Telegram Web Link
💐💐💐💐💐💐💐💐

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

"በሰማይም ሰልፍ ሆነ:: ሚካኤልና መላእክቱ ዘንዶውን ተዋጉ:: ዘንዶውም ከመላእክቱ ጋር ተዋጋ:: አልቻላቸውምም:: ከዚያም ወዲያ በሰማይ ሥፍራ አልተገኘላቸውም:: ዓለሙንም ሁሉ የሚያስተው ዲያብሎስና ሰይጣን የሚባለው ታላቁ ዘንዶ እርሱም የቀደመው እባብ ወደ ምድር ተጣለ::"
(ራዕይ. 12:7)

👉👉👉 እንኳን ለመላእክት አለቃ ለሊቀ መልአክ ለቅዱስ ሚካኤል ዓመታዊ በዓል በሰላም በጤና አደረሰን አደረሳችሁ!!!

   
††† በዚህች ቀን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤልን ጨምሮ

👉 ቅዱስ ላሊበላ ጻድቅ (ንጉሠ ኢትዮዽያ)

👉 ቅድስት አፎምያና ባለቤቷ ቅዱስ አስተራኒቆስ

👉 ቅዱስ ባሕራን ቀሲስ

👉 ቅዱስ እለ እስክንድሮስ ሊቅ
አባ ዮስጦስ ሊቀ ዻዻሳት (የሐዋርያው ቅዱስ ማርቆስ ደቀ መዝሙር)

👉 አባ ቄርሎስ ሊቀ ዻዻሳት ይከበራሉ።


የቅዱስ ሚካኤል ምልጃው እና ፈጣን ተራዳኢነቱ አይለየን።

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

ኆኅተ ጥበብ ሰንበት ትምህርት ቤት

💐💐💐💐💐💐💐💐
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
🕊

[ እንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል እና ለቅዱሳኑ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፣ አደረሰን። ]

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †

🕊

በዚህች ቀን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤልን ጨምሮ ቅዱስ ላሊበላ: ቅድስት አፎምያና ቅዱስ ባሕራን ቀሲስ ይከበራሉ::

💖

🕊 † ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት †  🕊

ቅዱስ ሚካኤል በጥንተ ተፈጥሮ በኢዮር: ኃይላት በተባሉት ነገደ መላእክት ተሹሞ ነበር:: ሳጥናኤል በካደ ጊዜ እግዚአብሔር ባወቀ : አንድም በትሕትናውና ደግነቱ በ፺፱ኙ ነገደ መላእክት ላይ ሁሉ ተሹሟል::

ከፍጥረት ወገን ከእመቤታችን ቀጥሎ የቅዱስ ሚካኤልን ያሕል ክብርና ርሕሩሕ የለም:: በምልጃውም: በረዳትነቱም የታወቀ መልአክ ነው:: መጽሐፍ "መልአከ ምክሩ ለእግዚአብሔር" ይለዋል:: "ወስሙ መስተሣሕልም" ይለዋል:: ቂም የሌለው: ለምሕረት የሚፋጠን: ደግ መልአክ ነውና::

በብሉይ ኪዳን በመከራ ለነበሩ ቅዱሳን ሁሉ ሞገስ: ረዳትና አዳኝ ቢሆናቸው "መጋቤ ብሉይ" ተሰኝቷል:: እሥራኤልን ፵ ዘመን በበርሃ መርቷል: መግቧልም:: ቅዱስ መጽሐፍ ስለ እርሱ ብዙ ይላል:: [ዘፍ.፵፰፥፲፮, ኢያ. ፭፥፲፫, መሳ. ፲፫፥፲፯, ዳን. ፲፥፳፩, ፲፪፥፩, መዝ. ፴፫፥፯, ራዕይ. ፲፪፥፯] ደስ የሚለው ደግሞ ርሕሩሑ መልአክ ከእመቤታችን ጋር ልዩ ፍቅር አለው:: ከእናቷ ማሕጸን ጀምሮ እስከ ዛሬ እነሆ አብሯት አለ:: ደስ ብሎት ይታዘዛታል:: ማማለድ ሲፈልግም "እመቤቴ ሆይ! ቅደሚ" ይላታል:: ወደ እሳት መጋረጃ አብረው ገብተው ለዓለም ምሕረትን: በረከትን ያወርዳሉ::

ቅዱስ ሚካኤልን በዚሕች ዕለት ስለ እነዚህ ነገሮች እናከብረዋለን:-

፩. በመላእክት ሁሉ ላይ አለቃ ሆኖ መሾሙን
፪. ቅድስት አፎምያን መርዳቱን
፫. ቅዳሴ ቤቱን [ ግብፅ ውስጥ ]
፬. ቅዱስ ባሕራንን መጎብኘቱን
፭. ቅዱስ ላሊበላን ወደ ሰማያት ማሳረጉን
፮. ለፍጥረታት ሁሉ ምሕረት የሚጠይቅበት ዕለት ነውና

††† ሊቀ መላእክት በክንፈ ረድኤቱ ከክፉ ሁሉ ይጠብቀን::


🕊   †  ቅዱስ ላል ይበላ ንጉሥ  †   🕊

† በ፲፪ [12] ኛው መቶ ክ/ዘመን መጨረሻ ላይ በሃገራችን የነገሠው ቅዱስ ላሊበላ:-
- በብሥራተ መልአክ ተወልዷል
- ቅዱሳት መጻሕፍትን ገና በልጅነቱ አጥንቷል
- የንጉሥ ዘር ቢሆንም በጾምና ጸሎት: በትሕርምት አድጓል
- በወንድሙ ቢገረፍም ቂም አልነበረውም
- ስለ ወዳጆቹ ፍቅር መርዝ ጠጥቷል
- በዙፋን ላይ የኢትዮዽያ ንጉሥ ሆኖ ቢቀመጥም እርሱስ አኗኗሩ ገዳማዊ ነበር
- ከተባረከች ሚስቱ ቅድስት መስቀል ክብራ ጋር አንዲት ማዕድ ብቻ በቀን ይቀምሱ ነበር:: ለዛውም ለምለሙን ለነዳያን ሰጥተው እነርሱ የሚበሉት የእንጀራውን ቅርፍት [ጠርዝ] ብቻ ነበር::

በአካለ ሥጋ ወደ ሰማያት ተነጥቆ ብዙ ምሥጢራትን አይቷል
- በምሳሌውም ሃገረ ሮሃን [ላስታን] ገንብቷል
- ዛሬም ድረስ ምስጢር የሆኑት ፍልፍል አብያተ መቃድስ የእጆቹ ሥራዎች ናቸው::

ሥራውን ከፈጸመ በኋላ መንግሥቱን ለቅዱስ ነአኩቶ ለአብ አውርሶ: በመንኖ ጥሪትና በቅድስና ኑሮ በዚሕች ቀን አርፏል:: ጌታችን ስምህን ያከበረ: ዝክርህን የዘከረ: ከቤትህ ያደረውን: ከርስተ መንግስተ ሰማያት አካፍለዋለሁ ሲል ቃል ኪዳን ገብቶለታል::

††† በረከቱን: ክብሩን ያድለን::


🕊  †  ቅድስት አፎምያ  †   🕊

ከቅዱስ አስተራኒቆስ ጋር በተቀደሰ ትዳር የኖረች
- ምጽዋትን ያዘወተረች
- በፍቅረ ቅዱሳን የጸናች
- ንጽሕናዋን ጠብቃ ሰይጣንን ያሳፈረች ደግ እናት ናት:: ዛሬ የቅዱስ ሚካኤልን ስዕል ታቅፋ: በትእምርተ መስቀልም አማትባ አርፋለች: ቅዱሱ መልአክም ወደ ገነት አሳርጓታል::

🕊  †  ቅዱስ ባሕራን ቀሲስ  †  🕊

የደጋግ ክርስቲያኖች ግን የድሆች ልጅ:
- በሕጻንነቱ በግፍ ወደ ባሕር የተጣለ:
- በእግዚአብሔር ጥበብ አድጎ የግፈኛውን ንብረት የወረሰ:
- በመልካም ትዳር በቅስና ያገለገለ:
- ምጽዋትን ያዘወተረ: አብያተ ክርስቲያናትን ያሳነጸ ደግ ክርስቲያን ነው::
- በዚህች ቀን አርፎ ቅዱስ ሚካኤል ወዳጁ በዕረፍተ ገነት አኑሮታል::

† አምላካችን እግዚአብሔር ከቅዱሳኑ በረከት ይክፈለን:: አሜን:: †

🕊

[ † ሰኔ ፲፪ [ 12 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]

፩. ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት
፪. ቅዱስ ላሊበላ ጻድቅ [ንጉሠ ኢትዮዽያ]
፫. ቅድስት አፎምያና ባለቤቷ ቅዱስ አስተራኒቆስ
፬. ቅዱስ ባሕራን ቀሲስ
፭. ቅዱስ እለ እስክንድሮስ ሊቅ
፮. አባ ዮስጦስ ሊቀ ዻዻሳት [የሐዋርያው ቅዱስ ማርቆስ ደቀ መዝሙር]
፯. አባ ቄርሎስ ሊቀ ዻዻሳት

[ † ወርሐዊ በዓላት ]

፩. ቅዱስ ማቴዎስ ሐዋርያ
፪. ቅዱስ ድሜጥሮስ
፫. ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ
፬. ቅዱስ ቴዎድሮስ ምሥራቃዊ [ሰማዕት]
፭. ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ
፮. አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ

በሰማይም ሰልፍ ሆነ:: ሚካኤልና መላእክቱ ዘንዶውን ተዋጉ:: ዘንዶውም ከመላእክቱ ጋር ተዋጋ:: አልቻላቸውምም:: ከዚያም ወዲያ በሰማይ ሥፍራ አልተገኘላቸውም:: ዓለሙንም ሁሉ የሚያስተው ዲያብሎስና ሰይጣን የሚባለው ታላቁ ዘንዶ እርሱም የቀደመው እባብ ወደ ምድር ተጣለ:: † [ራዕይ.፲፪፥፯] (12:7)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
🕊

[ † እንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል እና ለጻድቁ አባ ዮሐንስ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፣ አደረሰን። † ]

† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †

🕊 †  ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት  †  🕊

† ቅዱስ ገብርኤል :-

- በራማ ከሚኖሩ ሊቃናት አንዱ::
- አርባብ በሚባሉ አሥር ነገዶች ላይ አለቅነትን የተሾመ::
- የስሙ ትርጓሜ "እግዚእ ወገብር" [ጌታና አገልጋይ] አንድም "አምላክ ወሰብእ" [የአምላክ ሰው መሆን] ማለት የሆነ::
- በመጀመሪያዋ የፍጥረት ቀን ዘጠና ዘጠኙን ነገደ መላእክት ያረጋጋ::
- ብርሃናውያን መላእክትን የሚመራ::
- በብሉይም ሆነ በሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት አብሣሪነቱ በስፋት የተነገረለት::
- በተለይ ደግሞ የወልደ እግዚአብሔርን ሰው የመሆን ዜና ይሸከም ዘንድ ያደለው::
- ከድንግል ማርያም ጎን በፍጹም የማይርቅ::
- በፈጣን ተራዳኢነቱ ብዙ ቅዱሳንን ያገለገለ ታላቅ ቀናዒ መልአክ ነው::

በዚሕች ዕለት እግዚአብሔር ቅዱስ ገብርኤልን ወደ ባቢሎን ልኮታል:: ሊቀ መላእክት ነቢዩ ዳንኤልን ከአናብስቱ ጥርስ እንዳዳነው መጽሐፍ ነግሮናል::

ይልቁኑ ታላቁ ነቢይ ዳንኤል የተማረኩ ወገኖቹን መመለስ እያሰበ በሃዘን ሲጸልይ በዚሕ ቀን ቅዱስ ገብርኤል ወርዶ ዳስሶታል:: ባርኮታል:: አጽናንቶታል:: ለዳንኤል በዋነኛነትም ሦስት ምሥጢራትን ገልጾለታል:-

፩. የቤተ እሥራኤልን ከሰባ ዘመን በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም መመለስ::

፪. የክርስቶስን ሰው መሆንና መሞት::

፫. የሐሳዌ መሲሕን በመጨረሻ ዘመን መምጣት ነግሮታል:: ስለዚህም እኛ ቅዱስ ገብርኤልን እንድናከብረው : በጸሎትም እንድንጠራው አባቶቻችን አዝዘውናል::

🕊 † አባ ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም †  🕊 

† ጻድቁ ሃገራቸው መካከለኛው ምሥራቅ አካባቢ ሲሆን የታላቁ ሊቅ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ባልንጀራ ናቸው:: ከሕፃንነታቸው ጀምሮ በክርስትና አድገው : ቅዱሳት መጻሕፍትን ተምረው ወደ ገዳም መንነዋል::

ከታላቁ ኮከበ ገዳም አባ ኢላርዮን ሥርዓተ መነኮሳትን አጥንተው አባ ኤስድሮስን በረድዕነት አገልግለዋል::

ከብዙ ዓመታት ትሕርምትና ገዳማዊ ሕይወት በኋላ የቅድስት ሃገር ኢየሩሳሌም ጳጳስ ሆነው ተሹመዋል:: በጵጵስናቸው ዘመን አንድ ከባድ ስሕተት ሠርተው ነበር::

እርሱም ለቤተ ክርስቲያንና ለነዳያን ከምእመናን የተሠበሠበውን ገንዘብ ለግል ጉዳያቸው አውለው ልብሳቸውና ቤታቸው ወርቅ በወርቅ ሆኖ ነበር:: ፈጣሪ ግን ይሕንን ብክነት ከእርሳቸው ያርቅ ዘንድ ቅዱስ ኤጲፋንዮስን ላከው::

እርሱም በምክንያት ከቆጵሮስ ኢየሩሳሌም ገባ:: ጓደኛ ናቸውና አሳምኖ የወርቅ ንብረቶቹን ሁሉ ወሰደ:: ለነዳያንም ሰጣቸው:: አባ ዮሐንስ ሊቁን "እቃየን ካልመለስክ" ብለው ቢይዙት ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ጸልዮ ዐይናቸው እንዲታወር አደረገ:: አንዳንዴ የታወረ ልብ የሚገለጠው እንዲሕ ነውና::

በደቂቃዎች ልዩነት ዐይነ ስውር የሆኑት አባ ዮሐንስ አለቀሱ:: ሊቁንም "ራራልኝ : አማልደኝ?" አሉት:: እርሱም ጸልዮ አንድ ዐይናቸውን ብቻ አበራላቸው:: "ለምን?" አሉት:: "ተግሳጽ ነው" አላቸው::

ከዚያች ቀን በኋላ አባ ዮሐንስ ወደ ልቡናቸው ተመለሱ:: ቤታቸውን ገዳም አደረጉት:: በሚደነቅ ቅድስና : ፍቅርና ሐዋርያዊ አገልግሎት ምዕመናንን አገልግለው በዚሕች ቀን በመልካም ሽምግልና ዐርፈዋል::

† የሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ረድኤት : የአባ ዮሐንስ በረከት አይለየን::

🕊

[ †  ሰኔ ፲፫ [ 13 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]

፩. ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት [ወደ ዳንኤል የወረደበት]
፪. አባ ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም
፫. አባታችን ቃይናን [ከአዳም አራተኛ ትውልድ]
፬. አባ ማትያን ጻድቅ

[ †  ወርኀዊ በዓላት ]

፩. እግዚአብሔር አብ
፪. ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት
፫. ዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት
፬. ቅዱስ አስከናፍር
፭. አሥራ ሦስቱ ግኁሳን አባቶች
፮. ቅዱስ አርሳንዮስ ጠቢብ ገዳማዊ
፯. አቡነ ዘርዐ ቡሩክ

" . . . በአምላኬም በእግዚአብሔር ፊት ስለ ተቀደሰው ስለ አምላኬ ተራራ ስለምን: ገናም በጸሎት ስናገር አስቀድሜ በራእይ አይቼው የነበረው ሰው ገብርኤል እነሆ እየበረረ መጣ:: በማታም መሥዋዕት ጊዜ ዳሰሰኝ:: አስተማረኝም: ተናገረኝም:: እንዲህም አለ :- "ዳንኤል ሆይ! ጥበብንና ማስተዋልን እሰጥህ ዘንድ አሁን መጥቻለሁ::" † [ዳን. ፱፥፳-፳፪]

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
Forwarded from M.A
"በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"።

            #ሰኔ ፱ (9) ቀን።

እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ_ኤርትራ_አገር የሚገኘው #ደብረ_ምዕዋን ለመሰረቱ ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ብፁዕ_አምላክ_ደቀ_መዝሙር ለሆኑት #ለአቡነ_በኵረ_ድንግል_ዘደብረ_ምዕዋን_ለዕረፍታቸው_በዐል በሰላም አደረሰን።

                          ✝️ ✝️ ✝️
#አቡነ_በኵረ_ድንግል፦ የአቡነ ብፁዐ አምላክ ረድእ የነበሩ ሲሆን እርሳቸውም ካረፉ በኋላ ተመርጠው በደብረ ምዕዋን ገዳም ላይ አበ ምኔት ሆነው ተሾመው ብዙ አገልግለዋል" ጻድቁ በምድረ ኤርትራ በምንኩስና እና በብሕትውና ጸንተው ለትልቅ ሰማያዊ ክብር የበቁ ታላቅ ጻድቅ ናቸው። በዓለ ዕረፍታቸው ሰኔ 9 ነው።

የአቡነ በኵረ ድንግል፦ አባታቸው ማርቆስ እናታቸው እግዚእ ክብራ የሚባሉ ሲሆን ጻድቁ ገና በእናታቸው ማሕፀን ሳሉ ብዙ ተኣምራት ይሠሩ ነበር" ሲወለዱም የእናታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ከነልጇ (ምስለ ፍቁር ወልዳ) በልባቸው ላይ ተሥላ ተገኝታለች" በማሕፃን ሳሉ ተመርጠዋልና በአኵሱም ሲወለዱ እንደሌሎቹ ቅዱሳን አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ›› ብለው ስመ ሥላሴን ጠርተው አመሰገኑ። በዚያ የነበሩና ይህንን የተመለከቱ ሰዎችም ባዩትና በሰሙት ነገር እጅግ ተደነቁ።

በ40ኛው ቀናቸውም በጥምቀት የሥላሴን ልጅነት እንዲቀበሉ ወላጆቻቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲወስዷቸው በወቅቱ የነበሩት ጳጳሱ አቡነ ሰላማ ሕፃኑ ትልቅ መነኵሴና የአቡነ ብፁዐ አምላክ ደቀ መዝሙር እንደሚሆን ተገልጾላቸው ትንቢት ተናገሩ። ዳግመኛም ጳጳሱ ቅብዓ ሜሮን ሊቀቡት ሲሉ ሥዕለ ማርያም ከነልጇ በሕፃኑ ደረት ላይ ተሥላ አይተዋት ደነገጡ ወዲያውም ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጸ ሳይፈሩ ሥርዓተ ጥምቀቱን እንዲፈጽሙ አዘዛቸው ዳግመኛም ..… "ስሙን በኵረ ድንግል በለው ትርጉሙም በልቡ ላይ ያየኸው ሥዕል ነው" ብሎ ነገራቸው" ሕፃኑም ከተጠመቀ በኋላ እመቤታችን ከነልጇ ጋር ተገልጻ በትእምርተ መስቀል ባረከችው ያ ትእምርተ መስቀልም ዳግመኛ በሰውነታቸው ላይ ተሳለ።

ከዚህም በኋላ አቡነ በኵረ ድንግል አድገው ቤተሰቦቻቸውን እየረዱ በእረኝነት እያገለገሉ በመልካም አስተዳደግ አደጉ" ዕድሜአቸው ለትምህርት እንደደረሰ ወላጆቻቸው ለንቡረ እድ ዮፍታሔ ሰጧቸውና አስተማሯቸው። ከቋንቋዎች ግእዝ፣ ዐረብ ዕብራይስጥ፣ ጽርዕ እና ሮማይስጥ ተማሩ፤ ብሉይንና ሐዲስን እንዲሁም ቅዱሳት መጻሕፍትን ሁሉ አጠናቀው ተማሩ። ቅኔ ድጓ ጾመ ድጓ እና የቅዱስ ያሬድን ዜማዎችም በሚገባ አጠኑ። ትምህርታቸውንም ከጨረሱ በኋላ መምህራቸው ወደ ሊቀ ጳጳስ ወሰዱአቸው በልባቸው ያለች የእመቤታችን ሥዕልም ለጳጳሱ ተገልጣ "ይህ የምወደው ልጄ ስለሆነ በልቡ ተሳልሁ ስለዚህ ዲቁና ቅስና ስጠው፣ ኤጲስ ቆጵስነትም ሹመው" አለቻቸው። ጳጳሱም ባዩትና በሰሙት ነገር ተደንቀው ተነሥተው እንደተባሉት በሦስቱ መዕረግ ሾሟቸው። ከሹመታቸውም በኋላ በአከባቢው ያሉ ሰዎች አቡነ በኩረ ድንግልን ብርሃን ለብሰው ስላዩዋቸው በጣም ተደነቁ።

ከዚህም በኋላ አቡነ በኵረ ድንግል ለአቅመ አዳም ሲደርሱ ወላጆቻቸው በሕገ ቤተ ክርስቲያን መሠረት ሚስት ሲያጩላቸው አቡነ በረ ድንግል ግን "እኔስ ፍላጎቴ በድንግልና መኖር እንጂ ማግባት አይደለም" ብለው ሌሊት ተነሥተው ከቤታቸው ጠፍተው ወደ እግዚአብሔር ቤት ሔደው "አቤቱ ጌታ ሆይ! ከዘለዓለም እሳት ከዲያብሎስ እሥራት ሰውረኝ መጥፎውን ሐሳብ ከእኔ አርቀህ ፍቃድህን እፈጽም ዘንድ እርዳኝ የእመቤታችን ሥዕል ከነልጇ በልቤ አለና ወደ ጋብቻ ዓለም ለመግባት ኅሊናዬ አልፈቀደልኝም ስለዚህ ፍቃድህ ቢሆንልኝ እንደ መላእክት ንጹሕ ሁኜ እንድኖር እለምንሃለሁ፣ አንተ ድኃና ምስኪን የማትንቅ አምላክ መሆንህን ዐውቃለሁና…" እያሉ ጸለዩ። እየጸለዩ ሳለ ክብርት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቅዱስ ሚካኤልንና ቅዱስ ገብርኤል አስከትላ ተገለጠችላቸውና "ልጄ ሆይ! ጸሎትህ ተሰምቷልና ወደ ደብረ ዳሞ ወደ አባትህ ሒድ፣ እንዲሁም ደግሞ ወደ ደብረ ናዝሬት ወደ ብፁዐ አምላክ ዘንድ ሒድ የብዙዎች አባትም ትሆናለህ" በማላት ከባረከቻቸው በኋላ ተሰወረች።

ከዚህም በኋላ ጻድቁ መጋቢት 9 ቀን በቦታቸው ሆነው በተመስጦ እየጸለዩ ሳሉ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል በደመና ተሸክሞ ወስዶ ደብረ ዳሞ የቅዱሳን ማረፍያ ቦታ አደረሳቸው። እመቤታችን እንደነገረቻቸው በገዳሙ አስቀድማ እንደነገረቻቸው ለረጅም ዓመታት በትሕትና ካገለገሉ በኋላ ወደ አባታቸው ወደ አቡነ ብፁዐ አምላክ ከረጅም ጉዞ በኋላ መጡ። አቡነ ብፁዐ አምላክም አስቀድመው መምጣታቸውን ያውቁ ነበርና አሁን ሲያገኗቸው እግዚአብሔርን አመስግነው በታላቅ ደስታና ትሕትና ተቀበሏቸው።

በገዳማቸውም በትሕትና እያገለገለ ከቆዩ በኋላ አንድ ቀን አቡነ ብፁዐ አምላክ "ዛሬ በእጅህ ቍርባን እንድንቀበል አንተ ቀድስ" አሏቸው። አቡነ በኩረ ድንግልም ቅዳሴ ገብተው አሐዱ አብ ቅዱስ… ብለው ሲጀምሩ ከመሬት ወደላይ 5 ሜትር ያህል ከፍ ብለው ታዩ፤ ይኽንንም አይተው አቡነ ብፁዐ አምላክ በጣም ተደንቀው እግዚአብሔርን አመሰገኑ። አቡነ በኵረ ድንግልም በእንዲህ ያለ ሕይወት አባታቸውን አቡነ ብፁዐ አምላክን ካገለገሉ በኋላ አቡነ ብፁዐ አምላክ ታኅሣሥ 9 ቀን የገዳማት መነኰሳትን ሰብስበው "ዛሬ ለሁላችሁ መሪ የሚሆን ትሑትና ደግ መምህር እሰጣችኋለሁ ከእኔ በታች እርሳቸውን ስሟቸው ታዘዙአቸውም" ብለው ነገሯቸው።

ዳግመኛም አባታችን አቡነ ብፁዐ አምላክ የዕረፍታቸው ጊዜ ሲደርስ የገዳሙን መነኰሳት ሰብስበው ከእርሳቸው በኋላ አባት እንዲሆኗቸው አቡነ በኵረ ድንግልን እጃቸውን ጭነው ባርከው ሾሟቸው። ከዚህም በኋላ አቡነ በኵረ ድንግል በጾም በጸሎት በስግደት ለገዳሙና በገዳሙ ለሚኖሩ መነኰሳት ሁሉ በትሕትና እያገለገሉ በታላቅ ተጋድሎ ኖሩ። የገዳሙ መነኰሳትም በጣም ወደዷቸው። ተጋድሏቸውንና አገልግሎታቸውንም በፈጸሙ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአቡነ በኵረ ድንግል እንዲህ የሚል ቃልኪዳን ገባላቸው።

"በስምህ ዝክር የሚዘክር ስምህን የሚጠራ በዕረፍትህ ቀን የታመሙትንና የታሰሩትን የጎበኘ በስምህ የተራበ ያበላ ያጠጣ የታረዘ ያለበሰ የልጁን ስም በስምህ የጠራ ይህን ሁሉ ያደረገውን እምረዋለሁ ክፉም አይነካውም፤ በደብረ ምዕዋን በአባትህ በብፁዐ አምላክ ቦታ በአንተም ቦታ የተቀበረ በቦታው ቅዱስ ቍርባን የተቀበለ ክፉ አያገኘውም፣ እምረዋለሁ፣ ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌምም አስገበዋለሁ ብሔረ ሕያዋንና ብሔረ ብፁዓንንም አወርሰዋለሁ…" የሚሉ ታላላቅ የምሕረት ኪዳናትን ከእግዚአብሔር ከተቀበሉ በኋላ ሰኔ 9 ቀን ትንሽ የራስ ምታት ሕመም ጀመራቸው። የገዳሙ መነኰሳትና ሌሎቹም ታላላቅ ቅዱሳን አባቶች እንደእነ አቡነ ዮሐንስ ዘደብረ ቢዘን ያሉት እንደየ ደረጃቸው ከያሉበት ተሰበሰቡ። በዚህም ጊዜ ሥሉስ ቅዱስ ተገልጸውላቸው ድጋሚ ቃልኪዳን ገብተውላቸው አረጋጓቸውና ቅድስት ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለየች።
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
🕊

†  በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ
አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡  †

[ †  እንኩዋን ለአራቱ ቅዱሳን አበው ሰማዕታት
ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ † ]


🕊 † አራቱ ቅዱሳን አበው ሰማዕታት † 🕊

፬ [4] ቱ ቅዱሳን አበው የዘመነ ሰማዕታት ፍሬዎች ሲሆኑ ስማቸው አባ አክራ አባ ዮሐንስ : አባ አብጥልማ እና አባ ፊልዾስ ይባላሉ:: ከመከራ ዘመን በፊት [ማለትም በቀደመ ሕይወታቸው]  ካህናትና ሃብታሞች ነበሩ:: ሀብቱ ግን በሥራ ብቻ የተገኘ ነው::

ታዲያ ቅዱሳኑ በያሉበት ሆነው በሀብታቸው እንግዳ እየተቀበሉ : ድሆችን እያበሉ: በክህነታቸው ደግሞ እያስተማሩና እየናዘዙ ትጉሃን ስለ ነበሩ በሰውም ሆነ በእግዚአብሔር ዘንድ ሞገስ ነበራቸው:: በእንዲህ ያለ ግብር ሳሉ ዘመነ ሰማዕታት አሐዱ አለ:: "ክርስቶስን ካዱ: ለጣዖት ስገዱ" እያሉ መኩዋንንቱና ነገሥታቱ ሕዝበ ክርስቲያኑን ያሰቃዩ ገቡ::

በዚህ ጊዜ ፬ [ 4 ] ቱ ቅዱሳን አንድ ነገር መከሩ:: በየእሥር ቤቱ የተጣሉ ክርስቲያኖችን ለማገልገል ቆረጡ:: እግረ መንገዳቸውን እያስተማሩ እሥረኞችን ያጽናኑ ገቡ:: የራበውን ያበላሉ: የተሰበረውን ይጠግናሉ: በቁስሉም ላይ መድኃኒትን ያደርጉ ነበር:: የመከራው ዘመን ግን እየረዘመ: ግፉም ከልክ እያለፈ መጣ::

በዚህ ጊዜ ፬ [ 4 ] ቱ ቅዱሳን ትልቁንና የመጨረሻውን ውሳኔ አስተላለፉ:: ከሰማዕታት ወገን ይቆጠሩ ዘንድ መርጠዋልና: ክርስቶስን በሞቱ ይመስሉት ዘንድ ሽተዋልና: የሩጫቸው መጨረሻ ሰማዕትነት እንዲሆን መረጡ::

አራቱም ያላቸውን ንብረት ሁሉ ሰብስበው ለነዳያን
አካፈሉ:: በትከሻቸው ካለች አጽፍ በቀር ስባሪ ገንዘብ ከሃብታቸው አላስቀሩም:: ከዚያ ጉዞ ወደ ምስክርነት አደባባይ [ዐውደ ስምዕ] አደረጉ::

በዙፋኑ የተቀመጠው የመኮንኑ ግርማ: መሬት ላይ የፈሰሰው የወገኖቻቸው ደም: የሠራዊቱ ድንፋታ ቅዱሳኑን አላስፈራቸውም:: በይፋ "ክርስቲያን ነን" ሲሉ ተናገሩ:: በዘመኑ እንዲሕ ብሎ መናገር አንገት የሚያስቆርጥ ትልቅ ድፍረት ነበር::

መኮንኑም ከበጐ ሃይማኖታቸው ይለያቸው ዘንድ በእሳት አቃጠላቸው:: እግዚአብሔር አዳናቸው:: በቀስትም: በስለትም: በብረትም ለቀናት አሰቃያቸው:: ቅዱሳኑ ግን አምላካቸውን አምነው ሁሉን በአኮቴት ተቀበሉ:: በመጨረሻ ግን በዚሕች ዕለት የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው ተገድለዋል:: ስለ ምጽዋታቸው: በጎ አገልግሎታቸውና ሰማዕትነታቸው ጻድቅ: ፈራጅ ከሆነ ፈጣሪ አክሊልን ተቀብለዋል::

የበረከት አምላክ ከወዳጆቹ ጸጋ ክብርን ያድለን::

🕊

[ † ሰኔ ፲፬ [ 14 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]

፩. ቅዱሳን አበው ሰማዕታት [አባ አክራ: አባ ዮሐንስ: አባ አብጥልማ: አባ ፊልዾስ]

[ †  ወርሐዊ በዓላት ]

፩. አቡነ አረጋዊ [ ዘሚካኤል ]
፪. ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ መርዓዊ
፫. ቅዱስ ፊልዾስ ሐዋርያ
፬. ቅዱስ ሙሴ [ የእግዚአብሔር ሰው ]
፭. አባ ስምዖን ገዳማዊ
፮. አባ ዮሐንስ ጻድቅ
፯. እናታችን ቅድስት ነሣሒት

" እግዚአብሔር ቅዱሳንን ስላገለገላችሁ: እስከ አሁንም ስለምታገለግሏቸው ያደረጋችሁትን ሥራ: ለስሙም ያሳያችሁትን ፍቅር ይረሳ ዘንድ ዓመጸኛ አይደለምና:: በእምነትና በትእግስትም የተስፋውን ቃል የሚወርሱትን እንድትመስሉ እንጂ ዳተኞች እንዳትሆኑ ተስፋ እስኪሞላ ድረስ እያንዳንዳችሁ ያን ትጋት እስከ መጨረሻ እንድታሳዩ እንመኛለን። " [ዕብ.፮፥፲-፲፫] (6:10-13)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
🕊

†  በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ
አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡  †

🕊 እንኳን አደረሳችሁ 🕊

[ †  እንኩዋን ለሰማዕቱ ቅዱስ ሚናስ ዓመታዊ
የቅዳሴ ቤት በዓል በሰላም አደረሳችሁ † ]


🕊 † ቅዱስ ሚናስ ምዕመን ሰማዕት † 🕊

ቅዱስ ሚናስ [ ማር_ሚና ] በምድረ ግብጽ ተወዳጅ ከሆኑ ሰማዕታት ዋነኛው ነው:: ልክ በሃገራችን ቅዱስ ጊዮርጊስ ልዩ ቦታ እንዳለው ሁሉ ግብፃውያን ማር ሚናስን ጠርተው አይጠግቡትም::

ምክንያቱም ከታላላቅ ሰማዕታት አንዱ በመሆኑና ዛሬም ድረስ ለጆሮና ለዐይን ድንቅ የሆኑ ተአምራትን ስለሚሠራ ነው:: በተለይ ለታመመ: ለደከመና ለተጨነቀ ፈጥኖ ደራሽ: ባለ በጐ መድኃኒት ፈዋሽና አማላጅ ነው::

ግብጽ ውስጥ ቅዱሱን የማያውቅ ሰው ካገኛችሁ እርሱ ኦርቶዶክሳዊ አይደለም ማለት ነው ሲባልም ሰምተናል:: በነገራችን ላይ ለቅዱሳን ተገቢውን ክብር በመስጠት: ታሪካቸውን በመጻፍ: በማጥናት: በመጽሔት: በፊልምና በመሳሰሉት ለሕዝብ በማስተዋወቅ ግብጻውያኑ ከእኛ ብዙ ርቀት ሒደዋል:: ዛሬ እንኩዋ የምንጠቀምበትን ስንክሳር ፹ [80] ከመቶ እጁን ያዘጋጁት እነርሱ ናቸው::

አባቶቻችንና እናቶቻችን ኢትዮዽያውያን ቅዱሳን ግን አብዛኞቹ ተረስተው ቀርተዋል:: መጽሐፈ ገድላቸውንም ብል በልቶታል:: ዛሬም የቤት ሥራው የእኛ ብቻ ነው::

ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና ቅዱስ ሚናስ [ትርጉሙ ታማኝና ቡሩክ ማለት ነው] :-

- በ፫ [3] ኛው መቶ ክ/ዘመን የነበረ የደጋግ ክርስቲያኖች ልጅ
- በልጅነቱ የቅድስና ሕይወትን ያጣጣመ
- በዘመኑ ሰው እጅግ ተወዳጅ የነበረ
- ሃብትን: ክብርን: ሥልጣንን ንቆ በጾምና በጸሎት የተወሰነ
- በመጨረሻም በክርስቶስ ስላመነ አላውያን የገደሉት ሰማዕት ነው::

እርሱ ሰማዕት ከሆነ ከበርካታ ዘመናት በሁዋላ ምዕመናን ክቡር አካሉን ፈልገው ያጡታል::

የሚገለጥበት ጊዜ ሲደርስ ግን እርሱ የተቀበረበት ምድረ በዳ የበጐችና የእረኞች መዋያ ነበርና ተአምራትን አደረገ:: አንድ እረኛ በጐቹ ድውያን ሆኑበት:: በዚያ ሰሞን ከቅዱሱ መቃብር ላይ ጸበል ፈልቆ ነበርና እረኛው ተርታ ውሃ ነው ብሎ በጎቹን ሲያጠጣቸው አንዱ ድውይ በግ ወደ ጸበሉ በመዘፈቁ ዳነ::

በዚህ የተገረመው እረኛ ሁሉንም የታመሙ በጐቹን አምጥቶ ነከራቸው:: እነርሱም ተፈወሱ:: ይህ ዜና በምድረ ግብፅ ሲሰማ ድውያን ሁሉ እየመጡ ይፈወሱ ገቡ:: ግን እነሱም ሆነ እረኛው ምክንያቱን ማወቅ አልቻሉም::

ነገሩ በሮም ንጉሥ ዘንድ ሲሰማ ሴት ልጁን ከሠራዊቱ ጋር ላካት:: ምክንያቱም እርሷ ከብዙ ዘመን ጀምራ መጻጉዕ ነበረችና ፈውስን አጥታ ነበር:: መጥታ ተጠመቀች: ፈጥናም ተፈወሰች:: እርሷ ግን እንደ ሌሎች ያዳናትን ማንነት ሳታውቅ መሔድ አልፈለገችምና ሱባዔ ገባች::

ቅዱስ ሚናስ በሌሊት ራዕይ መጥቶ ሥጋው እንዳለ ነገራት:: እርሷም መሬቱን አስቆፍራ የቅዱሱን አካል በክብር አስወጣች:: ከዚያም በንጉሡ ትዕዛዝ ምድረ በዳው ከተማ እንዲሆን ተቀየረ:: ስሙም " መርዩጥ " ተባለ:: ጸበሉ የነበረበት ቦታም ላይ የማር ሚናስ ቤተ_ክርስቲያን ታንጾበት በዚህች ዕለት ቅዳሴ ቤቱ ተከብሯል::

አምላካችን ከቅዱሱ ሰማዕት በረከትን ይክፈለን::

🕊

[ †  ሰኔ ፲፭ [ 15 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]

፩. ቅዱስ ሚናስ [ማር ሚና] ሰማዕት [ቅዳሴ ቤቱ]

[ † ወርሐዊ በዓላት ]

፩. ቅዱስ ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣ
፪. ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ [አፈ በረከት]
፫. ቅድስት እንባ መሪና
፬. ቅድስት ክርስጢና

" ፈጥኜ ወደ አንተ እንድመጣ ተስፋ አድርጌ ይሕን እጽፍልሃለሁ:: ብዘገይ ግን በእግዚአብሔር ማደሪያ ቤት መኖር እንዴት እንደሚገባ ታውቅ ዘንድ እጽፍልሃለሁ:: ቤቱም የእውነት ዓምድና መሠረት የሕያው እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ነው:: እግዚአብሔርንም የመምሠል ምሥጢር ያለ ጥርጥር ታላቅ ነው:: " [፩ጢሞ.፫፥፲፬] (3:14)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]

         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
"በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"።

              #ሰኔ_፲፭ (15) ቀን።

እንኳን #ለታላቁ_ሰማዕት_ለሰማይ_ጭፍራ ለተባለ #ለቅዱስ_ሚናስ_ቤተ_ ክርስቲያን_መርዩጥ በተባለ አገር #ለከበረችበት_ለቅዳሴ_ቤቱ_በዐል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።

                        ✝️ ✝️ ✝️
#የቅዱስ_ሚናስ_ቤተ_ክርስቲያን_ቅዳሴ_ቤት፦ ከዚህ አስቀድሞ የቅዱስ ሚናስ ሥጋ ተሠውሮ ይኖር ነበር ጌታችንም ሊገልጠው በወደደ ጊዜ ምክንያት አደረገ ይኸውም እንዲህ ነው ቅዱስ ሚናስ ሥጋው ተደፍኖ በሚኖርበት ኮረብታ አቅራቢያ በጎችን የሚያረባ አንድ ሰው በጎቹን እየጠበሸ ይኖር ነበር። ከዚያ እረኛ በጎች ውስጥ ደዌ ያለበት አንዱ በግ በዚያ በኮረብታው አጠገብ ባለ የጒድጓድ ውኃ ተጠምቆ ወዲያውኑ ከደዌው ዳነ እረኛውም አይቶ አደነቀ ሌሎችንም ደዌ ያለባቸውን አመጣ በዚያ ውኃም በታጠቡ ጊዜ ሁሉም ዳኑ።

ከዚህም በኋላ ይህ በቦታው ሁሉ ታወቀ ደዌ ያለባቸውም ሁሉ እየመጡ አፈሩን ከውኃው ጋራ አንድ አድርገው ለውሰው በመቀባት ወዲያውኑ ይድኑ ነበሩ ምክንያቱን ግን አላወቁም። በዚያ ውኃና በአፈሩ በሽተኞችን እንደሚያድን የዚያ በግ ጠባቂ ወሬው በሮሙ ንጉሥ ዘንድ ተሰማ ለንሡም የቊስል ደዌ የታመመች ልጅ ነበረችው ወደ በግ ጠባቂውም ላካት እርሱም በጎቹን እንደ አዳናቸው አዳናት። እርሷም በተፈወሰች ጊዜ ከዚያ ቦታ ፈውስ የሚደረግበትን ምክንያት ታውቅ ዘንድ ወደደች።

ከዚህም በኋላ ቅዱስ ሚናስ በሕልም ተገለጸላትና ሥጋዬ በዚህ ቦታ ተደፍኖ ስለሚኖር እነሆ አስቆፍረሽ ታወጪው ዘንድ እግዚአብሔር አዞሻል" አላት። ከእንቅልፍም በነቃች ጊዜ ቅዱስ ሚናስ እንዳዘዛት አደረገች የከበረ ሥጋውንም አወጣች በዚያም ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያን ሠራችለት ንጉሡም በዚያ ቦታ ከተማ እንዲሠሩ መኳንንቱንና ሹሞቹን አዘዛቸው ታላቅ ከተማም ተሠራች ስሟም መርዩጥ ተባለች።

እግዚአብሔር ከቅዱስ ሚናስ ሥጋ ቊጥር የሌላቸው ድንቆችንና ተአምራትን ገለጠ። ሊቀ ጳጳሳቱም ከኤጲስቆጶሳቱ መጥቶ ቤተ ክርስቲያኒቱን በዛሬዋ ሰኔ 15 ዕለት አከበራት በዚያቺም ቦታ የሚሠሩ የድንቆችና የተአምሮች ወሬ በቦታው ሁሉ ተሰማ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ሚናስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሰኔ15 ስንክሳር።

                           ✝️ ✝️ ✝️
"#ሰላም_ለቅዳሴ_ቤትከ እንተ ተሐንፀት በመርዩጥ። በትእዛዝ ንጉሥ ሥሉጥ። #ሚናስ ዘአንቃሕከ በድነ ሐራውያ እምጸጥ። አስተዋጺኦሙ ዕደው ዘበበ፪ቱ ቂራጥ። መባአ ለከ ዘነሥኡ በሤጥ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሰኔ_15

                           ✝️ ✝️ ✝️
#የዕለቱ_ምስባክ፦ "ውእተ አሚረ ተናገርኮሙ በራእይ ለደቂቅከ። ወትቤ እሬሲ ረድኤተ በላዕለ ኃይል። ወአልዐልኩ ኅሩይየ እምሕዝብየ"። መዝ 88፥19። የሚነበቡት መልዕክታት ኤፌ 7፥10-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 4፥16-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 25፥1-13። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 13፥44-51። የሚቀደሰው ቅዳሴ የወልደ ነጎድጓድ የቅዱስ ዮሐንስ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ሚናስ የቅዳሴ ቤት በዓልና የበዓለ ዕርገቱ ሰሞን  ለሁላችንም ይሁንልን።

@sigewe

https://www.tg-me.com/joinchat-AAAAAFGQ22bI0Ij80hYpFA

https://www.facebook.com/profile.php?id=100063896616886
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ተአምኆ ቅዱሳን)
2024/09/27 22:19:14
Back to Top
HTML Embed Code: