Telegram Web Link
ማኅበረ ቅዱሳን በምሥራቅ ወለጋ  4 ቦታዎች ላይ ለሚገኙ 145 ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ አደረገ፡፡ 

የማኅበረ ቅዱሳን ሙያና ማኅበራዊ አገልግሎት ማስተባበሪያ፣ በሀገራችን እያጋጠሙ ያሉ መጠነ ሰፊ ማኅበራዊ ቀውሶች በልዩ ልዩ የማኅበረሰብ ክፍሎች ላይ የሚያስከትሉትን ችግር ለማቃለል ልዩ ልዩ የማኅበራዊ ድጋፍ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽና በመተግበር ማኅበራዊና ሰብአዊ ሚናውን እየተወጣ እንዳለ ይታወቃል።

ማስተባበሪያው በማኅበራዊ ዘርፍ ከሚያደርጋቸው ድጋፎች መካከል በተለያዩ ምክንያቶች ትምህርታቸውን በተገቢ ሁኔታ ለመከታተል የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ሕጻናትና ታዳጊዎች የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ ማድረግ አንዱ ነው። በዚህ መሠረት በየዓመቱ እንደሚደረገው ከመስከረም11-12 ቀን 2017 ዓ.ም ከማኅበረ ቅዱሳን #ነቀምቴ ማእከል ጋር በመተባበር፣ በምሥራቅ ወለጋ 4 ቦታዎች ማለትም በሲቡ ስሬ፣ ጉደቱ አርጆ ፣ ነቀምቴ ከተማ እና ጅማ አርጆ በድምሩ ለ145 ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ እንዲደርሳቸው ተደርጓል።

በሌሎች አካባቢዎችም ተመሳሳይ ድጋፎችን በፍጥነት ለማድረስ ማስተባበሪያው እየሰራ መሆኑን የተገኘው መረጃ ያመለክታል። ስለሆነም የነገ ሀገርና ቤተ ክርስቲያን ተረካቢዎች ተስፋ ለማስቀጠል በሚደረገው የሰብአዊነት ሥራ ምእመናን፣ ማኅበራት፣ ልዩ ልዩ ተቋማትና በጎ አድራጊ ድርጅቶች የተለመደ ድጋፍ እንድታደርጉልን ሲል ጥሪውን ያቀርባል።
#በማኅበረ ቅዱሳን የማኅበራዊ ድጋፍና መልሶ ማቋቋም ሒሳብ ቁጥሮች፡-
1. በአሐዱ ባንክ - 0025393810901
2. በአቢሲንያ ባንክ - 37235458
3. በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ - 1000309803648
4. በወጋገን ባንክ - 0837331610101
5. በአዋሽ ባንክ 01329817420400
6. በወገን ፈንድ ፡- https://Www.wegenfund.com/mknu መጠቀም የምትችሉ መሆኑን እንገልጻለን።
በማኅበረ ቅዱሳን የደሴ ማእከል ለወሎ ዩንቨርሲቲ ዋናው ግቢ እና ለልዕለ ሕክምና ካምፖስ ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የአቀባበል መርሐ ግብር ማካሄዱን ገለጸ።

በመርሐ ግብሩ ላይ የደሴ ማእከል ምክትል ሰብሳቢ ፣የደብረ ዕንቁ ቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ቆሞስ አባ ወልደ ጊዮርጊስ ፣የማእከሉ ሥራ አስፈጻሚ አባላትና የግቢ ጉባኤ አገልግሎት ዋና ክፍል አባላት ተገኝተዋል።

በዕለቱ ለተማሪዎች መልእክት ያስተላለፉት የደብረ ዕንቁ ቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ቆሞስ አባ ወልደ ጊዮርጊስ እኛ ወጥተን ወርደን አምጠተን ማስተማር ሲኖርብን እናንተ መጥታችሁ አስተምሩን በማለታችሁ እጅግ እድለኞች ነን ብለዋል፡፡

አስተዳዳሪው አክለውም ወጀብ በበዛበት ዘመን ማኅበረ ቅዱሳን ባይኖር እናንተ ዓለም ትውጣችሁ ነበርና የተመቻቸላችሁን ዕድል ተጠቅማችሁ በሁለቱም የተሳለ ሰይፍ ሁናችሁ መውጣት አለባችሁ በማለት አሳስበዋል፡፡
የመስቀል ደመራ በዓል

የመስቀል ነገር በመጀመሪያ የተገለጸው በመላእክት ዓለም ነበር፡፡ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ሥነ ፍጥረትን በጻፈበት አክሲማሮስ በተባለ መጽሐፉ እግዚአብሔር መላእክትን ፈጥሮ በተሰወረባቸው ጊዜ ዲያብሎስ እኔ ፈጠርኳችሁ አለ፡፡ ያን ጊዜ በመላእክት ዓለም ረብሻ ሆነ፤ ከፊሉ ዲያብሎስን አምኖ ከእርሱ ጋር ሆነ፤ ቅዱስ ገብርኤል ግን የፈጠረንን እስክናገኝ በያለንበት ጸንተን እንቆይ አለ፤ ቅዱስ ሚካኤልና ሌሎች መላእክትም አብረው ጸንተው ቆዩ፤ ተጠራጥውም ከሁለቱም ጎን ሳይሆኑ የቀሩ ነበሩ፡፡

ከዚያም በመላእክትና በዲያብሎስ መካከል ጦርነት ተጀመረ፤ በተዋጉ ጊዜ ዲያብሎስ ሁለት ጊዜ አሸነፋቸው፤ ሆኖም መላእክት አምላካቸውን ‹‹ፈቃድህ ነውን?›› ብለው ቢጠይቁት፤ ‹‹ፈቃዴስ አይደለም፤ ድል የምታደርጉበትን ኃይል እንድታውቁት ብዬ ነው እንጂ›› ብሎ በክንፋቸው ላይ የብርሃን መስቀል ቀረጸላቸው፤ በእጃቸው ደግሞ የብርሃን መስቀል አስያዛቸው፤ ሄደውም ዲያብሎስን ቢገጥሙት በመስቀሉ ኃይል ድል ነሥተውታል፡፡ መላእክት ሳጥናኤልን ድል ያደረጉት በመስቀል ኃይል ነው (ራዕ. ፲፪፥፯፣ መዝ. ፶፱፥፬)፡፡
በዘመነ አበው መስቀል የመባረኪያ ምልክት እንደነበረ በመጽሐፍ ቅዱስ ተጠቅሷል፤ ዘፍጥረት ላይ ፤ ‹‹ያዕቆብ በሚሞትበት ጊዜ የዮሴፍን ልጆች በእምነት ባረካቸው›› ‹‹ወአስተሐለፈ እዴሁ ላዕለ ርዕሰ ኤፍሬም ወምናሴ፤ እጆቹን በኤፍሬምና በምናሴ ላይ በመስቀል ምልክት አድርጎ ጭኖ ባረካቸው›› ይላል፡፡ (ዘፍ. ፵፰፥፲፩)፤ ዕብ. ፲፩፥፳፪)

ዛሬም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህኑ ቀድሶ በሚወጣበት ጊዜ በእጆቹ ይባርካል፤ ይህም የሚያሳየው ቤተ ክርስቲያን መሠረቷ ከላይ በዓለመ መላእክት ከታች ደግሞ በዘመነ አበው ያየነው መስቀል መሆኑን ነው፡፡

መስቀል በብሉይ ኪዳን እንደየሀገሩ ሁኔታ ልዩ ልዩ ተግባራት ሲፈጸምበት ቆይቷል፡፡ ለምሳሌ፡- ለወንጀለኞች መቅጫነት አገልግሏል፤ ለአርማም ይጠቀሙበት ነበር፡፡

መስቀል በሐዲስ ኪዳን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳም በገባለት ቃል ኪዳን መሠረት ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ፣ ሰው ሆኖ፣ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ ድኅነትን ለሰው ልጆች ሰጥቶ፣ በመስቀሉ ተጣልተው የነበሩ ሰባቱን መስተፃርራን (ሰውና እግዚአብሔርን መላእክትና ሰውን፣ ነፍስና ሥጋን፣ ሕዝብና አሕዛብን) አስታርቋል፡፡

ደመራ
ደመራ ማለት መጨመር፣መሰብሰብ፣መከመር ነው፡፡ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም በመዝገበ ቃላት መጽሐፋቸው ደመራ የሚለውን ቃል ደመረ ከሚለው የግእዝ ቃል አውጥተው ደመራ ግእዝና አማርኛን ያስተባበረ መሆኑን ገልጸው የበዓለ መስቀል ዋዜማ እንጨቶች የሚደመሩበት መሆኑን አስረድተዋል፡፡

የታላቁ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ እናት ንግሥት እሌኒ ከቁስጥንጥንያ ተነሥታ የጌታችን መድኃኒችን ኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል ከተቀበረበት ለማውጣት ወደ ኢየሩሳሌም ሄደች፡፡ ኢየሩሳሌም በደረሰች ጊዜ የጌታችን መስቀል ተአምራትን እንዳያደርግ አይሁድ በምቀኝነት ቀብረውት ነበርና የተቀበረበትን ቦታ የሚያሳያት አጥታ በመፈለግ ብዙ ጊዜ አሳለፈች፡፡

በኋላ ግን አንድ ኪራኮስ የሚባል አረጋዊ አካባቢውን ነግሯት ደመራ አስደምራ ዕጣን አጢሳ ወደ ፈጣሪዋ ብትማፀን የዕጣኑ ጢስ ወደ ሰማይ ከወጣ በኋላ መንበረ ጸባዖት ደርሶ ተመልሶ መስቀሉ የተቀበረበትን ስፍራ አመለከታት፡፡

እርሷም በምልክቱ መሠረት ብታስቆፍር የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ክቡር መስቀል አገኘች፤ ከእርሱ መስቀል ጋር ሁለት ወንበዴዎች የተሰቀሉበትን መስቀል አብራ አግኝታው ስለነበር የጌታችን መስቀል ለይታ ያወቀችበት መንገድ ግን ድውያንን በመፈወሱ፣ አንካሳ በማበርታቱ፣ ጎባጣን በማቅናቱ የዕውራንንም ዐይን በማብራቱ ነው፡፡ ስለዚህም በየዓመቱ የመስቀልን በዓል ስናከብር ደመራ የምንደምረውና የምናበራው ንግሥት ዕሌኒን አብነት በማድረግ ነው፡፡

እርስዋም መስከረም ፲፯ ቁፋሮ አስጀምራ መጋቢት ፲ ቀን መስቀሉን አግኝታ አስወጥታ የቤተ ክርስቲያኑም መሠረት ወዲያው እንዲጣል አደረገች፡፡

የጌታ መስቀል ለብዙ ዓመታት በኢየሩሳሌም ከቆየ በኋላ ነገሥታት መስቀሉን ለመውሰድ ጠብ ፈጠሩ፡፡ በዚህ ጊዜ የአንጾኪያ፣ የኤፌሶን፣ የአርማንያ፣ የግሪክ፣የእስክንድርያ፣ የመሳሰሉት የሃይማኖት መሪዎች ጠቡን አበረዱት::

ከዚያም አያይዘው በኢየሩሳሌም የሚገኘውን የክርስቶስን መስቀል ለዐራት ከፍለው በስምምነት ተካፍለው ከሌሎች ታሪካዊ ንዋያተ ቅድሳት ጋር በየሀገራቸው ወስደው በክብር አስቀመጡት:: የቀኝ ክንፉ የደረሰው ለአፍሪቃ ስለነበር ከታሪካዊ ንዋየ ቅድሳት ጋር በግብፅ የሚገኘው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ተረክቦ ወስዶ በክብር አስቀመጠው፡፡

ኢትዮጵያዊው ንጉሥ ዳግማዊ ዳዊት የግብፅ ክርስቲያኖች በአማሌቃውያን ከሚደርስባቸው ተጽዕኖ ነጻ እንዲወጡ በማድረጋቸው የግብፅ ፓትርያርክ የከበሩ ስጦታዎችን ላኩላቸው:: ንጉሥ ዳግማዊ ዳዊት ግን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የምትፈልገው ወርቅ ሳይሆን ጌታ የተሰቀለበትን መስቀሉን እንደሆነ ገለጹላቸው::

በመሆኑም የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ግማደ መስቀሉን ከሌሎች ንዋየ ቅድሳት ጋር ለኢትዮጵያ ሰጥታለች:: ይህ ግማደ መስቀል በግሸን ማርያም ገዳም በእግዚአብሔር አብ ቤተ ክርስቲያን ሆኖ ኢትዮጵያን እየባረከ ይገኛል::

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መስቀልን ከሐዋርያት በተማረችው መሠረት የወርና የዓመት በዓል ሠርታ ታከብረዋለች::
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
የ2017 ዓ.ም የደመራ በዓል በመከበር ላይ ይገኝል።
"ዛሬም የመስቀሉ ቃል ማለት ሰዎች በነፍሳቸውም ሆነ በሥጋቸው የተሟላ ደኅንነት ያግኙ ማለት ነው፤ የመስቀሉ ቃል ማለት የሰዎች ሃይማኖታዊ ነጻነት ይከበር፤ በሕይወት የመኖር ሰብአዊ መብታቸውም ይጠበቅ ማለት ነው፤ የመስቀሉ ቃል ማለት ሰዎች በዚች ምድር በእኩልነት በአንድነት በመተጋገዝ በመረዳዳት በፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል በሰላም በፍቅር በስምምነት በመተባበር ይኑሩ ማለት ነው፤"

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ
ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት
በ2017 ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓል ከተናገሩት
መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
“እስመ ነገረ መስቀሉሰ ዕበድ ውእቱ በኀበ ኅጉላን ወበኀቤነሰ ለእለ ድኅነ ኃይለ እግዚአብሔር ውእቱ፤ የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት ነው፤ ለኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነው”(1ቆሮ. 1÷08)፤
በመስቀሉ ኃይል ከፍዳ ኃጢአት ያዳነን ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ ሰባት ዓመተ ምሕረት በዓለ ቅዱስ መስቀል በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ!
ጌታችን በዚህ ዓለም በተገለጸበት ዘመን የግሪካውያን ፍልስፍና ሰፊ ስፍራ አግኝቶ በመካከለኛው ምሥራቅ በሰሜን አፍሪካና በአውሮፓ የተስፋፋበት ዘመን ነበር፤ የግሪካውያን ባህልና ፍልስፍና የተመሠረተው በግዙፉ ቁስ ላይ እንደመሆኑ በግዙፉ መሳሪያ ላይ የሚተማመን ነበረ፤ ይህ ዓይነት አስተሳሰብ ሥር ሰዶ በነበረበት ጊዜ ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ በመንፈሳዊ ኃይል በዚህ ዓለም ተገለጠ፤ ጌታችን በሰው መካከል ተገኝቶ አጋንንትን ወደ ጥልቁ ሲያሰምጥ፣ ልዩ ልዩ በሽታና ደዌ ያላቸውን ሲያድን፣ ሙታንን ሲያነሣ፣ ብዙ ተአምራትንና አስደናቂ ነገሮችን ሲያሳይ በመንፈሳዊ ኃይል እንጂ በቁሳዊ ኃይል አልነበረም፤ በመሆኑም በወቅቱ በዓለም ውስጥ ቁሳዊ ኃይልና መንፈሳዊ ኃይል ተብለው የሚታወቁ እነዚህ ሁለት ኃይላት እርስ በርስ ይጋጩ ነበር፤ ዓለም በቁሳዊ ኃይል ተማምኖ በጉልበት የሚያደቀውን በመሳሪያ የሚቀጠቅጠውን ሲሻ፣ መንፈሳዊው ኃይል ደግሞ ከቊሳዊ ኃይል በላይ የሆነውን መለኮታዊ ኃይል በመጠቀም የሰውን ሁለንተና ሕይወት ለማዳን ይሰራ ነበር፤
እነዚህ ኃይሎች ከሥር መሠረቱ አነሣሣቸው፣ አመጣጣቸውና የኋላ ጀርባቸው የተለያየ በመሆኑ የሚጣጣሙ አልነበሩም፤ በዚህ ዓለም ጥበብ ወይም ፍልስፍና የሚተማመኑቱ ግሪካውያን የመስቀሉን ቃል ሲሰሙ እንደ ሞኝነትም እንደ ድክመትም አድርገው ይመለከቱ ነበር፤ ወልደ እግዚአብሔር በሥጋ በዚህ ዓለም ተገለጠ፤ በለበሰው ሥጋም በኛ ፈንታ ቤዛ ሆኖ በመስቀል ላይ ሞተ፤ በሞቱም እኛን ከረቂቁ ፍዳ ኃጢአት አዳነን የሚለውን የመስቀሉ ቃል ወይም አስተምህሮ ቁሳውያን እንደሞኝነትም እንደ ደካማነትም በመመልከታቸው ለጊዜውም ቢሆን የመስቀሉ ቃል ጠጥሮአቸዋል፡፡

ይህም በመሆኑ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመስቀሉ ቃል ሞኝነት መስሎ ለሚታያቸው የመጨረሻ ዕድላቸው መጥፋት ነው፤ በሌላ በኩል ደግሞ የመስቀሉ ቃል ሰውን ለማዳን የተደረገ የእግዚብሔር ኃይል እንደሆነ አምነው ለሚቀበሉና ለሚኖሩበት የመጨረሻ ዕድላቸው መዳን ነው በማለት የሁለቱም ዕድል አነጻጽሮ ይገልጻል፤ የቊሳውያን ግንዛቤ በቊሳዊው ዓለም የተገደበ ስለሆነ ስለ መንፈሳዊው ዓለም የሚያውቁት ባለመኖሩና ለማወቅም ተነሳሽነቱ በማነሱ፣ በሌላም በኩል መንፈሳውያኑ ደግሞ ከቊሳዊው ዓለም ባለፈ መንፈሳዊው ዓለም መኖሩና ዘላቂና ወሳኝ ኃይልም ያለው መንፈሳዊው ዘንድ ነው ስለሆነም ሰው በቊሳዊ ኃይል ሳይሆን በመንፈሳዊ ኃይል ዘላቂ ድኅነትን ያገኛል ብለው በማስተማራቸው ልዩነቱ ተፈጥሮአል፤ ከዚህ አንጻር የችግሩ ዋና ማጠንጠኛ የመንፈሳዊው ኃይል መኖርና አለመኖር ማወቅ ወይም ማመንና አለማመን ነበረ፤ ይህ እሳቤ ዛሬም ሳይቀር የዓለምን እሳቤ እንደሰነጠቀ ነው፤

ይሁን እንጂ በንጹህ ኅሊና በቅን ሰብእና እንደዚሁም በጥልቅ አእምሮ ለሚያስተውለው ሰው፣ ሓቁ ብዙም የራቀና የረቀቀ አይደለም፤ ምክንያቱም ዓለም እየተመራ ያለው በሚታየው ግዙፍና ደካማ ቊስ ሳይሆን በማይታየውና በረቂቁ መንፈሳዊ ኃይል እንደሆነ ሥነ ፍጥረት ይመሰክራልና ነው፤ በዓለማችን ለሚከናወኑት ቊሳዊና መንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ሁሉ ሙሉ መልስ ያለው መንፈሳዊው ኃይል እንጂ ቊሳዊው ኃይል አይደለም፤ እንዳልሆነም ኅሊናችን ይመሰክርልናል፡፡ ዛሬ በከፍተኛ ሃይማኖታዊ ሥነ በዓል የምናከብረው የቅዱስ መስቀል በዓልም ከዚህ በላይ የጠቀስነው የሁለቱ አካላት ግጭት የፈጠረው ክሥተት ነው፤ መንፈሳዊው ሰው ከመስቀሉ በቀር ከፍዳ ኃጢአት እድንበታለሁ የምለው ሌላ ትምክህት የለኝም ብሎ የመስቀሉን ዘላቂ አዳኝነትን ከፍ አድርጎ ሲዘምር፣ ቊሳዊው ኃይል አልተመቸውም፤ ዝም ብሎ ማየትም ምርጫው አልነበረም፤ ስለሆነም ባለው ዓቅም ሁሉ ተንቀሳቅሶ መስቀሉን ከገጸ ምድር በማስወገድ በእሱ ላይ የተመሠረተውን አስተምህሮና እምነት እንዳይነሣም እንዳይወሳም በማሰብ መስቀሉን ቀበረ፤ ቊሳውያን መስቀሉን ቢቀብሩትም የመስቀሉን ቃል ሊቀብሩ አልቻሉም፤

ምክንያቱም የመስቀሉ ቃል ቊሳዊ ሳይሆን መንፈሳዊ፣ ውጫዊ ሳይሆን ውስጣዊ፣ ምድራዊ ሳይሆን ሰማያዊ፣ ሰብአዊ ሳይሆን መለኮታዊ፣ ጊዜያዊ ሳይሆን ዘላለማዊ ነውና፤ ይህም በመሆኑ ቊሳዊ የሆነው ዕፀ መስቀል ቢቀበርም እሱ የተሸከመው ቃለ ድኅነት በረቂቁ የሰው አእምሮ ተቀርጾና ተዘግቦ ስለሚኖር ተቀብሮ ሊቀር አልቻለም፤ በሂደትም ያልተቀበረው የመስቀሉ ቃለ ድኅነት በንግሥት ዕሌኒ አእምሮ ውስጥ የእምነት ኃይል አቀጣጥሎ የተቀበረውን ዕፀ መስቀል በዛሬው ዕለት ከጥልቅ ጉድጓድ አውጥቶአል፤ በዚህም አሸናፊነቱን አረጋግጦአል፤ ዛሬ የምናከብረው በዓልም ይኸው ኃይለ እግዚአብሔር ለማሰብና በሱ ያለንን እምነት ለማስጠበቅና ቃለ ድኅነቱን ለማሥረጽ ነው፤ መስቀል ኃያልና አሸናፊ ቢሆንም ረቂቁንም ሆነ ግዙፉን ጠላት የሚያሸንፈው በሐቅና በሰላም፣ ኅሊናን በመርታትና በማሳመን እንጂ እንደ ቊሳዊ ኃይል አይደለምና እነሆ ዕፀ መስቀሉ በዛሬው ዕለት በኃይለ እግዚአብሔር በታጀበ ጢሰ-ዕጣን ከተቀበረበት ጉድጓድ በሰላም ሊወጣ ችሎአል፡፡

የመስቀሉ ቃል ዛሬም ተቃራኒ ኃይል አላጣም፤ ዛሬም ለመስቀሉ ቃል ጀርባቸውን የሚሰጡ ሰዎች ብዙ ናቸው፤ ከዚህም የተነሣ ስጋቱ ጭንቀቱ ግጭቱ አለመተማመኑ በዓለማችን ከምን ጊዜውም በላይ ተንሰራፍቶአል፤ ሀገራችንም ከዚህ የተለየች ልትሆን አልቻለችም፤ በዓለ መስቀሉን ከማንኛውም ክፍለ ዓለም በተለየ ሥነ ሥርዓት ብናከብርም የመስቀሉ ሰላም ግን በሀገራችንና በሕዝባችን እየተነበበ አይደለም፤ ይህንን ለማስገንዘብ የሚተላለፈው መልእክትም እየተደመጠ አይመስልም፤ የመስቀሉ ቃል ማለት ሰዎች በነፍሳቸውም ሆነ በሥጋቸው የተሟላ ደኅንነት ያግኙ ማለት ነው፤ የመስቀሉ ቃል ማለት የሰዎች ሃይማኖታዊ ነጻነት ይከበር፤ በሕይወት የመኖር ሰብአዊ መብታቸውም ይጠበቅ ማለት ነው፤ የመስቀሉ ቃል ማለት ሰዎች በዚች ምድር በእኩልነት በአንድነት በመተጋገዝ በመረዳዳት በፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል በሰላም በፍቅር በስምምነት በመተባበር ይኑሩ ማለት ነው፤

የመስቀሉ ቃል ማለት የሰው ሕይወት በዚህ ዓለም የተገደበ አይደለም ዘላለማዊ በሆነው መንፈሳዊ ዓለምም ሕይወት በቀዋሚነት ይቀጥላልና እግዚአብሔርን ፍሩ፤ ለእርሱም ታዘዙና ተገዙ ማለት ነው፤ የመስቀሉ ቃል ማለት በኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በፈሰሰው ደም የመዳን ዕድል ተከፍቶላችኋልና በደሙ ታጥባችሁ ወደ እግዚብሔር መንግሥት ግቡ ማለት ነው፤ ይህንን የመስቀል ቃል ዓለም ብትቀበለው ኖሮ በየጊዜው እያንዣበባት ያለው ስጋት ሁሉ ቦታ አይኖረውም ነበር፤ አሁንም በመስቀሉ ስም ለዓለም ሕዝብም ሆነ ለሀገራችን ዜጎች ሁሉ የምናስተላልፈው ዓቢይ መልእክት የመስቀሉ ቃል ሁላችንንም በእኩልነትና በፍቅር የሚያስተናግድ ነውና እሱን እንቀበል፤ የዓለም ስጋቶች በሙሉ ሊቀረፉ የሚችሉ በመስቀሉ ቃል ብቻ ነውና የሚል ነው፡፡
እግዚአብሔር የተባረከና የተቀደሰ በዓል ያድርግልን፡፡
እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!! አሜን::

         አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስምወዕጨጌ ዘመንበረ
             ተክለ ሃይማኖት

     መስከረም 16 ቀን 2017ዓ.ም.
       አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
2024/09/30 06:16:57
Back to Top
HTML Embed Code: