Telegram Web Link
+ +  +እግዚአብሔር አምላክ ለሀገራችን እና ላለንበት ሀገር ሰላምን ይስጥልን አሜን++

መጽሐፈ ስንክሳር፣
ከዲ/ን ዮርዳኖስ ማስታወሻ
          
+++መልካም ዕለተ ሐሙስ መልካም በቀን+
+++
<<< በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ >>>

<<< ታሕሳስ 26 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት >>>

+" ቅድስት አንስጣስያ "+

=>እስኪ ዛሬ በጥቂቱ የተባረኩ (ቡሩካት) እናቶቻችን
እንዘክር:: "ቅድስት" የሚለው ቃል ለሁሉም ቅዱሳት
እናቶች ቢሰጥምቅሉ ለድንግል ማርያም ሲሰጥ ግን ትርጉሙ ይለያል::
እርሷ 'ቅድስተ ቅዱሳን: ንጽሕተ ንጹሐን: ቡርክት
እምቡሩካን:
ኅሪት እምኅሩያን ናትና::

+ከሰው ልጆችም ሁሉ ትበልጣለች:: ይቅርና የሰው ልጅን
ንጹሐን መላእክትንም በንጽሕናና በቅድስና
ትበልጣቸዋለች:: እርሷ
እመ ብርሃን: የአምላክ እናቱ: የሰውነታችን መመኪያ
ናትና::

+እመቤታችንን "ቅድስት" ስንል "ጽንዕት: ንጽሕት: ክብርት:
ልዩ" ማለታችን ነው:: 1."ንጽሕት" ትባላለች:: ሌሎች
ሰዎች (ቅዱሳን) ቢነጹ ከገቢር: ከነቢብ ኃጢአት ነው
እንጂ ከኃልዮ ኃጢአት አይደለም:: እርሷ ግን ከነቢብ:
ከገቢር:ከኃልዮ ንጽሕት ናት::

"ለመኑ ተውኅቦ ተደንግሎ ኅሊና: ለመላእክትሂ
ኢተክህሎሙ-ኃጢአትን ከማሰብ መጠበቅ ከሰው ልጆች
ለማን ተሰጠው: ይህስ
ለመላእክትም አልተቻላቸውም" እንዲል:: (ተአምረ
ማርያም)

2."ጽንዕት" እንላታለን:: ሴቶች ቢጸኑ ለጊዜው ነው እንጂ
በኋላ በጊዜው ተፈትሆ አለባቸው:: እመቤታችን ግን
ቅድመ ጸኒስ: ጊዜ ጸኒስ: ድኅረ ጸኒስ: ቅድመ ወሊድ: ጊዜ
ወሊድ: ድኅረ ወሊድ ድንግል ናትና::
"ጽንዕት በድንግልና አልባቲ ሙስና" እንዳላት:: (ቅዱስ
ያሬድ) ታላቁ ቅዱስ ባስልዮስም "ወትረ ድንግል ማርያም-
ማርያም ዘለዓለማዊት ድንግል ናት" እንዳለ:: (መጽሐፈ ቅዳሴ)

3.ድንግልን "ክብርት" እንላታለን:: ሌሎች ሴቶች ቢከብሩ
ጻድቃን ሰማዕታትን: ነቢያት ሐዋርያትን ወልደው ነው::
እመቤታችንን ግን የምናከብራት "ወላዲተ አምላክ-
የአምላክ እናቱ" ብለን ነውና::

4.እመቤታችንን "ልዩ" እንላታለን:: ከእርሷ በቀር እናት ሁና
ድንግል: እመቤት ሁና አገልጋይ የሆነች: በድንግልና
ወልዳ ወተትን (ሐሊበ ድንግልናዌን) ያስገኘች ሌላ ሴት
የለችምና::

+የእመ ብርሃን ይቆየንና ደግሞ ሌሎች ቅዱሳት
እናቶቻችንን እንመልከት:: እናቶቻችን ስናከብር
የምንጀምረው በቅድስትሔዋን ነው:: ብዙ ጊዜ የእናታችን ሔዋን ጥፋቷ እንጂ በጐ ነገሯ: ደግነቷ: ንስሃዋ አይነገርላትም:: ሆኖም
እናታችንቅድስት ሔዋን ክብር የሚገባት ሴት ናት::

*ክርስቶስ ሰው የሆነ እርሷንና ልጆቿን ለመቀደስ ነውና::
"ከመ ይስዓር መርገማ ለሔዋን ዲበ ዕፅ ተሰቅለ"
እንዲል::
(ድጉዋ)

+ቀጥሎ በብሉይ ኪዳን እነ ሐይከል: እድና: ሣራ: ርብቃ:
አስኔት: ሲፓራ: ሐና: ቤርሳቤህን የመሰሉ እናቶቻችን
በበጐው መንገድ ፈጣሪን ደስ አሰኝተዋል:: በዘመነ ሥጋዌም
ቅዱሳቱ ሐና: ኤልሳቤጥ: ማርያም: ሶፍያ: ሰሎሜ: ዮሐና
እና 36ቱ ቅዱሳት አንስት በጐነታቸው ያበራል::

+ከዚያ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ለ2,000 ዓመታት የተነሱ
አእላፍ ቅዱሳት እናቶቻችንን ግን ዘርዝረን አንዘልቃቸውም::
በቅድስናቸው አራዊትን ያሰገዱ: ነገሥታትን ያንቀጠቀጡ:
አጋንንትን የረገጡ: በዘንዶ ላይ የተጫሙ ብዙ እናቶችን
ቤተክርስቲያን አፍርታለች::

+ዛሬም ቢሆን በበርሃና በከተማ በጐውን ጐዳና የተከተሉ
ብዙ እናቶች እንዳሉን እናውቃለን:: አንድም እናምናለን::
ግን ግን በከተሞች የምንመለከተው ሥርዓቱን የለቀቀው
የበርካታ እህቶቻችን አካሔድ ለሃገርም ለቤተ
ክርስቲያንም ትልቅ ስጋት
ነው:: ክብርና ነውር የማይለይበት ዘመን ይመስላል::

+ይህንን እያነበባችሁ ያላችሁ እህቶቼ! አንድ ነገር
ልንገራችሁ:: በመልካቸው ብዙዎችን ያጋጩ: አጊጠው
በመታየታቸው ብዙዎችን ያሰናከሉ: ለብዙ ምዕመናንም
የጥፋት ምክንያት የሆኑ ብዙ ሴቶች በታሪክ ነበሩ::

+የሚያሳዝነው ግን ዛሬ ያሉት ከመሬት በታች ነው:: አፈር
በልቷቸዋል:: ስም አጠራራቸውም ጠፍቷል:: በጣም
የሚያሳዝነውደግሞ ዛሬ በዘለዓለማዊው እሳት እየተቃጠሉ በሲኦል:በጥልቁ ውስጥ አሉ::

+እናም ወገኖቼ! ይህን አውቀን እንንቃ:: ይህ ዓለም
ጠፊም: አጥፊም ነውና:: እድሜአችን ቢረዝምና ከዚህ
በኋላ ለ100 ዓመታት ብንኖርም እርሱም ማለቁ አይቀርምና::
ምርጫችን ዘለዓለማዊው ሕይወት ይሁን ትላለች ቅድስት
ቤተ ክርስቲያን::

+" ቅድስት አንስጣስያ "+

+ይህች ቅድስት እንደ በርካቶቹ ቅዱሳት እናቶቻችን ሁሉ
የዘመነ ሰማዕታት ፍሬ ናት:: በቀደመችው ታናሽ እስያ
አካባቢተወልዳ: የነገሥታት ዘር በመሆኗ ያደገችው በቤተ
መንግሥት ነው:: አባቷ ከክቡራኑ አንዱ ቢሆንም ሙያው
ጣዖትን ማምለክ ነበር::

+ጊዜው የመከራ በመሆኑ ብዙ ሴቶች የሚኖሩት
ክርስትናቸውን ደብቀው ነው:: ከእነዚህ መካከል አንዷ
ደግሞ የቅድስት አንስጣስያ እናት ናት:: ማንን እንደምታመልክ አረሚ ባሏ አያውቅም ነበር::

+አንስጣስያን በወለደች ጊዜም በድብቅ አስጠመቀቻት::
ከሕጻንነቷ ጀምሮም ፍቅረ ክርስትና እንዲያድርባት ነገረ
ሃይማኖትን አስተማረቻት:: ቅድስት አንስጣስያ ወጣት በሆነች ጊዜ ግን ከውበቷ የተነሳ ተመልካቿ በዛ:: እርሷ ግን ይህ ሁሉ
የዓለም ኮተት አይገባትም ነበር::

+በፈጣሪዋ ፍቅር ከመጠመዷ የተነሳ ለመሰል ነገሮች
ትኩረት አልነበራትም:: ትጾማለች: ትጸልያለች: ነዳያንና
እሥረኞችን ትጐበኛለች:: በዚህም ዘወትር ደስ ይላት ነበር:: ነገር ግን አባቷ ባላሰበችው ጊዜ ለአንድ አረማዊ አጋባት:: በጣም
አዘነች: ግን ተስፋ አልቆረጠችምና መፍትሔ ፈለገች::

+ድንግልናዋን እንዳያረክስ በጫጉላዋ ቀን ታመምኩ ብላ
ተኛች:: ከዚያ በኋላም አንዴ በልማደ አንስት: አንዴ
በሕመም እያመካኘች አላስቀርብ አለችው:: እርሱ የጦር አለቃ
በመሆኑ ወደ ጦርነት ሲሔድ እርሷ ታጥቃ ስለ ቀናች
እምነት የታሠሩ ክርስቲያኖችን ታገለግል ነበር::

+ቁስላቸውን እያጠበች: አንጀታቸውን በምግብ እየደገፈች
ደስ ታሰኛቸውም ነበር:: ባሏ ሲመለስ ግን ይህንን
በመስማቱ ድጋሚ እንዳትወጣ ቆልፎባት ወደ ጦርነት ተመለሰ::
ፈጽማ ስላዘነችበትም እግዚአብሔር በጠላቶቹ እጅ
አሳልፎ ሰጠውና ሞተ::

+እርሷም ከነ ድንግልናዋ ቀሪ ሕይወቷን ስትመራ
መከራው ወደ እርሷ ደረሰ:: ተይዛ ቀርባ በአረማውያን እጅ
ብዙ ተሰቃየች:: በዚህች ቀንም ስለ ክርስቶስ ተገድላ ክብረ
ሰማዕታትን ተቀዳጀች::

ቅዱስ አቦሊ ጻድቅ

+ቅዱሱ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ የክርስቶስን ሕማማት
ለመሳተፍ ሲተጉ ከኖሩ ጻድቃን አንዱ ነው:: መሉ ጊዜውን
በበርሃ ሲያሳልፍ ብዙ ተጋድሎን ፈጽሟል:: በተለይ ሲጸልይ
እግሩን ከዛፍ ላይ አስሮ: ቁልቁል ከባሕር ውስጥ ሰጥሞ
ነው:: ዛሬ ቤተ ክርስቲያን ዕረፍቱን ታስባለች::

=>አምላከ ቅዱሳን ጸጋውን: ክብሩን ያድለን:: ከወዳጆቹ
በረከትም አይለየን::

=>ታሕሳስ 26 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅድስት አንስጣስያ ሰማዕት
2.ቅዱስ አቦሊ ጻድቅ
3.ቅድሰት ዮልያና ሰማዕት

=>በ 26 የሚከበሩ ወርኀዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ
2.አቡነ ሐብተ ማርያም ጻድቅ
3.አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ
4.ቅዱሳን ሰማዕታተ ናግራን
5.ቅዱስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን
++"+ ለእናንተም ጠጉርን በመሸረብና ወርቅን
በማንጠልጠል ወይም ልብስን በመጐናጸፍ በውጭ የሆነ
ሽልማት አይሁንላችሁ::
ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ
የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለውን የማይጠፋውን ልብስ
ለብሶ የተሰወረ
የልብ ሰው ይሁንላችሁ:: +"+ (1ዼጥ. 3:3)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
Audio
ስንክሳር ዘወርሃ ታህሣሥ ሃያ ስድስት(፳፮)
https://www.tg-me.com/SinkisarZekidusan2
እንኩዋን ለሰማዕቱ "አባ አብሳዲ" እና ለጻድቁ "አባ በግዑ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+"+ ቅዱስ አባ አብሳዲ +"+

=>ቅዱሱን የመሰሉ አባቶች "መስተጋድላን" ይባላሉ በግዕዙ:: ለሃይማኖታቸው እስከ ደም ጠብታና እስከ መጨረሻዋ ህቅታ ድረስ መጋደላቸውን የሚያሳይ ነው:: መጋደል ጐዳናው ብዙ ዓይነት ነው::

+ከራሱ ጋር የሚጋደል አለ:: ከዓለም ጋር የሚጋደልም አለ:: የቅዱሳኑ ተጋድሎ ግን በዋነኝነት ከ2 አካላት ጋር ነው:: በመጀመሪያ ፍትወታት እኩያትን (ኃጣውዕን) ከሚያመጡ አጋንንት ጋር ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ "ሃይማኖቸታችሁን ካዱ: ለጣዖትም ስገዱ" ከሚሉ ከሃድያን ጋር የሚደረግ ትግል ነው::

+በተለይ 2ኛው እስከ ሞት የሚያደርስ ውሳኔን ይጠይቃል:: የዚህን ቅዱስ ሕይወት ለመረዳት ግን አንድ ነገርን ልብ እንድትሉልኝ እፈልጋለሁ::

+ያለንበት ዘመን ክርስትና በራድ (ቀዝቃዛ) በመሆኑ የቀደሙ አባቶች የጸና ተጋድሎ አንዳንዴ ግራ ሲያጋባን ተመልክቻለሁ:: ቅዱሳኑ ሁሌም አንድ ነገርን እያሰቡ ይኖራሉ:: ይኼውም በዘመኑ በርካቶቻችን የረሳነው: ወይም ማስታወስ የማንፈልገው ነገር ይመስላል::

+ሰማያዊው አምላክ ከዙፋኑ ወርዶ በተዋሐደው ሥጋ በቃል ሊገለጽ የማይችል መከራን ስለ እኛ ተቀብሏል:: ክርስትና ማለት ቀራንዮን በልብ ውስጥ መሳል ነው:: ፍቅረ መስቀሉን: የጌታንም ውለታ የሚያስብ ማንኛውም ሰው: የትኛውም ዓይነት መከራ ቢመጣበት አይታወክም::

+ቅዱሳኑም የፍቅራቸውና የትእግስታቸው ምሥጢር ይኼው ነው:: ጌታችን "የሚወደኝ ቢኖር የሞቱን መስቀል ተሸክሞ ይከተለኝ" (ማቴ. 16:18) እንዳለው ቅዱሳኑ ይህንን ቃል በቃል ሲፈጽሙት እነሆ እንመለከታለን::

+"+ ቅዱስ አባ አብሳዲ +"+

=>ቅዱሱ ሰማዕት ተወልዶ ያደገው በምድረ ግብጽ : በ3ኛው መቶ ክ/ዘ ነው:: እንደርሱ በቅድስና ያጌጠ ባልንጀራም ነበረው:: ስሙም ቅዱስ አላኒቆስ ነበር::

+እኒህ ክርስቲያኖች በዚያ የመከራ ዘመን ግራ ቀኝ ሳይሉ ትምሕርተ ቤተ ክርስቲያንን ጠንቅቀው ተምረዋል:: በጐውን ጐዳና አጽንተው በመገኘታቸውም መንፈስ ቅዱስ 2ቱንም በአንዴ ለእረኝነት ጠራቸው::

+ዽዽስና ከዚህ በፊት እንደ ተመለከትነው እዳ (ኃላፊነት) እንጂ ምድራዊ ክብርን ማጋበሻ መንገድ: ወይም የሥጋ ድሎትን መፍጠሪያ ዙፋን አይደለም:: ያም ሆኖ ምርጫው የመንፈስ ቅዱስ ሲሆን ደስ ያሰኛል::

+በእርግጥም የክርስቶስን መንጋ እንደሚገባ መምራትና በለመለመው የወንጌል መስክ ማሰማራት የሚያስገኘው ክብር በሰማያት ታላቅ ነው:: ያም ቢሆን ግን ከብዙ መከራ በሁዋላ እንጂ እንዲሁ በዋዛ አይደለም:: የእግዚአብሔር ጸጋውና መንግስቱ ያለ መከራ አትገኝምና::

+ቅዱሳኑ አባ አብሳዲና አባ አላኒቆስም ይህንን ኃላፊነት የተረዱ ነበርና ታጥቀው ሥራቸውን ጀመሩ:: እንደ ሐዋርያት ሥርዓትም ያላመነውን ማሳመን: ያመነውን በሃይማኖቱ ማጽናት: የጸናውን ደግሞ ለምሥጢራተ ቅድሳት (ሥጋ ወደሙ) ማብቃት የዘወትር ተግባራቸው ነበር::

+ቅዱሳኑ በዚህ ተጋድሏቸው ሳሉ ዜናቸው በየቦታው ተሰማ:: ነገር ግን ይህ ዝናቸው የወለደው መከራን ነበር:: በጊዜው አውሬው ዲዮቅልጢያኖስ ክርስቲያኖችን ከዋሉበት አላሳድር: ካደሩበትም አላውል ብሎ ነበር::

+ለክፋቱ እንዲመቸው በየሃገሩ ጨካኝ መኮንኖችን ሾመ:: በምድረ ግብጽም 2 ገዢዎችን ሲያኖር አንዱ አርያኖስ (በሁዋላ አምኖ ሰማዕት ሆኗል): 2ኛው ደግሞ ሔርሜኔዎስ ይባላሉ::

+እነዚህ መኩዋንንት ግብጽን ለ2 ተካፍለው: በሥራቸው ገዥዎችን ሹመው በግፍ ተግባራቸው ክርስቲያኖችን ይቀጡ ገቡ:: የስቃይ ተራው ደግሞ የ2ቱ ቅዱሳን (አባ አብሳዲና አባ አላኒቆስ) ነበርና ተከሰሱ::

+ለፍርድ ይቀርቡ ዘንድም አርያኖስ በማዘዙ ወታደሮች መጡ:: ነገሮችን አስቀድሞ የሚያውቀው ቅዱስ አብሳዲም ምንም ስለ ክርስቶስ ለመሞት ቢቸኩልም መንጋውን እንዲሁ ሊበትን ግን አልወደደም::

+ስለዚህም ወታደሮችን "እባካችሁ ሕዝቡን ልሰናበት : አንድ ቀን ታገሱኝ" አላቸው:: ወታደሮቹ ከፊቱ የሚታየው ግርማው ደንቁዋቸው ነበርና ፈቀዱለት:: ቅዱሱም ከሕይወቱ የቀረችውን 24 ሰዓት ይጠቀምባት ዘንድ ምዕመናን ልጆቹን ሁሉ ጠራ::

+ቅዳሴ ቀድሶ : ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ፈትቶ ለሁሉም አቀበላቸው:: (በጊዜው የማይቆርብ ክርስቲያን አልነበረምና)

+ከቅዳሴ መልስም የተፈጠረውን ሁሉ ነግሮ ወደ ክርስቶስ ሊሔድ እንደ ናፈቀ ነገራቸው:: ሊያስቀሩት እንደማይችሉ ሲረዱ ፈጽመው አዘኑ:: እርሱም በቀናችው እምነት እስከ ሞት ድረስ እንዲጸኑ አስተምሯቸው ከባልንጀራው ቅዱስ አላኒቆስ ጋር በወታደሮች እጅ ወደቀ::

+እነርሱም ቅዱሳኑን ወስደው በመኮንኑ አርያኖስ ፊት ለፍርድ አቀረቧቸው:: አርያኖስም የአባ አብሳዲ የፊቱ ግርማ ቢስበው ላለመግደል ወስኖ ሊያባብለው ወሰነ:: "አንተ ክቡር ሰው ነሕና ለንጉሡ ታዘዝ : ለጣዖትንም እጠን" አለው::

+ቅዱስ አላኒቆስ ግን "ክብሬ ክርስቶስ ነውና ፈጣሪየን በምንም ነገር አልለውጠውም" ሲል እቅጩን ነገረው:: እንደማያሳምነው ሲረዳም ከአባ አላኒቆስ ጋር ያሰቃዩአቸው ዘንድ አዘዘ::

+በምስክርነት አደባባይም በመንኮራኩር (አካልን የሚበጣጥስ ተሽከርካሪ ብረት ነው) አበራዩአቸው:: እግዚአብሔር ግን አዳናቸው:: እንደ ገና እሳት አስነድደው እዚያ ውስጥ ጨመሯቸው:: እሳቱም ግን ሊበላቸው አልቻለም::

+በመጨረሻም መኮንኑ አንገታቸው ይሰየፍ ዘንድ አዘዘ:: ከመሰየፋቸው በፊትም ቅዱሳኑ ጸሎትን አደረሱ:: አባ አብሳዲ ነጭ የቅዳሴ ልብሱን ለብሶ: ወደ ሰይፍ ቀረበ:: ወታደሮች ደግሞ ሁለቱን ቅዱሳን እንደታዘዙት ሰየፏቸው:: በክብርም ዐረፉ::

+"+ አባ በግዑ ጻድቅ +"+

=>እኒህ አባት በመካከለኛው ዘመን የሃገራችን ታሪክ ሰፊ ቦታን ይዘው ይገኛሉ:: ተጋድሏቸውን የፈጸሙት በደብረ ሐይቅ ነው:: ጻድቁ ብዙ ጊዜ የሁዋለኛው ዘመን ሙሴ ጸሊም ይባላሉ:: ብዙ የሕወታቸው ጐዳና ተመሳሳይ ነው::

+ልክ ቅዱስ ሙሴ ጸሊም ከኃጢአት ከሽፍትነት ሕይወት እንደ መጣው ሁሉ አባ በግዑም አስቸጋሪ ሰው እንደ ነበሩ ይነገርላቸዋል:: ከዚያ የከፋ የኃጢአት ኑሮ እግዚአብሔር ሲጠራቸው ግን ክሳደ ልቡናቸውን አላደነደኑም:: "እሺ" ብለው ንስሃ ገቡ እንጂ::

+ከዚያም በደብረ ሐይቅ (ወሎ) በፍጹም ተጋድሎ ኑረዋል:: ያዩ ሁሉም ፍጹም ያደንቁ ነበር:: ስትበላ: ስትጠጣ የኖረችውን ሰውነት ራሳቸውን ውሃ ለዘመናት በመከልከል ቀጥተዋታል:: ስለዚህም "ውሃ የማይጠጣው አባት" ይባሉም ነበር:: ጻድቁ ሲያርፉ ፈጣሪያቸው አክብሯቸዋል::

=>አምላከ አበው ቅዱሳን አሠረ ፍኖታቸውን ይግለጽልን:: ከበረከታቸውም ያድለን::

=>ታሕሳስ 27 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ አብሳዲ ሰማዕት
2.አባ አላኒቆስ ሰማዕት
3.አባ በግዑ ጻድቅ
4.አባ ፊልዾስ

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ
2.አቡነ መብዓ ጽዮን ጻድቅ
3.ቅዱስ መቃርስ (የመነኮሳት ሁሉ አለቃ)
4.ቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ
5.ቅዱስ ገላውዴዎስ ሰማዕት (ንጉሠ ኢትዮዽያ)
6.ቅዱስ ቢፋሞን ጻድቅና ሰማዕት
7.ማር ቅዱስ ፊቅጦር ሰማዕት
=>+"+ መቶ በግ ያለው ከእነርሱም አንዱ ቢጠፋ ዘጠና ዘጠኙን በበርሃ ትቶ የጠፋውን እስኪያገኘው ድረስ ሊፈልገው የማይሔድ ከእናንተ ማን ነው? ባገኘውም ጊዜ ደስ ብሎት በጫንቃው ይሸከመዋል:: ወደ ቤትም በመጣ ጊዜ ወዳጆቹንና ጐረቤቶቹን በአንድነት ጠርቶ 'የጠፋውን በጌን አግኝቼዋለሁና ከእኔ ጋር ደስ ይበላችሁ' ይላቸዋል:: እላችሁአለሁ: እንዲሁ ንስሃ ከማያስፈልጋቸው ከዘጠና ዘጠኝ ጻድቃን ይልቅ ንስሃ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ በሰማይ ደስታ ይሆናል:: +"+ (ሉቃ. 15:3-7)

   <<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
�-3� �� � � e� =� �@�
ASR by NLL APPS
ድርሳነ መድኃኔዓለም ወገድለ መብዓ ጽዮን ዘቀዳሚት ሰንበት.
https://www.tg-me.com/SinkisarZekidusan2
+ +  +እግዚአብሔር አምላክ ለሀገራችን እና ላለንበት ሀገር ሰላምን ይስጥልን አሜን++

መጽሐፈ ስንክሳር፣
ከዲ/ን ዮርዳኖስ ማስታወሻ
          
+++መልካም ዕለተ ቀዳሚት ሰንበት መልካም በቀን+
+++
Æ
Daniel:
እንኩዋን ለቅዱስ "አምላካችን አማኑኤል" : "ዕለተ ማርያም" እና "ዕለተ ጌና ስቡሕ" ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ

+*" ቅዱስ አማኑኤል "*+

=>የክርስትና ሃይማኖት እጅግ ብዙ ምሥጢራትን ያካትታል:: ታላቅ መዝገብ ነውና:: ሰዎች እናልፋለን:: ዓለምም ታረጃለች እንጂ ምሥጢረ ክርስትና አያረጅም:: እዚህ ቦታ ላይ ይጠናቀቃልም አይባልም::

+"አማኑኤል" የሚለውን ስም መረዳት የሚቻለው በአንድ መንገድ : እርሱም ምሥጢረ ሥላሴንና ምሥጢረ ሥጋዌን ጠንቅቆ በመማር ነው:: ምሥጢራት ደግሞ በእምነት ለማይኖር: በትሕትናም ለማይቀርብ የሚገለጡ አይደሉም::

+እግዚአብሔር አንድም ነው: ሦስትም ነው:: ጊዜ ሣይሠፈር: ዘመንም ሳይቆጠር እግዚአብሔር በስም: በአካል: በግብር ሦስትነቱ: በባሕርይ: በሕልውና: በመለኮትና በሥልጣን አንድነቱ የጸና አምላክ ነው::

+ከዓለም መፈጠር በፊት ስለ ነበረው ነገር የሚያውቅ ራሱ ሥላሴ ብቻ ነው:: ዓለምን ከፈጠረ በሁዋላም ምሥጢረ ሥላሴ (መለኮት) ብለን የምንማረው ትምሕርት እንድንና እንጠቀም ዘንድ እርሱ የገለጠልንን ያህል ብቻ ነው::

+ይኼውም በየጊዜው እርሱ ለወደዳቸውና ደስ ላሰኙት ቅዱሳኑ የገለጠው ምሥጢር ነው:: ከዚህ አልፈን በሥጋዊ አዕምሯችን ጌታን "እንመርምርሕ" ብንለው ግን ፍጻሜአችን ሞት: ማደሪያችንም ገሃነመ እሳት መሆኑ አይቀርም::

+ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና እግዚአብሔር በአንድነቱና ሦስትነቱ ሳለ ይህንን ዓለም ፈጠረ:: እግዚአብሔር ዓለምን ለምን ፈጠረ ቢሉ:- ስሙን ቀድሰን ክብሩን እንድንወርስ ነው:: ከዚህ የተረፈውን ምክንያት ግን ራሱ ባለቤቱ ያውቃል::

+እግዚአብሔር በሁዋለኛው ዘመን ሰው የሆነበት ምሥጢር እኛን ለማዳን ቢሆንም ይሔው ተግባሩ ዓለም ሳይፈጠር ያሰበው እንጂ በአዳም ውድቀት ምክንያት ድንገት የታሰበ አይደለም::

+እግዚአብሔር አዳምን በ7 ሃብታት አክብሮ በገነት ቢያኖረው "አትብላ" የተባለውን ዕፀ በለስ በላ:: በዚህም ከፈጣሪው ተጣልቶ: በሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ: በርደተ መቃብር ርደተ ገሃነም ተፈረደበት:: በሁዋላ ግን ንስሃ ስለ ገባ "ከ5 ቀን ተኩል (5,500 ዘመን) በሁዋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ" የሚል ቃል ኪዳንን ሰጠው::

+ከዚህ በሁዋላ ለ5,500 ዘመናት ጊዜ ወደ ታች ይቆጠር ጀመር:: ስለ እግዚአብሔር ሰው መሆንና ዓለምን ማዳንም ትንቢት ይነገር: ሱባኤ ይቆጠር: ምሳሌም ይመሰል ገባ::

+ከአዳም እስከ ሙሴ (ዘመነ አበው) ምሳሌያት ይበዛሉ:: ከሙሴ እስከ ዳዊት (ዘመነ መሣፍንት) ምሳሌያቱ እየጐሉ መጥተዋል:: ከልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት እስከ ቅዱስ ሚልክያስ ድረስ (በዘመነ ነቢያት / ነገሥት) ግን ትንቢቶች ስለ ክርስቶስና ስለ ማደሪያ እናቱ እንደ ጐርፍ ፈሰዋል::

+ነቢያትም የመሲህን መምጣት እየጠበቁ በጾም: በጸሎትና በትሕርምት ኑረዋል:: እንባቸውንም አፍሰው ቅድመ እግዚአብሔር ደርሶላቸዋል:: መድኅን ክርስቶስም ተወልዶ አድኗቸዋል::

+"አማኑኤል" የሚለው ቃል ከእብራይስጥ ልሳን (ከጽርዕ የሚሉም አሉ) በቀጥታ የተወረሰ ሲሆን ትርጉሙም "እግዚአብሔር ምስሌነ - እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆነ" እንደ ማለት ነው:: (ኢሳ. 7:14, ማቴ. 1:22) ምሥጢሩ ግን ከዚህ የሠፋ ነው::

+"አማኑኤል" ማለት "እግዚአብሔር ከሥጋችን ሥጋን: ከነፍሳችን ነፍስን ነስቶ በፍጹም ተዋሕዶ እኛን መሰለን" ማለት ነው:: በሌላ አነጋገርም "አምላክ ሰው ሆነ: ሰውም አምላክ ሆነ" እንደ ማለት ነው::

+ይሕንን ሲያደንቁ ቅዱሳን ሊቃውንት "ወዝንቱ ስም ዓቢይ: ወኢይደሉ ፈሊጦቶ-ይህ ስም ታላቅ ነው:: ወደ ሁለት ሊከፍሉት (ሊለዩት) አይገባም" ብለው ምሥጢረ ተዋሕዶን አስረድተዋል:: (ሃይ. አበ. ዘሳዊሮስ)

+ስለዚህም ከሦስቱ አካላት አንዱ ወልድ እኛን ያድን ዘንድ በተለየ አካሉና በከዊነ ቃልነቱ ፍጹም የድንግል ማርያምን ሥጋ ተዋሕዶ የሰውነትንም: የአምላክነቱንም ሥራ ሠርቶ አድኖናል::

+በማሕጸነ ድንግል ከተቀረጸባት ደቂቃ ጀምሮም ፍጹም ተዋሕዶን ፈጽሟልና መቼም መች አምላክም: ሰውም ነው እንጂ ወደ ሁለትነት: ማለትም አምላክን ለብቻ: ሰውን ለብቻ አናደርግም::

+ስለዚህም ዛሬም: ዘወትርም እግዚአብሔር ቃል የተዋሐደው ሥጋችን በዘባነ ኪሩብ ሲሠለስና ሲቀደስ ይኖራል:: እርሱ ጌታችን እስከዚህ ድረስ ወዶናልና::

+ፈጣሪያች በሦስትነቱ:- ሥላሴ (አብ: ወልድ: መንፈስ ቅዱስ): በአንድነቱ:- እግዚአብሔር: ኤልሻዳይ: አልፋ: ወዖ: ቤጣ: የውጣ: ኦሜጋ . . . እያልን እንደምንጠራው ሁሉ በሥጋዌው ምክንያት:- አማኑኤል: መድኃኔ ዓለም: ኢየሱስ: ክርስቶስ እያልን እንጠራዋለን::

+*" ዕለተ ጌና "*+

=>ከሳምንታት በፊት ጀምረን የክርስቶስን የማዳን ሥራ ለመገንዘብ እየሞከርን ቆይተናል:: በተለይ ታኅሳስ 7 ቀን "ስብከት" በሚል ስለ እግዚአብሔር ሰው መሆን ትንቢት መነገሩን: ምሳሌ መመሰሉን: ሱባኤ መቆጠሩን ተመልክተን ነበር::

+ቀጥለን ደግሞ ታኅሳስ 14 ቀን "ብርሃን" በሚል አምላካችን እንደ ምን ባለ ጥበቡ ብርሃኑን እንደ ሰጠን: አንድም ወደን ወደ ጨለማ በገባን ጌዜ ሥጋችንን ተዋሕዶ ብርሃን እንደ ሆነልን ለማየት ሞክረናል::

+ታኅሳስ 21 ቀን ደግሞ በበደላችን ምክንያት የነፍሳችንን እረኛ አጥተን ነበር:: ለእኛው በደል እርሱ ክሶ ድጋሚ መልካም እረኛችን ሆኖ በሥጋ ማርያም መለገለጡን አየን:: የዛሬው በዓል ዕለተ ጌና ደግሞ ማሠሪያው ነው::

+"ጌና" ማለት በቁሙ "ዕለተ ልደት ስቡሕ: ማለትም አምላክ ሰው የሆነበት ምስጉን ቀን" እንደ ማለት ነው:: ይህ ቀን ሁሌም በየዓመቱ "አማኑኤል (ጌና)" እየተባለ ይከበራል:: ምክንያቱ ደግሞ ጌታ የተጸነሰ መጋቢት 29 ቀን በመሆኑና ከዚህ ቀን 9 ወር ከ5 ቀናት ብንጨምር ይህ ዕለት ታሕሳስ 29 ቀን ይመጣል::

+ነገር ግን በ4ኛው ዓመት ዘመነ ዮሐንስ ዻጉሜን 6 ስትሆን 9 ወር ከ6 ቀን ስለሚሆን ቀኑን እንዳይለቅ በዘመነ ዮሐንስ ዕለተ ልደቱ ለክርስቶስ ታሕሳስ 28 ቀን ይከበራል:: ያም ሆኖ በዘመነ ዮሐንስ ታኅሳስ 28ን አክብረናል ብለን 29ን አንተወውም:: እርሱም ይከበራል::

+በዚያው ልክ ደግሞ በ3ቱ አዝማናት (በማቴዎስ: በማርቆስና በሉቃስ) ልደቱ በ29 ነው ብለን 28ን አንሽረውም:: "ጌና-አማኑኤል-ዕለተ ማርያም" እያልን እናከብረዋለን እንጂ:: ብዙ ጊዜም በተለምዶ በዓለ ልደትን "ጌና" በማለት ፈንታ "ገና" የምንል ብዙዎች አለን::

+ግን አበው ባቆዩልን ትውፊት "ጌና" ልደቱን የሚመለከት ሲሆን "ገና" ግን ባሕላዊ ጨዋታውን የሚመለከት ቃል ነው::

+*" ዕለተ ማርያም "*+

=>ዳግመኛ ይህ ቀን ዕለተ ማርያም ይባላል:: "ማርያም" የሚለው ቃል ብዙ ትርጉምን ያዘለ የእናታችንና የእመቤታችን: የተስፋችንና መመኪያችን: የድንግል እመ ብርሃን ስም ነው::

+ክርስቶስ ተጸነሰ-ተወለደ ስንል ለዚህ ሁሉ ምሥጢር ማካተቻና የድኅነታችን መጀመሪያ: የመመኪያችን ዘውድና የንጽሕናችን መሠረት ድንግል ማርያም ናትና ከፈጣሪ ቀጥሎ ታላቅ ክብር: ምስጋና: ስግደትና ውዳሴ ለእርሷ ይገባታል:: መድኅናችን ክርስቶስ ያዳነን በእርሷ ምክንያት ነውና::

+ሠለስቱ ምዕት (318ቱ ቅዱሳን ሊቃውንት) ይህንን ምሥጢር ሲያደንቁ እንዲህ ብለዋል:-
*በሥጋ ማርያም ጌታ ተጸነሰ
*በሥጋ ማርያም ጌታ ተወለደ
*በሥጋ ማርያም ጌታ አደገ
*በሥጋ ማርያም ጌታ ተጠመቀ::
*በሥጋ ማርያም ጌታ አስተማረ
*በሥጋ ማርያም ጌታ ተሰቀለ
*በሥጋ ማርያም ጌታ ሞተ
*በሥጋ

ማርያም ጌታ ተነሳ
*በሥጋ ማርያም ጌታ ዐረገ
*በሥጋ ማርያም ጌታ በአባቱ ቀኝ ተቀመጠ
*በሥጋ ማርያም ጌታ ዳግመኛ በሕያዋንና ሙታን ላይ ይፈርድ ዘንድ ከመለኮቱ ኃይል ጋር ይመጣል:: (መጽሐፈ ቅዳሴ)

+በዚያውም ላይ ለዘለዓለም ድኅነት የምንመገበው የጌታ ሥጋና ደም መለኮት የተዋሐደው የድንግል ማርያም ሥጋና ደም ነው::

<< ለድንግል ማርያም ክብርና ውዳሴ ከስግደት ጋር ይሁን !!! >>

=>የድንግል ማርያም ልጅ አማኑኤል ክርስቶስ በርሕራሔው ይማረን:: ከበረከተ ልደቱም ያሳትፈን::

=>ታሕሳስ 28 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.አማኑኤል አምላካችን
2.በዓለ ጌና ስቡሕ
3.ዕለተ ማርያም ድንግል
4."174" ሰማዕታት (የቅዱስ ዻውሎስ ማሕበር)

=>ወርኀዊ በዓላት
1.ቅዱሳን (አብርሃም: ይስሐቅና ያዕቆብ)
2.ቅዱስ እንድራኒቆስና ሚስቱ ቅድስት አትናስያ
3.ቅድስት ዓመተ ክክርስቶስ
4.ቅዱስ ቴዎድሮስ ሮማዊ
5.ቅዱስ አባዲርና ቅድስት ኢራኢ

=>+"+ የዳዊት ልጅ ዮሴፍ ሆይ! ከእርስዋ የተጸነሰው ከመንፈስ ቅዱስ ነውና እጮኛህን ማርያምን ለመውሰድ አትፍራ:: ልጅም ትወልዳለች:: እርሱ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ:: በነቢይ ከጌታ ዘንድ:-
'እነሆ ድንግል ትጸንሳለች:: ልጅም ትወልዳለች:: ስሙንም አማኑኤል ይሉታል::'
የተባለው ይፈጸም ዘንድ ይህ ሁሉ ሆኗል:: ትርጉዋሜውም እግዚአብሔር ከእኛ ጋር የሚል ነው:: +"+ (ማቴ. 1:20)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
Audio
ስንክሳር ዘወርሃ ታህሣሥ ሃያ ስምንት(፳፰)
https://www.tg-me.com/SinkisarZekidusan2
2024/09/30 10:21:46
Back to Top
HTML Embed Code: