Telegram Web Link
#ሚያዝያ_5
#አንድ_አምላክ_በሆነ_በአብ_በወልድ_በመንፈስ_ቅዱስ_ስም
ሚያዝያ አምስት በዚች ቀን የካህኑ የቡዝ ልጅ ታላቅ #ነቢዩ_ቅዱስ_ሕዝቅኤል አረፈ፣ የኢትዮጵያ ብርሃኗ #ማኅሌታዊው_ቅዱስ_ያሬድ የተወለደበት ነው፡፡

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ሕዝቅኤል_ነቢይ

ሚያዝያ አምስት በዚች ቀን የካህኑ የቡዝ ልጅ ታላቅ ነቢይ ሕዝቅኤል አረፈ። ይህም ካህንም ነቢይም ሆኖ ናቡከደነጾር የእስራኤልን ልጆች በማረካቸው ጊዜ ወደ ባቢሎን ተማርኮ ሔደ።

በባቢሎን አገርም ሳለ የትንቢት መንፈስ በላዩ አደረ በትንቢቱ ውስጥ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከከበረች ድንግል እመቤታችን ማርያም ስለ መወለዱና ከወለደችውም በኃላ በድንግልና ጸንታ ስለ መኖርዋ ተናገረ።

እንዲህም ብሎ ትንቢት ተናገረ እኔ ወደ ምሥራቅ ስመለከት የተዘጋች ደጅ አየሁ። ይህች በር ተዘግታ ትኖራለች አትከፈትም የሚገባባትም የለም። የእስራኤል ፈጣሪ እግዚአብሔር እንደተዘጋች ይገባባታልና ከእርሱ በቀር የሚገባም የሚወጣም የለም አለኝ።

ሁለተኛም ስለ ክርስትና ጥምቀት በንጹሕ ውኃ እረጫችኃለሁ ከኃጢአታችሁም ትነጻላችሁ ከርኲሰታችሁም ሁሉ። አዲስ ልብን እሰጣችኃላሁ አዲስ ዕውቀትንም አሳድርባችኃለሁ ድንቊርና ያለበትንም ልብ ከሰውነታችሁ አርቄ ዕውቀት ያለውን ልብ እሰጣችኃለሁ መንፈስ ቅዱስንም ተቀብለው የእግዚአብሔር ልጆች እንደሚሆኑ ተናገረ።

ሕዝቡንም ማስተማር ስለ መተዋቸው ካህናትን ሲገሠጽ ካላስተማራችኃቸውና ካላነቃችኃቸው የሰዎችን ነፍስ እግዚአብሔር ከእናንተ ይፈልጋል አላቸው።

ደግሞ ስለ ሥጋ መነሣት በሕይወት ለመኖርም ቢሆን ወይም በሥቃይ አስቀድሞ እንደነበሩት በድኖች ተነሥተው ከነፍሶቻቸው ጋራ አንድ ሊሆኑ አላቸው ብሎ ተናገረ። ለሚያነባቸው የሚጠቅሙ ብዙዎች ትምቢቶችን ተናገረ።

እግዚአብሔርም በእጆቹ ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶችን ገለጠ። የእስራኤል ልጆች በባቢሎን ሳሉ ጣዖት ባመለኩ ጊዜ ገሠጻቸው። ስለዚህም አለቆቻቸው በጠላትነት በላዩ ተነሥተው ገደሉት ይህም ሁሉ ትንቢቱ የክብር ባለቤት መድኃኒታችን ሰው ከመሆኑ በፊት ነው። የትንቢቱም ዘመን ሃያ ዓመት ነው።

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

#ቅዱስ_ያሬድ

ዳግመኛም በዚህች ቀን የኢትዮጵያ ብርሃኗ ማኅሌታዊው ቅዱስ ያሬድ የተወለደበት ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ ከእናቱ ቅድስት ክርስቲና (ታውክልያ) ከአባቱ ከቅዱስ አብዩድ (ይስሐቅ) በአክሱም በ505ዓ.ም ሚያዝያ 5 ቀን ተወለደ። አባቱ የአክሱም ጽዮን ቄሰ ገበዝ ነበር። በዚያን ጊዜ የብሉያትና የሐዲሳት መምህራንና ተማሪዎች የሚገኙት አክሱም ጽዮን ነውና የአኵሱም ቤተ ቀጢን (ቤተ ጉባኤ) መምህር የነበረው የእናቱ ወንድም አጎቱ መምህር ጌዴዎን ይባል ነበር።

ቅዱስ ያሬድ የሰባት ዓመት ብላቴና በኾነ ጊዜ አባቱ ስለ ሞተ ትምህርት ቤት ከመግባቱ በፊት በዚያ ዘመን አጠራር ለጌታው ዐደረ። ጌታውም የዐፄ ገብረ መስቀል ቢትወድድ አዛዥ ዜና ገብርኤል ይባላል። ያሬድን ዐቅሙ ለጉልበት ሥራ እንዳነሰ አይቶት "አንተ ልጅ ጋሻ ቢያስይዙህ አትችል፤ ሾተል ቢያሸክሙህ አይሆንልህ ለምን ከዚህ መጣህ?" ብሎ መለሰለት። ከዚያ በኋላ ከአጎቱ ዘንድ ሔደ። መምህሩም "ከዚህ የመጣህበት ምክንያት ምንድ ነው?" አለው። እርሱም "መጽሐፍት እማራለኹ ብዬ ነው የመጣኹት" አለው። መምህር ጌድዎንም ዐቅሙንና ዕውቀቱን በመገመት ለተማሪዎች "በሉ ፊደል አስቆጥሩት" አላቸውና ትምህርቱን ጀመረ። ኾኖም ቃለ እግዚአብሔርን የመቀበል ችሎታው ደካማ ስለነበር አብረው የሚማሩትም ሕፃናት "ሰነፍ ያሬድ ዕንጨት ስበር ውሃ ቅዳ" እያሉ አፌዙበት፤ ቀለዱበት። አጎቱ ጌዴዎንም ከትምህርቱ ድክመት የተነሣ በጨንገር (በአለንጋ) ቢገርፈው ሕፃኑ ያሬድም በዚህ ተበሳጭቶና ተስፋ ቆርጦ ከአክሱም ከተማ ወጥቶ ወደ እናቱ መንደር ወደ መደባይ ወለል ደረሰ። ለጥሙ ከምንጭ ውሃ ጠጥቶ ለድካሙ ከዛፋ ጥላ አረፈ። በምን ምክንያት ከጓደኞቹ በታች እንደኾነ ሲያስብና ሲያሰላስል ሲያዝንና ሲተክዝ ከቆየ በኋላ እግዚአብሔር አንድ የሚያጽናና ምልክት አሳየው። ይኸውም አንድ ትል የዛፏን ፍሬ ለመመገብ ፈልጎ ወደ ላይ እየወጣና እየወደቀ ተደጋጋሚ ሙከራ ሲያደርግ ከቆየ በኋላ በሰባተኛው ጊዜ ወደ ዛፋ ወጥቶ ፍሬዋን ሲመገብ ተመለከተ ተማሪ ያሬድም ከዚህ ትል ትዕግሥትን፣ ጽናትን፣ ጥረትን፣ ስኬትን ትምህርት ወስዶ እኔም እኮ ተስፋ ሳይቆርጥ ብዙ ጥረት ካደረግኹ እግዚአብሔር ያሳካልኛል ብሎ በተስፋ ተጽናንቶ እንደገና ወደ መምህሩ በመመለስ ትምህርቱን ለመቀጠል ወሰነ። ወደ መደባይ ያደረገው የነበረውን ጉዞ ሠርዞ ወደ አክሱም ከተማ ወደ መምህሩ ጌድዬን ጉባኤ ቤት ተመለሰ። በመጸጸት አጎቱን "አባቴ ስለተቆጣኸኝና ስለገረፍከኝ ተበሳጭቼ ሔጄ ነበር ፤ ነገር ግን በመንገድ ላይ እግዚአብሔር ስላስተማረኝ ተጸጽቼ መጥቻለኹ። ከእንግዲህስ ወዲህ እየተቆጣኽና እየገሠጽህ አስተምረኝ" ሲል አሳቡን ሳይደብቅ ገለጸለት።

አጎቱም ያሬድ ተጸጽቶ በመመለሱ በጣም ተደስቶ ዐይነ ልቡናውን ያበራለት ዘንድ ፈጣሪውን እያለቀሰ በለመነለት ጊዜ እግዚአብሔርም ጸሎቱን ሰምቶ ለያሬድ ዕውቀትን ገለጸለት። የያሬድ ኅሊናው ተከፍቶለት መዝሙረ ዳዊትን፣ ውዳሴ ማርያምን፣ መሓልየ ነቢያት፣ መሐልየ ሰሎሞንን፣ መጻሕፍተ ብሉያትንና ሐዲሳትን ንባባቸውን እስከ አገባባቸው አወቀ።

ቅዱስ ያሬድ ቅዱሳት መጻሕፍትን በቃሉ ይዞ ሲያስተምር ሳለ የትምህርቱን ጥራት፣ የሃይማኖት ጽናት፣ ደግነቱንና ትዕግስቱን፣ ትሕትናውና ተልኮውን በመምህሩና በካህናቱ ተመስክሮለት የአክሱም ጳጳሱ አባ ዮሐንስ ሢመተ ዲቁና ሾመው። ቅዱስ ያሬድ የታላቋ የአክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን አጋልጋይ ዲያቆን ኾነ።

ትምህርቱን በስፋት ስለቀጠለበት የመጻሕፍት ብሉያትና ሐዲሳት፣የመጻሕፍት ሊቃውንት ትርጓሜ ሊቅ ኾነ። ቅዱስ ያሬድም ለመንፈሳዊ አገልግሎት ወደ ኢትዮጵያ ከመጡት ከዘጠኙ ቅዱሳን ጋራ በቤተ ቀንጢን ጉባኤ ቤት ይውል ስለነበር ገዳማዊ ሕይወት ከእነርሱ በመማር እንደ እነ አቡነ አረጋዊ፣ አባ ገሪማ፣ አባ ጰንጠሌዎን በድንግልና ተወስኖ በንጽሕና ሲያገለግል ቆይቷል።

ለቅዱስ ያሬድ ሰማያዊ ዜማ መገለጽ፦ ኅዳር5 ቀን 527ዓ.ም ከጠዋቱ በሦስት ሰዓት እግዚአብሔር ከኤዶም ገነት ሦስት አዕዋፍን (መላእክት በአዕዋፍ ተመስለው) እርሱ ወዳለበት ላከለት። እነርሱም ያሬድ ባለበት ቦታ አንጻር በአየር ላይ ረብበው በግእዝ ቋንቋ "ብፁዕ ያሬድ ብፅዕት ከርሥ እንተ ጾረተከ ወብፁዕት አጥባት እለ ሐፀናከ (የተመሰገንክና የተባረክ ያሬድ ሆይ፤ አንተን የተሸከመች ማሕፀን የተመሰገነች ናት፤ አንተን ያሳደጉ ጡቶችም የተመሰገኑ ናቸው") ብለው አወደሱት። ቅዱስ ያሬድም ይህን ቃል በሰማ ጊዜ ወደ ሰማይ አንጋጦ ሦስቱን አዕዋፍ አየና "እናንተ በሰው አንደበት የምትናገሩ ከወዴት መጣችኹ" አላቸው። ከሦስቱ አዕዋፍ አንዷም "ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ማሕሌትን ሰምተኽ እንድታዜም የተመረጥኽ መኾኑን እነግርህና እናበሥርህ ዘንድ ወደ አንተ ተልከን መጥተናል" አለችው። ከዚያም ቅዱሳን መላእክት በዜማ ወደሚያመሰግኑባት ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም በአካል ተነጠቀ።
በዚያም ቅዱሳን መላእክት የሚታየውንና የማይታየውን የፈጠረ እግዚአብሔር በቅኔና በከፍተኛ ደምፅ ያለማቋረጥ በመንበሩ ዙሪያ ኾነው ሲያመሰግኑ እንዲሁም የእንዚራ፣ የበገና የመሰንቆ ድምፅ በሰማ ጊዜ ካለበት ሥፍራ እነርሱ ወዳሉበት ሊገባ ወደደ ነገር ግን አልተቻለውም። በመጨረሻም እነዚያ አዕዋፍ ወደ እርሱ ተመልሰው መጡ። "ያሬድ ሆይ፤ የሰማኸውን አስተውለኸዋል?" ብለው ጠየቁት እርሱም "አላስተዋልኸም" ብሎ መለሰላቸው። እንግዲያውስ አዲሱን የእግዚአብሔር ምስጋና ጥራ፤ እርሱም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነው። ከእግዚአብሔር መዘምራን ከቅዱሳን መላእክት በየዐይነቱ ዜማ ያለውን ማሕሌት ትማራለኽ፤ ታጠናለኽ" አሉት። ከዚህ በኋላ ቅዱስ ያሬድ ማሕሌቱን በየዓይነቱ አውጥቶ "መልካምን ነገር ልቤ ተናገረ" እያለ ከቅዱሳን መላእክት ተማረ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ " ሌሎችን አገልጋዮች ሰዎች ይሾሟቸዋል፤ አንተን ግን እኔ ሢመተ ክህነት (ቅስና) ሾሜኻለሁ" አለው።

ቅዱስ ያሬድም የመላእክት ሥርዓታቸው ዐይቶ፤ ማሕሌታቸውን አጥንቶ ኅዳር6 ቀን 527ዓ.ም በጠዋት ሦስት ሰዓት ወደ ቀድሞ ቦታው ተመልልሷል። ከዚያም ኾኖ ፊቱን ታቦተ ጽዮን ወዳለችበት ወደ ምሥራቅ አዙሮ እጆቹን ዘርግቶ እንዲህ ብሎ ሰማያዊ ዜማን ለመጀመርያ ጊዜ በአኵሱም አደባባይ (ዐውደ ምሕረት) ዘመረ።

"ሃሌ ሉያ ለአብ፣ ሃሌ ሉያ ለወልድ፣ ሃሌ ሉያ ወለመንፈስ ቅዱስ ቀዳሚሃ ለጽዮን ሰማየ ሣረረ ወበዳግም አርአዮ ለሙሴ ዘከመ ይገብር ግብር ግብራ ለደብተራ። ብሎ በዓራራይ ዜማ አዜመ። ይህም ማለት ዓለም ሳይፈጠር ለነበረ ዓለምን አሳልፎ ለዘለዓለም ለሚኖር አሁንም ላለ ለአብ ምስጋና ይገባል፤ ለወልድም ምስጋና ይገባል፤ ለመንፈስ ቅዱስም ምስጋና ይገባል፤ ከጽዮን አስቀድሞ ሰማይን ፈጠረ፤ ዳግመኛም ደብተራ ኦሪትን እንዴት አድርጎ መሥራት እንዳለበት ለሙሴ አሳየው ማለት ነው። ስለምን በዓራራይ ዜማ ጀመረ ቢሉ ቋንቋን የሚያናግር ምስጢር የሚያስተረጉም መንፈስ ቅዱስ የገለጠልኝ ዜማ ነው ሲል ነው። ምክንያቱም ዓራራይ ዜማ የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ነውና።

ከሰማይ እንደተመለሰ ለመጀመሪያ ጊዜ ጣዕመ ዜማውን ያሰማበት ቦታ "ሙራደ ቃል" (የቃል መውረጃ) እየተባለ ይጠራል። ይኸውም ዜማው ከሰማይ የወረደ ለመኾኑ እውነተኛ ማስረጃ ነው። ይህችንም ዜማ "አርያም" አላት። ይህም ማለት ከመላእክት ወይም ከሰማይ የተገኘች ማለት ነው።

ከዚህም በኋላ ከብሉይና ከሐዲስ፣ ከሊቃውንት መጻሕፍትም ከነአትናቴዎስ፣ ቄርሎስ፣ ዮሐንስ አፈወርቅ መጻሕፍት ለምስጋናና ለጸሎት የተስማሙትን ቃላት እየመረጠና እያቀና በአራቱ ክፍለ ዘመን፣ በመፀውና በሐጋይ በጸደይና በክረምት እንዲነገር አድርጎ ወስኖ አዘጋጀ። የመጽሐፉ የድርሰቱ ስም ድጓ ተባለ። ድጓ ማለትም በትግርኛ ደጉዓ ማለት መዝሙረ ኃዘን፥ የኃዘን ዜማ፥ ማለት ነው። ሙሾ። የዜማውን ዓይነት በሦስት ክፍል ወስኖ ተናግሮታል። እነርሱም ግእዝ፣ ዕዝል፣ ዓራራይ ይባላሉ። ግእዝ ማለትም አንደኛ በመጀመሪያ የተገኘ ማለት ነው፤ ዕዝል ማለትም ሁለተኛ ሆኖ ከግእዙ ጋር ተደርቦ፣ ተጨምሮ፣ ታዝሎ የሚነገር ማለት ነው። ዓራራይ ማለትም ሦስተኛ ተጨማሪ ሆኖ አራኅራኂ፣ ርኅራኄ፣ አሳዛኝ ልብን የሚመስጥና ደስ የሚያሰኝ ማለት ነው።መንግሥቱን ይህን ድርሰቱን ያዘጋጀበት ዘመን ከ540 ዓ.ም ሲሆን የመጨረሻ ልጁ አፄ ገብረ መስቀል ወረሰ።

አፄ ገብረ መስቀልና አባ አረጋዊ ቅዱስ ያሬድ እነዚህ ሦስቱ በአንድነት እንደነበሩ ታሪከ ነገሥቱና ገድለ አረጋዊ ይገልጽልናል። አቡነ አረጋዊ የደብረ ዳሞን ተራራ አቀማመጥ አይተው ደስ ስላላቸው፣ ንጉሡ አፄ ገብረ መስቀል በዚሁ ተራራ ላይ እንዲኖሩበትና እንዲጸልዩበት ፈቀደላቸው። እርሳቸውም ይህንን ተራራ ከተረከቡ በኋላ በተራራው ላይ የጸሎት ቤት ስለሌለ ንጉሡ አፄ ገብረ መስቀልን አንድ ቤተ ክርስቲያን እንዲሠራላቸው ለመኑት። ንጉሡም ቤተክርስቲያን ልሠራ የምችልበትን ሥፍራ መርጠው ያመልክቱኝ ብሎ ነገራቸው አቡነ አረጋዊም ተነሥተው ዞረው ቦታውን መርጠው አሳዩት።

ከዚህ በኋላ ንጉሡ በአዋጅና በትዕዛዝ ድንጋዩና እንጨቱ እየተሰበሰበ በከብትና በሠረገላ እየተጋዘ ተሰበሰበና ከታች ወደ ተራራው ላይ ወጥቶ ተሠራና የቤተ ክርስቲያኑ ሥራ በሁለት ዓመት አለቀ። ባለቀም ጊዜ የቤተክርስቲያኑ ሥራ ተመልካቾችን አስደነቀ።

ለዚሁም ቤተክርስቲያን ልዩ ልዩ የሆኑ አልባሳት፣ በወርቅ በብርና የተደጎሱና የተከፈፉ መጻሕፍትን አበረከቱ። ከማኅበረ በኩር የመጣውን የእመቤታችንን የቅድስት ድንግል ማርያምን ላይና አግብተው አቡነ አረጋዊ ባርከውና ቀድሰው ንጉሡና ጳጳሱ ቆረቡ። ከዚያም አፄ ገብረ መስቀል በተራራው ላይና በግርጌ ላሉት ሠራዊት ግብር አብልተው ነዳያን ሁሉ በንጉሡ ተደሰቱ።

ከዚህ በኋላ ቅዱስ ያሬድ በአክሱም ሲያስተምር ሳለ በንጉሡ አፄ ገብረመስቀልና አቡነ አረጋዊ፥ ወደዚህ ተራራ መጥቶ ቤተክርስቲያኑን እንዲጎበኝና እንዲዘምር ተጠርቶ ሲመጣ ከተራራው ሥር ሲደርስ የአቡነ አረጋዊን ደቀመዛሙርት ማትያስና ዮሴፍ የሚባሉትን ከወንዝ ዳር ዓሣ ሲያጠምዱ አግኝቶ "ዳኅንኑ ዝስኩ አረጋዊ አቡክሙ ፤ ይህ አረጋዊ አባታችሁ ደህና ነው?" ብሎ ጠየቃቸው። እነርሱም ደኅንነታቸውን ነገሩት። ከዚያም ቅዱስ ያሬድ ወደ ተራራው ላይ ወጥቶ ከአቡነ አረጋዊ ጋር በመንፈሳዊ አምኃ በፍቅር ተገናኙ ወደ ቤተክርስቲያኑም ሄዶ 3 ጊዜ ሰግዶ ከተሳለመ በኋላ የሕንጻውን ማማር በአድናቆት ተመልክቶ ከፍ ባለ የዜማ ድምፅ እያጉረመረመ እንዲህ ሲል ዘመረ። "ይሄውፅዋ መላዕክት እንተ በሰማያት ይሄውፅዋ መላዕክት እስመ ማኅደረ መለኮት ዖድክዋ ዖድክዋ ዖድክዋ ወርኢኩ ሥነ ሕንፄሃ ለቅድስት ቤተክርስቲያን ምሥአል ወምስጋድ ወምሥትስራየ ኃጢአት ይዕቲ ቅድስት ደብተራ"።
የሚለውን መዝሙር ከዘመረ በኋላ ስምንት ቀን ያህል ከአቡነ አረጋዊ ጋር ሰንብቶ ተመለሰ።

ከዚህ በኋላ ንጉሡ አፄ ገብረ መስቀልና አቡነ አረጋዊ ከቅዱስ ያሬድበጣና አብረው ወደ ሌላ ጠቅላይ ግዛት ጉብኝት ሄዱ። ከዚያም በጣና በአንዱ ደሴት ላይ የቅዱስ ቂርቆስን ቤተ ክርስቲያን ሠርተው ተቀመጡ። በዚያም ቦታ ቅዱስ ያሬድ ሁለት ዓመት አስተማረ። እርሱ እራሱ ጻፈው የሚባል ድጓ ምልክት የሌለው ዛሬ በዚሁ ደሴት በጣና ቂርቆስ ይገኛል።

ከዚህም ደሴት ከጣና ቂርቆስ ተነሥተው ንጉሡና አቡነ አረጋዊ ቅዱስ ያሬድም ወደ ደጋው ወደ ጋይንት ወጡ። በዚያም አንድ ትልቅ ተራራ አግኝተው መውጫው ጠፍቶባቸው ሲጨነቁ አንድ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ መጥቶ አቡነ አረጋዊን "ዑድ አባ መንገለ ምሥራቅ ወዑዳ ለዛቲ ደብር፤ ዙር አባ ወደ እርስዋም ትወጣ ዘንድ በምሥራቅ በኩል ዙር" አላቸው ወደ ምስራቅ ሲዞሩ መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነጭ ሐረግ ዘረጋላቸው እርሱን ይዘው ወደ ተራራው ላይ ወጡ። በዚሁ ተራራ ላይ የእመቤታችንንአምባ ክርስቲያን ሠሩ። የተራራውም ስም እስከ ዛሬ ድረስ ዙር አምባ ተብሎ ይጠራል። በዚህ ገዳም ምሥራቃዊ አቅጣጫ ቅዱስ ያሬድን የምትዘክር "ከርሞ አይደርቅ" የምትባል ዛፍ አለች። ቅዱስ ያሬድ በዚች ዛፍ ሥር ተቀምጦ ዝማሬ መዋሥዕት የተባለውን መጽሐፍ ለሦስት ዓመት ከሦስት ወር ስላስተማረበት ይህም ቦታ ገዳም እስከ ዛሬ ድረስ የዝማሬና የመዋሥዕት ምስክር ቦታ ሆኖ ይኖራል።
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ያሬድ ከአኵሱም ወደ ማይኪራህ አምርቶ እመቤታችን ቅዱስ ኤፍሬምን በአካለ ነፍስ ከሶርያ አባ ሕርያቆስ ከብሕንሳ አምጥታ ውዳሴዋንና ቅዳሴዋን ንባቡን እየነገሩት በዜማ እንዲደርስላት አድርጋለች። ከዚህም አያይዞ ለሥጋ ወደሙ ጸሎት የሚያገለግሉትን ንባቡ የሌሎች ሊቃውንት ድርሰት የሆኑትን ዐሥራ አራቱን ቅዳሴዎች በዜማ አዘጋጀ።

ከዚህ በኋላ ቅዱስ ያሬድ ወደ ሰሜን ተራሮች ጸለምት ሔዶ ምዕራፍ የተባለውን ድርሰቱን ደረሰ። ከዚህ በኋላ አገው፣ ፎገራ እና ወደ ሌሎችም ቦታዎች እየዞረ አስተማረ።

ቅዱስ ያሬድ በቅድስት አኵሰም ወንበር ዘርግቶ፣ ጉባኤ አስፍቶ ደቀ መዛሙርቱን እያስተማረ ሲኖር በጾመ፵ ሱባኤ ላይ ሳለ አንድ ቀን በምኵራብ ሰሞን ስለምናኔው እያስታወሰ በተመስጦ ሲዘምር የዜማው ጣዕም እንኳን ሌላውን ራሱን እጅግ ይመሥጠው ነበር። በጣዕመ ዝማሬው ተመሥጦ ሲያዳምጥ የነበረው ኢትዮጵያዊው ንጉሥ የዐፄ ገብረ መስቀል ዐይን ዐይኑን እየተመለከተ ሳይታወቀው በመስቀል ስላጢኑ (በበትረ መንግሥቱ ዘንግ) ጫፍ የቅዱስ ያሬድን እግር ወጋው። ቅዱስ ያሬድ ግንቀጠለ፤ ከሰማያት የተገኘች ቃለ ማሕሌቱን እስኪፈጽም ድረስ ከቆመበት ሳይንቀሳቀስ ሕመሙ ሳይታወቀው ደሙም ያለማቋረጥ ፈሰሰ።

ቅዱስ ያሬድ የጀመረውን በፈጸመ ጊዜ ንጉሡ ደንግጦ በትሩን ከቅዱስ ያሬድ እግያሬድን ቢነቅለው ደሙ በኃይል ይፈስ ጀመር። ያን ጊዜ ንጉሡ ዐፄ ገብረ መስቀል የቅዱስ ያሬድን ትዕግሥት ባለ ጊዜ በመደነቅ፣ በመገረምና በመደንገጥ ዝም በማለት አፉን ይዞ ቆመና ምድራዊ ዋጋ የሚፈልግ መስሎት "ካህን ያሬድ ሆይ የምትፈልገውን ዋጋ ጠይቀኝ" አለው። ቅዱስ ያሬድ መልሶ "የፈለግኹትን እንዳትከለክለኝ ቃል ኪዳን ግባልኝ" አለው። ንጉሡም የጸና ቃል ኪዳን ለቅዱስ ያሬድ ገባለት። ቅዱስ ያሬድም " ከዚህ ሐላፊ ዓለም ክብር ተለይቼ መናኝ ሆኜ እንድኖር ተወኝ ያሬድ አሰናብተኝ" ብሎ አሳብን ገለጸለት። ከዚህም በኋላ ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል ካህን የጠየቀውን እንዳይከለክለው ከአፉ የወጣውን መሐላ አስቦ በምናኔ አሰናበተው እንጂ ሊከለክለው አልቻለም።

ቅዱስ ያሬድ ካህንም የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ታቦት ወዳለችበት ጽዮን ማርያም ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ሁለት እጆቹን በታቦተ ጽዮን ላይ አኑሮ "ቅድስት ወብፅዕት፣ ስብሕት ወቡርክት፣ክብር ወልዕልት አንቀጸ ብርሃን መዓርገ ሕይወት" ብሎ በደረሰው አንቀጸ ብርሃን ጸሎት እመቤታችንን አመሰገነ። በዚህ ጊዜ እጁ በታቦተ ጽዮን ላይ ረቦ በመንፈስ ቅዱስ እየተቃኘ ስለነበር ከመሬት አንድ ክንድ ከፍ ከፍ ብሎ ይታይ ነበር። እስከመጨረሻው በከፍተኛ ቃል በዕዝል ዜማ እየዘመረ እግዚአብሔር እና እመቤታችንን ከአመሰገነ በኋላ እመቤታችን በጸሎት መንገድ እንድትመራውና እስከ ፍጻሜ ገድሉ ትረዳው ዘንድ በጸሎት ለመናት። እመቤታችንም መልሳ "ሰማያዊት ጽዮን ያደረግኻት መቅደሴን፣ በመዝሙር በማሕሌት ምስጋና የኪሩቤልና የሱራፌል ወገን ሰማያውያን ያደረግኻቸው ልጆቼ ካህናትን እንዴትድረስ ትተህ ትሔዳለህ" ብላ ቃል በቃል አነጋገረችው። የመንገዱን ስንብት እስክትፈቅድለት በለቅሶና በእንባ ዳግመኛ ለመናት እርሷም እንዲሔድ ፈቀደችለት።

የቅዱስ ያሬድ ምናኔ፦ ወደ ገዳም ሊሄድ ተዘጋጀ በዚህ ጊዜ የሚወዱት ካህናት፣ ደቀ መዛሙርቱ ሁሉ ተከትለውት እስከ ተከዜ ወንዝ ድረስ ሸኙት። ከእርሱ በሚለዩበትም ጊዜ "ሰላመ ነሳእነ ወሰላም ኃደግነ ለክሙ ወሰላመ እግዚአብሔር የሀሉ ምስለ ኩልክሙ፤ ሰላምን ከእናንተ ተቀበልን ለእናንተም ሰላምን ተውንላችሁ የእግዚአብሔር ሰላምም ከሁላችሁ ጋራ ይኹን" ብሎ በዜማ ተሰናበታቸው። ዳግመኛ "ወሰላም እግዚአብሔር እንተ ኵሉ ባቲ ተሀሉ ወትረ ምስለ ኵልክሙ፤ ፍቅርና ስምምነት ሁሉ ያለበት የእግዚአብሔር ሰላምታ ሁል ጊዜ ከሁላችሁ ጋራ ትኑር" ብሎ በጣዕ ዜማው መረቃቸው። ካህናቱም ይህን ሰምተው አለቀሱ። እርሱም ከእርሱ ጋራ አለቀሰ። በዚሁ ጣዕመ ዜማው የመጨረሻ ቡራኬውን ሰጣቸውና እርስ በእርሳቸው ተሳስመው ተነሰነባብተው ከእርሱ በመለየታቸው እያዘኑና እየተከዙ ወደ አገራቸው አኵሱም ተመለሱ። እርሱ ግን የተከዜን ወንዝ ተሻገረ። የወንዙ ፏፏቴና ጎርፍ እንሚጮህ አንበሳ ሲጮህ በሰማ ጊዜ "አኅለፍኮሙ በእግር እንተ የብስ ማእከለ ባሕር ተከዜ...፤ በተከዜ ባሕር መካከል በእግር እንደሚሻገር በደረቅ አሻገርካቸው..." እያለ በረቀቀ ምስጢር እግዚአብሔርን በማመስገን እየዘመረ ሲሒድ አንዲት ሴት ውሃ ቀድታ ወደ ቤቶ ስትመለስ ድምፁን ሰምታ ወይ ቃል! ወይ ቃል! እንዴት አንጀት ይበላል! ምንኛስ ያሳዝናል! ብላ ደጋግማ በማድነቅ ስለ ተናገረች ቅዱስ ያሬድ ቆሞ የዘመረባት ቦታ "ወይ ቃል" ተብላ ተጠራች። ዛሬ ይህች ቦታ ጎንደር ክፍለ አገር ደባርቅ አካባቢ "ወይ ቃል" ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ተብላ ትጠራለች።

ቅዱስ ያሬድ ወደ ሰሜን ተራሮች ሔዶ  ጸለምት ወጥቶ ብርድ በጸናበት በረዶ በተከማቸበት ሳኔር ተብሎ በሚጠራ በሐዊ ዐምባ ጽመና ይዞ ተቀመጠ። በዚያም በብዙ ትጋት በጾምና በጸሎት ይልቁንም በስብሐት እግዚአብሔር ብቻ ተወስኖ ጉባኤ ዘርግቶ፣ ትምህርት አስፍቶ ከሱራፌል መላእክት እንደተማረው አድርጎ ከጸለምት፣ ከስሜን፣ ከአገውና ከሌላ አገር ወደ እርሱ የሚመጡትን ሰዎች ሁሉ ማሕሌተ እግዚአብሔር እያስተማረ ኖረ።

ቅዱስ ያሬድ ከትውልድ አገሩ አኵሱም መንኖ ከወጣ በኋላ ትዕግሥቱን እያዘወተረ ወደ እርሱ የመጡትን ሁሉ በማስተማር በገዳመ ስሜን ኖረ። ቅዱስ ቍርባን ለመቀበልና ቅዱሳት ገዳማትን ለመሳለም በፈለገ ጊዜ በሠረገላ ብርሃን ተጭኖ አኵሱም ደርሶ ቅዱስ ቍርባን ተቀብሎ ሌሎች ገዳማትንም ይሳለም ነበር።

በመጨረሻ ቅዱስ ያሬድ ካህን ዘመኑን ሁሉ በመላእክት ማኅሌት እግዚአብሔርን በማገልገልና ይህን ማኅሌት ለሚከተሉት ደቀ መዛሙርት በማስተማር ዘመኑን ፈጽሞ ለሃያ ሁለት ዓመታት በላይ በምናኔ ታግሦ በገድሉና በጣዕመ ዜማው ፀላኤ ሠናያትን ድል አድርጎ ከዚህ ዓለም ድካምና መከራ የሚያርፍበት፣ የሚሰወርበት ቀንና ሰዓት መድረሱን በጸጋ በዐወቀ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱን ሰብስቦ "ይቤ ጳውሎስ ኃላፊ ንብረቱ ለዝንቱ ዓለም አኃውየ አስተፋጥኑ ገቢረ ሠናየ አነሰ በድረየኒ ፈጸምኩ ወሃይማኖትየኒ ሠለጥኩ እንከሰ ጽኑሕ ሊተ አክሊል ዘየዓሥየኒ መኰንነ ጽድቅ"  2ጢሞ4፥7-8 እያለ በሚያራራ ቃል ምክሩን ሰጥቶ ተሰናበታቸው። እነርሱም ምክሩን ተቀብለው "አባ አቡነ፣ አባ መምህርነ አይቴ ተሐውር ወለመኑ ተኀድገነ፤ አባታችን መምህራችን ወደ የት ትሔዳለኽ? ለማንስ ትተወናለኽ? እያሉ ሲያዝኑ ሲያለቅሱ በአንድ ዋሻ ውስጥ ገብቶ ግንቦት11 ቀን በ571ዓ.ም ተሰወረ። (ምንጭ፦ የቤተ ክርስቲያን ብርሃን ቅዱስ ያሬድና የቅዱስ ያሬድ ታሪክ ከሚሉት መጻሕፍት።)

ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

#ሚያዝያ_5_ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት፣
፩, #እግዚአብሔር ሰንበትን ቀደሰ
፪, ቅዱስ ሕዝቅኤል ነብይ
፫, ቅዱስ ዲዮስቆሮስ (ክፉ ላለመናገር ድንጋይ ጎርሶ የኖረ አባት)
፬, ቅድስት ታኦድራ
፭, ቅዱስ አርሳኒ
፮, ቅዱስ ያሬድ ካህን ልደቱ

#ወርኃዊ_በዓላት
፩, ቅዱስ ጴጥሮስ ሊቀ ሐዋርያት
፪, ቅዱስ ጳውሎስ ሐዋርያ
፫, አቡነ #ገብረ_መንፈስ_ቅዱስ ጻድቅ (አባ ገብረ ሕይወት)
፬, ቅዱስ ዮሐኒ ኢትዮጵያዊ
፭, ቅዱስ አሞኒ ዘናሒሶ
ነብዩ ሕዝቅኤል ስለ እርሷ መሰከረ። ድንቅ በሆነ ታላቅ ቁልፍ የተዘጋ ደጅ በምሥራቅ አየሁ አለ። ከኃያላን ጌታ በቀር ወደ እርሷ ገብቶ የወጣ የለም። ብሎ የተናገረው ቃል በውዳሴ ማርያም በየትኛው ክፍል ይገኛል?
Anonymous Quiz
62%
በረቡዕ የውዳሴ ማርያም ክፍል
15%
በአርብ የውዳሴ ማርያም ክፍል
13%
በእሁድ የውዳሴ ማርያም ክፍል
10%
በሰኞ የውዳሴ ማርያም ክፍል
በጣዕመ ዝማሬው ተመሥጦ ሲያዳምጥ የነበረውና ዐይን ዐይኑን እየተመለከተ ሳይታወቀው በመስቀል ስላጢኑ (በበትረ መንግሥቱ ዘንግ) ጫፍ የቅዱስ ያሬድን እግር የወጋው ንጉሥ ማን ይባላል?
Anonymous Quiz
11%
ንጉሥ አፄ ዳዊት
32%
ንጉሥ አፄ ዘርዐ ያዕቆብ
55%
ንጉሥ አፄ ገብረ መስቀል
3%
ንጉሥ አፄ ፋሲል
“ወንድሞቼ ሆይ፥ እምነት አለኝ የሚል፥ ሥራ ግን የሌለው ሰው ቢኖር ምን ይጠቅመዋል? እምነቱስ ሊያድነው ይችላልን?”👈ይህ ጥቅስ(ቃል) በየትኛው የመጽሐፍ ክፍል ውስጥ ይገኛል? ቅድሚያ መጽሐፍ ቅዱስዎን ገልጠው ያረጋግጡ!!
Anonymous Quiz
17%
ሮሜ 10፥17
26%
ያዕቆብ 2፥26
7%
ያዕቆብ 2፥20
29%
1ኛ ቆሮንቶስ 13፥13
21%
ያዕቆብ 2፥14
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
ሚያዝያ 6-አባታችን ቅዱስ አዳምና እናታችን ቅድስት ሄዋን ዓመታዊ መታሰቢያ በዓላቸው ነው፡፡
+ በዮረዳኖስ በረሃ ብቻዋን 47 ዓመት ስትጋደል የኖረችው የከበረች ቅድስት ግብፃዊት ማርያም ዕረፍቷ ነው፡፡
+ ጌታችን በከበረች በቅድስት ትንሣኤው ሳምንት ለሐዋርያው ቶማስ ተገለጠለትና የእጆቹንና የእግሮቹን የችንካሮች ምልክት አሳየው፤ በጦር የተወጋ ጎኑን ያስዳሰሰው እንደዛሬዋ ባለችው ጥንተ ዕለት ነው፡፡ ቅዱስ ቶማስም በዚህ ጊዜ ‹‹ጌታዬና ፈጣሪዬ ሆይ ከሞት መነሣትህን አመንኩ›› አለ፡፡
+ ልበ አምላክ ነቢዩ ቅዱስ ዳዊት ልደቱ ነው፡፡
+ ጻድቁ ኖኅ ልደቱ ነው፡፡
ቅድስት ማርያም ግብፃዊት፡- ገና በ12 ዓመቷ ሰይጣን ስለ ዝሙት ፍቅር ያለ ዋጋ ሥጋዋን እስከመስጠት አድርሷት ነበር፡፡ ጌታችን ወደ መቃብሩ የሚሄዱ ሰዎችን ገልጦላት ከእነርሱ ጋር ትሄድ ዘንድ ወደደችና በመርከብ ተሳፈረች፡፡ የመርከብ ዋጋ እንኳን ሳትከፍል ሰውነቷን ሰጠቻቸውና ይህንንም ሥራዋን ኢየሩሳሌም እስክትደርስ አላቆመችም ነበር፡፡ ወደ ጌታችን መቃብር ቤት ልትገባ ስትል ግን መለኮታዊ ኃይል መግባት ከለከላት፡፡ ከሚገቡ ሰዎች ጋር ለመግባት ብዙ ደከመች፡፡ በኋላ ግን ስለ ረከሰ ሥጋዋ አስባ በእመቤታችን ሥዕል ሥር ወድቃ አለቀሰች፡፡ ‹‹ያዘዝሽኝን ሁሉ እፈጽማለሁ ተዋሽን›› አለቻትና መግባት ቻለች፡፡ ወደ ሥዕሏም ተመልሳ አለቀሰች፡፡ ከሥዕሏም ድምፅ ወጣና ‹‹ወደ ዮርዳኖስ በረሃ ሂጂ›› አለቻት፡፡ ዮርዳኖስን ተሸግራ ሄዳ 47 ዓመት በበረሃ ብቻዋን ስትጋደል ኖረች፡፡ ሰይጣንም በዝሙት ጦር ይዋጋት ነበር፡፡ 40 ጾምን ሊፈጽም ቅዱስ ዞሲማስ ወደ በረሃው መጣ፡፡

በዚያ በረሃ ውስጥ የሚጽናናበትን ነገር እንዲሰጠው ወደ ጌታችን ጸለየና ማርያምን ገለጠለት፡፡ ሲጠጋት ሮጣ አመለጠችውና ‹‹ዞሲማስ ሆይ ጨርቅ ጣልልኝ›› ብላ በስሙ ስትጠራው እጅግ ደነገጠ፡፡ ልብሱንም ከሰጣት በኋለ ሰገደላት፡፡ ገድሏንም እንድትነግረው በብዙ ለመናትና ነገረችው፡፡ በዓመቱ ሥጋ ወደሙን አምጥቶ እንዲያቆርባት ጠየቀችው፡፡ በዓመቱ መጥቶ አቆረባት፡፡ አሁንም በዓመቱ ይመጣ ዘንድ ለመነችው፡፡ ድጋሚም ሲመጣ ዐርፋ አንበሳ አስክሬኗን ሲጠብቀው አገኛት፡፡ አንበሳውም መቃብሯን ቆፍሮ አሳየውና ገንዞ ቀበራት፡፡ ገድሏንም ለመነኮሳቱ ሁሉ ነገራቸው፡፡

አባ ዞሲማስም ከደጋግ ክርስቲያን ፍልስጤማውያን ወላጆች የተገኘ ጻድቅ ነበር፡፡ ለመምህርም ሰጥተውት በሚገባ ተምሮ ካደገ በኋላ መነኮሰ፡፡ ሲሠራም ሆነ ሲበላ እንኳን ምስጋናን ከአፉ የማያቋርጥ ደገኛ አባት ከሆነ ከ45 ዓመት በኋላ ቅስና ተቀበለ፡፡ ተጋድሎውንም ጨምሮ 13 ዓመት ከቆየ በኋላ ሰይጣን በልቡ ክፉ ሀብን አሳደረበት፡፡ በልቡም ከበጎ ሥራዎች ሁሉ እኔ ያልሠራሁት ምን ነገር አለ?›› ይል ጀመር፡፡ ጌታችንም ሊተወው አልወደደምና መልአኩን ልኮ ወደ ዮርዳኖስ አቅራቢያ ወዳለው በረሃ እንዲሄድ ነገረው፡፡ በዚያም ሌሎች ደጋግ አባቶችን አገኘና ከእነርሱ ተማረ፡፡ በዚያም ሳለ ወደ በረሃው ገብቶ የሚጽናናበት ነገር ይገልጥለት ዘንድ ወደ ጌታችን በጸለየ ጊዜ ነው ማርያምን ያገኛት፡፡ ዞሲማስ ብሔረ ብፁዓንም ድረስ ሄዶ የቅዱሳንን አኗኗራቸውንና ገድላቸውን አይቶ የጻፈልን ታላቅ አባት ነው፡፡ (ሙሉ ገድሉን በዕረፍቱ ዕለት ሚያዝያ 9 ቀን እናየዋለን) ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን!

+ + +
ጻዲቁ ኖኅ፡- እርሱም ከአባታችን አዳም ጀምሮ 10ኛ ትውልድ ነው፡፡ ከታናሽነቱ ጀምሮ ኃጢአት እንደሚበዛና ደጋጎች እንደሚያንሱ ሥጋ የለበሰ ሁሉ በጥፋት ውኃ እንደሚደመሰስ አምላካዊ ምሥጢርን የሚያይ ሆነ፡፡ ስለዚህም ፊቱ የተቋጠረ ሆኖ ፈጽሞ ያለቅስ ነበር፡፡

ጻድቁ ኖኅ ኖኅም የአቡዚር ልጅ የሆነች ሐይከል የምትባል ሴት አግብቶ ወደ እርሷ ሦስት ጊዜ ቢገባ ሦስት ልጆችን ሴም ካም ያፌትን ወለዳቸው፡፡ ከዚህም በኋላ እግዚአብሔር ለኖኅ ከደብር ቅዱስ ዕንጨት ቆርጦ መርከብን እንዲያሠራ ካዘዘው በኋላ አሠራሯን በዝርዝርና በጥልቀት አስረዳው፡፡ የቃየል ልጆችም ኖኅን መርከብ ሲሠራ አይተው ዘበቱበት፡፡ የአዳምንም ሥጋ ወስዶ በውስጡ አኖረ፡፡ ሴም ወርቁን፣ ካም ከርቤውን፣ ያፌት ዕጣኑን ወስደው ወደ መርከብ አስገቡ፡፡ ኖኅም ከልጆቹና 500 ዓመት ድንግልናውን ጠብቆ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ለአባታችን አዳም ሥጋ ሲያገለግል ኖረ፡፡ ከዚህም በኋላ ሚስት እንዲያገባ እግዚአብሔር አዘዘው፡፡ ሥጋ የለበሰ ሁሉ እንደሚደመሰስ ከእርሱ ዘር በቀር የሚተርፍ እንደሌለ ነገረው፡፡ ጻድቁ ከሚስቶቻቸው ጋራ ወደ መርከቡ ገባ፡፡ ንጹሐን የሆኑት እንስሳትና አእዋፋት ሴትና ወንድ ሰባት ሰባት፣ ንጹሐን ካልሆኑት ደግሞ ሁለት ሁለት ሴትና ወንድ አስገባ፡፡ ከዚያም ሰማይ ተከፍቶ የምድርም ምንጮች ሁሉ ተነድለው ራጃጅም ተራራዎችም እስኪሸፈኑ ድረስ 40 ቀንና 40 ሌሊት ዘነመ፡፡ ውኃውም በላያቸው 15 ክንድ ከፍ አለና ሥጋ የለበሰ ሁሉ ሞተ፡፡

ከ150 ቀንም በኋላ እግዚአብሔር ኖኅን አስቦ ነፋስን በምድር ላይ አመጣና ውኃውን አጎደለ፡፡ ምንጮች ተደፍነው የሰማይ መስኮት ተዘጋ፡፡ መርከቢቱም በ7ኛው በ12ው ቀን አራራት ተራራ ላይ አረፈች፡፡ ከጊዜም በኋላ እግዚአብሔር ኖኅን ከነቤተሰቡ አንድ ላይ ከመርከቡ እንዲወርዱ አዘዘው፡፡ ኖኅም መሠዊያን ሠርቶ ንጹሕ ከሆኑት ሁሉ ወስዶ መሥዋዕት ባቀረበ ጊዜ እግዚአብሔር መልካም መዓዛን አሸተተ፡፡ ዳግመኛም ምድርን በንፍር ውኃ እንዳያጠፋ ቃልኪዳን ገባለት፡፡ ምድር ፀንታ በምትኖርበት ዘመን ሁሉ ዘር መከር፣ ቅዝቃዜና ሙቀት፣ በጋና ክረምት፣ መዓልትና ሌሊት እንደማይቋረጥ ቃልኪዳን ገባለት፡፡ እግዚአብሔርም ኖኅንና ልጆቹን ባረካቸው፡፡ ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉዋት ግዟት አላቸው፡፡
ኖኅም ምድርን ያርሳት ይቆፍርራትም ጀመር፡፡ ወይንም ተክሎ ከእርሶ ፍሬውን አድርሶ ወይን ጠጥቶ በሰከረና ራሱን በሳተ ጊዜ የከነዓን አባት ካም የኖኅን ራቁትነት አይቶ ሳቀ፣ ሄዶም ለሁለቱ ወንድሞቹ ነገራቸው፡፡ ያፌትና ሴምም ልብስ ወስደው የአባታቸውን ርቃን ሸፈኑ፡፡ ኖኅም ከስካሩ በነቃ ጊዜ ሁሉም ያደረጉትን ዐወቀ፡፡ ‹ከነዓን የተረገመ ይሁን፣ ለወንድሞቹም ተገዥ አገልጋይ ይሁን› ብሎ ከረገመው በኋላ ‹‹የሴም ፈጣሪ እግዚአብሔር ይመስገን፣ እግዚአብሔርም የያፌትን አገር ያስፋ፣ በሴም ቤትም ይደር›› ብሎ መረቃቸው፡፡ አባታችን ኖኅ ‹‹እግዚአብሔር በሴም ቤት ይደር›› ማለቱ የጌታችንን ሰው መሆን በትንቢት መናገሩ ነው፡፡ እርሱም ከጥፋት ውኃ በኋላ 350 ኖረ፡፡ በአጠቃይ ዕድሜው 950 ዓመት በሆነ ጊዜ በሰላም ዐረፈ፡፡
የአባታችን የቅዱስ አባ ኖኅ ረድኤት በረከቱ ይደርብን በጸሎቱ ይማረን!
+ + +
ንጉሠ እስራኤል ቅዱስ ዳዊት፡- ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ነሐሴ 13 ቀን ተጸነሰ፣ በሚያዝያ 6 ቀን በይሁዳ በቤተልሔም ሀገር ተወልደ። 1ኛ ሳሙ 16፡10-11፡፡
ዳዊት ማለት ‹‹ኅሩይ›› ማለት ነው። አንድም ‹‹ልበ አምላክ›› ማለት ነው። ሐዋ 13፡22፡፡ ትውልዱ ከነገደ ይሁዳ ነው። አባቱ እሴይ እናቱ ሁብሊ ይባላሉ። ሁብሊ መልከ መልካም ሴት ነበረች። ከጎረቤታቸው ያለ ጎልማሳ መልኳን እያየ በሐጸ ዝሙት ተነደፈ። እሴይ የእሷም ፈቃድ እንደሆነ አውቆ መንገድ እሄዳለሁ ብሎ ስንቁን ይዞ ወጣ። የሄደ መስሎ ከዚያው ውሎ ሲመሽ በልብሱ ተሸፋፍኖ ድምጹን ለውጦ ያንን ሰው መስሎ ገብቶ ከእርሷ ጋር አድሮ ጎህ ሳይቀድ ወጥቶ ሄደ። ዳዊት በዚህ ዕለት ተጸንሷል።
“እነሆ፥ በዓመፃ ተፀነስሁ፥ እናቴም በኃጢአት ወለደችኝ” (መዝ 50፡5) ማለቱ ስለዚህ ነው። ቅዱሱም ተወልዶ ጉልበቱ ከጸና በኋላ የአባቱን በጎች ሲጠብቅ አድጓል።

እረኛና ብላቴና የነበረ ቢሆንም የፍልስጤማውያኑን ኃያል ሰው ጎልያድን በ12 ዓመቱ 5 ጠጠርን ከወንዝ ለቅሞ በወንጭፍ ወርውሮ ገድሏል፡፡ 1ኛ ሳሙ 12፡45-51፡፡ ንጉሥ ሳዖል በጌልቦአ ተራራ በራሱ እጅ ከሞተ በኋላ አስቀድሞ በይሁዳ 7 ዓመት በመላው እስራኤል 33 ዓመት ነግሡዋል፡፡ 2ኛ ሳሙ 2፡4፤ 5፡1-5፡፡ ‹‹እግዚአብሔር እንደ ልቡ የሆነ ሰው መርጦአል” (1ኛ ሳሙ 13፡14) ተብሎ በእግዚአብሔር የተመረጠና ነገረ ሥጋዌን፣ ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታን፣ ዳግም ምጽዓትን፣ ነገረ ማርያምን፣ ክብረ ቅዱሳንን፣ በስፋትና በጥልቀት የተናገረ የብሉይ ኪዳን ‹‹ወንጌላዊ›› የተባለ ቅዱስ ነቢይ ነው። “ብዙ ውሾች ከብበውኛልና የክፋተኞች ጉባኤም ያዘኝ እጆቼንና እግሮቼን ቸነከሩኝ። አጥንቶቼ ሁሉ ተቈጠሩ እነርሱም አዩኝ ተመለከቱኝም። ልብሶቼን ለራሳቸው ተከፋፈሉ፥ በቀሚሴም ላይ ዕጣ ተጣጣሉ…” እያለ የጌታችንን መከራ መስቀል በትንቢት ተናግሯል፡፡ መዝ 21 (22)፡ 16-18፡፡

“አምላክ በእልልታ፥ እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ።”፣ “ከክብሩ ውበት ከጽዮን እግዚአብሔር ግልጥ ሆኖ ይመጣል። አምላካችን ይመጣል ዝምም አይልም እሳት በፊት ይቃጠላል፥ በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ…” እያለ የጌታችንን ዕርገቱንና ዳግመኛ ለፍርድ የሚመጣ መሆኑን በግልጽ ተናግሯል፡፡ መዝ 46(47)፡4-5፣ መዝ 49(50)፡ 1-5፡፡ “የንጉሦች ሴት ልጆች ለክብርህ ናቸው በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” እያለ የእመቤታችንን ክብር አይቶ በትንቢት ተናግሯል፡፡ መዝ 44(45)፡9፡፡

ቅዱስ ዳዊት ታላቅና ገናና የከበረ ንጉሥ ከመሆኑ የተነሣ መንግሥቱ የመሢሕ መንግሥት ምሳሌ ሆኗል፤ መሢሑም ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዳዊት ስም ብዙ ጊዜ በመጽሐፍ ቅዱስ ተጠቅሶ ይገኛል። (ኢሳ 9፡7፣ ኤር 23፡5-6፣ ኤር 33፡14-17፣ ሕዝ 34፡23፣ ሆሴዕ 3፡5) በሐዲስ ኪዳንም ወንጌላዊያኑ ጌታችንን ‹‹የዳዊት ልጅ›› በማለት ነው መጀመሪያ ነገረ ልደቱን ማውሳት የጀመሩት፡፡ ማቴ 1፡1፡፡ ራሱ ጌታችንም ‹‹እኔ የእሴይ ሥርና የዳዊት ዘር ነኝ›› ብሏል፡፡ ራእ 22፡16፡፡
ቅዱስ ዳዊት 7 ሀብታት የተሰጡት ጻድቅ አባት ነው፡፡ እነዚህም የተሰጡት ሀብታት፡- ሀብተ ክህነት፣ ሀብተ መንግሥት፣ ሀብተ መዊዕ (የማሸነፍ ሀብት)፣ ሀብተ ትንቢት፣ ሀብተ ኃይል፣ ሀብተ በገና (ዝማሬ) እና ሀብተ ፈውስ ናቸው። ቅዱስ ዳዊት 24 ሰዓት ሙሉ የእግዚአብሔር ምስጋና እንዳይቋረጥ መዘምራንን መድቦ እንዲያገለግሉ ያደርግ ነበር፡፡ ራሱም 10 አውታር ባለው በገና ሌት ተቀን በፍጹም ተመስጦ ያመሰግን ነበር፡፡ በመዝሙሩም አጋንንትን ያቃጥል ነበር፡፡ መዝሙረ ዳዊት በውስጡ የያዘው ሚሥጢር እጅግ ጥልቅ ነው፡፡ አባቶቻችን ዛሬም በዱር በጫካ ሆነው መዝሙረ ዳዊትን አብዝተው ይደግማሉ፡፡ እንኳንስ የሰው ልጅ ይቅርና ‹‹መዝሙረ ዳዊትን›› ሰማያውያን ቅዱሳን መላእክትም እግዚአብሔርን ለማመስገኛነት ተጠቅመውበታል፡፡ ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት እድሜ ዘመኑን እግዚአብሔርን በማገልገልና በመፍራት ኖሮ በታኅሣሥ 23 ቀን በሰላም ዐርፎ በኢየሩሳሌም ተቀብሯል፡፡
ረድኤት በረከቱ ይደርብን በጸሎቱ ይማረን!
† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን †

እንኳን አደረሳችሁ፤ አደረሰን።

† ሚያዝያ 6 †

=>ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዚህች ዕለት እነዚህን ታላላቅ ቅዱሳን ታስባለች:-

† ቅድስት ማርያም ግብፃዊት †

† በዚች ቀን በበረሀ የምትኖር ግብፃዊት ማርያም አረፈች። ይቺም ቅድስት ከእስክንድርያ አገር ሁና ወላጆቿ ክርስቲያን ናቸው። እድሜዋ አስራ ሁለት አመት በሆናት ጊዜ የመልካም ስራና የሰው ሁሉ ጠላት ሸንግሎ አሳታት በእርሷም የማይቆጠሩ የብዙዎችን ነፍስ አጠመደ እርሱ ሰይጣን ስለ ዝሙት ፍቅር ያለ ዋጋ ስጋዋን እስከ መስጠት አድርሷታልና ።

በዚህም በረከሰ ስራ ውስጥ ኖረች በየእለቱም የኃጢአት ፍቅር በላይዋ ይጨመርባት ነበር። ሰውን የሚወድ የእግዚአብሄርም ቸርነት ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ሊባረኩ ወደ ኢየሩሳሌም ለመሄድ የሚሹ ሰዎችን ገለጠላት።

ከእሳቸውም ጋራ ትሄድ ዘንድ ልቧ ተነሳሳ ከብዙ ሰዎችም ጋራ በመርከብ ተሳፈረች። ባለ መርከቦችም የመርከብ ዋጋ በጠየቋት ጊዜ ስለ መርከብ ዋጋ ያመነዝሩባት ዘንድ ሰውነቷን ሰጠቻቸው ኢየሩሳሌምም እስከ ደረሰች ይህን ስራ አልተወችም።

የክብረ ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር ወደ አለች ቤተ ክርስቲያን ትገባ ዘንድ በወደደች ጊዜ መለኮታዊት ኃይል መግባትን ከለከለቻት። እርሷም ከሚገቡ ሰዎች ጋራ ትገባ ዘንድ ብዙ ጊዜ ደከመች ነገር ግን ከለከላት እንጂ የጌታ ኃይል አልተዋትም።

ከዚህም በኃላ ስለ ረከሰ ስራዋ አሰበች በልቧም እያዘነችና እየተከዘች ወደ ሰማይ ወደ እግዚአብሄር አይኖቿን አቀናች በማንጋጠጥዋም ውስጥ አምላክን የወለደች የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ስእል አየች።

በፊቷም አለቀሰች ፍጥረቶችን ሁሉ የምትረጅአቸው አምላክን የወለደሽ እመቤቴ ተዋሽኝ ከሁሉ ሰዎች ጋራ ገብቼ የመጣሁበትን ስራዬን የፈፀምኩ እንደሆነ ያዘዝሽኝን ሁሉ እኔ አደርጋለሁ ብላ በማመን ለመነቻት።

ቤተ ክርስቲያን ፈጥና ገባች በገባችም ጊዜ የበአሉን ስራ ፈፀመች። ከዚህም በኃላ አምላክን ወደ ወለደች ወደ እመቤታችን ወደ ከበረች ድንግል ማርያም ስእል ተመልሳ ወደ እርሷ መሪር ልቅሶ እያለቀሰች ረጅም ፀሎትን ፀለየች ነፍሰዋን ለማዳን እርስዋ ወደ ወደደችው ትመራት ዘንድ አምላክን ከወለደች ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ስእል ከዮርዳኖስ በረሀ ብትገቢ አንቺ እረፍትንና ድኀነትን ታገኚ አለሽ የሚል ቃል ወጣ።

ከእመቤታችን አምላክን ከወለደች ከቅድስት ድንግል ማርያም ስእል ይህን ቃል ተቀብላ ወድያውኑ ወጣች። በውጪም አንድ ሰው አግኝታ ሁለት ግርሽ ሰጣትና አምባሻ ገዛችሸት።

ከዚያም በኃላ የዮርዳኖስን ወንዝ ተሻግራ ፅኑእ ተጋድሎ እየተጋደለች በበረሀው ውስጥ አርባ ሰባት አመት ኖረች ሰይጣንም አስቀድማ በነበረችበት በዝሙት ጦር ይዋጋት ነበር።

እርሷ ግን በተጋድሎ ፀናች ከዚያም ከገዛችው አምባሻ ብዙ ቀን ተመገበች። ሁለት ሁለት ቀን ሶስት ሶስት ቀን ፁማ ከዚያ አምባሻ ጥቂት ትቀምስ ነበር በአለቀም ጊዜ የዱር ሳር ተመገበች።

በዚያችም በዮርዳኖስ በረሀ እየተዘዋወረች አርባ አባት አመት ሲፈፀምላት እንደ ገዳሙ ልማድ የከበረች አርባ ፆምን ሊፈፅም ቅዱስ ዘሲማስ ወደዚያች በረሀ መጣ። በሱ ደብር ላሉ መነኲሳት ልማዳቸው ስለሆነ በየአመቱ ወደ በረሀ ወጥተው የከበረች የአርባ ቀን ፆም እስከ ምትፈፀም በፆምና በፀሎት ተፀምደው በገድል ይቆያሉ ።

ስለዚህም ዘሲማስ ወደ ዮርዳኖስ በረሀ በወጣ ጊዜ የሚፅናናበትን ያሳየው ዘንድ እግዚአብሄርን ለመነው። በበረሀውም ውስጥ ሲዘዋወር ይቺን ቅድስት ሴት ከሩቅ አያት የሰይጣን  ምትሀት መሰለችው በፀለየም ጊዜ ከሰው ወገን እንደሆነች ተገለጠለችለት።

ወደርሷም ሄደ እርሷ ግን ከእርሱ ሸሸች ወደርሷም ይደርስ ዘንድ ከኃላዋ በመሮጥ ተከተሉት። ከዚህም በኃላ ዘሲማስ ሆይ ከእኔ ጋራ መነጋገር ከፈለግህ ጨርቅን በምድር ላይ ጣልልኝ እከለልበት ዘንድ ብላ በስሙ ጠራችው።

በስሙ በጠራችውም ጊዜ እጅግ አድንቆ ጨርቁን ጣለላት ያን ጊዜም ለብሳ ሰገደችለት እርሱም ሰገደላት እርስበርሳቸውም ሰላምታ ተሰጣጥተው በላዩዋ ይፀልይላት ዘንድ ለመነችው እርሱ ካህን ነውና ካህን ሰለሆነ።

ከዚህም በኃላ ገድሏን ታስረዳው ዘንድ ቅዱስ ዘሲማስ ለመናት ከእርሷ የሆነውን ሁሉ ከመጀመሪያው እስከመጨረሻው ነገረቸው። እርሷም በሚመጣው አመት የክብር ባለቤት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ስጋውንና ደሙን ከእርሱ ጋራ ያመጣላት ዘንድ ለመነችው እርሱም እሺ አላት።

አመትም በሆነ ጊዜ ስጋውንና ደሙን በፅዋ ውስጥ ያዘ ደግሞ በለስ ተምርንና በውኃ የራሰ ምስርን ይዞ ወደርሷ ወደ ዮርዳኖስ በረሀ መጣ ቅድስት ማርያምን በዮርዳኖስ ወንዝ ዳር ስትሄድ አያት ወደርሱም ደርሳ እርስበርሳቸው ሰላምታ ተሰጣጡ በአንድነትም ፀለዩ ከዚህም በኃላ ስጋውንና ደሙን አቀበላት።

በለሱን ተምሩንና ምስሩንም አቀረበላትና ትመገብለት ዘንድ ለመናት ስለ በረከት ከምስሩ በእጇ ጥቂት ወሰደች። ደግሞም በሁለተኛው አመት ወደእርሷ ይመለስ ዘንድ ለመነችው ።ሁለተኛ አመትም በሆነ ጊዜ ወደዚያ ወደ ዮርዳኖስ በረሀ መጣ ያቺ ቅድስት ሴት ሙታ አገኛት በራስጌዋም ድኀዪቱን ግብፃዊት ማርያምን ከተፈጠረችበት አፈር ውስጥ ቅበራት የሚል ፅሁፍ አገኘ።ከፅሁፉ ቃልም የተነሳ አደነቀ።

ያን ጊዜም ከግርጌዋ አንበሳን ሲጠብቃት አየ እርሱ መቃብርዋን በምን እቆፍራለሁ ብሎ ያስብ ነበር በዚያም ጊዜ ያ አንበሳ በጥፍሮቹ ምድሩን ቆፈረ የከበረ ዘሲማስም በላይዋ ፀሎት አድርጎ ቀበራት ።

ወደ ገዳሙም ተመልሶ ለመነኮሳቱ የዚችን የከበረች ግብፃዊት ማርያምን ገድሏን እንዳስረዳችው ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ነገራቸው እጅግም አደነቁ ምስጉን ልኡል እግዚአብሄርንም አመስገኑት። መላው እድሜዋም ሰማንያ አምስት ሆኗታል።

ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ †

በዚች እለት የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በትንሳኤው ሳምንት ለሀዋርያው ቶማስ ተገለጠለት በእጆቹና በእግሮቹ ውስጥ የችንካሮቹን ምልክትም አሳየው የቶማስንም እጅ ይዞ በመለኮታዊ ጉኑ ውስጥ አኖረውና በጦር የተወጋበትን ቦታ አሳየው ቶማስም  ጌታዬና ፈጣሪዬ መነሳትህን አመንኩ አለ።

ጌታችንም ብታየኝ አመንከኝ የሚመሰገንስ ሳያየኝ የሚአምንብኝ ነው ብሎ መለሰለት። በትርጓሜ ወንጌልም እንዲህ ይላል ቶማስ በመድኀኒታችን ጐን ውስጥ እጁን በአስገባ ጊዜ እጁ በመለኮት እሳት ተቃጠለ ፣በመለኮቱም ደግሞ በታመነ ጊዜ እጁ ከመቃጠል ዳነች ።

" አባታችን አዳም "

=>አባታችን አዳም የመጀመሪያው ፍጥረት (በኩረ ፍጥረት) ነው:: አባታችን አዳም:-

*በኩረ ነቢያት
*በኩረ ካኅናት
*በኩረ ነገሥትም ነው::
*በርሱ ስሕተት ዓለም ወደ መከራ ቢገባም ወልድን ከዙፋኑ የሳበው የአዳም ንስሃና ፍቅር ነው::

+አባታችን ለ100 ዓመታት የንስሃ ለቅሶን አልቅሷል:: ስለዚህ አባታችን አዳም ቅዱስ ነው:: ከሌሎቹ ቅዱሳን ቢበልጥ እንጂ አያንስም::

+ለአባታችን አዳም የተናገርነው ሁሉ ለእናታችን ሔዋንም ገንዘቧ ነው:: ዛሬ የሁለቱም የዕረፍታቸው መታሠቢያ ነው::

=>አባታችን ቅዱስ ኖሕም ከላሜሕ የተወለደው በዚሁ ቀን ነው::
=>አምላካችን እግዚአብሔር ለሰማይ ለምድሩ በቅድስናቸው ከከበዱ ወዳጆቹ በረከትን ያድለን::=>ሚያዝያ 6 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱሳን አዳምና ሔዋን (የዕረፍታቸው መታሠቢያ)
2.ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት (ልደቱ)
3.አባታችን ቅዱስ ኖኅ (ልደቱ)
4.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ (የጌታችንን ጐኑን የዳሰሰበት)
5.ቅድስት ማርያም ግብፃዊት (ከኃጢአት ሕይወት ተመልሳ በፍፁም ቅድስናዋ የተመሠከረላት እናት)

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅድስት ደብረ ቁስቁዋም
2.እናታችን ሐይከል
3.ቅዱስ ኤልያስ ነቢይ
4.ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ
5.ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ
6.ቅድስት ሰሎሜ
7.አባ አርከ ሥሉስ
8.አባ ጽጌ ድንግል
9.ቅድስት አርሴማ ድንግል

=>+"+ እንግዲህ ምን እላለሁ? ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ: ስለ ሶምሶንም: ስለ ዮፍታሔም: ስለ ዳዊትና ስለ ሳሙኤልም: ስለ ነቢያትም እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛልና::

እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ:: ጽድቅን አደረጉ:: የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ:: የአንበሶችን አፍ ዘጉ:: የእሳትን ኃይል አጠፉ:: ከሰይፍ ስለት አመለጡ:: ከድካማቸው በረቱ:: በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ:: የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ:: +"+ (ዕብ. 11:32-35

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
2024/09/24 07:16:20
Back to Top
HTML Embed Code: