣ ባዶውን አስቀሩት፡፡
አሁን የቀረው ተስፋውና አዲሷ ሚስቱ ናት፡፡ የድሮዋ ምስኪን እንደዶኮዩ አፈር
ቀመሰች፡፡ ይቺን በድህነት ቢያገባትም… ድህነቱን አላወቀችለትም፡፡
ሲብስበት… ያ ኮማንዶነቱ ይመጣበትና ‹‹ቱቦዋን ልዝጋው?›› ይላል፡፡ ቱቦዋን
መዝጋት፣ የገነትን በር መዝጋት፣ የፌሽታውን አፀድ መመንጠር ነው!! ከንፈሩን
ይነክስና ይተወዋል፡፡
‹‹ስማ ወንድ አጥቼ እንዳይመስልህ፤ አስሩን ነበር የማስከትለው፡፡ ደግሞ
ያንተ ጡንቻ ማርኮኝም አይደል፤ ስለምታሳዝነኝ ነው፡፡ ብቻህን ሳይህ አንጀቴ
ይንቦጫቦጫል፡፡›› ትለዋለች፡፡
‹‹አዝነሽ ሞተሻል!›› በአፉ አይናገርም፤ በልቡ ነው፡፡
ደሞ - ፌስቡክ ስትወድ!..ለጉድ ነው፡፡ አሁን ፖለቲካው ሲጦዝ ቀዝቀዝ ብላ
ይሆናል እንጂ፣ ያኔስ ቡናም አላፈላ ብላ ነበር፡፡ ዕቃ ስታቀብል እንኳ ዐይኗን -
ከስልኳ ላይ አትነቅልም፡፡
‹‹በስንቱ ተቃጥሎ - ይቻላል?... ሁለቱ አንድ ይሆናሉ›› የሚሉን፤ እኔና ይህቺን
ሴት ነው?
አመሻሽ ላይ ወደ ቤት ገብቶ ሳንጃውን ሲፈትሽ፣ ራሱም ግራ ገብቶታል፡፡
‹‹ይለያል ዘንድሮ የተመስገን ኑሮ!›› እያለ በራሱ ቀለደ፡፡ ቀስ ብሎ ወደ ጓዳ
ገባና ሞረደው፡፡
‹‹ምን እያደረግህ ነው?›› ጠየቀችው፡፡
‹‹ዝም ብዬ ነው!››
‹‹ምናልባት ሌላ ነገር አሰኝቶህ ከሆነ?››
‹‹አይ?! ለማታ ቢላዋ እየሳልኩ ነው››
‹‹ድንቄም! ለአንድ ኪሎ ሥጋ ክንድህን ባታዝልስ?...››
‹‹አይ ሙክት አመጣልሻለሁ!”
‹‹የታደሉትማ - ሰንጋም ይጥላሉ!››
‹‹ለድግስ ነዋ!.. አንቺን ደግሜ አላገባሽ?››
‹‹ያንዴውም ቆጭቶኛል ባክህ!››
እየተመላለሱ ከቆዩ በኋላ ወዴት እንደሚሄድም ሳያውቅ ከቤቱ ወጣ፡፡ ስራ
ቦታ ገባ ብሎ ወዲያው ውልቅ አለ፡፡ ሱቁ ቢዘጋ፣ ወይ ቢቀር ይሻለው ነበር፡፡
አልፎ አልፎ ካልሆነ ሥራ የለም፡፡ አንዳንዴ ከጓደኞቹ ጋ ወጣ ብሎ ድለላ
ቢጤ ባይሞክር፣ ትዳሩ ፈርሶ ነበር፡፡ ደግነቱ እዚያች ጦር ሀይሎች አካባቢ
ዘው - ዘው ይላል፡፡ ሲለውም በቻይና ኤምባሲ አድርጎ ወይራ ሰፈር፣ ከዚያም
ወደ ቤተል ሄዶ ይሸቃቅላል:: ዛሬ ግን ያም የለም፡፡ ጓደኞቹም የሉም:: በዚያ
ላይ ሚስቱ ጨቅጭቃዋለች፡፡ “አርግዛ ይሆን እንዴ?›› ብሎም ትንሽ አሰበ
እንደመተከዝ ብሎ፡፡
ምንም ሳያገኝ ከምሽቱ ሶስት ሰዓት ሆነ፡፡ ሚስቱ ስትደውል ስልክ አላነሳም፡፡
ቴክስት አደረገች፤ መልስ አልሰጣትም፡፡
‹‹ሰውየው አንተን እየጠበቅሁ መሰለኝ!››
በልቡ “እኔን አዳኝ፤ አንቺ ጌታ ያደረገሽ ፈጣሪ እርሱ ያውቃል!” ብሎ ዝም
አላት፡፡ ትንሽ ቆይቶ ስልኩን ዘጋው፡፡ ትንሽ ጂን ቢጤ ቀማምሷል፣ አንዱ
ጓደኛው ነው የለቀቀበት፡፡ ጨምር ሲለው መጨመር አልፈለገም፡፡
ድንገት ወደ አንዱ ዞርታ ሄዶ የቆመች መኪና አጠገብ፣ ተጠለለና ቆመ፡፡
ማንም የለም፡፡ ግራና ቀኝ ተገላመጠ፡፡ ወታደርነቱ ትዝ አለውና፤ በሩን
ሊፈለቅቅ ከጀለ፡፡ ውስጡ ተሟገተው፡፡ ሳያስበው ‹‹ምናባክ ታደርጋለህ፤
አንተ!›› ሲለው መልስ አልሰጠውም፡፡ በቀኝ እጁ የመኪናውን ቁልፍ እንዳለ
ሾለ ነው፡። በግራ እጁ ከሥጋ ቤት ያንጠለጠላትን ፌስታል ይዟል፡፡
‹‹አንተስ ምናባክ ታደርጋለህ!›› አለና ከፍቶ እንደገባ አነቀው፡፡ ግራና ቀኝ
ሲያይ ሰው የለም:: ደረቱን ወጋው፤ ከጀርባው በኩል የተቀመጠውን በፌስታል
የተጠቀለለ ሥጋ ያዘና አመለጠ፡፡
ሰውየው ሲያቃስት ምንም አልመሰለው፡፡
‹‹በሕግ አምላክ!›› አለና ወደቀ፡፡
ነፍሱን አያውቅም፡፡ ጦር ሀይሎች ደረሰና ታክሲ ተሳፍሮ እብስ አለ፡፡
የተከተለው የለም፡፡
እቤት ሲደርስ ለንቦጭዋን ጥላለች፡፡
እየሳቀ ወስዶ ስጋውን ሰጣት፡፡
‹‹ድንቄም ሥጋ!... ፍርምባና ወርች… ምን ያደርግልኛል!... ፍርምባ ቀን ሙሉ
ቢቀቀል የማይበስል ነው፣ ወርችም ለወጥ ካልሆነ፤ ለቁርጥ አይሆን! ለጥብስ
አይሆን! ውኃ ይተፋል!...››
ንግግርዋን ከአፏ ሳትጨርስ፣ ሳያስበው በጥፊ አጮላት፡፡ ድንገት ወደቀች፡፡
‹‹ወይኔ… ልጄን!... ወይኔ ልጄን!›› አለች፤ ሆዷን ይዛ፡፡
ከጎረቤት ሰዎች እየተግተለተሉ መጡ፡፡
አቻምየለሽ ወድቃለች፡፡
‹‹ውይ ጉዴ! ውይ ጉዴ!›› አለች፤ አዲሷ የጎረቤት ተከራይ፡፡ መልስ የሰጣት
የለም፡፡
‹‹… ወንድሜን ገደሉብኝ! ወንድሜን ገደሉብኝ?›› አለችና ተመልሳ ወጥታ
ሄደች፡፡
አቻምየለሽ እያዞራት ብድግ ስትል፣ ሌላዋ ጎረቤት መጣች›…
“እንከተላት ይሆን እንዴ?... ወንድሟን መኪናው ውስጥ ገደሉት!›› አለች፤
በድንጋጤ ተውጣ አዞረው:: “ምን ዐይነት ጦስ!፣ ምን ዐይነት ሰበብ ነው!››
እያለ… ጓዳ ገብቶ አልጋው ላይ በጀርባው ዝብ አለ፡፡

@wegoch
@wegoch
🎛 አሁን online ላላችሁ ብቻ ጠቅላላ
🌐 እውቀት ጥያቄና መልስ ውድድር ተጀመረ

1⃣ ለወጣ 100 🇲🇧 ያሸልማል
2⃣ ለወጣ 55 🇲🇧 ያሸልማል
3⃣ ለወጣ 25 🇲🇧 ያሸልማል

በቅድሚያ ጥያቄ አንድ ሚለውን ይጫኑ
መልካል እድል
ለጁምኣችን
💚


የተማሪው ፀሎት
Written by ደረጀ በላይነህ


እናቱ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንደሄደች ያየው ህፃን፣ ሮጦ መኝታ ቤት ገባና በሩን
ዘጋው፡፡ ወዲያው እናቱ ስታደርግ እንዳየው፣ ግድግዳ ላይ ከተለጠፈው
የመድሀኒዓለም ምስል ሥር ተንበርክኮ፡-
“አንተ የእናቴ አባት ስለሆንክ፣ አያቴ ነህ አይደል? አያት ደሞ ጥሩ ነው…” ዝም
ብሎ ምስሉን እያየ መናገር ቀጠለ - ሕጻኑ፡፡
“በቀደም ቡሄ የጨፈርንበትን ሳንቲም እማዬ ወሰደችብኝ፤ እኔን ሣንቲም
እንዳትሠርቅ ስትለኝ፣ እሺ እያልኳት፣ እሷ ግን ወሰደችብኝ፡፡ ጓደኞቼ እነ
ሮቤልና ሠለሞን ግን አልተወሰደባቸውም፡፡
“ደሞ የወሰደችብኝ ‹ደብተር መግዣ ይሆንሃል› ብላ ነው፡፡ የሮቤል እናት ግን
‹በዚህ ዓመት ዶክተር ዐቢይ ደብተር ይገዛላችኋል› ብለዋል፡፡ እኔም በዚህ
ዓመት ትምህርት እጀምራለሁ፡፡ እባክህ ለናቴ ቤተስኪያን ውስጥ ንገራት፡፡
ብስኩትና ከረሜላ መብላት እፈልጋለሁ፡፡ ጓደኞቼን እየለመንኩ መብላት
አስጠልቶኛል፡፡”
ከውጭ የእግር ኮቴ ሰማና ደነገጠ፡፡ ወደ ኋላ ዘወር ብሎ አየ፡፡ እናቱ
ከመጣች አንጠልጥላ ታስወጣዋለች፡፡ ጆሮውን ተክሎ አዳመጠ፡፡ እህቱ
ፌቨን ናት፡፡
“ሳሚ የት ሄዶ ነው? ሲንቀለቀል ደሞ መኪና እንዳይገጨው” ስትል ሰማትና
ሳቁ መጣ፡፡
“መድሃኔዓለም አጠገቤ እያለ መኪና ይገጭሃል ትላለች!” ድምፁን ቀንሶ፣
ለራሱ አጉተመተመ፡፡
“አሁን ለእንቁጣጣሽ አበባ የሚስልልኝ በቃሉም የለም፡፡ ሞቷል፤ አንተ ነህ
የወሰድከው አይደል፡፡ እናንተ ጋ ችቦና ሆያ ሆዬ አለ እንዴ? አንተ ጋ ሲመጡ
ስንት ብር ትሰጣቸዋለህ? ብሩን ምን ያደርጉበታል? በቃሉ ጥሩ ልጅ ነበር፡፡
አምና አበባ የሠራልኝ እርሱ ነበር፡፡ ክንፍ ያለው መልዐከ ነበር የሳለልኝ፣ እርሱ
መቼም አንተ ጋ ሲመጣ… ክንፍ ያወጣል፡፡ ለእኔም ክንፍ ብታወጣልኝ ደስ
ይለኛል፡፡ ታክሲ ውስጥ ወያሎቹ ‹ይክፈል፤ ወይም አስወርጂው!” እያሉ
ያሳቅቁኛል፡፡ እናቴንም ‹‹በሌላ ታክሲ ሂጂ›› እያሉ ያበሳጩዋታል፡፡ ያኔ ልቤ
ድው ድው ይላል፡፡ ዶክተር ዐቢይ ለልጆች ታክሲ እንዲገዛልን ንገረው፡፡›› አለና
ቆም ብሎ አየው - መድሃኒያለምን፡፡ የበግ ግልገል ታቅፎ ቆሟል፡፡
“እኔ ግን ከበግ የበለጠ ድመቴን እወዳታለሁ፣ ማታ ማታ በተኛሁበት መጥታ
ታቅፈኛለች፤ ታሞቀኛለች፡፡ ጅብ ከመጣ ግን ገና ድምፁን ስሰማ እናቴ ሥር
እገባለሁ፡፡››… (አንተ ያቀፍካትን ግልገል ስታድግ ታርዳታለህ እንዴ? እባክህ
አትረዳት፤ ታሳዝናለች፡፡ የሮቤል አባት ግን ጨካኝ ናቸው፡፡ ቤታቸው
ያደገችውን በግ ለፋሲካ አረዷት፡፡ አንተ ከሞት የተነሳህበት ቀን ነው ብለው
እርሷን አረዷት:: የዛን ዕለት ሮቤል ሲያለቅስ ነው የዋለው፡፡ በጣም ይወዳት
ነበር፡፡ ማታ ግን ሥጋዋን በልቷል፡፡ በግ ሳይታረድ ሥጋ መፍጠር አትችልም
እንዴ? በናትህ ሞክር…
ዶክተር ዐቢይ ደስ የሚለኝ… በግ አያርድም፡፡ “ሠላም ፍቅር” ነው የሚለው፡፡
‹‹መግደል መሸነፍ ነው” ሲል አልሰማኸውም? ለህፃናት የትምህርት ቤት
ቦርሳ ሲሸልም በቲቪ አይቼዋለሁ፡፡ ዘንድሮ ትምህርት ቤት ስገባ፣ ዶክተር
ዐቢይ የሚሰጠንን ቦርሣ ነው የምይዘው፡፡
‹‹የኔ እህት ሰላም ግን ትምህርት ቤት የገባችው የአጐታችንን ልጅ አሮጌ
ቦርሳ ይዛ ነው፡፡ አንተንም ዶክተር ዐቢይንም አመሰግናለሁ፡፡ በቀደም ይህንን
ስሰማ ቆንጆ መዝሙር ዘምሬልሃለሁ፡፡
ምሥጋና ይገባሃል
ምሥጋና ይገባሃል
አባቴ እግዚብሔር.. ብዬ፡፡
እማዬ ብትሰማ ግን ምን ትላለች? የእናት አባት አያት አይደለም እንዴ? አንተ
የኔ አያት ነህ ወይስ አባት?...››
እህቱ ሠላም ድንገት መጥታ በሩን በረገደችው፡፡ ለካ በሩን በደንብ
አልዘጋውም፡፡ ድንግጥ አለ፡፡
“አ…ን…ተ!”
መልስ አልሰጣትም፡፡
“እኔ የት ሄደ ብዬ መከራ ሳይ እዚህ ተንበርክከህልኛል? ደሞ ማን ፀልይ
ብሎህ ነው? የሆያሆዬ ገንዘብ ወሰዱብኝ›› ብለህ እያሳበቅህ ነው››
“ለኑሮ ውድነቱ እንደሆነ እናትህ አቤት የምትልበት አጥታ ወደ ፈጣሪ ልትጮህ
ሄዳለች፡፡ ዘይት ተወደደ፣ ጤፍ ሰማይ ነካ፣ ምስር የለም፣ ሽሮ ጠፋ፣ ቤታችን
የቀበሌ ባይሆን በረንዳ ወድቀን ነበር:: ኢንጂነር ታከለ ዑማ፤ ጐዳና ተዳዳሪ
እየሰበሰበ ወደ ቤት ሲያስገባ፣ ቤት ያለው ህዝብ የሚበላው አጥቶ ሊበተን
ነው፡፡ ይሄም ጀግና የተባለ ህዝብ፣ ጀግንነቱን የሚያሳየው ወንድሙን
በመግደል እየሆነ ነው፡፡ አየኸው ረሃብ ውስጥ ሆኖ እንኳ ወገኑን ለመግደል
ቢላ ይስላል?
እውነትህን ነው… አዋቂው ቂመኛ ስለሆነ ፀሎቱ መልስ አጥቷል፡፡ አንተ
በንፁህ ልብህ ብትፀልይ ነው የሚሻለው››
መልስ በሩን ዘግታበት ሄደች፡፡ ትንሽ ቆየና ተንበረከከ፡፡
“ጌታ ሆይ፤ ጉዴ ፈላ! እማዬ ትገድለኛለች፡፡ እህል ከተወደደ፣ ጉሊት ገበያ
ከሌለ፣ “አፈር ብላ! ያንተን ከርስ ከየት አምጥቼ ልሞላ ነው?...” ትላለች::
እባክህ ድህነትን አጥፋልን፣ ሁሉ ነገር ከተወደደ መሞታችን ነው፡፡››
እንባው ሳያውቀው በጉንጮቹ ወረደ፡፡
“ምሣ የለም፣ ከየት አባክ ላምጣልህ? ትለኛለች:: ሮቤል ግን በሚቀጥለው
ዐመት ትምህርት ቤት ምሳ ይዘጋጃል ብሎኛል፡፡ ዶክተር ዐቢይ ብር ከየት ነው
የሚያመጣው? ቦርሳ፣ ዩኒፎርም፣ ምሳ… እባክህ ለርሱ ገንዘብ በደንብ
ስጠው፡፡
‹‹አንተ አባትዋ ከሆንክ ግን እሷ ለምን ደሀ ሆነች? ሁሌ መድኃኔዓለም አባቴ
ነው… ትል የለ? አባት ደሞ ገንዘብ ይሰጣል፡፡ የሮቤል አባት አንዳንዴ ኬክ
ቤት ወስዶ ይጋብዘዋል፡፡ አንተ እማዬን አንዴም ጋበዘሃት አታውቅም? የእንጀራ
አባት ነህ እንዴ? …የእንጀራ አባት ደሞ ይማታል፡፡ ጓደኛችንን የእንጀራ እናቱ
ብዙ ቀን ምሳ ትከለክለዋለች፡፡ አንተስ እናት አለህ? እናትህ ሳትወልድህ
በፊት ዐለምን ፈጥረህ ነበር? ተወው በቃ! እማዬ ይህን ብትሰማ
ትገድለኛለች!
‹‹አንድ ቀን ልጅ፤ እንደ ልጅ አስብ!›› ብላ አናቴን ብላኛለች፡፡ ሌላ ቀን ደሞ
‹‹እግዚአብሔርን ማን ፈጠረው?›› ብዬአት ቀጥቅጣኛለች፡፡ ይሄን
እንዳትነግራት፡፡
ወደ ግድግዳው ተጠግቶ ምስሉን ግጥም አድርጐ እየሳመ፤ ‹‹እኔ
እወድሃለሁ… አንተም አሳድገኝ፤ ሳድግ ምርጥ መዝሙር አውጥቼ
እዘምርልሃለሁ! አንተም ድምፄን አሳምርልኝ፤ ትምህርት የምጀምር ቀን ደግሞ
መጥቼ እነግርሃለሁ!...
‹‹አደራ እንዳትረሳ ለዶክተር ዐቢይ ገንዘብ ስጠው፡፡ ለእርሱ ከሰጠኸው ሁሉን
ነገር ይሰጠናል::›› እህቱ እየሮጠች መጣች፡፡
“ሳሚ ተነስ! እማዬ እየመጣች ነው፤ ትጠፈጥፍሃለች! ማን ፀልይልኝ አለህ
ነው የምትለው! የአባታችንን ቂም በእኛ ልትወጣ ነው መሰለኝ፡፡ ቀድሞውኑ
ወታደር ማን አግቢ አላት? እዚያ በረሃ እየኖረ ብቻውን እንዲሆን ፈልጋ ነው?
ተሳሳትኩ ካለ ይቅርታ አታደርግለትም?”
“አባዬ አለ እንዴ?” ህጻኑ ጠየቀ፡፡
“አታውቅም ነበር?”
“እማዬ ሞቷል ብላኛለች?”
“ተናድዳ ነው! እኔ በፌስ ቡክ አግቻቸዋለሁ
“እባክሽ ፌስ ቡክ አሳዪኝ!”
“ቀስ ብለህ እደግ!” ጥላው ሄደች፡፡
በጥድፊያ፤ “እባክህ ጌታዬ አባዬና እማዬን አስታርቃቸው!”
እንባው ጉንጩን አለበሰው፡፡
“ቡሄ የጨፈርኩበትን ገንዘብ ተወውና… እማዬና አባዬን እንዲታረቁ
አድርጋቸው! ባክህ እኔም አባቴን አጠገቤ ላግኘው፡፡
“የኔ መድናኔዓለም ምን ይሳንሃል”
“እውነት” አለች ሠላም፡፡

ውብ ቀን!💚


@wegoch
@wegoch
..ደብዳቤ ለሄዋኔ..
[አብርሃም የሙሉ]

ሰላም ላንቺ ባለሽበት ካለሁበት፡፡ ሄዋኔ እንደምን አለሽ? እኔ በቸርነቱ እንደ ክፋቴ እየኖርኩ አለሁኝ፡፡ አንቺስ እንደኔ ከፍተሽ ይሆን? ለፈጣሪሽ አስቸግረሽ ይሆን? ለመልካም፡፡

እኔ ጋር ሂወት መራራ ናት፡፡ ፍሬም የላትም፡፡ እኔም አንቺን እንጂ ሂወትን አልወዳትም፡፡ እልፍ ሂወት ባይኔ ሽው ብላለች፤ ልቤን ነካክታኛለች፤ በውበቷ ጥላኝ ውበቴን ንቃለች፤ እንደሌለኝ አውቃ እንዳትኖረኝ ሄዳለች፡፡ እኔ ጋራ ሂወት አላፊ ሁና አልፋለች፡፡

አንቺ ጋራ ሂወት እንዴት ነው? ፍሬ ቢስ ሆነብሽ? እኔን እንጂ ሂወትን እንደማትወጂው አውቃለሁ፡፡ እልፍ ሂወት በአይንሽ ላይ ሽው ብሏል?፤ ልብሽን ነካክቶታል?፤ በውበቱ ጥሎሽ ውበትሽን ንቆታል?፤ እንደሌለሽ አውቆ እንዳይኖርሽ ሄዷል? አንቺ ጋራም ሂወት አላፊ ሁኖ አልፏል? ለመልካም፡፡

ሄዋኔ የቀይ ዳማ ሁኚ፤ ጠይም ሁኚ፤ ወይም ጥቁር፤ የ'ኔም መልክ ከሰው የተለየ አይደለም፡፡ ሰውነቴ ሰውነትሽን ይናፍቃል፡፡ ንፁህ ልቤ ንፁህ ልብሽን ሲጠብቅ፤ ይነጋል ይመሻል፡፡

ሄዋኔ ምን ያህል ከናፍሮች ያንቺን እንደሚመስሉ ታውቂያለሽ? ከናፍሮችሽን ከንፈሮቼ ተርበዋል፤ አፍንጫዬ የጡትሽን መዓዛ ለመታጠን ጓጉቷል፤ እጆቼ ወገብሽ ላይ ለመጠምጠም ቸኩለዋል፤ አካላቴ ጭኖችሽ ውስጥ ለመገኘት ይሻል፤ ከዚ ሁሉ በላይ ግን አይኖቼ አይንሽን ለማየት፤ ጆሮዎቼ ድምፅሽን ለመስማት ቸኩለዋል፡፡

አዳምሽ ነኝ። ሄዋኔ ነሽ፡፡
እናፍቅሻለሁ። ትናፍቂኛለሽ፡፡

እስክንገናኝ፤ እስክንተያይ ሰላምሽ ለሰላሜ ይብዛ፡፡ ባለሽበት ካለሁበት ቸር ቆይኝ፡፡🌹


@wegoch
@wegoch
@wegoch
ለቅዳሚታችን!
💚

“የይቅርታ ጫፍ!” በለቅሶ ድንኳን
ውስጥ!
Written by ደ.በ


ድሬደዋ በዓመት የተወሰኑ ቀናት ቢዘንብ እንኳ፣ እንደዚህ የከበደና
ከተማውን ያጨለመ ዝናብ ታይቶም አይታወቅ፡፡ ሰው ሁሉ ግራ ተጋባ፣
ሀዘንተኛው የሚለው ጠፋው፡፡ አንዳች እርም ነገር ያለበት፣ ጠማማ ሰው
ቢሆን - ምናልባት ፈጣሪም ቁጣውን ሊያሳይ ነው ይባል ነበር፡፡ ደግሞስ
ድሬዳዋ ገብቶ እኛሁን ሳይነቅል፣ አውሬነቱን ሳይጥል የሚወጣ የታለና፡-
ድሬዳዋ እንደ አሜሪካ ናት፡፡ ሰው ሁሉ ከያገሩ ይዞት የመጣውን መሰሪነትና
ጠማማነት፣ በዚያች ከተማ እህል ውሃ ታጥቦ፣ በሽንቱም በላቡም
ይወጣለትና እንዳገሬው ሰው ገራምና ደግ ይሆናል፡፡
የሰላማዊት እናትም ያው የድሬደዋ ሰው ናቸው:: ገደቆሬ ተወልደው ከዚራ
ያደጉ፡፡ ታዲያ የእኒህ ደግ ሴት ቀብር እንዲያምር፣ ዝናቡ ለምን አልቆም አለ?
ሰላማዊት ዝናብ እየዘነበ፣ የርሷም ጉንጮች ላይ እንባዋ እንዳይዘንብ
አልከለከለችውም፤ “እማ ገመናዬ!!... እማዬ ጓዳዬ!” ትላለች፡፡
ከፊሉ ሰው እርሷን እያየ አብሯት ያለቅሳል:: ሌላው ደግሞ እንዳታለቅስ የቆ
የባጡን ያወራል:: “ተዪ-- የእግዜርን ዐይን አትውጊ! ስንት ወጣት ባጭር
በሚቀጭበት ሀገር! … ስንቱ ሞቶ አስከሬን በሚቃጠልበት ዘመን … በቃ
አስታምመሻል … በቃ!”
እርሷ ግን ትንሽ እንደማቆም ትልና፤ “እማ አጋለጥሺኝ … እማዬ ገመናዬን …
ገለጥሺው!” እያለች ትቀጥላለች፡፡
ቤቱ ሰው በሰው ሆኗል፣ ድንኳኑም በሰው ታጭቋል፡፡ የእናቷ ልከኛ ቪላ ቤት፣
ሰርክም ሰው አያጣም፡፡ ጎረቤት እንደ ቤቱ ገብቶ በልቶ የሚጠጣበት ቤት
ነው፡፡ ይህ ቀድሞ የነበረ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ በሙስሊም ፆም፣
ጎረቤቶቻቸውን ሾርባ ሰርተው፣ ሳንቡሳ ቴምር ገዝተው፣ ቤታቸው ይጋብዙ
ነበር፡፡ ደግ ሴት ነበሩ፡፡ ጨዋታስ ሲያውቁበት!
“ጉድ አደረግሺኝ! ጉድ አደረግሺኝ!”
ለቅሶው መሀል የስምንት ዓመት ልጇ ስልኳን ይዛ እየሮጠች መጣ፤ “እማዬ
ስልክ?”
ቁጥሩን አየት አድርጋ፤ “ሄሎ! … ሄሎ! እንዴት ነህ!” ድምፅዋ ተለውጧል
“እንደዚህ ራስሽን አትጉጂ! … የናንተ ሀገር ሰው ልቅሶ ያበዛል!” አላት
“እናቴ ኮ ናት! …” አለች፤ ለስለስ ብላ፡፡
ብዙ ዐይኖች ወደርሷ አፍጥጠዋል፡፡ አንዳች ነገር ቀይ ፊቷ ላይ ማንበብ
ከጅለዋል፡፡ ቀጥ ብሎ ቁልቁል የወረደው አፍንጫዋን፣ አስሬ ስታልበው
ሳያቋርጡ ያያሉ፡፡ ለጊዜው እነርሱም ለቅሶውን አቁመዋል፡፡
“የናንተ ሀገር ሰው ልቅሶ የሚያበዛው በቁም ስለማይረዳ ነው፤ ፀፀት ነው!”
ይላታል፡፡
“አንቺ ግን እናትሽን የምትችይውን ሁሉ አድርገሽላታል፤ በቃ ያለ ነው፡፡
በርግጥ ጌጡ ልዩ ሰው ነበረች፤ ግን በቃ ፈጣሪ ደግ ሰው አይሞትም! ወይም
ዕድሜ ይጠግባል” አላለም፡፡ ብዙ ደግ ሰዎች ያለ ዕድሜያቸው እንደተቀጩ
ቅዱስ መጽሐፍም ይናገራል፡፡ የማቱሳላን እድሜ አልመኝላቸውም!” ሲላት
የወትሮ ንግግሩ ትዝ አላትና ወደ ሳቅ ልትገባ ነበር፡፡ ደስ ሲለው የሀገሩ
ደራስያን መጽሀፍት ውስጥ ያሉትን ገፀ ባህርያት ህይወት ሊጠቅስላት
ይችላል ወይም ከሼክስፒር ቴአትር፣ አሊያም ከጆን ሚልተን ስንኞች፣ ከጆን
ኪትስ ሶኔቶች … ፀባዩን ስለምታውቅ ገርሟት ዘጋችው፡፡ ይልቅስ ቀን ስለሆነ፣
እናቷንም አንድ ሁለቴ መጥቶ ስላገኛቸው በሀዘን የሚሰበር መስሏት በነበር፡፡
… የፈረንጅ ነገር! ብላ ዝም አለችው፡፡ ሰባት ዓመት ሙሉ አብረው ኑው፣ ፀባዩ
ለምን እንደገረማት ራስዋን ገረማት፡፡
ከአሁን በኋላ ምን ዓይነት ህይወት፣ ምን ዓይነት ትዳር ይኖራቸው እንደሆነ
እያለመች ወደ ልቅሶው ገባች፡፡ እናትዋን የሚያውቁ በዝምድና የሚገናኙ፣
ጎረቤት ሆነው ብዙ ዓመታት ያሳለፉ ሁሉ እያለቀሱ ይገባሉ፡፡ አንዳንዶቹ
ለእርሷ ብሰው ስለሚያለቅሱ እንዲተዉ ይለመናሉ፡፡ በዚያ ዝናብ፣ በዞያ ዶፍ
ውስጥ እንኳ የልቅስተኛው ቁጥር እየጨመረ መሄዱን አላቋረጠም ነበር፡፡
ወንዱም ሴቱም እያለቀሰ፣ ወይም አንገቱን ዝቅ እንዳደረገ ይገባል፡፡
በውጭ ስንዴ ለቀማው፣ ድስት መጣዱ፣ የተለያየ ነገር ማዘጋጀቱ ለእድር ብቻ
አልተተወም፡፡ ወንዱ እንጨት ፈለጣ፣ ሴቱ ማዕድ ቤትና እልፍኝ ውስጥ
ስራውን ቀጥሏል፡፡ በሞቃቱ ወራት ቢሆን ብዙ ነገሩ ከባድ ይሆን ነበር፡-
ዝናቡ ቀስ እያለ ሲያባራ የቀብሩ ጉዳይ የማይቀር ሆነ፡፡ እዚያም በተመሳሳይ
የሚያለቅሰው አልቅሶ፣ ዝም ብሎ ሀዘኑን በሆዱ የያዘውም ይዞ፣ ቀሳውስቱ
የቀብሩን ስነ ስርዐት አስፈፅመው ተመለሱ፡፡ አሁን ፈተናው የሰላማዊት
የብቻዋ ነበር፡፡ ከባለቤትዋ ጋር ስላላት የትዳር ጉዞ ማሰብ፣ ማውጣት፣
ማውረድና መወሰን አለባት፡፡ እናትዋ ጋ የሚኖሩትን ሁለት ልጆቿን ጉዳይ ምን
እንደምታደርግ ግራ ገብቷታል:: ባለቤትዋ የማያውቀው የሁለት ልጇቿ ጉዳይ፣
አደባባይ የሚሰጣበት፣ገመናዋ የሚወጣበት ቀን እየደረሰ ነው፡፡
ባልዋ የምድር ባቡር ሰራተኛ ሆኖ ድሬደዋ ሲሰራ፣ ራስዋን እንደ ልጆች እናት
አድርጋ ስላልነገረችው ግር ብሏታል፡፡ ሁለት ጓደኞቿ ለባሎቻቸው ሳይነግሩ
አግብተው፣ በመጨረሻ ነገሩ ሲገለጥ የደረሰባቸውን አበሳ ታስታውሳለች፡፡
ሁለቱም በባሎቻቸው ተደብድበው፣ ንብረታቸውን ተነጥቀው ተሰኝተዋል::
“አታለልሺኝ” የሚል ሙሾ ተሟሽቶባቸዋል፡፡ ለዚያውም የእነርሱ አንድ ልጅ
ነው፡፡
“እማዬ ገመናዬን ዘረገፍሺው!” አለች፤ አመለጣትና፡፡
ብዙ ሰዎች ኑሮዋ ለንደን መሆኑንና ፈረንጅ ባል እንዳላት እንጂ ሌላ ብዙ ነገር
አያውቁም፡፡ ሁሉንም የሚያውቁት እርሷና እናቷ ናቸው፡፡ ፈረንጁ ሁለት ጊዜ
ከእርሷ ጋር ሲመጣ፣ ልጆቿን ጅጅጋ ያሉት አክስቷ ጋ አስቀምጣቸው ነበር፡፡
ደግነቱ ትምህርት ቤት ተዘግቶ ስለነበረ ብዙም አላስጨነቃት፡፡ ጊዜውን
በክረምት ያደረገችውም አውቃ ነበር፡፡ አሁን ግን ልጆቿን ለማን ጥላ፣ በምን
አንጀቷ ትኖራለች! … ያበጠው ይፈንዳ! … ፈረንጁ ከእነ ልጆቿ ከተቀበላት
ተቀባለት፡፡ አለዚያም አንደ ሁኔታው ትኖራለች፡፡ ግን ያዝንባታል፣
ያሸማቅቃታል፡፡
በዚህ ዓይነት መሳቀቅ ከቆየች በኋላ አጅሬው ከተፍ አለ፡፡ ከአየር ማረፊያ፣
ወደ ቤታቸው ሲመጣ፣ ትንሽም አልተደናገረም፡፡
በሚገባ ተቀበለችው፡፡ እርሱም “መጽሀፍቱን፣ ቅዱሱን እርኩሱን እየጠቀሰ
ሊያፅናናት ሞከረ:: አንዳንዴ የሚጠቅሳትን ሀሳብ ጠቀሰላት፤ በጥሩ ጊዜ ስለ
paygmalion አወራት፡፡ ዕድለኛው የግሪክ ንጉስ አፈታሪክ፡፡ አንዲት ቆንጆ
ልጅ ሀውልት አድርጎ ሰርቶ፣ ያችን ደረቅ ሀውልት ላይ ያያትን የራሱን ፍጡር
ቢያደንቅ፣ የፍቅር አምላክ የምትባለው አፍሮዳይት ህይወት ዘራችባትና ሚስቱ
አድርጓት፣ በተድላ ስለኖረው ዕድለኛም ቆጥሮ ነገራት፡፡ ራሱን እንደ ዕድለኛ
ቆጥሮ፣ከራሱን ጋር ሊያወዳድረው ሞከረ፡፡
ዛሬ ይህንን ለምን እንዳነሳበት ባታውቅም ውስጧ እየተናጠ፣ ነፍሷ ባንዳች
ሞገድ እየተናወጠ ነበረ:: አሁን ግን የቁርጡ ሰዓት እየመጣ ነው:: ከጎረቤት
ያሉትን አንድ የዕድሜ ባለፀጋ መምህር አስቀምጣ፣ ከዚህ ቀደም ልጆች
እንዳሏት ሳትነግረው ስለ ፈፀመችው ጋብቻ መፀፀቷን ልትገልጽለት አሰበች፣
ከዚያም ወደ መኝታ ክፍል አስገብታው ልትወጣ ስትል፣ አፈፍ አድርጎ ያዛት፡፡
ከጎረቤት ሰው ልትጠራ እንዳሰበች ነገረችው፡፡
“አያስፈልግም! … አያስፈልግም!”
ደነገጠች፡፡
“እኔ ፕያግማሊን ነኝ፤ ዕድለኛ ነኝ ብዬሻለሁ!”
ግራ ተጋባች፡፡
“አንቺን በመምረጤ ዕድለኛ ነኝ፡፡ አደራሽን! አንቺ ግን ራስሽን እንደ
ፍራንካንስቴን አትቁጠሪ!”
ምን ማለቱ እንደሆነ ቀድሞም ታውቀዋለች፡፡ ሰው ራሱ በሰራው ስራ መከራ
እንደሚያይ አትቁጠሪ እያላት ነው፡፡ ይህ ፍራንካንስቴን የሼሌ ገፀ ባህሪ ነው፡፡
የሜዲካል ኮሌጅ ተማሪ ፈጥሮት፣
ፈጣሪውን የገደለ፣ ህይወቱን የበላ ገፀ
ባህሪ! ተገረመች፡፡ ራስሽን ዕድለ ቢስ አታድርጊ እያላት ነው፡፡
“Keep up our pious love!”
ድንቄም አለች፡፡
ስሚኝ “ሁለቱን ልጆችሽን አምጫቸው፣ ካገባሁሽ ቀን ይልቅ፣ የወደድኩሽ ዛሬ
ነው፡፡ አንቺ ድንቅ ሴት መሆንሽ ዛሬ ከአየር ማረፊያ ስመጣ ነው የሰማሁት!
ዛሬ የእናትሽ ልቅሶ ላይ ባትሆኚ፣ ሼሌ ገዝቼ ደግሜ እሞሽርሻለሁ!
ሰላማዊት ድንገት መሬት ምንጣፉ ላይ ወደቀች፡፡
“እኔን ስለምታፈቅሪኝ፣ እኔን ከማጣት ይልቅ የምትወጃቸውን ሁለት ልጆችሽን
ህይወት፣ ለኔ ለጣዖትሽ ሰዋሽ!! ፍቅር ከዚህ በላይ የሚገለጥበት መስቀል
የለም!” ብሏት አብሯት ዝብ አለ፡፡
ወገቧን ይዞ ሲያነሳት አዲስ የሚናኝ የፍቅር መዐዛ፣ የነፍሱን እልፍኝ
እያላወሰው ነበር፡፡ እርሷ በጉንጯ ከሚወርደው እንባ በቀር ቃል
አልነበራትም፡፡

ሸጋ ሸጊቱ ቅዳሜ!💚

@wegoch
@wegoch
ለውብ ቀን!💚

የዛሬ 90 አመት የወጣ የአውዳመት ዜና!


ከመጠጥ የሚገኝ ጉዳት


ታህሳስ 29 የክርስቶስ ልደት እለት አቶ ……… የሚባል እንጦጦ ራጉኤል ገዳም ውስጥ
የነበረ ሰው በልደት በዓል ቀን አራዳ አረቄ ሲጠጣ ውሎ ወደ ማታ በፈረስ ተቀምጦ ወደ
ቤቱ ሲወጣ ራጉኤል አፋፍ በደረሰ ጊዜ ሰውነቱ በመጠጥ ዝሏልና ተኮርቻ ተገልብጦ
ወደቀ፤ እነሳለሁ መስሎት እየተንከተከተ /እየሳቀ/ አረሀ ላረሀ ሲንደባለል አሽከሩ እንደ እሱ
አልባሰበትም ነበርና ከቤቱ ሄዶ ሰዎች ይዞ እስቲመጣ ድረስ እሱ አረፋ ደፍቆ ሆዱ ተነፍቶ
ሞቶ ተገኘ። ብዙ ሞኞች ጋኔን ገደለው እያሉ ያወራሉ ግን ካረቄ የበለጠ ጋኔን እንደሌለ
ባያውቁ ነው።


ብርሃንና ሰላም ጋዜጣ

ጥር 6 ቀን 1918 ዓ.ም

@wegoch
@wegoch
ጡ...ጡ....ጡ..ጡ..ጡጥ! 

ያልሰማህ ስማ ፣ የሰማህ ላልሰማ አሰማ !

ነገ ነሀሴ 28 ካሲዮፒያ የበጎ አድራጎት ማህበር በብሄራዊ ቲያትር የጥበብ ምሽት አዘጋጅቷል ። 

የጥበብ ምሽቱም ዓላማ አቅም የሌላቸውን ታዳጊ ተማሪዎች በመማርያ ቁሳቁሶች መርዳት ሲሆን መግቢያውም አንድ ደርዘን ደብተር ይሆን ዘንድ ተወስኗል ። 

በ 11።30 ፕሮግራም ላይ ሲሆን ብዙ የምንወዳቸው ገጣሚዎች እና የጥበብ ሰዎች ስራዎቻቸውን ይዘው የሚቀርቡ ይሆናል ። 

ወገኔ እነሆ ይሄን ፕሮግራም ታልመጣህ ዘንዳ ማርያምን አይማረኝ አልምርህም !

...
ጡ....ጡ....ጡ....ጥ!

ያልሰማህ ስማ! ...የሰማህ ላልሰማ ሼር በማድረግ አሰማ !!
@wegoch
2024/09/27 19:18:34
Back to Top
HTML Embed Code: