Telegram Web Link
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from TIKVAH-ETHIOPIA
🔈#የእገዛጥሪ

" ወንድማችንን ታደጉልን ! " - ጓደኞቹ

አቤል ተሾመ (ናቲ ) ከ1 አመት በፊት ( 2015 ሀምሌ ) በClinical Pharmacy ከሐረር ጤና ሳይንስ ኮሌጅ በከፍተኛ መዓረግ መመረቁን ቤተሰቦቹና ጓደኞቹ ይናገራሉ።

ከዛሬ 7 ወር በፊት በድንገኛ  አጣዳፊ የኩላሊት ጉዳት (Acute kidney injury) እና የደም ግፊት ፣ ገለምሶ ሆስፒታል በህክምና ሲረዳ ቆይቶ ወዲያው ወደ ጥቁር አንበሳ ሪፈር ይባላል።

በጥቁር አንበሳ የውስጥ ደዌ ፣ የኩላሊት ስፔሻሊቲ ንዑስ ክፍል (Nephrology Department ) ላለፉት 7 ወራት የህክምና ክትትል ሲያረግ ጎን ለጎንም ላለፉት 3 ወራት በመቻራ ( ዳሮ ለቡ ) ሆስፒታል በተመረቀበት ሞያ ህዝቡን እያገለገለ ነበር።

ከወር በፊት ግን ህመሙ ከቁጥጥር ውጭ ሆኖ ክትትል በሚያረግበት ክፍል፣ የኩላሊቶቹ ጉዳት የመጨረሻ ደረጃ End stage renal disease እንደደረሰ እናም የኩላሊት እጥበትና ንቅለ-ተከላ እንደሚያስፈልገው እንደተረገረው አስረድተዋል።

ለዚህም ህክምና ቢያንስ እስከ 2 ሚሊየን እና ከዚያም በላይ እንደሚያስፈልገው ተገልጾለታል።

" አሁን ላይ ወደ ቅዱስ ጷውሎስ ተዘዋውሮ የቅድመ ንቅለ ተከላ ሂደት ጀምሯል " ያሉት ቤተሰቦቹና ጓደኞቹ " ሆኖም የዚህ ህክምና ወጪ ከአንድ ፋርማሲስት ( Pharmacist ) እና መንግስት ሰራተኛ ቤተሰቡ አቅም በላይ ስለሆነ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በቻለው አቅም እንዲደግፈው " ሲል ተማጽነዋል።

የሒሳብ ቁጥር የአባቱ 1000055784772 Teshome Nigusse (CBE)  እንዲሁም የራሱ 1000055874895 Abel Teshome (CBE) እንደሆነ ገልጸዋል።

@tikvahethiopia
Please open Telegram to view this post
VIEW IN TELEGRAM
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊

[ † እንኳን ለቅዱስ መርቆሬዎስ እና ለቅዱሳኑ ቴክላ : አበከረዙን : ዱማድዮስ እና ኄኖክ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፤ አደረሰን። † ]

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †


🕊 † ቅዱስ መርቆሬዎስ ሰማዕተ ሮሜ † 🕊

† ቅዱሱ ከቀደምት ሰማዕታት አንዱ ሲሆን በ፪፻ [200] ዓ/ም አካባቢ እንደ ተወለደ ይታመናል:: ወላጆቹ ከጣዖት አምልኮ ወደ ክርስትና የመጡት በተአምር ነው:: ስማቸውም ታቦትና_ኖኅ ይባላሉ:: ቅዱሱ መጀመሪያ "ፒሉፓዴር" ይባል ነበር:: ትርጉሙ "የአብ ወዳጅ" እንደ ማለት ነው::

ቀጥሎም "መርቆሬዎስ" ተብሏል:: ይኸውም " የኢየሱስ ክርስቶስ አገል ጋይ" እንደ ማለት ነው:: በጦርነት ኃይለኛ: በመልኩ ደመ ግቡና ተወዳጅ የነበረው ቅዱስ መርቆሬዎስ ስለ ክርስትናው መከራን የተቀበለው በ፳ [20] ዓመቱ ነው:: ዘመኑም በዳኬዎስ ቀዳማዊ ነው::

ስለ ሃይማኖቱም ለ፭ [5] ዓመታት መከራን ታግሦ በ፳፭ [25] ዓመቱ [ማለትም በ፪፻፳፭ [225] ዓ/ም] ሕዳር ፳፭ [25] ቀን አንገቱን ተከልሏል:: በዓለማቀፍ ደረጃም ቅዱስ መርቆሬዎስ ክብሩ ከሊቀ ሰማዕታት ቀጥሎ የሚገኝ ነው::

በተለይ ዛሬ ሐምሌ ፳፭ [25] ቀን ቅዳሴ ቤቱ ሲሆን ቤቱ በታነጸበት ሁሉ ተአምራትን ያደርጋል:: ስለዚህ ነገር ታሪክ ብቻ ሳይሆን እኛ ኃጥአንም ምስክሮች ነን:: ጋሹ አምባን ጨምሮ ዛሬም ቅዱሱ ድንቆችን ይሠራል::


🕊 †  ቅዱስ ኄኖክ ነቢይ  †  🕊

† ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ኄኖክ ከአባታችን አዳም ፯ [7] ኛው ደግ ሰው ሲሆን አባቱ ያሬድ ይባላል:: በእርግጥ ቅዱሱ ሚስት አግብቶ ማቱሳላና ሌሎች ልጆችን ወልዷል:: አካሔዱ ግን ከእግዚአብሔር ጋር ነበርና ሞትን አላየም::

ነቢዩ_ኄኖክ በ1486 ዓ/ዓ የመጀመሪያውን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል [መጽሐፈ_ኄኖክን] ጽፏል:: የዚሕ መጽሐፍ ባለቤት ደግሞ ሃገራችን ናት:: ቅዱሱ ብዙ ሰማያዊ ምሥጢሮችን ተመልክቷል::

የእርሱ ሞትን አለመቅመስ በአቤል ሞት የፈሩትን ውሉደ_አዳም በተስፋ አነቃቅቷቸዋል::
"በአቤል አፍርሆሙ:
ወበኄኖክ አንቅሆሙ" እንዳለው ሊቁ:: [ዘፍ.፭፥፳፬] (5:24, ኄኖክ.፬፥፩]  (4:1)


🕊 †  ቅድስት ቴክላ ሐዋርያዊት  †  🕊

† እናታችን ቅድስት ቴክላ በኒቆምድያ ተወልዳ ያደገች: ከአሕዛባዊ እምነት ወደ ክርስትና በሐዋርያው ቅዱስ_ዻውሎስ አማካኝነት የመጣች እናት ናት:: እርሷ ክርስትናን ከልብ ለሚሹ ሴቶች ሁሉ መሪና ትልቅ ት/ቤት ናት:: ወንጌልን ከሐዋርያው ስትማር ምሥጢሩ እየመሰጣት አንዳንዴ ለ፫ [3] ቀናት ምግብ አትቀምስም ነበር::

እጅግ ቆንጆ ወጣትና የሃብታሞች ልጅ ብትሆንም ስለ ክርስቶስ ሁሉን ለመናቅና መስቀሉን ለመሸከም አልተቸገረችም:: ከኒቆምድያ እስከ አንጾኪያ ወንጌልን ሰብካለች:: ወላጆቿን ጨምሮ ብዙ ነፍሳትን አድናለች:: በፈንታውም ብዙ መከራን ተቀብላ በዚህ ቀን ዐርፋለች:: ቤተ ክርስትያን " ሐዋርያዊት" ብላ ታከብራታለች::


🕊 † ቅዱስ አበከረዙን ጻድቅ ወሰማዕት † 🕊

† ስም አጠራሩ የከበረ ታላቁ አባ_አበከረዙን ወደ ክርስትና የተጠራው ከሽፍታነት [ስርቆት] ሕይወት ነው:: ከአጋሮቹ ጋር ገዳም ለመዝረፍ ሒደው አንድ ባሕታዊ ከማታ ፲፪ ሰዓት [12:00] እስከ ጧት ፲፪ ሰዓት [12:00] ሲጸልይ አይተው ተጸጽተው ንስሃ ገብተዋል::

አበከረዙን ግን ዓለምን ንቆ በምናኔ ለ፯ [7] ዓመታት ተጋድሏል:: ነገር ግን ሰማዕት ለመሆን ከነበረው ፍቅር የተነሳ ከገዳም ወደ ከሃድያን ነገሥታት ሃገር ሔዶ ስመ ክርስቶስን ሰብኩዋል:: በእርሱ ላይ ከደረሱ ስቃዮች ብዛት የተነሳ ከሥጋው: ከአጥንቱና ከደሙ የተረፈለት የለም::

እንዲያውም አንዴ በዓየር ላይ ዘቅዝቀው ሰቅለው ደሙ በአፍና በአፍንጫው እየጐረፈ ለ፲ [10] ቀናት ቆይቷል:: በወቅቱ የመኮንኑ ሴት ልጅ እየመጣች ያለ ርሕሪሔ ታሰቃየው ነበርና እርሷን መልአክ ወርዶ ቀሥፎ ገደላት::

እርሱ በተሰቀለ በ፳፪ [22] ኛው ቀን: እርሷ በተቀበረች በደግሞ በ፲፪ [12] ኛው ቀን ከተሰቀለበት አውርደውት ከሞት አስነስቷታል:: ታላቁ አበከረዙንን በዚህች ቀን ብዙ አሰቃይተው: ወገቡን ሰብረው: አንገቱንም ሰይፈው ገድለውታል::


🕊 † ቅዱስ ዱማድዮስ ሶርያዊ  †  🕊

† ለቤተ ክርስቲያን በንጹሕ ሕይወታቸው ካበሩላት ዐበይት ቅዱሳን አንዱ ቅዱስ_ዱማድዮስ ነው:: እርሱ ወደ ክርስትና የመጣው ከባዕድ አምልኮ ሲሆን መሪው መንፈስ_ቅዱስ ነው:: ጣዕመ ሕይወቱን ሲሰሙት ዕዝነ ልቡናን ደስ ያሰኛል::

ገና በወጣትነቱ እንደ ሐዋርያት ሰብኮ አሕዛብን አሳምኗል:: እንደ ጻድቃን አካሉ አልቆ አጥንቶቹ እስኪታዩ ተጋድሏል:: እርሱ ድንግል: ንጹሕ: መነኮስ: ባሕታዊና ካህን ነው:: ግን ውዳሴ ከንቱን አምርሮ ይጠላል:: በዚህ ምክንያት ካደረበት አይውልም: ከዋለበትም አያድርም::

እርሱ በጸሎቱ የተዘጉ ማሕጸኖችን ከፍቷል:: ዕውራንን አብርቷል:: ለምጻሞችን አንጽቷል:: አንካሶችን አርትቷል:: በፈጣሪው ኃይል ፈሳሽ ወንዝን አቁሟል:: እንደ ገናም እንደ ነበረው መልሶታል::

የቅዱስ ዱማድዮስ መጨረሻው ደግሞ ሰማዕትነት ነው:: በበዓቱ ውስጥ ሳለ ከደቀ መዝሙሩ ጋር ክፉዎች በድንጋይ ወግረው ገድለውታል:: ድንጋዩም የኮረብታ ያህል ነበር:: ልክ በዓመቱ በዚህች ዕለት ምዕመናን ሥጋውን አፍልሠዋል::

† ቸር አምላክ ከነቢያት: ሐዋርያት: ጻድቃንና ሰማዕታት ክብርን ያሳትፈን::

🕊

[  †  ሐምሌ ፳፭ [ 25 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  ]

፩. ቅዱስ መርቆሬዎስ ሰማዕት [ቅዳሴ ቤቱ]
፪. ቅዱስ ኄኖክ ነቢይ [ዕርገቱ]
፫. ቅድስት ቴክላ ሐዋርያዊት
፬. ቅዱስ አበከረዙን ታላቁ [ጻድቅና ሰማዕት]
፭. ቅዱስ ዱማድዮስ ሶርያዊ [ጻድቅና ሰማዕት]
፮. ቅድስት ኢላርያ ሰማዕት
፯. ቅዱሳት ቴክላ ወሙጊ ሰማዕታት
፰. ቅዱስ እንዲኒና ሰማዕት
፱. አባ ይስሐቅ ሰማዕት
፲. አባ ሕጻን ሞዐ ዘደብረ ሊባኖስ
፲፩. ፳፭ ሺህ "25,000" ሰማዕታት [የአትሪብ /ግብፅ/ ሰዎች]

[   †  ወርሐዊ በዓላት   ]

፩. ቅዱስ ይሁዳ ሐዋርያ [ከ፸፪ [72] ቱ አርድእት]
፪. አቡነ አቢብ [አባ ቡላ]
፫. ቅዱስ አባ አቡፋና ጻድቅ

† "እግዚአብሔር ቅዱሳንን ስላገለገላችሁ: እስከ አሁንም ስለምታገለግሏቸው ያደረጋችሁትን ሥራ: ለስሙም ያሳያችሁትን ፍቅር ይረሳ ዘንድ ዓመጸኛ አይደለምና:: በእምነትና በትእግስትም የተስፋውን ቃል የሚወርሱትን እንድትመስሉ እንጂ ዳተኞች እንዳትሆኑ ተስፋ እስኪሞላ ድረስ እያንዳንዳችሁ ያን ትጋት እስከ መጨረሻ እንድታሳዩ እንመኛለን::" † [ዕብ.፮፥፲-፲፫] (6:10-13)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]


         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
                          †                          

   [   🕊  ማር መርቆሬዎስ   🕊   ]  

🍒▬▬▬▬▬▬▬▬▬▬🍒               

🕊 † " ፒሉፓዴር " የአብ ወዳጅ † 🕊

እንኳን አደረሰን !

በዓለ ልደቱ ወቅዳሴ ቤቱ ለማር መርቆሬዎስ ፤ መፍቀሬ አብ።

ሰላም ለኅሊናከ ዘኢየአምር ቅያሜ ፤
....

ኦ ! በኅሊናህ ቂም በቀል የሌለብህ ! መዓዛህ እንደ ጣፋጭ ሽቱ የሆነ ! ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ [ ከሃዲዎች ] እንደ ደመና የበተኑህ ! የተጋድሎ ምስክርነትን የፈጸምህ ! ኦ! መርቆሬዎስ ዘሮሜ ! [ አርኬ ]

🕊

[ በከመ ልማድከ ፍጡነ ተራድአነ ] እንደልማድህ ፈጥነህ እርዳን !

🍒

†                       †                       †
💖                    🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
🕊

[ † እንኳን ለአቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን : ለአረጋዊ ቅዱስ ዮሴፍ እና አባ ጢሞቴዎስ ዘአልቦ ጥሪት ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣ አደረሰን። † ]

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †


🕊 † አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን †  🕊

† ቅዱሱ በትውልዳቸው ግሪካዊ ቢሆኑም ሶርያ አካባቢ እንዳደጉ ይታመናል:: በቀደመ ስማቸው ፍሬምናጦስ የሚባሉት አቡነ ሰላማ ወደ ኢትዮዽያ የመጡት በአደጋ ምክንያት [በድንገት] ቢመስልም ውስጡ ግን ፈቃደ እግዚአብሔር ነበረበት::

በድንበር ጠባቂዎች [በአደጋ ጣዮች] ከባልንጀራቸው ኤዴስዮስ ጋር ተይዘው ወደ አክሱም የመጡት በንጉሥ ታዜር [አይዛና] እና በሚስቱ ሶፍያ [አሕየዋ] ዘመን ነው:: ጊዜው በውል ባይታወቅም በ፬ [4] ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው::

ፍሬምናጦስ ምንም የመጡበት ዓላማ ስብከተ ወንጌል ባይሆንም በአክሱም ቤተ መንግስት አካባቢ ይሰበኩ ነበር:: ያን ጊዜ በጃንደረባው ቅዱስ ባኮስ የተቀጣጠለው የክርስትና ችቦ ውስጥ ውስጡን በሃገሪቱ ነበረና ፍሬምናጦስ አልተቸገሩም:: በተለይ ሕጻናቱን [ኢዛናና ሳይዛናን] ገና ከልጅነት ስላስተማሯቸው ነገሮች የተሳኩ ሆኑ::

ልክ ንጉሥ ታዜር እንደ ሞተ ሁለቱ ሕጻናት በመንበሩ ተቀመጡ:: ፍሬምናጦስንም ወደ ግብፅ ዻዻስና ጥምቀት ከመጻሕፍት ጋር እንዲመጣላቸው ላኩ:: ሐዋርያዊ ቅዱስ አትናቴዎስም ፍሬምናጦስን "ሰላማ" ብሎ ሰይሞ : በዽዽስና : በንዋየ ቅድሳትና በመጻሕፍት ሸልሞ መለሳቸው::

አቡነ ሰላማ ወደ ኢትዮዽያ እንደተመለሱ ከነገሥታቱ ጀምረው ለሕዝቡ ጥምቀትን አደሉ:: ኢዛናና ሳይዛናም አብርሃ [አበራ] እና አጽብሃ [አነጋ] ተብለው ስማቸው ተደነገለ:: ከዚያ በሁዋላ ድንቅ በሚሆን አገልግሎት ነገሥታቱ : ዻዻሱ ሰላማና ሊቀ ካህናቱ እንበረም ለክርስትና መስፋፋት በጋራ ሠርተዋል::

†  የአቡነ ሰላማ ትሩፋቶች :-

፩. ዽዽስናና ክህነትን ከእውነተኛ ምንጭ አምተዋል::
፪. ክርስትናና ጥምቀትን በሃገራችን አስፋፍተዋል::
፫. ቅዱሳት መጻሕፍትን ከውጭ ልሳኖች ተርጉመዋል::
፬. ገዳማዊ ሕይወትን ጀምረዋል::
፭. አብያተ ክርስቲያናትን አንጸዋል::
፮. ግዕዝ ቋንቋን አሻሽለዋል::
ሀ. ከግራ ወደ ቀኝ እንዲፃፍ
ለ. እርባታ እንዲኖረው
ሐ. ከ"አበገደ" ወደ "ሀለሐመ" ቀይረዋል::

ባላቸው ንጹሕ የቅድስና ሕይወት ለሕዝቡ ምሳሌ ሆነዋ:: "ወበእንተዝ ተሰይመ ከሳቴ ብርሃን" እንዲል ገድላቸው በነዚህ ምክንያቶች "ከሣቴ ብርሃን" [ብርሃንን የገለጠ] ሲባሉ ይኖራሉ:: በመጨረሻም ከመልካሙ ገድል በሁዋላ በ፫፻፶፪ [352] ዓ/ም ዐርፈው ተቀብረዋል::


🕊  †  ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ  †   🕊

† በሐዲስ ኪዳን መጀመሪያ አካባቢ ስም አጠራራቸው ከከበረ ደጋግ እሥራኤላውያን አንዱ የእመቤታችን ጠባቂ ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ ነው:: ትውልዱ ከነገደ ይሁዳ ሲሆን አባቱ ያዕቆብ ይሰኛል::

በጉብዝናው ወራት የእመቤታችንን አክስት ማርያምን አግብቶ ብዙ ልጆችን ወልዶ አርጅቷል:: ከልጆቹም ዮሳ: ያዕቆብ: ይሁዳ: ስምዖን እና ሰሎሜ በቅዱስ መጽሐፍ ተዘክረዋል:: ቅዱስ ዮሴፍ እድሜው ፸፭ [75] ሲሆን ሚስቱ ማርያም ሞተችበት::

ከጥቂት ወራት በሁዋላም በመንፈስ ቅዱስ ድንግል ማርያምን ሊያገለግል ተመረጠ:: "እጮኛ" የሚለውም ለዛ ነው:: [ለአገልግሎት ነው የታጨው] እመቤታችን ለአረጋዊ ዮሴፍ በ፪ [2] ወገን ልጁ [ዘመዱ] ናት::

፩. የሚስቱ ማርያም የእህት [የሐና] ልጅ ናት::
፪. የቅድመ አያቱ የአልዓዛር የልጅ ልጅ ናት::

ደጉ ሽማግሌ ቅዱስ ዮሴፍ ምን ቢያረጅ እመቤታችንን ለማገልገል አልደከመውም:: አብሯት ተሰደደ:: ረሃብ ጥማቷን: ጭንቅና መከራዋን: ሐዘንና ችግሯን ተካፍሏል:: ከእመ ብርሃንና አምላክ ልጇ ጋር ለ፲፮ [16] ዓመታት ኑሯል::

ከእነዚህ ዘመናት በሁዋላም በ፲፮ [16] ዓ/ም : በተወለደ በ፺፩ [91] ዓመቱ ሲያርፍ ጌታችን "ሥጋሕ አይፈርስም" ብሎ ቃል ኪዳን ገብቶለታል::
"ኢየሱስ ክርስቶስ በከመ አሠፈዎ ኪዳነ::
ኢበልየ በመቃብር ወኢሂ ማሰነ::
እስከ ዮም በድኑ ሐለወ ድኁነ::" እንዳለ መጽሐፈ ስንክሳር::


🕊 † ቅዱስ ጢሞቴዎስ ዘአልቦ ጥሪት † 🕊

† ይህ ቅዱስ አባት በ፬ [4] ኛው መቶ ክ/ዘመን የእስክንድርያ ፓትርያርክ የነበረ አባት ነው:: ዘመነ ሲመቱም ከ፫፻፸፯ [377] እስከ ፫፻፹፯ [387] ድረስ ለ፲ [10] ዓመታት ነው:: በእነዚህ ዘመናቱ "ዘአልቦ ጥሪት" [ገንዘብ የሌለው / ነዳዩ አባት] ነበር የሚባለው:: ገንዘብንና ዓለምን የናቀ አባት ነበር::

ቅዱስ ጢሞቴዎስ የቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ደቀ መዝሙር እንደ መሆኑ ከመንፈሳዊ አባቱ መልካም ሕይወትን ወርሷል:: ምሥጢራትንም አጥንቷል:: በዘመኑ የአርዮስ ውላጆች ቤተ ክርስቲያንን ያስቸግሩ ነበርና ከእነርሱ ጋር ተዋግቷል:: ምዕመኑንም ከተኩላዎች ይጠብቅ ዘንድ ተግቷል::

በ፫፻፹፩ [381] ዓ/ም በቁስጥንጥንያ ጉባዔ በተደረገ ጊዜ ማሕበሩን በሊቀ መንበርነት መርቷል:: ለመቅዶንዮስ : ለሰባልዮስና ለአቡሊናርዮስ ኑፋቄዎችም ተገቢውን ምላሽ ሰጥቶ አውግዟል:: ቅዱስ ጢሞቴዎስ ዘአልቦ ጥሪት በቅድስና ተመላልሶ በ፫፻፹፯ [387] ዓ/ም በዚህች ቀን ዐርፏል::

† ፈጣሪ ከአቡነ ሰላማ : ከአረጋዊ ዮሴፍና ከቅዱስ ጢሞቴዎስ በረከትን ያሳትፈን::

🕊

[  † ሐምሌ ፳፮ [ 26 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት  ]

፩. ቅዱስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን
፪. ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ [የድንግል ማርያም ጠባቂ]
፫. ቅዱስ አባ ጢሞቴዎስ [ዘአልቦ ጥሪት]
፬. አባ ሮዲስ

[   †  ወርሐዊ በዓላት   ]

፩. ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ
፪. አቡነ ሐብተ ማርያም ጻድቅ
፫. አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ
፬. ቅዱሳን ሰማዕታተ ናግራን

† " እናንተ የምድር ጨው ናችሁ . . . እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ:: በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሠወር አይቻላትም:: መብራትንም አብርተው በዕንቅብ በታች አይደለም እንጂ በመቅረዙ ላይ ያናሩታል:: በቤት ላሉት ሁሉም ያበራል:: መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ::" † [ማቴ.፭፥፲፫] (5:13-16)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]


         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (♱ ባሕራን ♱)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
"በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"።

ሐምሌ ፳፯ (27) ቀን።

እንኳን #ለኢትዮጵያዊቷ_ጻድቅ ለታላቁ ለጻድቅ ንጉሥ #ለቅዱስ_ላሊበላ_ባለቤት (ሚስት) #ለቅድስት_መስቀል_ክብራ_ለዕረፍቷ_በዐል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።


#ቅድስት_መስቀል_ክብራ፡- የትውልድ ሀገሯ ትግራይ ሽሬ አካባቢ ነው፡፡ ይኽችም ቅድስት የታላቁ ጻጽቅ ንጉሥ የቅዱስ ላሊበላ ባለቤት ስትሆን ሁለቱን ያጋባቸው መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ነው። መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ቅዱስ ላሊበላን ወደ ሰማይ ነጥቆ ወስዶ የሚያንጻቸውውን የሕንጻ ዲዛኖችና ሌሎችንም ብዙ ምሥጢራትን ካሳየውና ወደ ምድር ከመለሰው በኃላ ድጋሚ ተገልጦለት "...እንደ አንተ የተመረጠች ናት እንደ ልብህም ትሆናለች፣ ሥራዋም ከሥራህ አያንስም እርሷ የተመረጠች የእግዚአብሔር አገልጋይ ናትና" በማለት መልአኩ የቅድስት መስቀል ክብራን ንጽሕናና ቅድስና መስክሮላታል፡፡

ቅድስት መስቀል ክብራ ከቅዱስ ላሊበላ ይትባረክን የወለደች ሲሆን በ23 ዓመት ውስጥ ቅዱስ ላሊበላ 11 እጅግ አስደናቂ የሆኑ ፍልፍል ቤተ መቅደሶቹን ከመላእክት ጋር ሲያንጽ ብታየው ልቧ በመንፈሳዊ ተመስጦ ተመልቶ እርሷም እግዚአብሔር ፈቅዶላት አስደናቂውን የአባ ሊባኖስን ቤተመቅደስ ራሷ እንዳነጸችው መጽሐፈ ገድሏና ገድለ ቅዱስ ላሊበላ ያስረዳል፡፡ ከዚህም በኋላ ቅድስት መስቀል ክብራን መንና ትግራይ ገባች። ወደ ትግራይ እየመራ የወሰዳት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ መልአኩ እርሷን በትግራይ ቅዱስ ሚካኤል እንዲጠብቃት ከተዋት በኃላ ቅዱስ ላሊበላን ደግሞ ወደ ኢየሩሳሌምና ወደ መንግሥተ ሰማያት አውጥቶታል፡፡

ቅድስት መስቀል ክብራም በትግራይ ሆና መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል እየጠበቃት ከሰው ተለይታ በታላቅ ተጋድሎ ኖረች፡፡ በቀን እልፍ እልፍ እየሰገደች በታላቅ ተጋድሎ ስትኖር ጌታችን ተገልጦ ክብሯ ከ 36ቱ ቅዱሳት አንስት ጋር እኩል መሆኑን ነግሯታል፡፡ ይኽችም ቅድስት ብዙ ሐዋርያዊ አገልግሎት ፈጽማለች፡፡ ለምሳሌ በመስቀል ጦርነት ጊዜ እስላሞች ከባሕር ማዶ እየፈለሱ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ በፍቅር እየተቀበለችና እያስተናገደች ሃይማኖትንና ሕገ እግዚአብሔርን እያስተማረች ወደ ክርስትና እንደገቡና እንዲጠመቁ አድርጋለች፡፡

ቅድስት መስቀል ክብራም በትግራይ ክልል ሽሬ አውራጃ መደባይ ታብር በተባለው ቦታ ላይ በስማ የተሰራ ትልቅ ገዳም አላት። እጅግ ውብ በሆኑ ሰንሰላታማ ትላላልቅ ድንጋዮች መካከል የሚገኝ አስደናቂና ጥንታዊ ገዳም ነው። ገዳሙ ከሽሬ ከተማ በእግር የ 7 ሰዓት መንገድ ያስኬዳል። የቅድስት መስቀል ክብራ ረድኤት በረከቷ ይደርብን፣ በጸሎቷ እግዚአብሔር አምላክ ይማረን፡፡ ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳንና ቅዱሳት በዐላት።

@sigewe

https://www.tg-me.com/joinchat-AAAAAFGQ22bI0Ij80hYpFA

https://www.facebook.com/profile.php?id=100063896616886

https://www.facebook.com/profile.php?id=61552828743736&mibextid=ZbWKw
2024/09/29 23:31:44
Back to Top
HTML Embed Code: