Telegram Web Link
#ሐምሌ_26

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ሃያ ስድስት በዚች ቀን የእመቤታችን ድንግል ማርያም እጮኛዋ ለጌታችንም አሳዳጊው ለመሆን የተገባው #ጻድቁ_ዮሴፍ አረፈ፣ ለኢትዮጵያ ሀገር ብርሃንን የገለጠ ቅዱስ አባት #አባ_ሰላማ አረፈ፣ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_ጢሞቴዎስ አረፈ፣ #አቡነ_ሳሙኤል_ዘደብረ_ሃሌሉያ ዕረፍታቸው ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ጻድቁ_ዮሴፍ

ሐምሌ ሃያ ስድስት በዚች ቀን መልካም ሽምግልና የነበረው የእመቤታችን ድንግል ማርያም እጮኛዋ ድካሟን ለመሳተፍ ክብር ይግባውና ለ #ጌታችንም አሳዳጊው ለመሆኑ የተገባው ጻድቁ ዮሴፍ አረፈ።

እርሱም #እምቤታችንን በርሱ ዘንድ ካስጠበቋት ጀምሮ በሁሉ ነገር ያገለግላት ነበር። በመከራዋም ሁሉ አልተለያትም። በወለደችም ጊዜ በቤተ ልሔም ከርሷ ጋራ ነበረ። ወደ ግብጽም በተሰደደች ጊዜ ከእርሷ ጋራ ብዙ መከራ ደረሰበት። ከዚህም ዓለም የሚለይበት ጊዜው በደረሰ ጊዜ ወንዶችና ሴቶች ልጆቹን ጠርቶ ተሰናበታቸው እጆቹንም ዘርግቶ ነፍሱን በ #እግዚአብሔር እጅ ሰጠ። የዘላለምንም ሕይወት ወረሰ።

በአረፈበትም ጊዜ #ጌታችን ወደርሱ መጥቶ እጆቹን በላዩ ጫነ ለሥጋውም መፍረስና መበስበስ እንዳያገኘው ኃይልን ሰጠው በአባቱ በያዕቆብም መቃበር አኖሩት። ዕረፍቱም ክብር ይግባውና ከ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሥጋዊ በዐሥራ ስድስት ዓመት ነው።

#ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ሰላማ_ከሳቴ_ብርሃን

በዚችም ቀን ለኢትዮጵያ ሀገር ብርሃንን የገለጠ ቅዱስ አባት አባ ሰላማ አረፈ። ዜናውም እንዲህ ነው ስሙ ሜሮጵዮስ የሚባል የጥበበኞች አለቃ አንድ ሰው ወደ ሕንድ አገር ሊአልፍ ወዶ ከጢሮስ አገር መጣ ከእርሱም ጋራ ከዘመዶቹ ወገን የሆኑ ሁለት ብላቴኖች ነበሩ። የአንደኛው ስሙ ፍሬምናጦስ የሁለተኛውም ኤዴስዮስ ይባላል። ሲድራኮስ የሚሉትም አሉ። በኢትዮጵያ በኩል ወዳለው ወደ አፍሪቃ ባሕር ወደብ ደረሱ ልቡ የተመኘችውን የኢትዮጵያን አገር መልካምነቷን ሁሉ ተመለከተ።

ከዚህም በኃላ በድንገት ወንበዴዎች ተነሥተው በመርከብ ከአሉት ሁሉ ጋር ገደሉት እኒህ ሁለት ልጆች ግን ተረፉ። የአገሩ ሰዎችም አገኙዋቸው ወደ ንጉሥም ወስደው አንደ እጅ መነሻ አድርገው እነርሱን ሰጡት ንጉሡም ተቀበላቸው።

ከጥቂት ቀኖች በኃላም ንጉሡ ኤዴስዮስን በፊቱ የሚቆም ጋሻ ዣግሬ አድርጎ ሾመው ፍሬምናጦስን ግን በገንዘቡ ሁሉ ላይ በጅሮንድ አድርጎ ሾመው ይህም ንጉሥ የአብርሀና የአጽብሐ አባታቸው ስሙ አይዛና የተባለው ነበር። እነርሱ ሕፃናት ሳሉም አረፈ። እኒህም አካለ መጠን እስከሚያደርሱ ድረስ የንጉሡን ልጆች እያሳደጉ ኖሩ ክብር ይግባውና በ #ክርስቶስ ማመንንም አስተማሩዋቸው።

የንጉሡም ልጆች አድገው በነገሡ ጊዜ ኤዴስዮስ ወደ አገሩ ተመለሰ ፍሬምናጦስ ግን ወደ ግብጽ ሔደ ወደ እስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ወደ አባ አትናቴዎስም ደረሰ። የደረሰብትንም ሁሉ ነገረው። ስለ ኢትዮጵያውያንም ሃይማኖት ጳጳስ ሳይኖራቸው ክብር ይግባውና በ #ጌታችን_በኢየሱስ_ክርስቶስ እንዴት እንዳመኑ ነገረው። አባ አትናቴዎስም በሰማ ጊዜ እጅግ አደነቀ ፍሬምናጦስንም የነጻ ሕዝብ አገር ለሆነችው ለኢትዮጵያ አገር ጳጳስ ይሆን ዘንድ ግድ አለው። ጵጵስነትንም ሾመ ከታላቅ አክብሮት ጋራ ላከው በአብርሀና በአጽብሐ ዘመነ መንግሥትም ወደ ኢትዮጵያ በደረሰ ጊዜ በክብር ተቀበሉት።

በኢትዮጵያም አገሮች ሁሉ የቀናች ሃይማኖትን ሰበከ አስተማረም ክብር ይግባውና #ክርስቶስን የጌትነቱን ብርሀን በሁሉ አገሮች ገለጠ ስለዚህም ብርሃንን ገላጭ ሰላማ ተባለ ሁሉንም አስተካክሎ በሰላም አረፈ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ አባት ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ጢሞቴዎስ

በዚችም ቀን ከአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ቁጥር ውስጥ የሆነው የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ ጢሞቴዎስ አረፈ። በተሾመ ጊዜም የክርስቶስን መንጋዎች ከአርዮስ ከመቅዶንዮስና ከሰባልዮስ ተኩላዎች ጠበቀ።

ይህም አባት በተሾመ በስድስተኛው ዓመት ለክርስቲያን ወገኖች ደግ የሆነ ቴዎዶስዮስ ነገሠ በዚያችም ዓመት ክብር ይግባውና #መንፈስ_ቅዱስን ስለ ካደው ስለ መቅዶንዮስ በቁስጥንጥንያ የተሰበሰቡ የመቶ ሃምሳ ቅዱሳን ኤጲስቆጶሳት ጉባኤ ተደረገ ይህም አባት ጢሞቴዎስ ሊቀ ጉባኤ ሆኖ መቅዶንዮስንና ሰባልዮስን አቡሊናርዮስንም ተከራከራቸው። ረትቶም አሳፈራቸው። እነሆ የክህደታቸውንና የክርክራቸውንም ነገር የካቲት አንድ ቀን ላይ ጽፈናል።

ከዚህም በኃላ ይህ አባት በሹመቱ ዘመን አብያተ ክርስቲያናትን በማነፅና በሚገባውም ሥራ ሁሉ በእድሳታቸውም አሰበ። ለመጻተኞችም ቤቶችን ሠራላቸው።

መንጋዎቹንም ሁልጊዜ ያስተምራቸው ነበር በመልካም እውቀቱና በትምህርቱ ጣዕም ሁልጊዜም በማስረዳቱ በቀናች ሃይማኖት አጸናቸው። ከአርዮስና ከመቅዶንዮስ ወገኖችም ብዙዎቹን መልሶ ክብር ይግባውና የ #ጌታችን_የኢየሱስ_ክርስቶስ ወደ ሆነች የቀናች ሃይማኖት አስገባቸው።

በወንጌላዊው ማርቆስ መንበርም ላይ ዘጠኝ ዓመት ተኩል ኖረ ከዚያም በኃላ በሰላም አረፈ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_ሳሙኤል_ዘደብረ_ሃሌሉያ

በዚህችም ቀን አቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ሃሌሉያ ዕረፍታቸው ነው፡፡ የትውልድ ሀገራቸው ተንቤን ነው፡፡ አባታቸው ይስሐለነ እግዚእ እናታቸው ትቀድሰነ ማርያም ይባላሉ፡፡ አቡነ አቢየ እግዚእ አጎታቸው ናቸው፡፡ እናታቸው እሳቸውን ፀንሳ ሳለ ቡራኬ ለመቀበል ወደ ወንድሟ ስትሄድ አቡነ አቢየ እግዚእ መሬት ላይ ወድቀው ሰግደውላታል፡፡ ደቀ መዛሙርቶቻቸውም ‹‹ለዚህች ሴት እንዴት ሰገዱላት?›› ብለው ቢጠይቋቸው አቡነ አቢየ እግዚእ ስለ አቡነ ሳሙኤል ክብርና ጽድቅ ትንቢት ነግረዋቸዋል፡፡

አቡነ ሳሙኤል ሲወለዱ እናታቸው ለአቡነ አቢየ እግዚእ ሰጠቻቸው፣ እርሳቸውም በሃይማኖት በመግባር ኮትኩተው ሁሉን አስተምረው አሳደጓቸው፡፡ አባታችን የጻድቃንና የሰማዕታትን ታሪክ እያነበቡ ያዝኑና ያለቅሱ ነበር፡፡ እንደ እነርሱ በሆንኩም እያሉ ይመኙ ነበር፡፡ አቡነ አቢየ እግዚእ ሀሳባቸውን በመንፈስ ተረድተውላቸው ነበርና መርቀው ባርከው አሰናበቷቸው፡፡ አቡነ ሳሙኤልም በሕፃንነታቸው መንነው ወደ አቡነ እንጦንዮስ ገዳም ገብተው በ14 ዓመታቸው መነኮሱ፡፡

ከየት እንደመጣ የማይታወቅና መላ አካሉ እንደበረዶ ነጭ የሆነ አንበሳ መጥቶ እየመራቸው አሁን ደብረ ሃሌሉያ እየተባለ ወደሚጠራው ገዳማቸው ሄደው በዓታቸውን አጽንተው ገዳሙን መሠረቱት፡፡ አቡነ ሳሙኤል ዘሀለሎም እየተባሉ ይጠራሉ፡፡

ጻድቁ የጌታችን መከራ በማሰብ ከተወለዱ ጀምሮ ተላጭተውት የማያውቁትን ፀጉራቸውን ከትልቅ ዛፍ ላይ እያሠሩ ይጸልዩ ነበር፡፡ እንዲሁ አድርገው ዛፍ ላይ ራሳቸውን ሰቅለው 40 ቀንና 40 ሌሊት ሲጸልዩ በመጨረሻ የታሠሩበት ፀጉራቸው ተነቅሎ ከመሬት ላይ ወደቁ፡፡ ደማቸውም እንደ ውኃ ፈሰሰ፡፡ ክብር ይግባውና #ጌታችንም ቅዱስ ሚካኤልንና ቅዱስ ገብርኤልን አስከትሎ ተገልጦላቸው እጃቸውን ይዞ አንሥቷቸዋል፡፡ ‹‹ምን እንዳደርግልህ ትወዳለህ?›› ቢላቸው ስለ ሀገራችን ሰላም ይልቁንም በዚህ በቆረቆሩት ገዳማቸው የሚኖሩትን ልጆቻቸውን እንዲጠብቅላቸው ለመኑት፡፡ #ጌታችንም
በገዳማቸው ውስጥ በፍጹም ሕማም፣ ደዌና ተስቦ በሽታ እንደማይገባ ቃልኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡

ለመንግሥተ ሰማያትም ያልታጨ ሰው በዚህ ገዳም ገብቶ አይቀበርም፡፡ ጻድቁ ከዛፉ ላይ ወድቀው ሳለ #ጌታችንን እጨብጣለሁ ብለው የዘረጓት እጃቸው እያበራች ኖራለች፡፡ እንደ መብረቅም እየጮኸች ለገዳሙ እንደ ደወል ታገለግል ነበር፡፡ በመጨረሻም ሊያርፉ ሲሉ ልጆቻቸውን ሰብስበው ባርከዋቸዋል፡፡ ያ አቡነ ሳሙኤል የባረኩበት ቡራኬም በመጽሐፈ ግንዘት ላይ ተደንግጎ ይገኛል፡፡ ዛሬም ድረስ ሰው ሲሞት ‹‹ቡራኬ ዘአቡነ ሳሙኤል›› ብሎ ካህኑ ይደግማል፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ በከተማ አካባቢ ግን እየተደረገ አይደለም፡፡ አቡነ ሳሙኤል ብዙዎችን ያመነኮሱ ሲሆን እንደነ አቡነ ተጠምቀ መድኅን፣ አቡነ ዘኢየሱስ፣ አቡነ ገብረ ክርስቶስ ያሉ ሌሎችንም በርካታ መነኮሳትን አፍርተዋል፡፡

አባታችንን ያመነኮሷቸው አባት አቡነ እንጦንዮስ ሊጠይቋቸው ወደ ደብረ ሃሌሉያ ሄደው ሲመለሱ እንዲላላካቸው አንድ ትንሽ ልጅ ትተውላቸው ተመለሱ፡፡ አቡነ ሳሙኤልም በጥበብ መንፈሳዊ ኮትኩተው አሳደጉት፡፡

አንድ ቀን ምግባቸው የሚሆን የእንጨት ፍሬዎችን ለመልቀም ከበዓታቸው ሲወጡ ልጃቸው እንዳይደክምባቸው በማሰብ በገዳማቸው ትተውት ለመሄድ አሰቡ፡፡ ብቻውን ስለሆነ አስፈሪ አራዊት እንዳያስደነግጡት በማሰብ ጉድጓድ ቆፍረው በዚያ አኑረውት ሄዱ፡፡ ርቀው ሄደው የእንጨቶችን ፍሬ ሲለቅሙ በጫካው እሳት ተስቶ ገዳማቸውንም ሙሉ በሙሉ አቃጠለው፡፡ ጻድቁ ስለ ልጃቸው ወደ ፈጣሪያቸው ጸልየው ካበቁ በኋላ ወደ ገዳማቸው ቢሄዱ የልጃቸው የራስ ፀጉር እንኳን ሳትቃጠል በሰላም አገኝተውታል፡፡ ያ ልጅም በኋላ አቡነ ገብረ መስቀል የተባለው ገድለኛ አባት ነው፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ሐምሌ_26 እና #ከገድላት_አንደበት)
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ሐምሌ_26_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ጢሞቴዎስ 6
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
³ እነዚህን አስተምርና ምከር። ማንም ልዩ ትምህርት የሚያስተምር ከጌታችንም ከኢየሱስ ክርስቶስ በሆነው ጤናማ ቃልና እግዚአብሔርን ለመምሰል በሚስማማ ትምህርት የማይጠጋ ቢሆን፥
⁴-⁵ በትዕቢት ተነፍቶአል አንዳችም አያውቅም፥ ነገር ግን ምርመራን በቃልም መዋጋትን እንደ በሽተኛ ይናፍቃል፤ ከእነዚህም ቅንዓትና ክርክር ስድብም ክፉ አሳብም እርስ በርስ መናደድም ይወጣሉ፥ አእምሮአቸውም በጠፋባቸው እውነትንም በተቀሙ፥ እግዚአብሔርን መምሰል ማትረፊያ የሚሆን በመሰላቸው ሰዎች ይገኛሉ። እንደነዚህ ካሉት ራቅ።
⁶ ኑሮዬ ይበቃኛል ለሚለው ግን እግዚአብሔርን መምሰል እጅግ ማትረፊያ ነው፤
⁷ ወደ ዓለም ምንም እንኳ አላመጣንምና፥
⁸ አንዳችንም ልንወስድ አይቻለንም፤ ምግብና ልብስ ከኖረን ግን፥ እርሱ ይበቃናል።
⁹ ዳሩ ግን ባለ ጠጎች ሊሆኑ የሚፈልጉ በጥፋትና በመፍረስ ሰዎችን በሚያሰጥምና በሚያሰንፍ በሚጎዳም በብዙ ምኞትና በፈተና በወጥመድም ይወድቃሉ።
¹⁰ ገንዘብን መውደድ የክፋት ሁሉ ሥር ነውና፥ አንዳንዶች ይህን ሲመኙ፥ ከሃይማኖት ተሳስተው በብዙ ሥቃይ ራሳቸውን ወጉ።
¹¹ አንተ ግን፥ የእግዚአብሔር ሰው ሆይ፥ ከዚህ ሽሽ፤ ጽድቅንና እግዚአብሔርን መምሰል እምነትንም ፍቅርንም መጽናትንም የዋህነትንም ተከታተል።
¹² መልካሙን የእምነት ገድል ተጋደል፥ የተጠራህለትንም በብዙም ምስክሮች ፊት በመልካም መታመን የታመንህለትን የዘላለምን ሕይወት ያዝ።
¹³ ሁሉን በሕይወት በሚጠብቅ በእግዚአብሔር ፊት፥ በጴንጤናዊውም በጲላጦስ ዘንድ መልካሙን መታመን በመሰከረ በክርስቶስ ኢየሱስ ፊት አዝሃለሁ፤
¹⁴ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እስኪገለጥ ድረስ ያለ እድፍና ያለ ነቀፋ ሆነህ ትእዛዙን ጠብቅ፤
¹⁵ ያንም መገለጡን በራሱ ጊዜ ብፁዕና ብቻውን የሆነ ገዥ፥ የነገሥታት ንጉሥና የጌቶች ጌታ፥ ያሳያል።
¹⁶ እርሱ ብቻ የማይሞት ነው፤ ማንም ሊቀርበው በማይችል ብርሃን ይኖራል፤ አንድ ሰው እንኳ አላየውም ሊያይም አይቻለውም፤ ለእርሱ ክብርና የዘላለም ኃይል ይሁን፤ አሜን።
¹⁷ በአሁኑ ዘመን ባለ ጠጎች የሆኑት የትዕቢትን ነገር እንዳያስቡ፥ ደስም እንዲለን ሁሉን አትርፎ በሚሰጠን በሕያው እግዚአብሔር እንጂ በሚያልፍ ባለ ጠግነት ተስፋ እንዳያደርጉ እዘዛቸው።
¹⁸-¹⁹ እውነተኛውን ሕይወት ይይዙ ዘንድ፥ ለሚመጣው ዘመን ለራሳቸው መልካም መሠረት የሚሆንላቸውን መዝገብ እየሰበሰቡ፥ መልካምን እንዲያደርጉ በበጎም ሥራ ባለ ጠጎች እንዲሆኑ፥ ሊረዱና ሊያካፍሉም የተዘጋጁ እንዲሆኑ ምከራቸው።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ዮሐንስ 2
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ ልጆቼ ሆይ፥ ኃጢአትን እንዳታደርጉ ይህን እጽፍላችኋለሁ። ማንም ኃጢአትን ቢያደርግ ከአብ ዘንድ ጠበቃ አለን እርሱም ጻድቅ የሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።
² እርሱም የኃጢአታችን ማስተስሪያ ነው፥ ለኃጢአታችንም ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን ለዓለሙ ሁሉ ኃጢአት እንጂ።
³ ትእዛዛቱንም ብንጠብቅ በዚህ እንዳወቅነው እናውቃለን።
⁴ አውቄዋለሁ የሚል ትእዛዛቱንም የማይጠብቅ ውሸተኛ ነው እውነትም በእርሱ ውስጥ የለም።
⁵ ቃሉን ግን የሚጠብቅ ሁሉ በእርሱ የእግዚአብሔር ፍቅር በእውነት ተፈጽሞአል። በእርሱ እንዳለን በዚህ እናውቃለን፤
⁶ በእርሱ እኖራለሁ የሚል እርሱ እንደ ተመላለሰ ራሱ ደግሞ ሊመላለስ ይገባዋል።
⁷ ወንድሞች ሆይ፥ ከመጀመሪያ የነበረቻችሁ አሮጌ ትእዛዝ እንጂ የምጽፍላችሁ አዲስ ትእዛዝ አይደለችም፤ አሮጌይቱ ትእዛዝ የሰማችኋት ቃል ናት።
⁸ ዳግመኛ አዲስ ትእዛዝን እጽፍላችኋለሁ፥ ይህም ነገር በእርሱ በእናንተም እውነተኛ ነው፤ ጨለማው ያልፋልና እውነተኛውም ብርሃን አሁን ይበራል።
⁹ በብርሃን አለሁ የሚል ወንድሙንም የሚጠላ እስከ አሁን በጨለማ አለ።
¹⁰ ወንድሙንም የሚወድ በብርሃን ይኖራል ማሰናከያም የለበትም፤
¹¹ ወንድሙን የሚጠላ ግን በጨለማ አለ፥ በጨለማም ይመላለሳል፥ የሚሄድበትንም አያውቅም፥ ጨለማው ዓይኖቹን አሳውሮታልና።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 5
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²⁰ ሂዱና ቆማችሁ የዚህን ሕይወት ቃል ሁሉ ለሕዝብ በመቅደስ ንገሩ አላቸው።
²¹ በሰሙም ጊዜ ማልደው ወደ መቅደስ ገብተው አስተማሩ። ግን ሊቀ ካህናቱና ከእርሱ ጋር የነበሩት መጥተው ሸንጎውንና የእስራኤልን ልጆች ሽማግሌዎች ሁሉ በአንድነት ጠሩ፥ ያመጡአቸውም ዘንድ ወደ ወኅኒ ላኩ።
²²-²³ ሎሌዎችም መጥተው በወኅኒው አላገኙአቸውም፤ ተመልሰውም፦ ወኅኒው በጣም በጥንቃቄ ተዘግቶ ጠባቂዎችም በደጁ ፊት ቆመው አገኘን፥ በከፈትን ጊዜ ግን በውስጡ አንድ ስንኳ አላገኘንም አሉአቸው።
²⁴ የመቅደስ አዛዥና የካህናት አለቆችም ይህን ነገር በሰሙ ጊዜ፦ እንጃ ይህ ምን ይሆን? እያሉ ስለ እነርሱ አመነቱ።
²⁵ አንድ ሰውም መጥቶ፦ እነሆ፥ በወኅኒ ያኖራችኋቸው ሰዎች እየቆሙ ሕዝቡንም እያስተማሩ በመቅደስ ናቸው ብሎ አወራላቸው።
²⁶ በዚያን ጊዜ አዛዡ ከሎሌዎች ጋር ሄዶ አመጣቸው፥ በኃይል ግን አይደለም፤ ሕዝቡ እንዳይወግሩአቸው ይፈሩ ነበርና።
²⁷ አምጥተውም በሸንጎ አቆሙአቸው።
²⁸ ሊቀ ካህናቱም፦ በዚህ ስም እንዳታስተምሩ አጥብቀን አላዘዝናችሁምን? እነሆም፥ ኢየሩሳሌምን በትምህርታችሁ ሞልታችኋል፤ የዚያንም ሰው ደም በእኛ ታመጡብን ዘንድ ታስባላችሁ ብሎ ጠየቃቸው።
²⁹ ጴጥሮስና ሐዋርያትም መልሰው አሉ፦ ከሰው ይልቅ ለእግዚአብሔር ልንታዘዝ ይገባል።
³⁰ እናንተ በእንጨት ላይ ሰቅላችሁ የገደላችሁትን ኢየሱስን የአባቶቻችን አምላክ አስነሣው፤
³¹ ይህን እግዚአብሔር፥ ለእስራኤል ንስሐን የኃጢአትንም ስርየት ይሰጥ ዘንድ፥ ራስም መድኃኒትም አድርጎ በቀኙ ከፍ ከፍ አደረገው።
³² እኛም ለዚህ ነገር ምስክሮች ነን፥ ደግሞም እግዚአብሔር ለሚታዘዙት የሰጠው መንፈስ ቅዱስ ምስክር ነው።
³³ እነርሱም ሲሰሙ በጣም ተቈጡ ሊገድሉአቸውም አሰቡ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ሐምሌ_26_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ይምጹኡ ተናብልት እምግብፅ። ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር። ነገስተ ምድር ሰብሕዎ ለእግዚአብሔር"። መዝ 67፥31-32።
"መኳንንት ከግብጽ ይመጣሉ፤ ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች።
የምድር ነገሥታት፥ ለእግዚአብሔር ተቀኙ፥ ለጌታም ዘምሩ"። መዝ 67፥31-32።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ሐምሌ_26_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ማቴዎስ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁸ የኢየሱስ ክርስቶስም ልደት እንዲህ ነበረ። እናቱ ማርያም ለዮሴፍ በታጨች ጊዜ ሳይገናኙ ከመንፈስ ቅዱስ ፀንሳ ተገኘች።
¹⁹ እጮኛዋ ዮሴፍም ጻድቅ ሆኖ ሊገልጣት ስላልወደደ በስውር ሊተዋት አሰበ።
²⁰ እርሱ ግን ይህን ሲያስብ፥ እነሆ የጌታ መልአክ በሕልም ታየው፥ እንዲህም አለ፦ የዳዊት ልጅ ዮሴፍ ሆይ፥ ከእርስዋ የተፀነሰው ከመንፈስ ቅዱስ ነውና እጮኛህን ማርያምን ለመውሰድ አትፍራ።
²¹ ልጅም ትወልዳለች፤ እርሱ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ።
²² በነቢይ ከጌታ ዘንድ፦
²³ እነሆ፥ ድንግል ትፀንሳለች ልጅም ትወልዳለች፥ ስሙንም አማኑኤል ይሉታል የተባለው ይፈጸም ዘንድ ይህ ሁሉ ሆኖአል፥ ትርጓሜውም፦ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር የሚል ነው።
²⁴ ዮሴፍም ከእንቅልፉ ነቅቶ የጌታ መልአክ እንዳዘዘው አደረገ፤ እጮኛውንም ወሰደ፤
²⁵ የበኩር ልጅዋንም እስክትወልድ ድረስ አላወቃትም፤ ስሙንም ኢየሱስ አለው።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #እመቤታችን_ማርያም ወይም የ #ሠለስቱ_ምዕት_ቅዳሴ ነው። መልካም የአረጋዊው የ #ቅዱስ_ዮሴፍ፣ የአባ #ሰላም_ከሳቴ_ብርሃን የዕረፍት በዓልና የአቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ሃሌሉያ የዕረፍት በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የአቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ሃሌሉያ አጎት የሆኑትና በምግባር በሐይማኖት ኮትኩተው ያሳደጓቸው አባት ማን ይባላሉ?
Anonymous Quiz
41%
አቡነ አቢየ እግዚእ
19%
አቡነ መድኃኒነ እግዚእ
28%
አቡነ ዜና ማርቆስ
13%
አቡነ ተክለ ሐይማኖት
አረጋዊ ቅዱስ ዮሴፍ ከወለዳቸው ልጆች መካከል አይደለም(ችም)?
Anonymous Quiz
23%
ስምዖን
25%
ሰሎሜ
20%
ቢንያም
33%
ዮሳ
ጻድቁ የጌታችን መከራ በማሰብ ከተወለዱ ጀምሮ ተላጭተውት የማያውቁትን ፀጉራቸውን ከትልቅ ዛፍ ላይ እያሠሩ ይጸልዩ ነበር፡፡ እንዲሁ አድርገው ዛፍ ላይ ራሳቸውን ሰቅለው 40 ቀንና 40 ሌሊት ሲጸልዩ በመጨረሻ የታሠሩበት ፀጉራቸው ተነቅሎ ከመሬት ላይ የወደቁት አባት ማን ይባላሉ?
Anonymous Quiz
18%
አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ
32%
አቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ
36%
አቡነ ሳሙኤል ዘቆይጻ
14%
አቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ሃሌሉያ
አቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ለሃገራችን ኢትዮጵያ የመጀመሪያው ሊቀ ጳጳስ ተደርገው የተሾሙበት ቀን መቼ ነው?
Anonymous Quiz
35%
መጋቢት 18
31%
መስከረም 18
23%
ጥቅምት 18
12%
ታኅሳስ 18
አቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ለሃገራችን ኢትዮጵያ ጳጳስ አድርገው ሹመው የላኩልን የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ማን ይባላሉ?
Anonymous Quiz
9%
ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ቴዎፍሎስ
17%
ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ቄርሎስ
57%
ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ አትናቴዎስ
17%
ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ እለእስክንድሮስ
በቁስጥንጥንያ የተሰበሰቡ የመቶ ሃምሳ ቅዱሳን ኤጲስቆጶሳት ሊቀ ጉባኤ ሆኖ መቅዶንዮስንና ሰባልዮስን አቡሊናርዮስንም የተከራከራቸው ቅዱስ አባት ማን ይባላል?
Anonymous Quiz
9%
የሮም ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ጢሞቴዎስ
45%
የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ጢሞቴዎስ
32%
ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ እለእስክንድሮስ
14%
ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ቴዎፍሎስ
አረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ ያረፈው ክብር ይግባውና ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋዊ(ሥጋን ከለበሰ)____ዓመት በኃላ ነው።
Anonymous Quiz
19%
ከ10 ዓመት
22%
ከ15 ዓመት
26%
ከ16 ዓመት
33%
ከ25 ዓመት
#ሐምሌ_27

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ሃያ ሰባት በዚህች ቀን ኢትዮጵያዊቷ #ቅድስት_መስቀል ክብራ ዕረፍቷ ነው፣

#ቅድስት_መስቀል_ክብራ

በዚህችም ቀን ኢትዮጵያዊቷ ቅድስት መስቀል ክብራ ዕረፍቷ ነው፡፡ ይኽችም ቅድስት የቅዱስ ላሊበላ ባለቤት ስትሆን የትውልድ ሀገሯ ወሎ ላስታ ቡግና ነው፡፡ የታላቁ ጻድቅ ንጉሥ የቅዱስ ላሊበላ ሚስት ናት፡፡ ከእርሱም ደገኛውን ይትባረክን ወልዳለች፡፡ ቅዱስ ላሊበላን እና ቅድስት መስቀል ክብራን ሁለቱ እንዲጋቡ ያዘዛቸው መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ቅዱስ ላሊበላን ወደ ሰማይ ነጥቆ ወስዶ የሚያንጻቸውውን የሕንጻ ዲዛኖችና ሌሎችንም ብዙ ምሥጢራትን ካሳየውና ወደ ምድር ከመለሰው በኃላ ድጋሚ ተገልጦለት "እንዳንተ የተመረጠች ናት እንደ ልብህም ትሆናለች፣ ሥራዋም ከሥራህ አያንስም እርሷ የተመረጠች የእግዚአብሔር አገልጋይ ናትና" በማለት መልአኩ የቅድስት መስቀል ክብራን ንጽሕናና ቅድስና መስክሮላታል፡፡

ቅዱስ ላሊበላ 11 እጅግ አስደናቂ የሆኑ ፍልፍል ቤተ መቅደሶቹን ከመላእክት ጋር ሲያንጽ ብታየው ልቧ በመንፈሳዊ ተመስጦ ተመልቶ እርሷም እግዚአብሔር ፈቅዶላት አስደናቂውን የአባ ሊባኖስን ቤተመቅደስ ራሷ እንዳነጸችው መጽሐፈ ገድሏና ገድለ ቅዱስ ላሊበላ ያስረዳል፡፡

ቅድስት መስቀል ክብራን ወደ ትግራይ እየመራ የወሰዳት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ እርሷን በትግራይ ቅዱስ ሚካኤል እንዲጠብቃት ከተዋት በኃላ ቅዱስ ላሊበላን ደግሞ ወደ ኢየሩሳሌምና ወደ መንግሥተ ሰማያት አውጥቶታል፡፡

ቅድስት መስቀል ክብራም በትግራይ ሆና መልአኩ እየጠበቃት ከሰው ተለይታ በታላቅ ተጋድሎ ኖረች፡፡ በቀን እልፍ እልፍ እየሰገደች በታላቅ ተጋድሎ ስትኖር ጌታችን ተገልጦ ክብሯ ከ36ቱ ቅዱሳት አንስት ጋር እኩል መሆኑን ነግሯታል፡፡

ይኽችም ቅድስት ብዙ ሐዋርያዊ አገልግሎት ፈጽማለች፡፡ ለምሳሌ በመስቀል ጦርነት ጊዜ እስላሞች ከባሕር ማዶ እየፈለሱ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ በፍቅር እየተቀበለችና እያስተናገደች ሃይማኖትንና ሕገ እግዚአብሔርን እያስተማረች ወደ ክርስትና እንደገቡና እንዱጠመቁ አድርጋለች፡፡

ቅድስት መስቀል ክብራም በትግራይ ክልል ሽሬ አውራጃ መደባይ ታብር በተባለው ቦታ ላይ በስማ የተሰራ ትልቅ ገዳም አላት። እጅግ ውብ በሆኑ ሰንሰላታማ ትላላልቅ ድንጋዮች መካከል የሚገኝ አስደናቂና ጥንታዊ ገዳም ነው። ገዳሙ ከሽሬ ከተማ በእግር የ 7 ሰዓት መንገድ ያስኬዳል።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት መስቀል ክብራ ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
2024/09/22 19:22:44
Back to Top
HTML Embed Code: