Telegram Web Link
#ነሐሴ_9

#አባ_ኦሪ

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዘጠኝ በዚች ቀን ስጥኑፍ ከሚባል አገር የከበረ ቄስ አባ ኦሪ ምስክር ሁኖ ሞተ። ይህ ቅዱስ ብዙ ርኅራኄ ያለው በሥጋው በነፍሱም ንጹሕ የሆነ ነው ብዙ ጊዜም አምላካዊ ራእይን ያያል። ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በመሠዊያው ላይ ታይቶ ብዙ ምሥጢራትን ገለጠለት።

ከዚህም በኋላ የአባ ኦሪ ዜናው በኒቅዮስ አገር መኰንን ዘንድ ተሰማ ወደርሱም አስቀርቦ ለአማልክት ዕጣን አቅርብ አለው እርሱም ለረከሱና ለተሠሩ አማልክት አልሠዋም ብሎ እምቢ አለው።

መኰንኑም ተቆጥቶ በብዙ ሥራ አስፈራራው ቅዱስ ኦሪም ሥቃዩን ምንም ምን አልፈራውም ጹኑ ሥቃይንም አሠቃየው። ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ አገር ላከው በዚያም ጽኑዕ የሆነ ሥቃይን አሠቃይተው በወህኒ ቤት ጣሉት። በዚያም ድንቆች ተአምራቶችን በማድረግ በሽተኞችን ፈወሳቸው ።

ዜናውም በተሰማ ጊዜ ደዌ ያለባቸው ሁሉ ከየአገሩ ብዙዎች ሰዎች ወደርሱ መጥተው አዳናቸው። ይህንንም መኰንኑ ሰምቶ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ በመንግስተ ሰማያትም የሰማዕትነትን አክሊል ተቀበለ።

ከዚህም በኋላ የከበረ ዮልዮስ ሥጋውን አንሥቶ ገንዘው ወደ ሀገሩ ስጥኑፍም ላከው። የመከራውም ወራት ካለፈ በኋላ ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያን ሠርተውለት ሥጋውን በውስጧ አኖሩ ከሥጋውም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። በማመንም ለሚመጡ በሽተኞች ሁሉ ታላቅ ፈውስ ሆነ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሱ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_9)
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነሐሴ_9_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ፊልጵስዩስ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹² ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ይህ የደረሰብኝ በእውነት ወንጌልን ለማስፋት እንደ ሆነ ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ።
¹³ ስለዚህም እስራቴ ስለ ክርስቶስ እንዲሆን በንጉሥ ዘበኞች ሁሉና በሌሎች ሁሉ ዘንድ ተገልጦአል፥
¹⁴ በጌታም ካሉት ወንድሞች የሚበዙት ስለ እስራቴ ታምነው የእግዚአብሔርን ቃል እንዲነግሩ ያለ ፍርሃት ከፊት ይልቅ ይደፍራሉ።
¹⁵ አንዳንዶች ከቅንአትና ከክርክር እንኳ ሌሎች ግን ከበጎ ፈቃድ የተነሣ ክርስቶስን ይሰብኩታል፤
¹⁶ እነዚህ ወንጌልን መመከቻ ለማድረግ እንደ ተሾምሁ አውቀው በፍቅር ይሰብካሉ፥
¹⁷ እነዚያ ግን በእስራቴ ላይ መከራን ሊያመጡብኝ መስሎአቸው፥ ለወገናቸው የሚጠቅም ፈልገው በቅን አሳብ ሳይሆኑ ስለ ክርስቶስ ያወራሉ።
¹⁸ ምን አለ? ቢሆንም በሁሉ ጎዳና፥ በማመካኘት ቢሆን ወይም በቅንነት ቢሆን፥ ክርስቶስ ይሰበካል ስለዚህም ደስ ብሎኛል።
¹⁹ ወደ ፊትም ደግሞ ደስ ይለኛል፤ ይህ በጸሎታችሁና በኢየሱስ ክርስቶስ መንፈስ መሰጠት ለመዳኔ እንዲሆንልኝ አውቃለሁና፥
²⁰ ይህ ናፍቆቴ ተስፋዬም ነውና፤ በአንድ ነገር እንኳ አላፍርም ነገር ግን በሕይወት ብኖር ወይም ብሞት፥ ክርስቶስ በግልጥነት ሁሉ እንደ ወትሮው አሁን ደግሞ በስጋዬ ይከብራል።
²¹ ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ፥ ሞትም ጥቅም ነውና።
²² ነገር ግን በስጋ መኖር ለእኔ የሥራ ፍሬ ቢሆን፥ ምን እንድመርጥ ኣላስታውቅም።
²³ በእነዚህም በሁለቱ እጨነቃለሁ፤ ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፥ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና፤
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
2ኛ ዮሐንስ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁶ እንደ ትእዛዛቱም እንሄድ ዘንድ ይህ ፍቅር ነው፤ ከመጀመሪያ እንደ ሰማችሁ፥ በእርስዋ ትሄዱ ዘንድ ትእዛዙ ይህች ናት።
⁷ ብዙ አሳቾች ወደ ዓለም ገብተዋልና እነርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ እንደ መጣ የማያምኑ ናቸው፤ ይህ አሳቹና የክርስቶስ ተቃዋሚው ነው።
⁸ ሙሉ ደመወዝን እንድትቀበሉ እንጂ የሠራችሁትን እንዳታጠፉ ለራሳችሁ ተጠንቀቁ።
⁹ ለሚወጣ ሁሉ በክርስቶስም ትምህርት ለማይኖር ሰው አምላክ የለውም፤ በክርስቶስ ትምህርት ለሚኖር አብና ወልድ አሉት።
¹⁰ ማንም ወደ እናንተ ቢመጣ ይህንም ትምህርት ባያመጣ በቤታችሁ አትቀበሉት ሰላምም አትበሉት፤
¹¹ ሰላም የሚለው ሰው በክፉ ሥራው ይካፈላልና።
¹² እንድጽፍላችሁ የምፈልገው ብዙ ነገር ሳለኝ በወረቀትና በቀለም ልጽፈው አልወድም፥ ዳሩ ግን ደስታችሁ ፍጹም እንዲሆን ወደ እናንተ ልመጣ አፍ ለአፍም ልናገራችሁ ተስፋ አደርጋለሁ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 15
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁹ ስለዚህ ከአሕዛብ ወደ እግዚአብሔር የዞሩትን እንዳናስቸግራቸው፥
²⁰ ነገር ግን ከጣዖት ርኵሰትና ከዝሙት ከታነቀም ከደምም ይርቁ ዘንድ እንድንጽፍላቸው እቈርጣለሁ።
²¹ ሙሴስ ከቀደሙት ትውልድ ጀምሮ በሰንበት በሰንበት በምኵራቦቹ ሲያነቡ በየከተማው እርሱን የሚሰብኩ አሉት።
²² ያን ጊዜ ሐዋርያትና ሽማግሌዎች ከቤተ ክርስቲያኑ ሁሉ ጋር ከእነርሱ የተመረጡትን ሰዎች ከጳውሎስና ከበርናባስ ጋር ወደ አንጾኪያ ይልኩ ዘንድ ፈቀዱ፤ እነርሱም በወንድሞች መካከል ዋናዎች ሆነው በርስያን የተባለው ይሁዳና ሲላስ ነበሩ።
²³ እንዲህም ጽፈው በእነርሱ እጅ ላኩ። ሐዋርያትና ሽማግሌዎች ወንድሞችም በአንጾኪያና በሶርያ በኪልቅያም ለሚኖሩ ከአሕዛብ ወገን ለሆኑ ወንድሞች ሰላምታ ያቀርባሉ።
²⁴ ያላዘዝናቸው ሰዎች ከእኛ ወጥተው፦ ትገረዙ ዘንድና ሕግን ትጠብቁ ዘንድ ይገባችኋል ብለው ልባችሁን እያወኩ በቃል እንዳናወጡአችሁ ስለ ሰማን፥
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_9_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ወትቀውም ንግሥት በየማንከ። በአልባሰ ወርቅ ዑጽፍት ወኊብርት። ስምዒ ወለትየ ወርእዪ ወአጽምዒ ዕዝነኪ"። መዝ 44፥9-10።
"የንጉሦች ሴት ልጆች ለክብርህ ናቸው፤ በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች። ልጄ ሆይ፥ ስሚ እዪ ጆሮሽንም አዘንብዪ፤ ወገንሽን ያባትሽንም ቤት እርሺ"። መዝ 44፥9-10።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_9_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ዮሐንስ 10
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ወደ በጎች በረት በበሩ የማይገባ በሌላ መንገድ ግን የሚወጣ እርሱ ሌባ ወንበዴም ነው፤
² በበሩ የሚገባ ግን የበጎች እረኛ ነው።
³ ለእርሱ በረኛው ይከፍትለታል፤ በጎቹም ድምፁን ይሰሙታል፥ የራሱንም በጎች በየስማቸው ጠርቶ ይወስዳቸዋል።
⁴ የራሱንም ሁሉ ካወጣቸው በኋላ በፊታቸው ይሄዳል፥ በጎቹም ድምፁን ያውቃሉና ይከተሉታል፤
⁵ ከሌላው ግን ይሸሻሉ እንጂ አይከተሉትም፥ የሌሎችን ድምፅ አያውቁምና።
⁶ ኢየሱስ ይህን ምሳሌ ነገራቸው፤ እነርሱ ግን የነገራቸው ምን እንደ ሆነ አላስተዋሉም።
⁷ ኢየሱስም ደግሞ አላቸው፦ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ እኔ የበጎች በር ነኝ።
⁸ ከእኔ በፊት የመጡ ሁሉ ሌቦችና ወንበዴዎች ናቸው፤ ዳሩ ግን በጎቹ አልሰሙአቸውም።
⁹ በሩ እኔ ነኝ፤ በእኔ የሚገባ ቢኖር ይድናል፥ ይገባልም ይወጣልም መሰማርያም ያገኛል።
¹⁰ ሌባው ሊሰርቅና ሊያርድ ሊያጠፋም እንጂ ስለ ሌላ አይመጣም፤ እኔ ሕይወት እንዲሆንላቸው እንዲበዛላቸውም መጣሁ።
¹¹ መልካም እረኛ እኔ ነኝ። መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል።
¹² እረኛ ያልሆነው በጎቹም የእርሱ ያልሆኑ ሞያተኛ ግን ተኵላ ሲመጣ ባየ ጊዜ በጎቹን ትቶ ይሸሻል፤ ተኵላም ይነጥቃቸዋል በጎቹንም ይበትናቸዋል።
¹³ ሞያተኛ ስለ ሆነ ለበጎቹም ስለማይገደው ሞያተኛው ይሸሻል።
¹⁴-¹⁵ መልካም እረኛ እኔ ነኝ፥ አብም እንደሚያውቀኝ እኔም አብን እንደማውቀው የራሴን በጎች አውቃለሁ የራሴም በጎች ያውቁኛል፤ ነፍሴንም ስለ በጎች አኖራለሁ።
¹⁶ ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምፄንም ይሰማሉ፥ አንድም መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ።
¹⁷ ነፍሴን ደግሞ አነሣት ዘንድ አኖራለሁና ስለዚህ አብ ይወደኛል።
¹⁸ እኔ በፈቃዴ አኖራታለሁ እንጂ ከእኔ ማንም አይወስዳትም። ላኖራት ሥልጣን አለኝ ደግሞም ላነሣት ሥልጣን አለኝ ይህችን ትእዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ።
¹⁹ እንግዲህ ከዚህ ቃል የተነሣ በአይሁድ መካከል እንደ ገና መለያየት ሆነ።
²⁰ ከእነርሱም ብዙዎች፦ ጋኔን አለበት አብዶአልም፤ ስለ ምንስ ትሰሙታላችሁ? አሉ።
²¹ ሌሎችም፦ ይህ ጋኔን ያለበት ሰው ቃል አይደለም፤ ጋኔን የዕውሮችን ዓይኖች ሊከፍት ይችላልን? አሉ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #እመቤታች_የማርያም_ቅዳሴ ነው። መልካም የእመቤታችን የጽንሰት በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነሐሴ_10

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥር በዚህች ቀን የታላቁ ጻድቅና ገዳማዊ #አባ_ዓቢየ_እግዚእ ዓመታዊ የተአምር በዓል ነው፣ #ቅዱስ_መጥራ በሰማዕትነት ሞተ፣ #ቅዱስ_ሐርስጥፎሮስ በሰማዕትነት ሞተ፣ የከበሩ #ቅዱሳን_ቢካቦስና_ዮሐንስ በሰማዕትነት ሞቱ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_ዓቢየ_እግዚእ_ኢትዮዽያዊ

ነሐሴ ዐሥር በዚህች ቀን የታላቁ ጻድቅና ገዳማዊ አባ ዓቢየ እግዚእ ዓመታዊ የተአምር በዓል ነው። አባ ዓቢየ እግዚእ የተወለዱት በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን ትግራይ ተንቤን (መረታ) ውስጥ ነው። የተባረኩ ወላጆቻቸው ያፍቅረነ እግዚእ እና ጽርሐ ቅድሳት ይባላሉ። አጥምቀው "ዓቢየ እግዚእ" ሲሉ ስም ያወጡላቸው የወቅቱ ጳጳስ ሰላማ መተርጉመ መጻሕፍት ናቸው። ትርጉሙም 'በጌታ ዘንድ ታላቅ ሰው' ማለት ነው።

ዓቢየ እግዚእ በሕፃንነታቸው ሌሊት ሌሊት ባሕር ውስጥ ሰጥመው ሲጸልዩ አድረው ቀን ቀን እየተማሩ ብሉይ ከሐዲስ ጠነቀቁ። ገና በወጣትነታቸው ወደ ታላቁ መነኮስ አቡነ መድኃኒነ እግዚእ (ደብረ በንኮል) ሔደው መንኩሰዋል።

በገዳሙ በጾም በጸሎትና በስግደት ተወስነው ከኖሩ በኋላ ወደ ዋልድባ ሔደው የተሰወረች ቤተ ክርስቲያን አግኝተዋል። በጊዜው በአርባ ቀን አንዲት ቅጠል ብቻ ለቁመተ ሥጋ ይበሉ ነበር።

ከዚያም ወደ ሃገራቸው ተንቤን ተመልሰው ዛሬም ድረስ ድንቅ ሆኖ የሚታየውን ገዳም መሥርተው ብዙ መናንያንን አፍርተዋል። ዓቢየ እግዚእ ገዳማዊና ጻድቅ ብቻ ሳይሆን ሐዋርያዊ አባትም ነበሩ። ከትግራይ እስከ ደንቢያ ደግሞ ሃገረ ስብከታቸው ነው።

አንድ ጊዜ ደቀ መዛሙርትን አስከትለው ለስብከት ሲንቀሳቀሱ ተከዜ ወንዝ አካባቢ ደረሱ። ቀኑ ነሐሴ ዐሥር ነውና ተከዜ እስከ ገደፉ ሞልቶ ለሦስት ቀናት ባለመጉደሉ ከአንድ ሺ በላይ ሰዎች ሲያለቅሱ ደረሱ። ጻድቁ በአካባቢው የነበሩት ኢ-አማንያን (አሕዛብ) ቢሆኑም ራርተዋልና "አምላከ ሙሴ" ብለው ጸልየው ወደ ጥልቁ ውስጥ ገቡ።

ቅዱስ ሚካኤል አብሯቸው ነበርና ተከዜ ግራና ቀኝ ተከፍሎ መሃሉ የብስ ሆነ። ይሕን ድንቅ ያዩ ከዘጠኝ መቶ አርባ በላይ አሕዛብም አምነው በጻድቁ እጅ ተጠምቀዋል። ይሕም ዘወትር ነሐሴ ዐሥር ቀን በቤተ ክርስቲያናቸው (ጐንደር) ይከበራል።

ከዚያም እያስተማሩ ጐንደር ደረሱ። ያኔ ጐንደር በቀሃና አንገረብ ወንዞች የታጠረች አንዲት መንደር ነበረች። ጻድቁ ቀን ቀን እየሰበኩ ማታ ዛሬ ቤተ ክርስቲያናቸው የታነጸበት ሥፍራ ላይ ሲጸልዩ ያድሩ ነበር።

በዚያ ዘመን ጐንደር ውስጥ ጅብ እባብና መሠል አራዊት ገብተው ሕዝቡን ጨረሱት። ይሕንን የተመለከቱት አባ ዓቢየ እግዚእ ወደ እግዚአብሔር አለቀሱ። በፍጹም ልባቸውም ስለ ሕዝቡ ለመኑ። የለመኑትን የማይነሳ ጌታ ወደ ጻድቁ ቀርቦ "በስምሕ የተማጸኑ በቃል ኪዳንህ ያመኑ: በምድር አራዊት አይሠለጥኑባቸውም። በሰማይም እሳትን አያዩም። ጐንደርንም አራዊት ገብተው ሰውን አይጐዱም።" ብሏቸው አርጓል።

አባ ዓቢየ እግዚእ በገዳማቸው ተንቤን ለብዙ ዘመናት በቅድስና ኑረው ሦስት ሙታንን አስነስተው ብዙ ድውያንን ፈውሰው ብሔረ ብጹዓንን ጎብኝተው የድኅነት ቃል ኪዳንም ተቀብለው በመቶ አርባ ዓመታቸው ግንቦት ዐሥራ ዘጠኝ ቀን አርፈዋል። የጻድቁ ክብር ለሁሉ ነውና እናስባቸው።

ይህች ዕለት ባሕረ ተከዜን ከፍለው ሕዝቡን ያሻገሩባት አሕዛብንም ያጠመቁባት ናትና በገዳማቸው ጐንደር ውስጥ በሚገኘው ቤተ ክርስቲያናቸውም ይከበራል።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጻድቁ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_መጥራ

በዚህች ቀን በእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት በቅዱስ ዲሜጥሮስ ዘመንና በከሀዲው ንጉሥ በዳኬዎስ ዘመነ መንግሥት ቅዱስ መጥራ በሰማዕትነት ሞተ።

ይህም ቅዱስ የክብር ባለቤት #ክርስቶስን ክደው ለጣዖት መስገድን የሚያዝ የንጉሡን ደብዳቤ በሰማ ጊዜ ይህ ቅዱስ ወዲያውኑ ሒዶ ከወርቅ የተሠራ የአጵሎንን ክንድ ሰረቀ በየጥቂቱም ሰባብሮና ቆራርጦ ለድኆችና ለችግረኞች ሰጣቸው።

የጣዖቱም አገልጋዮች ክንዱ ተቆርጦ አጵሎንን በአገኙት ጊዜ ስለርሱ ብዙዎችን ሰዎች ያዟቸው። በዚያንም ጊዜ ወደ መኰንኑ ቀርቦ ክርስቲያን እንደሆነ በፊቱ ታመነ ሁለተኛም የአጵሎንን የወርቅ ክንድ የወሰድኩ እኔ ነኝ ለድኆችና ለችግረኞችም ሰጠኃ ኋቸው አለው።

መኰንኑም በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጣ አስጨናቂ የሆነ ታላቅ ሥቃይንም አሠቃየው ከዚህም በኋላ ከእሳት ውስጥ ጨመሩት #እግዚአብሔርም አዳነው ያለ ጥፋትም በጤና አወጣው።

ከዚህም በኋላ እጆቹንና እግሮቹን ቆረጡ ብዙ ደም ከአፍንጫው ወደ ምድር እስከ ሚወርድ ዘቅዝቀው በዕንጨት ላይ ሰቀሉት።

በዚያንም ጊዜ የ #እግዚአብሔር መልአክ ወርዶ ቅዱስ መጥራንን ፈታው ከተሰቀለበትም አውርዶ በመዳሠሥ አዳነው። አንድ ዕውር ሰውም መጣ ከአፍንጫው ከወረደውም ደም ወስዶ ዐይኖቹን ቀባ ወዲያውኑ አየ። መኰንኑም ከማሠቃየቱ የተነሣ በሰለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። የምስክርነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀዳጀ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ መጥራ ጸሎት ይማረን በረከቱም ይደርብን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሐርስጥፎሮስ

በዚህችም ቀን ዳግመኛ በከሀዲ መክስምያኖስ እጅ ቅዱስ ሐርስጥፎሮስ በሰማዕትነት ሞተ። በንጉሥ መክስምያኖስ ፊት በአቆሙት ጊዜ ለአማልክት ሠዋ አለው። የከበረ ሐርስጥፎሮስም እንዲህ ብሎ መለሰለት እኔ #እግዚአብሔር_ኢየሱስ_ክርስቶስን አመልከዋለሁ ለእርሱም እሠዋለሁ። ንጉሡም ተቆጥቶ ሥጋው ተቆራርጦ በምድር ላይ እስቲወድቅ በበትር ይደበድቡት ዘንድ አዘዘ እንዲሁም አደረጉበት።

ከዚህም በኋላ ወደ ወህኒ ቤት ጣሉት በላህያቸውም እንዲአስቱት ሁለት ሴቶችን ንጉሡ ወደርሱ ላከ ቅዱሱ ግን የ #ክርስቶስን ሃይማኖት አስተማራቸው የዛሬ የሆነ የዚህንም ዓለም ኃላፊነት አስገነዘባቸው ወደ መክስምያኖስም በተመለሱ ጊዜ እንዴት አደረጋችሁ አላቸው።

እነርሱም እንዲህ አሉት በከበረ ሐርስጥፎሮስ አምላክ የክብር ባለቤት በሆነ በ #ክርስቶስ እኛ እናምናለን ንጉሡም ሰምቶ አንዲቱን በዕንጨት ላይ ሰቅለው እንዲአቃጥሏት ሁለተኛዋን በአንገቷ ደንጊያ አንጠልጥለው ቊልቊል እንዲሰቅሏት አዘዘና ምስክርነታቸውን እንዲህ ፈጸሙ።

ከዚህም በኋላ ዕንጨቶችን ሰብስበው በማንደጃው ውስጥ አድርገው አነደዱ የከበረ ሐርስጥፎሮስን እጅና እግሩ እንደ ታሠረ ከውስጡ ጨመሩት ያን ጊዜም በስመ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ አለ እሳቱ ከቶ ምንም አልነካውም። ሕዝቡም ይህን አይተው የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ዐሥር ሺህ ያህል ሰዎች አምነው በሰማዕትነት ሞቱ።

ሁለተኛም የብረት ሠሌዳዎችን በእሳት አግለው አመጡ ቅዱሱንም በላያቸው በአስተኙት ጊዜ ምንም ምን የነካው የለም። ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው በክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሃያ ሺህ አንድ መቶ ሰዎችና አርባ ሕፃናት አምነው ምስክር ሁነው ሞቱ።

ንጉሥ መክስምያኖስም አይቶ እጅግ ተቆጣ የቅዱስ ሐርስጥፎሮስንም ራስ በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። ከንጉሡም ዘንድ በወጣ ጊዜ ጸሎትን አደረገ ፊቱንም በ #መስቀል ምልክት አማተበ ከዚህም በኋላ ምስክርነቱን ፈጸመ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ሐርስጥፎስ እና በቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ይደርብን ለዘላለሙ አሜን።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱሳን_ቢካቦስና_ዮሐንስ

በዚህችም ቀን እስሙናይን ከሚባል አገር የከበሩ ቢካቦስና ዮሐንስ ሌሎችም ከእሳቸው ጋራ በሰማዕትነት ሞቱ። ይህም ቅዱስ ቢካቦስ ክርስቲያን ሲሆን በሥውር ወታደር ሆነ። አንጥያኮስ ለሚባል መኰንንም ስለ ዮሐንስና ስለ ኤጲስቆጶስ አባ አክሎግ ከተርሴስ አገር ስለ ናሕር ስለ አባ ፊልጶስም እነርሱ ክርስቲያኖች እንደሆኑ ነገር ሠሩባቸው።

መኰንኑም እነርሱን አቅርቦ እናንት ክርስቲያኖች ናችሁን አላቸው እኛ በእውነት ክርስቲያን ነን በሕያው #እግዚአብሔር ልጅ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ እናምናለን አሉት። መኰንኑም ይህን ነገር ትታችሁ ለአማልክት ሠዉ አላቸው።

ቅዱሳኑም እንዲህ ብለው መለሱለት እኛስ ለረከሱና ለተናቁ አማልክት አንሠዋም ሰማይና ምድርን ከፈጠረ ከ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ በቀር። መኰንኑም ሰምቶ እጅግ ተቆጣ ምስክርነታቸውንም እስከፈጸሙ ድረስ አሠቃያቸው።

ቅዱስ ቢካቦስን ግን ከአሠቃየው በኋላ አሠረውና ከመንኰራኲር ውስጥ ጨመረው ዘቅዝቆም ሰቀለው ሕዋሳቱንም ቆራረጠው #ጌታችንም ያስታግሠውና ያበረታው ነበር ያለ ጉዳትም ጤናማ አድርጎ አስነሳው።

ከዚህም በኋላ በርሙን ወደሚባል አገር ከብዙዎች ሰማዕታት ጋራ ላከው በመርከብም ውስጥ እህልና ውኃ ሳይቀምሱ ሃያ ስድስት ቀኖች ኖሩ። በርሙን ወደሚባል አገርም በደረሱ ጊዜ ጽኑ ሥቃይን አሠቃይተው በምሳር ቆረጡት የምስክርነቱንም ተጋድሎ ፈጸመ በመንግሥተ ሰማያትም አክሊልን ተቀበለ።

ከሀገረ በርሙን ሹማምንቶችም አንድ ባለ ጸጋ ሰው መጥቶ የቅዱስ ቢካቦስን ሥጋ ወስዶ በአማሩ ልብሶች ገነዘው ወደ አገሩ እስሙናይንም ላከው። በመከራውም ወራት ቊጥር የሌላቸው ብዙዎች ሰዎች በሰማዕትነት ሞቱ ከእርሱም ጋራ የተገደሉ ዘጠና አምስት ሰዎች ናቸው።

ከዚህም በኋላ ለቅዱሱ ቤተ ክርስቲያን ሠርተውለት ሥጋውን በውስጧ አኖሩ ከእርሱም ብዙ ድንቅ ተአምር ተገለጠ።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሱ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_10 እና #ዲያቆን_ዮርዳኖስ_አበበ)
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነሐሴ_10_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ዕብራውያን 10
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²² ከክፉ ሕሊና ለመንጻት ልባችንን ተረጭተን ሰውነታችንንም በጥሩ ውኃ ታጥበን በተረዳንበት እምነት በቅን ልብ እንቅረብ፤
²³ የተስፋን ቃል የሰጠው የታመነ ነውና እንዳይነቃነቅ የተስፋችንን ምስክርነት እንጠብቅ፤
²⁴ ለፍቅርና ለመልካምም ሥራ እንድንነቃቃ እርስ በርሳችን እንተያይ፤
²⁵ በአንዳንዶችም ዘንድ ልማድ እንደ ሆነው፥ መሰብሰባችንን አንተው እርስ በርሳችን እንመካከር እንጂ፤ ይልቁንም ቀኑ ሲቀርብ እያያችሁ አብልጣችሁ ይህን አድርጉ።
²⁶ የእውነትን እውቀት ከተቀበልን በኋላ ወደን ኃጢአት ብናደርግ ከእንግዲህ ወዲህ ስለ ኃጢአት መሥዋዕት አይቀርልንምና፥
²⁷ የሚያስፈራ ግን የፍርድ መጠበቅ ተቃዋሚዎችንም ሊበላ ያለው የእሳት ብርታት አለ።
²⁸ የሙሴን ሕግ የናቀ ሰው ሁለት ወይም ሦስት ቢመሰክሩበት ያለ ርኅራኄ ይሞታል፤
²⁹ የእግዚአብሔርን ልጅ የረገጠ ያንንም የተቀደሰበትን የኪዳኑን ደም እንደ ርኵስ ነገር የቆጠረ የጸጋውንም መንፈስ ያክፋፋ፥ እንዴት ይልቅ የሚብስ ቅጣት የሚገባው ይመስላችኋል?
³⁰ በቀል የእኔ ነው፥ እኔ ብድራትን እመልሳለሁ ያለውን እናውቃለንና፤ ደግሞም፦ ጌታ በሕዝቡ ይፈርዳል።
³¹ በሕያው እግዚአብሔር እጅ መውደቅ የሚያስፈራ ነው።
³²-³³ ነገር ግን ግማሽ በነቀፋና በጭንቅ እንደ መጫወቻ ስለ ሆናችሁ ግማሽም እንዲህ ካሉት ጋር ስለ ተካፈላችሁ፥ ብርሃን ከበራላችሁ በኋላ መከራ በሆነበት በትልቅ ተጋድሎ የጸናችሁበትን የቀደመውን ዘመን አስቡ።
³⁴ የሚበልጥና ለዘወትር የሚኖር ገንዘብ በሰማይ ራሳችሁ እንዳላችሁ አውቃችሁ፥ በእስራቴ ራራችሁልኝ የገንዘባችሁንም ንጥቂያ በደስታ ተቀበላችሁ።
³⁵ እንግዲህ ታላቅ ብድራት ያለውን ድፍረታችሁን አትጣሉ።
³⁶ የእግዚአብሔርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን የተስፋ ቃል እንድታገኙ መጽናት ያስፈልጋችኋልና።
³⁷ ገና በጣም ጥቂት ጊዜ ነው፥ ሊመጣ ያለውም ይመጣል አይዘገይምም፤
³⁸ ጻድቅ ግን በእምነት ይኖራል ወደ ኋላም ቢያፈገፍግ፥ ነፍሴ በእርሱ ደስ አይላትም።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ጴጥሮስ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁶-⁷ በዚህም እጅግ ደስ ይላችኋል፥ ነገር ግን በእሳት ምንም ቢፈተን ከሚጠፋው ወርቅ ይልቅ አብልጦ የሚከብር የተፈተነ እምነታችሁ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ፥ ለምስጋናና ለክብር ለውዳሴም ይገኝ ዘንድ አሁን ለጥቂት ጊዜ ቢያስፈልግ በልዩ ልዩ ፈተና አዝናችኋል።
⁸-⁹ እርሱንም ሳታዩት ትወዱታላችሁ፤ አሁንም ምንም ባታዩት በእርሱ አምናችሁ፥ የእምነታችሁን ፍፃሜ እርሱም የነፍሳችሁን መዳን እየተቀበላችሁ፥ በማይነገርና ክብር በሞላበት ሐሤት ደስ ይላችኋል።
¹⁰ ለእናንተም ስለሚሰጠው ጸጋ ትንቢት የተናገሩት ነቢያት ስለዚህ መዳን ተግተው እየፈለጉ መረመሩት፤
¹¹ በእነርሱም የነበረ የክርስቶስ መንፈስ፥ ስለ ክርስቶስ መከራ ከእርሱም በኋላ ስለሚመጣው ክብር አስቀድሞ እየመሰከረ፥ በምን ወይም እንዴት ባለ ዘመን እንዳመለከተ ይመረምሩ ነበር።
¹² ለእነርሱም ከሰማይ በተላከ በመንፈስ ቅዱስ ወንጌልን የሰበኩላችሁ ሰዎች አሁን ባወሩላችሁ ነገር እናንተን እንጂ ራሳቸውን እንዳላገለገሉ ተገለጠላቸው፤ ይህንም ነገር መላእክቱ ሊመለከቱ ይመኛሉ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 4
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
³¹ ከጸለዩም በኋላ ተሰብስበው የነበሩበት ስፍራ ተናወጠ፥ በሁሉም መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው፥ የእግዚአብሔርንም ቃል በግልጥ ተናገሩ።
³² ያመኑትም ሕዝብ አንድ ልብ አንዲትም ነፍስ ነበሩአቸው፥ ገንዘባቸውም ሁሉ በአንድነት ነበረ እንጂ ካለው አንድ ነገር ስንኳ የራሱ እንደ ሆነ ማንም አልተናገረም።
³³ ሐዋርያትም የጌታን የኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ በታላቅ ኃይል ይመሰክሩ ነበር፤ በሁሉም ላይ ታላቅ ጸጋ ነበረባቸው።
³⁴ በመካከላቸው አንድ ስንኳ ችግረኛ አልነበረምና፤ መሬት ወይም ቤት ያላቸው ሁሉ እየሸጡ የተሸጠውን ዋጋ ያመጡ ነበርና፥
³⁵ በሐዋርያትም እግር አጠገብ ያኖሩ ነበር፤ ማናቸውም እንደሚፈልግ መጠን ለእያንዳንዱ ያካፍሉት ነበር።
³⁶ ትውልዱም የቆጵሮስ ሰው የነበረ አንድ ሌዋዊ ዮሴፍ የሚሉት ነበረ፥ እርሱም በሐዋርያት በርናባስ ተባለ ትርጓሜውም የመጽናናት ልጅ ነው፤
³⁷ እርሻም ነበረውና ሽጦ ገንዘቡን አምጥቶ ከሐዋርያት እግር አጠገብ አኖረው።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_10_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ተዘከር ማኅበረከ ዘአቅደምከ ፈጢረ፡፡ ወአድኀንከ በትረ ርስትከ። ደብረ ጽዮን ዘኀደርከ ውስቴታ"። መዝ 73፥2-3።
“አስቀድመህ የፈጠርሃትን ማኅበርህን፥ የተቤዤሃትንም የርስትህን በትር፥ በእርስዋ ያደርህባትን የጽዮንን ተራራ አስብ።” መዝ 73፥2-3።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_10_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሉቃስ 16
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁹ እኔም እላችኋለሁ፥ የዓመፃ ገንዘብ ሲያልቅ በዘላለም ቤቶች እንዲቀበሉአችሁ፥ በእርሱ ወዳጆችን ለራሳችሁ አድርጉ።
¹⁰ ከሁሉ በሚያንስ የታመነ በብዙ ደግሞ የታመነ ነው፥ ከሁሉ በሚያንስም የሚያምፅ በብዙ ደግሞ ዓመፀኛ ነው።
¹¹ እንግዲያስ በዓመፃ ገንዘብ ካልታመናችሁ፥ እውነተኛውን ገንዘብ ማን አደራ ይሰጣችኋል?
¹² በሌላ ሰው ገንዘብ ካልታመናችሁ፥ የእናንተን ማን ይሰጣችኋል?
¹³ ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ባርያ ማንም የለም፤ ወይም አንዱን ይጠላልና ሁለተኛውንም ይወዳል፥ ወይም ወደ አንዱ ይጠጋል ሁለተኛውንም ይንቃል። ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም።
¹⁴ ገንዘብንም የሚወዱ ፈሪሳውያን ይህን ሁሉ ሰምተው ያፌዙበት ነበር።
¹⁵ እንዲህም አላቸው፦ ራሳችሁን በሰው ፊት የምታጸድቁ እናንተ ናችሁ፥ ነገር ግን እግዚአብሔር ልባችሁን ያውቃል፤ በሰው ዘንድ የከበረ በእግዚአብሔር ፊት ርኵሰት ነውና።
¹⁶ ሕግና ነቢያት እስከ ዮሐንስ ነበሩ፤ ከዚያ ጀምሮ የእግዚአብሔር መንግሥት ይሰበካል፤ ሁሉም ወደ እርስዋ በኃይል ይገቡባታል።
¹⁷ ነገር ግን ከሕግ አንዲት ነጥብ ከምትወድቅ ሰማይና ምድር ሊያልፍ ይቀላል።
¹⁸ ሚስቱንም የሚፈታ ሁሉ ሌላይቱንም የሚያገባ ያመነዝራል፥ ከባልዋም የተፈታችውን የሚያገባ ያመነዝራል።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #እመቤታች_የማርያም_ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነሐሴ_11

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥራ አንድ በዚህች ቀን #አባ_ሞይስስ አረፈ፣ #የቅዱስ_ፋሲለደስ_ማኅበርተኞች በሰማዕትነት ሞቱ፣ #ቅዱስ_አብጥልማዎስ በሰማዕትነት ሞተ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ኤጲስቆጶስ_አባ_ሞይስስ

ነሐሴ ዐሥራ አንድ በዚህች ቀን የአውሲም አገር ኤጲስቆጶስ አባ ሞይስስ አረፈ። ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ ንጹሕ ድንግልም ነበረ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትንም ሁሉ ተምሮ ዲቁና ተሾመ። ከዚህም በኋላ ወጥቶ ወደ አስቄጥስ ገዳም ገባ። በአንድ ጻድቅ ሰው ዘንድም መነኰሰ በዚያም እያገለገለ በጠባብዋ መንገድም ተጠምዶ ያለመብልና መጠጥ ያለእንቅልፍም እየተጋደለ ዐሥራ ስምንት ዓመት ኖረ።

ከብዙ ፍቅርና ትሕትና ጋር ዘወትር በጾምና በጸሎት ይተጋ ነበር። ትሩፋቱም በበዛ ጊዜ ከአባ ገሞስ በኋላ በአውሲም ከተማ ኤጲስቆጶስ ይሆን ዘንድ #እግዚአብሔር መረጠው። ይህም አባ ሞይስስ በተሾመ ጊዜ ትሩፋት መሥራትን አብዝቶ ጨመረ ስለ እነርሱም በጸሎት እየተጋ መንጋዎቹን ነጣቂዎች ከሆኑ ከዲያብሎስ ተኲላዎች ጠበቀ።

በሕይወቱም ዘመን ሁሉ ከዚህ ከኃላፊው ዓለም ገንዘብ የሚሰበስብ አልነበረም። አባ ሚካኤልም በእስክንድርያ ከተማ ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜና ደሙ ሳይፈስ ሰማዕት በሆነ ጊዜ ይህ አባ ሞይስስ በእሥር ቤት ከእርሱ ጋር ነበር ብዙ ስለገረፉት እግሮቹንም ለረጅም ጊዜ በእግር ብረት አሥረው ስለ አሠቃዩት ብዙ መከራ ደረሰበት።

በዚህ አባት ሞይስስ እጅም #እግዚአብሔር ብዙዎች ድንቆችንና ተአምራቶችን አደረገ የሚያውቁትም በተአምራቶቹ ደግነቱንና ትሩፋቱን ተረዱ። ዳግመኛም ሀብተ ትንቢት የተሰጠው ከመሆኑም በፊት ብዙ ነገርን ተናገረ እንደተናገረውም ይሆን ነበር። የምስር ኤጲስቆጶስ ስለሆነው ስለ አባ ቴዎድሮስ ከሔደበት እንደማይመለስ ትንቢት ተናግሮበት እንዲሁ ተፈጸመበት።

ዳግመኛም ሀብተ ፈውስ ተሰጥቶት ነበር። ብዙዎች ሕሙማንንም ፈወሳቸው። ገድሉንም በመልካም ሽምግልና ፈጸመ። #እግዘአብሔርንም አገልግሎ ጥቂት ታመመ የሚያርፍበትንም ጊዜ አውቆ ሕዝቡን ጠራቸውና ባረካቸው በቀናች ሃይማኖትም ጸንተው እንዲኖሩ አዘዛቸው። ከዚህም በኋላ አረፈ። አለቀሱለትም ለኤጲስቆጶሳትም እንደሚገባ በዝማሬና በማኀሌት በታላቅ ክብር ገንዘው ቀበሩት ከሥጋውም ታላላቅ ተአምራቶች ተገለጡ ለሕሙማንም የሚሆን ፈውስ ተገለጠ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ፋሲለደስ_ማኅበርተኞች

በህች ቀን በአንጾኪያ ከተማ የሠራዊት አለቃ ከነበረው ከቅዱስ ፋሲለደስ ጋራ ሦስት መቶ ሰዎች በማዕትነት ሞቱ።

ከሃዲው ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ በሚገዛበት አገር ሁሉ ክርስቶስን ያልካዱትን ምእመናን ማስገደልና ማሳደድ ጀመረ፡፡ ብዙ ሰማዕታትም ወደ ንጉሡ የሰማዕትነት አዳባባይ እየመጡ በ #ጌታችን ስም ደማቸውን አፈሰሱ፡፡ ቅዱስ ፋሲለደስም ሰማዕት ይሆን ዘንድ ወደ #ጌታችን ይጸልይ ጀመር፡፡ በመኝታም ሳለ ቅዱስ ሚካኤል ታዞ ወደ እርሱ መጥቶ ሰላምታ ሰጠውና ‹‹በምድር አለቃ ሆነህ ሆነህ ሁሉን እንደምታዝ በሰማይም የ #ክርስቶስ ወታደሮቹ የሆኑ የሰማዕታት አለቃ ሆነሃልና ደስ ይበልህ›› አለው፡፡ ዳግመኛም ‹‹ወደ #ጌታህ ዘንድ አደርስህ ዘንድ ተነሥ›› አለውና በክንፎቹ ተሸክሞ ወደ ሰማይ አሳረገውና በ #ጌታችን ፊት አቆመው፡፡ #ጌታችንም ለቅዱስ ፋሲለደስ ሰላምታ ከሰጠው በኋላ ስለ ስሙ ይቀበል ዘንድ ስላለው መከራና በሰማይም ስለሚያገኘው ክብር ነገረው፡፡ ሰማዕታት ይሆኑ ያላቸውንም ሁሉን ስማቸውን እየጠራ ነገረው፡፡ አባድርና እኅቱ ኢራኒ፣ የህርማኖስ ልጅ ፊቅጦር፣ ምሥራቃዊ ቴዎድሮስ፣ ገላውዴዮስ፣ አራቱም ልጆቹ አውሳብዮስና መቃርስ እንዲሁም ሁለቱ ሴቶች ልጆቹ፣ የንጉሡ ልጅ ዮስጦስና አቦሊ ሚስቱም ታውክልያ… እነዚህንና ሌሎቹንም ሁሉ ስማቸውን እየጠራ #ጌታችን ሰማዕት እንደሚሆኑ ለቅዱስ ፋሲለደስ ነገረው፡፡ እርሱ ግን ከብዙ ተጋድሎ በኋላ ሰማዕት እንደሚሆን ነገረው፡፡ በሌሎቹ ሰማዕታትም ሆነ በእርሱ ላይ የሚደረስበትን መከራ እና በኋላም የሚያገኙትን ክብር ሁሉ በዝርዝር ነገረው፡፡ ብዙ ቃልኪዳንም ገባለት፡፡ የሰማዕታትንና የቅዱሳንን መኖሪያ ካሳየው በኋላ ሰማዕትነቱን ሲፈጽም የሚያገኘውን ክብር መሆኑን ነግሮት በገነት ውኃ በምለአኩ እጅ እንዲጠመቅ ካደረገው በኋላ ወደ ምድር መለሰው፡፡ ከዚህም በኋላ ንጉሡ ብዙዎቹን ታላላቅ ሰማዕታት እጅግ አሠቃይቶ ሁሉንም በየተራ ገደላቸው፡፡ ቅዱስ ፋሲለደስን ግን አምስት ከተማዎች ወዳሉበት አፍሪካ ላኩት፡፡ በዚያም ብዙ እጅግ አሠቃቂ ሥቃዮችን አደረሱበት፡፡ ከእርሱ ጋር ያመኑ ከ7 ሺህ በላይ ክርስቲያኖችን ሰየፏቸው፡፡ ቅዱስ ፋሲለደስንም ሰውነቱን በመንኰራኩር ፈጭተው በመጋዝ ሰነጣጥቀው ገደሉት፡፡ ነገር ግን #ጌታችን ከሞት አስነሣው፡፡ እጅግ ብዙ አሕዛብም በአምላከ ፋሲለደስ አመኑ፡፡ ጣዖቶቻቸውንም ረገሙባቸው፡፡ በዚህም ወቅት 14ሺህ 737 ሰዎችን አንገታቸውን በሰይፍ ቆረጧቸው፡፡ ሰማዕትነታቸውንም ፈጸሙ፡፡ ቅዱስ ፋሲለደስን ዳግመኛ በምጣድ ላይ አስተኝተው እሳት አነደደዱበት፡፡ በተራራ ላይ ጥልቅ ጉድጓድ ቆፍረው በዚያ ቀበሩት፡፡ አሁንም #ጌታችን ከሞት አስነሥቶት በመኰንኑ ፊት እንዲቆም አደረገው፡፡ ንጉሡንም ‹‹አምላኬ ፍጹም ጤነኛ አድርጎ አስነሥቶኛልና እፈር፣ የረከሱ ጣዖቶችህም ይፈሩ›› አለው፡፡ ሕዝቡም ይህን ተአምር ባዩ ጊዜ በ #ጌታችን አምነው አንገታቸውን ተሰይፈው በሰማዕትነት ሞቱ፡፡ ቁጥራቸውም 2300 ነበሩ፡፡ ቅዱስ ፋሲለደስንም ደግመኛ ሰውነቱን በመንኰራኩር ከፈጩት በኋላ በብረት ምጣድ ላይ አስተኝተው ከሥሩ እሳት አነደዱበት፡፡ #ጌታችንም ከቁስሉ ፈውሶት ትልቅ ቃልኪዳን ሰጠውና ሰማዕትነቱን በትዕግስት እንዲፈጽም ነገረው፡፡ ንጉሡም አማካሪዎቹን ምን ማድረግ እንዳለበት ሲያማክራቸው ‹‹ፋሲለደስን ምንም ብናሠቃየው ሊሞት አልቻለም በእርሱም ምክንያት የሀገሩ ሰዎች ሁሉ አልቀዋልና ራሱን ቆርጠን ብንጥለው ይሻላል›› አሉት፡፡ መኰንኑም ራሱን እንዲቆርጡት አዘዘና ቅዱስ ፋሲለደስ መስከረም 11 ቀን ሰማዕትነቱን ፈጸመ፡፡ የቅዱስ ፋሲለደስ ማኅበርተኞች ቁጥራቸው 2 ሺህ ሰባት ሰዎች መስከረም 7 ቀን ዐረፉ፡፡ እንዲሁም መስከረም 9 ቀን ቁጥራቸው 14 ሺህ 737 ማኅበርተኞቹ በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ የሰማዕታቱ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አብጥልማዎስ_ሰማዕት

በዚችም ቀን ከላይኛው ግብጽ ከመኑፍ ከተማ ቅዱስ አብጥልማዎስ በሰማዕትነት ሞተ። ይህንንም ቅዱስ ክርስቲያን እንደሆነ በመኰንኑ ዘንድ ነገር ሠሩበት።

መኰንኑም በአስቀረበው ጊዜ በፊቱ ክብር ይግባውና በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ታመነ ጽኑዕ የሆነ ሥቃይንም አሠቃይቶ ራሱን በሰይፍ አስቆረጠው የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታቱ ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_11 እና #ከገድላት_አንደበት)
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነሐሴ_11_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ቆሮንቶስ 5
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹¹ አሁን ግን ወንድሞች ከሚባሉት አንዱ ሴሰኛ ወይም ገንዘብን የሚመኝ ወይም ጣዖትን የሚያመልክ ወይም ተሳዳቢ ወይም ሰካር ወይም ነጣቂ ቢሆን ከእርሱ ጋር እንዳትተባበሩ እጽፍላችኋለሁ፤ እንደነዚህ ካለው ጋር መብል እንኳን አትብሉ።
¹² በውጭ ባሉ ሰዎች ላይ መፍረድ ምን አግዶኝ? በውስጥ ባሉ ሰዎች ላይ እናንተ አትፈርዱምን?
¹³ በውጭ ባሉቱ ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል። ክፉውን ከመካከላችሁ አውጡት።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ዮሐንስ 2
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁴ አባቶች ሆይ፥ ከመጀመሪያ የነበረውን አውቃችኋልና እጽፍላችኋለሁ። ጐበዞች ሆይ፥ ብርቱዎች ስለ ሆናችሁ የእግዚአብሔርም ቃል በእናንተ ስለሚኖር ክፉውንም ስለ አሸነፋችሁ እጽፍላችኋለሁ።
¹⁵-¹⁶ ዓለምን ወይም በዓለም ያሉትን አትውደዱ፤ በዓለም ያለው ሁሉ እርሱም የሥጋ ምኞትና የዓይን አምሮት ስለ ገንዘብም መመካት ከዓለም ስለ ሆነ እንጂ ከአባት ስላልሆነ፥ ማንም ዓለምን ቢወድ የአባት ፍቅር በእርሱ ውስጥ የለም።
¹⁷ ዓለሙም ምኞቱም ያልፋሉ፤ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ ግን ለዘላለም ይኖራል።
¹⁸ ልጆች ሆይ፥ መጨረሻው ሰዓት ነው፥ የክርስቶስም ተቃዋሚ ይመጣ ዘንድ እንደ ሰማችሁ አሁን እንኳ ብዙዎች የክርስቶስ ተቃዋሚዎች ተነሥተዋል፤ ስለዚህም መጨረሻው ሰዓት እንደ ሆነ እናውቃለን።
¹⁹ ከእኛ ዘንድ ወጡ፥ ዳሩ ግን ከእኛ ወገን አልነበሩም፤ ከእኛ ወገንስ ቢሆኑ ከእኛ ጋር ጸንተው በኖሩ ነበር፤ ነገር ግን ሁሉ ከእኛ ወገን እንዳልሆኑ ይገለጡ ዘንድ ወጡ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 12
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁸ በነጋም ጊዜ፦ ጴጥሮስን ምን አግኝቶት ይሆን? ብለው በጭፍሮች ዘንድ ብዙ ሁከት ሆነ።
¹⁹ ሄሮድስም አስፈልጎ ባጣው ጊዜ ጠባቂዎችን መረመረ ይገድሉአቸውም ዘንድ አዘዘ፤ ከይሁዳም ወደ ቂሣርያ ወርዶ በዚያ ተቀመጠ።
²⁰ ከጢሮስና ከሲዶና ሰዎችም ጋር ተጣልቶ ነበር፤ በአንድ ልብ ሆነውም ወደ እርሱ መጡ፥ የንጉሥንም ቢትወደድ ብላስጦስን እሺ አሰኝተው ዕርቅ ለመኑ፥ አገራቸው ከንጉሥ አገር ምግብ ያገኝ ነበረና።
²¹ በተቀጠረ ቀንም ሄሮድስ ልብሰ መንግሥቱን ለብሶ በዙፋን ተቀመጠ እነርሱንም ተናገራቸው፤
²² ሕዝቡም፦ የእግዚአብሔር ድምፅ ነው የሰውም አይደለም ብለው ጮኹ።
²³ ለእግዚአብሔርም ክብር ስላልሰጠ ያን ጊዜ የጌታ መልአክ መታው በትልም ተበልቶ ሞተ።
²⁴ የእግዚአብሔር ቃል ግን ያድግና ይበዛ ነበር።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_11_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ህየንተ አበውኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ። ወትሠይም(ሚ)ዮሙ መላእክተ በኵሉ ምድር። ወይዘክሩ ስመኪ በኵሉ ትውልደ ትውልድ"። መዝ 44፥16-17።
"በአባቶችሽ ፋንታ ልጆች ተወለዱልሽ፥ በምድርም ሁሉ ላይ ገዥዎች አድርገሽ ትሾሚያቸዋለሽ። ለልጅ ልጅ ሁሉ ስምሽን ያሳስባሉ፤ ስለዚህ ለዓለምና ለዘላለም። አሕዛብ ይገዙልሃል"። መዝ 44፥16-17።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_11_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሉቃስ 6
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²⁰ እርሱም ወደ ደቀ መዛሙርቱ ዓይኑን አነሣ እንዲህም አላቸው፦ እናንተ ድሆች ብፁዓን ናችሁ፥ የእግዚአብሔር መንግሥት የእናንተ ነውና።
²¹ እናንተ አሁን የምትራቡ ብፁዓን ናችሁ፥ ትጠግባላችሁና። እናንተ አሁን የምታለቅሱ ብፁዓን ናችሁ፥ ትስቃላችሁና።
²² ሰዎች ስለ ሰው ልጅ ሲጠሉአችሁ ሲለዩአችሁም ሲነቅፉአችሁም ስማችሁንም እንደ ክፉ ሲያወጡ፥ ብፁዓን ናችሁ።
²³ እነሆ፥ ዋጋችሁ በሰማይ ታላቅ ነውና በዚያን ቀን ደስ ይበላችሁ ዝለሉም፤ አባቶቻቸው ነቢያትን እንዲህ ያደርጉባቸው ነበርና።
²⁴ ነገር ግን እናንተ ባለ ጠጎች ወዮላችሁ፥ መጽናናታችሁን ተቀብላችኋልና።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #እመቤታች_የማርያም_ቅዳሴ ነው። መልካም የእመቤታችን የጽንሰት በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነሐሴ_12

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ዐሥራ ሁለት በዚች ቀን የመላእክት አለቃ የከበረ #ቅዱስ_ሚካኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው፣ #ቅዱስ_ቈስጠንጢኖስ ወደ ሮሜ ከተማ ገባ በሮሜ አገሮችም ሁሉ ላይ ነገሠ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሚካኤል_ሊቀ_መላእክት

ነሐሴ ዐሥራ ሁለት በዚች ቀን የመላእክት አለቃ የከበረ ሚካኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው።

በዚች ቀን #እግዚአብሔር ወደ ዕሌኒ ልጅ ወደ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ልኮታልና ለእርሱም ጠላቶቹን እስከ አሸነፋቸው መንግሥቱም እስከ ጸናች ድረስ ኃይልን ሰጠው የጣዖታትንም ቤት አፍርሶ አብያተ ክርስቲያናትን ሠራ። በጌጥም ሁሉ አስጌጣቸው።

ስለዚህም አባቶቻችን የቤተክርስቲያን መምህራን የከበረ የመላእክት አለቃ የሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ በየወሩ በዐሥራ ሁለተኛው ቀን እናደርግ ዘንድ አዘዙን።

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ በከበረ መልአክ አማላጅነት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ታላቁ_ንጉሥ_ቅዱስ_ቆስጠንጢኖስ

በዚህችም ቀን ቈስጠንጢኖስ ወደ ሮሜ ከተማ ገባ በሮሜ አገሮችም ሁሉ ላይ ነገሠ።

(ዜናውም መጋቢት ሃያ ስምንት ቀን ላይ ተጽፏል።)
የዚህ ቅዱስ የአባቱ ስም ቍንስጣ የእናቱ ስም ዕሌኒ ነው ቊንስጣም በራንጥያ ለሚባል አገር ንጉሥ ነው መክስምያኖስም በሮሜ በአንጾኪያና በግብጽ ላይ ነግሦ ነበር።

ይህም ቍስጣ አረማዊ ነበር ግን በጎ ሥራ ያለው እውነትን የሚወድ በልቡናውም ይቅርታና ርኃራኄን የተመላ ክፋት የሌለበት ነው። ወደሮሐ ከተማ በሔደ ጊዜ ዕሌኒን አይቶ ሚስት ልትሆነው አገባት እርሷም ክርስቲያናዊት ናት። ንጉሥ ቈስጠንጢኖስንም ፀንሳ ወለደችው ስሙንም ቈስጠንጢኖስ ብላ ጠራቸው ይህም ዝንጉርጒር ማለት ነው።

ከዚህም በኋላ ንጉሥ ቊንስጣ ዕሌኒን በዚያው ትቷት ወደ በራንጥያ ከተማ ተመለሰ። እርሷም ልጇን እያሳደገች በዚያው ኖረች የክርስትናን ትምህርት አስተማረችው ይቅርታንና ርኅራኄን በክርስቲያን ወገኖች ላይ እንዲያደርግ በልቡናው ትዘራበት ነበር። እርሷ ክርስቲያን ስትሆን የክርስትና ጥምቀትን ታጠምቀው ዘንድ አልደፈረችም መንፈሳዊ ዕውቀትን ሁሉ በማስተማር አሳደገችው ዳግመኛም ለመንግሥት ልጆች የሚገባውንም ሁሉ።

ከዚያም በኋላ ወደ አባቱ ሰደደችው አባቱም በአየው ጊዜ ደስ ተሰኘበት ዕውቀትን የተመላ ሁኖ ፈረስ በመጋለብም ብርቱና የጸና ሆኖ አግኝቶታልና በበታቹም መስፍን አድርጎ ሹሞ በመንግሥቱ ሥራ ላይ ሁሉ ሥልጣን ሰጠው።

ከሁለት ዓመትም በኋላ አባቱ አረፈ ቈስጠንጢኖስም መንግሥቱን ሁሉ ተረከበ የቀና ፍርድንም የሚፈርድ ሆነ ከእርሱ በፊት የነበሩ ነገሥታት የጫኑባቸውን ጽኑ አገዛዝ ከሰዎች ላይ አስወገደ። አሕዛብም ሁሉ ታዘዙለት ወደዱትም የአገዛዙ ቅንነትና የፍርዱ ትክክለኛነት በአገሮች ሁሉ እስቲሰማ ተገዙለት።

የሮሜ ሰዎች ታላላቆች መልእክትን ወደርሱ ላኩ ከከሀዲ መክስምያኖስ ጽኑ አገዛዝ እንዲያድናቸው እየለመኑ እርሱ አሠቃይቷቸው ነበርና። መልእክታቸውንም በአነበቡ ጊዜ ስለ ደረሰባቸው መከራ እጅግ አዘነ ያድናቸውም ዘንድ ምን እደሚያደርግ በዐደባባይ ተቀምጦ እያሰበ ሲያዝን እነሆ ከቀኑ በስድስት ሰዓት በቀትር ጊዜ ኅብሩ እንደ ከዋክብት የሆነ መስቀል ታየው በላዩም በዮናኒ ቋንቋ ኒኮስጣጣን የሚል ጹሑፍ አለ ትርጓሜውም በዚህ ጠላትህን ድል ታደርጋለህ ማለት ነው።

#መስቀሉም ብርሃን የፀሐይን ብርሃን ሲሸፍነው በአየ ጊዜ አደነቀ። በላዩ ስለተጻፈውም አስቦ ለጭፍሮቹ አለቆችና ለመንግሥቱ ታላላቅ ባለሥልጣኖች አሳያቸው። እነርሱም ቢሆኑ ይህ መስቀል ስለምን እንደተገለጠ አላወቁም።

በዚያችም ሌሊት የ #እግዚአብሔር መልአክ ለቈስጠንጢኖስ በራእይ ተገልጦ እንዲህ አለው በቀኑ እኩሌታ በቀትር በአየኸው በዚያ #መስቀል አምሳል ላንተ ምልክት አድርግ በርሱም ጠላትህን ድል ታደርጋለህ አለው። ከእንቅልፉም በነቃ ጊዜ ልቡ ጸና የወርቅ መስቀልም አሠርቶ በነገሠበት ዘውድ ላይ አደረገው መኳንንቱንና ወታደሮቹን ጭፍሮቹን ሁሉ #መስቀል ሠርተው በጦር መሣሪያቸው ላይ ያደርጉ ዘንድ አዘዛቸው እነርሱም እንዳዘዛቸው አደረጉ።

ይህም የሆነው በበራንጥያ በነገሠ በሰባተኛ ዓመቱ ነው። የሮሜን ሰዎች ከሥቃያቸው ሊያድናቸው ሠራዊቱን ሰብስቦ ተነሥቶ ወጣ። መክስምያኖስም ሰምቶ በታላቅ ወንዝ ላይም ታላቅ ድልድይ ሠርቶ ወደ ቈስጠንጢኖስም ተሻግሮ ከእርሱ ጋራ ተዋጋ።

#መስቀሉም ምልክት ቀድሞ በታየ ጊዜ የመክስምያኖስ ሠራዊት ድል ይሆኑ ነበር የቈስጠንጢኖስም ሠራዊት ከመክስምያኖስ ሰራዊት ብዙ ሰው ገደሉ። የቀሩትም ሸሽተው ሲሔዱ ከመክስምያኖስ ጋር ሊሻገሩና ወደ ሮሜ ሊገቡ ድልድይ ላይ ወጡ ድልድዩም ፈርሶ ፈርዖን ከሠራዊቱ ጋራ እንደ ሠጠመ እንዲሁ መክስምያኖስ ከሠራዊቱ ጋራ ሠጠመ።

ቈስጠንጢኖስም ወደ ሮሜ ከተማ ሲገባ የሮሜ ሰዎች ከካህናት ጋራ መብራቶች ይዘው በእንቍ የተሸለሙ አክሊሎችን ደፍተው እምቢልታ እየነፉ ተቀበሉት የተማሩ ሊቃውንትም የከበረ #መስቀልን ሲያመሰግኑት የሀገራችን መዳኛ ይሉት ነበር ለከበረ #መስቀልም ሰባት ቀን በዓል አደረጉ።

ቈስጠንጢኖስም ዳግመኛ በሮሜ ነገሠ ከሀዲዎች የሆኑ መክስምያኖስና ዲዮቅልጥያኖስ ስለ ክብር ባለቤት ስለ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሃይማኖት ያሠሩአቸውን እሥረኞች ሁሉንም ፈታቸው ደግሞ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ ብሎ ዓዋጅ አስነገረ።

ዳግመኛም ክርስቲያኖችን እንዲአከብሩአቸው እንጂ እንዳያዋርዱአቸው የጣዖታቱንም ገንዘብና ምድራቸውን ለካህናት እንዲሰጧቸው አዘዘ ክርስቲያኖች በአረማውያን ላይ እንዲሾሙ አደረገ። ዳግመኛም አባቶቻችን ሐዋርያት እንዳዘዙ ማንም ሰው በሰሙነ ሕማማት ሥራ እንዳይሠራ አዘዘ።

በነገሠ በሥስራ አንድ ዓመት በሮሜ ሊቀ ጳጳሳት በሶል ጴጥሮስ እጅ የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቀ። ሠራዊቱም ሁሉ። ይህም የከበረ #መስቀል ከተገለጠለት በኋላ በአራት ዓመት ነው።

ከዚህ በኋላም በእርሱ ርዳታና ድል ያገኘበትን የሚያድን ስለ ሆነ ስለ #ጌታችን_መስቀል ትመረምር ዘንድ እናቱ ዕሌኒን ወደ ኢየሩሳሌም ላካት። እርሷም ዐመፀኞች አይሁድ ቀብረው ከደፈኑት ቦታ አወጣችው።

በዘመኑ ሃይማኖታቸው የቀና የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ጳጳሳት የአንድነት ስብሰባ በኒቅያ ስለ አርዮስ ተደረገ። ለክርስቲያኖች መመሪያ በበጎ አሠራር ክርስቲያናዊት ሥርዓት ተሰራች።

ከዚህም በኋላ በበራንጥያ ታላቅ ከተማ ሊሠራ አሰበ እንደ አሰበውም ታላቅ ከተማ ሠርቶ በስሙ ቍስጥንጥንያ ብሎ ጠራት። በውስጧም አምላክን በወለደች በ #እመቤታችን_በቅድስት_ድንግል_ማርያም ስም በአግያና በሶፍያም ታላቅ ቤተ ክርስቲያን ሠራ መንፈሳዊ በሆነ በመልካም ጌጥ ሁሉ አስጌጣት። በውስጥዋ ከሐዋርያት የብዙዎቹን ዓፅም ከሰማዕታትና ከቅዱሳን ጻድቃን ሥጋቸውን ስለሚሰበስብ።

የክብር ባለቤት #ጌታችንን ደስ አሰኝቶ መልካም ተጋድሎውን ከፈጸመ በኋላ በኒቆምድያ ከተማ ጥቂት ታሞ መጋቢት ሃያ ስምንት አረፈ።

ገንዘውም በወርቅ ሣጥን አድርገው ተሸክመው ወደ ቊስጥንጥንያ አደረሱት የጳጳሳት አለቆችና ካህናቱ ከሁሉ ሕዝብ ጋር ወጥተው ተቀበሉት በብዙ ጸሎት በመዘመርና በማኅሌት በምስጋና ወደ ከበሩ ሐዋርያት ቤተ መቅደስ አስገብተው በክብር አኖሩት።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_እና_መጋቢት_28)
2024/09/24 11:22:16
Back to Top
HTML Embed Code: