Telegram Web Link
Forwarded from ዝክረ ቅዱሳን zikre kidusan (ɴᴀᴛɴᴀᴇʟ)
"የኛ መጽሀፍ እናንተ ናችሁ ፦በመጋቤ ሐዲስ ወቡሉይ ቆሞስ አባ ገብረ ኪዳን ፦የሰማእትነት ዋጋ የቅድሰት አርሴማ" on YouTube
https://youtu.be/dEMeoNrS-Ng
Forwarded from ዝክረ ቅዱሳን zikre kidusan (ɴᴀᴛɴᴀᴇʟ)
††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን። †††

††† ጥቅምት 3 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት †††

+" ቅዱስ ጊዮርጊስ ሐዲስ "+

††† ሰማዕቱ የተወለደው በምድረ ግብጽ አሕዛብ (ተንባላት) በሰለጠኑበት የመጀመሪያው ዘመን ነበር:: በተለይ ተንባላቱ ግብፅና ሶርያን ከያዙ በኋላ ባልተጠበቀ ፍጥነት በኃይልም በሰውም ተደራጅተው ነበር:: ቅዱስ ጊዮርጊስ (ልብ በሉልኝ ሊቀ ሰማዕታት አይደለም) የተወለደው በዚህ አስቸጋሪ ጊዜ ነበር::

+እናቱ የተመሠከረላት ክርስቲያን ብትሆንም እንዳለመታደል አባቱ ተንባላታዊ (አሕዛብ) ነበር:: ስሙንም መዛሕዝም ይሉታል:: ሕጻኑ እንደተወለደ ያወጡለት ስም አሕዛባዊ ከመሆኑ ባለፈ በሰዓቱ መጠመቅ አልቻለም:: የወቅቱ ሕግ ከወላጆቹ አንዱ አሕዛባዊ ከሆነና አጠምቃለሁ ቢባል የሚከተለው ሰይፍ ነበር:: በዚሕ ምክንያት ሳይጠመቅ 7 ዓመት ሞላው::

+እናቱ ግን ሕጻን ቢሆንም ፍቅረ ክርስትናን ታስተምረው ነበር:: ባይጠመቅም ጸበሉን: እመነቱን ትቀባው ነበር:: ደብቃ ቅዳሴ ታሰማውም ነበር:: አንድ ቀን ግን ሕጻናት ሲቆርቡ አይቶ ካልቆረብኩ ብሎ አለቀሰ:: ምን ታድርገው? ወደ ውጪ አውጥታ ከአውሎግያ (የሰንበት በረከት) አበላችው:: "ጌታየ! ልጄን እርዳው" አለች::

+ልክ በአፉ ሲቀምሳት መዓዛ መንፈስ ቅዱስ አደረበትና ፍጹም ተደሰተ:: ትንሽ ከፍ ሲል ለምን እንደማይጠመቅና እንደማይቆርብ እናቱን ጠየቃት:: "ልጄ ሆይ! ይገድሉሃል" አለችው::
ከዚህች ቀን ጀምሮ የሚጠመቅበትን ዘዴ ይፈልግ ጀመር::

+አስቀድሞ ትምሕርተ ክርስትናን ተማረ:: ለአካለ መጠን ሲደርስ አፈላልጐ ጠንካራ ክርስቲያን የሆነች ሴት አገባ:: ጥቂት ጊዜ ከቆየ በኋላ ሚስቱን ስለ መጠመቅ አማከራት:: "ሌላ ሃገር ሒደህ ተጠመቅ" አለችው:: ከግብፅ ተነስቶ ሶርያ ገባ::
አባቶችን አፈላልጎ ተጠመቀ:: ቀጥሎም መንገዱን ወደ ልዳ አደረገ::

+ወደ ደብሩ ተጠግቶ አባቶችን "ስም አውጡልኝ" ቢላቸው መንፈስ ቅዱስ አናግሯቸው "ጊዮርጊስ" አሉት:: እሱም ደስ እያለው: ባጭር ታጥቆ የልዳውን ቅዱስ ጊዮርጊስ ያገለግለው ገባ:: ትንሽ ቆይቶ ሁከት መንፈሳዊ ተሰማው:: ማለትም ስለ ሃይማኖቱ ደሙን ማፍሰስ ፈለገና ወደ ግብፅ ተመለሰ::

+በዚያ ያሉ አሕዛብ በክርስትና ስም: ልብስና ሞገስ ሲመለከቱት ተበሳጩ:: ዕለቱኑ አሠሩት:: ሌሊት እናቱና ሚስቱ መጥተው አሉት:- "አደራ! ፍቅረ ዓለም እንዳያታልልህ:: ሰማዕት ብትሆን ላንተም ክብር: ለእኛም ሞገስ ነው" ብለውም አጽናኑት:: እንዲህ ያሉ እናትና ሚስት ማግኘትም ታላቅ እድል ነው::

+ሐዲስ ጊዮርጊስም ጸና:: ከዚያች ቀን ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት ደበደቡት: አካሉን ቆራረጡት: ደሙንም መሬት ላይ አንጠፈጠፉት:: በየመንገዱ እየጎተቱ ተሳለቁበት:: እርሱ ግን ክርስቶስን ወዷልና ሁሉን ታገሰ:: ሌሊት በሆነ ጊዜም ጌታችን ተገልጦ "ከሰማዕታት ተቆጠርህ" አለው::

+በማግስቱ በአደባባይ አንገቱን በሰይፍ ቆረጡት:: ክፋታቸው የጸና ነውና ሥጋውን በእሳት አቃጠሉት:: ወደ ባሕርም ጣሉት:: እናቱ ከባሕር ስታወጣው ግን ምንም አላገኘውም ነበር:: በዚሕች ቀን እናቱና ሚስቱ በክብር ቀብረውታል::

+" አባ ስምዖን ሊቀ ዻዻሳት "+

+በምድረ ግብጽ ተነስተው: በማርቆስ ወንጌላዊ መንበር ላይ ይቀመጡ ዘንድ ከተገባቸው ሊቃነ ዻዻሳት አንዱ እኒህ አባት ናቸው:: ከልጅነታቸው መንነው ብዙ ዘመናትን በተጋድሎ በማሳለፋቸው ሥጋዊ አካላቸው ደካማ ሆኖ ነበር::

+ከገዳማዊ አገልግሎታቸው ቀጥሎም ከእርሳቸው በፊት ለነበሩ ሁለት ፓትሪያርኮች ረዳት ሆነው አገልግለዋል:: በዚህ ጊዜም ለመንጋው የሚሆኑ ተግባራትን ከመፈጸማቸው ባሻገር በጾምና በጸሎት መጋደልን አልተዉም ነበር::

+ጊዜው ደርሶ በእግዚአብሔር ፈቃድ: በሕዝቡና ዻዻሳቱ ምርጫ: የእስክንድርያ 51ኛ ፓትርያርክ ሲሆኑ እርሳቸው እንደ ሌሎቹ አበው 'አልፈልግም' ብለው ነበር::

+ቀደም ሲል እንዳልነው አካላቸው በተጋድሎ የተቀጠቀጠ ነበርና በመንበራቸው ላይ ለብዙ ጊዜ መቆየት አልቻሉም::እግራቸውን በጠና በመታመማቸው ፈጣሪ ነፍሳቸውን እንዲቀበል ለመኑት: እርሱም ሰማቸው:: ሊቀ ዻዻሳት ሆነው በተሾሙ በ165ኛው ቀን (ማለትም በ5 ወር ከ15 ቀናቸው) በክብር ዐርፈው ተቀብረዋል::

††† ቸሩ አምላክ ከሰማዕቱ ጽናትን: ትእግስትን: ጸጋ በረከትን ይክፈለን::

††† ጥቅምት 3 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ጊዮርጊስ ሐዲስ (ሰማዕት)
2.አባ ስምዖን ሊቀ ዻዻሳት
3.ቅዱስ ጐርጐርዮስ ዘአርማንያ
4.ቅድስት ታኦድራ ልዕልት
5.ቅድስት ታኦፊላ

††† " ስለዚሕ ወንድሞቼ ሆይ ጣዖትን ከማምለክ ሽሹ:: ልባሞች እንደመሆናችሁ እላለሁ:: በምለው ነገር እናንተ ፍረዱ:: የምንባርከው የበረከት ጽዋ ከክርስቶስ ደም ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? የምንቆርሰውስ እንጀራ ከክርስቶስ ሥጋ ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን?... እኛ ብዙዎች ስንሆን አንድ ሥጋ ነን:: ሁላችን ያን አንዱን እንጀራ እንካፈላለንና:: "††† (1ቆሮ. 10:14-18)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
Forwarded from ዝክረ ቅዱሳን zikre kidusan (ɴᴀᴛɴᴀᴇʟ)
Forwarded from ዝክረ ቅዱሳን zikre kidusan (ɴᴀᴛɴᴀᴇʟ)
አዲስ መንፈሳዊ መጽሐፍ ከዚያውም "ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን" "ኅብረ ሥርዐት ዘቤተ ክርስቲያን ኦርቶዶክሳዊት" በሚል ርእስ በኅትመት ላይ መሆኑን ስናበሥረዎ በደስታ ነው። በቅርቡ ገበያ ላይ ይውላል። አዲስ አበባ፣ጎንደር፣ ባሕር ዳር..... ይሰራጫል። በመጽሐፉ ውስጥ ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያንን በማብራሪያ ይማራሉ። አመክንዮአዊ ሐሳቦችን በአበው መንፈሳዊ አተያይ ይረዳሉ።በዘመናዊው ወጣት ዘንድ የሚነሡ ልዩ ልዩ ጥያቄዎችን በመ/ቅዱስ፣በፍትሐ ነገሥት እና በሌሎች የአበውን ትምህርት በያዙ የግእዝ መጻሕፍት ምስክርነት ለራስዎም ለሌላውም ይህን መጽሐፍ አንብበው ይመልሳሉ። ያንብቡ ይማሩ ይወቁ ይህን ይጠብቁ ይጽደቁ። "ካልተማሩ አያውቁ ካላወቁ አይጸድቁ" እንዲሉ።
Forwarded from ዝክረ ቅዱሳን zikre kidusan (ɴᴀᴛɴᴀᴇʟ)
2024/10/02 04:24:02
Back to Top
HTML Embed Code: