Telegram Web Link
እንኩዋን ለቅዱሳን "ሕጻናተ ቤተ ልሔም" እና "አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ሕጻናተ ቤተ ልሔም "*+

=>በሮሙ ቄሣር በአውግስጦስ ዘመን ሰው ሁሉ ይቆጠር ዘንድ አዋጅ ወጥቷልና እመ ብርሃን ማርያም ከቅዱሳኑ ዘመዶቿ ዮሴፍና ሰሎሜ ጋር ወደ አባቷ ዳዊት ከተማ ወደ ቤተ ልሔም ሔደች::

+በዚያም ሳሉ የምትወልድበት ጊዜ ቢደርስ በፍጹም ድንግልና እንደ ጸነሰችው ሁሉ በፍጹም ድንግልና ወለደችው:: (ኢሳ. 7:14, ሕዝ. 44:1) ተፈትሖም አላገኛትም:: ልማደ አንስትም አልጐበኛትም:: ምጥም አልነበረባትም::

+በጊዜውም በምሥራቅ የፋርስ: የባቢሎንና የሳባ ነገሥት አስቀድሞ ከበለዓም: በሁዋላም ከዠረደሸት በተረዱት መሠረት ኮከቡን በማየታቸው ታጥቀው ተነሱ::

+ከምሥራቅ አፍሪቃና ከእስያም በተመሳሳይ ኮከቡን በማየታቸው 12 ነገሥታት በየግላቸው 10 10 ሺህ ሠራዊትን እየያዙ ድንግልንና ንጉሥ ልጇን ፍለጋ ወጡ::

+12ቱ ነገሥታት ከነ ሠራዊታቸው ሲሔዱ ስንቃቸው በማለቁ 9 ነገሥታት ተስፋ ቆርጠው ተመለሱ:: 3ቱ ግን በፍጹም ጥብዓት ከ30ሺ ሠራዊት ጋር በኮከብ እየተመሩ ኢየሩሳሌም ደረሱ::

+እነዚህም መሊኩ የኢትዮዽያ (የሳባ ንጉሥ ተወራጅ): በዲዳስፋና መኑሲያ (ማንቱሲማር) ደግሞ የፋርስና የባቢሎን ነገሥታት ናቸው:: ወደ ኢየሩሳሌም ሲደርሱም ሔሮድስና ሠራዊቱ ታወኩ::

+እነርሱ ግን የቤተ ልሔምን ዜና ከጠየቁ በሁዋላ በጐል ድንግል ማርያምን: ክርስቶስን: ዮሴፍና ሰሎሜን አገኙ:: ለ2 ዓመታት እነርሱን ፍለጋ ደክመዋል: ተንከራተዋልና ደስታቸው ወሰን አጣ::

+በእመቤታችንና በልጇ ፊት በደስታ ዘለሉ:: "አንፈርዓጹ ሰብአ ሰገል" እንዲል:: ወርቁን: እጣኑንና ከርቤውንም ገብረው በግንባራቸው በፊቱ ሰገዱ:: 3 ጊዜ እየወጡ እየገቡ ቢመለከቱት በኪነ ጥበቡ አንዴ እንደ ሕጻን: በ2ኛው እንደ ወጣት: በ3ኛው እንደ አረጋዊ ሆኖ ታይቷቸው ፈጽመው አድንቀዋል::

+ወደ ሃገራቸው ሲመለሱም "ወአስነቀቶሙ ሕብስተ ሰገም" እንዲል የገብስ ዳቦ ጋግራ ድንግል ሰጠቻቸው:: እነርሱም ይህንን እየተመገቡ የ2 ዓመቱን መንገድ በ40 ቀን ሲጨርሱት ዳቦው ግን ያ ሁሉ ሺህ ሰው ተመግቦት አላለቀም:: ተአምራትንም ሠርቷል::

+ሰብአ ሰገል ቅዱስ መልአክ እንደ ነገራቸው በሔሮድስ ዘንድ ሳይሆን በሌላ ጐዳና ተጉዘው ሃገራቸውን መግባታቸውን ንጉሡ ሰማ:: እንደ ዘበቱበት ሲያውቅም የሚያደርገው ጠፍቶበት ወደ ቤቱ ገባ::

+በሕሊናው የሚመላለሰውም አንድ ነገር ብቻ ነበር:: የአይሁድ ንጉሥ የተባለውን (እርሱስ የሰማይና የምድር ሁሉ ንጉሥ ነው) እንዴት ሊያጠፋው እንደሚችል ያስብ ነበር:: በዚያች ሰዓትም ሰይጣን በሰው ተመስሎ ወደ እርሱ ቀረበ::

+ሕጻኑን እንዴት ሊገድለው እንደሚችል ነግሮት: በዓለም ታይቶ የማይታወቀውን ጭካኔ አስተማረው:: ርጉም ሔሮድስም ሠራዊቱን ጠርቶ "አዋጅ ንገሩልኝ" አላቸው::

+እነርሱም "በቤተ ልሔምና በአውራጃዋ: በይሁዳም የምትገኙ እናቶች:- አውግስጦስ ቄሣር ሕጻናትን በማርና በወተት አሳድገህ ለሹመት አብቃልኝ: ለእናቶቻቸውም ወርቅና ብር ስጥልኝ ስላለ 2 ዓመትና ከዚያ በታች የሆናቸውን ሕጻናት ሁሉ አምጡ" እያሉ አዋጁን ነገሩ::

+የቤተ ልሔምና የአካባቢዋ እናቶችም ያላቸው አንድም: ሁለትም እየያዙ: የሌላቸው ደግሞ እየተዋሱ ወደ ሔሮድስ ዘንድ ይዘዋቸው መጡ:: ያን ጊዜ አውሬው ሔሮድስ እናቶችን በአንድ ቦታ እንዲታጐሩ አድርጐ ሕጻናቱን በወታደሮቹ አሳፍሶ ወደ ተራራ አወጣቸው::

+በሥፍራውም ተወዳዳሪ በሌለው ጭካኔ 1,200 ወታደሮቹን አሰልፎ ሕጻናቱን አሳረዳቸው:: ሰይፍ የበላቸው የቤተ ልሔም ሕጻናት ቁጥርም 144,000 ሆነ::

+የሕጻናቱ ደም ከተራራው እንደ ጐርፍ ወረደ:: የእናቶች የጡት ወተትም በመሬት ላይ ይፈስ ነበርና ተቀላቀለ:: የቤተ ልሔም እናቶች አንጀታቸው በእጥፉ ተቆረጠ:: ታላቅ ሰቆቃም አካቢውን ሞላው:: ዋይታም ሆነ::

+ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ እንዳለው ነቢዩ ኤርምያስ የተናገረው ትንቢት ተፈጸመ:: "ራሔል ስለ ልጆቿ አለቀሰች:: የሉምና መጽናናት አልቻለችም" (ማቴ. 2:18, ኤር. 31:15)

+ሰይጣን ግን አላማው እንዳልተሳካና ድንግልና አምላክ ልጇ መሸሻቸውን ሲያውቅ ይህንኑ ለሔሮድስ ሹክ አለው:: ስለዚህም ንግሥተ አርያም ድንግል ማርያምና ወልደ አምላክ ልጇ በስደት ለ3 ዓመት ከ6 ወር ተንገላቱ::

+እንደ ገናም ክፉ ሰዎች መጥተው ለሔሮድስ አሉት:- "አንተ የምትሻው በዘካርያስ ቤት አለና ግደለው::"
ሔሮድስም ወታደሮቹን ልኮ: ሕጻኑን ቅዱስ ዮሐንስን ቢያጣው ደጉን ነቢይ: አረጋዊ ዘካርያስን በቤተ መቅደስ መካከል ገድሎታል::

+በጊዜው የሚፈርድ እግዚአብሔርም ስለ ሕጻናቱ ደም ተበቅሎ ሔሮድስን አጠፋው:: ወደ እመቀ እመቃትም አወረደው:: 144 ሺው ንጹሐን ሕጻናት ግን ስልጣነ ሰማይ ተሰጣቸው:: ከእነርሱ በቀር ማንም በማያውቀው ምሥጢርና ዜማ ፈጣሪያቸውን ይሠልሱትና ይቀድሱት ዘንድም አደላቸው:: (ራዕ. 14:1)

+አባ ሕርያቆስ በሐዳፌ ነፍስ ድርሰቱ "ያስምዓነ ቃለ መሰናቁት ዘሕጻናት-የሕጻናትን የመሰንቆ ድምጽ ያሰማን" እንዳለ:: (ቅዳሴ ማርያም)

+እነዚህ 144 ሺህ ንጹሐን ሕጻናት ዛሬ በሰማይ ለምዕመናን ምሕረትን: ለጨካኞች ፍርድን ይለምናሉ:: በፍርድ ቀንም በጌታ ፊት በክብር ቅንዋቶቹን ይዘው ይመጣሉ::

<< ክብራቸው ታላቅ ነውና ለቅዱሳን ሕጻናት ምስጋና ይሁን !! >>

+*" አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ "*+

=>በሃገራችን እጅግ ዝነኛ ከሆኑ ቅዱሳን አንዱ አባ ሊባኖስ ናቸው:: እርሳቸው እንደ ተስዓቱ (ዘጠኙ) ቅዱሳንና አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ሁሉ ከውጪ ሃገር የመጡ ናቸው::

+የነበሩበት ዘመንም 5ኛው መቶ ክ/ዘመን መጨረሻና 6ኛው መቶ ክ/ዘመን ውስጥ ነው:: ጻድቁ አባ ሊባኖስን "አባ መጣዕ" እያሉ መጥራት የተለመደ ነው:: "መጣዕ" ማለት ኤርትራ ውስጥ የሚገኝና ጻድቁ በተጋድሏቸው የቀደሱት ቦታ ነው:: ጥንተ ታሪካቸውስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-

+አባ ሊባኖስ ትውልዳቸው ከሮም ታላላቅ ሰዎች ነው:: አባታቸው አብርሃም: እናታቸው ደግሞ ንግሥት ይባላሉ:: በብሥራተ መልአክ ተጸንሰው ስለ ተወለዱ ስማቸውም በዚያው "ሊባኖስ" ተብሏል::

+"ሊባኖስ" እመ ብርሃን የተወለደችበት ቅዱስ ሥፍራ ሲሆን በጥሬ ትርጉሙ "ደጋ" ማለት ነው:: ምሥጢራዊ ትርጉሙ ግን ለጻድቅነት ያገለግላል:: አባ ሊባኖስ በሃገራቸው ሮም ከወላጆቻቸው ጋር አድገው ለአካለ መጠን ሲደርሱ ከወደ ቁስጥንጥንያ ሸጋ ብላቴና አጭተው አጋቧቸው::

+ወጣቱ አባ ሊባኖስ ግን ማታ "ወደ ጫጉላ አልገባም" ብለው እንቢ አሉ:: ለዚያች ሌሊት ብቻ ከአባታቸው ጋር እንዲያድሩ ተፈቀደላቸው:: መጻሕፍትን የተማሩ ነበሩና በሌሊት ምን እንደሚያደርጉ ሲያወጡ: ሲያወርዱ ቅዱስ መልአክ ከሰማይ ወርዶ 3 ጊዜ "ሊባኖስ" ብሎ ጠራቸው::

+"እነሆኝ ጌታየ!" ቢሉት ከአባታቸው ጐን ነጥሎ እያጫወተ ሳይታወቃቸው ከሮም ግብጽ (ገዳመ ዳውናስ) አደረሳቸው::

+በጊዜው ታላቁ ኮከብ ቅዱስ ዻኩሚስ ነበር:: አባ ሊባኖስን አስተምሮ አመነኮሳቸው: በዓትም ለየላቸው:: በዚያ ለተወሰነ ጊዜ እንደቆዩም ቅዱሱ መልአክ መጥቶ "ለዘለዓለም መጠሪያህ በዚያ ነውና ወደ ኢትዮዽያ ሒድ" አላቸው::
+እየመራም ከግብጽ አክሱም አደረሳቸው:: አባ ሊባኖስም በዚያ በዓት ወቅረው ይጸልዩ ጀመር:: ጥቂት ቆይተውም ለስብከተ ወንጌል ተሰማሩ:: በተለይ በ6ኛው መቶ ክ/ዘመን በስብከት ከአክሱምሸዋ (ግራርያ) ደርሰዋል::

+ተመልሰው ወደ አክሱም ሔደው: ጸበልን አፍልቀው ነበርና ድውያንን ፈወሱ:: ሙትን አስነሱ:: በዚህ የቀኑት የአካባቢው ሰዎች ግን "ምትሐተኛ ነህ" ብለው አባረሯቸው:: ጻድቁም ዶርቃ በምትባል ቦታ ለ3 ዓመት ሲኖሩ በአክሱም ዝናብ አልዘንብ አለ::

+ጥፋታቸው የገባቸው የአክሱም ካህናት ወደ ጻድቁ ሔደው "ይማሩን" ቢሏቸው ዘንቦላቸዋል:: አባ ሊባኖስ ግን ወደ ሽዋ ተመልሰው በደብረ አስቦ ለመኖር ቢሞክሩ አልተሳካም:: ስሙ የአንተ: ማደሪያነቱ ግን የቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ነውና ወደ "መጣዕ" ሒድ አላቸው መልአኩ::

+እርሳቸውም ወደ መጣዕ (ኤርትራ) ወርደው ታላቅ ገዳም አነጹ:: ጸበሎችን አፈለቁ:: ብዙ አርድእትንም አፈሩ:: በዚያም በቅድስናና በገቢረ ተአምራት ኑረው ጥር 3 ቀን በ140 ዓመታቸው ዐርፈዋል:: የላሊበላውን ቤተ አባ ሊባኖስን ጨምሮ በርካታ አብያተ መቃድስ በሃገራችን አሏቸው::

=>የሕጻናቱና የጻድቁ አምላክ እኛን ይማረን:: ከበረከታቸውም ያሣትፈን::

=>ጥር 3 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1."144 ሺ" ቅዱሳን ሕጻናት
2.አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ
3.አባ አሞን መስተጋድል

=>ወርኀዊ በዓላት
1.በዓታ ለእግዝእትነ ማርያም ድንግል
2.ቅዱሳን ኢያቄም ወሐና
3.ቅዱሳን ካህናት (ዘካርያስና ስምዖን)
4.አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ
5.አቡነ ዜና ማርቆስ
6.ቅዱስ ቄርሎስ ዓምደ ሃይማኖት
7.አቡነ መድኃኒነ እግዚእ ጻድቅ

=>+"+ አየሁም: እነሆም በጉ በጽዮን ተራራ ቆሞ ነበር:: ከእርሱም ጋር ስሙና የአባቱ ስም: የመንፈስ ቅዱስም ስም በግምባራቸው የተጻፈላቸው መቶ አርባ አራት ሺህ ነበሩ . . . ደርዳሪዎችም በገና እንደ ሚደረድሩ ያለ ድምጽ ሰማሁ:: በዙፋኑም ፊት: በአራቱም እንስሶችና በሊቃውንቱ ፊት አዲስ ምስጋና አመሰገኑ:: ከምድርም ከተዋጁት ከመቶ አርባ አራት ሺህ በቀር ያን ቅኔ ሊማር ለማንም አልተቻለውም:: ከሴቶች ጋር ያልረከሱ እነዚህ ናቸው:: ድንግሎች ናቸውና:: +"+ (ራዕ. 14:1)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞

++ እንኩዋን ለፍቁረ እግዚእ ዮሐንስ ሐዋርያ: ወልደ ነጐድጉዋድ ዓመታዊ የፍልሠት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ++

++ ቅዱስ ዮሐንስ ፍቁረ እግዚእ ++

=>አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቅዱስ ወንጌሉ እንደነገረን በመንግስተ ሰማያት ታላቁ ሰው ወንጌላዊው ዮሐንስ ነው:: ቅዱሱ ሐዋርያ ከዘብዴዎስና ከማርያም ባውፍልያ ተወልዶ: በገሊላ አካባቢ አድጐ: ገና በወጣትነቱ መድኃኔ ዓለምን ተከትሎታል::

+ቅዱስ ዮሐንስ ከሐዋርያት ቀድሞ ጌታን ከመከተሉ ባሻገር በምንም ምክንያት ከጐኑ አይጠፋም ነበር:: ስለ ንጽሕናውና በጐ የፍቅር ሕሊናው ሕጻን ሳለ በወንድሞቹ ሐዋርያት ዘንድ ሞገሱ ከፍ ያለ ነው:: ጌታችንን እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ በመከተሉ ድንግል እመቤታችንን ተቀብሏል::

+ከእርሷ ጋር ለ15 ዓመታት ቢቀመጥ መዝገበ ምሥጢር ሆነ:: ስንኩዋን ከሰው ልጆች ይቅርና ከልዑላኑ መላዕክትም ማዕረጉ ከፍ አለ:: ሰው ቢበቃ መላእክትን ሊያይ ይቻለዋል:: ቅዱስ ዮሐንስን ግን መላእክት ሊያዩት ይከብዳቸዋል:: ከፍጥረት ወገን ከእመ ብርሃን ቀጥሎ ክቡር እርሱ ነው::

+ቅዱስ ዮሐንስ በታናሽ እስያ ለ7ቱ አብያተ ክርስቲያናት መስበኩ ይታሰባል:: ቅዱሱ ከጌታችን ዕርገት በሁዋላ ለ70 ዓመታት በዚህ ምድር ሲኖር አብዛኛውን ጊዜውን ያሳለፈው በኤፌሶን አካባቢ ነው:: ሕዝቡን ወደ ክርስትና ለማምጣት በአፍም በመጽሐፍም ደክሟል::

+3 መልዕክታት: ራዕዩንና ወንጌልን ጽፎላቸዋል:: ሕይወትን ስለ ሰበከላቸው በፈንታው ብዙ አሰቃይተውታል:: ከእሳት እስከ ስለት: እስከ መጋዝም በስተእርጅና ደርሶበታል:: እርሱ ግን በትእግስቱ ገንዘብ አድርጉዋቸዋል::

+" ቅዱሱ በኤፌሶን "+

=>ይህቺ ኤፌሶን የሚሏት ሃገር መገኛዋ በቀድሞው ታናሽ እስያ (አሁን ቱርክ አካባቢ) ሲሆን ብዙ ሐዋርያት አስተምረውባታል:: ያም ሆኖ የሚፈለገውን ያህል ለውጥ ያመጣች አልነበረችምና ቅዱስ ዮሐንስ ሊሔድ ተነሳ::

+ከደቀ መዛሙርቱ መካከልም ቅዱስ አብሮኮሮስን (ከ72ቱ አርድእት አንዱ ነው) አስከትሎ እየጸለዩ በመርከብ ላይ ተሳፈሩ:: ሐዋርያት አበው መከረኞች ናቸውና ማዕበል ተነሳባቸው:: በጥቂት አፍታም መርከባቸው በማዕበሉ ተበታተነች::

+ቅዱስ አብሮኮሮስ በስባሪ ላይ ተሳፍሮ ወደ አንዲት ደሴት ደረሰ:: ግን ከንጹሑ መምሕሩ ቅዱስ ዮሐንስ ተለይቷልና አለቀሰ:: ፍቁረ እግዚእ ግን ያለ ምግብና ውሃ ማዕበለ ባሕር እያማታው ለ40 ቀናት ቆየ::

+እርሱ በፈጣሪው ፍቅር የተመሰጠ ነበርና አለመመገቡ አልጐዳውም:: በ40ኛው ቀን ግን ደቀ መዝሙሩ ወዳለበት ደሴት ማዕበሉ አደረሰው:: 2ቱ ቅዱሳን ተፈላልገው ተገናኙ:: እጅግም ደስ ብሏቸው ፈጣሪን አመሰገኑ::

+አምላካቸው ወደዚህች ደሴት ያመጣቸው በጥበቡ ነውና ሲዘዋወሩ 2 ነገርን አስተዋሉ:: 1ኛ የደሴቷ ሁሉም ነዋሪ የሚያመልኩት ጣዖትን ነው:: 2ኛ አብዛኞቹ ልዑላን (የቤተ መንግስት ውላጆች) ናቸው:: ሮምና የሚሏት አንዲት ሴት ደግሞ እነዚህን ሁሉ እየመገበች ታስተዳድራለች::

+ቅዱሳኑ በቦታው በቀጥታ ትምሕርተ ወንጌልን ቢናገሩ እንደ ማይቀበሏቸው ስለ ተረዱ ሌላ ፈሊጥን አሰቡ:: እንዳሰቡትም ወደ እመቤት ሮምና ቤት ሒደው በባርነት ተቀጠሩ::

+ለእርሷም "ድሮ የአባትሽ ባሮች የነበርን ሰዎች ነን" ስላሏት 2ቱን ቅዱሳን እሳት አንዳጅና ገንዳ አጣቢ አደረገቻቸው:: ለሰማይ ለምድሩ የከበዱ እነዚህ ቅዱሳን የካዱትን ይመልሱ ዘንድ በባርነት ግፍን ተቀበሉ:: የመከር (የማሳመኛ) ጊዜ ሲደርስም አንዳች አጋጣሚ ተፈጠረ::

+ቅዱሳኑ ዮሐንስና አብሮኮሮስ ወደ መታጠቢያ ቤቱ ሲገቡ ሰይጣን በውስጥ ኖሮ ደንግጧልና እወጣለሁ ብሎ ሲሮጥ የንጉሡን ልጅ ረግጦ ገደለው:: ሮምናና የአካባቢው ሰዎች ከበው ሲላቀሱ ቅዱሳኑ ቀረቡ::

+ሮምና ግን በቁጣ "ልትሣለቁ ነው የመጣችሁ?" በሚል ቅዱስ ዮሐንስን በጥፊ መታችው:: መላእክት እንኩዋ ቀና ብለው ሊያዩት የሚከብዳቸው ሐዋርያ ይህንን ታገሰ:: በጥፊ ወደ መታችው ሴት ቀረብ ብሎም "አትዘኚ! ልጁ ይነሳል" አላትና ጸለየ::

+ወደ ሞተውም ቀረብ ብሎ በጌታችን ስም አስነሳው:: በዚህ ጊዜም ሮምናን ጨምሮ በሥፍራው የነበሩ ሰዎች ለቅዱስ ዮሐንስ ሰገዱ:: እርሱ ግን ሁሉንም አስነስቶ ትምሕርተ ሃይማኖትን: ፍቅረ ክርስቶስን ሰበከላቸው::

+በስመ ሥላሴ አጥምቆ: ካህናትን ሹሞ: ቤተ ክርስቲያንም አንጾላቸው ወጥቷል:: በሁዋላም ለሮምናና ለደሴቷ ሰዎች ክታብ (መልዕክትን) ጽፎላቸዋል:: ይህች መልዕክት ዛሬ 2ኛዋ የዮሐንስ መልዕክት ተብላ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ትታወቃለች::

+ቅዱስ ዮሐንስ ቀጥሎ የተጉዋዘው ወደ ኤፌሶን ነው:: በዚህች ከተማ የምትመለክ አርጤምስ (አርጢሞስ) የሚሏት ጣዖት ነበረች:: አርጤምስ ማለት መልክ የነበራት ትዕቢተኛ ሴት ስትሆን አስማተኛ ባሏ ነው እንድትመለክ ያደረጋት::

+ቅዱስ ዻውሎስ ብዙ ምዕመናን ከእርሷ እንዲርቁ ማድረግ ችሏል:: ጨርሶ ያጠፋት ግን ቅዱስ ዮሐንስ ነው:: በቦታውም ብዙ ግፍ ደርሶበት: በርካታ ተአምራትን አድርጉዋል:: ቤተ ጣዖቱንም በተአምራት አፍርሶታል::

+" የፍቅር ሐዋርያ "+

=>ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ዮሐንስን 'የፍቅር ሐዋርያ' ትለዋለች:: ለ70 ዘመናት በቆየ ስብከቱ ስለ ፍቅር ብዙ አስተምሯል:: ፍቅርንም በተግባር አስተምሯል:: በየደቂቃውም "ደቂቅየ ተፋቀሩ በበይናቲክሙ - ልጆቼ ሆይ! እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ" እያለ ይሰብክ ነበር::

+በተለይ ደግሞ ከፈጣሪው ክርስቶስ ጋር የነበረው ፍቅር ፍጹም የተለየ ነበር:: በዚህ ምክንያትም ጌታ ባረገ ጊዜ እንዲህ ብሎታል:- "ለፍጡር ከሚገለጥ ምሥጢር ከአንተ የምሠውረው የለኝም" ብሎታል::

+ቀጥሎም በንጹሕ አፉ ስሞታል:: ሊቁ:-
"ሰላም ለአፉከ ለዮሐንስ ዘሰዓሞ:
ንጽሐ ኅሊናሁ ወልቡ ለዐይነ ፍትወትከ ሶበ አደሞ" እንዳለው:: (መልክዐ ኢየሱስ)

=>ቅዱስ ዮሐንስ ከእመቤታችንም ጋር ልዩ ፍቅር ነበረው:: እርሷ እንደ ልጇ ስትወደው: እርሱ ደግሞ እንደ እናቱ ልቡ እስኪነድ ድረስ ይወዳት ነበር:: እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ ተከትሎ ያገኛት እመቤቱ ናትና::

+ከዚያ ሁሉ ጸጋና ማዕረግ የመድረሱ ምሥጢርም ድንግል ናት:: ለ15 ዓመታት በጽላሎተ ረድኤቷ (በረዳትነቷ ጥላ) ተደግፎ አብሯት ሲኖር ብዙ ተምሯል:: ከመላእክትም በላይ ከብሯል:: ከንጽሕናዋ በረከትም ተካፍሏል::

+ስለ ድንግል ማርያምም "ነገረ ማርያም" የሚል ድርሰት ሲኖረው "የሰኔ ጐልጐታንም" የጻፈው እርሱ ነው::

+ድንግል ባረፈችበት ቀንም ልክ እንደ ልጇ ክርስቶስ እርሷም ስማው: ታቅፋው ዐርፋለች:: ሊቃውንቱ ለዚህ አይደል በንጹሕ ከንፈሮቿ መሳምን (መባረክን) ሲሹ:-
"በከመ ሰዓምኪ ርዕሰ ዮሐንስ ቀዳሚ:
ስዒሞትየ ማርያም ድግሚ" ያሉት::

+ታላቁ ቅዱስ ሐዋርያ ዕድሜው 90 ዓመት በሆነው ጊዜ በዚህች ዕለት ተሰውሯል:: ከዚያ አስቀድሞም የዓለምን ፍጻሜ ተመልክቷል:: ዛሬ ያለበትን የየሚያውቅ ቸር ፈጣሪው ነው::

=>እናት ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ዮሐንስን ስትጠራው እንዲሕ ነው:-
*ወንጌላዊ
*ሐዋርያ
*ሰማዕት ዘእንበለ ደም
*አቡቀለምሲስ (ምሥጢራትን ያየ)
*ታኦሎጐስ (ነባቤ መለኮት)
*ወልደ ነጐድጉዋድ
*ደቀ መለኮት ወምሥጢር
*ፍቁረ እግዚእ
*ርዕሰ ደናግል (የደናግል አለቃ)
*ቁጹረ ገጽ
*ዘረፈቀ ውስተ ሕጽኑ ለኢየሱስ (ከጌታ ጎን የሚቀመጥ)
*ንስር ሠራሪ*ልዑለ ስብከት
*ምድራዊው መልዐክ
*ዓምደ ብርሐን
*ሐዋርያ ትንቢት
*ቀርነ ቤተ ክርስቲያን
*ኮከበ ከዋክብት

=>በቅዱስ ዮሐንስ ላይ ያደረ የእመቤታችን ድንግል ማርያምና የአንድ ልጇ ፍቅር በእኛም ላይ ይደር::

=>ቅዱስ ዮሐንስን የወደደ ጌታ በፍቅሩ ይጠግነን:: ከእናቱ ፍቅር አድርሶ በሐዋርያው በረከት ያስጊጠን::

=>ጥር 4 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ዮሐንስ ሐዋርያ
(ፍቁረ እግዚእ)
2.አባ ናርዶስ ጻድቅ (ዘደብረ ቢዘን)
3.ቅዱስ ጊዮርጊስ
4.ቅዱስ ማርቴና

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ
2.ቅዱስ እንድርያስ ሐዋርያ
3.ቅድስት ሶፍያ ሰማዕት
4.ቅዱስ ዮሐንስ ዘሐራቅሊ (ሰማዕት)

=>+"+ በጌታ ኢየሱስ መስቀል አጠገብ እናቱ: የእናቱም እህት: የቀለዮዻም ሚስት ማርያም: መግደላዊትም ማርያም ቆመው ነበር:: ጌታ ኢየሱስም እናቱን: ይወደው የነበረውንም ደቀ መዝሙር በአጠገቡ ቆሞ ባየ ጊዜ እናቱን 'አንቺ ሆይ! እነሆ ልጅሽ' አላት:: ከዚህ በሁዋላ ደቀ መዝሙሩን 'እናትህ እነሁዋት' አለው:: ከዚህም ሰዓት ጀምሮ ደቀ መዝሙሩ ወደ ቤቱ ወሰዳት:: +"+ (ዮሐ. 19:25)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
እንኳን ለቅዱስ "ማቴዎስ ነዳይ" እና "ቅዱስ አውስግንዮስ አረጋዊ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ቅዱስ አባ ማቴዎስ "*+

=>ቅዱሱ አባት በቤተ ክርስቲያናችን ስመ ጥር ነው:: በተለይ ትርጉዋሜ ወንጌል ላይ እንደ አብነት ሲጠቀስ የተአምረ ማርያምን ሥርዓት በማዘጋጀቱ የበዓላት መቅድመ ተአምር ላይ ስሙ አለ:: ቅዱሱ ለእመቤታችን በነበረው ፍቅር ድንግል ብዙ ጊዜ ትገለጥለት ነበርና::

+ቅዱስ ማቴዎስ ግብጻዊ አባት ሲሆን የነበረው በመካከለኛው ዘመን ውስጥ (ማለትም በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን) ነው:: በቤቱም መልካም ወላጆችና ያዕቆብ የሚባል ወንድምም ነበረው::

+እንዲያውም አንዴ እናቱ ቅዱሱን ጸንሳ ሳለች የበቁ አበው ሆዷን እጅ ነስተው "ቅዱስ ፍሬ በማኅጸንሽ ውስጥ አለ" እንዳሏት ይነገራል:: ቅዱስ ማቴዎስ በልጅነቱ ወደ እግዚአብሔር ከመገስገስ: ቅዱስ ቃሉን ከመማር በዘለለ ሌላ ሃሳብ አልነበረበትም::

+ወጣት ሲሆንም ወላጆቹ ተከታትለው በማረፋቸው ከወንድሙ ያዕቆብ ጋር ለብቻቸው ቀሩ:: ብዙ የወላጆቹ ሃብት ቢኖርም ቅዱስ ማቴዎስ ስለ መካፈል አላሰበም:: ከለበሳት ጨርቅ በቀር ምንም ሳይይዝ ወደ በርሃ ገሰገሰ::

+ሊመነኩስ ወዶ የደብረ ቅዱስ አቡፋናን አበው ቢጠይቃቸው "አይሆንም" አሉት:: ምክንያቱም በጊዜው ወንድሙን ያውቁት ስለ ነበር እየመጣ እንዳያውካቸው "አስፈቅድ" ማለታቸው ነበር:: ቅዱስ ማቴዎስ ግን ወደ ሌላ ገዳም ሔዶ አለቀሰ::

+አባቶችም ወደ ወንድሙ ሔደው ስለ ማለዱት ፈቀደለት:: ስለዚህም በደብረ አቡፋና መነኮሰ:: ትንሽ ቆይቶ ግን ወንድሙ ያዕቆብ "ለወንድሜ ያልሆነች ዓለም ለእኔም አትረባኝም" ብሎ: በርሃ ገብቶ በቅቶ ዐርፏል::

+ቅዱስ ማቴዎስም በገዳሙ በፍቅርና በመታዘዝ ሲያገለግል ዜና ትጋቱ ተሰማ:: ይህንን ከሰሙት ዻዻሳት አንዱ አባ ዼጥሮስ ያለ ፈቃዱ ከገዳም አስወጥቶ በመንበረ ዽዽስናው ረዳት አደረገው:: እርሱ ግን አንገቱን አቀርቅሮ ተጋድሎውን በጾምና በጸሎት ቀጠለ::

+ነገር ግን ሰይጣን በሴቶች አድሮ ፈተነው:: በጣም አዝኖ ዻዻሱን "አሰናብተኝ" አለው:: "እንቢ" ቢለው የክብር ልብሱን (የዻዻሱን) አውጥቶ በመቀስ ብጥስጥስ አደረገውና በዻዻሱ ፊት አኖረለት::

+ፈጽሞ የተበሳጨው ዻዻሱም በየቀኑ 300 እንዲሰግድ: ወደ ቤት እንዳይጠለልና ሌሎች ቀኖናዎችን ቅጣት ሰጥቶ ወደ በርሃ አሳደደው:: ቅዱስ ማቴዎስም መሻቱ ይህቺው ነበረችና ደስ እያለው ሔደ::

+ለ2 ዓመታትም የቀኑ ሐሩር: የሌሊቱ ቁር እየተፈራረቀበት ቅጣቱን በመፈጸሙ የፍትሐት ደብዳቤ ተላከለት:: አንድ ቀን ግን በገዳሙ የነበረ አንድ የበቃ አባት ክብረ ማቴዎስ ተገልጦለት "የብዙዎች አባት ትሆናለህ" አለው::

+ውዳሴ ከንቱን ፈጽሞ የሚጠላት ቅዱሱ ግን አዘነ:: ሰዎች እያከበሩት ስለተቸገረም ገዳሙን ለቀቀ:: በሔደበት ገዳምም ድንቅ ነገሮቹን እያዩ ሲያከብሩት በአንድ ገዳም የማይቀመጥ ሆነ:: ከአንዱ ወደ ሌላውም ይሔድ ነበረ::

+ቅዱስ ማቴዎስ ከዻዻሱ ዘንድ እያለ ቅስናን ሹሞት ነበርና በገዳማት ይቀድሳል:: ከብቃቱም የተነሳ በቅዳሴ ሰዓት ማሕበረ መላእክትን ያያቸው ነበር:: መድኃኒታችን ክርስቶስም ሕጻን መስሎ ከፊቱ ይቀመጥ ነበር:: ስለዚህ ነገርም ዕንባው እንደ ዥረት ውሃ ይፈስ ነበር:: እየቀደሰም ተመስጦ (ተደሞ) ይመጣበት ነበር::

+ዘወትር የፈጣሪውን ጌትነት እያደነቀ ይመራመር ነበርና አንዴ ቀና ቢል 7ቱ ሰማያት ተከፈቱለት:: እግዚአብሔርንም ከጽርሐ አርያም (7ኛው ሰማይ) ከፍ ብሎ አየው:: ደንግጦ ዝቅ ቢል ደግሞ ከጥልቁ በታች ተመለከተው::

+በዚህ ጊዜ "ይህን ያሳየኸኝ ጌታየ እኔ ማነኝ!" ሲል አለቀሰ:: ሁሌ ዐርብም ሕማማተ ክርስቶስን: በተለይ መድኃኒታችን መቸንከሩን እያሰበ ረጅም ችንካርን በጉልበቱ ውስጥ ይከት ነበር:: ለቀናት ስለማያወጣውም ደሙ ፈሶ አካሉ መልኩ ይቀይር ነበር::

+እንዲህ ካሉ የቅድስናና የተጋድሎ ዓመታት በሁዋላም ሌላ ጥሪ ከፈጣሪው መጣለት:: አበው በጸሎት ላይ ሳለ መጥተው አሠሩት:: "ምን አደረኩዋችሁ አባቶቼ?" ቢላቸው የግብጽ ፓትርያርክ ነህ ከዚህ በሁዋላ" አሉት:: ቢለምናቸውም እንቢ አሉት::

+"እንግዲያውስ" ብሎ: ምላሱን አውጥቶ: በመቀስ ቆርጦ ጣላት:: መናገር የማይችል ሰው ክህነት አይሾምምና:: (እንዲህ ነበር አበው ሥልጣንን የሚሸሿት) ነገር ግን እመቤታችን ከሰማይ ወርዳ "ወዳጄ! ነገሩ የልጄ ፈቃድ ስለ ሆነ እሺ በላቸው" ብላ አዲስ ምላስን ሰጠችው::

+የግብጽ 87ኛ ሊቀ ዻዻሳት ሆኖ ሥርዓተ ሲመቱ ሲፈጸም የወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ራሱ በዚያ ነበረችና ክንፍ አውጥታ: በራ ቅዱስ ማቴዎስን ስትስመው ሁሉም አዩ:: ከሰማይም ማሕበረ መላእክት "አክዮስ-ይገባዋል" ብለው ሲጮሁ ተሰማ::

+ቅዱስ ማቴዎስ ምንም ፓትርያርክ ቢሆንም ለትምሕርት: ለቅዳሴና መሰል ነገሮች ካልሆነ ከበዓቱ አይወጣም ነበር:: ገንዘብ የሌለው: ጥሩ ልብስ የማይለብስ ነበርና "ነዳዩ" እየተባለ እስካሁን ይጠራል::

+በዘመነ ዽዽስናው ብዙ ተግባራትን ሲከውን ዋኖቹ ግን የእመቤታችን ተአምር በሥርዓት እንዲነበብ ማድረጉ ቀድሞ ይጠቀሳል:: በተረፈም የጌታችን ግማደ መስቀሉ ወደ ኢትዮዽያ እንዲመጣም ትልቅ አስተዋጽኦን አድርጉዋል::

+በተሰጠው የትንቢት ሃብትም ወደ ፊት የሚፈጸሙ ነገሮችን ተመልክቷል:: የተናገራቸውም ሁሉ ተፈጽመዋል:: በመጨረሻው ግን ያሰቃየው የነበረው የወቅቱ የግብጽ ከሊፋ (ክፉ ሰው) አስጠርቶ አካሉ እስኪደቅ ድረስ ገረፈው::

+ቅዱስ ማቴዎስም ወደ እመቤታችን ጮኸ:: ድንግልም ወርዳ አጽናናችውና "አሳርፍሃለሁ" አለችው:: ሕዝቡን ተሰናብቶም በዚህች ቀን ዐርፏል::

+*" ቅዱስ አውስግንዮስ አረጋዊ "*+

=>ይህ ቅዱስ ሽማግሌ በሃይማኖቱ ጽናት: በምግባሩ ብዛት ለወጣቶች አብነት መሆን የቻለ አባት ነው:: በብዛት የሚታወቀው በሰማዕትነቱ ቢሆንም በቅዱስ ሰውነቱ በርካታ መልካም ነገሮችን ሠርቷል::

+በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን መነሻ አካባቢ (ዘመነ ሰማዕታት ሊጠናቀቅ ሲል ማለት ነው) የቅዱስ ቆስጠንጢኖስ (የንጉሡ) ወታደር ሁኖ ተቀጠረ:: ንጉሡ ወደ መክስምያኖስ ለጦርነት ሲሔድ በሰማይ ላይ መስቀልና "ኒኮስጣጣን" የሚል ጽሑፍን ተመልክቷል::

+ሁሉም ሰው ለመተርጐም ሲፈራ ወጣቱ አውስግንዮስ ግን በድፍረት ለንጉሡ ክብረ መስቀልንና ትርጉሙን አስረዳ:: በቅዱሱ ንጉሥ ሥርም በወታደርነት ለ20 ዓመታት አገለገለ::

+ከዚያም ሥጋዊ ተግባሩን ትቶ በጾምና በጸሎት: ሰዎችንም በማስታረቅ: በማስተማርም ተወሰነ:: ፈጣሪ ጸጋውን አብዝቶለትም ዕድሜው 110 ዓመት ደረሰ::

+በጊዜውም የነበረው ከሃዲው ዑልያኖስ "ሰዎችን አስታርቀሃልና ክርስቶስን አምልከሃል" በሚል በዚህች ቀን አንገቱን አሰይፎታል:: ዑልያኖስን ደግሞ ቅዱስ መርቆሬዎስ ተበቅሎታል::

=>አምላከ ቅዱሳን ስለ አባቶቻችን ሲል ይማረን:: ከበረከታቸውም ይክፈለን::

=>ጥር 5 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ አባ ማቴዎስ
2.ቅዱስ አውስግንዮስ አረጋዊ (ሰማዕት)
3.ቅድስት እስክንድርያ
4.ቅድስት አውስያ ሰማዕት

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ዼጥሮስ ሊቀ ሐዋርያት
2.ቅዱስ ዻውሎስ ብርሃነ ዓለም
3.አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ
4.ቅዱስ ዮሐኒ ኢትዮዽያዊ
5.ቅዱስ አሞኒ ዘናሒሶ
6.ቅድስት አውጋንያ (ሰማዕትና ጻድቅ)
=>+"+ አባቶች ሆይ! ከመጀመሪያ የነበረውን አውቃቹሃልና እጽፍላቹሃለሁ:: ጐበዞች ሆይ! ክፉውን አሸንፋቹሃልና እጽፍላቹሃለሁ:: ልጆች ሆይ! አብን አውቃቹሃልና እጽፍላቹሃለሁ:: አባቶች ሆይ! ከመጀመሪያ የነበረውን አውቃቹሃልና እጽፍላቹሃለሁ:: ጐበዞች ሆይ! ብርቱ ስለ ሆናችሁ: የእግዚአብሔርም ቃል በእናንተ ስለሚኖር: ክፉውንም ስላሸነፋችሁ እጽፍላቹሃለሁ:: +"+ (1ዮሐ. 2:13)

   <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
እንኩዋን ለአጋእዝተ ዓለም "ሥላሴ" እና "ቅዱስ ሶል ዼጥሮስ" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ሥሉስ ቅዱስ "*+

=>ምሥጢራት በእምነት ለማይኖር: በትሕትናም ለማይቀርብ የሚገለጡ አይደሉም::

+እግዚአብሔር አንድም ነው: ሦስትም ነው:: ጊዜ ሣይሠፈር ዘመንም ሳይቆጠር እግዚአብሔር በስም: በአካል: በግብር ሦስትነቱ: በባሕርይ: በሕልውና: በመለኮትና በሥልጣን አንድነቱ የጸና አምላክ ነው::

+ከዓለም መፈጠር በፊት ስለ ነበረው ነገር የሚያውቅ ራሱ ሥላሴ ብቻ ነው:: ዓለምን ከፈጠረ በሁዋላም ምሥጢረ ሥላሴ (መለኮት) ብለን የምንማረው ትምሕርት እንድንና እንጠቀም ዘንድ እርሱ የገለጠልንን ያህል ብቻ ነው::

+ይኼውም በየጊዜው እርሱ ለወደዳቸውና ደስ ላሰኙት ቅዱሳኑ የገለጠው ምሥጢር ነው:: ከዚህ አልፈን በሥጋዊ አዕምሯችን ጌታን "እንመርምርሕ" ብንለው ግን ፍጻሜአችን ሞት: ማደሪያችንም ገሃነመ እሳት መሆኑ አይቀርም::

+እግዚአብሔር በአንድነቱና ሦስትነቱ ሳለ ይህንን ዓለም ፈጠረ:: እግዚአብሔር ዓለምን ለምን ፈጠረ ቢሉ:- ስሙን ቀድሰን ክብሩን እንድንወርስ ነው:: ከዚህ የተረፈውን ምክንያት ግን ራሱ ያውቃል::

=>በአንድነቱ ምንታዌ (ሁለትነት): በሦስትነቱ ርባዔ (አራትነት) የሌለበት የዘለዓለም አምላክ: የፍጥረታት ሁሉ ፈጣሪ እግዚአብሔር ነው:: አብ: ወልድ: መንፈስ ቅዱስ በስም: በአካል: በግብር ሦስትነት በባሕርይ: በሕልውናና በፈቃድ አንድነት የጸኑ ናቸው:: በዚህ ጊዜ ተገኙ: በዚህ ጊዜ ያልፋሉ አይባሉም:: መጀመሪያም መጨረሻም እነርሱ ናቸውና::

+ርሕሩሐን ናቸውና በእናት ሥርዓት "ቅድስት ሥላሴ" እንላቸዋለን:: የሚጠላቸው (የማያምንባቸውን) አይጠሉም:: የሚወዳቸውን ግን እጽፍ ድርብ ይወዱታል:: በቤቱም መጥተው ያድራሉ::

+ከፍጥረታት ወገን ከእመቤታችን ቀጥሎ የአብርሃምን ያህል በሥላሴ ዘንድ የተወደደ ፍጡር የለም:: አባታችን ቅዱስ አብርሃም የደግነት ሁሉ አባት ነውና በኬብሮን : በመምሬ ዛፍ ሥር ሥላሴን ተቀብሎ አስተናግዷል::

+አባታችን አብርሃም በ99 ዓመቱ: እናታችን ሣራ በ89 ዓመቷ ሥላሴን በድንኩዋናቸው አስተናገዱ:: አብርሃም እግራቸውን አጠበ:: (ወይ መታደል!) በጀርባውም አዘላቸው:: (ድንቅ አባት!) ምሳቸውንም አቀረበላቸው:: እንደሚበሉ ሆኑለት:: በዚያው ዕለትም የይስሐቅን መወለድ አበሠሩት::

+ሥላሴን ያስተናገደች ድንኩዋን (ሐይመት) የድንግል እመቤታችን ማርያም ምሳሌ ናት:: በድንግል ላይ አብ ለአጽንኦ: መንፈስ ቅዱስ ለአንጽሖ: ወልድ በተለየ አካሉ ለሥጋዌ በእርሷ ላይ አርፈዋል / አድረዋልና::

=>በዓለ ሥላሴ በዚህ ቀን የሚከበረው ስለ 2 ምክንያቶች ነው:: ቀዳሚው ሕንጻ ሰናዖርን ማፍረሳቸው ሲሆን 2ኛው ደግሞ ቅዳሴ ቤታቸው ነው::

+*" ሕንጻ ሰናዖር "*+

=>ሰናዖር ከሺዎች ዓመታት በፊት በአሁኗ ኢራቅ አካባቢ እንደ ነበረ የሚነገርለት ግዛት ሲሆን ስሙ ለሃገሪቱም: ለንጉሡም በተመሳሳይ ያገለግል ነበር:: ከናምሩድ ክፋት በሁዋላ ሰናዖርና ወገኖቹ ከሰይጣን ተወዳጁ::

+ከጥፋት ውሃ (ከኖኅ ዕረፍት) በሁዋላ በሥፍራው በአንድነት ይኖሩ ነበርና እርስ በርሳቸው "ኑ ሳንበተን ስማችን የሚጠራበትን ሕንጻ እንሥራ:: በዚያውም አባቶቻችን በውሃ ያጠፋ እግዚአብሔርን እንውጋው" ተባባሉ::

+ቀጥለውም ሰማይ ጠቀስ ፎቅን ገነቡ:: ከሕንጻው መርዘም የተነሳ በጸሐይ አብስለው በልተዋል ይባላል:: ቀጥለውም ጦር እያነሱ ፈጣሪን ሊወጉ ወርውረዋል::

+መቼም የእነዚህን ሰዎች ክፋትና ቂልነት ስንሰማ ይገርመን ይሆናል:: ግንኮ ዛሬ ሰለጠንኩ በሚለው ዓለም እየተሠራ ያለው ከዚህ የከፋ ነው:: ቸርነቱ ቢጠብቀን እንጂ እንደ ክፋታችንስ ጠፊ ነበርን::

+ርሕሩሐን ሥላሴ ግን የሰናዖር ሰዎች የሠሩትን አይተው ማጥፋት ሲችሉ አላደረጉትም:: የባሪያቸውን የኖኅን ቃል ኪዳን አስበዋልና:: ይልቁኑ "ንዑ ንረድ ወንክአው ነገሮሙ ለከለዳውያን-ቁዋንቁዋቸው እንደባልቀው" አሉ እንጂ::

+ከለዳውያን ልሳናቸው ተደበላልቆ 71 ቁዋንቁዎች ተፈጠሩ:: እነርሱም ስምምነት አጥተው ተበተኑ:: ሥላሴም ያን ሕንጻ በነፋስ ትቢያ እንዲሆን በተኑት:: ስለዚህም እስከ ዛሬ ሥፍራው "ባቢሎን (ዝሩት)" ሲባል ይኖራል::

+" ቅዳሴ ቤት "+

=>ልክ የዛሬ 324 ዓመት: አድያም ሰገድ ኢያሱ በኢትዮዽያ በነገሡ በ10ኛው ዓመት: (በ1684 ዓ/ም) በጐንደር ከተማ ንግሥተ አድባራት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ተሰርታ ተጠናቃለች::

+ጥር 7 ቀንም ሊቁ ክፍለ ዮሐንስን ጨምሮ በርካታ ምዕመናን: ሠራዊት: መሣፍንትና ሊቃውንት ባሉበት ቅዳሴ ቤታቸው ተከብሯል:: በዕለቱም ታላቅ ሐሴት ተደርጉዋል:: ኢያሱ አድያም ሰገድ ኃያል: ደግ: ጥበበኛ: አስተዋይ: መናኝ ንጉሥ ነውና::

+ቤተ ሥላሴን አስጊጿታልና ከዚህ ቀን ጀምሮ ጥር ሥላሴ በድምቀት የሚከበር ሆኗል:: ነገር ግን በተሠራች በ16 ዓመቷ ደጉ ኢያሱ ከተገደለ በሁዋላ ቤተ ክርስቲያኑ በአደጋ ፈርሷል:: ዛሬ የምናየው በ1708 ዓ/ም በልጁ በአፄ ዳዊት ሣልሳዊ የታነጸውን ነው::

+*" ቅዱስ ሶል ዼጥሮስ "*+

=>የሊብያው አርዮስ ጌትነት ገንዘቡ የሆነ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ክዶ ሊያስክድ ሲሯሯጥ በፈቃደ እግዚአብሔር: በጻድቁ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ጥሪ: 2348 ምሑራን ከመላው ዓለም ተሰበሰቡ::

+ከተሰበሰበው ብዙ ሰው መካከል የአበውን ደቀ መዛሙርት ሳንቆጥር ሃይማኖታቸው የቀና: ምግባራቸው የጸና 318ቱ አበው ሊቃውንት ተገኙ::

+እነዚህ አባቶች "ሊቃውንት" ሲባሉ እንዲሁ በእውቀት ብቻ የበሰሉ እንዳይመስሉን:: 318ቱ አበው እኩሎቹ በዘመነ ሰማዕታት እጅና እግራቸውን የተቆረጡና ለሃይማኖታቸው ብዙ ዋጋ የከፈሉ ናቸው::

+እኩሎቹ ደግሞ በገዳማዊ ሕይወት ያጌጡ: ፍቅረ ክርስቶስ በውስጣቸው የሚነድ: የመንፈስ ቅዱስ ቤት ናቸው:: እስኪ እናውቃቸው ዘንድ የጥቂቶችን ማንነት በስምና መገለጫ እንመልከት::

1.ቅዱስ ቶማስ ዘመርዓስ (በዘመነ ሰማዕታት ለ22 ዓመት ሲቆራርጡት ኖረው በጉባኤው ላይ የተገኘው ያለ እጅ: እግር: ጀሮ: ከንፈር: ቅንድብ ነው)

2.ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ (ስለ ቀናች እምነት ለ50 ዓመታት የተጋደለና ለ15 ዓመታት በስደት የኖረ ነው)

3.ቅዱስ እለእስክንድሮስ ሊቅ (ከሰማይ ብርሃን ይወርድለት የነበረ አባት ነው)

4.ታላቁ ቅዱስ ባስልዮስ (በጸሎቱ አጋንንትን ያንቀጠቀጠ: ነፍሳትን ከሲዖል የቀማና ከከዊነ እሳት የደረሰ አባት ነው)

5.ቅዱስ ጐርጐርዮስ ዘአርማንያ (ስለ ቀናች እምነት መጸዳጃ ጉድጉዋድ ውስጥ ለ15 ዓመታት ተጥሎ የኖረ ሰማዕት ነው)

6.ቅዱስ ኒቆላዎስ ዘሜራ (ከሕጻንነቱ የተቀደሰ: በበርሃ የተጋደለ: በዘመነ ሰማዕታት ብዙ መከራን የተቀበለ አባት ነው)

7.ቅዱስ ያዕቆብ ዘንጽቢን (በደግነቱ ሙታንን ያስነሳ: ወንዝን በጸሎቱ ያቆመ: በንጽሕና የተጋደለ አባት ነው)

8.ቅዱስ ሶል ዼጥሮስ (ቅዱሱን ንጉሥ ያጠመቀ: ቁስጥንጥንያን በወንጌል ያበራ ሊቅ ነው)

9.ቅዱስ ኤዎስጣቴዎስ (ስለ ቀናች እምነቱ ብዙ ግፍ የደረሰበትና በስደት ያረፈ አባት ነው)
+እንደ አርዮስ ሐሳብ መድኃኒታችን ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ አይደለም (ሎቱ ስብሐት!!) ማለት ክርስትናን ከሥሩ ፈንቅሎ መጣል ነው::
+ስለ ክርስቶስ እግዚአብሔርነት ብሉይም ሐዲስም እየመሰከሩ:-
(ኢሳ. 9:6, መዝ. 46:5, 77:65, ዘካ. 14:4, ዮሐ. 1:1, 10:30, ራዕይ. 1:8, ሮሜ. 9:5 . . .)
አርዮስና የዛሬ መሰሎቹአንዲት ጥቅስ ይዘው ክርስትናን ከመሠረቱ ለመናድ መሞከራቸው በእርግጥም ከሰይጣን መላካቸውን ያሳያል::

+በወቅቱም በመወገዙ አርዮስ ወደ ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ ሔዶ ከሰሰ:: ቅዱሱ ንጉሥም የጉዳዩን ክብደት ተመልክቶ የዓለም ሊቃውንት ይሰበሰቡ ዘንድ አዘዘ::

+በ325 ዓ/ም (በኛው በ318 ዓ/ም) ለ40 ቀናት የሚቆይ ሱባኤን ያዙ:: ሱባኤውን ሲጨርሱም በ4ቱ ፓትርያርኮች (እለእስክንድሮስ: ሶል ዼጥሮስ: ዮናክንዲኖስና ኤዎስጣቴዎስ) መሪነት: በእለእስክንድሮስ ሊቀ መንበርነት: በአትናቴዎስ ጸሐፊነት ጉባኤው ተጀመረ::

+በጉባኤው ሙሉ ስልጣን በሰማይ ከፈጣሪ: በምድር ከንጉሡ የተሰጣቸው አበው አርዮስን ተከራክረው ከነ ጀሌዎቹ ምላሽ አሳጡት:: ክርስቶስ አምላክ ወልደ አምላክ: ሥግው ቃል: ራሱም እግዚአብሔር መሆኑን አስረዱት::

+በጉባኤው መጨረሻም አልመለስም በማለቱ አርዮስን አወገዙ: ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እንደሚገባ አደራጁ:: አባቶችም ሥራቸውን ከጨረሱ በሁዋላ ቅዱስ ቆስጠንጢኖስን ባርከው ወደየ ሃገረ ስብከታቸው ተመልሰዋል::

+ቅዱስ ሶል ዼጥሮስም ከጉባዔው ከተመለሰ በሁዋላ በጐ ጐዳናውን አቅንቶ ቀጥሏል:: ብዙ ድርሳናትን ደርሶ: በድካም ሰብኮ ኢአማንያንን መልሷል:: ፈላስፎችንም ድል ነስቶ አሳምኗል:: መናፍቃን ደግሞ ፈጽመው ይፈሩት ነበር:: ሊቀ ዽዽስናን በተሾመ በ11 ዓመቱም በዚህች ቀን ዐርፏል::

=>የሥላሴ ቸርነት ከሁላችን ጋር ይሁንና ጥር 7 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.በዓለ ሥሉስ ቅዱስ
2.ቅዱስ ሶል ዼጥሮስ
3.ቅዱስ ኤፍሬም
4.ቅዱስ ሰሎሞን

=>ወርሐዊ በዓላት
1.አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ
2.አባ ሲኖዳ (የባሕታውያን አለቃ)
3.አባ ዳንኤል ዘገዳመ ሲሐት
4.አባ ባውላ ገዳማዊ
5.ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ
6.ቅዱስ አግናጥዮስ (ለአንበሳ የተሰጠ)

=>+"+ የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ: የእግዚአብሔርም ፍቅር: የመንፈስ ቅዱስም ሕብረት ከሁላችሁ ጋር ይሁን:: አሜን:: +"+ (ቆሮ. 13:14)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ አምላክ አሜን:: †††

=>+"+ እንኩዋን ለቅዱሳን አበው "አባ መቃርስ" እና "ቅዱስ ሚክያስ ነቢይ" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ +"+

+*" ታላቁ ቅዱስ መቃርስ "*+

=>ታላቁ ቅዱስ መቃርስ (ቅዱስ መቃሬ) "ጽድቅ እንደ መቃርስ" የተባለለት የመነኮሳት ሁሉ አለቃ: ከ80 ዓመታት በላይ በበርሃ የኖረ: በግብፅ ትልቁን ገዳም (አስቄጥስን) የመሠረተ: ከ50,000 በላይ መነኮሳትን ይመራና ይመግብ የነበረ ፍፁም ጻድቅ ነው::

+በ4ኛው መቶ ክ/ዘ አርዮሳውያን ደጉን ታላቅ አባት በሰንሰለት አስረው ከግብፅ ወደ እስያ በርሃ ከጉዋደኛው ቅዱስ መቃርዮስ እስክንድርያዊ ጋር አሰድደውታል:: በዚያ ለ2 ዓመታት ስቃይን ከተቀበሉ በሁዋላ በአረማውያን ፊት ድንቅ ተአምር አድርገው አረማውያንን ከነ ንጉሳቸው አጥምቀዋል::

+በተሰደዱባት ሃገርም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ (ስም አጠራሩ ይክበርና) እመቤታችንን: ቅዱሳን ሐዋርያትን: አዕላፍ መላእክትን: በተለይ ደግሞ ቅዱሳኑን ዳዊትን: ዮሐንስ መጥምቁንና ወንጌላዊውን: ማርቆስን: ዼጥሮስን: ዻውሎስን አስከትሎ ወርዶ ተገልጦላቸዋል:: በቅዱስ አንደበቱም የምሕረት ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል::

+ታላቁ ቅዱስ መቃርስና ባልንጀራው መቃርዮስ ከ2 ዓመታት ስደትና መከራ በሁዋላ ስደት በወጡባት ዕለት መልዐኩ ኪሩብ በክንፉ ተሽክሞ ወደ ግብፅ መልሷቸዋል:: በወቅቱም ጻድቁን ለመቀበል ከ50,000 በላይ የሚሆኑ ልጆቻቸው መነኮሳት በዝማሬ ወጥተዋል::

=>ቅዱስ መቃርስ ካረፈ በሁዋላ ከክቡር ሥጋው ብዙ ተአምራት ይታዩ ነበርና የሃገሩ (የሳስዊር) ሰዎች ሊወስዱት ፈለጉ:: ሳስዊር ማለት ቅዱሱ ተወልዶ ያደገባት ወላጆቹ (አብርሃምና ሣራ ይባላሉ) የኖሩባት ቦታ ናት:: የምትገኘውም ግብጽ ውስጥ ነው::

+በምድረ ግብጽ: በተለይም በገዳመ አስቄጥስ የአባ መቃርስን ያህል ክቡርና ተወዳጅ የለምና የሃገሩ ሰዎች የነበራቸው አማራጭ መስረቅ ነበር:: መሥረቅ ኃጢአት ቢሆንም እነሱ ግን ስለ ፍቅር: አንድም ለበረከት አደረጉት::

+ወደ ሳስዊርም ወስደው: ቤተ ክርስቲያን በቅዱሱ ስም አንጸው በክብር አኖሩት:: በዚያም ለመቶዎች ዓመታት ተቀመጠ:: በ7ኛው መቶ ክ/ዘመን ግን ተንባላት (እስላሞች) መጥተው ቤተ ክርስቲያኑን አጠቁ:: በዚህ ጊዜም ሕዝቡ የጻድቁን አጽም ይዘው ሸሹ:: በሌላ ቦታም እንደ ገና በስሙ ቤተ ክርስቲያን አንጸው በዚያ አኖሩት::

+በእነዚህ ሁሉ ዓመታት የመንፈሳዊ አባታቸውን ሥጋ ያጡት የገዳመ አስቄጥስ ቅዱሳን ያዝኑ ይጸልዩ ነበርና ልመናቸውን ፈጣሪ ሰማ:: አባ ሚካኤል ሊቀ ዻዻሳት በነበረበት ዘመን: ከገዳሙ ለሌላ ተግባር ወደ ሳስዊር የተላኩ አበው ከታላቁ አባት ቤተ ክርስቲያን ሲደርሱ ሰውነታቸው ታወከ::

+ይዘው ለመውሰድ ሙከራ ቢያደርጉ ሊሳካላቸው አልቻለም:: ምክንያቱም የቤተ ክርስቲያኑ ጠባቂ ደወል ደውሎ ሕዝቡን ሁሉ ጠርቶ ነበርና:: ሕዝቡና ሃገረ ገዢው የሆነውን ሲሰሙ "የቅዱሱን ሥጋ ብትነኩ እንገላቹሃለን" ብለው ሰይፍ: ዱላ: ጐመድና ጦር ይዘው መጡባቸው::

+መነኮሳቱ ግን ባዷቸውን ሊመለሱ አልፈቀዱምና ሌሊቱን ሲያለቅሱና ሲጸልዩ አደሩ:: መንፈቀ ሌሊት በሆነ ጊዜም ታላቁ መቃርስ በግርማ ወርዶ መኮንኑን "ለምን ወደ ልጆቼ እንዳልሔድ ትከለክለኛለህ?" ሲል በራዕይ ተቆጣው:: በዚህ ምክንያትም መነኮሳቱ የቅዱሱን ሥጋ ተቀበሉ::

+ሕዝቡም በዝማሬና በማሕኅሌት: ከብዙ እንባ ጋር ሸኟቸው:: ታላቁ መቃሬ ወደ ገዳሙ ሲደርስም ታላቅ ደስታ ተደረገ:: ቅዱሳን ልጆቹ ከመንፈሳዊ አባታቸው ተባርከው በክብር አኑረውታል::

=>ይህቺ ዕለት ቅዳሴ ቤቱ ስትሆን የተቀደሰችውም በ7ኛው መቶ ክ/ዘ በአባ ብንያሚን እጀ ነው::

+*" ቅዱስ ሚክያስ ነቢይ "*+

=>ነቢይ ማለት በቁሙ ኃላፍያትን (አልፎ የተሠወረውን ምሥጢር): መጻዕያትን (ገና ለወደ ፊት የሚሆነውን) የሚያውቅ ሰው ማለት ነው:: ሃብተ ትንቢት የእግዚአብሔር የባሕርይ ገንዘቡ ሲሆን እርሱ ለወደደው ደግሞ በጸጋ ይሰጠዋል:: እነዚህም ከጌታ ሃብተ ትንቢት የተሰጣቸው አባቶችና እናቶች "ቅዱሳን ነቢያት" በመባል ይታወቃሉ::

+ዘመነ ነቢያት ተብሎ የሚታወቀው ብሉይ ኪዳን ቢሆንም እስከ ምጽዓት ድረስ ጸጋውን እግዚአብሔር ለፈቀደላቸው አይነሳቸውም:: በሐዋርያት መካከልም ቅዱስ አጋቦስን የመሰሉ ነቢያት ነበሩ:: (ሐዋ. 11:27)

+ቅዱሳን ነቢያት ከእግዚአብሔር እየተላኩ ሰውን ከፈጣሪው እንዲታረቅ ይመክራሉ: ይገስጻሉ:: ከበጐ ሃይማኖታቸውና ንጽሕናቸው የተነሳም እግዚአብሔርን በተለያየ አርአያና አምሳል አይተውታል::
"እስመ በአንጽሖ መንፈስ ርዕይዎ ነቢያት ለእግዚአብሔር:: ወተናጸሩ ገጸ በገጽ::" እንዳለ አባ ሕርያቆስ:: (ቅዳሴ ማርያም)

+የብዙ ነቢያት ፍጻሜአቸው መከራን መቀበል ነው:: እውነትን ስለ ተናገሩ: አንዳንዶቹም በእሳት: አንዳንዶቹም በሰይፍ: አንዳንዶቹም በመጋዝ ተፈትነዋል:: ሌሎቹ ለአናብስት ሲጣሉ ቀሪዎቹ ደግሞ በድንጋይ ተወግረዋል::

+ስለዚህም መከራቸው ለቤተ ክርስቲያን መሠረት ተብለዋል:: ጌታም ለደቀ መዛሙርቱ "ሌሎች ደከሙ: እናንተ በድካማቸው ገባችሁ" ብሎ የነቢያቱን መከራ ተናግሯል:: (ዮሐ. 4:36)

+ነቢያት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስና እና ድንግል እናቱን ለማየት ብዙ ጥረዋል: ሽተዋልም:: "ብዙ ነቢያትና ጻድቃን እናንተ የምታዩትን ሊያዩ ሹ" እንዳለ ጌታ በወንጌል:: (ማቴ. 13:16, 1ዼጥ. 1:10) ዛሬ ግን በሰማያት ጸጋ በዝቶላቸው: ክብር ተሰጥቷቸው ሐሴትን ያደርጋሉ::

+ቅዱሳን ነቢያት በዋነኝነት 15ቱ አበው ነቢያት: 4ቱ ዐበይት ነቢያት: 12ቱ ደቂቀ ነቢያትና ካልአን ነቢያት ተብለው በ4 ይከፈላሉ::

=>"15ቱ አበው ነቢያት" ማለት:-
*ቅዱስ አዳም አባታችን
*ሴት
*ሔኖስ
*ቃይናን
*መላልኤል
*ያሬድ

*ኄኖክ
*ማቱሳላ
*ላሜሕ
*ኖኅ
*አብርሃም
*ይስሐቅ
*ያዕቆብ
*ሙሴና
*ሳሙኤል ናቸው::

=>"4ቱ ዐበይት ነቢያት"
*ቅዱስ ኢሳይያስ ልዑለ ቃል
*ቅዱስ ኤርምያስ
*ቅዱስ ሕዝቅኤልና
*ቅዱስ ዳንኤል ናቸው::

=>"12ቱ ደቂቀ ነቢያት"
*ቅዱስ ሆሴዕ
*አሞጽ
*ሚክያስ
*ዮናስ
*ናሆም
*አብድዩ
*ሶፎንያስ
*ሐጌ
*ኢዩኤል
*ዕንባቆም
*ዘካርያስና
*ሚልክያስ ናቸው::

=>"ካልአን ነቢያት" ደግሞ:-
*እነ ኢያሱ
*ሶምሶን
*ዮፍታሔ
*ጌዴዎን
*ዳዊት
*ሰሎሞን
*ኤልያስና
*ኤልሳዕ ሌሎችም ናቸው::

=>ነቢያት በከተማም ይከፈላሉ::
*የይሁዳ (ኢየሩሳሌም):
*የሰማርያ (እሥራኤል)ና

*የባቢሎን (በምርኮ ጊዜ) ተብለው ይጠራሉ:: በዘመን አከፋፈል ደግሞ:-
*ከአዳም እስከ ዮሴፍ (የዘመነ አበው ነቢያት):
*ከሊቀ ነቢያት ሙሴ እስከ ነቢዩ ሳሙኤል (የዘመነ መሳፍንት ነቢያት)

*ከቅዱስ ዳዊት እስከ ዘሩባቤል ያሉት (የዘመነ ነገሥት ነቢያት):
*ከዘሩባቤል ዕረፍት እስከ መጥምቁ ዮሐንስ ያሉት ደግሞ (የዘመነ ካህናት ነቢያት) ይባላሉ::
+ስለ ቅዱሳን ነቢያት በጥቂቱ ይህንን ካልን ወደ ዕለቱ በዓል እንመለስ::
2024/10/01 11:35:27
Back to Top
HTML Embed Code: