Telegram Web Link
#መስከረም_4

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም አራት በዚህች ቀን #ወንጌላዊው_ቅዱስ_ዮሐንስ ልደቱ ነው፣ የድባው #አቡነ_ሙሴ እረፍታቸው ነው፣ #ነቢዩ_ኢያሱ_ወልደ_ነዌ አረፈ፣ #አባ_መቃርስ_ሊቀ_ዻዻሳት አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ወንጌላዊ

መስከረም አራት በዚህች ዕለት ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ከእናቱ ማርያም ባውፍልያ ከአባቱ ዘበዴዎስ የተወለደበት ዕለት እንደሆነ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌልን ለመስበክ ዕጣ የደረሰው እስያ ስለነበር ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን አስከትሎ ሄደ፡፡ ይኽችውም ኤፌሶን በጥንቱ በታናሽ እስያ በዛሬው የቱርክ ግዛት ውስጥ ከተማ ናት፡፡ ዛሬ ኢያዞሎክ ተብላ የጥንት ታሪኳ ጠፍቷል፡፡ አስቀድሞ ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን ሰብኮባታል፡፡ ደቀ መዝሙሩን ቅዱስ ጢሞቴዎስንም በከተማዋ ላይ ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾሞት ነበር፡፡ እርሱም በግፍ እስከተገደለበት ጊዜ ድረስ ቅዱስ ዮሐንስን እየረዳው በከተማዋ ብዙ አገልግሏል፡፡ በኋላ ግን በግፍ ገድለውታል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ኤፌሶን ለመሄድ በመርከብ ሲሳፈር መርከቡ በማዕበል ተሰበረ፡፡ ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን መዕበሉ ወደ አንዲት ደሴት አደረሰው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን በመርከቡ ስባሪ ተንጠልጥሎ በባሕሩ ማዕበል መካከል 40 ቀንና 40 ሌሊት ከኖረ በኋላ ማዕበሉ ተፍቶ አብሮኮሮስ ካለበት ደሴት አደረሰውና ተያይዘው ኤፌሶን ከተማ ገቡ፡፡ የከተማይቱም ሰዎች እጅግ ክፉዎች ስለነበሩ መጀመሪያ ላይ ቅዱስ ወንጌልን መስበክ አልቻሉም ነበር፡፡ እነርሱም እጅግ ክፉዎች መሆናቸውን ስላወቀ ቅዱስ ዮሐንስ ገና ዕጣው ሲደርሰው በሀዘን አልቅሶ ነበር፡፡ አሁንም ከተማው በገቡ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ ምክንያት በመፍጠር ሮምና ለምትባል ሴት የውሽባ ቤቷ እሳት አንዳጅ ሆኖ አብሮኮሮስም ዕቃ አጣቢ ሆነው ተቀጠሩ፡፡ የቀጠረቻቸው ሴትም እጅግ ታሠቃያቸው ጀመር፡፡ ባሮቿ እንደሆኑ ተስማምተው ስለጻፉላት ትደበድባቸውም ነበር፡፡

እነርሱም በታላቅ ጉስቁልና ውስጥ እየኖሩ እያለ በአንዲት ዕለት የአገረ ገዥው ልጅ ለመታጠብ ወደ ውሽባው ቤት ገባ፡፡ በውሽባ ቤቱም የሰይጣን ኃይል ስለነበረበት የመኰንኑን ልጅ አንቆ ገደለው፡፡ የአገሪቱም ሰዎች ሁሉ ለሞተው የመኰንን ልጅ ሊያለቅሱ ሲሰበሰቡ ቅዱስ ዮሐንስም አብሮ ቆሞ ሲመለከት ሮምና መጥታ "በጌታዬ ልጅ ሞት ልትደሰት መጣህን" እያለች ረገመችው፡፡ እርሱም "አይዞሽ አትዘኚ" አላትና ወደ ሞተው ልጅ ቀርቦ በመስቀል ምልክት ካማተበበት በኋላ በፊቱ እፍ አለበት፡፡ የሞተውም ልጅ ድኖ ተነሣ፡፡ የሀገሪቱም ሰዎች እጅግ ደነገጡ፡፡ ሮምናም ደንግጣ " #እግዚአብሔር የሚሉት አምላክ አንተ ነህን" ብላ ጠየቀችው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም "በፍጹም እኔ አምላክ አይደለሁም፣ እኔ የእርሱ አገልጋዩና ሐዋርያው ነኝ እንጂ" አላት፡፡ ሮምናም ስለበደለቻቸው በደል ሁሉ መሪር ዕንባን እያለቀሰች ይቅር እንዲሏት ለመነቻቸው፡፡ እነርሱም አረጋጉዋት፡፡ ከሕዝቡም ውስጥ ብዙዎቹ በ #ጌታችን አመኑ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ሌሎች ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን እያደረገ ወንጌልን እየሰበከ ከጣዖት አገልጋዮች በቀር ሁሉንም አሳምኖ አጠመቃቸው፡፡ አገልጋዮችን ኤጲስቆጶሳትን፣ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ከሾመላቸው በኋላ ወደ ሌሎች አቅራቢያ አገሮች ሄደ፡፡

በመጨረሻም በከሃዲውና በጨካኙ በድምጥያኖስ ዘመን በጣዖት አምላኪዎች ተከሶ ለፍርድ ቀረበ፡፡ በፈላ ውኃ ካሠቃዩት በኋለ በፍጥሞ ደሴት አጋዙት፡፡ በዚያም ሳለ ራእዩን ተመልክቶ ጻፈው፡፡ ድምጥያኖስም ከተገደለ በኋላ ከግዞቱ ተመልሶ ሦስቱን መልእክታቱንና ቅዱስ ወንጌሉን ጽፏል፡፡ #ጌታችንም አስቀድሞ ሞትን እንደማይቀምስ ለዮሐንስ ቃል ገብቶለት ነበርና (ዮሐ 21፡22) ጥር 4 ቀን እንደ ኤልያስና ሄኖክ ሞትን እንዳያይ ወደ ብሔረ ሕያዋን ወስዶታል።

#ጌታችን ለዮሐንስ ያልነገረው እርሱም ያላስተማረው ምሥጢር የለም፡፡ ወንጌሉን መጻፍ ሲጀምር "በመጀመሪያ ቃል ነበረ፣ ቃልም በ #እግዚአብሔር ዘንድ ነበረ…" ብሎ የ #ጌታችን ነገር ተመራምሮ ለመድረስ ሲል በመሀል መልአኩን በዮርዳኖስ ባሕር ላይ ሲሄድ አገኘው፡፡ መልአኩም የዮርዳኖስን ባሕር በእንቁላል ቅርፊት እየጨለፈ ወደ ውጭ ሲያፈስ ተመለከተው፡፡ ዮሐንስም ተገርሞ "ምን ማድረግህ ነው" አለው፡፡ መልአኩም "የዮርዳኖስን ባሕር ቀድቼ እየደፋሁ ልጨርሰው ነው" ሲለው ዮሐንስም መልሶ "ታዲያ በእንቁላል ስባሪ ነውን?" አለው፡፡ መልአኩም "አዎን" አለው፡፡ ዮሐንስም "በከንቱ ደከምክ" አለው፡፡ ይህን ጊዜ መልአኩም መልሶ "አንተስ እንጂ ደግሞ የአምላክን መገኘት፣ አኗኗሩንም ተመራምረህ በጥበብ ለማግኘት ብለህ 'በመጀመሪያ ቃል ነበረ፣ ቃልም በ #እግዚአብሔር ዘንድ ነበረ..' ብለህ ጀምረህ የለምን? አንተ #ጌታን ተመራምረህ ካገኘህና ከደረስክበት እኔም የዮርዳኖስን ወንዝ በዚህ እንቁላል ቅርፊት ቀድቼ እጨርሰዋለሁ" አለው፡፡ ዮሐንስም ይህን ጊዜ ደንግጦ ዝቅ ብሎ "ስሙ ዮሐንስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ…" ብሎ ሀሳቡን ለወጠና ሌላ ታሪክ ቀጠለ፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ #ጌታችንን እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ በመከተሉ ክርስቲያኖችን ሁሉ ወክሎ #እመቤታችንን በአደራ የተቀበለ እርሱም ለእመቤታችን በአደራ የተሰጠ ሲሆን #እመቤታችንን ከወሰዳት በኋላ ለ16 ዓመት እየተንከባከበ ጠብቋታል፡፡ እናቱም በሕፃንነቱ ስለሞተች #እመቤታችን ናት እየተንከባከበች ያሳደገችው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በመልኩም ከ #ጌታችን ጋር ይመሳል ነበር፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ሥዕል የመሳል ተሰጥኦም ነበረው፡፡ #ጌታችን በተሰቀለበት ዘመን የነበረው ጢባርዮስ ቄሳር ልጁ በሽተኛ ነበር፡፡ የ #ጌታችንን የማዳን ሥራ እየሰማ እነ ጲላጦስም ስለ #ጌታችን የሚጽፉለትን ይሰማ ስለነበር ልጁን ከ #ጌታችን መቃብር ላይ እንዲያኖሩለት ላከው፡፡ ልጁም ፈጥኖ ተፈወሰለት፡፡ ጢባርዮስ ቄሳርም በልጁ መዳን ምክንያት የ #ጌታችንን ውለታ ማስቀመጥ ፈልጎ የ #ጌታችንን ሥዕሉን የሚሥልለትን ሲያጠያይቅ ዮሐንስን አገናኙት፡፡ ዮሐንስም #ጌታችንን ልክ በዕለተ ዓርብ እንደተሰቀለ አድርጎ በመሣል ለጢባርዮስ ቄሳር ሰጠው፡፡ ሲሥለውም በመጀመሪያ #ጌታችንን ልክ እንደተሰቀለ አድርጎ ራቁቱን ነበር የሳለው፡፡ ዮሐንስ የሳለው የ #ጌታችን ሥዕልም አፍ አውጥቶ "በመጀመሪያ አይሁድ በኢየሩሳሌም ራቁቴን ሰቀሉኝ፣ አሁን ደግሞ አንተ ድጋሚ በሮም ራቁቴን ትሰቅለኝን?" ብሎ ተናገረው፡፡ ዮሐንስም እጅግ ደንግጦ "እንዴት አድርጌ ልሳልህ?" ብሎ የሳለውን ሥዕል ቢጠይቀው ሥዕሉም "ከለሜዳ አልብሰህ ሳለኝ" አለው፡፡ ዮሐንስም እንዳለው ከለሜዳ አልብሶ ከሳለው በኋላ ሥዕሉን ትኩር ብሎ ተመልክቶ ቢስመው ከንፈሩ አንድ ቀን ተኩል ያህል ተጣብቆ ቆይቷል፡፡ ዛሬም ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የምትጠቀምባቸውን የ #ጌታችንን ስነ ስቅለት የሚያሳዩ ሥዕሎች መገኛቸው ይህ ወንጌላዊው ዮሐንስ የሳለው ሥዕል ነው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በተለያዩ ስሞች ይጠራል፦
በሕይወቱና በኑሮው ሁሉ #ጌታችንን ለመምሰል ይጥር ነበርና ጌታችንም እጅግ ይወደው ስለነበር "#ፍቁረ_እግዚእ" ተባለ፣ የታላቁ ያዕቆብ ታናሽ ወንድም ስለሆነና አባቱም ዘብድዮስ ስለሚባል "#ዮሐንስ_ወልደ_ዘብድዮስ" ተባለ፣ ለ #ጌታችን ባለው ቅናትና ከወንድሙ ጋር ሆነው ባሳዩት የኃይል ሥራ እንዲሁም የ #ጌታችንን አምላክነት በመግለጡ "#ወልደ_ነጎድጓድ" ተብሏል፡፡ ነገረ መለኮትን ከሌሎቹ በበለጠ ሁኔታ አስፍቶና አምልቶ በማስተማሩ "#ነባቤ_መነኮት ወይም #ታኦሎጎስ" ተብሏል። ኃላፊውንና መጻዒውን ጊዜ በራእዩ ስለገለጠ "#አቡቀለምሲስ" ተባለ፣ ይህም በግሪክኛ #ባለራእይ ማለት ነው፡፡ የጌታችንን መከራ መስቀሉን እያስታወሰ 70 ዘመን ሙሉ እያለቀሰ ስለኖረና ፊቱም በሀዘን ስለተቋጠረ "#ቁጹረ_ገጽ" ተብሏል፡፡

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው በቅዱስ ዮሐንስ ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_ሙሴ_ዘድባ

በዚህች ቀን የድባው አቡነ ሙሴ እረፍታቸው ነው። የትውልድ አገራቸው እስራኤል ልዩ ቦታው ቃና ዘገሊላ ነው። ጽንሰታቸውን ቅዱስ ሩፋኤል መጋቢት 8 ቀን ሲያበስር ልደታቸውን ደግሞ ቅዱስ ገብርኤል ታኅሣሥ 8 ቀን የመወለዳቸውን ብሥራት ተናግሯል፡፡ ሲወለዱ ሚካኤል ወገብርኤል በሰው አምሳል ተገልጠው "የ #እግዚአብሔር ሰው ሙሴ" ብለው ስም አወጡላቸው፡፡

በተወለዱም በ40ኛ ቀናቸው ከተጠመቁ በኋላ ቅዱስ ሚካኤል አቅፎ ይዟቸው #ጌታችን በቅዱሳን እጆቹ አቁርቧቸዋል፡፡ በእሳቸውም ምክንያት በዚያች ዕለት በቤተ ክርስቲያን የነበሩት ሰዎች ሁሉ ክቡራን በሆኑ በ #ጌታችን እጆች ቆርበዋል፡፡ የአቡነ ሙሴ አባታቸው ዮስጦስ ለሐዋርያው ናትናኤል አጎቱ ነው፡፡ እናታቸው ጵርስቅላ ጌታችን በሠርግ ቤት ተገኝቶ ውኃውን ወደ ወይን የለወጠለት የዶኪማስ ልጅ ናት፡፡

#ጌታችን ወደ ዶኪማስ ቤት ሠርግ ተጠርቶ የሄደው ዶኪማስ ናትናኤልን ‹‹ሠርጌን እንዲባርክልኝ #ጌታ_ኢየሱስን ከእናቱ ጋር ጥራልኝ›› ብሎት ነው፡፡ #ጌታችን በስብከቱ ‹‹ሕፃናትን ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ አትከልሏቸው›› ብሎ ብሎ ካቀፋቸውና
ካስተማረባቸው ሕፃናት አንዱ ይኽ አቡነ ሙሴ ናቸው፡፡ ጻድቁ ዋሻዎችን እየፈለፈሉ የቅዱሳን ሐዋርያትን ዐፅም በክብር ያስቀምጡ ነበር፡፡ የተሠወሩ አብያተ ክርስቲያናትን በማነጽ ወንጌልን በማስተማር ብዙ መከራ የተቀበሉ አባት ናቸው፡፡ በ #እግዚአብሔር ፈቃድ በግብፅ "ንጉሥ አንስጣስዮስ" ተብለው 40 ዓመት በንግሥና እና በድንግልና ኖረዋል፡፡

ከዚህም በኋላ በ #እግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ በመልአክም ምክር ዮናኒ የተባለውን ሌላ ሰው አንግሠው ወደ አስቄጥስ ገዳም ገብተው መነኮሱ፡፡ በገዳሙም በታላቅ ተጋድሎ ከኖሩ በኋላ የመጀመሪያው የኢትዮጵያ የእኛ ጳጳስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ሲያርፉ በቅዱስ አትናቴዎስ ተሹመው 2ኛው የኢትዮጵያ ጳጳስ ሆነው ‹‹አቡነ ሰላማ ካልዕ›› ተብለው ተሾመው ወደ አገራችን መጡ፡፡ ከመሾማቸው በፊት አባቶቻችን አቡነ አትናቴዎስን ‹‹ጳጳስ ይላኩልን›› ብለው መልእክት ሲልኩባቸው አቡነ አትናቴዎስም ወደ አስቄጥስ ገዳም በመሄድ #እግዚአብሔርን በጸሎት ቢጠይቁት የታዘዘ መልአክ መጥቶ ‹‹የ #እግዚአብሔር ሰው ሙሴን ላክላቸው›› አላቸው፡፡ መነኮሳቱም ሁሉ እንዲሁ አሉ፡፡ ከዚህም በኋላ ሲሾሙ ሚካኤልና ገብርኤል በወርቅ ወንበር ላይ አስቀምጠዋቸው ‹‹ይገባዋል ይገባዋል›› ብለው ቅብአ ክህነት ቀብተዋቸዋል (ጵጵስና ሾመዋቸዋል፡፡) አቡነ ሙሴም ከተሾሙ በኋላ 14000 መነኮሳትን አስከትለው ወደ ቅድስት አገራችን መጡ፡፡ አቡነ ሙሴ ንግሥናቸውን ትተው ወደ ኢትዮጵያ መተው 16 ፍልፍል ቤተመቅደሶችን የሠሩ ሲሆን 8ቱ የተሰወሩ ናቸው፡፡

በገዳማቸው በቅድስቱ ውስጥ ጥልቀቱ የማይታወቅ እጅግ ጥልቅ የሆነ ጉድጓድ አለ፡፡ በውስጡም ስውራኑ አብያተ ክርስቲያናት ይገኙበታል፡፡ ከአንድ ወጥ ድንጋይ የተቀረጸውና ፍልፍል የሆነው የገዳማቸው የቤተልሔሙ ስፋት ሜትር ከሃያ ሲሆን ጣራው እንደ አቡነ አሮን ክፍት ሆኖ ሳለ ዝናብ ግን አይገባበትም፡፡ ዝናብ የማያስገባው የቀዳዳው ስፋት አንድ ሜትር በአንድ ሜትር ነው፡፡ ጻድቁ በሀገራችንም ዕፁብ ድንቅ የሆኑ ብዙ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናትን በማነጽና ወንጌልን በማስተማር ብዙ ደክመዋል፡፡ በተለይም በዋናነት የሚታወቁት በሰሜን ወሎ አውራጃ ወልድያ ወረዳ መቄት ልዩ ቦታው ገረገራ የሚገኘው ‹‹አዲስ አንባ ዋሻ መድኃኔዓለም›› እና መጀመሪያ እንደመጡ ያረፉባት ‹‹ድባ ማርያም›› ይጠቀሳሉ፡፡

ይህችውም ድባ ማርያም ገዳም ታላቁ አባት አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ የመነኮሱባት ናት፡፡ ጻድቁ አቡነ ሙሴ መስከረም 4 ቀን ጌታችን ቃልኪዳን ሲገባላቸው እነዚህን ሁለት ገዳማቸውን ‹‹እንደ አስቄጥስ ገዳም እንደ አቡነ እንጦንስ ማኅበር ይሁኑልህ›› ብሏቸዋል፡፡ በገዳማቸው ከሚኖሩት ቅዱሳን ውስጥ 400 ወንዶች መነኮሳትና 200 ሴቶች መነኮሳያት እንደተሰወሩ መጽሐፈ ገድላቸው ይናገራል፡፡

ጻድቁ ሌላው ለየት የሚያደርጋቸው ነገር ቢኖር ገና በእናቷ ማኅፀን ሳትፀነስ የቅድስት አርሴማን ጽላት ያሠሩላት መሆናቸው ነው፡፡ ቁመቱ 2 ሜትር ከ70 የሆነ ግሩም ቤተ መቅደስም ፈልፍለው አንጸውላታል፡፡ #ጌታችንም የሰማዕቷን ጽናትና ረድኤት ከቦታው እንደማይለይባቸው ቃል ገብቶላቸዋል፡፡ በቃል ኪዳናቸው የታመኑትን ልጆቻቸውን መተትና መርዝ አይጎዳቸውም፡፡ ይህም #ጌታችን የሰጣቸው ልዩ ቃልኪዳናቸው ነው፡፡ ጻድቁ እንደ አቡነ ዘርዐ ቡሩክ 12 ክንፍ የተሰጣቸው ታላቅ የምሕረት አባት ናቸው፡፡

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጻድቁ አቡነ ሙሴ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ትድረሰን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ነቢይ_ኢያሱ_ወልደ_ነዌ

ኢያሱ ማለት የቃሉ ትርጉም መድኃኒት ማለት ነው፡፡ ኢያሱ መባሉ ስለሁለት ነገር ነው አሜሊቃዊያን ድል አድርጎ እስራኤልን ምድረ ርስት እንዲወርሱ አድርጎልና ሁለተኛው ኢያሱ ለ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ምሳሌ እንዲሆን አስቀድሞ #ጌታ ያውቃልና ይህም ኢያሱ አሕዛብን ድል አድርጎ ምድረ ርስት እንዳስገባቸው የሁላችን #ጌታ_ኢየሱስ_ክርስቶስ ዲያቢሎስን ድል አድርጎ መንግስቱን አውርሶናልና ኢያሱ በ #ጌታችን ይመሰላል፡፡

ኢያሱ ነቢይ የተወለደው በምድረ ግብጽ በባርነት ከነበሩ እሥራኤላውያን ሲሆን የቀደመ ስሙ አውሴ ይባላል:: ዘመኑ #‎እግዚአብሔር ሕዝቡን ከ215 ዓመታት ባርነት ሊያወጣ የተቃረበበት ነውና ሙሴ ነቢይ ከምድያም ሲመለስ ከመረጣቸው ተከታዮቹ ዋነኛው ኢያሱ ነበር:: እሥራኤል ከባርነት ሲወጡ ሙሴ 80 ዓመቱ ኢያሱ ደግሞ 40 ዓመቱ ነበር። ሕዝቡ ልበ ደንዳና አልታዘዝ ባይ ነበርና ለአርባ ቀናት ብቻ የታሠበላቸውን መንገድ አርባ ዓመታት እንዲሆን አደረጉት:: በዚህ ጊዜ ኢያሱ ከመምህሩ ከሙሴና ከሕዝቡ አልተለየም::

ሊቀ ነቢያት ሙሴ ‎ደብረ ናባው ላይ ባረፈ ጊዜ ሕዝቡን ካህናቱንና ታቦተ ጽዮንን ተረከበ:: በዚህ ወቅትም እድሜው ሠማንያ ዓመት ነበር፡፡ #እግዚአብሔርም በእስራኤል ላይ ሾመው፡፡ ሕዝቡንም በትጋት ያገለግል ነበር፡፡ በድንቅ ተዓምራት ዮርዳኖስን ከፍሎ አሻገረ የኢያሪኮን ቅጥር አፈረሰ ጠላቶቹን ድል ነስቶ ምድረ ርስት ከነአንን በ #እግዚአብሔር በኢያሱ መሪነት እንድወርሱ አድርጎል፡፡

ታላቁ ነቢይ ኢያሱ ግን በተወለደ በ120 ዓመቱ መስከረም 3 ቀን በእዚች ዕለት በወገኖቹ መካከል ዐርፎ በያዕቆብ መቃብር ተቀበረ:: እሥራኤልም ለሠላሳ ቀናት አለቀሱለት::
#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን በረከቱ ይደርብን እኛንም በቅዱሱ ምልጃ ይማረን ለዘላለሙ አሜን፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አባ_መቃርስ_ሊቀ_ዻዻሳት

ዳግመኛም በዚህች ቀን ቅዱስ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ መቃርስ አረፈ። እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ከቍጥራቸው ውስጥ ነው።

ይህም አባት ከታናሽነቱ ጀምሮ በገድል የተጠመደ ሆነ የምንኲስናንም ልብስ ሊለብስ ወዶ ወደ አስቄጥስ ገዳም ወጣ። በዚያም በመጀመሪያው አባት በአባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መነኰሰ በምንኲስና ያለውንም ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለ።

እርሱም ሁልጊዜ መጻሕፍትን የሚያነብና ትርጓሜያቸውንም የሚያስረዳ ሁኗልና በትሩፋት ስራ ከፍ ከፍ ባለ ጊዜ ቅስና ተሾመ። ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ ሚካኤልም በአረፈ ጊዜ ኤጲስቆጶሳቱ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔዱ።

ከእርሳቸውም ጋር ሃይማኖታቸው የቀና ብዙዎች አዋቂዎች ካህናት ነበሩ በአስቄጥስ ገዳም ከሚኖሩ ከታላላቅ መነኰሳትም ጋራ ስብሰባ አድርገው ለዚች ለከበረች ሹመት ስለሚገባው ሰው እየመረመሩ ብዙ ቀኖች ተቀመጡ።

ከዚህም በኋላ የተሻለና ለዚች ለከበረች ሹመት የሚገባ ይህን አባ መቃርስን አግኝተው ሊቀ ጵጵስና ሊሾሙት ሁሉም በአንድ ምክር ተስማው። ስለ ትሩፋቱና ስለ ተጋድሎው በአስቄጥስ ገዳም የሚኖሩ ብዙ መነኰሳት ምስክሮች ሁነዋልና ይዘውትም ሊሔዱ ያለ ፍቃዱ ይዘው አሰሩት እርሱ ግን እንዲህ እያለ ይጮህ ነበር።

እኔ ለዚች ለከበረች ሹመት የማልገባ ነኝ እናቴ ሁለት ባሎችን አግብታ ስለነበር ይህንንም ያለው እንዲተዉት እንጂ እናቱ ግን በአንድ ባል ብቻ የኖረች ሌላ የማታውቅ ንጽሕት እንደሆነች ስለርሷ ብዙዎች ምስክሮች ሁነዋልና። ስለዚህ እሊቀ የተናገረውን ምክንያት አልተቀበሉትም።

ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ወስደው ሊቀ ጵጵስና ሾሙት ከዚያም ወደ ምስር አውጥተው በመዓልቃ በሚገኘው አምላክን በወለደች በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሹመቱ ደብዳቤ በዮናኒ በቅብጥ በአረብ ቋንቋ ተነበበች።

ከዚህም በኋላ በሹመቱ ወራት በጎ ስራ ትሩፋትን ተጋድሎውን አብዝቶ የሚሰራ ሆነ ። ሁል ጊዜም ለህዝቡ #እግዚአብሔርን እንዲፈሩ ያስተምራቸዋል ስለ ነፍሳቸውም ድኀነት ይገሥጻቸው ነበር።

በሹመቱ ወራትም ከራሱ ከሚገባው ከግብሩ ለቤተ ክርስቲያን ይሰጣል ለድኆችና ለችግረኞችም ይመጸውታል እንጂ ከቤተ ክርስቲያን ገንዘብ ምንም ምን አልወሰደም። በሹመቱም ሃያ ሰባት ዓመት ኖረ #እግዚአብሔርንም አገልግሎ ደስ አሰኝቶ በሰላም በፍቅር ሳለ አረፈ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ለዘላለሙ ከእኛ ጋር ትኑር አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኅ_መስከረም_4#ከገድላት_አንደበት)
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#መስከረም_4_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ጢሞቴዎስ 3
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ ማንም ኤጲስ ቆጶስነትን ቢፈልግ መልካምን ሥራ ይመኛል የሚለው ቃል የታመነ ነው።
² እንግዲህ ኤጲስ ቆጶስ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል፤ የማይነቀፍ፥ የአንዲት ሚስት ባል፥ ልከኛ፥ ራሱን የሚገዛ፥ እንደሚገባው የሚሰራ፥ እንግዳ ተቀባይ፥ ለማስተማር የሚበቃ፥
³ የማይሰክር፥ የማይጨቃጨቅ ነገር ግን ገር የሆነ፥ የማይከራከር፥ ገንዘብን የማይወድ፥
⁴ ልጆቹን በጭምትነት ሁሉ እየገዛ የራሱን ቤት በመልካም የሚያስተዳድር፤
⁵ ሰው ግን የራሱን ቤት እንዲያስተዳድር ባያውቅ፥ የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን እንዴት ይጠብቃታል?
⁶ በትዕቢት ተነፍቶ በዲያብሎስ ፍርድ እንዳይወድቅ፥ አዲስ ክርስቲያን አይሁን።
⁷ በዲያብሎስ ነቀፋና ወጥመድም እንዳይወድቅ፥ በውጭ ካሉት ሰዎች ደግሞ መልካም ምስክር ሊኖረው ይገባዋል።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ጴጥሮስ 5
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁹ በዓለም ያሉት ወንድሞቻችሁ ያን መከራ በሙሉ እንዲቀበሉ እያወቃችሁ በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት።
¹⁰ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዘላለም ክብሩ የጠራችሁ የጸጋ ሁሉ አምላክ ለጥቂት ጊዜ መከራን ከተቀበላችሁ በኋላ ራሱ ፍጹማን ያደርጋችኋል ያጸናችሁማል ያበረታችሁማል።
¹¹ ለእርሱ ክብርና ኃይል እስከዘላለም ድረስ ይሁን፤ አሜን።
¹² እየመከርኋችሁና የምትቆሙባት ጸጋ እውነትኛ የእግዚአብሔር ጸጋ እንድትሆን እየመሰከርሁላችሁ፥ የታመነ ወንድም እንደ ሆነ በቈጠርሁት በስልዋኖስ እጅ በአጭሩ ጽፌላችኋለሁ።
¹³ ከእናንተ ጋር ተመርጣ በባቢሎን ያለች ቤተ ክርስቲያን ልጄም ማርቆስ ሰላምታ ያቀርቡላችኋል።
¹⁴ በፍቅር አሳሳም እርስ በርሳችሁ ሰላምታ ተሰጣጡ። በክርስቶስ ላላችሁ ለሁላችሁ ሰላም ይሁን። አሜን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 7
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁴⁴ እንዳየው ምስል አድርጎ ይሠራት ዘንድ ሙሴን ተናግሮ እንዳዘዘው፥ የምስክር ድንኳን ከአባቶቻችን ዘንድ በምድረ በዳ ነበረች፤
⁴⁵ አባቶቻችንም ደግሞ በተራ ተቀብለው እግዚአብሔር በፊታቸው ያወጣቸውን የአሕዛብን አገር በያዙት ጊዜ ከኢያሱ ጋር አገቡአት፥ እስከ ዳዊት ዘመንም ድረስ ኖረች።
⁴⁶ እርሱም በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ አግኝቶ ለያዕቆብ አምላክ ማደሪያን ያገኝ ዘንድ ለመነ።
⁴⁷ ነገር ግን ሰሎሞን ቤት ሠራለት።
⁴⁸-⁵⁰ ነገር ግን ነቢዩ፦ ሰማይ ዙፋኔ ነው ምድርም የእግሬ መረገጫ ናት፤ ለእኔ ምን ዓይነት ቤት ትሠራላችሁ? ይላል ጌታ፥ ወይስ የማርፍበት ስፍራ ምንድር ነው? ይህንስ ሁሉ እጄ የሠራችው አይደለምን? እንዳለ፥ ልዑል የሰው እጅ በሠራችው አይኖርም።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#መስከረም_4_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ወወሀብኮሙ ትእምርተ ለእለ ይፈርሁከ። ከመ ያምሥጡ እምገጸ ቅስት። ወይድኀኑ ፍቁራኒከ"። መዝ 59፥4-5።
"ከቀስት ፊት ያመልጡ ዘንድ፥ ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው። ወዳጆችህ እንዲድኑ በቀኝህ አድን፥ አድምጠኝም"።መዝ 59፥4-5።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#መስከረም_4_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ዮሐንስ 10
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ወደ በጎች በረት በበሩ የማይገባ በሌላ መንገድ ግን የሚወጣ እርሱ ሌባ ወንበዴም ነው፤
² በበሩ የሚገባ ግን የበጎች እረኛ ነው።
³ ለእርሱ በረኛው ይከፍትለታል፤ በጎቹም ድምፁን ይሰሙታል፥ የራሱንም በጎች በየስማቸው ጠርቶ ይወስዳቸዋል።
⁴ የራሱንም ሁሉ ካወጣቸው በኋላ በፊታቸው ይሄዳል፥ በጎቹም ድምፁን ያውቃሉና ይከተሉታል፤
⁵ ከሌላው ግን ይሸሻሉ እንጂ አይከተሉትም፥ የሌሎችን ድምፅ አያውቁምና።
⁶ ኢየሱስ ይህን ምሳሌ ነገራቸው፤ እነርሱ ግን የነገራቸው ምን እንደ ሆነ አላስተዋሉም።
⁷ ኢየሱስም ደግሞ አላቸው፦ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ እኔ የበጎች በር ነኝ።
⁸ ከእኔ በፊት የመጡ ሁሉ ሌቦችና ወንበዴዎች ናቸው፤ ዳሩ ግን በጎቹ አልሰሙአቸውም።
⁹ በሩ እኔ ነኝ፤ በእኔ የሚገባ ቢኖር ይድናል፥ ይገባልም ይወጣልም መሰማርያም ያገኛል።
¹⁰ ሌባው ሊሰርቅና ሊያርድ ሊያጠፋም እንጂ ስለ ሌላ አይመጣም፤ እኔ ሕይወት እንዲሆንላቸው እንዲበዛላቸውም መጣሁ።
¹¹ መልካም እረኛ እኔ ነኝ። መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል።
¹² እረኛ ያልሆነው በጎቹም የእርሱ ያልሆኑ ሞያተኛ ግን ተኵላ ሲመጣ ባየ ጊዜ በጎቹን ትቶ ይሸሻል፤ ተኵላም ይነጥቃቸዋል በጎቹንም ይበትናቸዋል።
¹³ ሞያተኛ ስለ ሆነ ለበጎቹም ስለማይገደው ሞያተኛው ይሸሻል።
¹⁴-¹⁵ መልካም እረኛ እኔ ነኝ፥ አብም እንደሚያውቀኝ እኔም አብን እንደማውቀው የራሴን በጎች አውቃለሁ የራሴም በጎች ያውቁኛል፤ ነፍሴንም ስለ በጎች አኖራለሁ።
¹⁶ ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምፄንም ይሰማሉ፥ አንድም መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ።
¹⁷ ነፍሴን ደግሞ አነሣት ዘንድ አኖራለሁና ስለዚህ አብ ይወደኛል።
¹⁸ እኔ በፈቃዴ አኖራታለሁ እንጂ ከእኔ ማንም አይወስዳትም። ላኖራት ሥልጣን አለኝ ደግሞም ላነሣት ሥልጣን አለኝ ይህችን ትእዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ።
¹⁹ እንግዲህ ከዚህ ቃል የተነሣ በአይሁድ መካከል እንደ ገና መለያየት ሆነ።
²⁰ ከእነርሱም ብዙዎች፦ ጋኔን አለበት አብዶአልም፤ ስለ ምንስ ትሰሙታላችሁ? አሉ።
²¹ ሌሎችም፦ ይህ ጋኔን ያለበት ሰው ቃል አይደለም፤ ጋኔን የዕውሮችን ዓይኖች ሊከፍት ይችላልን? አሉ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #ሠለስቱ_ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የሐዋርያው የቅዱስ ዮሐንስ የልደት በዓል እና የብፁዕ አባ ሙሴ ዕረፍት፣ የቅዱስ ኢያሱ ወልደ ነዌ የዕረፍት በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#መስከረም_5

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም አምስት በዚች ቀን #ቅድስት_ሶፊያ_ሰማዕት ከሁለት ልጆቿ ጋር በሰማዕትነት አረፈች፣ #አቡነ_አሮን_መንክራዊ እረፍት ነው፣ #ቅዱስ_ማማስ_ሰማዕት በሰማዕትነት አረፈ፣ ኢትዮጵያዊው ጻድቅ #አፄ_ልብነ_ድንግል እረፍቱ ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ሶፊያ_ሰማዕት

መስከረም አምስት በዚች ቀን የከበረች ሶፊያ ከሁለት ልጆቿ አክሶስናና በርናባ ከሚባሉት ጋር በሰማዕትነት ሞተች ።

ዘመነ ሰማዕታት በሚል በሚታወቀው 3ኛው መቶ ክ/ዘመን ብዙ ቅዱሳት እናቶቻችን ስለ ፍቅረ ክርስቶስ አንገታቸውን ሰጥተዋል:: አንዳንዶቹ ደግሞ ሕይወታቸው እጅግ የሚያምር ነበር:: ከእነዚህ ቅዱሳት እናቶቻችን አንዷ ዛሬ የምናከብራት ሐጊያ ሶፊያ ናት::

በዚህ ስም ከሚጠሩት አንዷ ስትሆን በቀደመ ሕይወቷ #ክርስቶስን አታውቅም ነበር:: ጣዖትን የሚያመልኩ ወላጆቿ አሳድገው አጋቧት:: ከትዳሯም 2 ቡሩካት ሴቶች ልጆች ወልዳለች:: ስማቸውም አክሶስናና በርናባ ይባላል:: ልጆቿ ልብ እያገኙ በሔዱ ጊዜ ቅድስት ሶፍያ ስለ እውነተኛው አምላክ ትመራመር ገባች::

በወቅቱ የነበሩ ብዙ ሃይማኖቶችን መዘነች:: ከክርስትና በቀር ግን ሌሎቹ ሚዛን እንደማይመቱም አስተዋለች:: "እውነተኛው አምላክ ሆይ! ምራኝ እርዳኝም" ስትል ጸለየች:: #መድኃኔዓለም ለጠሩት አያሳፍርምና ፈጥኖ በጐውን ጐዳና አሳያት።

ድኅነት ለልጆቿም ይሆን ዘንድ ሁለቱንም ጠርታ ስለ ክርስትና አማከረቻቸው:: ደስ ብሏቸው ተቀበሏት:: እርሷም ጊዜ ሳታጠፋ ወደ ዻዻስ ሒዳ ማሕተመ ክርስትና: ሃብተ ውልድናን ትቀበል ዘንድ ከልጆቿ ጋር ተጠመቀች:: በቅድስናና ደስ በሚያሰኝ አኗኗርም እስከ መከራ ቀን ቆየች::

የመከራ ጊዜ ሲደርስም ልጆቿን ጠርታ "ስለ ክርስቶስ ፍቅር እንሙት" አለቻቸው:: ቡሩካቱ አክሶስናና በርናባም ደስ እያላቸው "እሺ" አሏት:: ወዲያውም በመኮንኑ ፊት ቀርበው ክርስቶስን ከመካድና ከስቃይ ሞት የትኛውን እንደሚመርጡ ቢጠየቁ እነርሱ መሞትን መረጡ:: ወደ እሥር ቤትም ከተቷቸው::

ቅድስት ሶፍያ 2 ልጆቿ ይጸኑላት ዘንድ አዘውትራ ገድለ ሰማዕታትን እና ክብራቸውን ትተርክላቸው ነበር:: በተለይ የታላቁዋን አንጌቤናይት (እመቤት) ሶፍያንና የ3 ልጆቿን (ዺስጢስ: አላዺስና አጋዺስ) ተጋድሎ እየነገረች ታጸናቸው ነበር።

ከእሥር በኋላ ግርፋት ታዞባቸው እናት ራቁቷን ስትገረፍ መልአክ ወርዶ ሲጋርዳት ልጆች በማየታቸው ደስ አላቸው:: ቅድስት ሐጊያ ሶፍያና 2 ልጆቿ እጅግ የበዛ ስቃይን ስለ ቀናች እምነት ተቀበሉ:: ምላስ እስከ መቆረጥም ደረሱ:: በመጨረሻ ግን በዚህች ቀን ተገድለው አክሊለ ሰማዕታትን ገንዘብ አደረጉ

የመከራ ዘመን ካለፈ በኋላ ታላቁ ንጉሥ ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ የሁሉን ቅዱሳን ቤት ሠርቶ የእርሷን በመዘንጋቱ ለራሱ ባሰራው ቤተ መንግስት ላይ ተአምር ታይቷል። ለ3 ያህል ጊዜ ስሙን ሲያስቀርጽ መልአክ እየወረደ ይፍቀው የሶፍያንም ስም ይጽፈው ነበር።

በመጨረሻም ንጉሡ ልጁን እስከ መገበር ደርሶ ቤተ መንግስቱ የቅድስት ሶፍያና የ2 ልጆቿ ቤተ ክርስቲያን ለመሆን በቅቷል:: ምንም ለ3 ጊዜያት ያህል ሙሉ እድሳት ቢደረግለትም ዛሬ አሕዛብ የያዙትን ይህንን ቅርስ ንጉሡ የሠራው ከ1700 ዓመታት በፊት ነው።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_አሮን_መንክራዊ

በዚህች ቀን አቡነ አሮን መንክራዊ ዕረፍታቸው ነው፡፡ አቡነ አሮን ወላጅ አባታቸው የላስታው ጻድቁ ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል ናቸው፡፡ እናታቸው አመተ ማርያም ይባላሉ፡፡ የላስታ ነገሥታት የዘር ሐረጋቸው ከንጉሥ ሰሎሞን ዘር ሲያያዝ የመጣ ነው፡፡

ከ10ኛው እስከ 13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን (920-1253 ዓ.ም ገደማ) በላስታ ቡግና ምድር የነገሡ የላስታ ቡግና ተወላጅ የሆኑ የኢትዮጵያ ቅዱሳን ነገሥታት የንግሥናቸው መጠሪያ ‹‹የዛጉዌ ሥርወ መንግሥት›› ወይም ‹‹የላስታ መንግሥት›› በመባል ይታወቃል፡፡ የንጉሥ ሰሎሞን ዘር የሆነው መራ ክርስቶስ 3 ልጆችን ወለደ፡፡ እነርሱም ጠንጠውድም፣ ግርማ ስዩምና ዣን ስዩም ናቸው፡፡ ጠንጠውድም ገብረ መስቀልን ወለደ፣ ገብረ መስቀልም አቡነ አሮንን ወለደ፣ ግርማ ስዩም ይምርሐነ ክርስቶስን ወለደ፣ ዣን ስዩም ደግሞ ገብረ ማርያምንና ላሊበላን ወለደ፡፡ ገብረ ማርያምም ነዓኲቶ ለአብን ወለደ፡፡ እነዚህ ቅዱሳን ነገሥታት እንደ መልከጼዴቅ (ዘፍ14፡18) ክህነትን ከንግሥና፣ ቅድስናን ከንጽሕና ጋር አንድ አድርገው በመያዝ #እግዚአብሔርንም ሕዝብንም በቅድስናና በንጽሕና አገልግለው አልፈዋል፡፡

አቡነ አሮን ግን ገና በ7 ዓመታቸው ነው ዓለምን ፍጹም ንቀው በአቡነ በጸሎተ ሚካኤል እጅ የመነኮሱት፡፡ በ16 ዓመታቸውም ዋልድባ ገዳም ገብተዋል፡፡ ነሐሴ 5 ቀን ገና ሲወለዱ ሙት አስነሥተዋል፡፡ በሀገራችን እየተዘዋወሩ ወንጌልን ሲሰብኩ የሸዋው ንጉሥ አንኮበር ድረስ ጠርቷቸው ሲሔዱ አዋሽ ወንዝ ሞልቶባቸው አገኙት፡፡ ሲሻገሩም ዳዊታቸውን ወስደባቸው፡፡ ‹‹ልጆቼን አመነኮስክብኝ›› በሚል ሰበብ ንጉሡ 7 ዓመት በግዞት አስሮ አስቀመጣቸው፡፡ ነገር ግን ከ7 ዓመት በኋላ አቡነ አሮን ተመልሰው በአዋሽ ወንዝ ሲመጡ መልአክ መጣና ‹‹መቋሚያህን ወደ ወንዙ ላክ›› አላቸው፡፡ መቋሚያቸውንም ቢልኩ ከ7 ዓመት በፊት ወደ ወንዙ ገብቶባቸው የነበረውን ዳዊታቸውን ይዘው አወጡ፡፡ ዳዊቱም በውኃው አልራሰም ነበር፣ ይልቁንም አቧራውን አራግፈው ፈጣሪያቸውን አመስግነው ዳዊታቸውን ይዘው ሄደዋል፡፡ ያ ዳዊታቸው ዛሬም ድረስ በጋይንት አበርጉት ቅዱስ ሚካኤል ይገኛል፡፡

ሰሜን ወሎ መቄት ወረዳ ውስጥ የሚገኘው እጅግ አስደናቂ ገዳማቸው ፍልፍል ዋሻ ሲሆን ጣራው ክፍት ነው፣ ክፍት በሆነው ጣራ በኩል ፀሐይ ሲገባ ስለሚያቃጥል ጥላ ይይዛሉ ነገር ግን የጻድቁ ግዝት ስላለበት ዝናብ ወደ መቅደሱ ፈጽሞ አይገባም፡፡ እጅግ አስደናቂ ነው፡፡ አቡነ አሮን በዋድላ ሜዳ አልፈው ሲሄዱ አንችም ሜዳ ላይ እንደ ኢያሱ ፀሐይን በቃላቸው ገዝተው አቁመዋታል፡፡

ከታች ጋይንት ተነሥተው መንገድ ሲሄዱ በሰንበት ቀን በሬ ጠምዶ ሲያርስ የነበረን ገበሬ ‹‹ለምን በሰንበት ታርሳለህ?›› ቢሉት ‹‹ምቀኛ መነኩሴ›› ብሎ በጅራፉ ቢገርፋቸው በሬዎቹ ግን ፈጽሞ አልንቀሳቀስ ብለው ቆመዋል፡፡ በዚህ የተናደደው ገበሬም አቡነ አሮንን መሬት ላይ ጥሎ ገረፋቸው፡፡ እሳቸውም ተነሥተው ሲሄዱ ዛፎች ተነቅለው እየተከተሏቸው፣ ቃልም አውጥተው በሰው አንደበት አመስግነዋቸዋል።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጻድቁ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ማማስ_በሰማዕት

በዚህችም ቀን ቅዱስ ማማስ በሰማዕትነት ሞተ የአባቱ ስም ቴዎዶስዮስ የእናቱም ያኖች ናቸው። በንጉሥ ዑልያኖስ ዘመንም ስለ ሃይማኖታቸው ይዘው አሠሩአቸው በእሥር ቤትም ሳሉ አረፉ።

አንዲት ክርስቲያናዊት ሴት መጥታ ይህን ሕፃን ወስዳ እንደ ልጅዋ አድርጋ አሳደገችው። ስሙንም ማማስ ብላ ሰየመችው ትርጓሜውም። የሙት ልጅ ማለት ነው አባትና እናት የለውምና።
ዐሥራ ስምንት ዓመትም በሆነው ጊዜ ወደ ከሀዲው ገዢ ሒደው ክርስቲያን ነው ብለው ወነጀሉት ይዘውም በበትሮች ደበደቡት በአንገቱም የሚከብድ ሸክም ታላቅ የዓረር ደንጊያ አንጠልጥለው ከባሕር ውስጥ ጣሉት። ክብር ይግባውና በ #እግዚአብሔር ኃይል ከባሕር ስጥመት ዳነ ወጥቶም በዋሻ ውስጥ ተሠውሮ ከጎሽ ወተትን እየተመገበ ተቀመጠ።

ከዚህም በኃላ ሁለተኛ ያዙት ወስደውም ከሚነድ እሳት ውስጥ ጨመሩት ክብር ይግባውና #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስም አዳነው። ዳግመኛም ተነጣጥቀው እንዲበሉት አንበሶችን በላዩ ሰደዱ በ #እግዚአብሔርም ኃይል በአንበሳ ላይ ተቀመጠ።

ከዚህም በኃላ ብዙ አሠቃዩት ሕዋሳቶቹ እስቲለያዩና የሆድ ዕቃው እስቲፈስ ጎተቱት ተጋድሎውንና ምስክርነቱን በዚህ ፈጽሞ የሰማዕትነት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም እኛንም በቅዱስ ማማስ ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አፄ_ልብነ_ድንግል

በዚህችም ቀን #እግዚአብሔርን የሚወድ ሃይማኖቱ የቀና ደግ ጻድቅ የኢትዮጵያ ንጉሥ ልብነ ድንግል አረፈ።

እኒህ ንጉሥ ኢትዮዽያን ለዓመታት (ከ1500 እስከ 1532 ዓ.ም) ቢያስተዳድሩም 15ቱ ዓመት ያለቀው በስደት ነው። ከደጋጉ አፄ ናዖድና ንግሥት ወለተ ማርያም ተወልደው በሥርዓቱ አድገው ቢነግሡም በክፉ መካሪዎች ጠንቅዋይ ወደ ቤታቸው ገብቶ ሃገሪቱን ለመከራ ዳርጓታል።

ዛሬም ድረስ ጠባሳው ያለቀቀው የግራኝ ወረራ ለ15 ዓመታት ሃገሪቱን ያለ ካህንና ቤተ ክርስቲያን አስቀርቷት ነበር። ብዙ ክርስቲያኖችም ሰልመው ቀርተዋል። አፄ ልብነ ድንግል ግን ደብረ ዳሞ ገዳም ውስጥ ገብተው ንስሃ ጀመሩ አለቀሱ ተማለሉ።

እመቤታችን ተገልጣም "ይቅርታን በነፍስህ እንጂ በሥጋህ አታገኝም" አለቻቸው። እርሳቸውም ሱባኤውን ቀጥለው ስብሐተ ፍቁርን፣ መልክአ ኤዶምን የመሰሉ መጻሕፍትን ደርሰው በዚህች ቀን ዐርፈዋል። እኛ ክርስቲያኖችም እናከብራቸዋለን።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_መስከረም_5#ከገድላት_አንደበት እና #ዝክረ_ቅዱሳን)
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#መስከረም_5_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ቆሮንቶስ 11
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁷ ነገር ግን በምትሰበሰቡበት ጊዜ ለሚከፋ እንጂ ለሚሻል ስላልሆነ ይህን ትእዛዝ ስሰጥ የማመሰግናችሁ አይደለም።
¹⁸ በመጀመሪያ ወደ ማኅበር ስትሰበሰቡ በመካከላችሁ መለያየት እንዳለ እሰማለሁና፥ በአንድ በኩልም አምናለሁ።
¹⁹ በእናንተ ዘንድ የተፈተኑት እንዲገለጡ በመካከላችሁ ወገኖች ደግሞ ሊሆኑ ግድ ነውና።
²⁰ እንግዲህ አብራችሁ ስትሰበሰቡ የምትበሉት የጌታ እራት አይደለም፤
²¹ በመብላት ጊዜ እያንዳንዱ የራሱን እራት ይበላልና፥ አንዱም ይራባል አንዱ ግን ይሰክራል።
²² የምትበሉባቸውና የምትጠጡባቸው ቤቶች የላችሁምን? ወይስ የእግዚአብሔርን ማኅበር ትንቃላችሁን አንዳችም የሌላቸውን ታሳፍራላችሁን? ምን ልበላችሁ? በዚህ ነገር ላመስግናችሁን? አላመሰግናችሁም።
²³ ለእናንተ ደግሞ አሳልፌ የሰጠሁትን እኔ ከጌታ ተቀብያለሁና፤
²⁴ ጌታ ኢየሱስ አልፎ በተሰጠበት በዚያች ሌሊት እንጀራን አንሥቶ አመሰገነ፥ ቆርሶም፦ እንካችሁ ብሉ፤ ይህ ስለ እናንተ የሚሆን ሥጋዬ ነው፤ ይህን ለመታሰቢያዬ አድርጉት አለ።
²⁵ እንደዚሁም ከእራት በኋላ ጽዋውን ደግሞ አንሥቶ፦ ይህ ጽዋ በደሜ የሚሆን አዲስ ኪዳን ነው፤ በጠጣችሁት ጊዜ ሁሉ ይህን ለመታሰቢያዬ አድርጉት አለ።
²⁶ ይህን እንጀራ በበላችሁ ጊዜ ሁሉ፥ ይህንም ጽዋ በጠጣችሁ ጊዜ ሁሉ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ሞቱን ትናገራላችሁና።
²⁷ ስለዚህ ሳይገባው ይህን እንጀራ የበላ ወይም የጌታን ጽዋ የጠጣ ሁሉ የጌታ ሥጋና ደም ዕዳ አለበት።
²⁸ ሰው ግን ራሱን ይፈትን፥ እንዲሁም ከእንጀራው ይብላ ከጽዋውም ይጠጣ፤
²⁹ ሳይገባው የሚበላና የሚጠጣ የጌታን ሥጋ ስለማይለይ ለራሱ ፍርድ ይበላልና፥ ይጠጣልምና።
³⁰ ስለዚህ በእናንተ ዘንድ የደከሙና የታመሙ ብዙዎች አሉ አያሌዎችም አንቀላፍተዋል።
³¹ ራሳችንን ብንመረምር ግን ባልተፈረደብንም ነበር፤
³² ነገር ግን በተፈረደብን ጊዜ ከዓለም ጋር እንዳንኮነን በጌታ እንገሠጻለን።
³³ ስለዚህ፥ ወንድሞቼ ሆይ፥ ለመብላት በተሰበሰባችሁ ጊዜ እርስ በርሳችሁ ተጠባበቁ።
³⁴ ማንም የራበው ቢኖር ለፍርድ እንዳትሰበሰቡ በቤቱ ይብላ። የቀረውንም ነገር በመጣሁ ጊዜ እደነግጋለሁ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ያዕቆብ 2
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ ወንድሞቼ ሆይ፥ በክብር ጌታ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ያለውን እምነት ለሰው ፊት በማድላት አትያዙ።
² የወርቅ ቀለበት ያደረገና የጌጥ ልብስ የለበሰ ሰው ወደ ጉባኤአችሁ ቢገባ፥ እድፍ ልብስም የለበሰ ድሀ ሰው ደግሞ ቢገባ፥
³ የጌጥ ልብስም የለበሰውን ተመልክታችሁ፦ አንተስ በዚህ በመልካም ስፍራ ተቀመጥ ብትሉት፥ ድሀውንም፦ አንተስ ወደዚያ ቁም ወይም ከእግሬ መረገጫ በታች ተቀመጥ ብትሉት፥ ራሳችሁን መለያየታችሁ አይደለምን?
⁴ ክፉ አሳብ ያላቸውም ዳኞች መሆናችሁ አይደለምን?
⁵ የተወደዳችሁ ወንድሞቼ ሆይ፥ ስሙ፤ እግዚአብሔር በእምነት ባለ ጠጎች እንዲሆኑ ለሚወዱትም ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን መንግሥት እንዲወርሱ የዚህን ዓለም ድሆች አልመረጠምን?
⁶ እናንተ ግን ድሆችን አዋረዳችሁ። ባለ ጠጎቹ የሚያስጨንቁአችሁ አይደሉምን? ወደ ፍርድ ቤትም የሚጎትቱአችሁ እነርሱ አይደሉምን?
⁷ የተጠራችሁበትን መልካሙን ስም የሚሰድቡ እነርሱ አይደሉምን?
⁸ ነገር ግን መጽሐፍ፦ ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ እንደሚል የንጉሥን ሕግ ብትፈጽሙ መልካም ታደርጋላችሁ፤
⁹ ለሰው ፊት ግን ብታደሉ ኃጢአትን ትሠራላችሁ፥ ሕግም እንደ ተላላፊዎች ይወቅሳችኋል።
¹⁰ ሕግን ሁሉ የሚጠብቅ፥ ነገር ግን በአንዱ የሚሰናከል ማንም ቢኖር በሁሉ በደለኛ ይሆናል፤ አታመንዝር ያለው ደግሞ፦ አትግደል ብሎአልና፤
¹¹ ባታመነዝርም፥ ነገር ግን ብትገድል፥ ሕግን ተላላፊ ሆነሃል።
¹² በነጻነት ሕግ ፍርድን ይቀበሉ ዘንድ እንዳላቸው ሰዎች እንዲህ ተናገሩ፥ እንዲህም አድርጉ።
¹³ ምሕረትን ለማያደርግ ምሕረት የሌለበት ፍርድ ይሆናልና፤ ምሕረትም በፍርድ ላይ ይመካል።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 18
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²⁴ በወገኑም የእስክንድርያ ሰው የሆነ ነገር አዋቂ የነበረ አጵሎስ የሚሉት አንድ አይሁዳዊ ሰው ወደ ኤፌሶን ወረደ፤ እርሱም በመጻሕፍት እውቀት የበረታ ነበረ።
²⁵ እርሱ የጌታን መንገድ የተማረ ነበረ፥ የዮሐንስንም ጥምቀት ብቻ አውቆ በመንፈስ ሲቃጠል ስለ ኢየሱስ ይናገርና በትክክል ያስተምር ነበር።
²⁶ እርሱም በምኵራብ ገልጦ ይናገር ጀመር። ጵርስቅላና አቂላም በሰሙት ጊዜ፥ ወስደው የእግዚአብሔርን መንገድ ከፊት ይልቅ በትክክል ገለጡለት።
²⁷ እርሱም ወደ አካይያ ማለፍ በፈቀደ ጊዜ፥ ወንድሞቹ አጸናኑት፥ ይቀበሉትም ዘንድ ወደ ደቀ መዛሙርት ጻፉለት፤ በደረሰም ጊዜ አምነው የነበሩትን በጸጋ እጅግ ይጠቅማቸው ነበር፤
²⁸ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ እንደ ሆነ ከመጻሕፍት እየገለጠ ለአይሁድ በሁሉ ፊት በጽኑ ያስረዳቸው ነበርና።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#መስከረም_5_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ሣህል ወርትዕ ተራከባ። ጽድቅ ወሰላም ተሰዐማ። ርትዕሰ እምድር ሠረፀት"። መዝ 84፥10-11።
"ምሕረትና እውነት ተገናኙ፤ ጽድቅና ሰላም ተስማሙ። እውነት ከምድር በቀለች፥ ጽድቅም ከሰማይ ተመለከተች"። መዝ 84፥10-11።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#መስከረም_5_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ዮሐንስ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁵ ዮሐንስ ስለ እርሱ መሰከረ እንዲህም ብሎ ጮኸ፦ ከእኔ በኋላ የሚመጣው እርሱ ከእኔ በፊት ነበረና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል፤ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነበረ።
¹⁶ እኛ ሁላችን ከሙላቱ ተቀብለን በጸጋ ላይ ጸጋ ተሰጥቶናልና ሕግ በሙሴ ተሰጥቶ ነበርና፤
¹⁷ ጸጋና እውነት ግን በኢየሱስ ክርስቶስ ሆነ።
¹⁸ መቼም ቢሆን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው።
¹⁹ አይሁድም፦ አንተ ማን ነህ? ብለው ይጠይቁት ዘንድ ከኢየሩሳሌም ካህናትንና ሌዋውያንን በላኩበት ጊዜ፥ የዮሐንስ ምስክርነት ይህ ነው።
²⁰ መሰከረም አልካደምም፤ እኔ ክርስቶስ አይደለሁም ብሎ መሰከረ።
²¹ እንኪያስ ማን ነህ? ኤልያስ ነህን? ብለው ጠየቁት። አይደለሁም አለ። ነቢዩ ነህን? አይደለሁም ብሎ መለሰ።
²² እንኪያስ፦ ማን ነህ? ለላኩን መልስ እንድንሰጥ፤ ስለራስህ ምን ትላለህ? አሉት።
²³ እርሱም፦ ነቢዩ ኢሳይያስ እንዳለ፦ የጌታን መንገድ አቅኑ ብሎ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ እኔ ነኝ አለ።
²⁴-²⁵ የተላኩትም ከፈሪሳውያን ነበሩና፦ እንኪያስ አንተ ክርስቶስ ወይም ኤልያስ ወይም ነቢዩ ካይደለህ፥ ስለ ምን ታጠምቃለህ? ብለው ጠየቁት።
²⁶ ዮሐንስ መልሶ፦ እኔ በውኃ አጠምቃለሁ፤ ዳሩ ግን እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሞአል፤
²⁷ እኔ የጫማውን ጠፍር ልፈታ የማይገባኝ፥ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ከእኔ ይልቅ የሚከብር ይህ ነው አላቸው።
²⁸ ይህ ነገር ዮሐንስ ያጠምቅበት በነበረው በዮርዳኖስ ማዶ በቢታንያ በቤተ ራባ ሆነ።
²⁹ በነገው ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ፦ እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ።
³⁰ አንድ ሰው ከእኔ በኋላ ይመጣል፥ ከእኔም በፊት ነበርና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል ብዬ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነው።
³¹ እኔም አላውቀውም ነበር፥ ዳሩ ግን ለእስራኤል ይገለጥ ዘንድ ስለዚህ በውኃ እያጠመቅሁ እኔ መጣሁ።
³² ዮሐንስም እንዲህ ብሎ መሰከረ፦ መንፈስ ከሰማይ እንደ ርግብ ሆኖ ሲወርድ አየሁ፤ በእርሱ ላይም ኖረ።
³³ እኔም አላውቀውም ነበር፥ ዳሩ ግን በውኃ አጠምቅ ዘንድ የላከኝ እርሱ፦ መንፈስ ሲወርድበትና ሲኖርበት የምታየው፥ በመንፈስ ቅዱስ የሚያጠምቅ እርሱ ነው አለኝ።
³⁴ እኔም አይቻለሁ እርሱም የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ መስክሬአለሁ።
³⁵ በነገው ደግሞ ዮሐንስ ከደቀ መዛሙርቱም ሁለት ቆመው ነበር፥
³⁶ ኢየሱስም ሲሄድ ተመልክቶ፦ እነሆ የእግዚአብሔር በግ አለ።
³⁷ ሁለቱም ደቀ መዛሙርት ሲናገር ሰምተው ኢየሱስን ተከተሉት።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #ቅዱሳን_ሐዋርያት ወይም የ #ቅዱስ_አትናቴዎስ_ቅዳሴ ነው። መልካም የአቡነ አሮን፣ የሰማዕት የቅድስት ሶፍያና የሁለቱ ልጆቿ፣ የቅዱስ ማማስ ሰማዕትና የአጼ ንብለ ድንግል የዕረፍት በዓልና ዕለተ ሰንበት ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#መስከረም_6

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ስድስት በዚች ቀን ታላቅ ነቢይ የአሞጽ ልጅ #ቅዱስ_ኢሳይያስ አረፈ፣ #የአቡነ_ሳሙኤል_ዘዋልድባ ዐፅማቸው ከዋልድባ አብረንታንት ወደ ደብረ ዓባይ የፈለሰበት ዕለት ነው፣ #ቅድስት_ሰብልትንያ በዲዮቀልጥያኖስ ዘመን በሰማዕትነት ሞተች።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ነቢዩ_ኢሳይያስ

መስከረም ስድስት በዚች ቀን ታላቅ ነቢይ የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ አረፈ። ይህም ነቢይ ለይሁዳ በነገሡ በአምስቱ ነገሥታት ዘመን አስተማረ ትንቢትም ተናገረ እሊህም አዝያን ኢዮአታም አካዝ ሕዝቅያስና ምናሴ ናቸው።

በአካዝ ዘመንም እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ። እነሆ ስለዚህ #እግዚአብሔር ምልክትን ይሰጣችኋል። እነሆ ድንግል ፀንሳ ወንድ ልጅን ትወልዳለች ስሙንም #አማኑኤል ትለዋለች። ትርጓሜውም #እግዚአብሔር ከእኛ ጋራ አንድ ሆነ ማለት ነው።

እርሱም በኃጢአታቸው ከሚመጣባቸው ፍዳ ወገኖቹን የሚያድናቸው ወደ ሃይማኖቱም የሚአስገባቸው እንደሆነ የእስራኤልንም ልጆች መሥዋዕታቸውንና ክህነታቸውን እንደሚሽር ከሐዲስ ወገኖችም የሚያመሰግኑት ካህናትን እንደሚሾም ተናገረ።

የፋርስ ንጉሥ ሰናክሬምም ኢየሩሳሌምን ከቦ የስድብ ቃልን በክብር ባለቤት በ #እግዚአብሔር ላይ በተናገረ ጊዜ የፋርስ ንጉሥ ሰናክሬምን ያጠፋው ዘንድ #እግዚአብሔር እንዳለው ለሕዝቅያስ ትንቢትን ተናገረ።

በዚያች ሌሊትም #እግዚአብሔር የላከው የመላእክት አለቃ #ቅዱስ_ሚካኤል ወደ ሠናክሬም ሰፈር መጥቶ ከፋርስ ሠራዊት መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ አርበኞችን ገደለ። የለኪሶ ሰዎች ሲነጋ በተነሡ ጊዜ የሞቱትን ሰዎች ሬሳ ሁሉ አዩ።

ሕዝቅያስም ታሞ ለሞት በተቃረበ ጊዜ የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ ወደርሱ መጥቶ #እግዚአብሔር ትሞታለህ እንጂ አትድንም ብሏልና ቤትህን አዘጋጅ አለው። ሕዝቅያስም ፊቱን ወደ ግድግዳው መልሶ ወደ #እግዚአብሔር ለመነ ፈጽሞ ጽኑ ልቅሶንም አለቀሰ።

ይህን ከነገረው በኋላ የ #እግዚአብሔር ቃል ወደ ነቢዩ ወደ ኢሳይያስ መጣ ሒደህ ለሕዝቅያስ የአባትህ የዳዊት ፈጣሪ #እግዚአብሔር ጸሎትህን ሰማሁ ዕንባህንም አየሁ። እነሆ በዘመንህ ላይ ዐሥራ አምስት ዓመት ጨመርኩልህ አለ በለው።

ዳግመኛም ስለ እስራኤል መማረክና ከምርኮ ስለ መመለሳቸው ትንቢት ተናገረ የፈሳሽ ውኃን ምንጭ በማፍሰስ በእጆቹ ላይ #እግዚአብሔር ምልክትን ገለጠ።

ክብር ይግባውና ስለ #መድኃኒታችን_ክርስቶስ መከራ ትንቢት ተናገረ እንዲህም አለ። እርሱም በመከራው ጊዜ ነገርን አልተናገረም እንደ በግ ይታረድ ዘንድ መጣ በግ በሚሸልተው ሰው ፊት እንደ ማይናገር እንዲሁ በመከራው ጊዜ አልተናገረም።

ከዚህም በኋላ ደግሞ በሕዝቅያስ ልጅ በንጉሥ ምናሴ ላይ ትንቢት ተናገር ጣዖትን ስለማቆሙና ስለማምለኩ ገሠጸው። ስለዚህም ንጉሥ ምናሴ ተቆጥቶ በዕንጨት መሰንጠቂያ መጋዝ በራሱና በእግሮቹ መካከል ሠነጠቀው ምስክርነቱንም በዚህ ፈጸመ።

ትንቢት እየተናገረ የኖረበትም ዘመን ሰብዓ ዓመት ከዚያም በላይ ይሆናል። እርሱም ያስተማረው ክብር ይግባውና #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ከመምጣቱ በፊት በዘጠኝ መቶ ዐሥራ ሦስት ዓመት ነው።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ነብይ ኢሳይያስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አባ_ሳሙኤል_ዘዋልድባ

ዳግመኛም በዚህች ቀን የዋልድባው የአቡነ ሳሙኤል ዐፅማቸው ከዋልድባ አብረንታንት ወደ ደብረ ዓባይ የፈለሰበት ዕለት ነው፡፡ አባ ሳሙኤል ዘዋልድባ ትውልዳቸው ከካህናቱ ወገን አክሱም ነው አባታቸው እስጢፋኖስ እናታቸው አመተ ማርያም ይባላሉ። ለመምህር ሰጥተዋቸው ሲማሩ አድገው በኋላም ወላጆቻቸው በሞት ሲለዩአቸው ደብረ በንኰል ገዳም ገብተው ሥርዓተ ምንኩስናን ከአበው እያጠኑ ለትልቁም ለትንሹም በትሕትና እየታዘዙ ውሃ እየቀዱ እንጨት እየሰበሩ በትኅርምት በጽሞና በጸሎት ይኖሩ ነበር።

ሰይጣን በውዳሴ ከንቱ ጾር ቢመጣባቸው ከማሕበረ መነኮሳቱ ተለይተው በተባሕትዎ ለመኖር ሽተው ወጥተው ሲሔዱ ተከዜ ደረሱ። ወንዙ ሞልቶ የማያሻግራቸው ቢሆን ውሃውን በትምህርተ #መስቀል ባርከው በአንድ እጃቸው መጽሐፍ በአንድ እጃቸው መብራት እንደያዙ ገብተው መብራቱ ሳይጠፋ መጽሐፉ ሳይበላሽ ተሻግረዋል። ዋልድባ ሲደርሱ #ጌታ እዚህ ተቀመጥ ስላላቸው ገዳም መሥርተው ሥርዓተ ምንኩስናን እያስተማሩ ተቀመጡ። ዛሬ በዋልድባ የሚያመሰግኑበት #ውዳሴ_ማርያም #ቅዳሴ_ማርያምን ከተከዜ ወዲህ ያመጡ እሳቸው ናቸው። ይህንን እየጸለዩ ሲሔዱ ክንድ ከስንዝር መሬት ለቀው ይታዩ ነበር። አንድ ቀንም ይህንን ጸሎት ደግመው ውኃውን ቢባርኩት ኅብስተ ሕይወት ሆነላቸው ከነደቀ መዛሙርቶቻቸው ተመግበውታል።

#እመቤታችንም የፍቅር መግለጫ ዕጣን፣ ወርቅ፣ እንቁ ሰጥታቸዋለች። ውዳሴዬን ከቅዳሴዬ አንድ አድርጎ የደገመውን አንተ ከገባህበት መካነ ሕይወት አስገባዋለሁ ብላ ቃልኪዳን ሰጥታቸዋለች። ጊዜ እረፍታቸው ሲደርስ #ጌታን በስብሐተ መላእክት ተገልጦ በስምህ የተማጸነውን በጎ የሰራውን፣ ዜና ገድልህን የጻፈውን፣ ያስጻፈውን፣ ያነበበ፣ የተማረ፣ ያስተማረ፣ እስከ አሥር ትውልድ ድረስ ምሬልሃለሁ። በዚህ ቦታ በዋልድባ የሚሰበሰቡ ልጆችህን ከእዳ ከፍዳ እሰውርልሃለሁ አላቸው። እንኪያስ ቦታዋን ባርክልኝ ብለው እንደ መሶብ አንስተው አስባርከዋታል #ጌታችንም እህል አይብቀልብሽ ኃጢአት አይሻገርብሽ ብሎ ቃል ኪዳን ገባላት ለገዳመ ዋሊ። አባታችን አቡነ ሳሙኤል በበዓታቸው ውስጥ ጸንተው ሲኖሩ ታህሣሥ 12 ቀን ያረፉ ሲሆን ዛሬ መስከረም 6 ግን ፍልሰተ አጽማቸው የተከናወነበት እለት ነው።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጻድቁ አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ሰብልትንያ

በዚህችም ቀን ቅድስት ሰብልትንያ በከ*ሀዲ ንጉሥ ዲዮቀልጥያኖስ ዘመን በሰማዕትነት ሞተች። ይችንም ቅድስት ዕድሜዋ ዘጠኝ ዓመት ሲሆን ከሀ*ድያን ያዙዋት እጆቿንና እግሮቿንም አሥረው ከሚነድ እሳት ውስጥ ጣሏት የክብር ንጉሥ በሆነ በ #እግዚአብሔርም ኃይል ከእሳት ዳነች።

ውኃን በተጠማች ጊዜ #እግዚአብሔርን ለምናው ውኃን አፈለቀላትና ጠጣች ክብር ምስጉን የሆነ #ጌታችንንም አመሰገነችው። ከዚህም በኋላ ነፍሷን በ #እግዚአብሔር እጅ አደራ ሰጥታ ራሷን ከእሳት ውስጥ ወረወረች ምስክርነቷንም ፈጸመች።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_መስከረም_6 እና #ከገድላት_አንደበት)
2024/09/25 09:11:25
Back to Top
HTML Embed Code: