Telegram Web Link
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
"በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"።

              #ነሐሴ ፫ (3) ቀን።

እንኳን #በገድል_ለተጠመዱ ስልሳ ክንድ የድንጋይ ምሰሶ ላይ ወጥተው በዚያም ሳይቀመጡ ቆመው እያስተማሩና እየጸለዩ #ለ42_ዓመታት ለተጋደሉ ለታላቁ አባት #ለአባ_ስምዖን_ዘዓምድ_ሶርያዊ ለዕረፍት በዐልና ከመንግሥት ወገን ለሆነች #ለቅድስት_ሶፍያ_ዘሮምና_ለሦስት_ሴት_ደናግል ልጆቿ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዐል በሰላም አደረሰን።

                           
#አባ_ስምዖን_ዘዓምድ_ሶርያዊ፦ ለዚህም ቅዱስ ስድስት ዓመት በሆነው ጊዜ አባቱ የበጎቹ ጠባቂ አደረገው። ወደ ቤተ ክርስቲያንም በመሔድ ሁል ጊዜ ቅዱሳት መጻሕፍትን ይሰማ ነበር የእግዚአብሔርም ቸርነት አነሳሥቶት ወደ አንድ ገዳም ሒዶ መነኰሰ ብዙ ዘመናትም በገድል ተጠምዶ ሲጋደልና ሰውነቱን ሲያስጨንቅ ኖረ።

ከዚህም በኋላ ገመዱ ሥጋውን ቆርጦ እስቲገባ ድረስ በወገቡ ላይ ገመድን አሠረ። ሥጋውም ተልቶ ከእርሱ ክፉ ሽታ ይወጣ ነበር ስለ ክፉ ሽታውም መነኰሳቱ አዘኑ ተጸየፉትም ወደ አበ ምኔቱም ተሰብስበው "ይህን መነኰስ ስምዖንን ከእኛ ዘንድ ካላወጣኸው አለዚያ አንተን ትተን ወደሌላ እንሔዳለን" አሉት እርሱም "ምን አደረገ" አላቸው እነርሱም "ጥራውና አንተ ራስህ እይ" አሉት። ጠርቶትም መጥቶ በፊቱ በቆመ ጊዜ ደም ከመግል ጋራ በእግሮቹ ላይ ሲፈስ አየ አበ ምኔቱንም እጅግ አስጨነቀው። ልብሶቹንም ገልጦ በሥጋው ውስጥ የገባውን ያንን ገመድ አየው አበ ምኔቱም በእርሱ ላይ ተቆጥቶ "ይህን ታደርግ ዘንድ እንዴት ደፈርክ" አለው በታላቅ ድካምም ያንን ገመድ ከሥጋው ውስጥ አወጡት ቍስሉም እስከሚድን መድኃኒት እያደረጉለት ኃምሳ ቀኖች ያህል ኖረ።

ከዚህም በኋላ አበ ምኔቱ እንዲህ አለው "ልጄ ስምዖን ሆይ እንግዲህስ ወደ ፈለግኸው ቦታ ሒድ" ከዚያም ወጥቶ ሔደ በደረቅ ጕድጓድ ውስጥም ገብቶ ከእባቦችና ከጊንጦች ጋራ ኖረ።

ከዚህም በኋላ "አገልጋዩ ስምዖንን ለምን ሰደድከው አሁንም ፈልገህ መልሰው በፍርድ ቀን እርሱ ከአንተ ይሻላልና" ብሎ ሲገሥጸው አበ ምኔቱ ራእይን አየ። አባ ስምዖንንም ከገዳሙ ስለመውጣቱ ገሠጸው። በነጋም ጊዜ አበ ምኔቱ ራእይን እንዳየ ስለ አባ ስምዖንም እንደገሠጸው ለመነኰሳቱ ነገራቸው ወንድሞችም ደንግጠው እጅግ አዘኑ "እስከምታገኙትም ሔዳችሁ በቦታው ሁሉ ፈልጉት" አላቸው ሔደውም ፈለጉት ግን አላገኙትም። ከዚህም በኋላ መብራትን አብርተው ወደ ጕድጓድ ውስጥ ገቡ ያለ መብልና መጠጥም ከእባቦችና ከጊንጦች ጋራ ተቀምጦ አዩት።

ገመድም አውረዱለትና ከዚያ አወጡት በፊቱም ሰግደው "በአንተ ላይ ያደረግነውን በደላችንን ይቅር በለን" አሉት "እኔንም ስለ አሳዘንኳችሁ ይቅር በሉኝ" አላቸው። ከዚህም በኋላ ወደ ገዳማቸው ወሰዱት በብዙ ገድልም ተጠምዶ ሲያገለግል ኖረ።

ከዚህም በኋላ ከዚያ ገዳም በሥውር ወጥቶ ወደ አንዲት ዐለት ቋጥኝ ደረሰ። በእርስዋም ላይ ሳያረፍና ሳይተኛ ስልሳ ቀን ቆመ። ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔር መልአክ ስለ ብዙ ሰዎች ድኅነት እግዚአብሔር እንደ ጠራው ነገረው። ከዚያም ሔዶ ቁመቱ ሠላሳ ክንድ የሚሆን የድንጋይ ምሰሶ አገኘ ድንቅ ተአምራትን እያደረገ በሽተኞችንም እየፈወሰ ወደርሱ የሚመጡትንም እያስተማረ ዐሥራ ሁለት ዓመት በድንጋይ ምሰሶው ላይ ቆመ።

አባቱም ፍልጎት ነበር ግን ሳያየው ሞተ እናቱ ግን ወሬውን ሰምታ ከብዙ ዘመናት በኋላ ወደርሱ መጣች በድንጋይ ምሰሶውም ላይ ቁሞ አገኘችው አይታውም አለቀሰች ከድንጋይ ምሰሶውም በታች ተኛች። ቅዱስ ስምዖንም ጌታችን በጎ ነገርን ያደርግላት ዘንድ ስለርሷ ለመነ ያን ጊዜም እንደተኛች ዐረፈችና ከደንጊያው ምሰሶ በታች ቀበሩዋት።

ሰይጣንም በእርሱ ላይ ቀንቶ እግሩን መታው ከእግሩ ትል እየወደቀ በአንዲት እግሩ ብዙ ዓመታት ኖረ። ከዚህም በኋላ የሽፍቶች አለቃ ወደርሱ መጥቶ ንስሐ ገባ ጥቂት ቀኖችም ኑሮ ዐረፈ በጸሎቱም ሕይወትን ወረሰ። ወደርሱ ስለሚመጡ ብዙ ሕዝቦችም የውኃ ጥማት እንዳያስጨንቃቸው ወደ እግዚአብሔር ለምኖ ከድንጋይ ምሰሶው በታች ውኃን አፈለቀላቸው።

ዳግመኛም ወደ ሌላ ምሰሶ ተዛወረ በእርሱም ላይ እየተጋደለ ሠላሳ ዓመት ኖረ። ብዙዎች አረማውያንንና ከሀድያንን ካስተማራቸውና ወደ ፈጠራቸው እግዚአብሔር ከመለሳቸው በኋላ ክብር ይግባውና ወደ ወደደው ክርስቶስ ሔደ በሰላምም ዐርፎ የዘላለም ሕይወትን ወረሰ።

ከዚህም በኋላ የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አባ ስምዖን እንዳረፈ በሰማ ጊዜ ካህናትን ዲያቆናትንና የአገሩን መኳንንቶች ከእርሱ ጋራ ይዞ የቅዱስ አባ ስምዖን ሥጋው ወዳለበት ደረሰ በታላቅ ክብርም ተሸክመው እየዘመሩና እያመሰገኑ ወደ እስክንድርያ አድርሰው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት ከሥጋውም ድንቆችና ተአምራቶች ታላቅ ፈውስም ተገለጡ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛን በመስተጋድል በአባ ስምዖን ዘአምድ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

                            
#ቅድስት_ሶፍያ_ሦስቱ_ደናግል_ልጆቿ፦ ለዚችም ቅድስት ብዙ ሀብትና ብዙ ጥሪት ነበራት ክብር ይግባውና ስለ ክርስቶስ ፍቅር የክርስቶስን መከራ መስቀል አንሥታ ትሸከም ዘንድ ከሦስት ሴቶች ልጆቿ ጋራ ወደ ሮም ከተማ ሔደች።

ንጉሥ እንድርያሰኖስም ክርስቲያን እንደ ሆነች አውቆ ከልጆቹ ጋራ ወደ አደባባይ አስቀረባትና ስለ ሀገርዋና ስለ ስሟ ጠየቃት እርሷም "የሚቀደመው ስሜ ክርስቲያን ነኝ ወላጆቼ ያውጡልኝ ስም ሶፊያ ነው እኔም በኢጣልያ ባለ ብዙ ወገን ነኝ ክብር ይግባውና በክርስቶስ ፈቃድም ልጆቼን መሥዋዕት አድርጌ ላቀርብ ወደ አገርህ መጣሁ" አለችው። ከዚህም በኋላ የከዳተኛው ንጉሥ ሥቃዩ እንዳያስፈራቸው ልጆቿን አበረታቻቸው።

ምስክርነታቸውንም ፈጽመው ከሞቱ በኋላ ገንዛ ከሮሜ ከተማ ውጭ ቀበረቻቸው። በሦስተኛውም ቀን መታሰቢያቸውን ታደርግ ዘንድ ልጆቿ ወደ ተቀበሩበት ከብዙዎች ከከተማው ሴቶች ጋራ ሔደች እንዲህ ብላም ጸለየች "አክሊላትን የተቀዳጃችሁ የምታምሩ ፍጹማት የሆናችሁ ልጆቼ ሆይ እኔንም ከእናንተ ጋራ ውሰዱኝ" ይህንንም እንዳለች ወዲያውኑ ዐረፈች ከልጆቿም ጋር ተቀበረች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት ሶፍያና በሦስቱ ደናግል ልጆቿ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

                          + + +
"#ሰላም_ለስምዖን_እንተ_ለሐቌሁ_አድንዖ። በኀብለ በቀልት ይቡስ ዘይገምዶ ወይበልዖ። በእንተ ዝንቱ እምደብር ሶበ አበምኔት አውጽኦ። በቃለ ተግሣጽ እግዚአብሔር አውሥኦ። ለገብርየ ስምዖን እንዘ ይብል አግብኦ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የነሐሴ_3

                            + + +
#የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ። ወለገጽኪ ይትመሀለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር። ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሥ፡ሐሴቦን"። መዝ 44፥12-13። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ተሰ 3፥1-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 3፥10-15 እና የሐዋ ሥራ 14፥20-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 18፥9-18። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታች የማርያም ቅዳሴ ነው፡፡ መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።


@sigewe

https://www.tg-me.com/joinchat-AAAAAFGQ22bI0Ij80hYpFA
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
Forwarded from M.A
🕯አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ🕯

🕯"እዌድሰኪ ኦ ድንግል ምልእተ ውዳሴ መጠነ ይክል አፉየ አስተበፅዕ ዕበየኪ ማርያም

ልሳነ ኪሩቤል ኢይክል አብጽሖ ውዳሴኪ ወአፈ ሱራፌል ኢይፌጽም ነጊረ ዕበየኪ ማርያም

ጽበተ ከርሥኪ ሰፍሐ እምርሕበ ሰማይ ወጸዳልኪ አብርሀ እምብርሃነ ፀሓይ አስከሬነ ወርቅ ጽሩይ መዝገበ ባሕርይ ቡርክት አንቲ ማርያም

ውድስት አንቲ በአፈ ነቢያት ወስብሕት በሐዋርያት አክሊለ በረከቱ ለያዕቆብ ወትምክሕተ ቤቱ ለእስራኤል

ሠርጸ መንግሥት ዘእምሥርወ እሴይ ወጽጌ ንጽሕት ዘእምጒንደ ዳዊት ወብኪ ይትሜዐዙ ኵሎሙ ቅዱሳን"🕯

ትርጉም:-

🕯ምስጋናን የተመላሽ ድንግል ሆይ አመሰግንሻለሁ፤ማርያም አንደበቴ እንደሚችል ገናንነትሽን አከብራለሁ።

የኪሩቤል አንደበትም ምስጋናሽን መፈጸም ማድረስ አይችልም ማርያም የሱራፌል አንደበትም ገናንነትሽን ተናግሮ አይፈጽምም።

ከሰማይ ስፋት ይልቅ የማሕፀንሽ ጽበት ሰፋ፤ወጋገንሽም(የፊትሽም ጸዳል) ከፀሓይ ብርሃን ይልቅ በራ፤የጥሩ ወርቅ ሣጥን የዕንቁ መዝገብ ማርያም አንቺ የተባረክሽ ነሽ።

የእስራኤል የቤቱ መመኪያ የያዕቆብ የበረከቱ አክሊል የሆንሽ ድንግል ማርያም በነቢያት አንደበት የተመሰገንሽ ነሽ በሐዋርያት ዘንድም የከበርሽ ነሽ።

ከእሴይ ሥር የተገኘሽ የመንግሥት ቡቃያ ነሽ ከዳዊት ግንድ የተገኘሽ ንጽሕት አበባ ነሽ፤ቅዱሳን ሁሉ በአንቺ ይሻተቱብሻል። 🕯

🕯መጽሐፈ ሰዓታት🕯
#ተወዳጁ_ልጅሽ_እንዲመግበኝ_ትለምኝልኝ_ዘንድ_እማጸንሻለሁ

እመቤቴ ድንግል ማርያም ሆይ እሰግድልሻለሁ። የመድኃኒት እናት ሆይ በመዓልትም በሌሊትም አማላጅ ትሆኝኝ ዘንድ እሰግድልሻለሁ። እመቤቴ ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ ከእርሱ የሚገኘውን ኃይልን ይሰጠኝ ዘንድ ከአንቺ ወደ ተወለደው ልጂሽ እንድትለምኝልኝ እማጸናለሁ። በመወለዱ ድኅነት የተገባሽ ሆነሻልና። በሔዋን ውድቀት ሆነ። አብ በመላእክት አለቃ በቅዱስ ገብርኤል አማካኝነት ሰላምን የላከልሽ እመቤቴ ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ እሰግድልሻለሁ። ሰላምታን ሰጠሽ ሰገደልሽም። ጸጋን የተመላሽ ሆይ እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ነውና ሰላምታ ይገባሻል። እነሆ ትጸንሻለሽ ልጅም ትወልጃለሽ፣ ስሙንም አማኑኤል ትይዋለሽ። የልዑል ኃይል ይጸልልሻል፤ ከአንቺ የሚወለደውም ቅዱስ ነው፤ እርሱም የልዑል ልጅ ይባላል አለሽ።

በተቀደሰው ስሙ ኅሊናዬን ልቡናዬን እንዲቀድስ ትለምኝው ዘንድ እማጸንሻለሁ። ንጽሕት ድንግል ማርያም ሆይ እሰግድልሻለሁ። የሕይወት ቃል ከአንቺ ሰው ይሆን ዘንድ በሥጋ ከአንቺ ይወለድ ዘንድ የተገባሽ የመድኃኒት እናት እመቤታችን ድንግል ማርያም ሆይ እሰግድልሻለሁ። ከአንቺ በመዋሐዱም እኛ ዳንን። እመቤቴ ድንግል ማርያም ሆይ እሰግድልሻለሁ። በእናታቸው ማሕፀን ሕፃናትን የሚስላቸው ከአባቱ እና ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም ሁሉን የፈጠረው በማሕፀንሽ የተቀረጸብሽ የብርሃን እናት ሆይ እሰግድልሻለሁ። ረቂቅ ድንቅ ምሥጢርን ዓለምንም ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣውን እመቤቴ ድንግል ማርያም ሆይ እለምንሻለሁ። በመንፈሳዊ ልደት ይወልደኝ ዘንድ ወደ እርሱ ዓለምና አዳኝ ወደ ሆነች ዕውቀት ከፍ ያደርገኝ ዘንድ ወደ እርሱ እንድትለምኝልኝ እለምንሻለሁ፣ አማጸንሻለሁ።

የሕይወት መገኛ የነገሥታት ንጉሥ የባለሥልጣናቱ ባለሥልጣን የአምላኮችን አምላክ በበረት ያስተኛሽው እመቤቴ ድንግል ማርያም ሆይ እሰግድልሻለሁ። አዳኝ ስለሆነው ስለስምሽ እንዲረዳኝ ትለምኝልኝ ዘንድም ወደ አንቺ እለምናለሁ፤ እማልዳለሁም። በማየቱ አዳምንና ከእርሱ ጋር ያሉትን ሁሉ ነጻ ያወጣውን በክንድሽ የታቀፍሽው እመቤቴ ድንግል ማርያም ሆይ እሰግድልሻለሁ።

በረቂቅ መመልከቱ እንዲመግበኝ ከሰይጣን መሰናክልም እንዲያድነኝ ትለምኝልኝ ዘንድ እለምንሻለሁ፤ እማጸንሽማለሁ። ዓለማትን ሁሉ ለሚመግበው ጡትሽን ያጠባሽው የመድኃኒት እናት እመቤቴ ድንግል ማርያም ሆይ እሰግድልሻለሁ፤ የሰማይ ኃይላት የሚመገቡትም ከእርሱ ነው። ነፍሴን በፈቃዱ ከጸጋው ይመግባት ዘንድ ወደ እርሱ እንድትለምኝልኝ እማጸንሻለሁ።

እመቤቴ ድግል ማርያም ሆይ ተወዳጁ ልጅሽ እንደ ፍጹም ፈቃዱ እንዲመግበኝ በየጊዜው በየሰዐቱ አማላጅ ሁኚኝ። ይህችም ወደ እርሱ የምትለምኝውን ልመና የተመላች መጽሐፍ ናት ። የለመንሁትን ሁሉ እርሱ ያደርግልሻልና። ኃጢአቴን ይቅር ይለኝ ዘንድ ወደ እርሱ እንድትለምኝልኝ እማጸንሻለሁ። ሰላምን ስለሰጠሽ ስለ አብ ከአንቺ ስለተወለደው አንቺንም ስለተዋሐደው ከአንቺም ሰው ስለሆነው ስለወልድ፣ ስለቀደሰሽ፣ ከሦስቱ ቅዱስ ለአንዱ ማደሪያ ለመሆን እስከሚገባሽ ድረስ ስላነጻሽ ስለመንፈስቅዱስም እለምንሻለሁ። አገልጋይሽን ተወዳጁ ልጅሽ እንዲመግበኝ ትለምኝልኝ ዘንድ እማጸንሻለሁ። ለዘለዓለሙ አሜን።

#ቅዱስ_ባስልዮስ_ዘቂሳርያ
(Deacon Birhanu Admass የተረጎመው)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊

†  እንኳን ለጻድቅ ንጉሥ ሕዝቅያስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፤ አደረሰን። †

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን ! †


†  🕊   ቅዱስ ሕዝቅያስ   🕊   †

† ቅዱስ መጽሐፍ እንደ ነገረን ከመድኃኒታችን ክርስቶስ ልደት ሰባት መቶ ዓመታት በፊት ሕዝቅያስ የሚባል ንጉሥ በይሁዳ ላይ ነግሦ ነበር:: ደጋጉ ዳዊትና ሰሎሞን ካረፉ በኋላ የሕዝቅያስን ያክል ቅን እና የእግዚአብሔር ሰው በእሥራኤል ላይ አልነገሰም:: ንጉሡ ጣዖት አምልኮን ነቃቅሎ አጥፍቶ ሕዝቡ እግዚአብሔርን ብቻ እንዲያመልክ አድርጐም ነበር::

ነገር ግን ቅዱስ ሕዝቅያስ በነገሠ በ፲፬ [14] ኛው ዓመት የአሕዛብ [የአሦር] ንጉሥ ሰናክሬም በጠላትነት ተነሳበት:: ወደ አካባቢውም መጥቶ: ከቦ አስጨነቀው:: ሰናክሬም በጦር እጅግ ኃይለኛ ነበር:: በዚያውም ላይ ጦር የሚመዙ ከመቶ ሰማንያ አምስት ሺ በላይ ብርቱ ተዋጊዎች ነበሩትና ሕዝቅያስ እንደማይችለው ተረድቶ መልእክተኛ ላከበት::

"እገብርልሃለሁ: የፈለግከውንም እሰጥሃለሁ:: ነገር ግን ሃገሬን አታጥፋ:: ኢየሩሳሌምን አታቃጥል: ሕዝቤንም አትግደል" በሚል ለመነው:: እጅ መንሻ ግብሩንም ከከተማዋ የተገኘውን ወርቅና ብር ሁሉ ጭኖ ላከለት::

ሰናክሬም ግን ሰይጣን ያደረበት ነውና የሕዝቅያስን ልመና ወደ ጐን ብሎ የእሥራኤልን አምላክ: ቅዱስ ስሙንም ተገዳደረ:: ለሕዝቅያስም "ከእኔ እጅ የሚያድንህ ማነው? ሕዝቡንም እግዚአብሔር ያድናል ብለህ አታታልላቸው" ሲል ላከበት:: ቅዱስ ሕዝቅያስ በዚህ ጊዜ የፈጣሪው ስም ሲቃለል ሰምቷልና ፈጽሞ አዘነ::

መልእክተኞችን ወደ ነቢዩ ቅዱስ ኢሳይያስ ልኮ እርሱ ወደ ቤተ መቅደስ ገባ:: በእግዚአብሔር ፊት ልብሱን ቀድዶ ማቅ ለበሰ:: ስለ ኢየሩሳሌምና ሕዝቡም ፈጽሞ አለቀሰ::

በዚህ ጊዜ እግዚአብሔር የሰናክሬምን መገዳደርና የሕዝቅያስን ልመና ሰምቷልና በኢሳይያስ አንደበት እንዲሕ አለ :- "ስለ ባሪያዬ ስለ ዳዊት ከተማዋን አድናታለሁ::"

በዚያች ሌሊትም ድንቅ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ከሰማያት በግርማ ወረደ:: ወደ ሰናክሬም የጦር ሠፈር ደርሶ አንድ ጊዜ የእሳት ሰይፉን መዝዞ ቢያሳያቸው ከአሕዛብ ሠራዊት መቶ ሰማንያ አምስት ሺ ኃያላን እንደ ቅጠል ረገፉ:: በለኪሶ የነበረው ሰናክሬም በጧት ቢነሳ ሠራዊቱ ሁሉ ወደ አስከሬን ክምር ተቀይሯል::

በድንጋጤ ወደ ነነዌ ሒዶ ወደ ጣዖት ቤቱ ሲገባ የራሱ ልጆች [አድራማሌክና ሳራሳር] ገደሉት:: ትዕቢተኛው ሰናክሬም ለአሕዛብ ሁሉ መዘባበቻ ሆነ:: ቅዱስ ሕዝቅያስ ግን በፈጣሪው ታምኗልና ቅዱስ ሚካኤል ሞገስ ሆኖት የዓለም ነገሥታት ሁሉ ፈሩት:: [፩ነገ.፲፰፥፲፫ ፣ ፲፱፥፩] (18:13, 19:1)

ቅዱስ ሕዝቅያስ የነሐስ እባቡን በማጥፋቱ: ሕዝቡን ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር በመመለሱ ቢደነቅም ሰው ነውና አንዲት ጥፋት አጠፋ:: በዘመኑ ታላቁ ነቢይ ልዑለ ቃል ኢሳይያስ ነበረና ሐረገ ትንቢትን ያፈስ ነበር:: ከተናገራቸው ትንቢቶችም አንዱ "ድንግል ትጸንሳለች: ወንድ ልጅም ትወልዳለች" የሚል ነበር:: [ኢሳ.፯፥፲፬] (7:14)

በወቅቱ የነበሩ አንዳንድ ክፉ መካሪዎች ቀርበው ንጉሡን በውዳሴ ከንቱ ጠለፉት:: "ንጉሥ ሆይ ! ሺህ ዓመት ንገሥ:: እንዳንተ ያለ ማንም የለም:: ነቢዩ የተናገረው ትንቢትም እኮ ላንተ ነው:: "ድንግል" የተባለች ኢየሩሳሌም ስትሆን "ወልድ-ወንድ ልጅ" የተባልክ ደግሞ አንተ ነህ" አሉት::

ይሕንን ጠማማ ትርጉም እህ ብሎ የሰማቸው ቅዱስ ሕዝቅያስ አልወቀሳቸውም:: ይልቁኑ ልቡ ወደ እነሱ አዘነበለ እንጂ:: በዚህ ምክንያት እግዚአብሔር ተቆጥቶ ኢሳይያስን ላከው:: ነቢዩም በቀጥታ መጥቶ ንጉሡን አለው :- "ትሞታለህ እንጂ አትተርፍምና ቤትህን ሥራ::"

ወዲያውኑ ሕዝቅያስ ታመመ: ደከመ:: ነገር ግን ፊቱን ወደ ቤተ መቅደስ አዙሮ ሊያዝን: ሊተክዝም ጀመረ:: አባቶቻችን ለየት የሚያደርጋቸው ይኼ ነው:: በቅድስና ኑረው: ሰው ናቸውና ይሳሳታሉ:: ነገር ግን ንጹሕና ፍጹም ንስሐን ከማቅረብ አያቋርጡም::

ንጉሡ ቅዱስ ሕዝቅያስ ወደ ፈጣሪ :- "ጌታ ሆይ ! እንደ ቸርነትህ በፊትህ በቅን መንገድ መሔዴን አስብና ይቅር በለኝ" ሲል ተማጸነ:: ይህ ሲሆን ቅዱስ ኢሳይያስ ገና ከንጉሡ አካባቢ አልራቀም ነበርና የእግዚአብሔር ቃል ወደ እርሱ መጣ::

ሕዝቅያስን በለው :- " ጸሎትህን ሰምቼ: ስለ ባለሟሌ ስለ ዳዊት ብዬ ምሬሐለሁ:: በዘመንህም ላይ አሥራ አምስት ዓመታትን ጨምሬልሃለሁ በለው" አለው:: ነቢዩም ወደ ንጉሡ ተመልሶ ይሕንኑ ነግሮ "እስከ ሦስት ቀን ድረስ ወደ ቤተ መቅደስ ድነህ ትመለሳለህ" አለው::

ቅዱስ ሕዝቅያስ "ይሕ እንደሚደረግ በምን አውቃለሁ?" አለው:: [ተጠራጥሮ ግን አይደለም: ድንቅ ተአምር ይገለጥ ዘንድ ነው እንጂ] ኢሳይያስም ፀሐይን ዓለም እያየ አሥር መዓርጋትን ወደ ኋላ መለሳት:: በወቅቱ ይህ ተአምር በመላው ዓለም ታይቶ: ተሰምቶም ነበርና ሕዝቅያስ ከፍ ከፍ አለ::

በቅን የሔደ: እግዚአብሔርም የወደደው እንዲህ ነው:: የዓለም ነገሥታት ሁሉ ለሕዝቅያስ አዘነበሉ: ገበሩለትም:: ለእርሱ ጌታ ድንቅ ነገርን አድርጐለታልና::

ቅዱስ ሕዝቅያስ በተጨመሩለት ዘመናት ሁሉ እግዚአብሔርን አመለከ:: በፊቱም በቅን ተጓዘ:: ከክርስቶስ የዘር ሐረግም በቀጥታ ተቆጠረ:: [ማቴ.፩፥፲] (1:10) ለአሥራ አምስት ዓመታት ሕዝቡን አስተዳድሮ በዚህች ቀን እድሜ ጠግቦ ዐርፏል:: በእርሱ ዙፋን ላይም ልጁ ምናሴ ተተክቷል::


†  🕊   አባ ማቴዎስ ገዳማዊ   🕊   †

† እኒህ ቅዱስ ሰው በ፬ [4] ኛው መቶ ክ/ዘ ፋርስ አካባቢ የነበሩ ጻድቅ ናቸው:: በወቅቱ ምንኩስና በአካባቢው ባለመስፋፋቱ ወደ ዱር እየወጡ የሚኖሩ አበው ነበሩና አባ ማቴዎስ አንዱ ናቸው:: እርሳቸው በበርሃ ልብሳቸው አልቆ አካላቸው የሚሸፈነው በጸጉራቸው ነበር::

የአሦር ንጉሥ የሰናክሬም ልጅ መርምሕናምን [እጅግ ታላቅ ሰማዕት ነው] ያሳመኑትና ያጠመቁት እርሳቸው ናቸው:: እኅቱን ሣራንም ከለምጿ አንጽተው ወደ ክርስትና መልሰዋል:: በዚህ ምክንያትም የፋርስ አውራጃ የሆነችው አሦር በሙሉ የክርስቲያኖች ቤት ሆናለች:: አባ ማቴዎስ ከዘመናት ተጋድሎ በኋላ በዚህች ቀን ዐርፈዋል::

† አምላከ ቅዱሳን እድሜ ለንስሐ: ዘመን ለፍስሃ አይንሳን:: የጻድቃኑ በረከትም ይደርብን::

🕊 

[   † ነሐሴ ፬ [ 4 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት   ]

፩. ቅዱስ ሕዝቅያስ ጻድቅ [ ንጉሠ ይሁዳ ]
፪. አባ ማቴዎስ ገዳማዊ
፫. ቅዱስ ዳዊት ሰማዕት

[  † ወርኀዊ በዓላት   ]

፩. ቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ [ወንጌላዊው]
፪. ቅዱስ እንድርያስ ሐዋርያ
፫. ቅድስት ሶፍያ ሰማዕት
፬. ቅዱስ ዮሐንስ ዘሐራቅሊ [ሰማዕት]

† " አቤቱ በኃይልህ ንጉሥ ደስ ይለዋል:: በማዳንህ እጅግ ሐሴትን ያደርጋል:: የልቡን ፈቃድ ሰጠኸው:: የከንፈሩንም ልመና አልከለከልኸውም:: በበጐ በረከት ደርሰህለታልና:: ከከበረ ዕንቁ የሆነ ዘውድን በራሱ ላይ አኖርህ:: ሕይወትን ለመነህ ሰጠኸውም:: ለረጅም ዘመን ለዘላለሙ:: በማዳንህ ክብሩ ታላቅ ነው::" † [መዝ. ፳፥፩-፭]

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]


         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
"በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"።

               #ነሐሴ ፬ (4) ቀን።

እንኳን #ከዳዊት_ዘር_ለሆነ ለአካዝ ልጅ ንስሃ በመግባቱ በእድሜ ላይ 15 ዓመት ለተጨመረለት #ለንጉሥ_ቅዱስ_ሕዝቅያስና እንደ በግ የጸጉር ልብስ ለብሶ በበረሃ ለሚኖር ሰማዕቱ #ቅዱስ_መርምኅናምን ላሳመነና እህቱን ሣራንም ከለምፅዋ ላነፃት ለአባታችን #አባ_ማቴዎስ_ለዕረፍታቸው_በዐል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከከበሩ #ዳዊትና_ወንድሞቹና ከግብጽ ደቡብ ስንካር ከሚባል አገር በሰማዕትነት ከዐረፈ #ከቅዱስ_ፊልጶስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።

                         

                             
#ቅዱስ_ንጉሥ_ሕዝቅያስ፦ ይህ ንጉሥ ከዳዊት ዘር የአካዝ ልጅ ነው። ከጻድቁ ንጉሥ ከዳዊት በኋላ እንደ ሕዝቅያስ ያለ በእስራኤል ውስጥ አልተሾመም ከዚህ ጻድቅ ንጉሥ በቀር ሁሉም ጣዖትን አምልከዋልና መሠዊያም ሠርተዋልና።

እርሱም በነገሠ ጊዜ ጣዖታትን ሰበረ መሠዊያቸውንም አፈረሰ ከነሐስ የተሠራውንም እባብ ቆራረጠ የእስራኤል ልጆች አምልከውት ነበርና እግዚአብሔርም ዘመነ መንግሥቱን እጅግ አሳመለት በጎ ነገርንም ሁሉ ሰጠው።

ሕዝቅያስም በነገሠ በዐሥራ አራተኛው ዘመን የፋርስ ንጉሥ ሰናክሬም መጥቶ ኢየሩሳሌምን ከበባት ይህም ሰናክሬም በዘመኑ እንደርሱ ያለ የሌለ ኃይለኛ ብርቱ የምድር ነገሥታት ሁሉ የፈሩትና የታዘዙለት ነው። ሕዝቅያስም ከእርሱ ግርማ የተነሣ ፈርቶ አገሩን እንዳያጠፋ ብዙ ወርቅና ብር እጅ መንሻ ላከለት ሰናክሬምም ደስ ብሎት ምንም ምን አልተቀበለም በእርሱ ላይና በልዑል እግዚአብሔር ላይ ተቆጥቶ "እግዚአብሔር ከእኔ እጅ ሊያድናችሁ አይችልም " በማለት የስድብ ቃል ላከ እንጂ።

ሁለተኛም በልዑል ስም ላይ ስድብና ቊጣ የተጻፈበትን ደብዳቤ ላከ ሕዝቅያስም በሰማ ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ቤት ገብቶ አለቀሰ ልብሱንም ቀዶ ማቅ ለበሰ እንዲህም ብሎ ጸለየ "አቤቱ የእስራኤል አምላክ በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ አንተም ብቻህን ዓለም መንግሥታት ላይ ንጉሥ የሆንክ አንተም ሰማይና ምድርን የፈጠርህ ልመናዬን አድምጥ። ዐይኖችህን ገልጠህ ተመልከት ሕያው እግዚአብሔር አንተን እያቃለለ ሰናክሬም የላከውን ቃሉን ስማ"።

ከዚህም በኋላ ንጉሥ ሕዝቅያስ የፋርስ ንጉሥ ሰናክሬም የተናገረውን እንዲነግሩትና ስለርሱና ስለ ሕዝቡ ይጸልይ ዘንድ ወደ ኢሳይያስ መልእክተኞችን ላከ። ኢሳይያስም ከእግዚአብሔር ቃልን ተቀብሎ እንዲህ ብሎ መለሰለት "ልብህን አጽና አትፍራ በዓለሙ ሁሉ እንደርሱ ያለ ያልተማ ዕፁብ ድንቅ የሆነ ሥራ በሰናክሬም ላይ ሊሠራ እግዚአብሔር አለውና"።

ከዚህም በኋላ እግዚአብሔር የላከው መልአክ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ ከፋርስ ሠራዊት መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ ሰዎችን ገደለ የለኪሶም ሰዎች ሲነጋ በተነሡ ጊዜ የሞቱትን ሰዎች ሬሳ ሁሉ አገኙ የተረፉትም ከንጉሣቸው ጋራ ሸሽተው ነነዌ አገር ገቡ። ሰናክሬምም ሊጸልይ ወደ ጣዖቱ ቤት በገባ ጊዜ ልጆቹ አድራማሌክና ሶርሶር በሰይፍ መትተው ገደሉት። ሕዝቅያስም ከሰናክሬም እጅ ድኖ የተመሰገነ እግዚአብሔርን አመሰገነው።

በዚያም ወራት ሕዝቅያስ ታመመ ለሞትም ደረሰ የአሞፅ ልጅ ኢሳይያስም ወደርሱ መጥቶ "እግዚአብሔር እንዲህ አለ ትሞታለህ እንጂ አትድንም ቤትህን ሥራ" አለው። ሕዝቅያስም ፊቱን ወደግድግዳው መልሶ ወደ እግዚአብሔር ለመነ እያመሰገነውም እንዲህ አለ "አቤቱ በቀና ልቡና በዕውነት ሥራ በፊትህ ጸንቼ እንደኖርኩ ፈቃድህንም እንደፈጸምሁ አስብ" ብሎ ሕዝቅያስ ፈጽሞ ጽኑዕ ልቅሶን አለቀሰ።

ኢሳይያስም ወደ መካከለኛው ዐፀድ ደረሰ እግዚአብሔርም እንዲህ ብሎ ተናገረው "ሒደህ ለወገኖቼ ንጉሥ ለሕዝቅያስ ያባትህ የዳዊት ፈጣሪ እግዚአብሔር እንዲህ አለ በለው። ጸሎትህን ሰማሁ ዕንባህንም አየሁ እነሆ እኔ አድንሃለሁ እስከ ሦስት ቀንም ወደ እግዚአብሔር ቤት ትመጣለህ። በዘመኖችህም ላይ ዐሥራ አምስት ዓመት ጨምሬልሃለሁ ከፋርስ ንጉሥ እጅም አድንሃለሁ ይቺንም አገር ስለ እኔና ስለ ባላሟሌ ዳዊት አጽንቼ እጠብቃታለሁ"።

ሕዝቅያስም ኢሳይያስን እንዲህ አለው "እግዚአብሔር እንደሚያድነኝ እስከ ሦስት ቀን ወደ እግዚአብሔር ቤት ለመውጣቴ ምልክት ምንድ ነው"። ኢሳይያስም እንዲህ አለው "የተናገረውን ቃል ያደርግ ዘንድ ከእግዚአብሔር የተገኘ ምልክቱ ይህ ነው አነሆ ጥላው ወደ ዐሥረኛው እርከን ይወርዳል። ወደ ዐሥረኛው እርከን ቢመለስ ምልክቱ ይህ ነው"። ሕዝያስም "እንዲህ አይደለም የጥላው ወደ ዐሥረኛ እርከ መመለስ ቀላል ነው። መመለስስ ከሆነ ፀሐይ ወደ ዐሥረኛው እርከን ይመለስ" አለ። ኢሳያስም ወደ እግዚአብሔር ጮኸ ፀሐይም ዐሥሩን እርከን ተመለሰ።

ሕዝቅያስንም የምድር ነገሥታት ሁሉ ፈሩት እጅ መንሻም አገቡለት የእግዚአብሔር ኃይል ከእርሱ ጋራ እንዳለ አውቀዋልና። በመንበረ መንግሥቱም ሃያ ዘጠኝ ዓመት ነግሦ ኖረ። እግዚአብሔርን አገልግሎ ነሐሴ 4 ቀን በሰላም ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በንጉሥ ቅዱስ ሕዝቅያስ በጸሎቱ ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

                              
በዚችም ቀን እንደ በግ የደጒር ልብስ ለብሶ በበረሃ የሚኖር #አባ_ማቴዎስ ዐረፈ። እርሱም መርኅናምን ያሳመነው ሣራንም ከለምፅዋ ያነፃት ነው። የአባ ማቴዎስ በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የነሐሴ 4 ስንክሳር።

                             
"#ሰላም_ለሕዝቅያስ_ዘጸለየ_በሕቁ። ዘተወሰከ ዘመኑ ወፈድፈደ እምኊልቁ። እመኒ ሶቤሃ ተዐየርዋ ለድድቁ። በእደ መልአክ ሠራዊት ፋርስ ኀልቁ። ወለመልኮሙ ቀተልዎ ደቁ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የነሐሴ_4

                            
#የዕለቱ_ምስባክ፦ "እግዚኦ በኃይልከ ይትፌሣሕ ንጉሥ። ወብዙኀ ይትኀሠይ በአድኅኖትከ። ፍትወተ ነፍሱ ወሀብኮ"። መዝ 20፥1-2። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 12፥16-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 5፥6-12 እና የሐዋ ሥራ 17፥23-28። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 14፥31-35። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታች የማርያም ቅዳሴ ነው፡፡ መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊

† እንኩዋን ለጻድቃን ቅዱሳን አባ_አብርሃም : ቅዱስ ዮሐንስ እና አባ ፊልዾስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ †

🕊 አባ አብርሃም ክቡር ገዳማዊ

ጻድቁ ግብጻዊ ሲሆን በ፬ኛው መቶ ክ/ዘ ከተነሱ ከዋክብት አንዱ ነው:: ክርስቲያን ወላጆቹ በሥርዓት አሳድገው "ሚስት አግባ" አሉት:: እሺ እንዳይላቸው ከልጅነቱ ጀምሮ የተመኘው ምናኔ ሊቀርበት ሆነ:: እንቢ እንዳይላቸው ደግሞ ወላጆቹ ያዝናሉና የልቡን በልቡ ይዞ "እሺ" አላቸው::

ሠርግ ተደግሶ: ተክሊል ተደርሶ: ከአንዲት ክርስቲያን ጋር አጋቡት:: በጋብቻው ማግስት ግን ከነ ድንግልናው ጠፍቶ በርሃ ገባ:: በዚያም አንዲት በዓት አዘጋጅቶ ፈቃደ ሥጋውን እየቀጣ: ፈቃደ ነፍሱን እያለመለመ ለ፲ ዓመታት ተቀመጠ::

በነዚያ ሁሉ ዘመናት የሞቀ አልለበሰም: የላመ የጣመ ነገር አልበላም:: የፀሐይ ብርሃን እንኩዋ አልተመለከተም:: በዚያ ወራትም ወሬ ነጋሪ ወደ በዓቱ መጥቶ "ወላጆችህ ዐረፉ:: በቤት ውስጥ ከ፮ ዓመት እህትህ ከማርያ በቀር ማንም የለምና የወላጆችህን ሃብት ውረስ" አለው::

አባ አብርሃም የሚያደርገውን ያውቃልና ከበርሃ ወጥቶ ወደ ሃገር ቤት ሔደ:: ትንሽ እህቱን [፮  ዓመቷ ነበር] ለቤተ ዘመድ አደራ ሰጥቶ: ሃብት ንብረቱን አንድ ሳያስቀር ለነዳያን በትኖ:ወደ በዓቱ ተመለሰ:: በዚያም እንዳስለመደ በጾምና ጸሎት ተወስኖ ለ፲ ዓመታት ቆየ::

ተጋድሎ በጀመረ በ፳ ዓመቱ እግዚአብሔር ለሌላ አገልግሎት ጠራው:: የግብጽ ሊቀ ዻዻስ አባ አብርሃምን አስመጥቶ ቅስናን ሾመውና "ሒደህ ወንጌልን ስበክ" አለው:: ችግሩ እርሱ የተላከባት ሃገር አንድም ክርስቲያን የሌለባት ከመሆኗ በባሰ እጅግ ጨካኝ ናቸው::

ማንም ደፍሮ በዚያ ሃገር ውስጥ ነገረ እግዚአብሔርን የሚናገር ሰው አልነበረም:: አባ አብርሃም ወደ ሃገር ገብቶ ወንጌልን ቢሰብክላቸው እንደ ልማዳቸው መሬት ላይ ጥለው ደበደቡት: አጥንቶቹንም ሰባበሩት:: ሞቷል ብለው ከከተማ ውጪም ጣሉት::

እርሱ ግን በፈጣሪው ኃይል ጸንቶ ተነሳ:: ማስተማሩ ብቻውን መፍትሔ እንደማይሆን ተረድቷልና ስለ እነሱ ተግቶ ይጸልይ ጀመር:: አሕዛብ ጠዋት ቢመጡ በከተማዋ መሐል ላይ ሲጸልይ አገኙት:: ስለ ተናደዱ ድጋሚ አካሉን በዱላ ሰባብረው እየጐተቱ ከከተማ አስወጡት:: በዚያም ከነ ሕይወቱ ቀበሩት::

ነገር ግን ጠዋት ሲመለሱ እዛችው ቦታ ላይ ሲጸልይ አገኙት:: ይሕ የሚደረገው ለእነርሱ ድኅነት መሆኑን አልተረዱምና እነርሱ በየቀኑ እየደበደቡና እያሰቃዩት እርሱ ስለ እነሱ እየጸለየ ፲ ዓመታት አለፉ:: ቅዱሳን ተስፋ አይቆርጡምና በመጨረሻው ተሳካለት::

የቅዱሱ የዘመናት ጸሎት ፍሬ አፍርቶ እግዚአብሔር በአሕዛብ ልቡና ያደሩ አጋንንትን አራቀለት:: አንድ ቀን ጠዋት የሃገሩ ሕዝብ ሁሉ [ወንዱ: ሴቱ: ትልቁ: ትንሹ] ወደ ጻድቁ መጸለያ መጡ:: ለእርሱስ የጠብ መስሎት ነበር:: እነርሱ ግን በአንድነት በፊቱ ተንበርክከው ሰገዱ:: ይቅር እንዲላቸውም ለመኑት::

ቅዱሱ ይሕንን ሲመለከት ሐሴትን አደረገ:: ሁሉንም በስመ ሥላሴ አጥምቆ ክርስቲያን አደረጋቸው:: አብያተ ክርስቲያናትንም አነጸላቸው:: በሁዋላ ግን በጣም ሲወዱትና ሲያከብሩት ተመልክቷልና ከውዳሴ ከንቱ [ስብሐት ብጡል] መለየት ፈለገ:: ፈጣሪንም በቸርነቱ እንዲጠብቃቸው ለምኖ: በሌሊት ጠፍቶ ወደ ነበረበት በርሃ ገባ::

እርሱ በበርሃ ሁኖ ስለ ትንሽ እህቱ ማርያ ያስብ ነበርና አስጠራት:: "ምን ትፈልጊያለሽ?" አላት:: እርሷም "እንዳንተ መሆን" ስላለችው አስተምሮ: ፈትኖ አመነኮሳት:: ለጥቂት ዓመታት በሥርዓት ከኖረች በሁዋላ ግን ችግር ተፈጠረ::

ከአንድ መነኩሴ ጋር በነበራት ያልተገባ ቅርርብ የዝሙት ፍላጐታቸውን መቆጣጠር ባለመቻላቸው በኃጢአት ወደቁ:: በዚህ ተስፋ ቆርጠው ፪ቱም ቆባቸውን ጥለው ከተማ ገቡ:: ይልቁኑ እርሷ [ማርያ] ሴተኛ አዳሪ ሆነች::

በዚያ ሰሞን ቅዱሱ አብርሃም ራዕይን ያያል:: ትልቅ ዘንዶ አንዲት ርግብን ሲውጣት: መልሶም ሲተፋት አይቶ እሕቱ መሆኗን ተረዳ:: ወዲያው ጥሩ ልብስና ፈረስ ተውሶ ተነሳና ወደ ከተማ ገባ:: የጦር መኮንን መስሎ እህቱ ቤት ገባ::

ሸሽታ እንዳታመልጠው ቤቱን ዘጋና ራሱን ገለጠላት:: ደንግጣ እንደ በድን ብትሆንም እርሱ አረጋጋት:: "እህቴ! ንስሃ ግቢ: አምላክ ይራራልሻል" አላት:: ልቧ ወደ ምክሩ አዘንብሏልና የእህቱን ነፍስ ማርኮ ወደ ገዳም ተመለሰ::

በዚያ በዓት ሠርቶላት: ቀኖናም ሰጥቷት ሔደ:: ማርያም ስለ ኃጢአቷ ፈንታ የምትገርም የቅድስና ሰው ሆነች:: ያየ ሁሉ እየተደነቀባት ከዓመታት ተጋድሎ በሁዋላ ዐረፈች:: አባ አብርሃም በተረፈ ዘመኑ በንጹሕ ገዳማዊ ሕይወት ተጠምዶ ኑሯል::

በዘመኑ ሁሉ በጥርሱ ስቆ: በከንፈሩም አልባሌ ነገርን ተናግሮ አያውቅም:: ልቡ በፈጣሪው ፍቅር የታሠረ ነበርና ሕማማተ ክርስቶስን እያሰበ እንባው ያለማቁዋረጥ ይፈስ ነበር:: ደግና ቅዱስ ሰው አብርሃም በዚህች ቀን ዐርፎ ተቀብሯል::

🕊 ቅዱስ ዮሐንስ ጻድቅ

ይህ ቅዱስ የነበረው በዘመነ ሰማዕታት ቢሆንም እንደ ሰማዕታት ስቃይ አልደረሰበትም:: ክርስቲያኖችን እንዲገድሉና አብያተ ክርስቲያናትን እንዲያቃጥሉ ከተመደቡ ወታደሮች አንዱ ነበረ:: ታዲያ እንዲገድላቸው የሚሰጡትን ክርስቲያኖች እየወሰደ ይደብቃቸው ነበር::

የመከራው ዘመን እስኪያልፍ ድረስም ይንከባከባቸው ነበር:: ሌሎች ወታደሮች እንዳይነቁበት ሁሌም "ክርስቲያኖችን በጣም እጠላለሁ" እያለ ያወራ ነበር:: እርሱ በሌሊት ሁሌም ለጸሎት ይተጋ ነበር:: በእንዲህ ያለ ግብር ኑሮም በዚህች ቀን በሰላም ዐርፏል::

🕊 አባ ፊልዾስ ዘደብረ ቢዘን

ደብረ ቢዘን በቀድሞ የኢትዮዽያ ክፍለ ሃገር [አሁን ኤርትራ] ውስጥ የሚገኝ ታላቅ ገዳም ነው:: ገዳሙ እመቤታችን ድንግል ማርያም በስደቷ ያረፈችበት: ጌታችን የባረከውና የመረጠው ቦታ ነው:: አባ ዮሐንስን: አባ ናርዶስንና ሌሎች ከዋክብት አበውን ያፈራ ሲሆን የአባ ፊልዾስን ያሕል ግን አልተገኘም::

ጻድቁ በግል የተጋድሎ ሕይወታቸው: ገዳሙን በአበ ምኔትነት በመምራታቸውና በስብከተ ወንጌል አገልግሎታቸው ምስጉን ነበሩ:: እርሳቸው ቅዱስ ሆነው አልበቃቸውምና ብዙ ቅዱሳንን ወልደዋል:: ይሕች ዕለትም የዕረፍታቸው መታሰቢያ ናት::

አምላከ ጻድቃን ገዳማትን ከመከራ ይጠብቅልን:: ከአባቶቻችን ቅዱሳን ጸጋ በረከትንም ይክፈለን:: 

[ † ነሐሴ ፭ [ 5 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]

፩. ቅዱስ አባ አብርሃም ገዳማዊ
፪. ቅድስት ማርያ እህቱ
፫. ቅዱስ ዮሐንስ ጻድቅ
፬. አባ ፊልዾስ ዘደብረ ቢዘን

[ † ወርሐዊ በዓላት ]

፩. ቅዱስ ዼጥሮስ ሊቀ ሐዋርያት
፪. ቅዱስ ዻውሎስ ብርሃነ ዓለም
፫. አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ
፬. ቅዱስ ዮሐኒ ኢትዮዽያዊ
፭. ቅዱስ አሞኒ ዘናሒሶ
፮. ቅድስት አውጋንያ [ሰማዕትና ጻድቅ]

" በድካም: አብዝቼ በመገረፍ: አብዝቼ በመታሠር: አትርፌ በመሞት ብዙ ጊዜ ሆንሁ:: በድካምና በጥረት: ብዙ ጊዜም እንቅልፍ በማጣት: በራብና በጥም: ብዙ ጊዜም በመጦም: በብርድና በራቁትነት ነበርሁ. . . የቀረውን ነገር ሳልቆጥር ዕለት ዕለት የሚከብድብኝ የአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ አሳብ ነው::" [፪ቆሮ.፲፩፥፳፫]

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር
† ወለወላዲቱ ድንግል
† ወለመስቀሉ ክቡር

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ]

       †             †              †
▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬
💖                🕊                💖
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
"በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"።

             #ነሐሴ ፭ (5) ቀን።

እንኳን #ለኢትዮያዊው_ጻድቅ በኤርትራ አገር በሐማሴን አውራጃ ከአስመራ ከተማ በስተምሥራቅ 25ኪ.ሜ ርቀት የሚገኝ አስደናቂ ገዳም #ዘደብረ_ቢዘን ለመሰረቱት እንደ ሐዋርያው #ቅዱስ_ጴጥሮስ በጥላቸው ድውያንን ይፈውሱ ለነበሩት ለአንዳዴ ባሕር ለአባታችን #ለአቡነ_ፊልጶስ ለዕረፍት በዓል በሰላም አደረሰን።

                           
#አቡነ_ፊልጶስ_ዘደብረ_ቢዘን፦ እንደ ነቢዩ ኤርምያስ በእናታቸው ማኅፀን ሳሉ የተመረጡና እንደተወለዱ ነው ሰማንያ አንዱን የብሉይ መጻሕፍትን አጠናቀው ያወቁት ናቸው፡፡ በ12 ዓመታቸውም ለመመንኰስና ገዳም ለመግባት ወስነው ወላጅ እናታቸውን "አሰናብቺኝ" በማለት ጠይቀዋል፡፡ ቅድስት እናታቸውም መርቀው ሸኟቸውና ትግራይ ውስጥ ወደሚገኘውና ደብረ ጸራቢ ወደሚባለው ገዳም ገቡ፡፡ የገዳሙ አስተዳዳሪ አቡነ በኪሞስም የምንኵስና ቀንበሩና ሸክሙ እጅግ ከባድ መሆኑን በመንገር ወደ እናታቸው እንዲመለሱ ቢመክሯቸውም አቡነ ፊልጶስ ግን ለምንኵስና የታጩ ሙሽራ መሆናቸውን ነገሯቸው፡፡ ከብዙ ፈተናም በኋላ አመነኰሷቸው፡፡

በገዳሙም እንጨት እየለቀሙና እየፈለጡ፣ ውኃ እየቀዱ፣ የክርስቶስን ሕማሙን ሞቱን እያሰቡ በጾምና ጸሎት ሲጋደሉ ከኖሩ በኋላ ጌታችን ተገልጦላቸው ወደ ሽሬ እንዲሄዱ ነገራቸውና ሽሬ አደያቦ ወደሚባለው ስፍራ ሄዱ፡፡ ብዙ አስደናቂ ተአምራት እያደረጉ ወንጌልን በሀገሩ ዞረው ሰበኩ፡፡ እንደ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በጥላቸው ድውያንን ይፈውሱ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ወደ ደብረ ቢዘን እንዲሄዱ ተነግሯቸው የእርሳቸውን በረከት ለመቀበል ከመጡ 16 ደጋግ መነኰሳት ጋር ወደ ደብረ ቢዘን ሄዱ፡፡ ይኸውም በኤርትራ ክፍለ ሀገር በሐማሴን አውራጃ ከአሥመራ ከተማ በስተምሥራቅ 25 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የሚገኘው አስደናቂው ገዳም ነው፡፡

ጻድቁ የሐይቅ እስጢፋኖስን ባሕር በተአምራት ያቃጠሉት አባት ናቸው፡፡ በንጉሡ በዐፄ ዳዊት ዘመን ሰንበትን አንድ ብቻ ናት እያሉ በአንደኛዋ ሰንበት ሥራ ሲሠሩ ጻድቁ አቡነ ፊልጶስ ይህን ሰምተው አንዲት ሰንበት የሚሉትን ሁሉ ተቃወሟቸው፡፡ ከግብፅ የመጡት ጳጳስም ቀደም ብሎ ከአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ አሁንም ከአቡነ ፊልጶስ ጋር ንጉሡ ዐፄ ዳዊት አከራክረዋቸው ጳጳሱም በክርክሩ ተረቱ፡፡ ክፉዎችም በአቡነ ፊሊጶስ ላይ በክፋት ተነሱባቸው፡፡ በአቁማዳ ጠቅልለው ሐይቅ ባሕር ውስጥ ጣሏቸው፡፡ በዚህም ጊዜ እሳቸው የተጣሉበት ባሕር በእሳት ተቃጥሎ ጽድቃቸውን መስክሮላቸዋል፡፡

ዛሬም ድረስ በሐይቅ እስጢፋኖስ ባሕር ዳርቻ ላይ የተቃጠለው ድንጋይ ምልክቱ በግልጽ ይታያል፡፡ በወቅቱ የንጉሡ ሚስት በዋናተኛ አስፈልጋ ከሐይቁ ውስጥ አስወጣቻቸው፡፡ እግራቸውንም አጥባቸው ስትጨርስ የእግራቸውን እጣቢ ጠጣችው፡፡ ወዲያውም "ከማኅፀንሽ ፍሬ ታላቅ ጻድቅ ልጅ ይወጣል" ብለው ትንቢት ነገሯት፡፡ በትንቢታቸውም መሠረት ታላቁ ጻድቅ ንጉሥ ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ተወልዱ፡፡ በወቅቱ በተፈጠረው አለመግባባትና ክፉዎችም በባሕር ውስጥ ስለጣሏቸው ንጉሡ ዐፄ ዳዊትም አቡነ ፊልጶስን ከልብ ይቅርታ ጠይቀው ወዲያው ታርቀዋል፡፡ በዘመናቸውም ርኃብ ስለነተሳ ጻድቁን ከገዳማቸው አስጠርተው "ምን ባደርግ ይሻለኛል?" ብለው አማክረዋቸዋል፡፡ አቡነ ፊልጶስም "የጌታችንን መስቀል ያስመጡ" ብለው መከሯቸው፡፡

ንጉሡ ዐፄ ዳዊትም በአቡን ፊልጶስ ምክር መሰረት ከኢየሩሳሌም፣ ከቍስጥንጥንያና ከእስክንድርያ መንግሥታት ጋር ተጻጽፈው ዐሥሩን ታላላቅ ቅዱሳን ይዘው ሄደው መስቀሉን መስከረም 10 ቀን አምጥተውታል፡፡ ቅዱስ መስቀሉን ያመጡት ዓሥሩ ቅዱሳንም የደብረ ቢዘኑ አቡነ ፊልጶስ ፣ የጣና ደሴቱ አቡነ ኂሩተ አምላክ፣ የጣና ደሴቱ አቡነ እንድርያስ፣ አቡነ በትረ ማርያም፣ አቡነ ዮሐንስ፣ አቡነ ታዴዎስ፣ አቡነ ያፍቅረነ እግዚእ፣ አቡነ ዘካርያስ፣ አቡነ ያሳይና አቡነ ቶማስ ናቸው፡፡ አቡነ ፊሊጶስ ዘደብረ ቢዘን በታላቅ ተጋድሎ ኖረው ከጌታችን ዘንድ ታላቅ ቃልኪዳን ከተቀበሉ በኋላ ነሐሴ 5 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል። ከአባታችን አቡነ ፊሊጶስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱስ ከሚለው መጽሐፍ።

                         
"#ሰላም_ለፊልጶስ_እንተ_ክህለ_ያዕዱ። ለዘጸውዖ ብእሲ ለውኂዘ ክረምት እምነ ሞገዱ። ወእምኔሁ አብ እለ መንፈስ ተወልዱ። እንዘ ይዜንው ኃይሎ ወምግባረ ጽድቁ ይንዕዱ። ስሙዓቲሁ ወጽአ ለዓለም በዐውዱ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የነሐሴ_5



@sigewe

https://www.tg-me.com/joinchat-AAAAAFGQ22bI0Ij80hYpFA

https://www.facebook.com/profile.php?id=100063896616886

https://www.facebook.com/profile.php?id=61552828743736&mibextid=ZbWKw
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
"በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"።

             #ነሐሴ ፭ (5) ቀን።

እንኳን #እህቱን_ቅድስት_ማርያን ከዘማዊነት ሕይወት ወደ ጽድቅ ሕይወት ለመራት ለታላቁ ተጋዳይ ለሌለው #ለአባ_አብርሃም_ለዕረፍት_በዓል፣ ለከበረ ተጋዳይ ወታደር #ለቅዱስ_ዮሐንስ_ለዕረፍት_በዐል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከአባ አብርሃም እህት ከቅድስት ማርያ ከመታሰቢያዋ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
                         
                           
#አባ_አብርሃም፦ የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ባለጸጎች ናቸው በተግሣጽና ፈሪሃ እግዚአብሔርን በማስተማር አሳደጉት ። በአደገ ጊዜም ያለ ፈቃዱ አጋቡት እግዚአብሔርም ወደሚፈቅደው ይመራው ዘንድ ሲለምን ኖረ። በሰባተኛውም ቀን በዐልጋው ላይ ሳለ የእግዚአብሔር ቸርነት አነሳሥቶት ከጫጉላ ቤቱ ወጣ ብርሃን እየመራው ሒዶ ባዶ ቤት አግኝቶ በውስጡ ገብቶ ኖረ ምግቡን ከሚቀበልባት ከጥቂት መስኮት በቀር መዝጊያ ሠርቶ ደጁን ዘጋ።

ዓለምን ከተወ በዓሥረኛው ዓመት አባትና እናቱ ብዙ ጥሪት ትተውለት ሞቱ እርሱ ግን ለድኆችና ለችግረኞች በትኖ በጾምና በጸሎት ተወስኖ እየተጋደለ ኖረ ከአንድ ዐጽፍና ሰሌን በቀር ምንም ምን ጥሪት አላኖረም እንዲህም ሆኖ ዐሥር ዓመት ተጋደለ።

እግዚአብሔርም ትዕግሥቱን አየ በአንዲት አገርም አረማውያን ነበሩ ከታናሾቻቸው እስከ ታላላቆቻቸው ወደ ሃይማኖት ሊመልሳቸው የሚችል የሌለ። በአንዲት ቀንም አባ አብርሃምን ጳጳሱ አሰበው ብርታቱንና ብልህነቱንም አይቶ ቄስ እንዲሆንና እነዚያን አረማውያን እንዲመልሳቸው አስገደደው በግድ አስጨንቆም ቅስና ሾመው ። ወደዚያም ቦታ ደርሶ ቤተ ክርስቲያን ሠራ እነዚያን አረማውያን እርሱን ፈጣሪያቸውን ወደ ማወቅ ይመልሳቸው ዘንድ በውስጧ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ።

በአነዲት ቀንም ወደ ጣዖቶቻቸው ቤት ገባ ያን ጊዜ ጣዖታቱን ከመቀመጫቸው ጣላቸው የአገር ሰዎችም በአዩ ጊዜ ቁጣን ተመልተው አብዝተው ደበደቡትና ከአገር አበረሩት በጥዋትም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲጸልይ አገኙት። ሁለተኛም በገመድ አሥረው ወደ ከተማው ውጭ ጐትተው በላዩም አፈር ቆልለው እንዳይሞት ጥቂት መተንፈሻ ትተው አልፈው ከዚያ ሔዱ። በእግዚአብሔርም ኃያል ተነሥቶ ሔደ ስለ መመለሳቸውም ሲጸልይ አገኙት በእንዲህ ያለ ሥራም እየተጋደለ ዐሥር ዓመት ኖረ።

የክብር ባለቤት እግዚአብሔርም ትዕግሥቱን አይቶ ወደ ቀናች ሃይማኖት ልባቸውን መለሰ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ከታናናሾች እስከ ታላላቆች ድረስ ሁሉንም አጠመቃቸው የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖትም ጸኑ።

ከዚህም በኋላ በሃይማኖታቸው መጽናታቸውን ባየ ጊዜ ከንቱ ውዳሴ እንዳያመጣበት ፈርቶ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ አገሪቱንም በመስቀል ምልክት አማተበባትና ማንም ሳያውቅ ወጥቶ ወደ ሌላ አገር ሔደ ።

ሰይጣንም በሚያስፈራው በብዙ ሥራ ይፈታተነው ነበር ቅዱሱም የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኃይል አሸነፈው። ጽኑ በሆነ ተጋድሎም ኖረ ያለ ዕንባም ሰዓት አላለፈችውም በጥርሶቹም አልሳቀም በከንፈሮቹም ፈገግ አላለም ስጋውን ቅባት አልነካውም ስጋውንና ደሙን ከሚቀበልበት ጊዜ በቀር ፊቱንና እግሩን አልታጠበም ።

እናትና አባቱ በስድስት ዓመቷ ትተዋት የሞቱ እኅት ነበረችው ስሟም ማርያ ይባላል ዘመዶቿም ወደ አብርሃም አምጥተዋት ፈሪሀ እግዚአብሔር ሃያ ዓመት ሆናት ድረስ ትሕትናንም እያስተማራት በእርሱ ዘንድ አደገች።

ከዚህም በኋላ ሰይጣን ቀንቶባት ከአንድ መነኩሴ ጋር አፋቀራት ድንግልናዋንም አጠፉች ልብሷንና አስኬማዋን ለውጣ ወደ ሌላ አገር ሔደች። አባ አብርሃምም በዚያች ሌሊት ታላቅ ከይሲ ርግቢቱን ሲውጣትና ጥቂት ቆይቶ ከእግሩ በታች ሲተፋት ራእይን አየ። በማግሥቱም ማርያ ከቦታዋ ታጣች አባ አብረሃምም ደነገጠ ወደ እግዚአብሔርም ከብዙ ዕንባ ጋር ጸለየ እርሷን ያገናኘው ዘንድ። ከጥቂት ወራትም በኋላ እኅቱ ያለችበትን አባ አብርሃም ሰማ ሰዎችም እንዳያውቁት የምንኵስናውን ልብስ ለውጦ ፊቱንም ተከናንቦ የወታደር ልብስ ለብሶ በፈረስ ተቀምጦ ወዳአለችበት አገር ሔደ ከዚያም ደርሶ ማርያ ወዳለችበት ገባ የመሸተኛንም ልብስ ለብሳ በአያት ጊዜ እጅግ አዘነ ነገር ግን እንዳትሸሸው እንድታውቀው አልሆነም።

ከዚህም በኋላ ለሚያገለግላት አሽከር ከማርያ ጋር የሚደሰትበት መብልና መጠጥ እንዲያዘጋጅ የወርቅ ዲናር ሰጠው ለርካሽ ሥራ እንደሚፈልጓት ሰዎች ይመስላት ዘንድ። ከራት በኋላም ወደ ውስጠኛው ቤት አስገባት በሩንም ዘጋ እጇንም ይዞ ራሱን ገለጠላት በአወቀችውም ጊዜ ደንግጣ እንደ በድን ሆነች "ልጄ ሆይ አይዞሽ ከእግዚአብሔር በቀር ከኃጢአት ንጹሕ የሆነ የለም ነገር ግን ወደ ንስሐ ተመለሺ ወደቦታሽም ገብተሽ የቀድሞ ሥርዓትሽን ያዢ" አላት እርሷም እሺ አለች።

በነጋም ጊዜም ወስዶ በፈረሱ አስቀመጣትና ደስ እያለው ተመለሰ እኅቱን ከሰይጣን እጅ ማርኳልና ወደቦታውም በደረሰ ጊዜ የቤቷን ደጅ ዘግቶላት ማቅ በመልበስ እየተጸጸተች የተጋድሎንም ሥራ እየተማረች በብርታቷና በተጋድሎዋ ያዩ ሁሉ እስቲአደንቁ ጸንታ ኖረች ።

እግዚአብሔርም በዚህ ቅዱስ ሰው እጆች ድንቆች ተአምራቶችን አደረገ አጋንንትን በማስወጣት በሽተኞችን በማዳን ከአንዲት ዓመትም በኋላ የማርያን ንስሓዋን አይቶ በሰባ ዘመኑ የተመሰገነ እግዚአብሔርን እያመሰገነ ነሐሴ 5 ቀን ዐረፈ።

ማርያ እኅቱም ከለቅሶ ጋር ትርኅምትን በማብዛት ቀንና ሌሊት እየተጋደለች ሌሎች አምስት ዓመታትን ኖረች ከዚያም በኋላ ዐረፈች ያዩዋትም በፊቷ ውስጥ ሰለአለው ብርሃን እግዚአብሔርን አመሰገኑ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ አብርሃም በጸሎቱ ይማረን ለዘላለሙ አሜን።

ተጋዳይ ወታደር የሆነ ቅዱስ ዮሐንስ፦ የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ክርስቲያኖች ናቸው እርሱም በከሀዲ በዑልያኖስ ሠራዊት ውስጥ ወታደር ሆነ። ንጉሡም ከባልንጀሮቹ ወታደሮች ጋራ ላከው የክርስቲያን ወገኖችንም በሚኖሩበት ቦታ ሁሉ እንዲአሠቃዩአቸው አዘዛቸው።

እርሱም ለባልንጀሮች ጭፍሮች ክርስቲያኖችን እጅግ እንደሚጠላቸውና እንደሚጣላቸው ይገልጽላቸዋል በጭልታም ገብቶ በጎ ነገርን የሚሹትን ሁሉ ይሰጣቸዋል ያጽናናቸዋልም። ሁል ጊዜም ይጸልያል ይጾማል ይመጸውታልም የቅዱሳንንም አኗኗር ኖረ ምስጉን እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላምዐአረፈ። ለእርሱም ለጌታ ምስጋና ይሁን። የቅዱሳንም በረከታቸው ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የነሐሴ 5 ስንክሳር።

                                  
@sigewe

https://www.tg-me.com/joinchat-AAAAAFGQ22bI0Ij80hYpFA

https://www.facebook.com/profile.php?id=100063896616886

https://www.facebook.com/profile.php?id=61552828743736&mibextid=ZbWKw
2024/09/30 19:21:12
Back to Top
HTML Embed Code: