Telegram Web Link
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነሐሴ_2_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ጢሞቴዎስ 2
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁸ እንግዲህ ወንዶች በስፍራ ሁሉ አለ ቍጣና አለ ክፉ አሳብ የተቀደሱትን እጆች እያነሱ እንዲጸልዩ እፈቅዳለሁ።
⁹-¹⁰ እንዲሁም ደግሞ ሴቶች በሚገባ ልብስ ከእፍረትና ራሳቸውን ከመግዛት ጋር ሰውነታቸውን ይሸልሙ፤ እግዚአብሔርን እንፈራለን ለሚሉት ሴቶች እንደሚገባ፥ መልካም በማድረግ እንጂ በሽሩባና በወርቅ ወይም በዕንቍ ወይም ዋጋው እጅግ በከበረ ልብስ አይሸለሙ።
¹¹ ሴት በነገር ሁሉ እየተገዛች በዝግታ ትማር፤
¹² ሴት ግን በዝግታ ትኑር እንጂ ልታስተምር ወይም በወንድ ላይ ልትሰለጥን አልፈቅድም።
¹³ አዳም ቀድሞ ተፈጥሮአልና፥ በኋላም ሔዋን ተፈጠረች።
¹⁴ የተታለለም አዳም አይደለም፥ ሴቲቱ ግን ተታልላ በመተላለፍ ወደቀች፤
¹⁵ ነገር ግን በእምነትና በፍቅር በቅድስናም ራሳቸውን እየገዙ ቢኖሩ በመውለድ ትድናለች።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ጴጥሮስ 3
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹-² እንዲሁም፥ እናንተ ሚስቶች ሆይ፥ ከባሎቻችሁ አንዳንዱ ለትምህርት የማይታዘዙ ቢኖሩ፥ በፍርሃት ያለውን ንጹሑን ኑሮአችሁን እየተመለከቱ ያለ ትምህርት በሚስቶቻቸው ኑሮ እንዲገኙ ተገዙላቸው።
³ ለእናንተም ጠጕርን በመሸረብና ወርቅን በማንጠልጠል ወይም ልብስን በመጎናጸፍ በውጭ የሆነ ሽልማት አይሁንላችሁ፥
⁴ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለውን የማይጠፋውን ልብስ ለብሶ የተሰወረ የልብ ሰው ይሁንላችሁ።
⁵ እንዲህ በቀድሞ ዘመን በእግዚአብሔር ተስፋ ያደረጉት ቅዱሳት ሴቶች ደግሞ ለባሎቻቸው ሲገዙ ተሸልመው ነበርና፤
⁶ እንዲሁም ሣራ ለአብርሃም፦ ጌታ ብላ እየጠራችው ታዘዘችለት፤ እናንተም ከሚያስደነግጥ ነገር አንዳች እንኳ ሳትፈሩ መልካም ብታደርጉ ልጆችዋ ናችሁ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 16
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹³ በሰንበት ቀንም ከከተማው በር ውጭ የጸሎት ስፍራ በዚያ መሆኑን ስላሰብን ወደ ወንዝ አጠገብ ወጣን፤ ተቀምጠንም ለተሰበሰቡት ሴቶች ተናገርን።
¹⁴ ከትያጥሮን ከተማም የመጣች ቀይ ሐር ሻጭ እግዚአብሔርን የምታመልክ ልድያ የሚሉአት አንዲት ሴት ትሰማ ነበረች፤ ጳውሎስም የሚናገረውን ታዳምጥ ዘንድ ጌታ ልብዋን ከፈተላት።
¹⁵ እርስዋም ከቤተ ሰዎችዋ ጋር ከተጠመቀች በኋላ፦ በጌታ የማምን እንድሆን ከፈረዳችሁልኝ፥ ወደ ቤቴ ገብታችሁ ኑሩ ብላ ለመነችን፤ በግድም አለችን።
¹⁶ ወደ ጸሎት ስፍራም ስንሄድ፥ የምዋርተኝነት መንፈስ የነበረባት ለጌቶችዋም እየጠነቈለች ብዙ ትርፍ ታመጣ የነበረች አንዲት ገረድ አገኘችን።
¹⁷ እርስዋ ጳውሎስንና እኛን እየተከተለች፦ የመዳንን መንገድ የሚነግሩአችሁ እነዚህ ሰዎች የልዑል አምላክ ባሪያዎች ናቸው ብላ ትጮኽ ነበር።
¹⁸ ይህንም እጅግ ቀን አደረገች። ጳውሎስ ግን ተቸገረና ዘወር ብሎ መንፈሱን፦ ከእርስዋ እንድትወጣ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አዝሃለሁ አለው፤ በዚያም ሰዓት ወጣ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_2_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ወይወስዱ ለንጉሥ ደናግል ድኅሬሃ። ወቢጻሂ ይወስዱ ለከ። ወይወስድዎን በትፍሥሕት ወበኃሤት"። መዝ 44፥14-15
"በኋላዋ ደናግሉን ለንጉሥ ይወስዳሉ፥ ባልንጀሮችዋንም ወደ አንተ ያቀርባሉ፤
በደስታና በሐሴት ይወስዱአቸዋል፥ ወደ ንጉሥ እልፍኝም ያስገቡአቸዋል"። መዝ 44፥14-15
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_2_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ዮሐንስ 8
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ ኢየሱስ ግን ወደ ደብረ ዘይት ሄደ።
² ማለዳም ደግሞ ወደ መቅደስ ደረሰ ሕዝቡም ሁሉ ወደ እርሱ መጡ። ተቀምጦም ያስተምራቸው ነበር።
³ ጻፎችና ፈሪሳውያንም በምንዝር የተያዘችን ሴት ወደ እርሱ አመጡ በመካከልም እርሱዋን አቁመው፦
⁴ መምህር ሆይ፥ ይህች ሴት ስታመነዝር ተገኝታ ተያዘች።
⁵ ሙሴም እንደነዚህ ያሉት እንዲወገሩ በሕግ አዘዘን፤ አንተስ ስለ እርስዋ ምን ትላለህ? አሉት።
⁶ የሚከሱበትንም እንዲያገኙ ሊፈትኑት ይህን አሉ። ኢየሱስ ግን ጐንበስ ብሎ በጣቱ በምድር ላይ ጻፈ፤
⁷ መላልሰው በጠየቁት ጊዜ ግን ቀና ብሎ፦ ከእናንተ ኃጢአት የሌለበት አስቀድሞ በድንጋይ ይውገራት አላቸው።
⁸ ደግሞም ጐንበስ ብሎ በጣቱ በምድር ላይ ጻፈ።
⁹ እነርሱም ይህን ሲሰሙ ሕሊናቸው ወቀሳቸውና ከሽማግሌዎች ጀምረው እስከ ኋለኞች አንድ አንድ እያሉ ወጡ፤ ኢየሱስም ብቻውን ቀረ ሴቲቱም በመካከል ቆማ ነበረች።
¹⁰ ኢየሱስም ቀና ብሎ ከሴቲቱ በቀር ማንንም ባላየ ጊዜ፦ አንቺ ሴት፥ እነዚያ ከሳሾችሽ ወዴት አሉ? የፈረደብሽ የለምን? አላት።
¹¹ እርስዋም፦ ጌታ ሆይ፥ አንድ ስንኳ አለች። ኢየሱስም፦ እኔም አልፈርድብሽም፤ ሂጂ ከአሁንም ጀምሮ ደግመሽ ኃጢአት አትሥሪ አላት።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #እመቤታች_የማርያም_ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ነሐሴ 3

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ ሦስት በዚህች ቀን በገድል የተጠመደ መስተጋድል የከበረ #አባ_ስምዖን_ዘዓምድ አረፈ፣ ከመንግሥት ወገን የሆነች #ቅድስት_ሶፍያ አረፈች።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ታላቁ_አባ_ስምዖን_ዘዓምድ

ነሐሴ ሦስት በዚህች ቀን በገድል የተጠመደ መስተጋድል የከበረ አባ ስምዖን ዘዓምድ አረፈ። ለዚህም ቅዱስ ስድስት ዓመት በሆነው ጊዜ አባቱ የበጎቹ ጠባቂ አደረገው። ወደ ቤተ ክርስቲያንም በመሔድ ሁል ጊዜ ቅዱሳት መጻሕፍትን ይሰማ ነበር የ #እግዚአብሔርም ቸርነት አነሳሥቶት ወደ አንድ ገዳም ሒዶ መነኰሰ ብዙ ዘመናትም በገድል ተጠምዶ ሲጋደልና ሰውነቱን ሲያስጨንቅ ኖረ።

ከዚህም በኋላ ገመዱ ሥጋውን ቆርጦ እስቲገባ ድረስ በወገቡ ላይ ገመድን አሠረ። ሥጋውም ተልቶ ከእርሱ ክፉ ሽታ ይወጣ ነበር ስለ ክፉ ሽታውም መነኰሳቱ አዘኑ ተጸየፉትም ወደ አበ ምኔቱም ተሰብስበው ይህን መነኰስ ስምዖንን ከእኛ ዘንድ ካላወጣኸው አለዚያ አንተን ትተን ወደሌላ እንሔዳለን አሉት እርሱም ምን አደረገ አላቸው እነርሱም ጥራውና አንተ ራስህ እይ አሉት።

ጠርቶትም መጥቶ በፊቱ በቆመ ጊዜ ደም ከመግል ጋራ በእግሮቹ ላይ ሲፈስ አየ አበ ምኔቱንም እጅግ አስጨነቀው። ልብሶቹንም ገልጦ በሥጋው ውስጥ የገባውን ያንን ገመድ አየው አበ ምኔቱም በእርሱ ላይ ተቆጥቶ ይህን ታደርግ ዘንድ እንዴት ደፈርክ አለው በታላቅ ድካምም ያንን ገመድ ከሥጋው ውስጥ አወጡት ቍስሉም እስከሚድን መድኃኒት እያደረጉለት ኃምሳ ቀኖች ያህል ኖረ።

ከዚህም በኋላ አበ ምኔቱ እንዲህ አለው ልጄ ስምዖን ሆይ እንግዲህስ ወደ ፈለግኸው ቦታ ሒድ ከዚያም ወጥቶ ሔደ በደረቅ ጕድጓድ ውስጥም ገብቶ ከእባቦችና ከጊንጦች ጋራ ኖረ።

ከዚህም በኋላ አገልጋዩ ስምዖንን ለምን ሰደድከው አሁንም ፈልገህ መልሰው በፍርድ ቀን እርሱ ከአንተ ይሻላልና ብሎ ሲገሥጸው አበ ምኔቱ ራእይን አየ። አባ ስምዖንንም ከገዳሙ ስለመውጣቱ ገሠጸው።

በነጋም ጊዜ አበ ምኔቱ ራእይን እንዳየ ስለ አባ ስምዖንም እንደገሠጸው ለመነኰሳቱ ነገራቸው ወንድሞችም ደንግጠው እጅግ አዘኑ እስከምታገኙትም ሔዳችሁ በቦታው ሁሉ ፈልጉት አላቸው ሔደውም ፈለጉት ግን አላገኙትም። ከዚህም በኋላ መብራትን አብርተው ወደ ጕድጓድ ውስጥ ገቡ ያለ መብልና መጠጥም ከእባቦችና ከጊንጦች ጋራ ተቀምጦ አዩት።

ገመድም አውረዱለትና ከዚያ አወጡት በፊቱም ሰግደው በአንተ ላይ ያደረግነውን በደላችንን ይቅር በለን አሉት እኔንም ስለ አሳዘንኳችሁ ይቅር በሉኝ አላቸው። ከዚህም በኋላ ወደ ገዳማቸው ወሰዱት በብዙ ገድልም ተጠምዶ ሲያገለግል ኖረ።

ከዚህም በኋላ ከዚያ ገዳም በሥውር ወጥቶ ወደ አንዲት ዐለት ቋጥኝ ደረሰ። በእርስዋም ላይ ሳያረፍና ሳይተኛ ስልሳ ቀን ቆመ። ከዚህም በኋላ የ #እግዚአብሔር መልአክ ስለ ብዙ ሰዎች ድኅነት #እግዚአብሔር እንደ ጠራው ነገረው። ከዚያም ሔዶ ቁመቱ ሠላሳ ክንድ የሚሆን የድንጋይ ምሰሶ አገኘ ድንቅ ተአምራትን እያደረገ በሽተኞችንም እየፈወሰ ወደርሱ የሚመጡትንም እያስተማረ ዐሥራ ሁለት ዓመት በድንጋይ ምሰሶው ላይ ቆመ።

አባቱም ፍልጎት ነበር ግን ሳያየው ሞተ እናቱ ግን ወሬውን ሰምታ ከብዙ ዘመናት በኋላ ወደርሱ መጣች በድንጋይ ምሰሶውም ላይ ቁሞ አገኘችው አይታውም አለቀሰች ከድንጋይ ምሰሶውም በታች ተኛች። ቅዱስ ስምዖንም #ጌታችን በጎ ነገርን ያደርግላት ዘንድ ስለርሷ ለመነ ያን ጊዜም እንደተኛች አረፈችና ከደንጊያው ምሰሶ በታች ቀበሩዋት።

ሰይጣንም በእርሱ ላይ ቀንቶ እግሩን መታው ከእግሩ ትል እየወደቀ በአንዲት እግሩ ብዙ ዓመታት ኖረ። ከዚህም በኋላ የሽፍቶች አለቃ ወደርሱ መጥቶ ንስሐ ገባ ጥቂት ቀኖችም ኑሮ አረፈ በጸሎቱም ሕይወትን ወረሰ። ወደርሱ ስለሚመጡ ብዙ ሕዝቦችም የውኃ ጥማት እንዳያስጨንቃቸው ወደ #እግዚአብሔር ለምኖ ከድንጋይ ምሰሶው በታች ውኃን አፈለቀላቸው።

ዳግመኛም ወደ ሌላ ምሰሶ ተዛወረ በእርሱም ላይ እየተጋደለ ሠላሳ ዓመት ኖረ። ብዙዎች አረማውያንንና ከሀድያንን ካስተማራቸውና ወደ ፈጠራቸው #እግዚአብሔር ከመለሳቸው በኋላ ክብር ይግባውና ወደ ወደደው #ክርስቶስ ሔደ በሰላምም አርፎ የዘላለም ሕይወትን ወረሰ።

ከዚህም በኋላ የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አባ ስምዖን እንዳረፈ በሰማ ጊዜ ካህናትን ዲያቆናትንና የአገሩን መኳንንቶች ከእርሱ ጋራ ይዞ የቅዱስ አባ ስምዖን ሥጋው ወዳለበት ደረሰ በታላቅ ክብርም ተሸክመው እየዘመሩና እያመሰገኑ ወደ እስክንድርያ አድርሰው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት ከሥጋውም ድንቆችና ተአምራቶች ታላቅ ፈውስም ተገለጡ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ መስተጋድል ጸሎት ይማረን በረከቱም ትድርሰን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅድስት_ሶፍያ_ቡርክትና_ደናግል_ልጆቿ

በዚችም ቀን ከመንግሥት ወገን የሆነች ሶፍያ አረፈች። ለዚችም ቅድስት ብዙ ሀብትና ብዙ ጥሪት ነበራት ክብር ይግባውና ስለ ክርስቶስ ፍቅር የክርስቶስን መከራ መስቀል አንሥታ ትሸከም ዘንድ ከሦስት ሴቶች ልጆቿ ጋራ ወደ ሮም ከተማ ሔደች።

ንጉሥ እንድርያሰኖስም ክርስቲያን እንደ ሆነች አውቆ ከልጆቹ ጋራ ወደ አደባባይ አስቀረባትና ስለ ሀገርዋና ስለ ስሟ ጠየቃት እርሷም የሚቀደመው ስሜ ክርስቲያን ነኝ ወላጆቼ ያውጡልኝ ስም ሶፊያ ነው እኔም በኢጣልያ ባለ ብዙ ወገን ነኝ ክብር ይግባውና በ #ክርስቶስ ፈቃድም ልጆቼን መሥዋዕት አድርጌ ላቀርብ ወደ አገርህ መጣሁ አለችው። ከዚህም በኋላ የከዳተኛው ንጉሥ ሥቃዩ እንዳያስፈራቸው ልጆቿን አበረታቻቸው።

ምስክርነታቸውንም ፈጽመው ከሞቱ በኋላ ገንዛ ከሮሜ ከተማ ውጭ ቀበረቻቸው።

በሦስተኛውም ቀን መታሰቢያቸውን ታደርግ ዘንድ ልጆቿ ወደ ተቀበሩበት ከብዙዎች ከከተማው ሴቶች ጋራ ሔደች እንዲህ ብላም ጸለየች አክሊላትን የተቀዳጃችሁ የምታምሩ ፍጹማት የሆናችሁ ልጆቼ ሆይ እኔንም ከእናንተ ጋራ ውሰዱኝ ይህንንም እንዳለች ወዲያውኑ አረፈች ከልጆቿም ጋር ተቀበረች።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_3)
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነሐሴ_3_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ተሰሎንቄ 3
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ ስለዚህ ወደ ፊት እንታገሥ ዘንድ ባልተቻለን ጊዜ፥ በአቴና ብቻችንን ልንቀር በጎ ፈቃዳችን ሆነ።
² ስለ እምነታችሁም እንዲያጸናችሁና እንዲመክራችሁ ወንድማችንን የእግዚአብሔርንም አገልጋይ ከእኛ ጋርም አብሮ በክርስቶስ ወንጌል የሚሠራውን ጢሞቴዎስን ላክነው፤
³ በዚህ መከራ ማንም እንዳይናውጥ፥ ለዚህ እንደ ተመረጥን ራሳችሁ ታውቃላችሁና።
⁴ በእውነት ከእናንተ ጋር ሳለን፥ መከራ እንቀበል ዘንድ እንዳለን አስቀድመን እንነግራችሁ ነበር፤ እንዲሁም ደግሞ ሆነ፥ ይህንም ታውቃላችሁ።
⁵ ስለዚህ እኔ ደግሞ ወደ ፊት እታገሥ ዘንድ ባልተቻለኝ ጊዜ፦ ፈታኝ ምናልባት ፈትኖአቸዋል ድካማችንም ከንቱ ሆኖአል ብዬ እምነታችሁን ለማወቅ ላክሁ።
⁶ አሁን ግን ጢሞቴዎስ ከእናንተ ዘንድ ወደ እኛ መጥቶ ስለ እምነታችሁና ስለ ፍቅራችሁ የምስራች ብሎ በነገረን ጊዜ፥ እኛም እናያችሁ ዘንድ እንደምንናፍቅ ታዩን ዘንድ እየናፈቃችሁ ሁልጊዜ በመልካም እንደምታስቡን በነገረን ጊዜ፥
⁷ ስለዚህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ በእምነታችሁ በኩል በችግራችንና በመከራችን ሁሉ ስለ እናንተ ተጽናናን፤
⁸ እናንተ በጌታ ጸንታችሁ ብትቆሙ፥ አሁን በሕይወት እንኖራለንና።
⁹-¹⁰ ፊታችሁን ልናይ በእምነታችሁም የጎደለውን ልንሞላበት ሌሊትና ቀን ከመጠን ይልቅ እየጸለይን በአምላካችን ፊት ከእናንተ የተነሣ ስለምንደሰተው ደስታ ሁሉ፥ ለእግዚአብሔር በእናንተ ምክንያት ምን ያህል ምስጋና እናስረክብ ዘንድ እንችላለን?
¹¹ አምላካችንና አባታችን ራሱ ጌታችንም ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እናንተ መንገዳችንን ያቅና፤
¹²-¹³ ጌታችንም ኢየሱስ ክርስቶስ ከቅዱሳኑ ሁሉ ጋር ሲመጣ፥ በአምላካችንና በአባታችን ፊት በቅድስና ነቀፋ የሌለበት አድርጎ ልባችሁን ያጸና ዘንድ፥ እኛ ደግሞ ለእናንተ እንደምንሆን ጌታ እርስ በእርሳችሁ ያላችሁን ለሁሉም የሚሆን ፍቅራችሁን ያብዛ ይጨምርም።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ጴጥሮስ 3
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁰ ሕይወትን ሊወድ መልካሞችንም ቀኖች ሊያይ የሚፈልግ ሰው፥ መላሱን ከክፉ ከንፈሮቹንም ተንኰልን ከመናገር ይከልክል፤
¹¹ ከክፉ ፈቀቅ ይበል፥ መልካምንም ያድርግ፥ ሰላምን ይሻ ይከተለውም፤
¹² የጌታ ዓይኖች ወደ ጻድቃን ናቸውና፥ ጆሮዎቹም ለጸሎታቸው ተከፍተዋል፥ የጌታ ፊት ግን ክፉ ነገርን በሚያደርጉ ላይ ነው።
¹³ በጎንም ለማድረግ ብትቀኑ የሚያስጨንቃችሁ ማን ነው?
¹⁴ ነገር ግን ስለ ጽድቅ እንኳ መከራን ብትቀበሉ ብፁዓን ናችሁ። ማስፈራራታቸውንም አትፍሩ አትናወጡም፥
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 14
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²⁰ ደቀ መዛሙርት ግን ከበውት ሳሉ፥ ተነስቶ ወደ ከተማ ገባ። በነገውም ከበርናባስ ጋር ወደ ደርቤን ወጣ።
²¹-²² በዚያችም ከተማ ወንጌልን ሰብከው እጅግ ደቀ መዛሙርትን ካደረጉ በኋላ፥ የደቀ መዛሙርትን ልብ እያጸኑ በሃይማኖትም ጸንተው እንዲኖሩ እየመከሩና፦ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ ያስፈልገናል እያሉ፥ ወደ ልስጥራን ወደ ኢቆንዮንም ወደ አንጾኪያም ተመለሱ።
²³ በየቤተ ክርስቲያኑም ሽማግሌዎችን ከሾሙላቸው በኋላ ጦመውም ከጸለዩ በኋላ፥ ላመኑበት ለጌታ አደራ ሰጡአቸው።
²⁴ በጲስድያም አልፈው ወደ ጵንፍልያ መጡ፥
²⁵ በጴርጌንም ቃሉን ከተናገሩ በኋላ ወደ አጣልያ ወረዱ፥
²⁶ ከዚያም ስለ ፈጸሙት ሥራ ለእግዚአብሔር ጸጋ አደራ ወደ ተሰጡበት ወደ አንጾኪያ በመርከብ ሄዱ።
²⁷ በደረሱም ጊዜ ቤተ ክርስቲያኑን ሰብስበው እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር ያደረገውን ሁሉ ለአሕዛብም የሃይማኖትን ደጅ እንደ ከፈተላቸው ተናገሩ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_3_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ። ወለገጽኪ ይትመሀለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር። ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሥ፡ሐሴቦን"። መዝ 44፥12-13።
"የጢሮስ ሴቶች ልጆች እጅ መንሻን ይዘው ይሰግዱለታል። የምድር ባለጠጎች አሕዛብ በፊትህ ይማለላሉ። ለሐሴቦን ንጉሥ ልጅ ሁሉ ክብርዋ ነው፤ ልብስዋ የወርቅ መጐናጸፊያ ነው"። መዝ 44፥12-13።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_3_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሉቃስ 18
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁹ ጻድቃን እንደ ሆኑ በራሳቸው ለሚታመኑና ሌሎቹን ሁሉ በጣም ለሚንቁ ይህን ምሳሌ ነገራቸው፥
¹⁰ እንዲህ ሲል፦ ሁለት ሰዎች ሊጸልዩ ወደ መቅደስ ወጡ፥ አንዱ ፈሪሳዊ ሁለተኛውም ቀራጭ።
¹¹ ፈሪሳዊም ቆሞ በልቡ ይህን ሲጸልይ፦ እግዚአብሔር ሆይ፥ እንደ ሌላ ሰው ሁሉ፥ ቀማኞችና ዓመፀኞች አመንዝሮችም፥ ወይም እንደዚህ ቀራጭ ስላልሆንሁ አመሰግንሃለሁ፤
¹² በየሳምንቱ ሁለት ጊዜ እጦማለሁ፥ ከማገኘውም ሁሉ አሥራት አወጣለሁ አለ።
¹³ ቀራጩ ግን በሩቅ ቆሞ ዓይኖቹን ወደ ሰማይ ሊያነሣ እንኳ አልወደደም፥ ነገር ግን፦ አምላክ ሆይ፥ እኔን ኃጢአተኛውን ማረኝ እያለ ደረቱን ይደቃ ነበር።
¹⁴ እላችኋለሁ፥ ከዚያ ይልቅ ይህ ጻድቅ ሆኖ ወደ ቤቱ ተመለሰ፤ ራሱን ከፍ የሚያደርግ ሁሉ ይዋረዳልና፥ ራሱን ግን የሚያዋርድ ከፍ ይላል።
¹⁵ እንዲዳስሳቸውም ሕፃናትን ደግሞ ወደ እርሱ አመጡ፤ ደቀ መዛሙርቱም አይተው ገሠጹአቸው።
¹⁶ ኢየሱስ ግን ሕፃናትን ወደ እርሱ ጠርቶ፦ ሕፃናት ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ ተዉአቸው አትከልክሉአቸውም፤ የእግዚአብሔር መንግሥት እንደ እነዚህ ላሉት ናትና።
¹⁷ እውነት እላችኋለሁ፥ የእግዚአብሔርን መንግሥት እንደ ሕፃን የማይቀበላት ሁሉ ከቶ አይገባባትም አለ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #እመቤታች_የማርያም_ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነሐሴ_4

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ አራት በዚህች ቀን ከዳዊት ዘር የሆነ የአካዝ ልጅ #ቅዱስ_ሕዝቅያስ ንጉሥ አረፈ፣ እንደ በግ የጸጒር ልብስ ለብሶ በበረሃ የሚኖር #አባ_ማቴዎስ አረፈ፣ በተጨማሪ በዚች ቀን የከበሩ #ዳዊትና_ወንድሞቹና ከግብጽ ደቡብ ስንካር ከሚባል አገር #ፊልጶስም በሰማዕትነት ሞቱ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሕዝቅያስ_ጻድቅ (ንጉሠ ይሁዳ)

ነሐሴ አራት በዚህች ቀን ከዳዊት ዘር የሆነ የአካዝ ልጅ ሕዝቅያስ ንጉሥ አረፈ። ከጻድቁ ንጉሥ ከዳዊት በኋላ እንደ ሕዝቅያስ ያለ በእስራኤል ውስጥ አልተሾመም ከዚህ ጻድቅ ንጉሥ በቀር ሁሉም ጣዖትን አምልከዋልና መሠዊያም ሠርተዋልና።

እርሱም በነገሠ ጊዜ ጣዖታትን ሰበረ መሠዊያቸውንም አፈረሰ ከነሐስ የተሠራውንም እባብ ቆራረጠ የእስራኤል ልጆች አምልከውት ነበርና #እግዚአብሔርም ዘመነ መንግሥቱን እጅግ አሳመረለት በጎ ነገርንም ሁሉ ሰጠው ።

ሕዝቅያስም በነገሠ በዐሥራ አራተኛው ዘመን የፋርስ ንጉሥ ሰናክሬም መጥቶ ኢየሩሳሌምን ከበባት ይህም ሰናክሬም በዘመኑ እንደርሱ ያለ የሌለ ኃይለኛ ብርቱ የምድር ነገሥታት ሁሉ የፈሩትና የታዘዙለት ነው ። ሕዝቅያስም ከእርሱ ግርማ የተነሣ ፈርቶ አገሩን እንዳያጠፋ ብዙ ወርቅና ብር እጅ መንሻ ላከለት ሰናክሬምም ደስ ብሎት ምንም ምን አልተቀበለም በእርሱ ላይና በልዑል #እግዚአብሔር ላይ ተቆጥቶ #እግዚአብሔር ከእኔ እጅ ሊያድናችሁ አይችልም በማለት የስድብን ቃል ላከ እንጂ ።

ሁለተኛም በልዑል ስም ላይ ስድብና ቍጣ የተጻፈበትን ደብዳቤ ላከ ሕዝቅያስም በሰማ ጊዜ ወደ #እግዚአብሔር ቤት ገብቶ አለቀሰ ልብሱንም ቀዶ ማቅ ለበሰ እንዲህም ብሎ ጸለየ ። አቤቱ የእስራኤል አምላክ በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ አንተም ብቻህን በዓለም መንግሥታት ላይ ንጉሥ የሆንክ አንተም ሰማይና ምድርን የፈጠርህ ልመናዬን አድምጥ ። ዐይኖችህን ገልጠህ ተመልከት ሕያው #እግዚአብሔር አንተን እያቃለለ ሰናክሬም የላከውን ቃሉን ስማ ።

ከዚህም በኋላ ንጉሥ ሕዝቅያስ የፋርስ ንጉሥ ሰናክሬም የተናገውን እንዲነግሩትና ስለርሱና ስለ ሕዝቡ ይጸልይ ዘንድ ወደ ኢሳይያስ መልእክተኞችን ላከ ። ኢሳይያስም ከ #እግዚአብሔር ቃልን ተቀብሎ እንዲህ ብሎ መለሰለት ልብህን አጽና አትፍራ በዓለሙ ሁሉ እንደርሱ ያለ ያልተሰማ ዕፁብ ድንቅ የሆነ ሥራ በሰናክሬም ላይ ሊሠራ #እግዚአብሔር አለውና ።

ከዚህም በኋላ #እግዚአብሔር የላከው መልአክ መጥቶ ከፋርስ ሠራዊት መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ ሰዎችን ገደለ የለኪሶም ሰዎች ሲነጋ በተነሡ ጊዜ የሞቱትን ሰዎች ሬሳ ሁሉ አገኙ የተረፉትም ከንጉሣቸው ጋራ ሸሽተው ነነዌ አገር ገቡ ። ሰናክሬምም ሊጸልይ ወደጣዖቱ ቤት በገባ ጊዜ ልጆቹ አድራማሌክና ሶርሶር በሰይፍ መትተው ገደሉት ። ሕዝቅያስም ከሰናክሬም እጅ ድኖ የተመሰገነ #እግዚአብሔርን አመሰገነ ።

በዚያም ወራት ሕዝቅያስ ታመመ ለሞትም ደረሰ የአሞፅ ልጅ ኢሳይያስም ወደረሱ መጥቶ #እግዚአብሔር እንዲህ አለ ትሞታለህ እንጂ አትድንምና ቤትህን ሥራ አለው። ሕዝቅያስም ፊቱን ወደግድግዳው መልሶ ወደ #እግዚአብሔር ለመነ እያመሰገነውም እንዲህ አለ አቤቱ በቀና ልቡና በዕውነት ሥራ በፊትህ ጸንቼ እንደኖርኩ ፈቃድህንም እንደፈጸምሁ አስብ ብሎ ሕዝቅያስ ፈጽሞ ጽኑዕ ልቅሶን አለቀሰ ።

ኢሳይያስም ወደ መካከለኛው ዐፀድ ደረሰ #እግዚአብሔርም እንዲህ ብሎ ተናገረው ሒደህ ለወገኖቼ ንጉሥ ለሕዝቅያስ ያባትህ የዳዊት ፈጣሪ #እግዚአብሔር እንዲህ አለ በለው ። ጸሎትህን ሰማሁ ዕንባህንም አየሁ እነሆ እኔ አድንሃለሁ እስከ ሦስት ቀንም ወደ #እግዚአብሔር ቤት ትወጣለህ ።

በዘመኖችህም ላይ ዐሥራ አምስት ዓመት ጨምሬልሃለሁ ከፋርስ ንጉሥ እጅም አድንሃለሁ ይቺንም አገር ስለ እኔና ስለ ባለሟሌ ዳዊት አጽንቼ እጠብቃታለሁ ። ሕዝቅያስም ኢሳይያስን እንዲህ አለው #እግዚአብሔር እንደሚያድነኝና እስከ ሦስት ቀን ወደ #እግዚአብሔር ቤት ለመውጣቴ ምልክቱ ምንድ ነው ።

ኢሳይያስም እንዲህ አለው የተናገረውን ቃል ያደርግ ዘንድ ከ #እግዚአብሔር የተገኘ ምልክቱ ይህ ነው እነሆ ጥላው ወደ ዐሥረኛው እርከን ቢመለስ ምልክቱ ይህ ነው ። ሕዝቅያስም እንዲህ አይደለም የጥላው ወደ ዐሥረኛ እርከን መመለስ ቀላል ነው ። መመለስስ ከሆነ ፀሐይ ወደ ዐሥረኛው እርከን ይመለስ አለ ። ኢሳይያስም ወደ #እግዚአብሔር ጮኸ ፀሐይም ዐሥሩን እርከን ተመለሰ ።

ሕዝቅያስንም የምድር ነገሥታት ሁሉ ፈሩት እጅ መንሻም አገቡለት የ #እግዚአብሔር ኃይል ከእርሱ ጋራ እንዳለ አውቀዋልና ። በመንበረ መንግሥቱም ሃያ ዘጠኝ ዓመት ነግሦ ኖረ ። #እግዚአብሔርን አገልግሎ በሰላም አረፈ ።

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አባ_ማቴዎስ_ገዳማዊ

በዚችም ቀን እንደ በግ የጸጒር ልብስ ለብሶ በበረሃ የሚኖር አባ ማቴዎስ አረፈ። ይኸውም አባ ማቴዎስ የአቶሩን ንጉሥ በተአምሩ ከነቤተሰቡ ያሳመነው ነው፡፡ በእርሱም ትምህርት በሀገሪቱ ብዙ ሰማዕታት ተገኝተዋል፡፡ ቅድስት ሣራና ወንድሟ መርምህናም አባታቸው የአቶር ንጉሥ ሲሆን እርሱም የተቀረጹ ጣዖታን ያመልክ ነበር፡፡ እናታቸው ግን አማኝ ክርስቲያን ነበረች፡፡ አባቱን ለምኖና አስፈቅዶ ወደ ዱር ሄዶ አራዊትን ለማደን በወጣ ጊዜ እናቱ የሰማይና የምድር አምላክ #እግዚአብሔር በላዩ በረከትን ያሳድርበት ዘንድ ከጸለየችለት በኋላ ሸኘችው፡፡

መርምህናም ከአርባ ፈረሰኛ አገልጋዮቹ ጋር ወጥቶ ሄደ፡፡ ወደ አንድ ተራራም ወጥቶ በዚያ አደረ፡፡ በሌሊትም የታዘዘ መልአክ ጠራውና ‹‹መርምህናም ሆይ ተነሥተህ ወደዚህ ተራራ ጫፍ ላይ ውጣ፣ ስሙ ማቴዎስ የሚባል ቅዱስ ሰው ታገኛለህ፡፡ እርሱም የሕይወትን ነገር ይነግርሃል›› አለው፡፡

ሲነጋም ወደ ተራራው ጫፍ ላይ ወጣና የበግ ጠጉር ለብሶ አባ ማቴዎስን ባገኘው ጊዜ እጅግ ፈራ፡፡ አባ ማቴዎስም ‹‹አይዞህ አትራ እኔም የእግዚአብሔር ፍጥረት ነኝና አትፍራ›› ብለው አበረቱት፡፡ መርምህናም የ #እግዚአብሔርን ስም ሲጠሩ ሲሰማ ‹‹አባቴ ከአማልክቶች በቀር አምላክ አለን?›› ብሎ ጠየቃቸው፡፡ አባታችንም የሃይማኖትን ነገር ሁሉንም አስተማሩት፡፡ መርምህናም ‹‹ከራስ ጠጉሯ እስከ እግር ጥፍሯ ድረስ በለምጽ የተመታች እኅት አለችኝና እርሷን የአምላክህን ስም ጠርተህ ካዳንክልኝ በእውነት በአምላክህ አምናለሁ›› አላቸው፡፡ ተያይዘውም ከተራራው ወርደው ወደ ንጉሡ ቤት ሄደው መርምህናም ለእናቱ ያጋጠመውን ነገር ነገራትና በለምጽ የተመታችውን እኅቱን ሣራን በሥውር ወደ አቡነ ማቴዎስ ዘንድ ወሰዳት፡፡ አቡነ ማቴዎስም መሬቱን ባርከው ውኃ አፍልቀው አጠመቋትና ከለምጹዋ ፈወሷት፡፡ አርባው ጭፍራዎችም አምነው በአባታችን እጅ ተጠመቁ፡፡

አባታችንም ሰማዕትነትን እንደሚቀበሉ ትንቢት ነግረዋቸው ባርከው መርቀው አሰናበቷቸው፡፡ የአቶሩም ንጉሥ ልጆቹንና ያመኑትን አርባውን ጭፍራዎቹን በሰይፍ ገደላቸው፡፡ ሰይጣንም በአቶሩ ንጉሥ አድሮ አሳበደው፡፡ እንደ እሪያም መጮህ ጀመረ፡፡

ክርስቲያን የሆነችው የቅዱስ መርምህናምና የቅደስት ሣራ እናታቸው ወደ አባ ማቴዎስ ሄዳ ንጉሡ በልጆቹ ላይ ያደረገውንና በእርሱም ላይ የተፈጸመበትን ነገር ነገረቻቸው፡፡ አባ ማቴዎስም ንጉሡን ዘይት ቀብተው ጸልየው ፈወሱት፡፡ በውስጡ አድሮበት የነበረውንም ሰይጣን በእሪያ መልክ ከንጉሡ ውስጥ አስወጡት፡፡
ንጉሡም ወደ ልቡ ሲመለስ በአቡነ ማቴዎስ ትምህርት በ #ጌታችን አመነ፡፡ በሚገዛቸው አገሮች ሁሉ ያሉትን ሰዎች ይዞ ከነቤተሰቡ ተጠመቀ፡፡ አቡነ ማቴዎስም #እግዚአብሔርን ሲያገለግሉ ኖረው በዚህች ዕለት በሰላም ዐረፉ፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_4)
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ነሐሴ_4_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሮሜ 12
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹⁶ እርስ በርሳችሁ በአንድ አሳብ ተስማሙ፤ የትዕቢትን ነገር አታስቡ፥ ነገር ግን የትሕትናን ነገር ለመሥራት ትጉ። ልባሞች የሆናችሁ አይምሰላችሁ።
¹⁷ ለማንም ስለ ክፉ ፈንታ ክፉን አትመልሱ፤ በሰው ሁሉ ፊት መልካም የሆነውን አስቡ።
¹⁸ ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ።
¹⁹ ተወዳጆች ሆይ፥ ራሳችሁ አትበቀሉ፥ ለቍጣው ፈንታ ስጡ እንጂ፤ በቀል የእኔ ነው፥ እኔ ብድራቱን እመልሳለሁ ይላል ጌታ ተብሎ ተጽፎአልና።
²⁰ ጠላትህ ግን ቢራብ አብላው፤ ቢጠማ አጠጣው፤ ይህን በማድረግህ በራሱ ላይ የእሳት ፍም ትከምራለህና።
²¹ ክፉውን በመልካም አሸንፍ እንጂ በክፉ አትሸነፍ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ጴጥሮስ 5
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
⁶ እንግዲህ በጊዜው ከፍ እንዲያደርጋችሁ ከኃይለኛው ከእግዚአብሔር እጅ በታች ራሳችሁን አዋርዱ፤
⁷ እርሱ ስለ እናንተ ያስባልና የሚያስጨንቃችሁን ሁሉ በእርሱ ላይ ጣሉት።
⁸ በመጠን ኑሩ ንቁም፥ ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና፤
⁹ በዓለም ያሉት ወንድሞቻችሁ ያን መከራ በሙሉ እንዲቀበሉ እያወቃችሁ በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት።
¹⁰ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዘላለም ክብሩ የጠራችሁ የጸጋ ሁሉ አምላክ ለጥቂት ጊዜ መከራን ከተቀበላችሁ በኋላ ራሱ ፍጹማን ያደርጋችኋል ያጸናችሁማል ያበረታችሁማል።
¹¹ ለእርሱ ክብርና ኃይል እስከዘላለም ድረስ ይሁን፤ አሜን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 17
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
²³ የምታመልኩትን እየተመለከትሁ ሳልፍ፦ ለማይታወቅ አምላክ የሚል ጽሕፈት ያለበትን መሠዊያ ደግሞ አግኝቼአለሁና፦ እንግዲህ ይህን ሳታውቁ የምታመልኩትን እኔ እነግራችኋለሁ።
²⁴ ዓለሙንና በእርሱ ያለውን ሁሉ የፈጠረ አምላክ እርሱ የሰማይና የምድር ጌታ ነውና እጅ በሠራው መቅደስ አይኖርም፤
²⁵ እርሱም ሕይወትንና እስትንፋስን ሁሉንም ለሁሉ ይሰጣልና አንዳች እንደሚጎድለው በሰው እጅ አይገለገልም።
²⁶-²⁷ ምናልባትም እየመረመሩ ያገኙት እንደ ሆነ፥ እግዚአብሔርን ይፈልጉ ዘንድ በምድር ሁሉ ላይ እንዲኖሩ የሰውን ወገኖች ሁሉ ከአንድ ፈጠረ፥ የተወሰኑትንም ዘመኖችና ለሚኖሩበት ስፍራ ዳርቻ መደበላቸው። ቢሆንም ከእያንዳንዳችን የራቀ አይደለም።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_4_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"እግዚኦ በኃይልከ ይትፌሣሕ ንጉሥ። ወብዙኀ ይትኀሠይ በአድኅኖትከ። ፍትወተ ነፍሱ ወሀብኮ"። መዝ 20፥1-2።
"አቤቱ፥ በኃይልህ ንጉሥ ደስ ይለዋል፤ በማዳንህ እጅግ ሐሤትን ያደርጋል። የልቡን ፈቃድ ሰጠኽው፥ የከንፈሩንም ልመና አልከለከልኸውም"። መዝ 20፥1-2።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ነሐሴ_4_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሉቃስ 14
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
³¹ ወይም ሌላውን ንጉሥ በጦርነት ሊጋጠም የሚሄድ፥ ከሁለት እልፍ ጋር የሚመጣበትን በአንድ እልፍ ሊገናኝ የሚችል እንደ ሆነ አስቀድሞ ተቀምጦ የማያስብ ንጉሥ ማን ነው?
³² ባይሆንስ ሌላው ገና ሩቅ ሳለ መልክተኞች ልኮ ዕርቅ ይለምናል።
³³ እንግዲህ እንደዚሁ ማንም ከእናንተ ያለውን ሁሉ የማይተው ደቀ መዝሙሬ ሊሆን አይችልም።
³⁴ ጨው መልካም ነው፤ ጨው አልጫ ቢሆን ግን በምን ይጣፈጣል?
³⁵ ለምድር ቢሆን ለፍግ መቈለያም ቢሆን አይረባም፤ ወደ ውጭ ይጥሉታል። የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️ 
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #እመቤታች_የማርያም_ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
➩** ለምን ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና አላት ቢሉ ?
ትርጓሜው :*
ጽንዕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና እመቤታችን ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሣን ለምኚልን አእምሮውን ጥበቡን በልቦናችን ሳዪልን አሳድሪልን፡፡

#ቅድስት አለ ንጽሕት ጽንዕት ክብርት ልዩ ሲል ነው፡፡

#ንጽሕት አለ :- ሌሎች ሴቶች ቢነጹ ከነቢብ(ከቃል ከመናገር)፣ ከገቢር(ከሥራ ከድርጊት) ነው ከሐልዮ (ከሐሳብ)አይነጹም፡፡ እርሷ ግን ከነቢብ(ከቃል ከመናገር) ከገቢር(ከሥራ ከድርጊት) ከሐልዮ (ከሐሳብ) ንጽሕት ናትና፡፡

#ጽንዕትም አለ :- ሌሎች ሴቶች ቢጸኑ ለጊዜው ነው፡፡ ኋላ ግን ተፈትሖ አለባቸው፡፡ እሷ ግን ቅድመ ፀኒስ(ከመፀነሷ በፊት) ጊዜ ፀኒስ(በፀነሰች ጊዜ) ድኅረ ፀኒስ(ከፀነሰች በኋላ) ቅድመ ወሊድ(ከመውለዷ በፊት) ጊዜ ወሊድ(በወለደች ጊዜ) ድኅረ ወሊድ(ከወለደች በኋላ) ፅንዕት በድንግልና ናትና፡፡

#ክብርትም አለ:- ሌሎች ሴቶችን ብናከብራቸው ጸድቃን ሰማዕታትን፤ ጳጳሳት ኤጲስ ቆጶሳትን፤ ቀሳውስት ዲያቆናትን፤ ነገሥታት መኳንንትን ወልዱ ብለን ነው፡፡ እሷን ግን ወላዲተ አምላክ፣ እመ አምላክ፣ እመ ብርሃን ብለን ነውና፡፡

#ልዩም አለ:- እናትነት ከድንግልና አስተባብራ የተገኘች ከእመቤታችን በቀር ሌላ ሴት የለችም ወደፊትም አትኖርምና ፡፡

#ሰአሊ/ሰዓሊ ለነ አለ፡፡

ዐይኑ ‹ዓ› ነው ያሉ እንደሆነ (ሰዓሊ ለነ) አእመሮውን ለብዎውን ሳይብን አሳድሪብን ማለት ነው፡፡ አልፋው ‹አ› ያሉ እንደሆነ (ሰአሊ ለነ) ለምኚልን ማለት ነው፡፡
#ነሐሴ_5

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ነሐሴ አምስት በዚህች ቀን የደብረ ቢዘን #አባ_ፊልጶስ አረፈ፣ #ቅዱስ_አባ_አብርሃም ገዳማዊ አረፈ፣ የከበረ ተጋዳይ ወታደር #ቅዱስ_ዮሐንስ_ጻድቅ አረፈ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#አቡነ_ፊልጶስ_ዘደብረ_ቢዘን

ነሐሴ አምስት በዚህች ቀን የደብረ ቢዘን አባ ፊልጶስ አረፈ። አቡነ ፊልጶስ ዘደብረ ቢዘን እንደ ነቢዩ ኤርምያስ በእናታቸው ማኅፀን ሳሉ የተመረጡና እንደተወለዱ ነው ሰማንያ አንዱን የብሉይ መጻሕፍትን አጠናቀው ያወቁት ናቸው፡፡ በ12 ዓመታቸውም ለመመንኮስና ገዳም ለመግባት ወስነው ወላጅ እናታቸውን አሰናብቺኝ በማለት ጠይቀዋል፡፡ ቅድስት እናታቸውም መርቀው ሸኟቸውና ትግራይ ውስጥ ወደሚገኘውና ደብረ ጸራቢ ወደሚባለው ገዳም ገቡ፡፡ የገዳሙ አስተዳዳሪ አቡነ በኪሞስም የምንኩስና ቀንበሩና ሸክሙ እጅግ ከባድ መሆኑን በመንገር ወደ እናታቸው እንዲመለሱ ቢመክሯቸውም አቡነ ፊልጶስ ግን ለምንኩስና የታጩ ሙሽራ መሆናቸውን ነገሯቸው፡፡ ከብዙ ፈተናም በኋላ አመነኮሷቸው፡፡

በገዳሙም እንጨት እየለቀሙና እየፈለጡ፣ ውኃ እየቀዱ፣ የክርስቶስን ሕማሙን ሞቱን እያሰቡ በጾምና ጸሎት ሲጋደሉ ከኖሩ በኋላ ጌታችን ተገልጦላቸው ወደ ሽሬ እንዲሄዱ ነገራቸውና ሽሬ አደያቦ ወደሚባለው ስፍራ ሄዱ፡፡ ብዙ አስደናቂ ተአምራት እያደረጉ ወንጌልን በሀገሩ ዞረው ሰበኩ፡፡ እንደ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በጥላቸው ድውያንን ይፈውሱ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ወደ ደብረ ቢዘን እንዲሄዱ ተነግሯቸው የእርሳቸውን በረከት ለመቀበል ከመጡ 16 ደጋግ መነኮሳት ጋር ወደ ደብረ ቢዘን ሄዱ፡፡ ይኸውም በኤርትራ ክፍለ ሀገር በሐማሴን አውራጃ ከአሥመራ ከተማ በስተምሥራቅ 25 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኘው አስደናቂው ገዳም ነው፡፡

ጻድቁ የሐይቅ እስጢፋኖስን ባሕር በተአምራት ያቃጠሉት አባት ናቸው፡፡ በንጉሡ በዐፄ ዳዊት ዘመን ሰንበትን አንድ ብቻ ናት እያሉ በአንደኛዋ ሰንበት ሥራ ሲሠሩ ጻድቁ አቡነ ፊልጶስ ይህን ሰምተው አንዲት ሰንበት የሚሉትን ሁሉ ተቃወሟቸው፡፡ ከግብፅ የመጡት ጳጳስም ቀደም ብሎ ከአቡነ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ አሁንም ከአቡነ ፊልጶስ ጋር ንጉሡ ዐፄ ዳዊት አከራክረዋቸው ጳጳሱም በክርክሩ ተረቱ፡፡ ክፉዎችም በአቡነ ፊሊጶስ ላይ በክፋት ተነሱባቸው፡፡ በአቁማዳ ጠቅልለው ሐይቅ ባሕር ውስጥ ጣሏቸው፡፡ በዚህም ጊዜ እሳቸው የተጣሉበት ባሕር በእሳት ተቃጥሎ ጽድቃቸውን መስክሮላቸዋል፡፡ ዛሬም ድረስ በሐይቅ እስጢፋኖስ ባሕር ዳርቻ ላይ የተቃጠለው ድንጋይ ምልክቱ በግልጽ ይታያል፡፡ በወቅቱ የንጉሡ ሚስት በዋናተኛ አስፈልጋ ከሐይቁ ውስጥ አስወጣቻቸው፡፡ እግራቸውንም አጥባቸው ስትጨርስ የእግራቸውን እጣቢ ጠጣችው፡፡ ወዲያውም ‹‹ከማኅፀንሽ ፍሬ ታላቅ ጻድቅ ልጅ ይወጣል›› ብለው ትንቢት ነገሯት፡፡ በትንቢታቸውም መሠረት ታላቁ ጻድቅ ንጉሥ ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ተወልዱ፡፡ በወቅቱ በተፈጠረው አለመግባባትና ክፉዎችም በባሕር ውስጥ ስለጣሏቸው ንጉሡ ዐፄ ዳዊትም አቡነ ፊልጶስን ከልብ ይቅርታ ጠይቀው ወዲያው ታርቀዋል፡፡ በዘመናቸውም ርኃብ ስለነተሳ ጻድቁን ከገዳማቸው አስጠርተው ‹‹ምን ባደርግ ይሻለኛል?›› ብለው አማክረዋቸዋል፡፡ አቡነ ፊልጶስም ‹‹የ #ጌታችንን መስቀል ያስመጡ›› ብለው መከሯቸው፡፡

ንጉሡ ዐፄ ዳዊትም በአቡን ፊልጶስ ምክር መሰረት ከኢየሩሳሌም፣ ከቍስጥንጥንያና ከእስክንድርያ መንግሥታት ጋር ተጻጽፈው ዓሥሩን ታላላቅ ቅዱሳን ይዘው ሄደው መስቀሉን መስከረም 10 ቀን አምጥተውታል፡፡ ቅዱስ መስቀሉን ያመጡት ዓሥሩ ቅዱሳንም የደብረ ቢዘኑ አቡነ ፊልጶስ ፣ የጣና ደሴቱ አቡነ ኂሩተ አምላክ፣ የጣና ደሴቱ አቡነ እንድርያስ፣ አቡነ በትረ ማርያም፣ አቡነ ዮሐንስ፣ አቡነ ታዴዎስ፣ አቡነ ያፍቅረነ እግዚእ፣ አቡነ ዘካርያስ፣ አቡነ ያሳይና አቡነ ቶማስ ናቸው፡፡ አቡነ ፊሊጶስ ዘደብረ ቢዘን በታላቅ ተጋድሎ ኖረው ከ #ጌታችን ዘንድ ታላቅ ቃልኪዳን ከተቀበሉ በኋላ ነሐሴ 5 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል፡፡

#ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_አባ_አብርሃም_ገዳማዊ

በዚህች ቀን ሌላው አብርሃም አረፈ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ባለጸጎች ናቸው በተግሣጽና ፈሪሃ እግዚአብሔርን በማስተማር አሳደጉት ። በአደገ ጊዜም ያለ ፈቃዱ አጋቡት #እግዚአብሔርም ወደሚፈቅደው ይመራው ዘንድ ሲለምን ኖረ።

በሰባተኛውም ቀን በዐልጋው ላይ ሳለ የ #እግዚአብሔር ቸርነት አነሳሥቶት ከጫጉላ ቤቱ ወጣ ብርሃን እየመራው ሒዶ ባዶ ቤት አግኝቶ በውስጡ ገብቶ ኖረ ምግቡን ከሚቀበልባት ከጥቂት መስኮት በቀር መዝጊያ ሠርቶ ደጁን ዘጋ።

ዓለምን ከተወ በዓሥረኛው ዓመት አባትና እናቱ ብዙ ጥሪት ትተውለት ሞቱ እርሱ ግን ለድኆችና ለችግረኞች በትኖ በጾምና በጸሎት ተወስኖ እየተጋደለ ኖረ ከአንድ ዐጽፍና ሰሌን በቀር ምንም ምን ጥሪት አላኖረም እንዲህም ሆኖ ዐሥር ዓመት ተጋደለ።

#እግዚአብሔርም ትዕግሥቱን አየ በአንዲት አገርም አረማውያን ነበሩ ከታናሾቻቸው እስከ ታላላቆቻቸው ወደ ሃይማኖት ሊመልሳቸው የሚችል የሌለ። በአንዲት ቀንም አባ አብርሃምን ጳጳሱ አሰበው ብርታቱንና ብልህነቱንም አይቶ ቄስ እንዲሆንና እነዚያን አረማውያን እንዲመልሳቸው አስገደደው በግድ አስጨንቆም ቅስና ሾመው ። ወደዚያም ቦታ ደርሶ ቤተ ክርስቲያን ሠራ እነዚያን አረማውያን እርሱን ፈጣሪያቸውን ወደ ማወቅ ይመልሳቸው ዘንድ በውስጧ ወደ #እግዚአብሔር ጸለየ።

በአንዲት ቀንም ወደ ጣዖቶቻቸው ቤት ገባ ያን ጊዜ ጣዖታቱን ከመቀመጫቸው ጣላቸው የአገር ሰዎችም በአዩ ጊዜ ቁጣን ተመልተው አብዝተው ደበደቡትና ከአገር አበረሩት በጥዋትም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲጸልይ አገኙት።

ሁለተኛም በገመድ አሥረው ወደ ከተማው ውጭ ጐትተው በላዩም አፈር ቆልለው እንዳይሞት ጥቂት መተንፈሻ ትተው አልፈው ከዚያ ሔዱ። በ #እግዚአብሔርም ኃያል ተነሥቶ ሔደ ስለ መመለሳቸውም ሲጸልይ አገኙት በእንዲህ ያለ ሥራም እየተጋደለ ዐሥር ዓመት ኖረ።

የክብር ባለቤት #እግዚአብሔርም ትዕግሥቱን አይቶ ወደ ቀናች ሃይማኖት ልባቸውን መለሰ በ #አብ#ወልድ#መንፈስ_ቅዱስ ስም ከታናናሾች እስከ ታላላቆች ድረስ ሁሉንም አጠመቃቸው
የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ሃይማኖትም ጸኑ።

ከዚህም በኋላ በሃይማኖታቸው መጽናታቸውን ባየ ጊዜ ከንቱ ውዳሴ እንዳያመጣበት ፈርቶ ወደ #እግዚአብሔር ጸለየ አገሪቱንም በ #መስቀል ምልክት አማተበባትና ማንም ሳያውቅ ወጥቶ ወደ ሌላ አገር ሔደ ።

ሰይጣንም በሚያስፈራው በብዙ ሥራ ይፈታተነው ነበር ቅዱሱም የክብር ባለቤት በሆነ በ #ጌታችን ኃይል አሸነፈው ። ጽኑ በሆነ ተጋድሎም ኖረ ያለ ዕንባም ሰዓት አላለፈችውም በጥርሶቹም አልሳቀም በከንፈሮቹም ፈገግ አላለም ስጋውን ቅባት አልነካውም ስጋውንና ደሙን ከሚቀበልበት ጊዜ በቀር ፊቱንና እግሩን አልታጠበም ።

እናትና አባቱ በስድስት ዓመቷ ትተዋት የሞቱ እኅት ነበረችው ስሟም ማርያ ይባላል ዘመዶቿም ወደ አብርሃም አምጥተዋት ፈሪሀ #እግዚአብሔር ሃያ ዓመት ሆናት ድረስ ትሕትናንም እያስተማራት በእርሱ ዘንድ አደገች።

ከዚህም በኋላ ሰይጣን ቀንቶባት ከአንድ መነኩሴ ጋር አፋቀራት ድንግልናዋንም አጠፉች ልብሷንና አስኬማዋን ለውጣ ወደ ሌላ አገር ሔደች።
አባ አብርሃምም በዚያች ሌሊት ታላቅ ከይሲ ርግቢቱን ሲውጣትና ጥቂት ቆይቶ ከእግሩ በታች ሲተፋት ራእይን አየ። በማግሥቱም ማርያ ከቦታዋ ታጣች አባ አብረሃምም ደነገጠ ወደ #እግዚአብሔርም ከብዙ ዕንባ ጋር ጸለየ እርሷን ያገናኘው ዘንድ።

ከጥቂት ወራትም በኋላ እኅቱ ያለችበትን አባ አብርሃም ሰማ ሰዎችም እንዳያውቁት የምንኩስናውን ልብስ ለውጦ ፊቱንም ተከናንቦ የወታደር ልብስ ለብሶ በፈረስ ተቀምጦ ወዳአለችበት አገር ሔደ ከዚያም ደርሶ ማርያ ወዳለችበት ገባ የመሸተኛንም ልብስ ለብሳ በአያት ጊዜ እጅግ አዘነ ነገር ግን እንዳትሸሸው እንድታውቀው አልሆነም።

ከዚህም በኋላ ለሚያገለግላት አሽከር ከማርያ ጋር የሚደሰትበት መብልና መጠጥ እንዲያዘጋጅ የወርቅ ዲናር ሰጠው ለርካሽ ሥራ እንደሚፈልጓት ሰዎች ይመስላት ዘንድ።

ከራት በኋላም ወደ ውስጠኛው ቤት አስገባት በሩንም ዘጋ እጇንም ይዞ ራሱን ገለጠላት በአወቀችውም ጊዜ ደንግጣ እንደ በድን ሆነች ልጄ ሆይ አይዞሽ ከ #እግዚአብሔር በቀር ከኃጢአት ንጹሕ የሆነ የለም ነገር ግን ወደ ንስሐ ተመለሺ ወደቦታሽም ገብተሽ የቀድሞ ሥርዓትሽን ያዢ አላት እርሷም እሺ አለች።

በነጋም ጊዜም ወስዶ በፈረሱ አስቀመጣትና ደስ እያለው ተመለሰ እኅቱን ከሰይጣን እጅ ማርኳልና ወደቦታውም በደረሰ ጊዜ የቤቷን ደጅ ዘግቶላት ማቅ በመልበስ እየተጸጸተች የተጋድሎንም ሥራ እየተማረች በብርታቷና በተጋድሎዋ ያዩ ሁሉ እስቲአደንቁ ጸንታ ኖረች ።

#እግዚአብሔርም በዚህ ቅዱስ ሰው እጆች ድንቆች ተአምራቶችን አደረገ አጋንንትን በማስወጣት በሽተኞችን በማዳን ከአንዲት ዓመትም በኋላ የማርያን ንስሓዋን አይቶ በሰባ ዘመኑ የተመሰገነ #እግዚአብሔርን እያመሰገነ አረፈ።

ማርያ እኅቱም ከለቅሶ ጋር ትርኅምትን በማብዛት ቀንና ሌሊት እየተጋደለች ሌሎች አምስት ዓመታትን ኖረች ከዚያም በኋላ አረፈች ያዩዋትም በፊቷ ውስጥ ስለአለው ብርሃን #እግዚአብሔርን አመሰገኑ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ዮሐንስ_ጻድቅ

በዚህችም ቀን የከበረ ተጋዳይ ወታደር ዮሐንስ አረፈ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ክርስቲያኖች ናቸው እርሱም በከሀዲ በዑልያኖስ ሠራዊት ውስጥ ወታደር ሆነ። ንጉሡም ከባልንጀሮቹ ወታደሮች ጋራ ላከው የክርስቲያን ወገኖችንም በሚኖሩበት ቦታ ሁሉ እንዲአሠቃዩአቸው አዘዛቸው።

እርሱም ለባልንጀሮች ጭፍሮች ክርስቲያኖችን እጅግ እንደሚጠላቸውና እንደሚጣላቸው ይገልጽላቸዋል በጭልታም ገብቶ በጎ ነገርን የሚሹትን ሁሉ ይሰጣቸዋል ያጽናናቸዋልም። ሁል ጊዜም ይጸልያል ይጾማል ይመጸውታልም የቅዱሳንንም አኗኗር ኖረ ምስጉን #እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም አረፈ።

#ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ነሐሴ_5 እና #ከገድላት_አንደበት)
2024/09/23 23:23:28
Back to Top
HTML Embed Code: