Telegram Web Link
✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞✞✞

✞✞✞ እንኩዋን ለነቢዩ #ቅዱስ_ዮናስ እና ለእናታችን #ቅድስት_አውፎምያ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞✞✞

✞✞✞ ቅዱስ ዮናስ ነቢይ ✞✞✞

=>በቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ ከ12ቱ #ደቂቀ_ነቢያት አንዱ የሆነው #ቅዱስ_ዮናስ ከክርስቶስ ልደት 800 ዓመታት በፊት እንደ ነበረ ይታመናል:: #ሊቃውንት እንዳስተማሩን ደግሞ እናቱ #ቅዱስ_ኤልያስን የመገበችው የሰራፕታዋ መበለት ናት:: ቅዱስ ዮናስ ገና ሕጻን ሳለ በእሥራኤል ምድር ዝናብ ለ3 ዓመታት ከ6 ወራት ተከልክሎ ነበር::

+ይሕንንም ያደረገው ደጉ ነቢይ ኤልያስ ለአምልኮተ እግዚአብሔር ቀንቶ ነው:: በወቅቱ ኤልያስ በሰራፕታ ሳለ ሕጻኑ ዮናስ ታሞ ሞተ:: ልጇ የሞተባት መበለትም ኤልያስን ለመነችው:: ኤልያስም ወደ ፈጣሪው ማልዶ ሕጻኑን ዮናስን ከሞት አስነስቶታል:: ትንሽ ከፍ ባለ ጊዜም ከጉዋደኞቹ (ከነቢያቱ) #አብድዩና #ኤልሳዕ ጋር ሆነው ታላቁን ነቢይ ኤልያስን ተከትለውታል::

+ኤልያስ ካረገ በሁዋላ ሁሉም በየተሰጣቸው አገልግሎት ተሠማርተዋል:: ቅዱስ ዮናስን #እግዚአብሔር "ወደ ነነዌ ሒደሕ ንስሃን ስበክ" አለው:: ዮናስ ግን የፈጣሪውን መሐሪነት ጠንቅቆ ያውቃልና አልሔድም አለ:: (ተመልከቱ የየዋሕነት ብዛት)

+እግዚአብሔር እየደጋገመ እንዲሔድ ሲነግረው ነቢዩ "እንዲሕ የሚዘበዝበኝ ከፊቱ ብቀመጥ አይደል" ብሎ ሊኮበልል ወጣ:: ነገር ግን አልቀናውም:: በእርሱ ምክንያት ማዕበል ተነሳ:: ሕዝቡም ሊያልቁ ሆነ:: ከእንቅልፉ የነቃው ዮናስ ከመርከቡ ላሉት አሕዛብ አምልኮተ እግዚአብሔርን ሰብኮላቸው: በእርሱ ጠያቂነት ሐምሌ 15 ቀን ወደ ባሕር ጥለውታል::

+አሣ አንበሪም ተቀብሎታል:: በግዙፉ አሣ ውስጥም ያለ እንቅልፍ በጾም: በጸሎትና በምስጋና 3 ለቀን ቆይቷል::
ሙስና ሳያገኘውም በዚህች ቀን አሣ አንበሪው #ነነዌ ዳር ላይ ተፍቶታል:: ቅዱስ ዮናስ እግዚአብሔር እንዳዘዘው "እስከ ሠሉስ ዕለት ትትገፈታእ ነነዌ ዓባይ ሃገር" /እስከ ሦስት ቀን ድረስ ነነዌ ትገለበጣለች (ዮናስ 3:4)/ ብሎ አሰምቶ ሰበከ::

+የነነዌ ሰዎችም በስብከተ ዮናስ አምነው: ንስሃም ገብተው ድነዋል:: በዚህም ጌታችን በወንጌል ላይ አመስግኗቸዋል:: ቅዱስ ዮናስ መኮብለሉ #በሐዲስ_ኪዳን ለሚደረገው ምስጢረ ትንሳኤ ጥላ (ምሳሌ) ነውና ይደነቃል:: (ማቴ. 12:38) ነቢዩ ግን በተረፈ ሕይወቱ ሕዝቡን ሲያስተምር: ፈጣሪውን ሲያገለግል ኑሮ በመልካም ሽምግልና ዐርፏል::

+"+ ቅድስት አውፎምያ ሰማዕት +"+

=>እናታችን #ቅድስት_አውፎምያ (ስሟ አፎምያ አይደለም:: በስሕተት "ው" መካከል ላይ የገባች እንዳይመስልዎ:: እስመ ከመዝ ስማ-ስሟ እንዲሁ ነው የሚጠራው) በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን ከነበሩ ወጣት ክርስቲያኖች አንዷ ናት:: ገና ከልጅነቷ ልቧ በፍቅረ ክርስቶስ የተነደፈ ነበር::

+በዚህም ምክንያት ራሷን በጾምና በጸሎት ወስና ትኖር ነበር:: እድሜዋ ገና በአሥራዎቹ ቢሆንም በመንኖ ጥሪት መኖር ምርጫዋ ነበር:: ሊቃውንት አበው ከሰማዕትነቷ ደርበው "ጻድቅት አውፎምያ" እያሉም ይጠሯታል::

+አንድ ቀን ግን መንገድ ወጥታ ነበርና ክርስቲያኖች ሲሰቃዩ ተመለከተች:: ምንም ጥፋት ሳይገኝባቸው ክርስቶስን ስላመለኩ ብቻ ይሙት በቃ ተፈርዶባቸው ሊገደሉ እየተወሰዱ ነበር:: አሕዛብ ግብራቸው የአውሬ ነውና ርሕራሔ የላቸውም:: ሰማዕታቱ ደማቸው በየመንገዱ እየፈሰሰ ጥቁር ሰንሰለት በአንገታቸው: በእጃቸውና በእግራቸው ላይ አድርገው ይጐትቷቸው ነበር::

+ቅድስት አውፎምያ የተደረገውን ሁሉ ተመልክታ አምርራ አለቀሰች:: ፈጠን ብላም ወደ መኮንኑ ቀርባ ገሰጸችው::
"አንተ አእምሮ የጎደለህ! እንዴት ክርስቲያኖችን እንዲህ ታሰቃያለህ? አምላካቸው #ጌታ_ክርስቶስ ታጋሽ ባይሆን ኑሮ በቅጽበት ከገጸ ምድር ባጠፋህ ነበር" አለችው::

+በድፍረቷ የተገረመው መኮንኑ "አንቺስ ማንን ታመልኪያለሽ?" ሲል ጠየቃት:: እርሷም "ሰማይና ምድርን የፈጠረውን: ስለ እኛ ሲል በቀራንዮ አንባ የተሠዋውን #ኢየሱስ ክርስቶስን አመልካለሁ" ስትል መለሰችለት:: በዚያች ሰዓት የመኮንኑ ቁጣ በቅድስቷ ላይ ነደደ::

+ነገር ግን ቁጣውን ከቁም ነገር አልቆጠረችውምና እንዲያሰቃዩዋት አዘዘ:: ወታደሮቹ ሥጋዋን በብዙ አሰቃዩ:: ብላቴናዋ አውፎምያ ግን ጽንዕት ናትና አልቻሏትም:: በመጨረሻ በእሳት ተቃጥላ ትሞት ዘንድ ተፈረደባት::

+እሳቱ ከመሬት ከፍ ባለ ጊዜ ወደ ውስጥ ወረወሯት:: በእሳቱ መካከል ቁማ ለረዥም ጊዜ ጸለየች:: ከዚያም ነፍሷን አሳልፋ ሰጠች:: ምዕመናን በክብር ገንዘው ቀብረዋታል::

=>አምላካችን ከነቢዩና ከሰማዕቷ ወዳጆቹ በረከት ይክፈለን::

=>ሐምሌ 17 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ዮናስ ነቢይ (ከአሣ አንበሪ ሆድ የወጣበት)
2.ቅድስት አውፎምያ (ጻድቅትና ሰማዕት)
3.ቅዱስ ዮስጦስ ሰማዕት (ታላቁ)
4.ቅዱስ ዘካርያስ

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ እስጢፋኖስ ሊቀ ዲያቆናት (ቀዳሜ ሰማዕት)
2.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ወልደ ዘብዴዎስ)
3.ቅዱሳን አበው መክሲሞስና ዱማቴዎስ
4.አባ ገሪማ ዘመደራ
5.አባ ዸላሞን ፈላሢ
6.አባ ለትጹን የዋህ
7.ቅዱስ ኤዺፋንዮስ ሊቅ (ዘደሴተ ቆዽሮስ)

=>+"+ በዚያን ጊዜ ከጻፎችና ከፈሪሳውያን አንዳንዶቹ መለሱና:- 'መምሕር ሆይ! ከአንተ ምልክት እንድናይ እንወዳለን' አሉት:: እርሱ ግን መልሶ እንዲህ አላቸው:- 'ክፉና አመንዝራ ትውልድ ምልክት ይሻል:: ከነቢዩም ከዮናስ ምልክት በቀር ምልክት አይሰጠውም:: ዮናስ በአሣ አንበሪ ሆድ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት እንደ ነበረ እንዲሁ የሰው ልጅ በምድር ልብ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ይኖራል:: የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነስተው ይፈርዱበታል:: በዮናስ ስብከት ንስሃ ገብተዋልና:: እነሆም ከዮናስ የሚበልጥ ከዚህ አለ:: +"+ (ማቴ. 12:38)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>

" ፍቅር ያጌብረኒ ከመ እንግር ዜናሆሙ ለቅዱሳን"::/የቅዱሳንን ዜና(ታሪክ) እንድመሰክር ፍቅር ያስገድደኛል::  አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ /መጽሐፈ ምሥጢር/
https://www.tg-me.com/zikirekdusn
††† እንኳን ለሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ †††

††† ይህ ቅዱስ ሐዋርያ በአባቶቻችን ሐዋርያት መካከል ትልቅ ሞገስ የነበረውና "የጌታችን ወንድም" ተብሎ የተጠራ ነው:: ቅዱስ ያዕቆብ ወላጅ አባቱ አረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ (የእመቤታችን ጠባቂ) ሲሆን በልጅነቱ የሞተችው እናቱ ደግሞ ማርያም ትባላለች:: በቤት ውስጥም ስምዖን: ዮሳና ይሁዳ የተባሉ ወንድሞችና ሰሎሜ የምትባል እህትም ነበረችው::

እናቱ ማርያም ከሞተች በኋላ ዕጓለ-ማውታ (ደሃ አደግ) ሆኖ ነበር:: ነገር ግን በፈቃደ እግዚአብሔር አረጋዊ ዮሴፍ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ከቤተ መቅደስ ሊጠብቃት (ሊያገለግላት) ተቀብሎ ሲመጣ ያ ቤተሰብ ተቀየረ:: የበረከት: የምሕረትና የሰላም እመቤት የአምላክ እናቱ ገብታለችና ያ የሐዘን ቤት ደስታ ሞላው::

እመ ብርሃን ግን ገና ወደ ዮሴፍ ልጆች ስትደርስ አለቀሰች:: የአክስቷ ልጆች የሚንከባከባቸው አጥተው ቆሽሸው ነበር:: በተለይ ደግሞ ትንሹ ቅዱስ ያዕቆብ ያሳዝን ነበር:: እመ ብርሃን ማረፍ አልፈለገችም:: ወዲያው ማድጋ አንስታ ወደ ምንጭ ወርዳ ውኃ አምጥታ የሕፃኑን ገላ አጠበችው:: (በአምላክ እናት የታጠበ ሰውነት ምስጋና በጸጋ ይገባዋል::)

እመቤታችን ጌታ ከመወለዱ በፊት ለዘጠኝ ወራት: ከተወለደ በኋላ ደግሞ ለሁለት ዓመታት ሕፃኑን ያዕቆብን ተንከባከበችው:: ለሦስት ዓመት ከስድስት ወር ግን ድንግል ማርያም አምላክ ልጇን ይዛ ተሰዳለችና ተለያዩ:: ከስደት መልስ ግን ለሃያ አምስት ዓመታት ቅዱስ ያዕቆብ ከጌታችን ጋር ሲያድግ ወላጅ እናቱ ትዝ ብላው አታውቅም:: አማናዊቷ እናት ከጐኑ ነበረችና::

ሊቃውንት እንደ ነገሩን እመቤታችን ለቅዱስ ያዕቆብ ያልሰጠችው ነገር ቢኖር ሐሊበ ድንግልናዌ (የድንግልና ወተትን) ብቻ ነው:: ስለዚህም:-
"እመ ያዕቆብ በጸጋ ማርያም ንግሥተ ኩሉ" ይላል መጽሐፍ:: (መልክዐ ስዕል)

††† ቅዱስ ያዕቆብ "የጌታ ወንድም" ተብሎ በተደጋጋሚ በሐዲስ ኪዳን ተጠርቷል:: ለዚህ ምክንያቱ
1.ለሰላሳ ዓመታት ሳይነጣጠሉ አብረው በማደጋቸው
2.የጌታችን የሥጋ አያቱ (የቅድስት ሐና) የእህት ልጅ በመሆኑ
3.በዮሴፍ በኩልም የአንድ ቅድመ አያት ልጆች በመሆናቸው
4.ጌታችን ከትህትናው የተነሳ ደቀ መዛሙርቱን "ወንድሞች" ይላቸው ስለ ነበር ነው:: (ሥጋቸውን ተዋሕዶ ተገኝቷልና::)

ራሱ ቅዱስ ያዕቆብ ግን "የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ ነኝ" ብሎ በፈጣሪና በፍጡር መካከል ያለውን ልዩነት ገልጧል:: (ያዕ. 1:1) ቅዱስ ያዕቆብ ጌታችን ሲያስተምር ተከተለው::
¤ከሰባ ሁለቱ አርድእት ተቆጠረ
¤ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ወንጌልን ተማረ
¤ለመጀመሪያ ጊዜ ከድንግል ማርያምና ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር ሆኖ "የጌታን ትንሣኤ ሳላይ እህል አልቀምስም" ብሎ ማክፈልን አስተማረ
¤መንፈስ ቅዱስን ተሞልቶ ወንጌልን አስተማረ
¤የኢየሩሳሌም የመጀመሪያው ሊቀ ጳጳስ ሆኖ አገለገለ
¤በመጀመሪያዎቹ የክርስትና ዘመናት የሐዋርያት ሲኖዶሶችን በሊቀ መንበርነት መራ
¤ሙታንን አስንስቶ
¤ድውያንን ፈውሶ
¤የመካኖችን ማኅጸን ከፍቶ: አጋንንትንም አስወጥቶ ብዙ ተዓምራትን ሠራ:: እጅግ ብዙ አይሁዳውያንን ወደ አሚነ ክርስቶስ መልሶ መልካሙን ገድል ተጋደለ::

በመጨረሻ ዘመኑ ያላመኑ የአይሁድ አለቆች ወደ ቤቱ ተሰብስበው "የናዝሬቱ ኢየሱስ ማነው? የማንስ ልጅ ነው?" ሲሉ ጠየቁት:: እነርሱ ሰይጣን በሰለጠነበት ልቡናቸው "የዮሴፍ ልጅ ነው: የእኔም ወንድሜ ነው" እንዲላቸው ጠብቀው ነበር:: (ሎቱ ስብሐት ወአኮቴት)

††† በልቡናቸው ያሰቡትን ተንኮል የተረዳው ሐዋርያ ወደ ቤቱ ጣራ ወጥቶ መናገር ጀመረ:: "ለስም አጠራሩ ጌትነት ይሁንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ:-
አምላክ:
ወልደ አምላክ:
ወልደ አብ:
ወልደ ማርያም:
ሥግው ቃል:
እግዚአብሔር ነው:: እኔም ፍጡሩና ባሪያው እንጂ እንደምታስቡት ወንድሙ አይደለሁም" አላቸው::

ንዴታቸውን መቆጣጠር ያልቻሉት አይሁድ ከላይ ወጥተው ወደ መሬት ወረወሩት:: በገድል የተቀጠቀጠ አካሉንም እየተፈራረቁ ደበደቡት:: አንዱ ግን ከእንጨት የተሠራ ትልቅ ገንዳ አምጥቶ የቅዱሱን ራስ ደጋግሞ መታው:: ጭንቅላቱም እንዳልነበር ሆነ:: ሰማዕቱ ሐዋርያ ቅዱስ ያዕቆብ ወደ ወደደው ክርስቶስ በዚህች ቀን ሔደ::

ቅዱሱ ሐዋርያ ያዕቆብ ቤቱን እንደ ቤተ መቅደስ አበው ሐዋርያት ይጠቀሙባት ነበር:: በመላ ዘመኑ የሚያገድፍ ነገር (ጥሉላት) ቀምሶ : ጸጉሩን ተላጭቶ : ገላውን ታጥቦና ልብሱን ቀይሮ አያውቅም::
"ወዝንቱ ጻድቅ እኅወ እግዚእነ::
ኢያብአ ውስተ አፉሁ ሥጋ ወወይነ::
ወኢገብረ ሎቱ ክልኤተ ክዳነ" እንዲል::

††† ከጾም : ከጸሎትና ከመቆሙ ብዛትም እግሩ አብጦ አላራምድህ ብሎት ነበር:: ስለዚህም አበው "ጻድቁ (ገዳማዊው) ሐዋርያ" ይሉታል::

††† ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንድሙ ይባል ዘንድ ካደለው ሐዋርያ በረከትን ያድለን:: በምልጃውም ምሕረትን ይላክልን::

††† ሐምሌ 18 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ያዕቆብ ሐዋርያ (ከሰባ ሁለቱ አርድእት-የመጀመሪያው የኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳሳት)
2.ቅዱስ አትናቴዎስ ሰማዕት
3.ቅዱስ እንድራኒቆስ ሰማዕት
4.ዘጠኝ ሺህ ሰማዕታት (የቅዱስ ኤስድሮስ ማኅበር)

††† ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ፊልጶስ ሐዋርያ
2.አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ሰባኬ ሃይማኖት (ረባን)
3.አቡነ አኖሬዎስ ዘደብረ ጽጋጋ
4.ማር ያዕቆብ ግብጻዊ

††† "የእግዚአብሔርና የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ ያዕቆብ: ለተበተኑ ለአሥራ ሁለቱ ወገኖች:: ሰላም ለእናንተ ይሁን:: ወንድሞቼ ሆይ! የእምነታችሁ መፈተን ትዕግስትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቁጠሩት:: ትዕግስትም ምንም የሚጐድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም::" †††
(ያዕ. ፩፥፩)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

https://www.tg-me.com/zikirekdusn
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
#ሐምሌ_18_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበቡት_መልእክታት👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
1ኛ ቆሮንቶስ 15
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ ወንድሞች ሆይ፥ የሰበክሁላችሁን ደግሞም የተቀበላችሁትን በእርሱም ደግሞ የቆማችሁበትን በእርሱም ደግሞ የምትድኑበትን ወንጌል አሳስባችኋለሁ፤
² በከንቱ ካላመናችሁ በቀር፥ ብታስቡት፥ በምን ቃል እንደ ሰበክሁላችሁ አሳስባችኋለሁ።
³ እኔ ደግሞ የተቀበልሁትን ከሁሉ በፊት አሳልፌ ሰጠኋችሁ እንዲህ ብዬ፦ መጽሐፍ እንደሚል ክርስቶስ ስለ ኃጢአታችን ሞተ፥ ተቀበረም፥
⁴ መጽሐፍም እንደሚል በሦስተኛው ቀን ተነሣ፥
⁵ ለኬፋም ታየ በኋላም ለአሥራ ሁለቱ፤
⁶ ከዚያም በኋላ ከአምስት መቶ ለሚበዙ ወንድሞች በአንድ ጊዜ ታየ፤ ከእነርሱም የሚበዙቱ እስከ አሁን አሉ አንዳንዶች ግን አንቀላፍተዋል፤
⁷ ከዚያም በኋላ ለያዕቆብ ኋላም ለሐዋርያት ሁሉ ታየ፤
⁸ ከሁሉም በኋላ እንደ ጭንጋፍ ለምሆን ለእኔ ደግሞ ታየኝ።
⁹ እኔ ከሐዋርያት ሁሉ የማንስ ነኝና፥ የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ስላሳደድሁ ሐዋርያ ተብዬ ልጠራ የማይገባኝ፤
¹⁰ ነገር ግን በእግዚአብሔር ጸጋ የሆንሁ እኔ ነኝ፤ ለእኔም የተሰጠኝ ጸጋው ከንቱ አልነበረም ከሁላቸው ይልቅ ግን ደከምሁ፥ ዳሩ ግን ከእኔ ጋር ያለው የእግዚአብሔር ጸጋ ነው እንጂ እኔ አይደለሁም።
¹¹ እንግዲህስ እኔ ብሆን እነርሱም ቢሆኑ እንዲሁ እንሰብካለን እንዲሁም አመናችሁ።
¹² ክርስቶስ ከሙታን እንደ ተነሣ የሚሰበክ ከሆነ ግን ከእናንተ አንዳንዶቹ፦ ትንሣኤ ሙታን የለም እንዴት ይላሉ?
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ያዕቆብ 1
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ የእግዚአብሔርና የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ ያዕቆብ ለተበተኑ ለአሥራ ሁለቱ ወገኖች፤ ሰላም ለእናንተ ይሁን።
²-³ ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት
⁴ ትዕግሥትም ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም።
⁵ ከእናንተ ግን ማንም ጥበብ ቢጎድለው፥ ሳይነቅፍ በልግስና ለሁሉ የሚሰጠውን እግዚአብሔርን ይለምን፥ ለእርሱም ይሰጠዋል።
⁶ ነገር ግን በምንም ሳይጠራጠር በእምነት ይለምን፤ የሚጠራጠር ሰው በነፋስ የተገፋና የተነቃነቀ የባሕርን ማዕበል ይመስላልና።
⁷-⁸ ሁለት አሳብ ላለው በመንገዱም ሁሉ ለሚወላውል ለዚያ ሰው ከጌታ ዘንድ አንዳች እንዲያገኝ አይምሰለው።
⁹-¹⁰ የተዋረደው ወንድም ግን በከፍታው፥ ባለ ጠጋም በውርደቱ ይመካ፤ እንደ ሣር አበባ ያልፋልና።
¹¹ ፀሐይ ከትኵሳት ጋር ይወጣልና፥ ሣርንም ያጠወልጋልና፥ አበባውም ይረግፋልና፥ የመልኩም ውበት ይጠፋልና፤ እንዲሁ ደግሞ ባለ ጠጋው በመንገዱ ይዝላል።
¹² በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፤ ከተፈተነ በኋላ ለሚወዱት ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን የሕይወትን አክሊል ይቀበላልና።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ሐዋርያት 15
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹³ እነርሱም ዝም ካሉ በኋላ ያዕቆብ እንዲህ ብሎ መለሰ፦ ወንድሞች ሆይ፥ ስሙኝ።
¹⁴ እግዚአብሔር ለስሙ የሚሆንን ወገን ከአሕዛብ ይወስድ ዘንድ አስቀድሞ እንዴት እንደ ጐበኘ ስምዖን ተርኮአል።
¹⁵ ከዚህም ጋር የነቢያት ቃል ይሰማማል፥ እንዲህ ተብሎ እንደ ተጻፈ፦
¹⁶-¹⁷ ከዚህ በኋላ የቀሩት ሰዎችና በስሜ የተጠሩት አሕዛብ ሁሉ ጌታን ይፈልጉ ዘንድ እመለሳለሁ፥ የወደቀችውንም የዳዊትን ድንኳን እንደ ገና እሠራታለሁ፥ ፍራሽዋንም እንደ ገና እሠራታለሁ እንደ ገናም አቆማታለሁ ይላል ይህን የሚያደርግ ጌታ።
¹⁸ ከጥንት ጀምሮ ሥራው ሁሉ በእግዚአብሔር ዘንድ የታወቀ ነው።
¹⁹ ስለዚህ ከአሕዛብ ወደ እግዚአብሔር የዞሩትን እንዳናስቸግራቸው፥
²⁰ ነገር ግን ከጣዖት ርኵሰትና ከዝሙት ከታነቀም ከደምም ይርቁ ዘንድ እንድንጽፍላቸው እቈርጣለሁ።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ሐምሌ_18_ቀን_በቅዳሴ_ሰዓት_የሚነበበው_የሚዜመው_የቅዳሴ_ምስባክ👇

✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
"ወኢነበርኩ ውስተ ዐውደ ከንቱ። ወኢቦእኩ ምስለ ዐማፅያን። ጸላዕኩ ማኅበረ እኩያን "። መዝ.25፥4-5።
"በከንቱ ሸንጎ አልተቀመጥሁም፥ ከዓመፀኞችም ጋር አልገባሁም። የክፉዎችን ማኅበር ጠላሁ፥ ከዝንጉዎችም ጋር አልቀመጥም"። መዝ.25፥4-5።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️

#ሐምሌ_18_ቀን_የእለቱን_ወንጌል_እናንብብ📖👇
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
ማርቆስ 6
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ ከዚያም ወጥቶ ወደ ገዛ አገሩ መጣ ደቀ መዛሙርቱም ተከተሉት።
² ሰንበትም በሆነ ጊዜ በምኵራብ ያስተምር ጀመር፤ ብዙዎችም ሰምተው ተገረሙና፦ እነዚህን ነገሮች ይህ ከወዴት አገኛቸው? ለዚህ የተሰጠችው ጥበብ ምንድር ናት? በእጁም የሚደረጉ እንደነዚህ ያሉ ተአምራት ምንድር ናቸው?
³ ይህስ ጸራቢው የማርያም ልጅ የያቆብም የዮሳም የይሁዳም የስምዖንም ወንድም አይደለምን? እኅቶቹስ በዚህ በእኛ ዘንድ አይደሉምን? አሉ፤ ይሰናከሉበትም ነበር።
⁴ ኢየሱስም፦ ነቢይ ከገዛ አገሩና ከገዛ ዘመዶቹ ከገዛ ቤቱም በቀር ሳይከበር አይቀርም አላቸው።
⁵ በዚያም በጥቂቶች ድውዮች ላይ እጁን ጭኖ ከመፈወስ በቀር፥ ተአምር ሊያደርግ ምንም አልቻለም።
⁶ ስለ አለማመናቸውም ተደነቀ። በመንደሮችም እያስተማረ ይዞር ነበር።
⁷ አስራ ሁለቱንም ወደ እርሱ ጠራ ሁለት ሁለቱንም ይልካቸው ጀመር፥ በርኵሳን መናፍስትም ላይ ሥልጣን ሰጣቸው፥
⁸ ለመንገድም ከበትር በቀር እንጀራም ቢሆን ከረጢትም ቢሆን መሐለቅም በመቀነታቸው ቢሆን እንዳይዙ አዘዛቸው።
⁹ በእግራችሁ ጫማ አድርጉ እንጂ ሁለት እጀ ጠባብ አትልበሱ አለ።
¹⁰ በማናቸውም ስፍራ ወደ ቤት ብትገቡ ከዚያ እስክትወጡ ድረስ በዚያው ተቀመጡ።
¹¹ ከማይቀበሉአችሁና ከማይሰሙአችሁ ስፍራ ሁሉ፥ ከዚያ ወጥታችሁ ምስክር ይሆንባቸው ዘንድ ከእግራችሁ በታች ያለውን ትቢያ አራግፉ። እውነት እላችኋለሁ፥ ከዚያች ከተማ ይልቅ ለሰዶምና ለገሞራ በፍርድ ቀን ይቀልላቸዋል አላቸው።
¹² ወጥተውም ንስሐ እንዲገቡ ሰበኩ፥ ብዙ አጋንንትንም አወጡ፥
¹³ ብዙ ድውዮችንም ዘይት እየቀቡ ፈወሱአቸው።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የሚቀደሰው ቅዳሴ የ #ቅዱሳን_ሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የ #ሐዋርያው_ቅዱስ_ያዕቆብ_ወልደ_ዮሴፍ የዕረፍት በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።
✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️✝️
የያዕቆብ መልእክት (3).pdf
1.3 MB
📚⛪️ የያዕቆብ መልእክት አንድምታ⛪️📚 
#ሐምሌ_19

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
ሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ በዚህች ቀን ሕፃኑ #ቅዱስ_ቂርቆስ እና #እናቱ_ቅድስት_ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራ ተቀበሉ፣ #ቅዱሳን_ሱርስ_ኀርማን_ያኑፋና_ስንጣንያ የሚባሉ የእስና ሀገር ሰዎች በሰማዕትነት ሞቱ፣ ብልህ የሆነ #ቅዱስ_በጥላን በሰማዕትነት ሞተ።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ቂርቆስና_እናቱ_ቅድስት_ኢየሉጣ

ሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ በዚህች ቀን ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራ ተቀበሉ። ይህም ሕፃን ዕድሜው ሦስት ዓመት ሲሆነው ከሮሜ አገር ወደሌላ ሀገር እናቱ ይዛው ሸሸች በዚያም የሸሸችውን መኰንን አገኘችው።

ሰዎችም ነገር ሠሩባት ወደርሱ አስቀረባትና ስለ አምልኮ ጠየቃት እርሷም መኰንን ሆይ ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነው ሕፃን አለ አማልክቶችህን ማምለክ መልካም እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያስረዳን ዘንድ እርሱን ጠይቅ አለችው።

ሕፃኑም ወደአለበት ጭፍራውን ልኮ ወደርሱ አስመጣው ሕፃኑንም ፊቱ ብሩህና ደስተኛ እንደሆነ አየውና አንተ ደስተኛ ሕፃን ሆይ እንዴት ነህ አለው። ሕፃኑም መልሶ አዎ ለእኔ ደስታ ተጠብቆልኛል ላንተ ግን ኀዘንና ልቅሶ ጥርስ ማፋጨትም ነው መጽሐፍ ለዝንጉዎች ተድላ ደስታ የላቸውም ብሏልና አለው እግዚአብሔር ኃይልና ንግግርን ሰጥቶታልና ብዙ ተናገረ በዚያም ያሉትን እስከ አስደነገጣቸው ድረስ ንጉሡን መኳንንቱንና ጣዖታቱን ረገማቸው ከብርታቱም የተነሣ አደነቁ።

መኰንኑም በአፈረ ጊዜ በየአይነቱ በሆነ ሥቃይ ታላላቆች የማይችሉትን ታላቅና አስጨናቂ የሆነ ሥቃይን አሠቃየው እናቱንም ከርሱ ጋር እንደ እርሱ አሠቃያት እግዚአብሔርም ያለምንም ጉዳት ያነሣቸው ነበር። ብዙዎች አሕዛብም ይህን አይተው አደነቁ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አምነው በሰማዕትነት ሞቱ የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበሉ።

በሕፃኑ ላይም የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ አደረበት። ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶችንም አደረገ ብዙዎች በሽተኞችንም አዳናቸው።

ከዚህም በኋላ መኰንኑ በታላቅ የናስ ጋን ውስጥ ውኃ ጨምረው በእሳት ያፈሉት ዘንድ አዘዘ የፍላቱም ድምጽ እንደ ክረምት ነጐድጓድ ሆነ ያን ጊዜም ፍርሀትና የሃይማኖት ጉድለት በእናቱ ላይ ደረሰባት ሕፃኑም ስለ እናቱ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ።

ያን ጊዜ ጌታችን ልቧን ወደ ሰማይ አሳርጎ ለቅዱሳን ሰማዕታት የተዘጋጁ የብርሃን ማደሪያዎችን አየች ከዚህም በኋላ ጸናች እግዚአብሔርንም አመሰገነችው ልጅዋንም ልጄ ሆይ ከእንግዲህ አንተ አባቴ ነህ እኔም ልጅህ ነኝ አለችው።

ያቺ ከኔ የተወለድክባትም ቀን የተባረከች ናት አለች ወደዚያ ወደ ጋኑ ውስጥ በገቡ ጊዜም የውኃው ፍልሐት እንደ ንጋት ጊዜ ውርጭ ቀዘቀዘ ከእግዚአብሔር የታዘዘ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወርዶ የእሳቱን ኃይል አቀዝቅዞታልና።

ከዚህም በኋላ መኰንኑ ሥጋቸው ተቆራርጦ እስከሚወድቅ ድረስ በመቃጥን ውስጥ አድርገው እንዲጐትቷቸው አዘዘ ከእግዚአብሔርም የታዘዘ መልአክ አዳናቸው መኰንኑም በታላቅ ሥቃይ ያሠቃያቸው ዘንድ አስቦ እስኪመክር ድረስ በወህኒ ቤት ዘጋባቸው።

ያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሕፃኑ ቂርቆስ ወርዶ አጽናናው አረጋጋውም። ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱሳን_ሱርስ_ኀርማን_ያኑፋ_እና_ስንጣንያ

በዚህች ቀን ስማቸው ሱርስ፣ ኀርማን፣ ያኑፋ፣ ስንጣንያ የሚባሉ የእስና ሀገር ሰዎች በሰማዕትነት ሞቱ። የሰማዕትነታቸው ምክንያትም እንዲህ ነው መኰንኑ አርያኖስ ወደ እስና ከተማ ሦስት ጊዜ ደረሰ። በመጀመሪያ የተባረከች መስተጋድልት የሆነች ዳላዢን ገደላት። ስማቸውን አስቀድመን የጠራናቸው አራቱን ልጆቿንም ገደላቸው። የሰማዕትነታቸውም ፍጻሜ ግንቦት ሰባት ቀን ሆነ።

በሁለተኛም ጊዜ ስማቸው አውሳፍዮስ፣ ታማን፣ ኀርማን፣ ባኮስ የሚባል አራቱን መኳንንት ገደላቸው። የሰማዕትነታቸውም ፍጻሜ ሰኔ ሰባት ቀን ሆነ። በሦስተኛም ጊዜ በቤቷ ውስጥ በዐልጋዋ ላይ ተኝታ የነበረችውን አሮጊት የአርያኖስ ወታደሮች ስለ እነዚህ ቅዱሳን ከጠየቋት በኋላ ገደሏት።

ከዚህም በኋላ መኰንኑ ከክርስቲያን ወገን ያገኙትን ሁሉ እንዲገድሉ የተክል ማጠጫ በተባለች በከተማዋ ምዕራብም መግደልን እንዳያቋርጡ አዘዘ ወደ ከበረ አባት ወደ ባሕታዊ ይስሐቅም እስኪደርሱ ድረስ በመንገድ ብዙ ሕዝብን አገኙ።

ያን ጊዜም ጠባቂያቸው እንዲህ እያለ ያጽናናቸውና ያረጋጋቸው ነበር። ወደ ሰማያዊት መንግሥት እንድትገቡ ጸንታችሁ ታገሡ። እንዲህም ሲወስዷቸው መኰንኑ ደረሰ በአዩትም ጊዜ ሁሉም በአንድ ቃል እኛ ክርስቲያን ነን እያሉ በግልጽ ጮኹ መኰንኑም ሁሉንም እንደበግ ያርዷቸው ዘንድ አዘዘ።

ጭፍሮች ግን በላያቸው በሰይፎች አጋና ተጫወቱ። በዚችም በሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ ቀን የእስናን ከተማ ሰዎች ከታናሾቻቸው እስከ ታላቆቻቸው ሴቶችንና ወንዶችን ጨረሷቸው። የመላእክት ሠራዊትም ነፍሶቻቸውን ይቀበሉ የብርሃን አክሊሎችንም ያቀዳጁአቸው ነበር።

ከዚህም በኋላ መኰንኑ ከዚያ ወደ እስዋን ከተማ ሔደ ሁለተኛም ወደ እስና ከተማ ተመልሶ ሦስት ገበሬዎችን የእርሻ ዕቃቸውን ተሸክመው አገኘ። መኰንኑንም በአዩት ጊዜ እኛ ክርስቲያን ነን ብለው በግልጥ ጮኹ መኰንኑም ሰምቶ ይገድሏቸው ዘንድ አዘዘ በእርሻ መሣሪያቸውም ገደሏቸው የእነዚህም ስማቸው ሱሩፋስ፣ አንጣኪዮስ፣ ስሐድራ ይባላል የሰማዕትነታቸውም ፍጻሜ መስከረም ዐሥራ አንድ ቀን ነው።

ይህንንም ቅዱስ አባት ኤጲስቆጶስ ይስሐቅን መኰንኑ አሥሮ ለጣዖት እንዲሠዋ አስገደደው። እምቢ ባለውም ጊዜ ወደ እሳት እንዲወረውሩት አዘዘ የሰማዕትነቱም ፍጻሜ ታኅሣሥ ዐሥራ አራት ቀን ነው ምእመናንም ሥጋውን ወስደው ገንዘው ቀበሩት። የስደቱ ወራትም ከአለፈ በኋላ ቤተ ክርስቲያን ሠርተው በስሙ አከበሩዋት።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_በጥላን_ጠቢብ_ሰማዕት

በዚህችም ቀን ትዕማዳን ከምትባል ከተማ ብልህ የሆነ ቅዱስ በጥላን በሰማዕትነት ሞተ። አባቱም አረማዊ ነበረ ስሙም አውሱጢኪዮስ ነበር እናቱ ግን አማኝ ነበረች ስሟም ኤልያና ነበር። በአደገ ጊዜም አባቱ ጥበብን ሁሉ አስተማረው እጅግም አዋቂ ሆነ።

በበጥላን ቤት አቅራቢያም አንድ ቄስ ይኖር ነበር። በጥላንም በፊቱ ሲያልፍ መልኩንና ዕውቀቱን ብልህነቱንና አሰተዋይነቱንም ይመለከት ነበር ከሀዲ ስለመሆኑም ስለርሱ ያዝን ነበር። ቄሱም በጥላንን መንገድ መርቶ ወደ ቀናች ሃይማኖት ያስገባው ዘንድ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመነው።

ስለ በጥላንም ልመናውን በአዘወተረ ጊዜ በጥላን በእርሱ እጅ ያምን ዘንድ እንዳለው ጌታችን በራእይ ገለጠለት ቄሱም ደስ አለው ሁልጊዜም በፊቱ ሲያልፍ በጥላንን ያነጋግረውና ሰላምታ የሚሰጠው ነበር። ስለዚህም በመካከላቸው ፍቅር ጸና።

ከዚህም በኋላ በጥላን ወደ ቄሱ ቤት ይገባና ስለ ሃይማኖት ይነጋገር ነበር። ቄሱም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት ምን ያህል ክብር እንዳላት ለሚያምኑበትም ሁሉ ዕውቀትና ማስተዋል እንደሚሰጣቸው ድንቆችና ታላላቅ ተአምራቶች እንደሚደረግላቸው ታላቅ ፈውስም እንደሚያደርጉ ገለጠለት።

በጥላንም ክብር ይግባውና በክርስቶስ የሚያምኑ ተአምራትን እንደሚያደርጉ ይህን በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ ብሎት በዚያ ቄስ ትምህርት በጌታ አመነ ቄሱም ሁልጊዜ የሃይማኖትን ትምህርት ያስተምረው ጀመር።
በአንዲትም ዕለት ቅዱስ በጥላን በከተማው አደባባዮች ሲያልፍ እባብ የነደፈውን አንድ ሰው ሲጨነቅ አየው እባቡም በርሱ ዘንድ ቆሞ ነበር በልቡም የመምህሬን ቃል ልፈትን ክብር ይግባውና በክርስቶስ ከአመንክ በስሙ ታምራት ታደርጋለህ ብሎኛልና አለ። እባብ ወደ ነከሰውም ሰው ቀርቦ ኃይሉን ይገልጽለት ዘንድ እባቡንም ይገድለው ዘንድ ሰውዬውን ያድነው ዘንድ ክብር ይግባውና ወደ እግዚአብሔር ረጅም ጸሎትን ጸለየ ያን ጊዜም ሰውዬው ያለ ምንም ጉዳት ድኖ በጤና ተነሣ ከይሲውም ወደቀ ወዲያውም ሞተ። የበጥላንም ሃይማኖቱ ተጨመረለት።

ከዚህም በኋላ በጥላን ወደ ቄሱ ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቀ ሁልጊዜም ወደ ቄሱ እየመጣ ይማር ነበር። በአንዲት ቀንም ያድነው ዘንድ አንድ ዕውር መጣ። የቅዱስ በጥላን አባትም ባየው ጊዜ ዕውሩን ከውጭ መልሶ ሰደደው በጥላንም አባቱን ማነው የፈለገኝ ብሎ ጠየቀው አባቱም ልታድነው የማትችል አንድ ዕውር ነው አለው።

እርሱም አባቱን የእግዚአብሔርን ክብር ታይ ዘንድ አለህ አለው ይህንንም ብሎ ዕውሩን ጠራውና ዐይኖችህ ቢገለጡ ያዳነህን ታመልከዋለህን አለው ዕውሩም አዎን አምናለሁ አለ ቅዱስ በጥላን በዕውሩ ላይ ረጅም ጸሎትን ጸለየ እጆቹንም በዕውሩ ዐይኖች ላይ አኑሮ እንድታይ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እመን አለው ወዲያውኑም ዐይኖቹ ተገለጡ።

አባቱም ይህን ድንቅ ሥራ በአየ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታ በኢየሱስ ከዕውሩ ጋር አመነ ቅዱስ በጥላንም ወደ ቄሱ ወሰዳቸውና የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው። ከዚህም በኋላ ባሮቻቸውን ነፃ አወጡ ገንዘባቸውንም ለድኆችና ለችግረኞች አከፋፈሉ።

ቅዱስ በጥላንም ጥበብን ያደርግ ነበር። ያለ ዋጋም ሰዎችን ያድናቸው ነበር። ነገር ግን ክብር ይግባውና በክርስቶስ እንዲያምኑ ይሻ ነበር። ስለዚህም ጥበበኞች ሰዎች በእርሱ ላይ ተነሡ ወደ ንጉሥም ሒደው ከቄሱ ጋራና ከአዳነውም ዕውር ጋራ በጌታችንም ከአመኑ ከብዙዎች ጋራ ከሰሱት። ወደ ንጉሡም በቀረቡ ጊዜ ንጉሡ ተቆጥቶ ለአማልክት ሠዉ አላቸው ባልታዘዙለትም ጊዜ ራሶቻቸውን በሰይፍ አስቆረጠ። የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ።

ከዚህም በኋላ ቅዱስ በጥላንን የጸና ሥቃይን አሠቃየው። ከእርሱም ድንቆችና ተአምራቶች ተገለጡ በእጁም ብዙ ሰዎች ክብር ይግባውና በጌታችን አመኑ። በሰማዕትነትም ሞቱ። ንጉሡም አይቶ በበጥላን ላይ ተቆጣ። ለአንበሳም አስጣለው አንበሳውም እግሩን ላሰው እንጂ ክፉ አላደረገበትም። ሁለተኛም ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ በዚህም ምስክርነቱን ፈጽሞ በመንግሥተ ሰማያት አክሊልን ተቀበለ።

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ሐምሌ_19)
††† እንኳን ለቅዱሳኑ ገብርኤል ሊቀ መላእክት: ቂርቆስ ወኢየሉጣ: በጥላን ጠቢብ እና ሰማዕታተ እስና ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቅዱሳን ቂርቆስ ወኢየሉጣ: ወቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት †††

††† ቅድስት ኢየሉጣ እናታችን በዘመነ ሰማዕታት ከነበሩና በዚህ ስም ከሚጠሩ ቅዱሳት አንዷ ናት:: በወቅቱ ቅዱስ ቂርቆስ የሚባል ደግ ልጅ ወልዳ ባሏ ባለመኖሩ በመበለትነት ትኖር ነበር:: የዚያ ዘመን ክርስቲያኖች ለክርስቶስ የነበራቸው ፍቅር ከመነገር በላይ ነው:: በዛው ልክ ደግሞ መከራው በጸጉራቸው ቁጥር ልክ ነበር::

ከሮም ግዛት በአንዱ ከቅዱስ ልጇ ጋር የምትኖረው ቅድስት ኢየሉጣ የስደቱ ዘመን ሲመጣ እርሷም እንደ ሌሎቹ ክርስቲያኖች ተሰደደች:: እስክንድሮስ የተባለው ከሃዲ ንጉሥ ግን ያለችበት ድረስ ተከትሎ እንድትያዝና እንድትቀርብ አደረገ::

ወዲያውም "ስምሽ ማን ይባላል?" ቢላት "ክርስቲያን እባላለሁ" አለችው:: ንጉሡ ተቆጣ:: "መዋቲ ስሜን ከፈለክ ኢየሉጣ ይባላል" አለችው:: ንጉሡ መልሶ "አሁን ለጣዖት ካልሠዋሽ ሲጀመር ስቃይ: ቀጥሎም ሞት ይጠብቅሻል" ቢላት ቅድስቲቱ መልሳ "በከተማ ውስጥ የሦስት ዓመት ሕፃን አለና እርሱን አምጣው:: ማንን ማምለክ እንዳለብን ይነግረናል" አለችው::

አስፈልጐ ቅዱስ ቂርቆስን አስመጣው:: "ስምህ ማን ይባላል?" አለ ንጉሡ:: "ከማይደፈርስ ከንጹሕ ምንጭ የተቀዳ ጥሩ ምንጭ ስሜ ክርስቲያን ይባላል:: መዋቲ ስሜን ከፈለግህ ግን ቂርቆስ ይባላል" አለው::

ንጉሡ ሊያታልለው "ደስ የተሰኘህ ሕፃን" ቢለው ቅዱሱ ሕፃን "ትክክል ተናገርክ: ለእኔ በሰማያት ደስታ ይጠብቀኛል:: አንተ ግን እውነተኛው አምላክ ይፈርድብሃል" አለው:: በሦስት ዓመት ሕፃን አንደበት ዘለፋ የገጠመው ከሃዲ ተቆጣ::
እናትና ልጅን በብዙ መክፈልተ ኩነኔ አሰቃያቸው::

ሰውነታቸውን ቸነከረ: አካላቸውን ቆራረጠ: ዓይናቸውን አወጣ:: ሌላም ሊናገሩት የሚጨንቅ ስቃይን አሰቃያቸው:: በዚህች ቀን ግን ትልቅ ድስት አሰርቶ ባሩድ: አረር: ስብና የመሳሰሉትን ጨምረውበት በእሳት አፈሉት::

የእሳቱ ወላፈን አካባቢውን በላው:: በድስቱ ውስጥ ያለው ነገር እየፈላ ሲገላበጥ እንደ ክረምት ነጐድጓድ ይጮህ ነበር:: የስድስት ሰዓት የእግር መንገድ ድረስም ተሰምቷል:: ቅድስት ኢየሉጣ ይሔኔ ነበር ልቧ ድንግጥ ያለው:: ሕፃኑ ቂርቆስ የእናቱን ፍርሃት ሲመለከት ጸለየ::

"ፈጣሪዬ! ፍሬው ያለ ግንዱ አይቆምምና እኔን እንዳጸናሕ እናቴንም አጽናት" ሲል ለመነ::
"እግዚኦ ትፈቅድኑ ለፍሬሁ ተአልዶ:
እንዘ በእሳት ታውኢ ጉንዶ" እንዲል::
በዚያች ሰዓት ቅድስት ኢየሉጣ ዓይኖቿ ተከፍተው ሰማያዊ ክብርን ተመለከቱና ልቧ ወደ ድፍረቱ ተመለሰ::

ልጇንም "አንተ አባቴ ነህ: አንተን የተሸከመች ማኅጸኔ የተባረከች ናት" አለችው:: ከዚያም ሁለቱንም ወደ ፈላው ድስት ውስጥ ቢጨምሯቸው ፍጡነ ረድኤት ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወረደላቸው:: በበትረ መስቀሉ ባርኮ የፈላውን አቀዘቀዘው:: የነደደውን ውኃ አደረገው:: ቅዱሳኑ ቂርቆስና ኢየሉጣ ከብዙ መከራ በኋላ በሰማዕትነት አልፈዋል::

††† ቅዱስ በጥላን ጠቢብ †††

††† ቅዱሱ ከአሕዛብ ወላጆቹ ተወልዶ: ያደገውም በጣዖት አምልኮ ነው:: በሙያው እጅግ የተመሠከረለት ሐኪም ነበር:: የሃገሩ ሰዎች "ጠቢብ" እያሉም ይጠሩታል:: በጥላን ምንም ጣዖት አምላኪ ቢሆን በተፈጥሮው ተመራማሪና ቅን ነበር::

አንድ ካህንም በጐረቤቱ ነበርና ዘወትር ስለ ሃይማኖት ይከራከሩ ነበር:: ካህኑ ሌሊት ሌሊት ስለ በጥላን ተግቶ ይጸልይ ነበርና ተሳክቶለት አሳመነው::

አንድ ቀን በጥላን መንገድ ሲሔድ እባብ ሰው ነድፎ ለሞት ደርሶ አየውና ጸሎት አድርሶ ስመ ክርስቶስን ቢጠራ የተነደፈው ድኖ እባቡ ሞተ::

በዚህ ተዓምር ደስ ብሎት ወደ ካህኑ ሒዶ ተጠመቀ:: ከዚያም ጾም ጸሎትን ጀመረ:: በየቦታው እየዞረ ሕሙማንን እንደ ቀድሞው በመድኃኒት ሳይሆን በጸሎት ያድናቸው ነበር:: ስላዳናቸውም በርካቶቹ ወደ ክርስትና መጡ::

የአካባቢው ሰው: ወላጆቹን ጨምሮ ክርስቲያኖች ሆኑ:: በመጨረሻም ቅዱስ በጥላን: ቤተሰቦቹ: ካህኑና ከደዌ የዳኑት ወገኖቹ በአካባቢው ጣዖት አምላኪ ንጉሥ ፊት ቀርበው ክርስቶስን ሰብከው በሰማዕትነት ዐርፈዋል::

††† ቅዱሳን ሰማዕታተ እስና †††

††† እስና ማለት ግብጽ ውስጥ የምትገኝ የቀድሞ አውራጃ ናት:: በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን በከተማዋ በርካታ ክርስቲያኖች ይኖሩ ነበር:: የእንዴናው መኮንን መጥቶ "ክርስቶስን ካዱ: ለጣዖት ስገዱ" አላቸው:: ሕዝቡ በአንድ ድምጽ መለሱ:- "ይሕማ ፈጽሞ ሊደረግ አይችልም::" መኮንኑ ተቆጥቶ "ሁሉንም ግደሉ" አለ::

ወታደሮቹ ሰው አልመረጡም:: ከታዘለ ሕፃን አልጋ ላይ እስካለ ሽማግሌ: ከጤነኛ እስከ ሕመምተኛ: ሁሉንም ጨፈጨፏቸው:: ከተማዋ በደም ተነከረች:: ከከተማዋ ክርስቲያኖች ወሬ ለመንገር አንድ ሰው እንኳ አልተረፈም:: ሁሉም ስለ ክርስትና ደማቸውን አፈሰሱ::

††† ጌታችን ስለ ሰማዕታቱ ብሎ: ደማቸውንም አስቦ በሃይማኖታችን ያጽናን:: ከመከራም ይሰውረን:: በረከታቸውንም ያድለን::

††† ሐምሌ 19 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት
2.ቅዱስ ቂርቆስ ወእሙ ኢየሉጣ
3.ቅዱስ በጥላን ጠቢብ ሰማዕት እና ማኅበሩ
4.ቅዱሳን ሰማዕታተ እስና

††† ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት
2.አቡነ ዓቢየ እግዚእ ጻድቅ
3.አቡነ ስነ ኢየሱስ
4.አቡነ ዮሴፍ ብርሃነ ዓለም

††† "ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ: ወይስ ጭንቀት: ወይስ ስደት: ወይስ ራብ: ወይስ መራቆት: ወይስ ፍርሃት: ወይስ ሰይፍ ነውን?
'ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን:: እንደሚታረዱ በጐች ተቆጠርን::' ተብሎ እንደተጻፈው ነው::
በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን::" †††
(ሮሜ. ፰፥፴፭-፴፯)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
እንኳን ለቅዱስ ቂርቆስ ወኢየሉጣና ለሊቀ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ)

#ሐምሌ_፲፱#በዓለ_ቅዱስ_ገብርኤል_ወቅዱስ_ቂርቆስ_ወቅድስት_ኢየሉጣ_ወሥርዐተ_ማኅሌት፡፡
  በቀጨኔ ደ/.ሰ/መድኀኔ ዓለም ወደ.ት.ቅ.ገብርኤል.ቤ.ክ የፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት የተዘጋጀ

    ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት

✼ ነቢዩ ዳንኤል “ዐይኖቼንም አነሣሁ” አለና አስከትሎ “እነሆም በፍታ የለበሰውን ጥሩም የአፌዝን ወርቅ በወገቡ ላይ የታጠቀውን ሰው አየሁ፡፡
አካሉም እንደ ቢረሌ ይመስል ነበር፤ ፊቱም እንደ መብረቅ አምሳያ ነበረ፤ ዐይኖቹም #እንደሚንበለበል ፋና፣ ክንዶቹና እግሮቹም እንደ ጋለ ናስ፣ የቃሉም #ድምፅ እንደ ብዙ #ሕዝብ ድምፅ ነበረ፡፡… ይህንንም ታላቅ ራእይ አየሁ፤ ኃይልም አልቀረልኝም፤ ክብሬም ወደ ውርደት ተለወጠብኝ #ኃይልም አጣሁ፡፡ የቃሉንም ድምፅ ሰማሁ፤ የቃሉን ድምፅ በሰማሁ ጊዜ ደንግጬ በምደር ላይ #በግምባሬ_ተደፋሁ” አለ፡፡(ዳን.10፥5-9) ነቢዩ ዳንኤል እንዲህ ብሎ የተናገረው የመላእክትአለቃ የቅዱስ #ገብርኤልን አስፈሪ ግርማ በተመለከተ ጊዜ ነበር፡፡
✤ ገብርኤል የሚለው ቃል የሁለት ቃለት ጥምር ነው እነዚህም #ገብር እና #ኤል ሲሆኑ ትርጕማቸውም ገብር #አገልጋይ ማለት ሲሆን ኤል ማለት ደግሞ አምላክ ማለት ነው፤ በተገኛኘ ገብርኤል ማለት #የአምላክ_አገልጋይ /የእግዚአብሔርን ልጅ የሚመስል የአምላክ አገልጋይ ማለት ነው።

“እነሆ ከዋነኞቹ አለቆች” አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ”(ዳን.10፥13) ብሎ በተናገረው ንግግሩ በመላእክት ላይ የተሾሙ ሌሎች አለቆች እንዳሉ ማስተዋል እንችላለን፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በቅዱሳን መላእክት ዘንድ ስላሉት ነገዶች ሲገልጽ “… በሰማይ ያለውን በምደር ያለውን የሚታየውንና የማይታየውን መናብርትም ቢሆኑ አጋእዝትም ቢሆኑ መኳንንትም ቢሆኑ ቀደምትም ቢሆኑ ሁሉም በእጁ ሆነ፤ ሁሉም በእርሱ ለእርሱ ተፈጠረ” (ቈላ.1፥16) በማለት ይዘረዝራቸዋል፡፡ ከዚህ ተነሥተን መላእክት በተለያዩ ዐበይት ነገዶች የተከፈሉና ለእያንዳንዱም ነገድ የራሱ የሆነ አለቃ እንዳለው ማስተዋል እንችላለን፡፡
ቅዱስ ገብርኤልም ከእነዚህ ዐበይት የመላእክት ነገዶች መካከል አንዱ በሆነው #እርባብ በሚባለው ዐቢይ ነገድ ላይ የተሾመ ሲሆን ከ100ው ነገደ መላእክት መካከል ከበታቹ የሚመራቸው ዐሥር ነገደ መላእክት አሉት፤ ከተማቸውም በሰማየ #ራማ ነው፡፡

✼ ቅዱሳን መላእክት በቅዱስ ሚካኤል ፊት አውራሪነት የሰው ልጆች ጠላት የሆነውን ዲያብሎስን ተዋግተው ድል ከመንሳታቸው አስቀድሞ ቅዱስ ገብርኤል፣ እንደ አምላክ ሊመለክ የወደደውን ሳጥናኤልን በመቃወም ‹‹#ንቁም_በበህላዌነ_እስከ_ንረክቦ_ለአምላክነ - “አይዞአችሁ ፈጣሪያችን እስክናገኘው፣ እስክናውቀው ድረስ በያለንበት ጸንተን እንቁም፡፡” (አክሲማሮስ ገጽ.35) በማለት
#መላእክትን_ያረጋጋ_መልአክ_ነው፡፡ በተወዳጁ መልአክ በቅዱስ ሚካኤል መሪነት የሰው ልጆች ጠላት የሆነውን ዲያብሎስን ተዋግተው ድል እንዲያደርጉ ወደ ጥልቁ እንዲጣል አድርጓል ራእ12፥7፤ ነቢዩ ኢሳይያስ በሰማያት የሳጥናኤል ትዕቢትና ውድቀት ምን እንደሚመስል ሲጽፍልን “አንተ በንጋት የሚወጣ አጥቢያ ኮከብ ሆይ እንዴት ከሰማይ ወደቅህ! ወደ አሕዛብ መልእክትን የላክ አንተሆይ እንዴት እስከ ምድር ድረስ ተቀጠቀጥህ! አንተም በልብህ ወደ ሰማይ ዐርጋለሁ ዙፋኔንም ከእግዚአብሔር ከዋክብት በላይ ከፍ ከፍ አደረጋለሁ፤… በልዑልም እመሰላለሁ አልህ፡፡ ዛሬ ግን ወደ ሲኦል ትወድቃለህ፤ ወደ ምድር ጥልቅም ትወርዳለህ” (ኢሳ.1416) በማለት ገለጠልን፤ ወደ ምድር የጣሉት በመላእክት አለቃ በቅዱስ ሚካኤል  እና በቅዱስ ገብርኤል  መሪነት   ነበር፡፡

✼ ቅዱስ ገብርኤል ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ከሊቃነ መላእክት አንዱና በእግዚአብሔር ፊት የሚቆመው ታማኝ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ነው ብሏል ሉቃ 1፥19፤ ታላቁ ነቢይ ሄኖክም ስለ ነገረ
መላእክት በተናገረበት አንቀጽ እንዲህ ሲል መስክሯል ‹‹በአበቦች ላይ በገነትም በጻድቃን ላይ #በኪሩቤልም ላይ የተሾሙ ከከበሩ መላእክት አንዱ #ገብርኤል ነው፡፡›› ሄኖክ 6፥7፤ ‹‹በሦስተኛውም በመላእክት ሁሉ ላይ የተሾመ ቅዱስ ገብርኤል ነው››ሄኖክ 10፥14 እያለ የመልአኩን ክብር ተናግሯል፡፡

ቅዱስ ገብርኤል ቅዱሳን ይሆኑ ዘንድ ለተጠሩት መንፈሳዊ እውቀቱን የሚያካፍላቸው መልአክ ብቻ አይደለም፤ ለእግዚአብሔር በመገዛታቸው ምክንያት ከአላውያን ገዢዎች ከሚደርስባቸው መከራም የሚታደጋቸው መልአክም ነው፡፡ ነገር ግን ያደረጋቸው ተዓምራቶች በመጽሐፍ ቅዱስ፣ በመልክኡ፣ በድርሳኑ፣ በገድሉ፣ በተዓምሩ የተጻፉ ቢሆንም ሐምሌ 19 እና ታኅሣሥ 19 ያደረጋቸውን ተራዳኢነት  ፡-

✤✤✤ ሐምሌ 19 ቀን ሕፃኑ ቅዱስ #ቂርቆስና እናቱ ቅድስት #እየሉጣ በሰማዕትነት መከራ የተቀበሉበት፤ ሊቀ መላእክት  ቅዱስ #ገብርኤል ደግሞ #ከእቶን እሳት ያዳናቸው እለት ነው::
✤✼፠ #ታኅሣሥ_19 አናንያና(ሚሳቅ)፣ አዛርያ(ሲድራቅ) እና ሚሳኤል(አብደናጎ) ያዳናቸው ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ አናንያና(ሚሳቅ)፣ አዛርያ(ሲድራቅ) እና ሚሳኤል(አብደናጎ) የፋርስ ባቢሎን ንጉሥ የነበረው ናብከደነፆር በዱራ(አዱራን) በሚባል ስፍራ ላይ ላቆመው ጣዖት አንሰግድም በማለታቸው ወደ እቶን እሳት እንዲጣሉ አድርጓቸዋል ፤ በመልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት ግን ከእቶን እሳቱ የልብሳቸው ዘርፍ እንኳን እሳት ሳይነካው ድነዋል፡፡ (ይህንን በዓል የምናከብረው ታኅሣሥ 19 ስለሆነ ታሪኩን በስፋት ለመረዳት የታኅሳስ 19 ስንክሳርን ወይም የታኅሣሥ ወር ልጥፈችንን ወደ ሃሏ  በመመለስ ይመልከቱ ፡፡)
✤ ቅዱስ #ቂርቆስ እድሜው የሦስት ዓመት ሳለ እናቱ ቅድስት እየሉጣ ከሮሜ ወደ ሌላ ሃገር ሸሽታ ይዛው ሄደች በዚያም የሸሸችውን መኮንኑን አገኘችው። የሚያውቋትም ሰዎች ሸሽታ እንደመጣች ስለተረዱ ለመኮንኑ ነገር ሰሩባት። መኮንኑም ቅድስት አየሉጣን አስጠራትና ስለ አምልኮ ጠየቃት። ቅድስት ኢየሉጣም መኮንን ሆይ፡ እድሜው ሦስት አመት የሆነው ሕፃን አለ አማልክቶችህን ማምለክ መልካም እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያስረዳን ዘንድ እርሱን ጠይቅ አለችው። መኮንኑም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስም ወደ አለበት ጭፍራውን ልኮ ወደ እርሱ አስመጣው ሕፃኑንም ፊቱ ብሩህና ደስተኛ እንደሆነ አየውና አንተ ደስተኛ ሕፃን ሆይ እንዴት ነህ አለው። ሕጻን ቅዱስ ቂርቆስም መለሰለት እንዲህም አለው። አዎ እኔ በጣም ደስተኛ ነኝ ደስታየም ተጠብቆልኛል ላንተ ግን ኀዘንና ለቅሶ ጥርስ ማፋጨትም ነው፤ መጽሐፍ ቅዱስም ለዝንጉዎች ተድላ ደስታ የላቸውም ብሏልና አለው። እግዚአብሔር አምላክ ኃይልንና ንግግርን ሰጥቶታልና በዚያ ለተሰበሰቡት ሰዎች እስኪደነግጡ ድረስ ብዙ ተናገረ። ሕፃን ቅዱስ ቂርቆስም ንጉሱን መኳንንቱንና ጣዖታቱን ረገማቸው ከብርታቱም የተነሳ አደነቁ። መኮንኑም በአፈረ ጊዜ በየአይነቱ በሆነ ስቃይ፡ ታላላቆች አንኳ የማይችሉትን ታላቅ አስጨናቂ የሆነ ስቃይን አሰቃየው። እናቱ ቅድስት እየሉጣንምከእርሱ ጋር እንደ እርሱ በጣሙን አሰቃያት። እግዚአሔብሔር ግን ያለ ምንም ጉዳት ያነሳቸው ነበር። ብዙዎች አህዛብም ይህን አይተው አደነቁ ክብር ይግባውና በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት አምነው በሰማእትነት ሞቱ የሰማእትነትንም አክሊል ተቀበሉ። በሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ላይም የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ አደረበት። ታላላቅ ድንቅ ተአምራቶችንም ያደርግ ነበር። ብዙዎች በሽተኞችንም ያድናቸው ይፈውሳቸው ነበር

። ይህንን ያየ መኮንን በታላቅ የነሃስ ጋን ውስጥ ውሃ ጨምረው በእሳት ያፈሉት ዘንድ አዘዘ። የፍላቱም ድምጽ እንደ ክረምት ነጎድጓድ ሆነ ድምጹም በጣም ያስተጋባ ነበር። ይህን ያየችና የሰማች እናት ቅድስት እየሉጣም ፍርሃትና የሃይማኖት ጉድለት ታየባት። ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ግን እናቱ ቅድስት እየሉጣን ሁኔታዋን አይቶ ወደ አምላኩ እግዚአብሔር ጸለየ። ያን ጊዜ ልዑል እግዚአብሔር ልቧን ወደ ሰማይ አሳርጎ ለቅዱሳን ሰማዕታት የተዘጋጁ የብርሃን ማደሪያዎችን አሳያት። ቅድስት እየሉጣም እንደገና በሃይማኖቷ ጸናች። እግዚአብሔር አምላኳንም አመሰገነችው። ልጇን ሕፃኑን ቅዱስ ቂርቆስንም ልጄ ሆይ አንተ ከእንግዲህ አባቴ ነህ እኔም ልጅህ ነኝ አለችው። ቅድስት እየሉጣም ለልጇ ያች የተወለድክባት እለት ቀኗ የተባረከችና የተቀደሰች ናት አለችው። የመኳንንቱ ጭፍሮችም እሳት ወደ አለበት ጋኖች ውስጥ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱን ቅድስት እየሉጣን በጨመሯቸው ጊዜ የውሃው ፍላት ወደያውኑንቀዘቀዘ። ከእግዚአብሔር የታዘዘ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወርዶ የእሳቱን ኃይል አቀዝቅዞታልና። ይህን ያየ መኮንን ሥጋቸው ተቆራርጦ እስከሚወድቅ ድረስ በመቃጥን ውስጥ አድርገው አንዲጎትቷቸው አዘዘ። ከእግዚአብሔርም የታዘዘ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል አዳናቸው። መኮንኑም በታላቅ ስቃይ ያሰቃያቸው ዘንድ አስቦ እስኪመክር ድረስ በወህኒ ቤት ዘጋባቸው። በዚህን ጊዜ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕጻኑ ቅዱስ ቂርቆስን አረጋጋው አጽናናው። ስሙን ጠርተው መታሰቢያ ለሚያደርጉለትም በረከትን እንደሚያገኝ ቃል ኪዳን ሰጠው ። እግዚአብሔር አምላካችን የሕጻኑ ቅዱስ ቂርቆስና የእናቱ የቅድስት ኢየሉጣን በረከታቸውንና ረድኤታቸውን ያድለን አሜን።

ቅዱስ ቂርቆስና ቅድስት ኢየሉጣ በእግዚአብሔር ቸርነት በቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት በእሳት ከመጣል በንፍር ውሃ ከመለብለብ ከዳኑ በኋላ እለስክንድሮስ መከራውን ፈርተው ይመለሳሉ ብሎ በሀብለ ሰናስል እያሰረ በችንካር እየቸነከረ ሲያሰቃያቸው ቆየ፡፡ የማይሆንለት ሲሆን እጅ እግራቸውን አስሮ ከዝግ ቤት አስቀመጣቸው፡፡ ጌታም የመከራቸውን ጽናት የትዕግስታቸውን ብዛት አይቶ ከመከራ ሊያሳርፋቸው ሽቶ በመንፈቀ ሌሊት ተገልጾ፤ በመጣ ጊዜ “ሰላም ለከ ኦ ፍቁርየ ቂርቆስ” ወዳጄ ቂርቆስ ሆይ ሰላም ላንተ ይሁን፤ ብሎ ሠላምታ ከሰጠው በኋላ የመከራህን ጽናት፣ የትዕግስትህን ብዛት አይቼ ቃል ኪዳን ልገባልህ ነው።” “ዘመጠነዝ ገድለ ተጋዲልየ ምንተኑ ትዔስየኒ” በሕፃንነቴ ይህን ያህል ተጋድዬ የምትሰጠኝ ምንድነው?” አለው። “አዐሥየከ ዘሀሎ ውስተ መልብከ” በልብህ ያለውን ሁሉ እሰጥሃለሁ አለው። እንኪያስ በስሜ ቤተ ክርስቲያን ከታነጸበት ረሃብ፣ ቸነፈር፣ የሰው በሽታ፣ የከብት እልቂት፣ የእኅል የውሃ ጥፋት፣ አይሁን አለ። ጌታም ይሁንልህ በማለት ቃል ኪዳን ገብቶላታል፡፡ ደግሞም “ኢትቅብር ሥጋየ በዲበ ምድር” ሥጋዬ በምድር አይቀበር አለው። “አልቦ ዘይፈደፍደከ ዘእንበለ መንበረ መንግሥትየ ወማርያም ወላዲትየ ወዮሐንስ መጥምቅየ” (ከመንበረ መንግስቴ፣ ከማርያም እናቴ ከዮሐንስ መጥምቅም በቀር በመንግሥተ ሰማያት የሚበልጥህ የለም።)
“ወዓዲ ከመ ኢይስማን ሥጋከ ዲበ ሠረገላ ኤልያስ አነብረከ”
(ሥጋህን እንዳይፈርስ በኤልያስ ሠረገላ አኖርልሃለሁ) ብሎ ተስፋውን ነግሮታል። እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ በመኮንኑ በሰይፍ ጥር ፲፮ በሰማዕትነት ያረፈች ሲሆን ቅዱስ ቂርቆስን ግን ተመለስ ቢለው አልመለስም እምነቴንም አልክድም ባለው ጊዜ ሰይፍ ጃግሬውን ጠርቶ በጥር ፲፭ አስገድሎት ሰማዕትነትን ተቀብሏል፡፡ የእናቱ የቅድስት ኢየሉጣ መታሰቢያዋ ዕለት በየወሩ በ፲፮ እመቤታችን ቃል ኪዳን በተቀበለችበት ቀን በሚታሰብበት የቅድስት ኪዳነ ምህረት ቀን ይታሰባል።
የመልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ምልጃና ጸሎት፤ የቅዱስ ቂርቆስና የቅድስት ኢየሉጣ በረከታቸው ቃል ኪዳናቸው ይድረሰን በእውነት ይጠብቀን ለዘለዓለሙ አሜን፨

/በቀጨኔ ደ.ሰላም መድኀኔዓለምና ደ.ት.ቅ.ገብርኤል ቤ.ክ ፍኖተ ሕይወት ሰ.ት.ቤት ፤    ትምሕርት ዋና ክፍል ፥ ንዑስ ክፍል /ሕትመት እና ሚዲያ/  የተዘጋጀ ::  ꔰ
  #share
Contact: https://www.tg-me.com/finotehiwot1927
.Facebook...
https://www.facebook.com/FinoteHiwotSundaySchool
.Telegram...  https://www.tg-me.com/medihanaelem 
http://tiktok.com/@finotehiwot 
.YouTube    https://www.youtube.com/channel/UCWVKGH0mSJl47u44uopEb2w
                   www.finotehiwotsundayschool.com
ፍኖተ ሕይወት ሰንበት ት.ቤት .
Telegram (https://www.tg-me.com/finotehiwot1927)
2024/09/23 21:31:39
Back to Top
HTML Embed Code: