Telegram Web Link
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
"በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"።

      
          #ጳጒሜን ፪ (2) ቀን።

እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት አንዱ ለሆነው ሐዋርያው #ቅዱስ_ጳውሎስ_መልእክት_ለጻፈለት ለከበረ #ለሐዋርያው_ለቅዱስ_ቲቶ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።

                           
#ሐዋርያው_ቅዱስ_ቲቶ፦ የዚህም ቅዱስ ትውልዱ ቀርጤስ ከሚባል አገር ነው። እርሱም ለዮናናውያን ወገን ለሆነ ለአገረ ገዥው እኅት ልጅዋ ነው። ከታናሽነቱም የዮናናውያንን ትምህርትና ፍልስፍና ተምሮ እጅግ አዋቂ ሆነ በጠባዩም ቅን ሥራው ያማረ ለድኆችና ለችግረኞች መራራት የሚወድ ነው። ከሌሊቶችም በአንዲቱ "ቲቶ ሆይ ስለ ነፍስህ ድህነት ተጋደል ይህ ዓለም አይጠቅምህምና" የሚለውን በሕልሙ አየ። ከእንቅልፉም በነቃ ጊዜ ደነገጠ ምን እንደሚሠራም አላወቀም።

ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት በተሰማ ጊዜ ብዙዎች ሰዎችም ተአምራቱን እርስበርሳቸው ተነጋገሩ የአክራጥስ መኰንንም ሰምቶ አደነቀ ዕውነት እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ወይም የሥራይ እንደሆነ ሊያውቅ ሽቶ የሚልከው ብልህ ሰው ፈለገ የእኅቱንም ልጅ ቲቶንን መረጠው ከእርሱ የሚሻል የለምና። ሲልከውም ታላቅና ጥልቅ የሆነ ምርመራ እንዲመረምር አዘዘው።

ቲቶም ከይሁዳ ምድር በደረሰ ጊዜ የመድኃኒታችንን ድንቆች የሆኑ ተአምራቶቹን አየ ሕይወትነት ያላቸው ትምህርቶቹንም ሰማ። ከዮናናውያንም በትምህርታቸውና በሥራቸው መካከል ታላቅ የሆነ መራራቅን አግኝቶ የዮናናውያን ሃይማኖታቸው የቀናች እንዳልሆነች ለይቶ ዐወቀ።

ከዚህም በኋላ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ አመነ፤ ደቀ መዝሙሩም ሁኖ ተከተለው። ወደ እናቱ ወንድም ወደ አገረ ገዥውም መልእክትን ላከ የክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያስተምረውና የሚሠራው ዕውነት እንደሆነ ነገረው።

ጌታችንም ከሰባ ሁለቱ ደቀ መዛሙርቱ ውስጥ የተቆጠረ አደረገው ከዕርገቱም በኋላ ከሐዋርያት ጋር የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተቀብሎ ከእሳቸው ጋር በሀገሮች ሁሉ ዙሮ አስተማረ። ጌታችንም ጳውሎስን ጠርቶ ሐዋርያው በአደረገው ጊዜ ያን ጊዜ ሐዋርያ ጳውሎስን ተከተለው በብዙ አገሮችም ወንጌልን ሰበከ።
የከበረ ቅዱስ ጳውሎስም በሮሜ ከተማ ምስክር ሆኖ ከሞተ በኋላ ቅዱስ ቲቶ ወደ ሀገረ አክራጥስ ተመለሰ ቤተ ክርስቲያንም ሠርቶ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው በዙሪያቸው ላሉ አገሮችም እንዲሁ አደረገ።

ከዚህም በኋላ ሐዋርያዊ አገልግሎቱን ፈጽሞ ወደ ወደደው እግዚአብሔር ጳጒሜን 2 ቀን ሔደ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

                           
"#ሰላም_ለከ_ቲቶ_መስተሳልም። ለእከ ጳውሎስ ዘኮንከ እንበለ ድካም። ከመ ገሠጸከ በቃል ወይቤለከ በሕልም። ተጋደል በእንተ ነፍስከ በገድለ ሃይማኖት ፍጹም። ኢይበቊዓከ ዝንቱ ኃላፊ ዓለም"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጳጒሜን_2

                            
#የዕለቱ_ምስባክ፦ "ቀዳሚሃ ለጥበብ ፈሪሃ እግዚአብሔር። ምክር ሠናይት ለኵሉ ዘይገብራ። ወስብሐቲሁኒ ይነብር ለዓለም"። መዝ 110፥10። የሚነበቡት መልዕክታት ቲቶ 1፥1-11፣ 2ኛ ጴጥ 3፥7-14 እና የሐዋ ሥራ 4፥31-36። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥1-12። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የሐዋርያው የቅዱስ ቲቶ የዕረፍት በዓልና የጾም፣ የጸሎትና የምሕላ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊


[  † እንኳን ለቅዱስ ቲቶ ሐዋርያ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፤ አደረሰን። †  ]

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †


🕊  †   ቅዱስ ቲቶ ሐዋርያ   †   🕊  ]

† የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዝሙር ቅዱስ ቲቶ ከሰባ ሁለቱ አርድእት አንዱ ሲሆን በተወሰነ መንገድም ቢሆን የተዘነጋ ሐዋርያ አይደለም:: በተለይ ደግሞ ቅዱስ ጳውሎስ ከጻፋቸው አሥራ አራት መልእክታት መካከል አንዷ የተላከችው ለዚህ ቅዱስ በመሆኗ ታሪኩ እንኳ ባይነገር ስሙ አይረሳም:: ቅዱስ ጳውሎስም በመልዕክታቱ በጐ ስሙን እየደጋገመ ያነሳዋል::

ለመሆኑ ሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ ማን ነው?

ቅዱስ ቲቶ የተወለደው በ፩ ኛው መቶ ክ/ዘመን እስያ ውስጥ: ቀርጤስ በምትባል ከተማ ነው:: የዘር ሐረጉ ከእሥራኤልም: ከጽርእም [ግሪክ ለማለት ነው::] ይወለዳል:: አካባቢው አምልኮተ እግዚአብሔር የጠፋበት ስለሆነ እሱም: ቤተሰቦቹም የሚያመልኩት ከዋክብትን ነበር::

መዳን በእውቀት ይመስላቸው ስለ ነበር የአካባቢው ሰዎች የግሪክን ፍልስፍና ጠንክረው ይማሩ ነበር:: ቅዱስ ቲቶም በወጣትነቱ ወደ ት/ቤት ገብቶ የግሪክን ፍልሥፍናና የዮናናውያንን ጥበበ ሥጋ ተማረ:: በጥቂት ጊዜም የሁሉ የበላይ ሆነ::

ቅዱሱ በወቅቱ ምንም እውነተኛውን ፈጣሪ አያምልክ እንጂ በጠባዩ እጅግ ቅንና ደግ ነበር:: ምክንያቱን ሳያውቀው ለእኔ ቢጤዎች ያበላ: ያጠጣ: ይንከባከባቸውም ነበር:: እግዚአብሔር ግን የዚህ ቅን ሰው በጐነቱ እንዲሁ እንዲቀር አልወደደምና አንድ ቀን በራዕይ ተገለጠለት::

በራዕይም አንድ ምንነቱን ያልተረዳው ነገር "ቲቶ ሆይ! ስለ ነፍስህ ድኅነት ተጋደል:: ይህ ዓለም ኃላፊ ነው::" ሲለው ሰማ:: ከእንቅልፉ ነቅቶ በእጅጉ ደነገጠ:: የሚያደርገውንም አጣ:: ያናገራቸው ሁሉ ምንም ሊገባቸው አልቻለም::

ለተወሰነ ጊዜም ለጉዳዩ ምላሽ ሳያገኝለት በልቡ እየተመላለሰ ኖረ:: ድንገት ግን በዚያ ሰሞን ከወደ ኢየሩሳሌም አዲስ ዜና ተሰማ:: "ክርስቶስ የሚሉት ኢየሱስ: እርሱም የባሕርይ አምላክ የሆነ ወደ ምድር ወርዶ: ስለ እግዚአብሔር መንግስትም እየሰበከ ነው::" ሲሉ ለቲቶ ነገሩት::

"ሌላስ ምን አያችሁ?" አላቸው:: "በእጆቹ ድውያን ይፈወሳሉ:: ሙታን ይነሳሉ:: እውራን ያያሉ:: ለምጻሞች ይነጻሉ:: ሌሎች ብዙ ተአምራትም እየተደረጉ ነው::" አሉት:: የወቅቱ የሃገረ አክራጥስ መኮንን ፈላስፋ ነበርና ስለ ክርስቶስ ሲሰማ ሊመራመር ወደደ::

እርሱ መሔድ ስላልተቻለው "ብልህ ጥበበኛ ሰው ፈልጉልኝ::" ብሎ ተከታዮችን ቢልካቸው ከቲቶ የተሻለ በአካባቢው አልነበረምና እርሱኑ አመጡት:: መኮንኑ ቲቶን "ነገሩ ትክክል ወይም ስሕተት መሆኑን በጥልቅ መርምረህ ምላሽ አምጣልኝ::" ብሎ ላከው::

ቅዱስ ቲቶም ፈጥኖ ተነስቶ ወደ ኢየሩሳሌም ገሰገሰ:: ወደ ከተማዋ እንደገባም ጌታችንን አፈላልጐ አገኘው::
፩.ጌታችን ክርስቶስ በሥልጣነ ቃሉ ደዌያትን ሲያርቅ: አጋንንትን ሲያሳድዳቸው ተመልክቶ ይህ ሥራ የፍጡር እንዳልሆነ ተረዳ::
፪.ጌታችን የሚያስተምረው ትምሕርት ከግሪክ ፍልሥፍና እጅግ ርቆና መጥቆ አገኘው:: የግሪክ ፍልሥፍና መነሻውም ሆነ መድረሻው ሥጋዊ ነው:: ጌታ ግን በጣዕመ ቃሉ የሚያስተምረው ሰማያዊ: በዚያ ላይ ዘላለማዊ የሆነ ትምሕርት ነው:: በራዕይ "ስለ ነፍስህ ተጋደል::" ያለው ምሥጢር አሁን ተተረጐመለት::

በዚህ ምክንያትም ጊዜ አላጠፋም:: ወዲያውኑ አምኖ ተከታዩ ሆነ:: ጌታም ከሰባ ሁለቱ አርድእት ደመረው:: የአክራጥስ መኮንን "ምነው ዘገየህ?" ቢለው ያየውን ሁሉ ጽፎ: እንደማይመለስም አክሎ ደብዳቤ ላከለት::

ከዚህ በኋላ ቅዱስ ቲቶ ከጌታችን እግር ለሦስት ዓመታት ተምሮ: በበዓለ ሃምሳ መንፈስ ቅዱስን ተቀብሎ: በመላው እስያ ለስምንት ዓመታት ወንጌልን ሰብኳል:: ቅዱስ ጳውሎስ ባመነ ጊዜ ደግሞ የእርሱ ደቀ መዝሙር ሆኖ ለሃያ አምስት ዓመታት አስተምሯል::

ቅዱስ ጳውሎስ ሰማዕት ከሆነ በኋላ ደግሞ ወደ አክራጥስ ተመልሶ: ሕዝቡን አሳምኖና አጥምቆ: ቤተ ክርስቲያንን አንጿል:: ዕድሜው በደረሰ ጊዜም መምሕራንን: ካህናትን ሹሞላቸው: ባርኳቸውም በዚህች ቀን ዐርፏል::

† አምላከ ቅዱስ ቲቶ መልካሙን የሕይወት ምሥጢር ይግለጽልን:: ከሐዋርያውም በረከቱን ያድለን::

🕊

[  † ጳጉሜን ፪ [ 2 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  ]

1.ቅዱስ ቲቶ ሐዋርያ [ከሰባ ሁለቱ አርድእት]

[   † ወርኀዊ በዓላት   ]

-   የለም

† " የእግዚአብሔር ባሪያና የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የሆነ ጳውሎስ. . . መድኃኒታችን እግዚአብሔር እንዳዘዘ: ለእኔ አደራ በተሰጠኝ ስብከት ቃሉን ገለጠ: በሃይማኖት ኅብረት እውነተኛ ለሚሆን ልጄ ቲቶ:: ከእግዚአብሔርም አብ: ከመድኃኒታችንም ከጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ምሕረት: ሰላምም ይሁን::" † [ቲቶ. ፩፥፩]

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
                          †                          

🕊

እንኳን ለቅዱስ ሩፋኤል አመታዊ በአል በሰላም አደረሳችሁ !

🌼   🕊 ጳጉሜ ፫ ቅዱስ ሩፋኤል  🕊  🌼

                              
▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬


" ከከበሩት ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ እኔ ሩፋኤል ነኝ" እንዳለ:: [ጦቢት ፲፪፥፲፫]
                           
💖

ከባህሪው ቅድስና ፍጥረቱን በጸጋ ቅድስና መርጦ የሚለይ እግዚአብሔር አክብሮ እንዲህ ያለ ሰማያዊ ፀጋ ከሰጣቸው ቅዱሳን መላእክት መካከል በስልጣኑ ሊቀ መናብርት [ የመናብርት አለቃ ] የሆነ ፣ በሹመት ፈታሔ ማኅጸን [ ማሕጸን የሚፈታ ] ፣ ከሳቴ እውራን [ የእውራንን ዓይን የሚያበራ ] ፣ ሰዳዴ አጋንንት [ አጋንንትን የሚያባርር ] ፣ ፈዋሴ ድውያን (ድውያንን የሚፈውስ) ፣ አቃቤ ኆኅት [ የምህረትን ደጁ የሚጠብቅ ] ተብሎ የተገለጠ ከሊቃነ መላእክቱ ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል ተከትሎ የሚነሳ መልአክ ራሱን እንዲህ በማለት ገለጠ "የቅዱሳንን ጸሎት ከሚያሳርጉ ወደ ከበረ ወደ ገነነ ወደ እግዚአብሔር ጌትነት ከሚያገቡ ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ" [ጦቢ.፲፪፥፲፭]

ይህ የከበረ ታላቅ መልአክ ስሙ ሩፋኤል የሚለው ከአምላክ ለሰዎች የተሰጠ ፈውስ የሚለውን ይተካል " በሰው ቁስል የተሾመ ከከበሩ ከመላእክት አንዱ ሩፋኤል ነው።" [ሄኖ.፮÷፫]
ይህ መልአክ እንደሌሎቹ ሊቃነ መላእክት ሁሉ የሰው ልጆችን ይጠብቃቸዋል [ዳን.፬÷፲፫ ዘጸ.፳፫÷፳ መዝ. ፺÷፲፩] ያማልዳል ፣ ከፈጣሪ ያስታርቃቸዋል፡፡ [ዘካ.፩÷፲፪] በፈሪሐ እግዚአቤሔር እና በአክብሮተ መላእክት ያሉትን ምዕመናን ያድናቸዋል [ዘፍ.፵፱÷፲፭ መዝ.፫÷፴፯]

"እግዚአብሔር ሃይሉን የሚገልጥበትን ቅጣቱን ሊያሳይ ቢወድ አስቀድሞ መርጦ በወደዳቸው ለይቅርታ የተዘጋጁ የይቅርታ መላእክትን ያመጣል" [ሮሜ.፱÷፳፪]

የወላድ ማኅፀን እንዲፈታ ስለተሾመ አዋላጅ ብትኖርም ባትኖርም ሐኪም ሩፋኤል አይታጣም፡፡ በምጥ ጊዜ ሲጨነቁ ሴቶች ሁሉ የመልአኩን መልክ አንግተው "ማርያም ማርያም" ይላሉ ማየ ጸሎቱን ጠጥተው ቶሎ ፈጥነው ይወልዳሉ፡፡ "ሩፋኤል" እያሉ ደጅ ጠንተው ይማጸኑታል፡፡

ዜና ግብሩን ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ ከተናገረለት በመነሳት በቅዱሳን ላይ ድንቅ የሆነ እግዚአብሔር በመልአኩ አድሮ ያደረጋቸውን ተግባራት አበው የበረከት ምንጭ በሆነ ድርሳኑ ላይ አኑረው የበረከቱ ተካፋይ እንድንሆን ሰጥተውናል፡፡ በጉልህ ሠፍረው ከምናገኛቸው ብዙ ድንቅ ሥራዎች መሀል ጥቂቶቹን እነሆ፦

በሥነ-ስዕሉ የተማጸኑ ፣ በምልጃው ታምነው የጸኑ ቴዎዶስዮስንና ዲዮናስዮስን በገሃድ ተገልጾ ለንግስናና ለጵጵስና ክብር አብቅቷቸዋል፡፡

የንጉስ ቴዎዶስዮስ ልጅም ጻድቁ አኖሬዋስም በፈጣሪው ህግ እየተመራ የሊቀ መናብርቱን መታሰቢያ ቤተ መቅደስ አሳንጾ ሲያስመርቅ ለበለጠ ክብር ልቡን አነቃቅቶ ለታናሽ ወንድሙ ለአርቃዴዋስ የነጋሢነት ስልጣኑን ትቶ መንኖ በስውርና በጽሙና እዲኖር ረድቶታል፡፡

በሊቀጳጳሳት ቴዎፍሎስ ዘመን አባቶች ለሊቀ መናብርቱ ክብር በአሣ አንበሪ ጀርባ ላይ ያሳነጹትን መታሰቢያ ቤተ መቅደስ በወደቡ አጠገብ በእስክንድሪያ ሳለች ጠላት ዲያቢሎስ አነዋውጾ ለምስጋና የታደሙትን ምዕመናን ሊያጠፉ አሣ አንበሪውን ቢያውከው ወደ ሊቀ መናብርቱ ተማጽነው እርዳን ቢሉ ፈጥኖ ደርሶ በበትረ መስቀሉ [ዘንጉ] ገሥጾ ከጥፋት ታድጓቸዋል፡፡

በቅዱስ መጽሐፍም እንደተገለጠው ሣራ ወለተ ራጉኤልን አስማንድዮስ ከተባለው የጭን ጋንኤን ሲታደጋት የጦቢያን አባት የጦቢትን ዓይን አበራለት [መጽሐፍ ጦቢት]፡፡ ከዚህም አልፎ የይስሐቅን እናት ሣራን ፣ የሶምሶንን እናት [እንትኩይን] ምክነታቸውን የቆረጠ ወልዶ ለመሳም ያበቃቸው ይኸው ፈታሔ ማኅጸን የልዑል እግዚአብሔር መልአክተኛ ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡

" ሩፋኤል ሆይ ከላይ ከሰማይ ወርደህ የጻድቃንና የሰማዕታትን ጸሎት የምታሣርግላቸው አንተ ነህ ፡ ሩፉኤል ሆይ የድኩማን ኃይላቸው አንተ ነህና፡፡ ምስጋናዬን ጸሎቴን ወደላይ ታሣርግልኝ ዘንድ በእግዚአብሔር ወልድና በእናቱ በድንግል ማርያም ስም እማልድሃለሁ፡፡"

[  መልክአ ሩፋኤል  ]
                         
🕊
                            
የመልአኩ ጥበቃና የክንፎቹ መጋረድ ከተዋህዶ ምእመናን ጋር ይኑር አሜን።


†                       †                        †
🌼                    🍒                     🌼
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊

[  † እንኳን ለርኅወተ ሰማይ: ለቅዱስ ሩፋኤል: መልከ ጼዴቅ: ዘርዓ ያዕቆብና ሰራጵዮን ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፤ አደረሰን። †  ]

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †


†  🕊    ርኅወተ ሰማይ    🕊   †

† ይህች ዕለት የሰዎች ሁሉ ጸሎት የሚያርግባት: አራተኛው መጋቢ ኮከብ የሚያልፍባት: ለሰው ልጆች ከፈጣሪያቸው ጸጋ በረከት የሚሰጥባት ዕለት ስለሆነች "ርኅወተ ሰማይ-ሰማይ የሚከፈትባት ቀን::" ትባላለች::

አሁን በሰማይ መዘጋት መከፈት ኑሮበት አይደለም:: የሰው ልጆችን ልመና ቅዱሳን መላእክት ያለ ከልካይ የሚያሳርጉበት: አንድም ቅዱስ ሩፋኤል የዓመቱን የጸሎት መዝገብ የሚከፍትበት ቀን ስለሆነ እንዲህ ተባለ እንጂ::

እመቤታችን ድንግል ማርያም ለአጼ ናዖድ እንደ ነገረቻቸው በዚህች ዕለት ሁሉም ቅዱሳን ስለሚታሰቡ: የእግዚአብሔር የምሕረት መዝገቡ ስለሚከፈት: ዕለቷን ክብርት ያሰኛታል:: በቅዱስ ሩፋኤል አበጋዝነት [መሪነት] በዚህች ዕለት ለዓመት የሚበቃ ምሕረት ይገኛል::

ስለዚህም አባቶቻችን በዚህች ሌሊት ሦስት መቶ ስልሳ አምስት አቡነ ዘበሰማያትን ሲጸልዩ ያድራሉ:: በሌላ ወገን ደግሞ የጌታ ዳግም ምጽዓቱ መታሰቢያ እንደ መሆኗ ትልቅ ትኩረትም ይሰጣታል::
ቸሩ ጌታችን ከተከፈተች ገነት ከተነጠፈች ዕረፍት ሁላችንንም ያድርሰን::


†  🕊  ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት  🕊  † 

† ቅዱስ ሩፋኤል በቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት በደረጃው ሦስተኛ ነው:: በመጀመሪያዋ ዕለተ ፍጥረት እግዚአብሔር መቶ ነገደ መላእክትን ፈጥሮ በአሥር ከተማ ሲያኖራቸው የቅዱስ ሩፋኤል ዕድል ፈንታው ራማ ሆነች::

በዚያም "መናብርት" ተብለው ለሚጠሩ አሥሩ ነገድ አለቃ [መሪ] ሆኖ በፈጣሪው ተሹሟል:: በኋላም "መጋብያን" በሚባሉ በሃያ ሦስቱ ነገድ ላይ ሹሞታል:: ይህች ዕለትም በዓለ ሲመቱ ናት::

አንድ ቀን ጌታችን ክርስቶስ በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ ሐዋርያቱ ቅዱስ ሩፋኤልን እንዲያስተዋውቃቸው ለመኑት:: ጌታም ሦስቱን ሊቃናት [ሚካኤል: ገብርኤል እና ሩፋኤል] ይመጡ ዘንድ አዘዛቸው::

ቀጥሎም ቅዱስ ሩፋኤልን "ክብርህን ንገራቸው::" አለው:: እርሱም ለጌታ ሰግዶ ለሐዋርያት ብዙ ምሥጢር ነገራቸው:: በተለይ ስሙን ለሚጠሩ: መታሰቢያውን ለሚያከብሩ የሚደረገውን ጸጋ አብራርቶላቸው ዐረገ::

በመጽሐፈ ጦቢት ላይ ተጽፎ እንደምናገኘው ቅዱሱ መልአክ ሰው [አዛርያን] መስሎ: ጦብያን ለትዳር አብቅቶ: ሣራን አስማንድዮስ ከሚባል ሰይጣን አድኖ: የጦቢትን ዓይን አብርቷል:: በገድላተ ቅዱሳን እንደምናየውም ለብዙ ቅዱሳን ረዳታቸው ሆኖ ገድላቸውን አስፈጽሟል::

ታሪክ እንደሚለው ይህች ቀን ለቅዱስ ሩፋኤል ቅዳሴ ቤቱም ናት:: በ፬ኛው መቶ ክ/ዘመን በቅዱስ ቴዎፍሎስ ዘእስክንድርያ አማካኝነት ቤቱ ታንጿል:: የሚገርመው ደግሞ የታነጸው በዓሣ አንበሪ ጀርባ: ደሴት ላይ ነው:: በመልአኩ አጋዥነትም ለሦስት መቶ ዓመታት አገልግሏል::


† ቅዱስ ሩፋኤል

¤ መስተፍስሒ [ ልቡናን ደስ የሚያሰኝ ]
¤ አቃቤ ሥራይ [ ባለ መድኃኒት ፈዋሽ ]
¤ መዝገበ ጸሎት [ የጸሎት መዝገብ መክፈቻ የተሰጠው ]
¤ ሊቀ መናብርት [ በዙፋን ላይ በክብር የሚቀመጡ መላእክት መሪ ]
¤ ፈታሔ ማኅጸን [ የሰውንም ሆነ የእንስሳትን ማኅጸን የሚፈታ ]
¤ መወልድ [ አዋላጅ: ምጥን የሚያቀል ] ይባላል::
"ለሰብእ ወለእንስሳ ፈታሔ ማኅጸኖሙ አንተ" እንዲል::


†   🕊   ቅዱስ መልከ ጼዴቅ  🕊   †

† ካህኑ መልከ ጼዴቅን ቅዱስ ጳውሎስ "የትውልድ ቁጥር የለውም: ለዘመኑም ጥንትና ፍጻሜ የለውም::" ይለዋል:: [ዕብ.፯፥፫] ሐዋርያው ይህንን ያለው ለወልደ እግዚአብሔር ምሳሌ ሲያደርገው እንጂ ትውልዱ ከነገደ ካም ነው:: ወላጆቹም "ሚልኪ እና ሰሊማ" ይባላሉ::

ገና ከእናቱ ማኅጸን የተመረጠው ቅዱሱ "ካህነ ዓለም: ንጉሠ ሳሌም" ይባላል:: የዛሬ አምስት ሺ አምስት መቶ ዓመት አካባቢ ሴም ባኖረበት ቦታ [በደብረ ቀራንዮ] ለዘላለም ይኖራል:: ካህኑ መልከ ጼዴቅ ከሰው ወገን እጅግ ክቡርም ነው::


†  🕊   አፄ ዘርዓ ያዕቆብ   🕊  † 

† ሃይማኖቱ የቀና ኢትዮጵያዊው ንጉሥ አፄ ዘርዓ ያዕቆብ በኢትዮጵያ በነገሠባቸው ሠላሳ አራት ዓመታት [ከ1426 እስከ 1460 ዓ/ም] ብዙ በጐ ነገሮችን ሠርቷል:: ላለፉት ሰባ ዓመታት ግን አንዳንድ ጥቃቅን ሰብአዊ ስህተቶችን እየነቀሱ ተሐድሶዎቹ ስሙን ሲያጠፉት ኑረዋል::

ዛሬ ዛሬ ደግሞ የእኛ ቤት ሰዎችም ተቀላቅለዋቸዋል::
እነርሱ ያሉትን ይበሉ እንጂ ለእኛ ግን ዘርዓ ያዕቆብ ማለት :-

፩. ጣዖት አምልኮን ከሃገራችን ለማጥፋት ብዙ ሺህ ካህናትን አሰልጥኖ አሰማርቷል::
፪. የኑፋቄ ችግሮችን ለመቅረፍ ጉባኤያትን አዘጋጅቷል::
፫. ከአሥራ አንድ ያላነሱ መጻሕፍትን በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ደርሶ ለአገልግሎት አብቅቷል::
፬. ብዙ መጻሕፍትን ከውጪ አስመጥቶ አስተርጉሟል [በተለይ ተአምረ ማርያምን]
፭. ሰው ሁሉ ለእመ ብርሃንና ለመስቀሉ ፍቅር እንዲገዛ ጥረት አድርጓል
፮. እመቤታችንን በፍጹም ልቡ ከመውደዱ የተነሳ ዛሬ ድረስ በሃገራችን ድንግል ማርያም "የዘርዓ ያዕቆብ እመቤት" እየተባለች ትጠራለች::
፯. ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን አንጾ: ብዙ ሥርዓቶችም በሊቃውንት እንዲሠሩ አድርጐ: ሌሎች ብዙ በጐ ተግባራትንም ፈጽሞ በዚህች ቀን ዐርፏል::
ቤተ ክርስቲያን ስለውለታቸው ዘርዓ ያዕቆብን: እናታቸው ጽዮን ሞገሳን እና አባታቸው ዳዊትን በክብር ታስባለች::


†  🕊  ቅዱስ ሰራጵዮን ዘሰንዱን  🕊  †

† ይህ ቅዱስ እጅግ የበዛ ሃብቱን ለነዳያን አካፍሎ: ወደ ሌላ ሃገር ሔዶ ለባርነት ተሽጧል:: በተሸጠበት ሃገርም በጸሎት ተግቶ ከክህደት ወደ ሃይማኖት መልሷቸዋል:: ክብሩን ሲያውቁበትም በተመሳሳይ ወደ ሌላ ሃገር ሒዶ አሕዛብን አድኗል:: በፍጻሜው ወደ በርሃ ገብቶ በተጋድሎ ኑሮ በዚህች ቀን ዐርፏል::

† አምላከ ቅዱሳን የወዳጆቹን ሁሉ በረከትና ጸጋ ያብዛልን:: ለዓለምም ሰላሙን ይዘዝልን::

🕊

[  † ጳጉሜን ፫ [ 3 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  ]

፩ . ርኅወተ ሰማይ [የሰማይ መከፈት]
፪ . ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት
፫ . ቅዱስ መልከ ጼዴቅ ካህን
፬ . አፄ ዘርዓ ያዕቆብ ንጉሥ [የእመቤታችን ወዳጅ]
፭ . ቅዱስ ሰራጵዮን ዘሰንዱን
፮ . ቅዱስ አኖሬዎስ
፯ . ቅዱስ ቴዎፍሎስ
፰ . አባ ዮሐንስ
፱ . ቅዱስ ጦቢት
፲ . ቅዱሳን ጦብያና ሣራ

[  † ወርኀዊ በዓላት  ]

-  የለም

† " እውነት እውነት እላችኋለሁ:: ሰማይ ሲከፈት: የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ::" † [ዮሐ. ፩፥፶፪]

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]


         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊

[  † እንኳን ለቅዱስ አባ ባይሞን እና ለቅዱስ ሊባርዮስ ሊቅ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፤ አደረሰን። †  ]

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †


 †  🕊  አባ ባይሞን [ ጴሜን ]  🕊

† ይህ ቅዱስ አባት የ፬ [4]ኛው መቶ ክ/ዘ የቤተ ክርስቲያን ፍሬ ሲሆን ተሰምተው በማይጠገቡ መንፈሳዊ ቃላቱ [ምክሮቹ]ና በቅድስና ሕይወቱ ይታወቃል::

ጥንተ ነገሩስ እንደ ምን ነው ቢሉ :-

በተጠቀሰው ዘመን በምድረ ግብጽ የምትኖር አንዲት ደግ ሴት ነበረች:: አምላክ በፈቀደው ጋብቻ ውስጥ ገብታ ሰባት ወንዶች ልጆችን አፈራች:: ሰባቱም ወንድማማቾች ገና ሕፃን እያሉ አባት በመሞቱ እናት ፈተና ውስጥ ገባች::

ነገር ግን ብርቱ ሴት ነበረችና በወዟ ደክማ አሳደገቻቸው:: ሥጋዊ ማሳደጉስ ብዙም አይደንቅም:: ምክንያቱም ሁሉም እናቶች ይህንን ያደርጉታል ተብሎ ይታመናልና:: የዚህች እናት የሚገርመው ግን ሁሉንም ንጹሐን: የተባረኩ: የክርስቶስ ወዳጆች: የቤተ ክርስቲያንም አለኝታዎች እንዲሆኑ አድርጋ ማሳደጓ ነው::

እነዚህ ሰባቱ ወንድማማቾች :-

፩. አብርሃም
፪. ያዕቆብ
፫. ዮሴፍ
፬. ኢዮብ
፭. ዮሐንስ
፮. ላስልዮስ እና
፯. ባይሞን [ጴሜን] ይባላሉ:: ለእነዚህም ዮሐንስ በኩር ሲሆን ባይሞን መቁረጫ ነው::

ሰባቱም ወጣት በሆኑ ጊዜ ወገባቸውን ታጥቀው እናታቸውን ያገለግሉ: ለፈጣሪያቸው ይገዙ ያዙ:: ያየ ሁሉ "ከዓይን ያውጣችሁ::" የሚላቸው: ቡሩካንም ሆኑ:: አንድ ቀን ግን መንፈስ ቅዱስ በሰባቱ ልብ ውስጥ አንድ ቅን ሃሳብን አመጣ:: ሁሉም እንደ አንድ ልብ መካሪ: እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ስለ ምናኔ አወሱ::

ይህንን ዓለም ከነ ኮተቱ ይተውት ዘንድ መርጠዋልና ወደ በርሃ ለመሔድ ተስማሙ:: እናታቸው ምን መንፈሳዊ ብትሆን የትኛዋም እናት ሁሉን ልጆቿን በአንዴ ማጣትን አትፈልግምና አላማከሯትም:: ይልቁኑ እነርሱ ከሔዱ በኋላ እንዳትቸገር የምትታገዝበትን መንገድ አዘጋጅተውላት ተሰወሩ::

ሰባት ልጆቿን በአንዴ ያጣችው እናት ብቻ አይደለችም: ሁሉም አዘነ:: ተፈለጉ: ግን አየኋቸው የሚል ሰው አልተገኘም:: ሰባቱም ቅዱሳን ከቤታቸው እንደ ወጡ ወደ ገዳም ሔደው አንዲት በዓት ተቀበሉ:: ሰባቱም የሚጸልዩ በጋራ: የሚሠሩ: የሚመገቡ: የሚውሉ: የሚተኙም በጋራ ነው::

በአገልግሎታቸውም ሆነ በፍቅራቸው አበውን ደስ አሰኙ:: "እምኩሉ የዓቢ ተፋቅሮ - እርስ በእርስ መዋደድ ከሁሉ ይበልጣል::" እንዲሉ አበው:: ከዘመናት ተጋድሎ በኋላ ግን ዝናቸው ከገዳሙ አልፎ በከተሞች ተሰማ:: ይህንን የሰማችው እናታቸው የእርሷ ልጆች መሆናቸውን በማወቋ ፈጥና ወደ ገዳሙ ገሰገሰች::

"ልያችሁ ልጆቼ?" ስትልም ላከችባቸው:: እነሱ ግን "እናታችን በመንግስተ ሰማያት እንድታይን በዚህ ይቅርብሽ::" አሏት:: ምክንያቱም ሰባቱም የሴትን ፊት ላያዩ ቃል ገብተው ነበርና:: ይህ ለአንድ እናት ከባድ ቢሆንም እርሷ ግን ተረዳቻቸው:: ፈጥናም ወደ ቤቷ ተመለሰች::

ከኮከብ ኮከብ ይበልጣልና [፩ቆሮ.፲፭፥፵፩] (15:41) ከሰባቱ ቅዱሳን ደግሞ ትንሹ አባ ባይሞን የተለየ አባት ሆነ:: ከንጽሕናው: ቅድስናና ትጋቱ ባሻገር ከአንደበቱ የሚወጡ ቃላት ሕይወትነት ያላቸው ሆኑ:: በዘመኑም ከሕፃን እስከ አዋቂ ድረስ ብዙዎች ከመንፈሳዊ ቃላቱ ተጠቅመዋል::

እነዚህ ምክሮቹ ዛሬ ድረስ ለምዕመናንም ሆነ ለመነኮሳት ጣፋጮች ናቸው::
እልፍ አእላፍ ከሆኑ ምክሮቹ እስኪ አንድ አምስቱን እንጥቀስ :-

፩. "ባልንጀራህ በወደቀ ጊዜ በፍጹም ተስፋ አትቁረጥበት:: ይልቅስ አንቃው: አበረታታው: ሸክሙንም አቅልለት እንጂ::"

፪. "ለጥሩ ባልንጀራህ የምታደርገውን ደግነት ለክፉው በእጥፍ አድርግለት:: መድኃኒትን የሚሻ የታመመ ነውና:: አልያ ግን ለበጐው ያደረከው ከንቱ ነው::"

፫. "ባልንጀራህ በበደለ ጊዜ አትናቀው:: ያንተ ተራ በደረሰ ጊዜ ጌታህ ይንቅሃልና::"

፬. "የማንንም ኃጢአት አትግለጥ [አታውራ]:: ካላረፍክ ጌታ ያንተኑ ይገልጥብሃልና::"

፭. "አንደበትህ የተናገረውን ሁሉ ለመሥራት ታገል:: አልያ ውሸታም ትሆናለህ::"

ሰባቱ ቅዱሳን ወንድማማቾች ለብዙ ዓመታት በፍቅርና በተጋድሎ ኑረው በዚህች ቀን ዐርፈዋል::


†  🕊   ቅዱስ ሊባርዮስ ሊቅ   🕊  †

† ሊቁ ተወልዶ ያደገው በአውሮጳ ሮም ውስጥ ሲሆን የታላቁ ሊቅ ቅዱስ አትናቴዎስ ባልንጀራም ነበር:: በቀደመ ሕይወቱ ምሑርና ገዳማዊ በመሆኑ ሊቃውንት የሮም ፓትርያርክ አድርገው ሾሙት:: ዘመኑ አርዮሳውያን የሰለጠኑበት በመሆኑ ምዕመናንን ከተኩላ ለመጠበቅ እንቅልፍን አልተኛም::

የወቅቱ ንጉሥ ታናሹ ቆስጠንጢኖስ እምነቱ አርዮሳዊ በመሆኑ ቅዱሱን ያሰቃየው: ያሳድደውም ነበር:: ለበርካታ ዓመታትም ከመናፍቃንና ከአጋዥ ነገሥታት ጋር ስለ ሃይማኖቱ ተዋግቶ በዚህች ዕለት ዐርፏል::

† የአባቶቻችን አምላክ መፋቀራቸውንና ማስተዋላቸውን ያድለን:: ከበረከታቸውም ያሳትፈን::

🕊

[  † ጳጉሜን ፬ [ 4 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  ]

፩. ቅዱስ አባ ባይሞን [ ጴሜን ]
፪. ስድስቱ ወንድሞቹ [ አብርሃም: ያዕቆብ: ዮሴፍ: ኢዮብ: ላስልዮስና ዮሐንስ ]
፫. ቅዱስ ሊባርዮስ ሊቅ

[  † ወርኀዊ በዓላት  ]

- የለም

† " ለእውነት እየታዘዛችሁ: ግብዝነት ለሌለበት ለወንድማማች መዋደድ ነፍሳችሁን አንጽታችሁ እርስ በእርሳችሁ ከልባችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ:: ዳግመኛ የተወለዳችሁት ከሚጠፋ ዘር አይደለም:: በሕያውና ለዘላለም በሚኖር በእግዚአብሔር ቃል: ከማይጠፋ ዘር ነው እንጂ::" † [፩ጴጥ. ፩፥፳፪]

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊

[  † እንኳን ለታላቁ አባ በርሶማ እና ለቅዱስ አሞጽ ነቢይ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፤ አደረሰን።  ]

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †


†   🕊   ታላቁ አባ በርሶማ   🕊   †

† ታላቁ ገዳማዊ ሰው ቅዱስ በርሶማ ከኋለኛው ዘመን ጻድቃን አንዱ ሲሆን ተወልዶ ያደገውም በግብጽ ምስር(ካይሮ) ውስጥ ነው:: ዘመኑ በ14ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: የታላቁ በርሶማ ወላጆች ክርስቲያኖች ነበሩና ያሳደጉት በሃይማኖትና በምግባር እየኮተኮቱ ነው::

ቅዱሳት መጻሕፍትንም እንዲማር አድርገውት ወጣት በሆነ ጊዜ አንድ ሰሞን ተከታትለው ዐረፉ:: በወቅቱም ስለ ሃብት ክፍፍል ዘመዶቹ ተናገሩት:: ነገር ግን አንድ ጉልበተኛ አጐት ነበረውና ንብረቱን ሁሉ ቀማው:: ቅዱስ በርሶማ በልቡ አሰበ:- "እንዴት ነገ ለሚጠፋ ገንዘብ ፍርድ ቤት እሔዳለሁ?" አለ::

ቀጥሎም ይህችን ዓለም ይተዋት ዘንድ ወሰነ:: ከቤቱም እየዘመረ ወደ በረሃ ገሰገሰ:: "ምንት ይበቁዖ ለሰብእ ለእመ ኩሎ ዓለመ ረብሐ ወነፍሶ ኃጉለ - ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱን ካጐደለ ምን ይረባዋል::" [ማቴ.፲፮፥፳፮] (16:26) እያለም ጉዞውን ቀጠለ:: ልብሱን በመንገድ ለኔ ቢጤዎች ሰጥቶ ራቁቱን በአምስት ኮረብታዎች ውስጥ ተቀመጠ::

በዚያም የቀኑ ሐሩር: የሌሊቱ ቁር [ብርድ] ሲፈራረቅበት ለብዙ ዓመታት ኖረ:: እርሱ ግን ያ ሁሉ መከራ እያለፈበት ደስተኛ ነበር:: ዘወትር የዳዊትን መዝሙር ያለ ማቋረጥ ይዘምራል:: ገድላተ ቅዱሳንን እያነበበ መንፈሳዊ ቅናትን ይቀናል:: ያነበባትንም ነገር በተግባር ይፈጽማል::

ይህ ቅዱስ ስለ ራቁትነቱ እንዳይከፋው ዘወትር ራሱን "በርሶማ ሆይ! ከእውነተኛው ዳኛ ፊት ራቁትህን መቆምህ አይቀርምና የዛሬውን ጊዜአዊ ራቁትነትህን ታገስ" እያለ ይገስጽ ነበር:: እርሱ ለጸሎት ከቆመ የሚቀመጠው ከቀናት በኋላ ነው:: ያለ ዕለተ ሰንበት እህልን አይቀምስም::

ምግቡም የሻገተ እንጀራና ክፍቱን ያደረ ውኃ ነበር:: በእንዲህ ያለ ተጋድሎ እያለ ውዳሴ ከንቱ ስለ በዛበት ሸሽቶ ወደ ምሥር ሔዶ በቅዱስ መርቆሬዎስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ አደረ:: በዚያም እንዳስለመደ ለሠላሳ ዓመታት ተጋደለ::

በቦታው የጉድጓድ ውኃ ነበርና ሁሌ ሌሊት ወደ ውስጥ ሰጥሞ ይጸልይ ነበር:: እንደ ስለት የሚቆራርጠውን ውርጭም ይታገሥ ነበር:: በዚያ አካባቢ ብዙ ሰውና እንስሳትን የፈጀ አንድ ዘንዶ ነበርና በአካባቢው ሰው አያልፍም ነበር::

ታላቁ በርሶማ ግን ወደ ዘንዶው ዋሻ ሔደና ጸለየ:: "ጌታ ሆይ! በስምህ ለሚያምኑ የሰጠሃቸውን ሥልጣን አትንሳኝ?" ብሎ (ማር. 16:18) "በአንበሳና በዘንዶ ላይ ትጫናለህ::" የሚለውን መዝሙር ዘመረ:: [መዝ.፺፥፲፫] (90:13)

ዘንዶውንም "ና ውጣ::" ብሎ አዘዘው:: ወዲያው ወጥቶ ሰገደለት:: የጻድቁ ሰው አገልጋይም ሆነ:: የአካባቢው ሰውም እጅግ ደስ አላቸው:: ብዙ ጊዜም አገልግሏቸዋል:: [በሥዕሉ ላይ የምታዩት እርሱው ነው::]

ታላቁ አባ በርሶማ የሚያርፍበት ቀን በደረሰ ጊዜ ደቀ መዝሙሩን "እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ 'የብርቱ [የእግዚአብሔር] ልጅ' ብሎ ለሚጠራኝ በረድኤት እመጣለታለሁ::" ብሎ: ምላሱን በምላጭ ቆርጦ ጣለውና አሰምቶ ዘመረ::

"እግዚአብሔር ያበርህ ሊተ . . . እግዚአብሔር ያበራልኛል: ያድነኛልም:: ምን ያስፈራኛል::" አለ:: [መዝ.፳፮፥፩] (26:1) ልብ በሉልኝ! የሰው ልጅ ምላስ ከሌለው መዘመርም: መናገርም አይችልም:: ቅዱሳን ግን ሲበቁ ልሳን መንፈሳዊ ይሰጣቸዋል:: ከዚህ በኋላ በትእምርተ መስቀል አማትቦ ዐረፈ::

ፓትርያርኩን አባ ዮሐንስን ጨምሮ ሊቃነ ጳጳሳትና የምስር ሹማምንት ገንዘውት ከበረከቱ ተካፈሉ:: ገድሉ እንዳስቀመጠው በዘመኑ ሁሉ ምንጣፍ ላይ ተኝቶ አያውቅም:: "ማዕከለ ሥጋሁ ወምድር ኢገብረ መንጸፈ" እንዲል:: ያረፈውም በ1340 ዓ/ም ነው::


†  🕊   ቅዱስ አሞጽ ነቢይ   🕊  †

† አሞጽ ማለት "እግዚአብሔር ጽኑዓ ባሕርይ ነው: አንድም እግዚአብሔር ያጸናል::" ማለት ነው:: "ተወዳጅ ሰው" ተብሎም ይተረጐማል:: የነበረው ቅ.ል.ክርስቶስ በስምንት መቶ ዓመት ሲሆን አባቱ ቴና እናቱ ሜስታ ይባላሉ:: ትውልዱም ከነገደ ስምዖን ነው::

በትውፊት ይህ ቅዱስ ነቢይ የነቢዩ ኢሳይያስ አባት ነው የሚሉ ቢኖሩም ሁለቱ አሞጾች የተለያዩ መሆናቸውን ሊቃውንት ይናገራሉ:: ቅዱስ አሞጽ ዘጠኝ ምዕራፎች ባሉት መጽሐፈ ትንቢቱ ስለ ነገረ ድኅነት ብዙ ትንቢቶችን ተናግሯል::

ስለ ሃገራችን ኢትዮጵያም እንዲህ ብሏል :-
"የእሥራኤል ልጆች ሆይ! እናንተ ለእኔ እንደ ኢትዮጵያ ልጆች አይደላችሁምን? ይላል እግዚአብሔር::"
ቅዱሱ ነቢይ ወገኖቹን አብዝቶ ይገስጻቸው ስለ ነበር ተቆጥተው በዚህች ቀን ገድለውታል::

† የቅዱሳን አምላክ አዲሱን ዘመን ቅዱሳኑን አብዝተን የምናስብበት ያድርግልን:: ከበረከታቸውም ያድለን::

🕊

[  † ጳጉሜን ፭ [ 5 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  ]

፩. ታላቁ አባ በርሶማ
፪. ቅዱስ አሞጽ ነቢይ
፫. ቅዱስ ያዕቆብ ዘምስር
፬. አባ መግደር [እግዚአብሔር በጸሎቱ ይማረን]

[  † ወርኀዊ በዓላት  ]

- የለም

† " መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ:: ሩጫውን ጨርሻለሁ:: ሃይማኖቴን ጠብቄአለሁ:: ወደ ፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል:: ይህንም ጻድቅ: ፈራጅ የሆነው ጌታ ያን ቀን ለእኔ ያሰረክባል:: ደግሞም መገለጡን ለሚወዱት ሁሉ እንጂ ለእኔ ብቻ አይደለም::" † [፪ጢሞ. ፬፥፯]

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]


         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
2024/09/27 20:15:26
Back to Top
HTML Embed Code: