Telegram Web Link
‹‹ነገን ዛሬ እንሥራ››

ክፍል ስድስት


ውድ የእግዚአብሔር ቤተ ሰቦች! እንደምን ሰነበታችሁ? በዚህ ርእስ ቤተ ክርስቲያን ትናንት ለነበራት ድምቀት፣ ዛሬ ለገጠማት ተግዳሮት፣ ነገም ለሚኖራት ማንነት ክብረ ክህነትና ክብረ ምንኩስና የማይተካ አስተዋጽኦ እንዳላቸው እና እነዚህ ሁለት የክብረ ቤተ ክርስቲያን ምሰሶዎች የነገዋን ቤተ ክርስቲያን ሁኔታ ሊወስኑ እንደሚችሉ መንደርደሪያ ሐሳብ አንሥተን በመቀጠልም   “ክብረ ክህነት ትናንት እንዴት ነበር? ዛሬስ ምን ሁኔታ ላይ ነው ? ነገስ ምን መሆን አለበት?” የሚሉ ጉዳዮችን ዳስሰን እስከ ክፍል አምስት አብረን ዘልቀናል፡፡ በክፍል ስድስትና ቀጣዮቹ ክፍሎች ደግሞ “ክብረ ምንኩስና ትናንት፣ ዛሬና ነገ ምን ይመስላልና መምሰል አለበት” የሚለውን እናጋራችኋለን፤ አብራችሁን ዝለቁ! መልካም ንባብ!

ክብረ ምንኩስና፡-

ምንኩስና ምንድን ነው?


‹‹መንኮሰ›› መለኮሰ፣ ተለየ፣ ሞተ፣ ከዓለም፣ ከሕዝብ ተለየ” ማለት እንደሆነ የግእዝ መዝገበ ቃላት ይናገራል፡፡

‹‹መነኮስ›› ማለት ደግም “መነኩሴ፣ መናኝ፣ ድኻ፣ ከዓለም ከዘመድ የተለየ፣ ለዓለም የማይጨነቅ፣ ጥሬ ቆርጥሞ አዳሪ፣ ለራሱ ጥላ ለእግሩ ጫማ የሌለው” ማለት ሲሆን መናኝ ይህን ዓለም የመነነ፣ የናቀ፣ የተወ ማለትም ነው፡፡ ‹‹መነነ ዘንተ ዓለመ፤ ይህን ዓለም ተወ›› እንዲል፡፡ (ገጽ ፺፱)

‹‹ምንኩስና›› ማለት ደግሞ “ቆብ መድፋት፣ ከዚህ ዓለም መለየት፣ ሥጋዊ ስሜትን መግደል” ማለት ነው፡፡ (ሕያው ልሳን፣ መዝገበ ቃላት ገጽ ፺፰-፻፵፱)
ከላይ ከተሰጠው የግእዝ ትርጉም ተነሥተን ስንመረምረው ምንኩስና ማለት ምን ማለት እንደሆነና ምን ያክል ከባድ ኃላፊነት እንደሆነ እንረዳለን፡፡ ዓለሙንና አምሮቱን የናቀ፣ ስለ ጽድቅ ብሎ ራሱን ያደኸየ፣ “እኔ ለዓለም ሙት ነኝ፤ ዓለምም በእኔ ዘንድ ሙት ናት፤ የዓለም የሆነው ሹመቱ፣ ሽልማቱ፣ ሀብቱ፣ ንብረቱ አያስፈልገኝም፤ የሚስት ደስታ የልጅ ተስፋ ይቅርብኝ፤ ንጽሕ ጠብቄ፣ ከሴት ርቄ ራሴን ለመንግሥተ ሰማያት ጃንደረባ አድርጌ በጾም፣ በጸሎት፣ በትሩፋት ተወስኜ እኖራለሁ” ብሎ የወሰነ፣ ራሱን የለየ፣ ቁረንጮ አንጥፎ፣ ጠፍር ታጥቆ፣ ጥሬ ቆርጥሞ ለመኖር የማለ፣ ስለ ጽድቅ ብሎ ራሱን ያስራበ ያሰጠማ መሆኑን ተረድተናል፡፡ (ማቴ.፭፥፮)

‹‹ምንኩስናሰ ጥበበ ሕግ መሲሓዊት›› እንዳሉ ፫፻፣ ምንኩስና በወንጌል የተገኘች መሲሐዊት ሕግ ናት፤ ቀድሞ አልነበረችም፡፡ መነኮሳት በግብራቸው፣ በንጽሕናቸው ሰማያውያን መላእክት ተሰኝተዋልና፡፡ ‹‹መነኮሳት በምድር ያሉ መላእክት በሰማይ ያሉ ሰዎች ናቸው›› ይላል ፍትሐ ነገሥት፡። (ፍት መን አን ፲፥፫፻፵፬) ክርስቶስን የተከተሉ፣ ሐዋርያትን የመሰሉ ናቸውና፡፡ የመጀመሪያው የምንኩስና ሥርዓት ከዘመድ፣ ከእናት አባት መለየት፣ ከሀገር መውጣት ነው፡፡ ምክንያቱም መነኩሴ ማለት ‹‹ምውት ዘተፈልጠ እምዓለም፤ ከዚህ ዓለም የተለየ ሙት›› ማለት ነውና፡፡

ሲሰድቡት የማይሳደብ፣ ሲመቱት የማይማታ፣ ልቡ ክፉ ነገር ቂም በቀል፣ ልብስ ጉርስ የማያስብ ማለት ነው፡፡ የሞተ ሰው ይህ ሁሉ የለበትምና፡፡ ‹‹ልብስ ጉርስ ቢያስብ ጥቂት የሚበቃው ይሁን፡፡ ሰብአ ዓለምን ስንኳ አታስቡ›› ብሏል፡፡ መነኩሴ የነፍሱን ነገር ትቶ እንዴት ልብስ ጉርስ እያለ ያስብ፤ ይህ ምንኩስና አይባልም ከንቱ ነው፡፡ (መጽሐፈ ምዕዳን) እንዳለ፡፡ ምንኩስና ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተገኘ ሲሆን ቆቡ የአክሊለ ሶክ፣ ቀሚሱ የከለሜዳ፣ ቅናቱ የሐብል፣ አስኬማው የሰውነቱ ምሳሌ ነው፡፡ (የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ታሪክ ከልደተ ክርስቶስ እስከ ፳፻ ዓ.ም)

የምንኩስና ዓላማ ምንድን ነው?

ምንኩስና የዘለዓለምን መንግሥት ለመውረስ ይቻል ዘንድ ፍጹም ሆኖ መገኘት ነው፡፡ መጽሐፍ እንደሚነግረን የምንኩስና ዓላማ ፍጹም መሆን ነው፡፡ አንድ ሰው “የዘለዓለምን ሕይወት እወርስ ዘንድ ምን ላድርግ?” ብሎ ለጠየቀው ጥያቄ ጌታችን ኢየሱስ ክረስቶስ እንዲህ ብሎ መለሰለት፤ ‹‹ፍጹም ትሆን ዘንድ ትወዳለህን? ያለህን ሁሉ ሂደህ ሽጠህ ለነዳያንም መጽውተህ ና ተከተለኝ›› አለው፡፡ (ማቴ. ፲፱፥፳፩) ሰው ከእግዚአብሔር ይልቅ እናቱን አባቱን፣ ሚስቱን ልጁን ከወደደ እንዲሁም ሀብትና ንብረቱን ከመረጠ መነኩሴ እንደማይሆን ፍጹምም ሊሆን እንደማይችል፣ ፍጹም ሊሆን፣ የዘለዓለምን ሕይወት በምንኩስና ሊወርሳት የሚሻ ደግሞ ሁሉን ትቶ መከተልን፣ መመነንን፣ ከዘመድ አዝማድ መለየትን፣ ከሀገር መውጣትን፣ ራስን መለወጥን የሚፈልግ እንደሆነ ከጥቅሱ እንረዳለን፡፡

የቀደሙ አባቶቻችንም ይህን ሥርዓት አብነት አድርገው ከሀገር ርቀው፣ ከቤተ ሰብ ተደብቀው፣ ራሳቸውን ለውጠው፣ ከቤተ ዘመድ ከሚመጣ ፈተናና ከውዳሴ ከንቱም ተጠብቀው፣ በማይታወቁበት ቦታ በአት አጽንተው በመኖር ሕገ መነከሳትን የጠበቁ ለክብርም የበቁ ብዙዎች ናቸው፡፡

ምንም እንኳን ብቸኛው የሕይወት መንገድ ባይሆንም ምንኩስና ትልቁና ከምድራዊ ዓለም ለይቶ ከሰማያዊ ዓለም የሚቀላቅል፣ ከሰው ተራ አውጥቶ ከመላእክቱ ጋር የሚያዛምድ፣ ሥጋዊ ደማዊ ከሆነው ምድራዊ አስተሳብና አኗኗር ለይቶ ከማኅበረ መላእክት የሚደምር፣ ፍጽም ሆኖ ፍጹም የሚያደርግ አምላካዊ ሕግ መሆኑን ከፍትሐ ነገሥቱም ከወንጌሉም ከሕንፃ መነኮሳቱም የምንረዳው እውነት ነው፡፡ በጥቅሉ የምንኩስና ዓላማው ፍጹም ሆኖ ፍጹም የሆነውን አምላክ ተከትሎ ዘለዓለማዊ ርስቱን (መንግሥቱን) መውረስ መቻል ነው፡፡

ምንኩስና ትናንት፡-

ምንኩስና ትናንት በነበረችው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ክብሩ እንደ ፀሐይ የሞቀ፣ እንደ ጨረቃ የደመቀ፣ እንደ ከዋክብት የተንቆጠቆጠ ነበር፡፡ ምንኩስና ትናንት በኢትዮጵያ ምድር እንኳን ተራውን ምእመኑን ነገሥታቱን፣ መኳንንቱን መሳፍንቱን፣ የነገሥታቱን እና የባለጸጋዎችን ልጆችና ሚስቶቻቸውን ሳይቀር መማረክ የቻለ፣ ዘውድ አስወልቆ አስኬማ ያስደፋ፣ ልብሰ መንገሥት አስወልቆ ቆዳ መልበስን፣ ሰሌን ማንጠፍን፣ ቅል አንጠልጥሎ፣ ጓዝን ጠቅሎ ገዳም በረሃ መውረድን ያስቻለ ታላቅ ቅቡልነትና ገዥነት የነበረው ሥርዓት እና አስተምህሮ ነበር፡፡ (ግንቦት ፳ ስንክሳር)

እንደ ቀድሞዎቹ እንደነ ኤልያስ፣ እንደ ኋለኞቹ እንደነ መጥምቀ መለኮት ዮሐንስ ንጽሕናዬን ጠብቄ፣ ከሴት ርቄ እኖራለሁ ብሎ ሰውነቱን ለእግዚአብሔር አደራ በሰጠው አባ እንጦንስ ላይ ያደረው ጸጋ ምንኩስና ያደረባቸው በርካታ መናንያን በኢትዮጵያ ገዳማት ነበሩ፤ አሁንም ጥቂቶች ይኖራሉ፡፡

ምንኩስና ትናንት በኢትዮጵያ ቤተ ክረስቲያን የቅድስና፣ የንጽሕና፣ የመንፈሳዊነት ማሳያ ጥግ ነበር፡ ፡ዘንዶ የሚጫሙ፣ በባሕር ላይ የሚራመዱ፣ አንበሳ የሚጋልቡ፣ ራሳቸውን ከመግዛት አልፈው ተፈጥሮን የገዙ፣ ሃይማኖታቸው የጸና፣ ምግባራቸው የቀና፣ ተባርከው የሚባርኩ የሚያስባርኩ ተቀድሰው የሚቀድሱ የሚያስቀድሱ፣ ትምህርታቸው ሕይወት፣ ጸሎታቸው በረከት የሚያሰጥ፣ በአጽንኦ በአት በቀኖና ገዳማት የጸኑ፣ ሁሉ የሚያከብራቸው የሚያፍራቸው፣ በነገሥታት ሹመት፣ በባለጸጎች ምጽዋት የማይታለሉ፣ የሴት ፊት የአገልግል ፍትፍት የማያውቁ መነኮሳት ነበሩባት፡፡ ‹‹ይሔሶ ለመነኮስ በሊዐ ኅምዝ ዘይቀትል እምይብላ ምስለ ብእሲት እመኒ እኅቱ አው እሙ፤ከሴት ጋር ከመብላት ለመነኩሴ መርዝ ቢበላ ይሻለዋል፤ እኅቱም እናቱም ብትሆን›› እንዳለ አባ ብንያሚን የተባለ አባት(መ/ምዕዳን)፡፡

በእፍኝ ጥሬ፣ በጥርኝ ውኃ የሚኖሩ ግብረ መነኮሳትን፣ ሥርዓተ ገዳማትን ሳያፋልሱ በትጋት ዘመናቸውን የፈጸሙ ብዙ መነኮሳት የነበረባት ቤተ ክርስቲያን ነበረች፡፡ (ነበረች ስንል አሁን ምንም የለም ለማለት አይደለም መጠኑን ለመግለጽ እንጂ) ምንኩስና ትናንት ትልቅ የበረከት ምክንያት ነበር፡፡ መነኮሳት ትናንት የከተማ ሕይወት፣ የነገሥታት ፊት፣ የአደባባይ ሙግት አያውቁም ነበር፡፡ ለሁሉም ነገር ሰይፋቸው፣ ዘገራቸው ጸሎታቸው ነበር፡፡ የምንኩስና ኑሮ ፈጣሪን ማገልገል፣ ሕገ ምንኩስናን መጠበቅ፣ ከማናቸውም ዓለማዊ ኑሮ መከልከል መሆኑን በደንብ ያውቃሉ፡፡

ምንኩስናን በኢትዮጵያ ካስተዋወቁትና ከአስፋፉት ዘጠኙ ቅዱሳን ጀምሮ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በኢትየጵያ ቤተ ክርስቲያን የክብረ ቤተ ክርስቲያን መታያ፣ የብዙኃን ምኞት የጥቂቶች ስኬትና ኑሮ፣ የክርስትናችን ዓምድ ሆኖ ቆይቷል፡፡ ቅድስናቸው ከኢትዮጵያ አልፎ በሌሎች ዓለማት የታወቁ፣ ታላላቅ ገዳማትን መሥርተው፣ ደቀ መዛሙርት አፍርተው፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ጽፈው፣ ደጉሰው፣ ሃይማኖት እንዲጸና፣ ምግባር እንዲቀና፣ ፍትሕ ርትዕ እንዲሰፍን፣ ፍቅረ እግዚአብሔር ፍቅረ ቢጽ ያስተማሩ፣ ቃላቸው ጦር ጸሎታቸው አጥር ሆኖ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀ በርካታ መነኮሳትን ቤተ ክርስቲያናችን አፍርታለች፡፡

በጥቅሉ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የነበሩ መነኮሳት የእግዚአብሔር መልአክ ለአባ ጳኩሚስ ያሳየው ዓይነት መነኮሳት ነበሩ፡፡የእግዚአብሔር መላክ ለአባ ጳጉሚስ አምስት መልካም የሆኑ ማኅበራተ መነኮሳትን አሳይቶት ነበር፡፡
በበጎች የተመሰሉ መነኮሳት ፡- እንደ በጎች በማኅበር በአንድነት ሳይለያዩ በፍቅር እንደ አንድ አካል ሆነው በማኅበር የሚኖሩ መነኮሳት፣ ባለመለያየት፣ በቅንነት፣ በአንድነት የሚኖሩ ቅዱሳን መነኮሳትን የሚወክሉ መነኮሳትን፣

በርግብ የተመሰሉ መነኮሳት፡- በየዋህነትና በቅንነት በፍቅርና በአንድነት የሚኖሩ፣ ቢጠሏቸው፣ ቢሰድቧቸው፣ ቢጸየፏቸው የማይቀየሙ መነኮሳትን፣

በዋኖስ የተመሰሉ መነኮሳት፡- በጣፈጠና ባማረ ጣዕመ ዜማ ያለ ትዕቢትና ትምክህት በትሕትናና በፈሪሃ እግዚአብሔር በመንቀጥቀጥና እንባቸውን እያፈሰሱ ለፈጣሪያቸው የሚዘምሩና የሚያመሰግኑ መነኮሳትን በዋኖሶች መስሎ አሳይቶታል፤ የዋኖስ ድምፅ ጥዑም ነውና፡፡

በተጨማሪም በንቦች የተመሰሉ መነኮሳት፡- እንደ ንቦች ጠቢባን፣ እንደ ንብ በትጋት የጽድቅ ሥራዎችን ከገድላት የሚቀስሙ መነኮሳትን፣

በፌቆዎች የተመሰሉ መነኮሳትን፡- ያለንዝህላልነትና ያለመታከት በትጋት እንደ ፌቆዎች እየሮጡ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ሥራ የሚፋጠኑ መላኩ ለአባ ጳኩሚስ አሳይቶት አባታችንም አይቶ ማድነቁን ሕንፃ መነኮሳት ይነግረናል፡፡ (ሕንፃ መነኮሳት ክፍል ሦስት ቁጥር ፲) ትናንት በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንም አባ ጳኩሚስ ያያቸው ዓይነት መነኮሳትና ማኅበረ መነኮሳት እንደ ምድር አሸዋ፣ እንደ ሰማይ ከዋክብት በዝተውና ደምቀው የነበሩበት መሆኑን የበርካታ ገዳማትና መናንያን ታሪኮች ያስረዱናል፡፡

ለመሆኑ “ክብረ ምንኩስና ዛሬ ምን ሁኔታ ላይ ነው?” የሚለውን በክፍል ሰባት እንዳስሰዋለን ቸር እንሰንብት!
የጀርመንና አካባቢው እና የምሥራቅ ጎጃም አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮናስዮስ የዳግም ትንሣኤን በዓል ከችግረኞች ጋር አከበሩ።

ብፁዕነታቸው ግንቦት 04/2016 ዓ.ም በተካሄደ መርሐ ግብር "የአብነት ተማሪዎችን እና ችግረኞችን መርዳት ማገዝ የቅድስት ቤተከርስቲያን ተቀዳሚ ተግባር ሊሆን ይገባል ሲሉ ገልጸዋል።

ለአብነት ተማሪዎችና በችግር ያሉ ወገኖችን በዕለቱ የምሳ ግብዣ ያደረጉት የደ/ማርቆስ ከተማ ወ/ቤተ ክህነት ምግባረ ሰናይ ክፍል
፣በአድባራት የሰ/ት/ቤት ወጣቶች ኅብረት፣ በኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ኅብረት፣ በማኅበረ ቅዱሳን የደ/ማርቆስ ወረዳ ማእከል
በጋራ በመሆንና ምዕመናን በማስተባበር ነው።

ከምዕመናን የተሰበሰበውን የልብስ ስጦታ በብፁዕ አባታችን የተሰጠ ሲሆን ይህ በጎ ተግባር ተጠናክሮ እንዲቀጥል አባታዊ መመሪያ ሰጥተዋል የተሳተፋትንም አመስግነው በችግር ውስጥ ያሉ ወገኖችንም በእግዚአብሔር ቃል አጽናንተዋል።

ዘገባው የማኅበረ ቅዱሳን ደ/ማርቆስ ማእከል ሚዲያ ክፍል ነው
"..የሥጋ ስሜትን በመንፈሳዊው አገልግሎት ቀላቅሎ የሚወራጭ ቢኖር እሱ የያሬድ ልጅ አይደለም ።መንፈሳዊ ተመስጦ እንጂ እስክስታ የሚያስመታ ዝማሬ ቅዱስ ያሬድ አልደረሰም"ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ
    ሐመር መጽሔት ፴፪ ኛ ዓመት   ቁጥር ፭

የኅትመት ዘመን ፦ ግንቦት  ፳፻፲፮ ዓ.ም
አዘጋጅ ፦በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ  ቤተ ክርስቲያን ማኀበረ ቅዱሳን በልማት ተቋማት አስተዳደር  በመጽሔት ዝግጅት ክፍል የሚዘጋጅ ትምህርታዊ መጽሔት
•  ገጽ ብዛት፦፳፰
   ዋጋ ፦፵ ብር 
•  ሐመር  መጽሔት  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትምህርተ ሃይማኖት  ሥርዓትና ትወፊት ጠብቃ በልማት ተቋማት አስተዳደር  በመጽሔት ዝግጅት ክፍል  በየወሩ የምትወጣ መንፈሳዊ መጽሔት ናት፡፡
•  ሐመር መጽሔት ፴፪ ኛ ዓመት  ቁጥር ፭  ግንቦት  ፳፻፲፮ ዓ.ም በመልዕክት ዐምድ "#ቅዱስ አባት ሆይ እነዚህን የሰጠኸኝን  እንደእኛ አንድ ይሆኑ ዘንድ በስምህ ጠብቃቸው " በማለት ሁሉም አበው የክርስቶስ ማደሪያ ሆነው ከተገኙና መድኃዓለም ክርስቶስ በመካከላቸው ከሆነ የአንድነት ጠላት የሆነው ሰይጣን ፣መግቢያ ቀዳዳ ሊያገኝ ስለማይችል ፍጹም አንድነት  እንደሚፈጠር ያሳያል፡፡ አባቶቻችን ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በአገልግሎት ሂደት የተፈጠረና የሚፈጠር ማንኛውንም አይነት ልዩነት በውይይትና በምክክር  መፍታት እንደሚገባና እንደሚቻል ከራሳለው አልፈው ለዓለም ተግባራዊ ትምህርት ካልሰጡ ማን ሊሰጥ ይችላል?  ቤተ ክርስቲያንን ከፈተና ለመታደግ የብጹዓን አባቶች  እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ መሆን  ይጠበቅባቸዋል ። አጠቃላይ የሆነ የይቅርታና የዕርቅ መርሐ ግብር አዘጋጅቶ ሰላምን መመስረትና ፍቅርን ማጽናት ቀዳሚው የወቅቱ ጉዳይ እንደሆነ  ይጠቁማል።

  .#ዐውደ ስብከት  ሥር” #እግዚአብሔር አይዘገይም "  በሚል ርእስ   በብላቴናው ያሬድ አእምሮ ዕውቀትን ከማሳደር የዘገየ ሊመስላቸው  እንደሚችል  ያሳያል ።አንድን ነገር ሁል ጊዜ እኛ በምናየው በኩል ብቻ ያለውን ገጽ በመመልከት ነገር እናበላሻለን።  ዛሬ ከእኛ በታች የሆኑ ሁሉ ጊዜ ከእኛ በታች ሊሆን እንደሚችል ማሰብ እንደማይገባ ፣ከምድራዊ ጉባኤ ቤት የተሰናበተው ደቀ መዝሙር  ያሬድ በሰማዩ ጉባኤ ቤት ተካፋይ እንደሆነ ያትታል ።
     ቅዱስ ያሬድ ለቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ያዘጋጀ ሊቅ ነው። የሥጋ ስሜትን በመንፈሳዊው አገልግሎት ቀላቅሎ የሚወራጭ ቢኖር እሱ የያሬድ ልጅ አይደለም ።መንፈሳዊ ተመስጦ እንጂ እስክስታ የሚያስመታ ዝማሬ ቅዱስ ያሬድ አልደረሰምና በምንዘምርበት ጊዜ ከመንፈሳዊ ተመስጦ እንዳንወጣ ራሳችንን መግዛት ይኖርብናል ።
  #በትምህርተ ሃይማኖት ዐምድ ሥር “#ጰራቅሊጦስ የእውነት መንፈስ "በሚል ዐቢይ ርእስ  ጌታችን በኅምሳኛው መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት ቋንቋ እንደገለጸላቸው በበቂ  ማስረጃ የተደገፈ  ትምህርት ይዛለች።በቅዱሳን ሐዋርያት ላይ መንፈስ ቅዱስ ወረደ ሲባል እንዴት ነው?የሚለውን ጥያቄ መልስ ትሰጣለች ።በዓለ ጰራቅሊጦስ፣ቋንቋና ቤተ ክርስቲያን ያለውን ሁኔታ ያሳያል።መንፈስ ቅዱስ ለሰው የሚጠቅም  ለአገልግሎት የሚውል ቋንቋን እንጂ   አረፋ የሚያስደፍቅ  ትርጉም አልባ አጋንንታዊ ጬኸትን አይገልጥም ።በዓለ ጰራቅሊጦስን ስናስብ ከእኛ ምን እንደሚጠበቅ በዝርዝር ያሳያል ።

• ዐቢይ ጉዳይ  ዐምድ  ሥር  ደግሞ “#የቅዱስ ሲኖዶስ ኃይል  ክብርና ሥልጣን “ በሚል ርእስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ከሌሎች ቤተ እምነቶች የምትለይበት አንዱ ኦርቶዶክሳዊነት መገለጫ የቤተ ክርስቲያያኒቱ ሉዓላዊ ሥልጣን ባለቤትና የክርስቶስ እንደራሴ ቅዱስ ሲኖዶስ መሆኑን ያሳያል ። የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ነቀፋ የሌለባቸው ሲሆኑ መንጋው ይከተላቸዋል።ድምፃቸው ይሰማል።ልጆች በአባቶቻቸው መኩራት እንጂ ማፈር አይፈልጉም ።ልጆች በአባቶቻቸው መጽናናት እንጂ መሰቀቅ አይፈልጉም ።
    በሐመር መጽሔት በዐቢይ ጉዳይ ዐምድ ሥር  በቅዱስ ሲኖዶስ አባላት መካከል በሐሳብ መለያየት የሚመጣው የሆነ  ወገን የመንፈስ ቅዱስን ፈቃድ ሳይሆን የራሱን ምኞት መከተል ሲጀምር ነው ትላለች።  ቅዱስ ሲኖዶስን ራሱን ያስገኘው ምሥጢረ ክህነት እንደሆነ ያስተምራል። ከዱቁና እስከ ጵጵስና በሚሰጡ የክህነት መዓርጋት ለዚሁ የሚገቡ ሰዎችን የምንለይበት ሥርዓት በየጊዜው መጤን እንዳለበት ይጠቁማል ። ጳጳሳት ክህነት የሰጧቸውን ልጆቻቸውን ለመምከር ለመገሠጽ መሰቀቅ እንደማይገባቸው ያስገነዝባል።
የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ኘቀፋ የሌለባቸው ሲሆኑ መንጋው እንደሚከተላቸው ድምጻቸው እንደሚሰማ ያሳያል።
•  ክርስትና በማኀበራዊ ዐምድ ሥር  ደግሞ  " ትዳር _ክፍል ፩  “በማለት  ባልና ሚስት በትዳራቸው ደስተኛና ውጤታማ እንዲሆን ከሚረዷቸው ነገሮች መካከል አንዱ የመንፈስ አንድነት ነው፡፡ ትዳር ለዕድሜ ለኢኮኖሚ ለቤተሰብ ጭቅጭቅ ለልጅ ፍቅር መልስ መስጫ አይደለም፡፡ ትዳር የራሱ ምንነትና መገለጫዎች አሉት።ትዳር እንደ ዕድር ወይም እንደ ዕቁብ  ለመተጋገዝ ሲሉ ሰዎች የመሠረቱት ተቋም አይደለም፡፡ እነዚህ ማኅበራዊ አገልግሎት የሚሰጥባቸው ተቋማት እስከ ወደድህ አብረህ እስካለህ ብቻ በአባልነት የምትኖርባቸው ናቸው፡፡ የመኖርያ ቦታ ስትቀይር፡ ከአባላቱ ጋር መግባባት ካልቻልህ ወይም ደግሞ እንዲሁ ካልፈቀድህ አባልነትህን መተው ትችላለህ፡፡

ትዳር ግን የሰውን ባሕርይ፡ በባሕርይውም ያለውን ድካም፡ ለድካሙም የሚያስፈልገውን መፍትሄ ከሚያውቅ ከልዑል እግዚአብሔር የተሰጠ ስጦታ ነው፡፡

•  በእናስተዋውቃችሁ ዐምድ ሥር “#በእንተ ቅዱስ  ኤጲፋንዮስ ክፍል _፩  "  በሚል ርእስ ስለቅዱስ ኤጲፋንዮስ   ልደትና ዕድገት በስፋት ይዳስሳል ።

•  በነገዋ  ቤተ ክርስቲያን ዐምድ  ሥር “ነገን ዛሬ እንሥራ _ክፍል ፪ “ በሚል  ሕዝብ  ግንኙነት እና ትብብር አገልግሎት ማስተባበሪያ   ምንኩስናን በተመለከተ ፤በሥርዓተ ምንኩስና  ውስጥ  የሚነሱ ጉዳዮች ይዳስሳል ።ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ክብሯ ተጠብቆ ለቀጣይ ትውልድ ትተላለፍ ዘንድ ክህነት እና ምንኩስናን መጠበቅ ወሳኝ ጉዳይ እንደሆነ ይታወቃል ።

   #በኪነ ጥበብ ዐምድ "# ሎሚ  ክፍል _፩ " በሚል ያስነብባል።
•  የጥያቄዎቻችሁ መልስ ዐምድ “#ክርስትናና  ዘመናዊነት ክፍል ፩- " በሚል ርእስ ከመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሺፈራው  ጋር የተደረገ  ወቅታዊ ምላሽ ይዛለች  ።
   ሐመር መጽሔት ፴፪ ኛ ዓመት   ቁጥር ፭ በማሰራጨት ፡በማንበብና በማስነበብ የድርሻችን እንወጣ !
magazine @eotcmk.org  ሐመር መጽሔት  ዝግጅት  ክፍል
በህንድ ሀገር ማኅበረ ቅዱሳን ያስተማራቸው የማርዋዲ ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ተመረቁ።

በማኅበረ ቅዱሳን ሩቅ ምሥራቅ ማእከል አስተባባሪነት ላለፉት አራት ዓመታት ተከታታይ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ሲማሩ የነበሩ አሥራ ዘጠኝ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ግንቦት 4 ቀን 2016 ዓ/ም ተመረቁ።

በዚህ የተማሪዎች ምርቃት መርሐ ግብር ላይ የግቢ ጉባኤው አባላትና ተመራቂ ተማሪዎች የተገኙ ሲሆን የሩቅ ምሥራቅ ማእከል ጸሐፊ  እና የግቢ ጉባኤ ማስተባበሪያ ክፍል አባላት መርሐ ግብሩን በዙም (Zoom) ተከታትለዋል።

የሩቅ ምሥራቅ ማእከል የተተኪ ትዉልድ እና ግቢ ጉባኤ ማስተባበሪያ ክፍል ተጠሪ ዶ/ር ሲራክ ተከተል ለተመራቂዎች የእንኳን ደስ ያላችሁ መልእክት አስተላልፈዋል።

በመልእክታቸውም "ተመርቃችሁ ከወጣችሁ በኋላ በየአካባቢያችሁ በሚገኙ ማእከላት ሥር በመታቀፍ የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ተጠናክሮ እንዲቀጥል የድርሻችሁን እንድትወጡ ማኅበራችሁ ማኅበረ ቅዱሳን ያሳስባችኋል" ብለዋል። በተጨማሪም ለግቢ ጉባኤዉ ስኬት አስተዋጽኦ ላደረጉ መምህራንና አስተባባሪዎች ምስጋና አቅርበዋል።

በዕለቱም በዲ/ን ፋንታሁን የሩቅ ምሥራቅ ማእከል ጸሐፊ ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል። ተመራቂዎችመ‍እ መዝሙር ያቀረቡ ሲሆን ለተመራቂዎች የመስቀል ስጦታ በግቢ ግባኤው ሰብሳቢ መምህር ዋሲሁን አገሩ አማካኝነት ተበርክቷል።

በተመሳሳይ በህንድ ሀገር በኬአይአይቲ (KIIT) ግቢ ጉባኤ ስር ሆነዉ ላለፉት 3 ተካታታይ ዓመታት  ሲማሩ የነበሩ 5 የግቢ ጉባኤዉ አባላት ተመርቀዋል።

ዘገባውን የማኅበረ ቅዱሳን ሩቅ ምሥራቅ ማእከል ሚዲያ ክፍል አድርሶናል።
2024/09/28 20:18:44
Back to Top
HTML Embed Code: