Telegram Web Link
በታመምህ ጊዜ ድካም ይሰማሃል፤ ብርታት ያንስሃል፤ ፊትህም ይገረጣል፡፡ የዕለት ተዕለት ሥራዎችህን በአግባቡ ማከናወን ይሳንሃል፡፡ በዚህ ጊዜም ሕመምህ ምን ያህል እንደበረታ ሰዎች ያስተውላሉ፤ መታከም እንደሚገባህም ይነግሩሃል፡፡ ስለዚህ ወደ ሐኪም ትኼዳለህ፡፡ ወደ ሐኪም የምትኼደው ግን ሐኪሙ ምን እንዲያደርግልህ ነው? አሁን ለሚሰሙህ ስሜቶች የሚሽሩ መድኃኒቶችን እንዲሰጥህ ነው፡፡ ኾኖም ይሰሙህ የነበሩ ስሜቶች ቢሻሉህም ሰውነትህ አሁንም እንደ ደከመ፣ ፊትህ እንደ ገረጣ ከቀረ፣ የዕለት ተዕለት ሥራዎችህንም በአግባቡ ማከናወን ከተሳነህ፥ በተሰጠህ ሕክምና ደስተኛ ትኾናለህን? አትኾንም!

እውነታው ምንድን ነው?” ስንል ወደ ሐኪሙ የኼድከው የበሽታህን ምንጭ ለመታከም ሳይኾን የበሽታህን ምልክቶች ለማስታገሥ ስለ ኾነ ነው፡፡ በሌላ መልኩ ደግሞ የበሽታህ መንሥኤ እስካልታከመ ድረስ የበሽታህ ምልክቶች ለጊዜው ቢታገሡም ቅሉ፥ ፈጽመው ሊወገዱ እንደማይችሉ ሐኪሙ በደንብ ያውቃል፡፡

በክርስቶስ ክርስቲያን፣ በወልድ ውሉድ፣ በመንፈስ ቅዱስም መንፈሳውያን የተባልን እኛም እግዚአብሔር መንፈሳዊ በሽታችንን እንዲያስወግድልን እንሻለን፡፡ እንደ እውነታው ግን ብዙዎቻችን ወደ እግዚአብሔር ቀርበን እንዲያስወግድልን የምንሻው ምልክቶቹን ነው፡፡ ለምሳሌ ችግርን፣ ኀዘንን፣ ቀቢጸ ተስፋንና የመሳሰሉትን እንዲያርቅልን እንፈልጋለን፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ ከዚህ በተቃራኒ የእነዚህ ምክንያት የኾነውንና ሥር የሰደደውን፣ ዋና ምክንያትም የኾነውን መንፈሳዊ በሽታችንን ሳይሽር እነዚህን ምልክቶች ሊያርቅልን አይፈልግም፡፡ ችግር የሚኾነውም ይህን ጊዜ ነው፡፡ ምልክቶቹን እንዲያርቅልን ስንደክም፥ ወደ ውሳጤያችን ገብቶ የችግሩን ምንጭ ሊያርቅልን የሚችለውን የእግዚአብሔርን ጸጋ (ኃይልን) አጥብቀን እንቃወማለንና፡፡ በውሳጤያችን የተሸሸገውን በሽታ ማስወገድ አንፈልግም፡፡ አመለካከታችን እንዲለወጥ አንፈቅድም፡፡ እውነተኛ ለውጥ የሚመጣውና አማን በአማን የምንታከመው ግን የልባችንን ውሳጤ ለእግዚአብሔር ስንከፍትለትና እርሱም በዚያ በመረቀዘው ቁስላችን ላይ ጽኑ መድኃኒት ሲያስርልን ነው፡፡ እንዲለወጡ የምንፈልጋቸው ምልክቶች በእርግጥም የሚለወጡት ይህ በልባችን ውስጥ የተደበቀው መንፈሳዊ በሽታችን ሲጠፋ ነው፡፡

#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን †


[  †  መስከረም [ ፭ ] 5 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  †  ]

†  🕊   " ቅድስት ሐጊያ ሶፍያ "   🕊  †

ዘመነ ሰማዕታት በሚል በሚታወቀው ፫ [3] ኛው መቶ ክ/ዘመን ብዙ ቅዱሳት እናቶቻችን ስለ ፍቅረ ክርስቶስ አንገታቸውን ሰጥተዋል:: አንዳንዶቹ ደግሞ ሕይወታቸው እጅግ የሚያምር ነበር:: ከእነዚህ ቅዱሳት እናቶቻችን አንዷ ዛሬ የምናከብራት ሐጊያ ሶፊያ ናት::

በዚህ ስም ከሚጠሩት አንዷ ስትሆን በቀደመ ሕይወቷ ክርስቶስን አታውቅም ነበር:: ጣዖትን የሚያመልኩ ወላጆቿ አሳድገው አጋቧት:: ከትዳሯም ፪ [2] ቡሩካት ሴቶች ልጆች ወልዳለች:: ስማቸውም አክሶስናና በርናባ ይባላል:: ልጆቿ ልብ እያገኙ በሔዱ ጊዜ ቅድስት ሶፍያ ስለ እውነተኛው አምላክ ትመራመር ገባች::

በወቅቱ የነበሩ ብዙ ሃይማኖቶችን መዘነች:: ከክርስትና በቀር ግን ሌሎቹ ሚዛን እንደማይመቱም አስተዋለች:: "እውነኘተኛው አምላክ ሆይ! ምራኝ: እርዳኝም" ስትል ጸለየች:: መድኃኔ ዓለም ለጠሩት አያሳፍርምና ፈጥኖ በጐውን ጐዳና አሳያት::

ድኅነት ለልጆቿም ይሆን ዘንድ ሁለቱንም ጠርታ ስለ ክርስትና አማከረቻቸው:: ደስ ብሏቸው ተቀበሏት:: እርሷም ጊዜ ሳታጠፋ ወደ ዻዻስ ሒዳ ማሕተመ ክርስትና: ሃብተ ውልድናን ትቀበል ዘንድ ከልጆቿ ጋር ተጠመቀች:: በቅድስናና ደስ በሚያሰኝ አኗኗርም እስከ መከራ ቀን ቆየች::

የመከራ ጊዜ ሲደርስም ልጆቿን ጠርታ "ስለ ክርስቶስ ፍቅር እንሙት" አለቻቸው:: ቡሩካቱ አክሶስናና በርናባም ደስ እያላቸው "እሺ" አሏት:: ወዲያውም በመኮንኑ ፊት ቀርበው ክርስቶስን ከመካድና ከስቃይ ሞት የትኛውን እንደሚመርጡ ቢጠየቁ እነርሱ መሞትን መረጡ:: ወደ እሥር ቤትም ከተቷቸው::

ቅድስት ሶፍያ [፪] 2 ልጆቿ ይጸኑላት ዘንድ አዘውትራ ገድለ ሰማዕታትን እና ክብራቸውን ትተርክላቸው ነበር:: በተለይ የታላቁዋን አንጌቤናይት [እመቤት] ሶፍያንና የ፫ [3] ልጆቿን [ዺስጢስ: አላዺስና አጋዺስ] ተጋድሎ እየነገረች ታጸናቸው ነበር::

ከእሥር በኋላ ግርፋት ታዞባቸው እናት ራቁቷን ስትገረፍ መልአክ ወርዶ ሲጋርዳት ልጆች በማየታቸው ደስ አላቸው:: ቅድስት ሐጊያ ሶፍያና ፪ [2] ልጆቿ እጅግ የበዛ ስቃይን ስለ ቀናች እምነት ተቀበሉ:: ምላስ እስከ መቆረጥም ደረሱ:: በመጨረሻ ግን በዚህች ቀን ተገድለው አክሊለ ሰማዕታትን ገንዘብ አደረጉ::

የመከራ ዘመን ካለፈ በኋላ ታላቁ ንጉሥ ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ የሁሉን ቅዱሳን ቤት ሠርቶ የእርሷን በመዘንጋቱ ለራሱ ባሰራው ቤተ መንግስት ላይ ተአምር ታይቷል:: ለ፫ ያህል ጊዜ ስሙን ሲያስቀርጽ መልአክ እየወረደ ይፍቀው: የሶፍያንም ስም ይጽፈው ነበር::

በመጨረሻም ንጉሡ ልጁን እስከ መገበር ደርሶ ቤተ መንግስቱ የቅድስት ሶፍያና የ፪ ልጆቿ ቤተ ክርስቲያን ለመሆን በቅቷል:: ምንም ለ፫ ጊዜያት ያህል ሙሉ እድሳት ቢደረግለትም ዛሬ አሕዛብ የያዙትን ይህንን ቅርስ ንጉሡ የሠራው ከ፲፻፯፻ [1700] ዓመታት በፊት ነው::


†  🕊 ቅዱስ ማማስ ሰማዕት  🕊

የሰማዕቱ ወላጆች ቴዎዶስዮስና ታውፍና ሲባሉ ማማስ የሚለው የስሙ ትርጉም 'ዕጉዋለ ማውታ - እናት አባቱ የሞቱበት' ማለት ነው:: ለምን እንደዚህ ተባለ ቢሉ :- በዘመነ ሰማዕታት ስደት በሆነ ጊዜ ወላጆቹ ይዘውት ተሰደው ነበር:: ማምለጥ ባይችሉ ይዘው አሠሯቸው::

በእሥር ቤትም ከስቃዩ ብዛት ፪ [2] ቱም ልጃቸውን ማማስን እንዳቀፉት ሕይወታቸው አለፈች:: ሕጻኑ ሲያለቅስ የተመለከተች አንዲት ሴትም ራርታ እነርሱን አስቀብራ: እርሱን አሳድጋዋለች:: ስሙንም 'ማማስ' ብላዋለች::

ቅዱሱ ባደገ ጊዜ የወላጆቹን ጐዳና በመከተሉ ተይዞ ለፍርድ ቀረበ:: ክርስቶስን አልክድም በማለቱም ብዙ ስቃይን አሳልፎ በዚህች ቀን ሰማዕት ሆኗል:: ቅዱስ ማማስ ከዐበይት ሰማዕታት አንዱ ሲሆን በአንበሳ ጀርባ ላይም ይቀመጥ ነበር::


🕊  አቡነ አሮን መንክራዊ  🕊

ኢትዮዽያዊው ጻድቅ አቡነ አሮን በ፲፬ [14] ኛው መቶ ክ/ዘመን የነበሩ ኢትዮዽያዊ ሲሆኑ በገዳማዊ ሕይወታቸው: በሐዋርያዊ አገልግሎታቸውና ነገሥታቱን ሳይፈሩ በመገሰጻቸው ይታወቃሉ:: በተለይም ሕይወታቸው በተአምር የተሞላ ስለነበር 'አሮን መንክራዊ' [ድንቅ አባት] ተብለው ይጠራሉ::

አንዳንድ ጊዜም 'አሮን ዘመቄት /ዘደብረ ዳሬት/' በሚልም ይጠራሉ:: የአቡነ አሮን ወላጆች ገብረ መስቀልና ዓመተ ማርያም የሚባሉ ሲሆን ከልጅነታቸው ጀምረው በቅዱስ ቃሉ የታነጹ ነበሩ:: ምናኔን በደብረ ጐል: ከአቡነ በጸሎተ ሚካኤል ጀምረው ብዙ ገዳማትን መሥርተዋል:: በርካታ ደቀ መዛሙርትንም አፍርተዋል::

ለወንጌል አገልግሎት በወጡበት ጸሐይን አቁመው: ሕዝቡን ድንቅ አሰኝተዋል:: እንኳን ሰዉ ይቅርና አጋንንትም ያደንቁዋቸው ነበር:: ነገሥታቱንም ስለ ኃጢአታቸው በገሰጹ ጊዜ ራቁትነት: እሥራት: ግርፋትና ስደት ደርሶባቸዋል::

ጻድቁ ከብዙ ተጋድሎ በኋላ በዚህች ቀን ወሎ መቄት ውስጥ በሚገኘው ገዳማቸው ዐርፈው ተቀብረዋል:: ገዳሙ እስካሁን ያለ ሲሆን ድንቅ ጥበበ እግዚአብሔር የሚታይበት ነው:: ጣራው ክፍት ሲሆን ዝናብ አያስገባም::

†  🕊  አፄ ልብነ ድንግል  🕊  † 

እኒህ ንጉሥ ኢትዮዽያን ለዓመታት (ከ፲፻፭፻ [1500] እስከ ፲፻፭፻፴፪ [1532] ዓ/ም) ቢያስተዳድሩም ፲፭ ቱ ዓመት ያለቀው በስደት ነው:: ከደጋጉ አፄ ናዖድና ንግሥት ወለተ ማርያም ተወልደው: በሥርዓቱ አድገው ቢነግሡም: በክፉ መካሪዎች ጠንቅዋይ ወደ ቤታቸው ገብቶ ሃገሪቱን ለመከራ ዳርጉዋታል::

ዛሬም ድረስ ጠባሳው ያለቀቀው የግራኝ ወረራ ለ፲፭ ዓመታት ሃገሪቱን ያለ ካህንና ቤተ ክርስቲያን አስቀርቷት ነበር:: ብዙ ክርስቲያኖችም ሰልመው ቀርተዋል:: አፄ ልብነ ድንግል ግን ደብረ ዳሞ ገዳም ውስጥ ገብተው ንስሃ ጀመሩ: አለቀሱ: ተማለሉ::

እመቤታችን ተገልጣም "ይቅርታን በነፍስህ እንጂ በሥጋህ አታገኝም" አለቻቸው:: እርሳቸውም ሱባኤውን ቀጥለው: 'ስብሐተ ፍቁርን': 'መልክአ ኤዶምን' የመሰሉ መጻሕፍትን ደርሰው በዚህች ቀን በ ዓ/ም ዐርፈዋል:: እኛ ክርስቲያኖችም እናከብራቸዋለን::

የቅዱሳኑ አምላክ የወዳጆቹን ፈተና አስቦ ሃገራችንን ከጥፋት: ሕዝቡንም ከስደት ይሰውርልን:: ከበረከታቸውም አይለየን::

🕊

[  † መስከረም ፭ [ 5 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]

፩. ቅድስት ሶፍያ ሰማዕት
፪. ቅዱሳት አክሶስናና በርናባ
፫. ቅዱስ ማማስ ሰማዕት
፬. ቅዱሳን ቴዎዶስዮስና ታውፍና
፭. አቡነ አሮን መንክራዊ
፮. አፄ ልብነ ድንግል

[  †  ወርኀዊ የቅዱሳን  በዓላት ]

፩. ቅዱስ ዼጥሮስ ሊቀ ሐዋርያት
፪. ቅዱስ ዻውሎስ ብርሃነ ዓለም
፫. አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ
፬. ቅዱስ ዮሐኒ ኢትዮዽያዊ
፭. ቅዱስ አሞኒ ዘናሒሶ
፮. ቅድስት አውጋንያ [ሰማዕትና ጻድቅ]

" ሞቱን በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን: ትንሳኤውን በሚመስል ትንሳኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን:: ከእንግዲህስ ወዲያ ለኃጢአት እንዳንገዛ የኃጢአት ሥጋ ይሻር ዘንድ አሮጌው ሰዋችን ከእርሱ ጋር እንደ ተሰቀለ እናውቃለን::" [ሮሜ.፮፥፭]

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ]

        †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                  🕊                    💖
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊

†  በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን  †


[  † መስከረም [ ፮ ] 6 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  †   ]

†   🕊  ቅዱስ ኢሳይያስ ነቢይ  🕊  †

በቤተ ክርስቲያን ታሪክ የኢሳይያስን ያህል ትንቢት የተናገረ ነቢይ አይገኝም:: ከትንቢቱ ብዛትና ከምስጢሩ ጉልህነት የተነሳ: አንድም ደፋር ስለ ነበር 'ልዑለ ቃል' ተብሎ ተጠርቷል:: ቅዱስ ኢሳይያስ የተወለደው ከክርስቶስ ልደት ፰፻ [800] ዓመታት በፊት ሲሆን ለነቢይነት የተመረጠው ገና በወጣትነቱ ነበር::

ወላጆቹ  'ኢሳይያስ' [መድኃኒት] ያሉት በትምሕርቱ: በትንቢቱ የጸጋ መድኃኒትነት ስላለው ነው:: እርሱ በነቢይነት በተሾመበት ወራት ሊቀ ካህናቱ አዛርያስ: ንጉሡ ደግሞ ዖዝያን ይባሉ ነበር:: በሊቀ ካህናቱና በንጉሡ መካከል በተነሳ ጠብ ንጉሡ የበላይነቱን ለማሳየት ሃብተ ክህነት ሳይኖረው ሊያጥን ወደ ቤተ መቅደስ ገባ::

ይህንን የተመለከተው ኢሳይያስ ሊገስጸው ሲገባ 'ወዳጄ ነው' በሚል ዝም አለው:: ፈታሒ እግዚአብሔር ግን ዖዝያንን በለምጽ መታው:: የግንባሩን ለምጽ በሻሽ ቢሸፍነው ከሻሹ ላይ ወጣበት:: በእሥራኤል ለምጽ ያለበት እንኩዋን በዙፋን ከተማ ውስጥም መቀመጥ አይችልምና አስወጡት:: በእርሱ ፈንታም ኢዮአታም ነግሷል::

ኢሳይያስ ደግሞ እግዚአብሔር በሰጠው አንደበት ሙያ አልሠራበትምና ከንፈሩ ላይ ለምጽ ወጣበት:: እርሱንም ወስደው ጨለማ ቤት ዘጉበት:: ሃብተ ትንቢቱንም ተቀማ:: ቅዱሳን ትልቁ ሃብታቸው ንስሃቸው ነውና በዚያው ሆኖ ንስሃ ገባ: ተማለለ: ጾመ: ጸለየ::

እግዚአብሔርም ንስሃውን ተመለከተለት:: ከዚያም ንጉሡ ዖዝያን በሞተበት ዓመት ኢሳይያስ እግዚአብሔርን በረዥም [ልዑል] ዙፋኑ ላይ ተቀምጦ: ኪሩቤል ተሸክመውት: ሱራፌል [፳፬ [24] ቱ ካህናተ ሰማይ] "ቅዱስ: ቅዱስ: ቅዱስ" እያሉ ሲያመሰግኑት ተመለከተ:: [ኢሳ.፮፥፩] (6:1)

አበው ሲተረጉሙ "አንተ ያፈርከው ዖዝያን እነሆ ሞተ:: እኔ ግን መንግስቴ የዘለዓለም ነው" ሲለው ነው ይላሉ:: ያን ጊዜ እግዚአብሔር "ወደ ሕዝቤ ማንን እልካለሁ?" አለ:: ኢሳይያስም "ጌታየ! እኔ ከንፈሮቼ የረከሱ አለሁ" አለው:: እግዚአብሔርም ሱራፊን ላከለት:: መልአኩም ፍሕም [እሳት] በጉጠት አምጥቶ ከንፈሩን ቢዳስሰው ነጻ:: ሃብተ ትንቢቱም ተመለሰለት:: ይኸውም የሥጋ ወደሙ ምሳሌ ነው::

ከዚህች ቀን በኋላ ግን ኢሳይያስ የተለየ ሰው ሆነ:: ማንንም የማይፈራ እውነተኛ የልዑል ወታደር ሆነ:: ከኦዝያን በሁዋላ በየዘመናቸው 4ቱንም ነገሥታት ገሰጸ:: እነዚህም ኢዮአታም: አካዝ: ሕዝቅያስና ምናሴ ናቸው::

ቅዱስ ሕዝቅያስ በነገሠ በ፲፬ [14] ኛው ዓመት የአሦር ንጉሥ ሰናክሬም በጠላትነት ተነሳበት:: ወደ አካባቢውም መጥቶ: ከቦ አስጨነቀው:: ሰናክሬም በጦር እጅግ ኃይለኛ ነበር:: በዚያውም ላይ ጦር የሚመዙ ከ ፻፹፭ ሺህ [185,000] በላይ ብርቱ ተዋጊዎች ነበሩትና ሕዝቅያስ እንደማይችለው ተረድቶ መልእክተኛ ላከበት::

ሰናክሬም ግን ሰይጣን ያደረበት ነውና የሕዝቅያስን ልመና ወደ ጐን ብሎ የእሥራኤልን አምላክ: ቅዱስ ስሙንም ተገዳደረ:: ቅዱስ ሕዝቅያስ በዚህ ጊዜ የፈጣሪው ስም ሲቃለል ሰምቷልና ፈጽሞ አዘነ::

መልእክተኞችን ወደ ነቢዩ ቅዱስ ኢሳይያስ ልኮ እርሱ ወደ ቤተ መቅደስ ገባ:: በእግዚአብሔር ፊት ልብሱን ቀድዶ ማቅ ለበሰ:: ስለ ኢየሩሳሌምና ሕዝቡም ፈጽሞ አለቀሰ:: በዚህ ጊዜ እግዚአብሔር በኢሳይያስ አንደበት እንዲሕ አለ:- "ስለ ባሪያየ ስለ ዳዊት ከተማዋን አድናታለሁ::"

በዚያች ሌሊትም ድንቅ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ከሰማያት በግርማ ወረደ:: ወደ ሰናክሬም የጦር ሠፈር ደርሶ አንድ ጊዜ የእሳት ሰይፉን መዝዞ ቢያሳያቸው ከአሕዛብ ሠራዊት ፻፹፭ ሺህ [185] ሺ ኃያላን እንደ ቅጠል ረገፉ:: [፩ነገ.፲፰፥፲፫] (18:13) , [፲፱፥፩]

ታላቁ ነቢይ ልዑለ ቃል ኢሳይያስ ሐረገ ትንቢትን ያፈስ ነበርና ከተናገራቸው ትንቢቶችም አንዱ "ድንግል ትጸንሳለች: ወንድ ልጅም ትወልዳለች" የሚል ነበር:: [ኢሳ.፯፥፲፬]

በወቅቱ የነበሩ አንዳንድ ክፉ መካሪዎች ቀርበው ንጉሡን በውዳሴ ከንቱ ጠለፉት:: "ንጉሥ ሆይ! ሺህ ዓመት ንገሥ:: እንዳንተ ያለ ማንም የለም:: ነቢዩ የተናገረው ትንቢትም እኮ ላንተ ነው:: 'ድንግል' የተባለች ኢየሩሳሌም ስትሆን 'ወልድ-ወንድ ልጅ' የተባልክ ደግሞ አንተ ነህ" አሉት::

ይሕንን ጠማማ ትርጉም እህ ብሎ የሰማቸው ቅዱስ ሕዝቅያስ አልወቀሳቸውም:: በዚህ ምክንያት እግዚአብሔር ተቆጥቶ ኢሳይያስን ላከው:: ነቢዩም መጥቶ ንጉሡን አለው :- "ትሞታለህ እንጂ አትተርፍምና ቤትህን ሥራ::"

ወዲያውኑ ሕዝቅያስ ታመመ: ደከመ:: ንጉሡ ወደ ፈጣሪ :- "ጌታ ሆይ! እንደ ቸርነትሕ በፊትህ በቅን መንገድ መሔዴን አስብና ይቅር በለኝ" ሲል ተማጸነ:: ይህ ሲሆን ቅዱስ ኢሳይያስ ገና ከንጉሡ አካባቢ አልራቀም ነበርና የእግዚአብሔር ቃል ወደ እርሱ መጣ::

ሕዝቅያስን በለው :- "ጸሎትህን ሰምቼ: ስለ ባለሟሌ ስለ ዳዊት ብየ ምሬሐለሁ:: በዘመንህም ላይ ፲፭ [15] ዓመታትን ጨምሬልሃለሁ በለው" አለው:: ነቢዩም ወደ ንጉሡ ተመልሶ ይሕንኑ ነግሮ "እስከ ፫ ቀን ድረስ ወደ ቤተ መቅደስ ድነህ ትመለሳለህ" አለው::

ቅዱስ ሕዝቅያስ "ይሕ እንደሚደረግ በምን አውቃለሁ?" አለው:: ኢሳይያስም ፀሐይን ዓለም እያየ ፲ [10] መዓርጋትን ወደ ሁዋላ መለሳት::

ልዑለ ቃል ቅዱስ ኢሳይያስ ለ ፸ [70] ዘመናት ሕዝቡን አስተምሮ: ነገሥታቱን ገስጾ: ፷፰ [68] ምዕራፎች ያሉትን ሐረገ ትንቢት ጽፎ አረጀ:: በዘመኑ የነበረው ንጉሥ ምናሴ ግን ይባስ ብሎ ጣዖትን አቆመ: ለጣዖትም ሰገደ:: ቅዱሱ ይህንን ሲያደርግ ዝም አላለውም:: በአደባባይ ገሰጸው እንጂ::

በዚህ የተበሳጨ ምናሴም ሽማግሌውን ነቢይ በእንጨት መጋዝ ለሁለት አሰነጠቀው:: ቅዱስ ኢሳይያስ በዚህ ዓይነት ሞት በጐ ሕይወቱንና ሩጫውን ፈጸመ:: የተናገራቸው ትንቢቶች ግልጽ ስለ ሆኑ 'ደረቅ ሐዲስ' በመባል ይታወቃሉ::

ቸሩ አምላክ 'ደሃ ተበደለ: ፍርድ ተጉዋደለ' የሚሉ መምሕራን አባቶችን አይንሳን:: ከነቢዩም በረከቱን ይክፈለን::

[  † መስከረም ፮ [ 6 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]

፩. ቅዱስ ኢሳይያስ ነቢይ [ልዑለ ቃል]
፪. ቅድስት ሰብልትንያ ሰማዕት
፫. አባ ያዕቆብ ገዳማዊ
፬. ቅዱስ አናቲሞስ ኤዺስ ቆዾስ

[  †  ወርኀዊ የቅዱሳን በዓላት  ]

፩. ቅድስት ደብረ ቁስቁዋም
፪. አባታችን አዳምና እናታችን ሔዋን
፫. አባታችን ኖኅና እናታችን ሐይከል
፬. ቅዱስ ኤልያስ ነቢይ
፭. ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ
፮. ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ
፯. ቅድስት ሰሎሜ
፰. አባ አርከ ሥሉስ
፱. አባ ጽጌ ድንግል
፲. ቅድስት አርሴማ ድንግል


" ኑ እንዋቀስ ይላል እግዚአብሔር:: ኃጢአታችሁ እንደ አለላ ብትሆን እንደ አመዳይ ትነጻለች:: እንደ ደምም ብትቀላ እንደ ባዘቶ ትጠራለች:: እሺ ብትሉ: ለእኔም ብትታዘዙ የምድርን በረከት ትበላላችሁ:: እንቢ ብትሉ ግን: ብታምጹም ሰይፍ ይበላቹሃል:: የእግዚአብሔር አፍ ይህንን ተናግሯልና:: " [ኢሳ.፲፥፲፰]

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊

†  በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን  †


[  † መስከረም 7 [ ፯ ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  †  ]


እንኩዋን ለቅድስት ኤልሳቤጥ: ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ሊቅ እና አባ ሳዊርያኖስ ክቡር ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ


[  †  🕊 ቅድስት ኤልሳቤጥ  🕊  †  ]

በወንጌላዊው አንደበት የተመሰገነች እናታችን ቅድስት ኤልሳቤጥ ትውልዷ ከነገደ ሌዊ ነው:: ሐረገ ሙላዷም ከቅዱስ አሮን ካህን ወገን ይመዘዛል:: ከአሮን በቴክታና በጥሪቃ ወርዶ ሔርሜላ ላይ ይደርሳል::

ይህቺ ሔርሜላ የምትባል ደግ ሴት ማጣት ["ጣ" ጠብቆ ይነበብ] የሚባል የተባረከ ሰው አግብታ ፫ [3] ቡሩካት ልጆችን ወለደች:: የመጀመሪያዋን 'ማርያም' አሏት:: እርሷ ቅድስት ሰሎሜን ወለደች:: ሁለተኛዋን 'ሶፍያ' አሏት:: እርሷ ደግሞ ቅድስት ኤልሳቤጥን ወለደች::

ሦስተኛዋ ግን የተለየች ናት:: 'ሐና' ብለው ሰየሟት:: እርሷም የሰማይና የምድር ንግሥት የሆነችውን ድንግል ማርያምን ወለደች:: በዚህም መሠረት ድንግል ማርያም: ቅድስት ኤልሳቤጥና ቅድስት ሰሎሜ የእህትማማች ልጆች ናቸው::

ቅድስት ኤልሳቤጥ እድሜዋ በደረሰ ጊዜ ስም አጠራሩ የከበረ: ደግ ካህን ለሆነ: ለቅዱስ ዘካርያስ አጋቧት:: እርሷ የሊቀ ካህናቱ ሚስት ናትና ክብሯ ከፍ ያለ ነበር:: ምንም ልጅ ባይኖራትም ዘወትር በጸሎትና በጾም: ምጽዋትንም በማዘውተር: ነዳያንንም በማሰብ የምትኖር እናትም ነበረች::

ቅዱስ ወንጌል ላይ ከእመቤታችን ቀጥሎ የነዘካርያስን ቤተሰብ ያህል ክብሩ የተገለጠለት ፍጡር ይኖራል ብሎ መናገሩ ይከብዳል:: ቅዱስ ሉቃስ ወንጌሉን የጀመረው በዚህ ቅዱስ ቤተሰብ ነውና መንፈስ ቅዱስ እንዲህ ሲል አጽፎታል::
"ዘካርያስ ካህኑና ቅድስት ኤልሳቤጥ በሰውና በእግዚአብሔር ፊት ያለ ነቀፋ የሚኖሩ ጻድቃን ነበሩ" ይላቸዋል:: [ሉቃ.፩፥፮] (1:6)

የሰውን እንተወውና በእግዚአብሔር ፊት ያለ ነቀፋ መኖር ምን ይረቅ? ለዚህ አንክሮ [አድናቆት] ይገባል! እሊህ ቅዱሳን ባልና ሚስት ግን መካኖች በመሆናቸው ልጅ ሳይወልዱ ዘመናቸው አልፎ ነበር:: እንደ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት ዕድሜአቸው የኤልሳቤጥ ፺ [90] የዘካርያስ ፻ [100] ደግሞ ደርሶ ነበር::

ፍጹም መታገሳቸውን የተመለከተ ጌታ ግን በስተ እርጅናቸው ከሰው ሁሉ በላይ የሆነ ታላቅ ነቢይን ይሰጣቸው ዘንድ መልአከ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤልን ላከላቸው:: ቅድስቲቷ መስከረም ፳፮ [26] ቀን ታላቁን ሰው ጸንሳ ለ6 ወራት ራሷን ሠወረች::

ድንግል እመቤታችን ወደ እርሷ መጥታ 'ሰላም' ባለቻት ጊዜ ምንም ያሳደገቻት ልጇ ማለት ብትሆን: መንፈስ ቅዱስ ስለ ሞላባት እመ ብርሃንን አመስግናታለች:: ቡርክት: ብጽእት: ከፍጥረተ ዓለሙ የከበረች መሆኗንም መስክራለች::

በማሕጸኗ ያለ የ፮ [6] ወር ጽንስም የእመ አምላክን ድምጽ ቢሰማ በደስታ ዘሏል:: ለፈጣሪውም ስግደተ-ስባሔ አቅርቧል:: ቅድስት ኤልሳቤጥ አክላም "ወምንትኑ አነ ከመ ትምጽኢ ኀቤየ እሙ ለእግዚእየ-የጌታየ እናቱ ወደ እኔ ትመጪ ዘንድ እንዴት ይገባኛል?" ስትል በትኅትና ተናግራለች:: ከጌታ እናት ጋር ለ፫ [3] ወራት በአንድ ቤት ቆይታለች::

ቅዱስ ዮሐንስ ከተወለደ ፪ [2] ዓመት ከ፮ [6] ወር በሆነው ጊዜ ሰብአ ሰገል በመምጣታቸው በእሥራኤል ምድር የሚገኙ ሕጻናትን ሔሮድስ ቁዝ አስፈጀ:: ትንሽ ቆይቶም አይሁድ ለሔሮድስ ስለ ቅዱሱ ሕጻን ነገሩት:: "ሲጸነስ የአባቱን አንደበት የዘጋ: ሲወለድ ደግሞ የከፈተ 'ዮሐንስ' የሚባል ሕጻን አለና እሱንም ግደል" አሉ::

እናቱ ቅድስት ኤልሳቤጥ ይዛው ስትሸሽ ካህኑን ዘካርያስን ግን በቤተ መቅደስ መካከል ገድለውታል:: አረጋይት ኤልሳቤጥም ሕጻኑን እያሳደገች በገዳመ ዚፋታ ለ፫ [3] ፭ (5) ዓመታት ቆይታለች:: ቅዱስ ዮሐንስ ፭ [5] ፯ (7) ዓመት ሲሞላው ግን እዚያው በበርሃ እናቱ ዐረፈች:: ከሰማይ ዘካርያስና ስምዖን ወርደው ቀበሯት:: ኤልሳቤጥ ማለት 'እግዚአብሔር መሐላየ ነው': አንድም 'የጌታ አገልጋይ' ማለት ነው::


[ † 🕊 ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ሊቅ  🕊 †  ]

ይህ አባት የተዋሕዶ ሃይማኖታችን ምሰሶ ነው:: በ፭ [5] ኛው መቶ ክ/ዘመን በግብጽ ተወልዶ አድጐ: በልጅነቱ መጻሕፍትን ተምሮ: የምናኔ ሕይወትን መርጧል:: ቆይቶም የታላቁ ሊቅ ቅዱስ ቄርሎስ ረድእ ሆኖ ተምሯል: አገልግሎታል::

በጉባኤ ኤፌሶን ጊዜም ቅዱስ ቄርሎስን ተከትሎ ሒዶ ተሳትፏል:: በ፬፻፵፬ [444] ዓ/ም ታላቁን ሊቅ ተክቶ የእስክንድርያ ፳፭ [25] ኛ ፓትርያርክ ሆኖ ተሹሟል:: ለ፯ [7] ዓመታትም መጽሐፈ ቅዳሴውን [እምቅድመ ዓለምን] ጨምሮ ብዙ ድርሰቶችን ደርሷል:: በመልካም እረኝነትም ሕዝቡን ጠብቇል::

ዘመነ ሰማዕታትን ተከትሎ የመጣው የመናፍቃን ዘመን ሲሆን ለ፻፶ [150] ዓመታት ያህል መናፍቃን እንደ አሸን ፈልተዋል:: በዚያው ልክ ከዋክብት ቅዱሳን ሊቃውንት ነበሩና በየጊዜው ጉባኤያትን እየሠሩ: መናፍቃንን አሳፍረዋል:: ምዕመናንንም አጽንተዋል::

በ፬፻፶፩ [451] ዓ/ም የተፈጸመው ድርጊት ግን ዛሬም ድረስ ጠባሳው የሚለቅ አልሃነም:: ንጉሡ መርቅያንና ዻዻሱ ልዮን የንስጥሮስን ትምሕርት አለባብሰው ሊያስተምሩ ሲሞክሩ ግጭት በመፈጠሩ ቤተ ክርስቲያን ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ፪ [2] ተከፈለች::

በጉባኤው የነበሩ ፮፻፴፮ [636] ዻዻሳት ስቃይና ሞትን ፈርተው በኑፋቄ መጽሐፍ ላይ በመፈረማቸው "መለካውያን" [ከእግዚአብሔር ይልቅ ለንጉሥ የሚታዘዙ] ተባሉ:: ጉባኤውም "ጉባኤ ከለባት" [የውሾች ስብሰባ]: "ጉባኤ አብዳን" [የሰነፎች ጉባኤ] ተብሏል::

ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ግን "በኑፋቄው ላይ አልፈርምም" ከማለቱ አልፎ መናፍቃኑን አወገዛቸው:: በዚህ ምክንያት ወደ ጋግራ ደሴት ከ፯ [7] ደቀ መዛሙርቱ ጋር አሳደዱት:: በዚያም ለ፫ [3] ዓመታት ቆይቶ በ፬፻፶፬ [454] ዓ/ም ዐረፈ::

ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ከማረፉ በፊት በተሰደደባት ደሴተ ጋግራ ለ፫ [3] ዓመታት ብዙ መከራ ከመናፍቃን ደርሶበታል:: እርሱ ግን በትእግስቱና በትምሕርቱ ብዙዎችን ወደ ሃይማኖት መልሷል::

ቤተ ክርስቲያን እርሱን 'አበ ተዋሕዶ' [የተዋሕዶ እምነት አባትና አርበኛ] ትለዋለች:: የተነጨ ጺሙ: የረገፉ ጥርሶቹና የፈሰሰ ደሙ ዛሬም ድረስ ትልቅ ምስክርና የሃይማኖት ፍሬ ነውና::
"ያስተጻንዕ ህየ እለ ኀለዉ ደቂቀ:
ዘተነጽየ እምነ ጽሕሙ ወእም አስናኒሁ ዘወድቀ:
ፍሬ ሃይማኖቱ ፈነወ ብሔረ ርሑቀ" እንዲል::


[  † 🕊 ታላቁ አባ ሳዊርያኖስ  🕊 †  ]

የዚህን ቅዱስ ሰው ስም የሚጠራ አፍ ክቡር ነው:: ጣዕመ ሕይወቱ ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም:: እርሱ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የበቀለ: ፴ ፡ ፷ : ፻ [30: 60: 100] ፍሬዎችን ያፈራ የመንፈስ ቅዱስ ተክል ነው:: በትውልድ ሮማዊ ሲሆን የተወለደው በ፫፻፱ [309] ዓ/ም ነው::

ወላጆቹ በዚህ የንጉሥ ዘመዶች: በዚያ ደግሞ ባለጠጐች ነበሩ:: እነርሱ ለልጃቸው ጥበብን መርጠዋልና የግሪክን ፍልስፍና: የዮናናውያንን ጥበብ ሁሉ ተማረ:: ከዚያ በአንድ ልቡ ብሉይን: ሐዲስን ተምሮ ሲጠነቅቅ ወላጆቹ ዐረፉ::

ቅዱሱ ሳዊርያኖስም "የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር መስጠት አለብኝ" ብሎ ቀን ቀን ያለፈውን: ያገደመውን ሁሉ ሲያበላ: ሲያጠጣ: ነዳያንን ሲጐበኝ ይውላል:: ምሽት ሲል ደግሞ ወደ ቅዱሱ ንጉሥ [አኖሬዎስ] ቤተ መንግስት ገብቶ: ወገቡን ታጥቆ ከንጉሡ ጋር ሲጸልይና ሲሰግድ ያድራል::
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
ውዳሴ ከንቱ ሲበዛበት ንብረቱን ሁሉ ለነዳያን አካፍሎ ገብላ ወደምትባል ሃገር ሒዶ መነኮሰ:: ባጭር ጊዜም የብዙ ነፍሳት አባት ሆነ:: ብዙ ተአምራትንም ሠራ:: ትንሽ ቆይቶ ደግሞ የገብላ [ኤላ] ዻዻስ ሆኖ ተሾመ:: በዘመነ ሲመቱም እንቅልፍን አልተመለከተም:: ባጭር ታጥቆ ያላመኑትን ለማሳመን ደከመ እንጂ::

ጌታ ከእርሱ ጋር ነውና አይሁድን: መተተኞችንና አሕዛብን ሁሉ አሳምኖ ኤላ [ገብላ] አንድ የክርስቶስ መንጋ ሆነች:: የሚገርመው ከደግነቱ የተነሳ ሰይጣንን እንዳይገባ ከልክሎት በመንገድ ላይ ቁሞ ሲያለቅስ ይታይ ነበር:: ቅዱስ ሳዊርያኖስ ብዙ ድርሳናትን ደርሶ: እልፍ ፍሬንም አፍርቶ: በተወለደ በ፻ [100] ዓመቱ በ፬፻፰ [408] ዓ/ም ዐርፎ በክብር ተቀብሯል::

የእነዚህ ሁሉ ከዋክብት ቅዱሳን አምላክ ሃይማኖታችንን ይጠብቅልን:: ክፉውንም ሁሉ ያርቅልን:: ከበረከታቸውም ይክፈለን::

🕊

[  †  መስከረም ፯ [ 7 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት   ]

፩. እናታችን ቅድስት ኤልሳቤጥ
፪. ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ሊቅ [የተዋሕዶ ሃይማኖት አባት]
፫. ታላቁ ቅዱስ ሳዊርያኖስ
፬. ቅድስት ሐና [የእመ ብርሃን እናት-ልደቷ ነው]
፭. ቅዱሳን አጋቶን: ዼጥሮስ: ዮሐንስ: አሞንና እናታቸው ራፊቃ [ሰማዕታት]

[   †  ወርሐዊ በዓላት    ]

፩. ሥሉስ ቅዱስ [ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ]
፪. አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ
፫. አባ ሲኖዳ [ የባሕታውያን አለቃ ]
፬. አባ ዳንኤል ዘገዳመ ሲሐት
፭. አባ ባውላ ገዳማዊ
፮. ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ
፯. ቅዱስ አግናጥዮስ [ ለአንበሳ የተሰጠ ]

" ኤልሳቤጥም የማርያምን ሰላምታ በሰማች ጊዜ ጽንሱ በማሕጸኗ ውስጥ ዘለለ:: በኤልሳቤጥም መንፈስ ቅዱስ ሞላባት:: በታላቅ ድምጽም ጮኻ እንዲህ አለች:- 'አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ: የማሕጸንሽም ፍሬ የተባረከ ነው:: የጌታየ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይሆንልኛል? . . . ከጌታ የተነገረላት ቃል ይፈጸማልና ያመነች ብጽዕት ናት::" [ሉቃ.፩፥፵፩] (1:41)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

[  መስከረም ፰ [ 8 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት   ]


†   🕊  ቅዱስ ሙሴ ሊቀ ነቢያት  🕊  †

ቅዱሳን ነቢያት እጅግ ብዙ ናቸው:: ከፈጣሪያቸው የተቀበሉት ጸጋም ብዙና ልዩ ልዩ ነው:: ያም ሆኖ ከሁሉም ነቢያት ቅዱስ ሙሴ ይበልጣል:: መጽሐፍ እንደሚል ከእርሱም በፊት ቢሆን ከእርሱ በሁዋላ እንደ እርሱ ያለ ነቢይ አልተነሳምና:: ይህስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-

ዓለም በተፈጠረ በ፫ ሺህ ፮ መቶ [3,600] ዓመት እሥራኤል በረሃብ ምክንያት ፸፭ [75] ራሱን ወደ ምድረ ግብፅ ወረደ:: በዚያም ልጆቹና የልጅ ልጆቹ ለ፪፻፲፭ [215] ዓመታት ተከብረው: ለ፪፻፲፭ [215] ዓመታት ደግሞ በባርነት: በድምሩ ለ፬፻፴ [430] ዓመታት በምድረ ግብፅ ኑረዋል::

በባርነት ዘመናቸውም 'ራምሴና ጋምሴ' የሚባሉ ፪ [2] ከተሞችን [ዛሬ ፒራሚዶች የምንላቸውን] ገንብተዋል:: ግፋቸው እየበዛ ሲሔድ ግን ጩኸታቸው ቅድመ እግዚአብሔር ደረሰ:: ያድናቸውም ዘንድ አንድ ቅዱስ ሰው እንዲወለድ አደረገ:: ይኽም ሰው ሙሴ ይባላል::

ወላጆቹ መታመናቸውን በፈጣሪያቸው ያደረጉ 'እንበረም'ና 'ዮካብድ' ሲሆኑ ከሌዊ ነገድ ናቸው:: ከሙሴ ውጪም አሮንና ማርያምን ወልደዋል:: ቅዱስ ሙሴ በተወለደበት ወራት ወንድ የእሥራኤል ሕጻናት ይፈጁ ነበር:: ጌታ ግን በገዳዮቹ ልቡና ርሕራሔን አምጥቶ አትርፎታል::

በኋላም በ፫ [3] ወሩ ዓባይ ወንዝ ላይ ጥለውት ተርሙት [የፈርኦን ልጅ ናት] ወስዳ በቤተ መንግስት አሳድጋዋለች:: 'ሙሴ' ያለችውም እርሷ ናት:: 'ዕጉዋለ ማይ / እማይ ዘረከብክዎ' [ከውሃ የተገኘ] ለማለት ነው:: ወላጆቹ ያወጡለት ስም ግን 'ምልክአም' ይባላል:: ገና ሲወለድ ፊቱ እንደ መልአክ ያበራ ነበርና::

ቅዱስ ሙሴ ፭ [5] ዓመት በሆነው ጊዜ ፈርኦንን በጥፊ በመማታቱ ለፍርድ ቀርቦ እሳትን በመብላቱ አንደበቱ ኮልታፋ ሆኖ ቀርቷል:: እናቱ ዮካብድ ሞግዚት ሆና ስላሳደገችው ፵ [40] ዓመት በሆነው ጊዜ የፈርኦንን ቤት ምቾትና የንጉሥ ልጅ መባልን ናቀ:: ቅዱስ ዻውሎስ እንደሚለው በአሕዛብ ቤት ካለ ምቾት ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራን ሊቀበል ወዷልና:: [ዕብ.፲፩፥፳፬] (11:24)

አንድ ቀንም ለዕብራዊ ወገኑ ተበቅሎ ግብጻዊውን ገድሎት ወደ ምድያም ሸሸ:: በዚያም ለ፵ [40] ዓመታት የካህኑን ዮቶርን በጐች እየጠበቀ: ኢትዮዽያዊቱን ሲፓራን አግብቶ ኖረ:: ልጆንም አፈራ:: ፹ [80] ዓመት በሞላው ጊዜ እግዚአብሔር በደብረ ሲና ተናገረው:: ሕዝቡንም ከባርነት ቀንበር እንዲታደግ ላከው::

ቅዱስ ሙሴም ከወንድሙ አሮንና ከአውሴ [ኢያሱ] ጋር ግብጻውያንን በ፱ [9] መቅሰፍት: በ፲ [10] ኛ ሞተ በኩር መታ:: እሥራኤልንም ነጻ አወጣ:: ሊቀ ነቢያት የሠራቸው ሥራዎች ተዘርዝረው የሚያልቁ አይደሉም::

- እርሱ ባሕረ ኤርትራን ከፍሎ ሕዝቡን በደረቅ አሻግሯል::
- ግብጻውያንን ከነሠረገሎቻቸው በባሕር ውስጥ አስጥሟል::
- ለሕዝቡ መና ከደመና አውርዷል::
- ውሃን ከጨንጫ [ከዓለት] ላይ አፍልቁዋል::
- በብርሃን ምሰሶ መርቷቸዋል::
- በ7 ደመና ጋርዷቸዋል::
- ጠላቶቻቸውን ሁሉ ድል ነስቶላቸዋል::

ስለዚህ ፈንታ ግን ወገኖቹ ብዙ አሰቃይተውታል:: እርሱ ግን ደግ: ቅንና የዋህ ሰው ነውና ብዙ ጊዜ ራሱን ለእነሱ አሳልፎ ሰጥቷል:: "ሙሴሰ የዋህ እምኩሎሙ ደቂቀ እሥራኤል" እንዲል:: [ዘኁ.፲፪፥፫] (12:3) ቅዱስ ሙሴ ለ፵ [40] ዓመታት ሕዝቡን ሲመራ ከእግዚአብሔር ጋር ለ፭፻፸ [570] ጊዜ ተነጋግሯል::

ከጸጋው ብዛትም ፊቱ ብርሃን ስለ ነበር ሰዎች እርሱን ማየት አይችሉም ነበር:: ታቦተ ጽዮንንና ፲ [10]ሩ ቃላትን ተቀብሎ ጽላቱ ቢሰበሩ ራሱ ሠርቶ በጌታ እጅ ቃላቱ ተጽፈውለታል:: "የቀረው የቅዱሱ ሕይወት በመጻሕፍተ ኦሪት [በብሔረ ኦሪት] ውስጥ የተጻፉ አይደሉምን?"

እኔ ግን ደካማ ነኝና ይህቺ ትብቃኝ:: ቅዱስ: ክቡር: ታላቅ: ጻድቅ: ነቢይና ደግ ሰው ቅዱስ ሙሴ በ፻፳ [120] ዓመቱ ዐርፎ በደብረ ናባው ሊቃነ መላእክት ቅዱሳን ሚካኤል: ገብርኤልና ሳቁኤል ቀብረውታል:: መቃብሩንም ሠውረዋል:: [ይሁዳ.፩፥፱] (1:9)


†   🕊  ቅዱስ ዘካርያስ ካህን  🕊   †

ስም አጠራሩ የከበረ: ሽምግልናውም ያማረ ቅዱስ ዘካርያስ የቅድስት ኤልሳቤጥ ባል: የመጥምቁ ዮሐንስም አባት ነው:: በእሥራኤል ታሪክ የመጨረሻው ደግ ሊቀ ካህናት ነው:: ይህ ቅዱስ ሰው ከአሮን ወገን ተወልዶ: በሥርዓተ ኦሪት አድጐ: በወጣትነቱ መጻሕፍተ ብሉያትን ተምሮ: ሊቀ ካህንነቱን እጅ አድርጉዋል::

በጐልማሳነቱም ቅድስት ኤልሳቤጥን አግብቶ በደግነትና በምጽዋት አብሯት ኑሯል:: ከኢያቄምና ከሐና ጋር ቅርብ ወዳጆች ነበሩና አልተለያዩም:: ቅዱሱ ዘወትር ለማስተማር: ለመስዋዕትና ለማዕጠንት ይተጋ ነበር:: ጸሎቱና እጣኑም ወደ ቅድመ እግዚአብሔር ይደርስለት ነበር::

እስኪያረጅ ድረስ ባይወልድም አላማረረም:: ደስ የሚለው ደግሞ እመ ብርሃን ድንግል ማርያምን ከወላጆቿ ተቀብሎ ለ፲፪ [12] ዓመታት ያሳደጋት እርሱ ነው:: ዘወትር መላእክት ከበው ሲያገለግሏት እየተመለከተ ይመሰጥ ነበረ::

የልጅ አምሮቱን የሚረሳው ከእርሷ ጋር ሲሆን ነው:: እንደ አባት አሳደጋት: እንደ እመቤትም ጸጋ ክብር አሰጥታዋለች:: እድሜው መቶ ዓመት በሆነ ጊዜ በቅዱስ ገብርኤል ተበስሮ ዮሐንስን አገኘ:: ለ፱ [9] ወራት የተዘጋ አንደበቱ ሲከፈት "ይትባረክ እግዚአብሔር አምላከ እሥራኤል" ብሎ ትንቢትን ተናገረ::

ሔሮድስ ሕጻኑን ሊገድለው በፈለገ ጊዜም ሕጻኑን ቅዱስ ዮሐንስን ወስዶ በክንፈ ኪሩብ ላይ አስቀመጠውና መልአክ ወደ በርሃ ወሰደው:: ቅዱስ ዘካርያስን ግን በቤተ መቅደሱ መካከል ፸: ፹ [70: 80] ዓመት በንጽሕና ባገለገለበት ቦታ ላይ ገደሉት::

ሥጋውን አምላክ ሰውሮት የፈሰሰ ደሙ እንደ ድንጋይ ረግቶ ሲጮህ ተገኝቷል:: ለ፷፰ [68] ዓመታትም ደሙ ሲፈላ ኑሯል:: በ፸ [70] ዘመን ጥጦስ ቄሣር አይሁድን ሲያጠፋቸው ደሙ ዝም ብሏል:: ይህ ቅዱስ: ጻድቅ: ነቢይና ካህን ስሙ በተጠራ ጊዜ ሲዖል ደንግጣ ነፍሳትን እንደምትሰጥ ሊቃውንት ነግረውናል:: [ማቴ.፳፫፥፴፭] (23:35)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
......................................................

†   🕊   ቅዱስ አሮን ካህን    🕊   †

በቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት የቅዱሱ ካህን የአሮን በትር ሳይተክሏትና ውሃ ሳያጠጧት ለምልማ: አብባ: አፍርታ የተገኘችው በዚህ ቀን ነው:: ዳታን: አቤሮንና ቆሬ ከተከታዮቻቸው ጋር በፈጠሩት ሁከት ምድር ተከፍታ ከዋጠቻቸው በሁዋላ እግዚአብሔር የ፲፪ [12]ቱን ነገደ እሥራኤል በትር ሰብስቦ ሲጸልይበት እንዲያድር ሙሴን አዞት: እንዲሁ ሆነ::

በነጋም ጊዜ ይህቺ ደረቅ የነበረች በትረ አሮን 12 ፍሬ [ለውዝ: ገውዝ: በኩረ ሎሚ] አፍርታ ተገኘች:: [ዘኁ.፲፯፥፩-፲፩] (17:1-11) ለጊዜው ክህነት ከቤተ አሮን እንዳይወጣ ምልክት ሆናለች:: ለፍጻሜው ግን ምሳሌነቷ ለድንግል ማርያም ነው:: እመ ብርሃን የወንድ ዘር ምክንያት ሳይሆናት አምላክን ወልዳ ተገኝታለችና::

" ጸናጽል ዘውስተ ልብሱ ለአሮን ካህን: ወዓዲ በትር እንተ ሠረጸት: ወጸገየት: ወፈረየት" እንዳለ አባ ሕርያቆስ:: [ ቅዳሴ ማርያም ]

የእነዚህ ቅዱሳን ነቢያትና ካህናት አምላክ ደግነታቸውን አስቦ: ከግራ ቁመት: ከገሃነመ እሳትም ይሰውረን:: በረከታቸውንም ያብዛልን::

[ †  መስከረም ፰ [  8 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  ]

፩. ቅዱስ ሙሴ ሊቀ ነቢያት
፪. ቅዱስ ዘካርያስ ካህን (ጻድቅ ነቢይ)
፫. ቅዱስ አሮን ካህን
፬. ቅዱስ ዲማድዮስ ሰማዕት

" ሙሴ ካደገ በሁዋላ የፈርኦን የልጅ ልጅ እንዳይባል በእምነት እምቢ አለ:: ከግብጽም ብዙ ገንዘብ ይልቅ ስለ ክርስቶስ መነቀፍ እጅግ የሚበልጥ ባለጠግነት እንዲሆን አስቧልና:: ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መረጠ:: ብድራቱን ትኩር ብሎ ተመልክቷልና::" [ዕብ.፲፩፥፳፬] (11:24)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]


         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
2024/10/01 07:12:47
Back to Top
HTML Embed Code: