Telegram Web Link
Forwarded from M.A
አንድ በጣም ትልቅ ቆሻሻ የጫነ ጋሪ የሚገፋ ሰው ወደ ቤትህ መጥቶ "እባክህ በርህን ክፈትልኝና ይህን ቆሻሻ አንተ ቤት ላራግፈው?" ቢልህ፣ "ውይ የሚጥልበት ቢያጣ ነው። ባይቸገር ወደ እኔ አይመጣም ነበር" ብለህ ደጅህን ከፍተህ ታስገባዋለህ? በፍጹም፤ እንደውም "እንዴት ብታስበኝ ነው? ምነው ስታየው ቤት አልመሰለህም? እንዴት ሰው በሚኖርበት ቤት ቆሻሻ ካልደፋሁ ትላለህ? ስትል ለጠብ ትጋበዛለህ። መደፈርህ እያንገበገበህ  "እምቢ!" ብለህ ትቆጣለህ። በእርግጥም ያስቆጣል።

ግን ሌላ የሚከፋ ሽታ ያለው ቆሻሻን ጭኖ ለመጣ ባላጋራ እኮ በፈቃድህ የከፈትከው ቤት አለ። "የምን ቤት?" ብለህ ብትጠይቀኝ "ልብህ ነዋ" ብዬ እመልስልሃለሁ፤ "ማን ይኖርበታል?" ካልኸኝም "እግዚአብሔር ነዋ" እልሃለሁ።

አንተ ለመኖሪያ ቤትህ ጽዳት የምትጠነቀቀውን ያህል የያዕቆብ አምላክ ለሚያርፍበት ኅሊናህ ተጠንቅቀህ ታውቃለህ? ሰይጣን ጭኖ የሚያመጣውን የኃጢአት ቆሻሻ ሁሉ እሺ ብለህ ወደ ልብህ በማስገባት የፈጣሪህን መቅደስ ለምን ታቆሽሻለህ? ንጹሑ እግዚአብሔር የሚያድርበትን ቤት ሊያቆሽሽ በመጣ ሰይጣን ላይ እንዴት አልተቆጣህም? ድፍረቱ ለምን አላብከነከነህም?

እግዚአብሔር አንተ ልትኖርበት ከምትፈልገው ንጹሕ ቤት የበለጠ ጽዱ መቅደስ የማይፈልግ ይመስልሃል?

(Dn Abel Kassahun Mekuria )

ምንጭ ፦ ቤተ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
እንኩዋን ለሐዲስ ሰማዕት ቅዱስ ጊዮርጊስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ

#ቅዱስ_ጊዮርጊስ_ሐዲስ

=>ሰማዕቱ የተወለደው በምድረ ግብጽ አሕዛብ (ተንባላት) በሰለጠኑበት የመጀመሪያው ዘመን ነበር:: በተለይ ተንባላቱ ግብፅና ሶርያን ከያዙ በሁዋላ ባልተጠበቀ ፍጥነት በኃይልም በሰውም ተደራጅተው ነበር:: ቅዱስ ጊዮርጊስ (ልብ በሉልኝ ሊቀ ሰማዕታት አይደለም) የተወለደው በዚህ አስቸጋሪ ጊዜ ነበር::

+እናቱ የተመሠከረላት ክርስቲያን ብትሆንም እንዳለመታደል አባቱ ተንባላታዊ (አሕዛብ) ነበር:: ስሙንም መዛሕዝም ይሉታል:: ሕጻኑ እንደተወለደ ያወጡለት ስም አሕዛባዊ ከመሆኑ ባለፈ በሰዓቱ መጠመቅ አልቻለም:: የወቅቱ ሕግ ከወላጆቹ አንዱ አሕዛባዊ ከሆነና አጠምቃለሁ ቢባል የሚከተለው ሰይፍ ነበር:: በዚሕ ምክንያት ሳይጠመቅ 7 ዓመት ሞላው::

+እናቱ ግን ሕጻን ቢሆንም ፍቅረ ክርስትናን ታስተምረው ነበር:: ባይጠመቅም ጸበሉን: እመቱን ትቀባው ነበር:: ደብቃ ቅዳሴ ታሰማውም ነበር:: አንድ ቀን ግን ሕጻናት ሲቆርቡ አይቶ ካልቆረብኩ ብሎ አለቀሰ:: ምን ታድርገው? ወደ ውጪ አውጥታ ከአውሎግያ (የሰንበት በረከት) አበላችው:: "ጌታየ! ልጄን እርዳው" አለች::

+ልክ በአፉ ሲቀምሳት መዓዛ መንፈስ ቅዱስ አደረበትና ፍጹም ተደሰተ:: ትንሽ ከፍ ሲል ለምን እንደማይጠመቅና እንደማይቆርብ እናቱን ጠየቃት:: "ልጄ ሆይ! ይገድሉሃል" አለችው::
ከዚህች ቀን ጀምሮ የሚጠመቅበትን ዘዴ ይፈልግ ጀመር::

+አስቀድሞ ትምሕርተ ክርስትናን ተማረ:: ለአካለ መጠን ሲደርስ አፈላልጐ ጠንካራ ክርስቲያን የሆነች ሴት አገባ:: ጥቂት ጊዜ ከቆየ በሁዋላ ሚስቱን ስለ መጠመቅ አማከራት:: "ሌላ ሃገር ሒደህ ተጠመቅ" አለችው:: ከግብፅ ተነስቶ ሶርያ ገባ:: አባቶችን አፈላልጎ ተጠመቀ:: ቀጥሎም መንገዱን ወደ ልዳ አደረገ::

+ወደ ደብሩ ተጠግቶ አባቶችን "ስም አውጡልኝ" ቢላቸው #መንፈስ_ቅዱስ አናግሯቸው "#ጊዮርጊስ" አሉት:: እሱም ደስ እያለው: ባጭር ታጥቆ የልዳውን ቅዱስ ጊዮርጊስ ያገለግለው ገባ:: ትንሽ ቆይቶ ሁከት መንፈሳዊ ተሰማው:: ማለትም ስለ ሃይማኖቱ ደሙን ማፍሰስ ፈለገና ወደ ግብፅ ተመለሰ::

+በዚያ ያሉ አሕዛብ በክርስትና ስም: ልብስና ሞገስ ሲመለከቱት ተበሳጩ:: ዕለቱኑ አሠሩት:: ሌሊት እናቱና ሚስቱ መጥተው አሉት:- "አደራ! ፍቅረ ዓለም እንዳያታልልህ:: ሰማዕት ብትሆን ላንተም ክብር: ለእኛም ሞገስ ነው" ብለውም አጽናኑት:: (እንዲሕ ያሉ እናትና ሚስት ማግኘትም ታላቅ እድል ነው!!!)

+ሐዲስ ጊዮርጊስም ጸና:: ከዚያች ቀን ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት ደበደቡት: አካሉን ቆራረጡት: ደሙንም መሬት ላይ አንጠፈጠፉት:: በየመንገዱ እየጎተቱ ተሳለቁበት:: እርሱ ግን #ክርስቶስን ወዷልና ሁሉን ታገሰ:: ሌሊት በሆነ ጊዜም ጌታችን ተገልጦ "ከሰማዕታት ተቆጠርህ" አለው::

+በማግስቱ በአደባባይ አንገቱን በሰይፍ ቆረጡት:: ክፋታቸው የጸና ነውና ሥጋውን በእሳት አቃጠሉት:: ወደ ባሕርም ጣሉት:: እናቱ ከባሕር ስታወጣው ግን ምንም አላገኘውም ነበር:: በዚሕች ቀን እናቱና ሚስቱ በክብር ቀብረውታል::

=>ቸሩ አምላክ ከሰማዕቱ ጽናትን: ትእግስትን: ጸጋ በረከትን ይክፈለን::

=>ሰኔ 19 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ጊዮርጊስ ሐዲስ ሰማዕት
2.አባ ብሶይ አኖብ ሰማዕት (በአንበሳ ጀርባ ላይ የተቀመጠ አባት)
3.ቅዱሳን "5ቱ" ጭፍሮች (በብዙ ስቃይ ሰማዕት የሆኑ ባልንጀሮች)
4.አባቶቻችን የደብረ ቁዋዐት ጻድቃን

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት
2.ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት
3.አቡነ ዓቢየ እግዚእ ጻድቅ
4.አቡነ ስነ ኢየሱስ
5.አቡነ ዮሴፍ ብርሃነ ዓለም

=>+"+ ስለዚሕ #ወንድሞቼ_ሆይ! ጣዖትን ከማምለክ ሽሹ:: ልባሞች እንደመሆናችሁ እላለሁ:: በምለው ነገር እናንተ ፍረዱ:: የምንባርከው የበረከት ጽዋ ከክርስቶስ ደም ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? የምንቆርሰውስ እንጀራ ከክርስቶስ ሥጋ ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? . . . እኛ ብዙዎች ስንሆን አንድ ሥጋ ነን:: ሁላችን ያን አንዱን እንጀራ እንካፈላለንና:: +"+ (1ቆሮ. 10:14-18)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
ፍቅር ያጌብረኒ ከመ እንግር ዜናሆሙ ለቅዱሳን"::/የቅዱሳንን ዜና(ታሪክ) እንድመሰክር ፍቅር ያስገድደኛል::  አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ /መጽሐፈ ምሥጢር/
Forwarded from Bketa @¥
Please open Telegram to view this post
VIEW IN TELEGRAM
✞✞✞🌹 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ 🌹✞✞✞

🌹 እንኳን አደረሳችሁ 🌹

🌹 ሰኔ 21 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት🌹

=>ትናንት ለስም አጠራሩ ጌትነት ይሁንና ጌታችንና
መድኃኒታችን ኢየሱስ_ክርስቶስ ወደ ሐዋርያት ወረደ:: ፊልዽስዩስ በምትባል ሃገር በዼጥሮስ እጅ
የመጀመሪያዋን ቤተ_ክርስቲያን አነጸ ብለን ነበር:: በዚህች ዕለት ደግሞ አእላፍ
መላዕክትን: ሰማያውያን ቅዱሳንን እና እናቱን ቅድስት
ድንግል
ማርያምን ይዟት ወረደ::

+ሐዋርያቱ አብዛኞቹ እዛው ሲጸልዩ አድረው ነበርና ጌታችን
ከቅዳሴው በፊት 2 ነገሮችን አሳየ:-
1.አስቀድሞ ቤተ ክርስቲያኗን በድንግል እናቱ ስም አክብሮ
ሥርዓተ ቤተ ክርረስቲያንን አሳየ::
2.ቀጥሎ ደግሞ ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ_ዼጥሮስን ከመካከል አቁሞ "አርሳይሮስ" ሲል ሾመው:: ይኼውም የዓለም ሁሉ ሊቀ ዻዻሳት
(ፓትርያርክ) ማለት ነው:: በዚህ ጊዜ ቅዱሳን መላእክት
"አክዮስ" እያሉ 3 ጊዜ አሰምተው ጮሁ:: አክዮስ ማለት በግዕዙ
"ይደልዎ": በዐማርኛው ደግሞ "ይገባዋል: ያሥምርለት"
እንደ
ማለት ነው::

+ጌታችን ይሕን ከከወነ በኋላ ይቀድስ ዘንድ ጀመረ::
¤አማናዊት ማሕደሩን ድንግል ማርያምን መንበር አድርጎ:
¤ቅዱስ ዼጥሮስ እንደ ተራዳኢ ካህን ቆሞ:
¤ቅዱስ_እስጢፋኖስ ሠራኢ ዲያቆን ሆኖ:
¤ሐዋርያት ድንግልን ከበው:
¤መላእክተ ብርሃን በክብራቸው ቁመው ጌታችን ቀድሶ
ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለወዳጆቹ አቀበለ::

+በዚያች ዕለት በፍጡር አንደበት ተከናውኖ ሊነገር
የማይችል ደስታ ተደረገ:: ከቅዳሴ በኋላ ጌታችን
ሐዋርያትን
አዘዛቸው::
"ከዚህ ቀን ጀምሮ በመላው ዓለም በእናቴ በማርያም ስም
አብያተ ክርስቲያናትን እነጹ:: ይህችን ዕለት የሚያከብራትን
አከብረዋለሁ::" ብሏቸው ከድንግል እናቱ ከመላዕክቱ ጋር
ዐረገ::

+"+ ሰኔ_ጐልጐታ +"+

=>ዳግመኛ በዚህ ቀን ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ
ይታሰባል::
ይኸውም ከሕንድ አውራጃዎች በአንዱ ወንጌልን ሰብኮ
እኩሎቹ ሲያምኑ እኩሎቹ እንቢ አሉ:: ቅዱስ ቶማስም
ያመኑትን
"ከጣዖት አምልኮና ከዝሙት ሸሹ" ብሎ መከራቸው::
+ምክሩን ከሰሙት አንዱ በዚያው ምሽት ሊጠጣ ወደ
መሸታ ቤት ይገባል:: ሰው ሁሉ ከወጣ በኋላ ባለ
መሸተኛዋ ሴት
እንደለመደችው አብረው እንዲተኙ ስትጠይቀው "እንዴት
ሐዋርያው ከዝሙት ሽሹ እያለ እንዲህ ትይኛለሽ?" በሚል
ሰይፍ
አውጥቶ አንገቷን ቆረጣት::

+እርሱ መልካም ያደረገ መስሎታል:: የሠራው ሥራ
(መግደሉ) ግን አሕዛባዊ ግብር ነው:: በማግስቱ ቅዱስ
ቶማስ ነገሩን
ሰምቶ ሰዎችን ሰበሰበና "ይህንን የአውሬ ድርጊት የፈጸመ
ማነው?" ሲል ጠየቀ:: ፈጻሚው ግን አልታወቅም በሚል
ዝም
አለ:: ወዲያው ቅዱሱ ሐዋርያ ዳቦ አንስቶ ቆረሰና
"ለበረከት እያነሳችሁ ውሰዱ" አለ:: ሰውየው ተራውን
ጠብቆ ሊያነሳ
ሲል እጁ ሰለለች::

+ሐዋርያው "ምነው ልጄ! ምን ሆንክ?" አለው:: እሱም
እንዳላመለጠ ሲያውቅ እውነቱን ተናዘዘ:: ቅዱስ ቶማስ
ግን ሕዝቡ
ሁሉ እንደተሰበሰበ ያን ወጣት ገስጾ "አስከሬኑን
አምጡልኝ" አለ:: የወጣቱን እጅ ፈውሶ "በል . . .
የገደልኩሽ
እኔ: የሚያስነሳሽ ግን ጌታየ_ኢየሱስ_ክርስቶስ ነው . . . ብለህ አንገቷን ቀጥለው" አለው::

+እንዳለው ቢያደርግ የሞተችው አፈፍ ብላ ተነሳች::
ይህንን ተአምር ያዩ አሕዛብ አምነው ተጠምቀዋል::

=>ከሐዋርያው በረከት ይክፈለን::

=>ሰኔ 21 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም
2.ቅድስት ቤተ ክርስቲያን
3.ቅዱሳን ሐዋርያት
4.ቅዱስ ዼጥሮስ ሊቀ ሐዋርያት
5.ቅዱሳን ዻውሎስና በርናባስ
6.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ
7.ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ
8.ቅዱስ ጢሞቴዎስ ዘምስር (ሰማዕት)
9.አባ ከላድያኖስ ሊቀ ዻዻሳት

❖ወርኃዊ በዓላት
1፡ አበው ጎርጎርዮሳት
2፡ አባ ምዕመነ ድንግል
3፡ አባ ዓምደ ሥላሴ
4፡ አባ አሮን ሶርያዊ
5፡ አባ መርትያኖስ
6፡ አቡነ በጸሎተ ሚካኤል

=>+"+ ስለ ጽዮን ዝም አልልም . . .
አሕዛብም ጽድቅሽን: ነገሥታትም ሁሉ ክብርሽን ያያሉ::
የእግዚአብሔርም አፍ በሚጠራበት በአዲሱ ስም
ትጠሪያለሽ::
በእግዚአብሔር እጅ የክብር አክሊል በአምላክሽም እጅ
የመንግሥት ዘውድ ትሆኛለሽ:: +"+ (ኢሳ. 62:1-3)

<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>

""ፍቅር ያጌብረኒ ከመ እንግር ዜናሆሙ ለቅዱሳን""::/የቅዱሳንን ዜና(ታሪክ) እንድመሰክር ፍቅር ያስገድደኛል::  አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ /መጽሐፈ ምሥጢር/
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
🕊

[ † እንኳን ለቅዱሱ አባታችን የዋህ ዻውሊ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፣ አደረሰን። † ]

†  በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †


🕊  †  ቅዱስ ዻውሎስ የዋህ  †  🕊

† በ፬ [ 4 ] ኛው መቶ ክ/ዘመን መጀመሪያ አካባቢ ግብፅ ውስጥ ተወልዶ ያደገው ቅዱሱ ስሙ ዻውሎስ ቢሆንም ብዙ ጊዜ የሚጠራው "የዋህ ዻውሊ" በሚል ነው:: ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ :-

የዋህ ዻውሊ ከሕጻንነቱ ጀምሮ መጻሕፍትን የተማረ: ግን ደግሞ ትዕቢት: ቁጣና ቂምን የማያውቅ ገራገር ሰው ነው:: እድሜው ለአካለ መጠን ሲደርስ ቤተሰቦቹ ሚስት አግባ አሉት:: እርሱ ባያስብበትም ወገኖቹን ላለማሳዘን አገባ:: እንዳለመታደል ሆኖ ግን ያገባት ሴት በጣም ቆንጆ በዚያም ላይ ክፉ ነበረች:: የዋህ ዻውሊ ክፋቷን ሁሉ ታግሶ ለበርካታ ዓመታት አብሮ ኖረ:: ልጆችንም አፈሩ::

አሁንም ግን እርሷ ከክፋቷ ልትታገስ አልቻለችም:: ይባስ ብሎ ዻውሊ በሌለበት ከሌሎች ወንዶች ጋር ትዘሙት ያዘች:: የዋሁ ሰው ይሕንኑ ያውቃል ግን የእግዚአብሔርን ሥራ ዝም ብሎ በተስፋ ይጠብቅ ነበር:: ለነገሩስ እሱ ያርሳል: ይቆፍራል: ነዳያንን ያበላል: እንግዳ ይቀበላል እንጂ ክፋትን ለማሰብ ጊዜ አልነበረውም::

አንድ ቀን ግን ለሥራ ወደ በርሃ ወጥቶ አንድ ግሩም ዜና ሰማ:: "አባ እንጦንስ ምንኩስና የሚባል ሕይወተ መላእክትን ጀምሯል: ደቀ መዛሙርትንም ይቀበላል" አሉት:: ግን ሚስትና ልጆች አሉትና ምን ያደርጋል?

የዋህ ዻውሊ ሙሉ ቀን ሢሠራ ውሎ ወደ ቤቱ ሲመለስ ግን የጠበቀው ሌላ ነው:: ሚስቱ በራሱ መኝታ ላይ ከአገልጋይ እረኛው ጋር ራቁታቸውን አገኛቸው:: ልብ በሉልኝ በትክሻው ሞፈርና ምሳር: መጥረቢያም ይዟል:: እርሱ ግን ክፉን አላሰበም:: ጥሩ ልብስ አንስቶ ሁለቱንም አለበሳቸው:: እንዲሕም አላቸው:- "ከዚሕ በሁዋላ እኔ አልመለስም:: ሀብት ንብረቴን ውረሱ: በደስታም ኑሩ:: የልጆቼን ነገር ግን አደራ" ብሏቸው ተነሳ::

በእጁ ምንም አልያዘም:: በትከሻው ያለችውን ብጣሽ ጨርቅ ይዞ ወደ በርሀ ተጉዋዘ:: አባ እንጦንስም ተቀብለው አስተምረው አመነኮሱት:: ከዚያች ቀን ጀምሮ ራስን ዝቅ በማድረግ: በመታዘዝ አገለገለ:: ጾም: ጸሎትና ስግደቱንማ ማን ቆጥሮት::

እያለ እያለ ከብቅዐት ማዕርግ ደረሰ:: ምዕመናንም ሆነ መነኮሳት ሊጠይቁት ሲመጡ የእያንዳንዱ ኃጢአት በግንባራቸው ተጽፎ ይመለከት ነበርና ስለነሱ ሲያለቅስ ቅንድቡ ተላጠ:: ሰውነቱም አለቀ:: አንድ ቀን ጋኔን የያዘውን ሰው ፈውስ ብለው አመጡለት:: እርሱ ግን በአጋንንት ላይ ሥልጣን እያለው በትሕትና ተጠግቶ ጋኔኑን "አባ እንጦንስን ከምጠራብህ ቀስ ብለህ ውጣ" አለው:: ጋኔኑ ግን የፈራው መስሎት በትዕቢት "እንጦንስ ማነው?" አለው::

ያን ጊዜ የዋህ ዻውሊ እንደ እሳት ከጋለ ድንጋይ ላይ ቁሞ "ሕያው እግዚአብሔር ምስክሬ ነው:: ይሕ ጋኔን ካልወጣ አልወርድም" አለ:: ወዲያው በዘንዶ አምሳል ከሴትዮዋ ወጥቶ እየጮኸ ወደ ቀይ ባሕር ገባ:: ቅዱስ ዻውሊ የዋሕም እንዲሕ በቅድስና ተመላልሶ በዚሕች ቀን በመልካም ሽምግልና ዐርፏል::

" የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር: ደስታ: ሰላም: ትእግስት: ቸርነት: በጐነት: እምነት: የውሃት: ራስን መግዛት ነው:: እንደዚህ ያሉትን የሚከለክል ሕግ የለም:: የክርስቶስ ኢየሱስም የሆኑቱ ሥጋን ከክፉ መሻቱና ከምኞቱ ጋር ሰቀሉ::" [ገላ.፭፥፳፪] (5:22)

🕊

[ † ሰኔ ፳፪ [ 22 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]

፩. ቅዱስ አባ ዻውሊ የዋሕ
፪. ቅዱሳን ወክቡራን ቆዝሞስና ድምያኖስ [ ሰማዕታት ]
፫. ቅድስት ቴዎዳዳ ሰማዕት [ እናታቸው ]
፬. አንቲቆስ: ዮንዲኖስና አብራንዮስ [ ሰማዕታት ]

[ †  ወርኀዊ በዓላት ]

፩. ቅዱስ ዑራኤል ሊቀ መላእክት
፪. ቅዱስ ሉቃስ ወንጌላዊ
፫. ቅዱስ ደቅስዮስ [ የእመቤታችን ወዳጅ ]
፬. አባ እንጦንዮስ [ አበ መነኮሳት ]

[ † አምላካችን ከቅዱስ ዻውሊ የውሃትን: ትእግስትን : በጐነትን : ጸጋ በረከትን ይክፈለን:: አሜን:: † ]

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]


         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
🕊

✞   የሰኔ ፳፫ [ 23 ]   ✞

✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞

❖ እንኳን አደረሳችሁ ❖

❖ ሰኔ  ፳፫ [ 23 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

🕊 † ቅዱስ ሰሎሞን ንጉሠ እሥራኤል †  🕊

መፍቀሬ ጥበብ :

¤ ጠቢበ ጠቢባን:
¤ ንጉሠ እሥራኤል:
¤ ነቢየ ጽድቅ:
¤ መስተሣልም [ ሰላማዊ ]  . . . እየተባለ የሚጠራው ቅዱስ ሰሎሞን የታላቁ ነቢይና ንጉሥ ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊትና የቅድስት ቤርሳቤህ [ቤትስባ] ልጅ ነው:: ከ ፫ [3] ሺ ዓመታት በፊት የተወለደው ቅዱስ ሰሎሞን እስከ ፲፪ [12] ዓመቱ ድረስ በቤተ መንግሥት ከአባቱ ጋር አድጉዋል::

ቅዱስ ዳዊት ፸ [70] ዘመን በሞላው ጊዜ የአካሉን መድከም አይቶ አዶንያስ በጉልበት እነግሣለሁ ቢልም አልተሳካለትም:: እግዚአብሔር ሰሎሞንን መርጧልና ገና በ፲፪ [12] ዓመቱ ነገሠ:: ልበ አምላክ አባቱ ዳዊት ነፍሱ ከሥጋው ከመለየቷ በፊት መከረው::

"ልጄ ሆይ ! ልብህን ስጠኝ:: ፈጣሪህንም አምልክ" አለው::

ቅዱስ ሰሎሞን እንደ ነገሠ በገባዖን ለእግዚአብሔር መስዋዕትን አቀረበ:: ጌታም ተገልጾ "ምን ትፈልጋለህ?" አለው:: ሰሎሞንም ልክ እንደ አባቱ ማስተዋልን: ልቡናን ለመነ:: በዚህም ጌታ ደስ ስለተሰኘ "አልቦ እምቅድሜከ: ወአልቦ እምድኅሬከ - ከአንተም በፊት: ከአንተም በኋላ እንዳንተ ያለ ጠቢብና ባለጠጋ ሰው የለም: አይኖርም" ብሎት ተሠወረ:: ቅዱስ ሰሎሞን ለ፵ [40] ዓመታት በእሥራኤል ላይ ነገሠ::

ግሩም በሆነ ፍትሑ: በልዩ ጥበቡ ዓለም ተገዛለት:: እግዚአብሔር የመረጣት የእኛዋ ንግስተ ሳባ /አዜብ/ማክዳም ትፈትነው ዘንድ ሒዳ ምኒልክን [እብነ መለክን] ጸነሰች:: በኋላም ታቦተ ጽዮንና ሥርዓተ ኦሪት መጣልን:: ነቢየ ጽድቅ ቅዱስ ሰሎሞን ድንግል ማርያም ከእነሱ ዘር እንደምትወለድ ነግሮት ነበርና ያበጀሁ መስሎት ሴቶችን አብዝቶ ነበር::

ነገር ግን :-

¤ አንደኛ ሰው [ሥጋ ለባሽ] ነውና:
¤ ሁለተኛ ደግሞ ከብዙ ሴቶች መካከል ከአንዷ እመ ብርሃን ትገኛለች መስሎት ነበር:: ነገሩ መንገድ ስቶበት ከአሕዛብ
[ከፈርዖን ልጅ] ጋር በመወዳጀቱ ለጣዖት አሰገደችው:: እግዚአብሔር እጅግ አዘነ::

በራዕይ ተገልጦ "ስለ ወዳጄ ስለ ዳዊት ስል በአንተ ላይ ክፉን አላደርግም" አለው:: ታላቁ ነቢይ ሰሎሞን ይህንን ሲሰማ ወደ ልቡ ተመለሰ:: ማቅ ለብሶ: አመድ ነስንሶ በፍጹም ልቡ አለቀሰ:: ንስሃ ገባ:: መፍቀሬ ንስሃ ጌታችንም ንስሃውን ተቀበለው::

የይቅርታው መገለጫም ተወዳዳሪ የሌላቸውን ፭ [5] መጻሕፍት ገለጠለት:: ተናገራቸው:: ጻፋቸው:: እሊሕም :-

፩. መጽሐፈ ጥበብ
፪. መጽሐፈ ተግሣጽ
፫. መጽሐፈ መክብብ
፬. መጽሐፈ ምሳሌ
፭. መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን ናቸው::

ቅዱስ ሰሎሞን ልዩ የሆነውን ቤተ መቅደስ በመስራቱም ይደነቃል:: ደጉ ንጉሥ: ጠቢብና ነቢይ ሰሎሞን በዚህች ዕለት በ፶፪ [52] ዓመቱ ዐርፎ ወደ ፈጣሪው ሔዷል::

🕊  †   አባ ኖብ    †    🕊

ዳግመኛ በዚህ ቀን ታላቁ ሰማዕት አባ ኖብ አርፏል:: በዚሕ ስም የሚጠሩ ብዙ ቅዱሳን ቢኖሩም ዋናው ይኼው ቅዱስ ነው::

አባ ኖብ እንደ ገዳማውያን በበርሃ የተጋደለ: እንደ ሊቃውንት መጻሕፍትን ያመሰጠረ: በተለይ ደግሞ በዘመነ ሰማዕታት ጭንቅ ጭንቅ መከራዎችን የተቀበለ አባት ነው:: ስለ ገድሉ ብዛት "ኃያል ሰማዕት": አንገቱን ስላልተቆረጠም "ሰማዕት ዘእንበለ ደም" ይባላል:: ዘመነ ሰማዕታትን ካለፉ ፸፪ [72] ቱ ከዋክብትም አንዱ ነው::

ከመፍቀሬ ጥበብ ቅዱስ ሰሎሞን: ከኃያሉ ሰማዕት አባ ኖብ በረከትን አምላካችን ይክፈለን::

🕊

[ †  ሰኔ ፳፫ [ 23 ] ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት ]

፩. ነቢየ ጽድቅ ቅዱስ ሰሎሞን [ንጉሠ እሥራኤል]
፪. ቅዱስ አባ ኖብ [ሰማዕት ወጻድቅ]
፫. ቅዱሳን መርቆሬዎስ: ፊልዾስና ቶማስ [ሰማዕታት]

[ †  ወርኃዊ በዓላት ]

፩ ፡ ቅዱስ ዳዊት ልበ አምላክ
፪ ፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት
፫ ፡ ቅዱስ ጢሞቴዎስ ገዳማዊ
፬ ፡ አባ ሳሙኤል
፭ ፡ አባ ስምዖን
፮ ፡ አባ ገብርኤል
፯ ፡ ቅዱስ ዳንኤል ነቢይ

" የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ:: ደስ አያሰኙም የምትላቸውም ዓመታት ሳይደርሱ: ፀሐይ: ጨረቃና ከዋክብትም ሳይጨልሙ . . . አፈርም ወደ ነበረበት ምድር ሳይመለስ: ነፍስም ወደ ሰጠው ወደ እግዚአብሔር ሳይመለስ ፈጣሪህን አስብ:: ሰባኪው :- "ከንቱ: ከንቱ: ሁሉ ከንቱ ነው" ይላል::" [መክ.፲፪፥፩-፱]  (12:1-9)

† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †
† ወለወላዲቱ ድንግል †
† ወለመስቀሉ ክቡር †

[ ዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ  ]


         †              †               †
▬▬▬▬▬ ▬▬▬ ▬▬▬▬▬
💖                   🕊                    💖
Audio
Forwarded from ገድለ ቅዱሳን (ባሕራን)
✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞✞✞

✞✞✞ እንኩዋን ከዘመነ ጸደይ ወደ ዘመነ ክረምት መሸጋገሪያ ለሆነችው ዕለትና ለቅዱሳኑ ዓመታዊ ክብረ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞✞✞

=>ስንዱ እመቤት ቤተ ክርስቲያን (ሃገራችን) ሁሉ ነገሯ በሥርዓት ነውና ዓመቱን በዘመናት ከፍላ ትጠቀማለች:: እሊሕም ዘመናት መጸው (ጽጌ): ሐጋይ (በጋ): ጸደይ (በልግ)ና ክረምት ናቸው:: ዘመናቱ ወቅቶችን ከመለየትና ማሳወቅ ባሻገር የእኛ ሕይወትም ምሳሌዎች ናቸውና ልብ ልንላቸው ይገባል::

+በተለይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለስም አጠራሩ ጌትነት ይሁንና "ሽሽታችሁ (ስደታችሁ) በክረምትና በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ" ብሎናልና (ማቴ. 24:20) ልንጸልይ ይገባናል:: በዘመነ ክረምት ቅጠል እንጂ ፍሬ የለበትምና ፍሬ ምግባር ሣናፈራ ሞት እንዳይመጣ: አንድም ክረምት የዝናብና የጭቃ ጊዜ በመሆኑ እንኩዋንስ ለስደት ለኑሮም አይመችምና እንደ ሊቃውንት እንዲህ ብለን እንጸልይ:-

"በዝንቱ ክረምት በመዋዕሊነ:
እንበለ ፍሬ እንዘ በቆጽል ኀሎነ:
ናስተበቁዐከ እግዚኦ ኢይኩን ጉያነ::"
(ክረምት በተባለ በእኛ እድሜ:
ፍሬ ሳናፈራ በቅጠል /ያለ መልካም ሥራ/ ሳለን:
አቤቱ ጌታ ሆይ ስደትን አታምጣብን)

=>ቸሩ አምላካችን ከዘመነ መጸው በሰላም ያድርሰን:: ተረፈ ዘመኑንም የንስሃ: የፍሬና የበረከት ያድርግልን::

=>በዚሕች ዕለት እነዚህ ቅዱሳን ይከበራሉ:-

+" ቅዱስ ይሁዳ ሐዋርያ "+

+በዘመነ ሐዋርያት ይሁዳ ተብለው ይጠሩ ከነበሩት አንዱ የሆነው ቅዱሱ የአረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ ልጅ ሲሆን እናቱ ማርያም ትባል ነበር:: እናቱ ስትሞትበት ተጎድቶ የነበረ ቢሆንም ገና በልጅነቱ ድንግል ማርያም አግኝታው በፍጹም ጸጋ አሳድጋዋለች:: አስተዳደጉም ከጌታችን ጋር በአንድ ቤት ነበር::
ጌታችን እርሱንና ወንድሞቹን (ያዕቆብና ስምዖንን) ከ72ቱ አርድእት ቆጥሯቸዋል:: ቅዱስ ይሁዳ ወንጌል ላይ ከጌታችን ጋር መነጋገሩን ዮሐንስ ወንጌላዊ መዝግቧል:: (ዮሐ. 14:22)

+ቅዱስ ይሁዳ ከጌታችን እግር 3 ዓመት ተምሮ: መንፈስ ቅዱስንም ተቀብሎ ብዙ አሕጉራትን ዙሯል:: አይሁድንም አረማውያንንም ወደ ክርስቶስ ይመልስ ዘንድ ብዙ ድካምና ስቃይን በአኮቴት ተቀብሏል:: አንዲት አጭር (ባለ አንድ ምዕራፍ) መልእክትም ጽፏል:: አጭር ትምሰል እንጂ ምሥጢሯ እጅግ የሠፋ ነው:: ቅዱስ ይሁዳን በዚህች ቀን አረማውያን ገድለውት በሐዋርያነቱ ላይ የሰማዕትነትን ካባ ደርቧል::

+" ቅዱሳን ዺላጦስና አብሮቅላ "+

=>ብዙዎቻችን መስፍኑን ዺላጦስ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ጌታችን እንዳይሰቀል ከአይሁድ ጋር ሲከራከር እናውቀዋለን:: የጌታችን ሞቱ በፈቃዱ ነበርና አይሁድ እንቢ ሲሉት የክርስቶስን ንጽሕና መስክሮ: እጁንም ታጥቦ ሰጥቷቸዋል:: የዺላጦስ ታሪክ ግን እዚህ ላይ አያበቃም::

+ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጐ ከተነሳ በሁዋላ ትንሳኤውን በራዕይ ገልጦለት አይሁድን ተከራክሯቸዋል:: ውሸታም ወታደሮችንም ቀጥቷል:: በመጨረሻ ግን በሮም ቄሳር ተጠርቶ ከእሥራኤል እስከ ሮም ድረስ ሰብኮ በሮም አደባባይ አንገቱ ተሠይፏል::

+ቅድስት እናታችን አብሮቅላም የዺላጦስ ሚስት ስትሆን ቁጥሯ ከ36ቱ ቅዱሳት አንስት ነው:: ጌታችንን ተከትላ: ቤቷን ለሐዋርያት አስረክባ: ቤተ ክርስቲያንንም በዘመኗ አገልግላ ዐርፏለች:: ዛሬ ሁለቱም ቅዱሳን ይታሠባሉ::

=>ጌታችን ከሐዋርያው ይሁዳ: ከዺላጦስና አብሮቅላም ጸጋ በረከትን ያድለን::

=>ሰኔ 25 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ይሁዳ ሐዋርያ (ከ72ቱ አርድእት)
2.ሰማዕቱ ዺላጦስ መስፍን
3.ቅድስት አብሮቅላ (ሚስቱ)
4.አባ ዼጥሮስ ሊቀ ዻዻሳት
5.የጸደይ መውጫ / የክረምትመግቢያ

=>ወርሐዊ በዓላት
1.ቅዱስ መርቆሬዎስ ሰማዕት
2.ቅድስት ቴክላ ሐዋርያዊት
3.ቅዱስ አበከረዙን ሰማዕት
4.ቅዱስ ዱማድዮስ ሶርያዊ
5.አቡነ አቢብ /አባ ቡላ/
6.ቅዱስ አባ አቡፋና ጻድቅ

=>+"+ የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ: የያዕቆብም ወንድም የሆነ ይሁዳ በእግዚአብሔር አብ ተወደው: ለኢየሱስ ክርስቶስም ተጠብቀው ለተጠሩ:
ምሕረትና ሰላም: ፍቅርም ይብዛላችሁ::
ወዳጆች ሆይ! ስለምንካፈለው ስለ መዳናችን ልጽፍላችሁ እጅግ ተግቼ ሳለሁ ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለ ተሰጠ ሃይማኖት እንድትጋደሉ እየመከርኩዋችሁ እጽፍላችሁ ዘንድ ግድ ሆነብኝ:: +"+ (ይሁዳ. 1:1)

✞✞✞ ወስብሐት ለእግዚአብሔር ✞✞✞

" ፍቅር ያጌብረኒ ከመ እንግር ዜናሆሙ ለቅዱሳን"::/የቅዱሳንን ዜና(ታሪክ) እንድመሰክር ፍቅር ያስገድደኛል::  አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ /መጽሐፈ ምሥጢር/
2024/09/29 01:24:22
Back to Top
HTML Embed Code: