Telegram Web Link
እንካን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወርሃዊ በዓል አደረሰን:: ስምሽ ጉልበት ሆኖኝ ወጣሁት ዳገቱን  ድንግል ማርያም ባንቺ ምልጃ አለፍኩት ዳገቱን::

    #መልካም እለተ

     @ortodoxtewahedo
2500 ለሚሆኑ ወጣቶች የሱባኤ ጉባዔ ትምህርት ተጀመረ

| ጃንደረባው ሚድያ | መጋቢት 2016 ዓ.ም.|
አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ

የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ትውልድ እና አዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት በትብብር የሚያካሒዱት የሱባኤ ጉባኤ ትምህርት በሦስት አጥቢያ ሰንበት ትምህርት ቤቶች በመካሔድ ላይ ይገኛል::

በደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ እና መካነ ጎልጎታ ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ፍቁረ እግዚእ ሰንበት ትምህርት ቤት ፤ በቦሌ ደብረ ሳሌም መድኃኔዓለም የፈለገ ዮርዳኖስ ሰንበት ትምህርት ቤት እና በአፍሪካ ኅብረት ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ካቴድራል ሰንበት ትምህርት ቤቶች የተጀመረው ይህ ትምህርት
ለትምህርት ምቹ በሆነው በዐቢይ ጾም ለሃያ ስምንት ቀናት በየቀኑ የሚሠጥ እንደሆነ ተገልጾአል::

በትምህርቶቹ መክፈቻ ላይ በሦስቱም አጥቢያዎች ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ሰብሳቢ የሆኑት ላዕከ ኄራን መንክር ግርማ የእንኳን ደህና መጣችሁ እና የአንድነቱን መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን በዚህም መልዕክታቸው በአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት እና የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ትውልድ ጠቅላላ ማኅበር (ኢጃት) በ2015 ዓ.ም መጨረሻ ላይ በጋራ ሊሠሯቸው ከተፈራረሙባቸው ሦስት ፕሮጀክቶች ውስጥ አንዱ የሆነውን ሱባዔ ጉባዔን በትብብር ለማካሔድ ከአንድ ዓመት ላላነሰ ጊዜ ውይይት መደረጉን ፤ በሕገ ቤተ ክርስቲያን በመዋቅር ወጣቶችን ማስተማር ለሰንበት ትምህርት ቤቶች የተሠጠ ኃላፊነት እንደመሆኑ ሱባዔ ጉባዔን ከሥርዓተ ትምህርቱ ጀምሮ ከትምህርቱ በኋላ ስለ ተማሪዎቹ ሁኔታ ፣ ከሰንበት ትምህርት ቤት ሥርዓተ ትምህርት ጋር የሚኖራቸውን ቀጣይ ቆይታና የአጥቢያ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን የወጣቶች የመማር ማስተማር ሚና በዝርዝር ለአንድ ዓመት ያህል በአግባቡ ሲያጠና እንደነበር ገልጸዋል:: በሒደትም ተተኪ መምህራንን በጋራ በማብዛት ሙሉ በሙሉ ሰንበት ትምህርት ቤት በቀጣይ በኃላፊነት ቋሚ አባል አድርጎ ለማስተማር ዕቅድ መዘጋጀቱን ገልጸዋል::

አያይዘውም "ይህ የመጀመሪያው ዙር የጋራ ሱባዔ ጉባኤ እንደ ሙከራ ፕሮጀክት (pilot program) የሚካሔድ ሲሆን በቀጣይ በሁሉም አጥቢያዎች በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚካሔድና ስታንዳርዱን በጠበቀ መልኩ በሰንበት ትምህርት ቤቶች በኩል ወጣቶችን ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለመማረክ በትብብር የተዘጋጀ የወንጌል መረብ መሆኑን በንግግራቸው አውስተዋል::

በዕለቱ የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ያደረጉት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የማኅበራት ማደራጃ መምሪያ የኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ትውልድ ጠቅላላ ማኅበር የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ዲ/ን ዶ/ር ዳዊት ከበደ በበኩላቸው
"ኢጃት ለአምስት ዙር የሱባዔ ጉባኤ ትምህርትን ባስተማረበት ወቅት ከእንኳን ደስ ያላችሁ መግለጫ ውጪ ምንም ዓይነት የምስክር ወረቀት ያልሠጠበት ምክንያት ሕገ ቤተ ክርስቲያንን ጠብቆ ምእመናንን ለማስተማርና እንደ ሰንበት ትምህርት ቤት ያለ መዋቅር ውስጥ ለማስገባት በማሰብ ነው" በማለት ያስታወሱ ሲሆን በመጀመሪያ ዙር ይሄንን ያህል ተማሪ ከሰንበት ትምህርት ቤት ጋር ለማስተማር እንድንችል አንድነቱና የአጥቢያ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያሳዩት ቀና ትብብር እጅግ የሚያኮራ ነው" ብለዋል::

"የሱባዔ ጉባኤ ትምህርቱ እንዳለቀ ለአራት ወራት ተማሪዎች መመረቂያ ጽሑፍ እንዲያቀርቡ የታሰበ ሲሆን ከትምህርቱ በኋላም በተማሩበት አጥቢያ ሰንበት ትምህርት ቤት በአደራ ታቅፈው እንደሚጸኑና ትምህርትና አገልግሎቶች ላይ እንደሚሳተፉ ታቅዶአል:: በሱባዔ ጉባኤ ትምህርቱ ያለፉ ተማሪዎች ወደ ኢጃት የሚገቡበት ምንም ዓይነት አሠራር እንደማይኖር ከአንድነቱ ጋር ስምምነት አድርገናል" ብለዋል:: ትምህርቱን በሒደት ሙሉ በሙሉ ለሰንበት ትምህርት ቤቶች ለማስረከብ የተተኪ መምህራን ሥልጠና ለመጀመር በሒደት ላይ መሆኑን የአንድነቱና የኢጃት የጋራ ኮሚቴ አስታውቆአል::

"የሱባኤ ጉባኤ የ28 ቀናት ትምህርት ምግብ ለመብላት ሆድ እንደሚከፍት የማስጀመሪያ ገበታ (starter) ስለሆነ ተማሪዎችን በቤተ ክርስቲያን ለሚሠጠው ዋነኛ የቃለ እግዚአብሔር ምግብ (main course) ዝግጁ ለማድረግ እንጂ ጥልቅ የሆነችውን ቤተ ክርስቲያን በአንድ ወር ትምህርት ለማሳወቅ አልተነሣንም" ያሉት የኢጃት ሱባኤ ጉባኤ ሰብሳቢ አቶ ሕያው መኮንን ሲሆኑ አያይዘውም "በሒደት ትምህርቱን በብዙ አጥቢያዎች ለማስፋፋትና በመጨረሻም ለአጥቢያዎቹ በአደራ ለማስረከብ ዕቅድ አለን" ብለው ደምድመዋል:: ኢጃት እስካሁን ከአምስት ሺህ በላይ ወጣቶችን በሱባኤ ጉባኤ ያስተማረ መሆኑ ይታወሳል::

@ortodoxtewahedo
    የዐቢይ ጾም አራተኛ ሳምንት    

መ ጻ ጉ ዕ   

አራተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹መጻጒዕ› ይባላል፡፡

ስያሜው በዮሐንስ ወንጌል ፭፥፩ ላይ ከሚገኘው ኃይለ ቃል የተወሰደ ነው፡፡ በዚህ የወንጌል ክፍል ጌታችን በቤተ ሳይዳ ሕሙማንን እንደ ፈወሰ ተነግሮአል፡፡ ብዙ ሕሙማን ፈውስ ሽተው አንዲት የመጠመቂያ ሥፍራን ከበው ይኖሩ ነበር፡፡ በዚያች ሥፍራ ቀድሞ የወረደ እና የተጠመቀ አንድ በሽተኛ ብቻ ይፈወስ ነበር፡፡

ጌታችን በዚህ ሥፍራ ተገኝቶ በሽተኞችን ጐብኝቷል፡፡ በዚያም ልዩ ልዩ ደዌ ያለባቸው አምስት ዓይነት ሕሙማን እንደ ነበሩ ተገልጧል ፤ እነዚህም ፦ ሰውነታቸው የደረቀ ፣ የሰለለና ያበጠ ፤ እንደዚሁም ዕውራን እና ሐንካሳን ነበሩ፡፡ ከዚህ አምስት የተለያየ ዓይነት በሽታ ከተያዙ ሰዎች መካከል ደዌው የጸናበት ፣ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት በደዌ ዳኛ ፣ ባልጋ ቍራኛ ተይዞ የኖረው ፤ ከደዌው ጽናት የተነሣ ‹መጻጒዕ› ተብሎ የተጠራው በሽተኛ አንዱ ነበር፡፡

መጻጒዕ ስም አይደለም፡፡ ደዌ የጸናበት በሽተኛ ሕመምተኛ ማለት ነው እንጂ፡፡ ሰውየው ከበሽታው ጽናት የተነሣ ስሙ ጠፍቶ በበሽታው ሲጠራ የነበረ ነው፡፡ አምላካችን ይህን ሰው "አልጋህን ተሸክመህ ሒድ" ብሎ ሠላሳ ስምንት ዘመን የተኛበትን አልጋ ተሸክሞ ወደ ቤቱ እንዲገባ ማድረጉ የሚነገርበት ወቅት በመኾኑ ሳምንቱ ‹መጻጒዕ› ተብሎ በተፈወሰው በሽተኛ ስም ተሰይሟል፡፡ [ሙሉ ታሪኩን በዮሐንስ ወንጌል ፭፥፩-፲፯ ይመልከቱ]፡፡

ዛሬም ቢኾን በሰዎች ላይ ልዩ ልዩ ደዌያት አሉ ፤ የሥጋውን ደዌ ሐኪሞች ያውቁታል፡፡ ከዚህ የከፉ የነፍስ ደዌያት እጅግ ብዙዎች ናቸው፡፡ በኃጢአት ብዛት ልባቸው የደረቀና ያበጠ ፤ ሰውነታቸው የሰለለ ፤ ዓይነ ሕሊናቸው የታወረ ፤ እግረ ልቡናቸው የተሰበረ ብዙዎች ሕሙማን አሁንም አሉ፡፡ ፈውስን ይሻሉ ፤ ድኅነትን ይፈልጋሉ፡፡ እንደ መጻጕዕ ቦታቸውን ሳይለቁ እግዚአብሔርን በተስፋ ቢጠብቁት አንድ ቀን ይፈወሳሉ፡፡

[ በመምህር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ ]

@ortodoxtewahedo
“ችግሮች ቢኖሩም ራሳቸውን ለቤተ ክርስቲያን አሳልፈው የሚሰጡ ልጀች እንዳሉ አይተናል፤ ቤተ ክርስቲያን መሻገሯ አይቀርም”

ብፁዕ አቡነ አብርሃም የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የባሕር ዳርና ሰሜን ጎጃም አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

+++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++

የማኅበረ ቅዱሳን የ2016 ዓ.ም የሥራ አመራር ጠቅላላ ጉባኤ በመጨረሻ ቀን ውሎው ብፁዕ አቡነ አብርሃም የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የባሕር ዳርና ሰሜን ጎጃም አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተገኝተው ነበር።

የማኅበሩ ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም ለብፁዕነታቸው ገለጻ ያደረጉ ሲሆን በዚህ የሥራ አመራር ጉባኤ በሀገር ውስጥ ካሉን 55 ማእከላት ውስጥ ጦርነት ውስጥ ካሉ አካባቢዎች ሳይቀር ከ48 ማእከላት ሰብሳቢዎች እና ተወካዮች እንዲሁም ከውጭ 9 ማእከላት ተሳትፈዋል ብለዋል።

ሰብሳቢው አክለውም ጉባኤው በሁለት ቀን ውሎው የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አሁናዊ ችግሮችና መፍትሔዎች እንዲሁም የማኅበረ ቅዳሳን የአገልግሎት ድርሻ ላይ መወያየታቸውን አስታውቀዋል።

“ጽና፤ እጅግም በርታ” በሚል ኃይለ ቃል ቃለ ምእዳን የሰጡት
ብፁዕ አቡነ አብርሃም የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የባሕር ዳርና ሰሜን ጎጃም አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

“የኛ የሆነውን አሳልፎ ላለመስጠትና በክብር የተቀበልነውን በክብር ለቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ ጥንካሬ ያስፈልጋል፤ እናንተም ጽናት ባይኖራችሁ በዚህ ሁሉ መከራ መሀል አትገኙም።ችግሮች ቢኖሩም ራሳቸውን ለቤተ ክርስቲያን አሳልፈው የሚሰጡ ልጀች እንዳሉ አይተናል” ብለዋል።

ትውልዱ ጽናት ያለው የሚመስል ነገር ግን በጉዞ መሐል የሚንቀጠቀጥ የሚንገዳገድ ትውልድ መሆን የለበትም ሲሉም አብራርተዋል ።

“ከምእመን እስከአባቶች ከበረታን ቤተ ክርስቲያን ከእነሙሉ ክብሯ ትተላለፋለች፤ መሻገሯም አይቀርም” ያሉት ብፁዕ አቡነ አብርሃም “ ሌላ ጉልበት የለንም ጉልበታችንም ጽናታችንም እግዚአብሔር ነው፤ አቅጣጫ የሚሰጠንም ቃሉ ነው፤ እግዚአብሔር ሁሉን እንደሚያስተካክል እናምናለን የእኛ ድርሻ ግን እንወጣ ” ብለዋል።

ብፁዕነታቸው ማኅበሩ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጋር የበለጠ በመናበብና ግብዓት በመስጠት በፍቃደ እግዚአብሔርና በጥበብ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እናሻገር ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል።

በመጨረሻም ከውጭ ሀገራት የተሳተፉ አባላትን መነሻ በማድረግም “ጽኑ፤ በምትሠሩት መንፈሳዊ አገልግሎትም ቤተ ክርስቲያንን ድምጽ ስለሆናችሁ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ስም አመሰግናለሁ” ብለዋል።

@ortodoxtewahedo
2024/09/29 17:26:20
Back to Top
HTML Embed Code: