Telegram Web Link
💡ሰውየው በቤቱ አንድ ትልቅ ዛፍ ነበረው አሉ፤ ይህ ዛፍ ህልውናው እንዳይጠፋ በእጅጉ ይንከባከበው ነበር። በቀን በቀን፤ ሲመሽም ሲነጋም ወደ ዛፉ እየሄደ ምርጥ ጊዜ ያሳልፋል። ከእለታት አንድ ቀን ግን፤ ይህን ግዙፍ ዛፍ ትክ ብሎ ሲመለከተው  አንዳንድ ቅጠሎቹ ቀለማቸውን እየቀየሩ እየጠወለጉ መምጣታቸውን ተመለከተ፤ ሰውየው ሃዘን ገባው። ምንም  እንኳን ዛፉ ትልቅ እና ግዙፍ ቢሆንም፤ እንደምንም ከዛፉ እላይ እየወጣ፤ የጠወለጉትን ቅጠሎች በውሃ ማራሱን ተያያዘው። ተመልሰው ነፍስ እስኪዝሩ ድረስ፤ ሽቅብ ወደ ላይ እየወጣ ቅጠሎቹን እየወለወለ በውሃ ያርሳቸዋል።

......ለብዙ ቀን እንዲህ ሲለፋ ቆየ፤ ምንም እንኳን የተቻለውን ያህል ቢለፋም ቅጠሎቹ አንድ በአንድ ከመድረቅ እና ከመጠውለግ አልዳኑም። በመጨረሻ ሰውየው ከልፋቱ ብዛት ደከመው፤ የነበረውም ውሃ በሙሉ አለቀበት። ቀስ በቀስ ዛፉ መሞት ጀመረ……..

📍ይህ ሰው ሃይል እና ጉልበቱን እንዲሁም ሃብቱን በከንቱ አባከነው። የዛፉን ስር ውሃ እንደማጠጣት፤ የጠወለጉት  ቅጠሎች ላይ ጊዜውን በማጥፋቱ፤ ዛፉን በሙሉ አበላሸው። ምን አልባት ብልህ ሆኖ ስሩን በውሃ ቢያርሰው ኖሮ፤ የጠወለጉት ቅጠሎች መልሰው ባበቡ፤ ሌሎችም ከመጠውለግ በዳኑ ነበር።

💡አብዛኛዎቻችን እንዲህ ነን፤ ህይወታችን መታደግ የሚያቅተን፤ ትኩረታችን ሁሉ፤ ስራችን ላይ ሳይሆን ቅጠላችን ላይ ስለሆነ ነው። ቅጠሎቻችን ምንድን ናቸው? ባህሪያችን፤ ልምዳችን፤ ወይም ሌሎች የአስተሳሰባችን ውጤት የሆኑ ነገሮች ሊሆኑ ይችላሉ። ስራችን ግን ማንነታችን የሚበቅልበት አስተሳሰባችን ነው። ባህሪዎቻችን ወይም ተግባሮቻችን ሲጠወልጉ፤ ስራችንን እንደማስተካከል፤ ጊዜ እና ጉልበታችንን ለውጥ በማያመጡ ነገሮች ላይ እናጠፋለን።

📍የሁላችንንም ቅጠል የሚያጠወልገው ነገር ይለያያል፤ አንዳንዶቻችን በሱስ እንጠወልጋለን፤ አንዳንዶቻችን በስንፍና፤ አንዳንዶቻንች በቂ ፍቅር ስለሌለን፤ አንዳንዶቻችን በራሳችን ባለመተማመናችን፤ አንዳንዶቻችን ተስፋ በማጣት፤ ብቻ በተለያይዩ ምክንያቶች መጠውለግ እንጀምራለን። መጠወለጉ ሲያንገፈግፈን እና እንደገና ለማበብ ስንወስን ደግሞ መላው ይጠፋብናል። በለፋን ቁጥር ይበልጥ እንጠወልጋለን፤ ልፋታችን ከንቱ ይሆንብናል። ምክንያቱም ብዙዎቻችን እንደ ሰውየው፤ ጊዜያችንን የምናጠፋው ለውጥ በማናገኝባቸው ነገሮች ላይ ነውና።

💡የሁሉም ነገር መሰረት አይምሮዋችን ነው። የጠወለገውን ክፍላችንን እንደገና ህይወት መስጠት የሚያስችለን ብቸኛው መፍትሄ አስተሳሰባችን መቀየር ብቻ ነው። እራሳችንን እንደዛፉ ብንመለከት፤ የትኛው የህይወታችን ክፍል ነው እየጠወለገ ያለው? ልፊያችንስ ከተበላሸው ባህሪያችን ማለትም ከጠውለገው ቅጠላችን ጋር ነው ? ወይስ ስር ከሆነው አስተሳሰባችን ጋር ነው?

ውብ አሁን❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanityBot
ለማግኘት በምናደርገው ጥረት ውስጥ የማጣት ሥጋት፣ ዕረፍትን በመናፈቅ ውስጥ የሕመም ፍርሃት፣ ክብርን በመሻት ውስጥ የውድቀት ሥጋት፣ ሕይወትን በማፍቀር ውስጥ የሞት ፍርሃት፣ ድልን በመጠበቅ ውስጥ የሽንፈት ውጥረት በብርቱ ይታገለናል::

💎 ንቁ አእምሮ ያለው ሰው በራስ የመርካትም ሆነ ተስፋ የመቁረጥ ሁኔታ አይታይበትም:: የዘመኑን መርዶ አዘል ዜናዎች ቢሰማም ለመኖር ከሚያሳየው ጉጉትና ጥረት አይቦዝንም:: የሕይወትን አስቸጋሪ ገጽታዎች ቢጋፈጥም “አበቃልኝ” አይልም:: ይልቁንም የወደፊት ተስፋው በፈጣሪ አስተማማኝ እጆች ውስጥ ፍጻሜ እንዳለው ስለሚያውቅ እያንዳንዱን ዕለት በብልሃት በጭምትነትና በመታዘዝ ያሳልፋል:: አመለካከት የሕይወትን ስኬትና ውጤት ይወስናልና አስተሳሰባችን የቀና ከሆነ ስኬታማነታችንም የተረጋገጠ ነው::

💫 ማናኛችንም ብንሆን መታወክ የሌለበት ከፈተናና ከውጣ ውረድ የጸዳ መሻታችን ሁሉ የተሟላበት ኑሮ ቢኖረን እንፈልጋለን፣ ነገር ግን ሠው በመሆናችን ብቻ ደስታና ሃዘን፣ ማጣትና ማግኘት፣ መውደቅና መነሣት፣ ማመንና መከዳት እንዲሁም ውጣ-ውረድ የተሞላበት መሠናክል ይፈራረቁብናል፡፡ ዋናው ነገር በነዚህ ነገሮች ተፈትኖና ነጥሮ መውጣት ከሁላችንም ይጠበቃል፡፡

ፈጣሪ ይህንን ድንቅ አዕምሮ ወይም ልዩ መክሊት ሲሠጠን በመጣው ወጀብ እንድንወሠድ ሳይሆን በጥበብና በዕውቀት ችግሮችን ፈትተን፣ ትምህርት ወስደን፣ እንደወርቅ በእሳት ተፈትነን በማስተዋል ነጥረን እንድንወጣ ነው፡፡

💎አስደሳች ፍጻሜ አጠብቅ ፣ህይወት ሁሌም ሁለትዮሽ ናት፣ መኖርን ምሉዕ የምናደርገው ሁለት ተቃራኒዎችን በሚዛን በመከወን ነው፡፡ እንባም ሳቅም፣ ደስታም ኀዘንም ፣ መስጠትም መቀበልም ፡፡  መሙላትም መጉደልም። ሲጠቃለል ፣ ሕይወት ኅብረ ቀለሟ ያማረ ቀስተ ደመና ነች።
ውብ ጊዜ❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanityBot
📍አንዳንድ ወቅት አለ ስሜት የሚነዳ ፤ የሂወት ድግግሞሽ እንደጦስ ዶሮ የሚያዳክር፤  እጅ እና እግር እንደተጠፈረ  አቅም አልባነት የሚበላ ፤ አካባቢ ላይ ምን እንደተካሄደ የማይገባህ ።

አንዳንድ ወቅት አለ ማጤን ማመዛዘን ያንተ የማይሆንበት ፤ የመረጥከው ምርጫ የሚያድሞከሙክኽ።  መባተልን የምትመስልበት፤   የመጣህበት መንገድ አሳስቶህ የማትመለስበት ።

አንዳንድ ወቅት አለ ምርጫ የሚያባትልህ ፤   የመፍዘዝ ስሜት የሚሰማህ ፤   ሰው ሁሉ  የጠላኽ የሚመስልህ ፤  ኃላ  የመቅረት ስሜት የሚንጥህ ።

አንዳንድ ወቅት አለ  ማድረግ እንደሌለብህ እያወክ  የምታከናወነው ፤ የስሜትህ ባርያ የምትሆንበት ፤ መገኘት እንደሌለብህ እያወክህ የምትገኝበት  ።

እንዳንድ እለት አለ ብልጥ ነኝ ባዮች የሚበልጡ ፤ አራዳ ነኝ ባዮች የሚያሞኝህ፤ በዝባዦች የሚበዘብዙህ፤ ባለጡንቻዎች አቅማቸውን የሚለኩብህ

እንዲም ሁሉ ሆኖ ሳለ

በግዜ እናምናለን ። ግዜ ሃያል ነው ። ሁሉም ይስተካከላል፣ መስመር መስመር ይይዛል  ።አይነጋም ያልነው ጨለማ ስንቴ ነግቷል።

አድሃኖም ምትኩ

ውብ አዳር ❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanityBot
     
❤️አንዳንዶቻችን ከደስታ ይልቅ ሃዘንን፣ ከስኬት ይልቅ ችግር ላይ መቆዘም እንወዳለን።
እንዲህ ሆኜ...ተንከራትቼ...በዚህ ወጥቼ በዛ ገብቼ እያለን ችግሮቻችንን ሁሉ እንደከንቱ ውዳሴ ስንደጋግም፣ እንዲሁ ስናከብዳቸው እንውላለን ።

❤️አዎ! እርግጥ ነው ሁሉም ሰው የራሱ የማይመቹ የህይወት መንገዶችን ያልፋል ነገር ግን ችግሩን አብዝቶ ስላወራው ብቻ ከችግሩ ነፃ ይሆናል ማለት አይደለም። ይልቅ ለችግሩ ተገዢ እየሆነ ይሄዳል እንጂ...ከዛም ባለፈ ችግሩን ማንነቱ አድርጎ ይቀበላል።

❤️ወዳጄ ሆይ እስኪ አመስጋኝ እንሁን። ማታ ተኝቶ ጠዋት መንቃት በራሱ እኮ እራሱን የቻለ እድለኝነት፣  እራሱን የቻለ መመረጥ ነው። በጤንነት ብቻ መኖር በራሱ ድንቅ ነገር፣  ድንቅ ስጦታ ነው። በተሰጠን አመስጋኝ እንሁን የቀረው ነገር ወይም የኛ አይደለም ወይም ግዜውን ጠብቆ መምጣቱ አይቀርምና።

ፈጣሪ ሆይ

ካላየኃቸው እና ከማላቃቸው አደጋዎች ስላዳንከኝ ፣ በፈተና አፅንተህ ስላጠነከርከኝ ፣በፈተናዎች ወድቄ ስለተማርኩኝ

ክበሩን አንተ ውሰድ  🙏

ስታበይ እንደመታበዬ ፣ስበድል እንደ በደሌ ፣ ስወድቅ እንዳወዳደቄ፣ ሰጠግብ እንዳጠጋገቤ በሆንኩት ልክ ሳይሆን እንደ ቸርነትህ ስለምታኖረኝ

ክበሩን አንተ ውሰድ 🙏

የሚያስፈልገኝን ሁሉ ስለምትሰጠኝ ፣ በመንገዴ ሞገስ ስለሆንከኝ ፣ ዙሪያዬ በመልካም ሰዎች ስላስከበብከኝ ።

አመሰግናለሁ 🙏

በረከቴ ስለሚታየኝ ፣ጤናዬ ስለሚታወቀኝ፣ 
ህያውነትህን ተጠራጥሬ ስለማላውቅ

አመሰግናለሁ 🙏
                    
          ውብ ዛሬ !!❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanityBot
📍ወዳጄ ሆይ

አስተውል ምድራችን ስለፍትህ በሚያወሩ ግን ደግሞ ለሕግ በማይገዙ፣ፍቅርን በሚሰብኩ ግን በፍቅር ለመኖር ምንም ጥረት በማያደርጉ፣ የፈጣሪን ቃል በሚያደምጡ ግን ደግሞ ቃሉን በማይኖሩ ሰዎች የተሞላች ናት፡፡ ልብ በል ወሳኙ ነገር የምትኖርበት ቦታ ሳይሆን አኗኗርህ ነው፡፡ ከምታምንበት ነገርም በላይ ዋጋ ሊሰጠው የሚገባው ባመንክበት ነገር እንዴት ትኖራለህ የሚለው ነው

💡ወዳጄ ሆይ፥

ከዚህ አገር እዚያ አገር ፣ ከምዕራብም ምሥራቅ ይሻል በማለት አትዋትት ። ከሁሉ የሚሻለው ሕይወትን ከነሙሉ ትርጕሟ መቀበል ነው ። ማንም ሰው ከጠባቡ ግለኝነት ሕይወት ወደ ሰፊው ጠቅላላው የሰው ልጅ ምልከታ ከፍ እስኪል ድረስ መኖርን ተማረ አይባልም፡፡ እናም ማለዳ ማለዳ አዲስ ትርጉም ባለው መንገድ ለመኖር ራስህን መመልከትህ ወደ ፊት ከመመልከት ጋር ሊዋሐድ ይገባዋል፡፡

ወዳጄ ሆይ

ሕይወት በእንግዳ ክስተት የተሞላች ናት ። የታወከ ሌሊት ሲገጥምህ በሰላም ስላደርክባቸው ሌሊቶች አለማመስገንህን አስብ ። ወዳጅና ወዳጅን አጣልቶ አንዱን የአንዱ ጠባቂ በማድረግ ትርፍ ይገኛል ብለህ አትሸወድ፣ ከፍቅር እንጂ ከሴራ አንድም ትርፍ አይገኝም። ጉድጓድ መጀመሪያ የሚቀብረው ቆፋሪውን ነውና ክፋትን አታስብ ።

💡ወዳጄ ሆይ !

እልህ ከራስ ጋር ገመድ መጓተት ነው ። የማይቀጥሉ ነገሮችን መሬት ላይ አስቀምጣቸው ፤ አየር ላይ ከተበተኑ  ጉዳት ያመጣሉ ። “የጨዋ ልጅ ሲፋታ የሚጋባ ይመስላል” እንዲሉ ። ያለትግል ያለሁካታ በሰላም መራመድን ልመድ፣ የሃያ ዓመቱም የሰማንያ ዓመቱም ሁለቱም የዕድሜ ስስት አለባቸው ። በምናልባት መኖር ጉልበት ይጨርሳል ። ውሳኔ ማጣትም ዕድሜን ይፈጃል ፣ መኖርህ አለመኖር እንዳይሆን በማስተዋል ተራመድ ።

📍ወዳጄ ሆይ

ትልልቅ ዛፎች የጀመሩት ከችግኝ ነውና ትንሽነትህ ትልቅነትህን አልደርስበትም ብሎ አይስጋ ። በትዕግሥትና በጊዜ ውስጥ የማይደረስበት ነገር የለም። ሥር የሰደዱ ዛፎች ነፋስን ይቋቋማሉ ፣ ወደ ታች የጠለቁ መሠረቶች ብዙ ፎቅ ይሸከማሉ ። ሰውም በሳል ሲሆን በፈተና ይጸናል ፣ ፈተናና ነፋስ ያልፋሉና ። ነፋሱ ዘንበል ቢያደርግህም እንዲሰብርህ መፍቀድ የለብህም ። ብዙ ጫናዎችን ለመሸከም እውቀትና ማስተዋልን ገንዘብ አድርግ ፣ በክረምት ለመዝራት ዝናቡን የተሳቀቁ የአጨዳ ዘመን የላቸውም ። ያለ ውሳኔ በዚህ ዓለም ላይ መንቀዋለል ይቻላል ፣ መጓዝ ግን በፍጹም አይቻልም።

እናም ወዳጄ

ስንኖር ብዙ ነገሮች የተቀላቀሉባቸው ሰዎች ያጋጥሙናል ። ስለ ሰላም የሚያወራው በአሳቡ ብዙ ጦርነት ላይ ነው የአሳብ ፍልሚያ ያለባቸው ፖለቲካና ሃይማኖት የተቀላቀለባቸው የጦር መሣሪያ የጨበጡ ብዙዎች ናቸው። ጦርነት የሚቀሰቀሰውም የሚቆመውም በአንደበት ነው ። “እፍ ያነዳል ፣ እፍ ያጠፋል” እንዲሉ ። አእምሮ በእውቀት ያጣራል ፣ በጥበብ ያስውባል በማስተዋል ይተምናል ። የትኛውም ሰው ከእንቅልፉ የሚነቃው የህይወቱ ብርሃን ሲበራ ነው።

🔑 ጨለማ በብርሃን እንጂ በጉልበት አይወገድም፡፡ ፈጣሪ ብርሃን ሲሆንልህ ህይወትን በመአቀፋ ስትረዳ ወደ ጠራ ማንነት ትደርሳለህ ። ድፍርስ ቡና የሚጠጣው ሲሰክን ነው። የተቀላቀለ ማንነትም ድፍርስ በመሆኑ እርካታ የለውም። ከጨለማ ህይወት የራቀና ፍጹም ብርሃን የበዛበት ህይወት ይኖረን ዘንድ ፈጣሪ ይርዳን!  

          ውብ እረፍት ❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanityBot
💎አንዳንዱ ሰው ዛሬ የሚኖርበት ቀን ትናንቱ ነው:: ትናንት ወድቆ ነበር፣ ተሳስቶ ነበር ፡፡ ትናንት የሆነ ነገር በህይወቱ አልፏል፡፡ ትናንቶቹ በትዝታ እየመጡ ዛሬውን ይነጥቁታል፡፡ የሰው ልጅ ውድቀቱ ብቻ ሳይሆን ስኬቱም ጠላቱ ነው ይባላል፡፡

📍በረጋ ውሀ ላይ ሁሉም ሰው ጎበዝ ካፒቴን መሆን ይችላል፤ግን የእውነተኛው ካፒቴን ችሎታ በማእበሉ ጊዜ ይታያል፣ እንደሚባለው ሁሉ የህይወታችንም መሪነት ትናንት አሁንና ወደፊት በገጠሙንና በሚገጥሙን መሰናክሎች ይፈተናል። የውስጥ ጥንካሬያችንም በነዚሁ ጊዜያት ይፈተሻል።

የተሳካ ህይወት መኖር የማይፈልግ ሰው ያለ አይመስለኝም፡፡ ሁሉም ሰው ታሪክ መፃፍ ይፈልጋል፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ ራሱን መመርመር አለበት ፣ የሰው ልጅ ከፍታና ዝቅታ፣ መነሳትና መውደቅ በሚገነባው የስብዕና ጥንካሬ ላይ የተንጠለጠለ ነው፡፡ ስለዚህ ይህንን በምናወራበት ሰዓት ነገ ብለን ስናስብ፣ ጊዜያችንን አዲስ ማድረግ እንችላለን፡፡ ምክንያቱም አእምሮዋችን ስላለ ፣ አእምሮዋችን ሁሉን ያስታውሳል፡፡

💎እራስን መለወጥ ቀላል ጉዞ አይደለም። እንደ አብዮት ቆጥረን ለዘመናት ተብትቦን የኖረውን ማንነት ገርስሰን መጣል አለብን ፣ ደካማው ማንነታችን ወርዶ ስኬታማው ማንነታችን ሊነግስ ይገባዋል።

ብዙዎቻችን ውስጣችን ትርምስምስ ብሏል፤ የምንፈልገውን አናውቅም፤ የምንራመድበትን መንገድ አናውቅም፤ ብዙ ሃሳቦች በውስጣችን አሉ፤ ግን በየትኛው ሃሳብ ጸንተን እንኑር? ለዚህ ነው በራሳችን ላይ አብዮት መጥራት
የሚያስፈልገን። ህይወት እጅግ አጭር ናት፤የፈለግነውን አይነት ኑሮ ለመኖር፤ እራሳችንን መለወጥ ግድ ይለናል፤ ደካማውን ጥለን፤ መልካሙን እኛነታችንን ልንተክል ጊዜው አሁን ነው።

           ውብ ቅዳሜ❤️

@Ethiohumanity
@Ethiohumanity

@EthiohumanityBot
💡ያለፈበት ብቻ ያውቀዋል!!

ትልልቅ ቦታ ላይ የደረሱን ሰዎች ስለ ትናንት ህይወታቸው ስትጠይቃቸው ሁሉም ፊት ላይ ደስተኝነትን አታነብም:: ሁሉም በእምባ እናም በትጋዜ ተሞልተው ይነግሩሀል፣ ከሙቀት ዋሻህ ውስጥ የምትወጣበት፣ከተወዳጅነት አጀብታ ለነፍስህ ፍላጎትና ለህልምህ የምትወርድበት ጥልቁና አስፈሪው የህይወት መንገድህ ነው።

📍ያስፈራል ልብ ያርዳል ነገር ግን ነፍስን ለጥበብ ይቀርፃል። በዛ ውስጥ ሰው ይርብሀል ።ተቃዋሚህ ይበዛል:: እጅ ጠቋሚው ተሳላቂው ይከብሀል:: ብታወራ የሚረዳህ አንዳች አይኖርም!! የሚፈርድ እልፍ ይሆናል...ህመሙ ጥልቅ! የስሜት ጉዳቶቹም ብርቱዎች ናቸው።

ለዚህም ነው ብዙ ሰዎች ትልቅ ህልም እያላቸው ትንሽ ሆነው መኖርን የሚመርጡት!አስፈሪውም ትልቅ ህልምህ ወደ ትልቅነት የሚመራህ በትናንሽ የህይወት ጉዳዶች ውስጥ መሆኑም ነው። ብቻህን የምታለቅስበት ብቻህን የምትፋለምበት ብቻህን ሞትን ምትናፍቅበት ግን ደግሞ ብቻህን የምትዘምርበት ብቻህን የምትፀልይበት ብቻህን አምላኬ ብለህ ከፈጣሪህ ጋር የምትነጋገርበትም መንገድ ነው።

💡መከራ የፈጣሪ ትህምርት ቤት ነው። "ስቃዮች መገፋቶች መድከሞች መውደቆች  ሁሉም የነፍስ ጥልቅ ህመሞችህ በስተጀርባ መምህሩ አምላክህ አለ።ለዛም ነው ማስተርስ ጫንኩኝ ከሚለው ሰው በተሻለ ህይወት ያስተማረቻቸው አለምን ሲመሩ ሲቆጣጠሩት የትምመለከተው!

''ሰውን ካስተማረው ፈጣሪ በጥበብ አስውቦ የቀረፀው ይበልጣል'' ከሙቀት ጎጆህ ስትወጣ! ህልምህን ከፈጣሪህ ምሪት ጋር ትከተለዋለህ! የግድ ይሆንብሀል አማራጭ ታጣለትህ ብትቀመጥ የሚወጋህ ሺ ስለሚሆን ይግድ ትጓዛለህ እየዛልክ ትጠነክራለህ እየሞትክ ህያው ትሆናለህ እየወረድክ ከፍፍ ትላለህ የግድ ይሆንብሀል...!

📍ህይወት ፊቷን የምምትሰጠው ጠንካራ ጡንቻ ላላቸው ሳይሆን ጠንካራ መንፈስ ላላቸው ነው። ከውስጥ የመነጨ ጠንካራ መንፈስ ሲኖረን ምንም ያህል ችግር ምንም ያህል ስቃይ ከላያችን ቢረበረቡ ምንም ሳያሳስበን
ምንም ተስፋ ሳያስቆርጠን ወደፊት
ግስጋሴያችንን እንቀጥላለን። ሩጫችንንም መሰናክሉን እያለፍን እንሮጣለን።

💡ወደ ቁልቁለቱም ድፈር! ወደ አስፈሪው መንገድ በድፍረት ጥለቅ ፣ አንድ ሰው መሰረታዊ እሱነቱን በቀጥታ መጋፈጥ አለበት። ለብቻው ሆኖ አይምሮውን በመክፈት ውስጡ ያለውን ነገር መመልከት አለበት። ይህ የድፍረት ተግባር ነው። ከውስጥ ወዳለው ሲዖል ለመግባት የሚያስችል የድፍረት ተግባር....። እርቃን ማንነትን ለመመልከት የሚወሰድ የድፍረት እርምጃ ነው። ታላቅ ድፍረት ያስፈልጋል።

📍የህይወትህን ሲኦል ካልተጋፈጥክ የስኬትህን ብርሀን መቼም አትለብሰውም ፣ የከፍታውን መንገድ በመውርደት ፣ የደስታውን መንገድ በሀዘን ፣ የንግስናን መንገድ በባርነት ፣ የመሪነትን መንገድ በተመሪነት ፣ የስኬትንም መንገድ በውድቀት በኩል ውስጥ ትገናኛቸዋለህ!

አለም ለደፋሮች ታደላለች። ወደ ከፍ ያለ ማንነት ጉዞ ፣ስትጀምር የነፍስክ ጥንካሬ ተአምራዊ ወደ ሆነ ቦታ ያደርሥሀል፣ ድፋር ሁን! ለህልምህ ቆራጥ ሁን ፣ የህይወት ብርሀንህ የሚወለደው ከዛ እርምጃህ ነው!

ዉብ ጊዜን ተመኘን

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanityBot
የዛሬ ደስታህ የዛሬ ነው። የነገ ደስታህ የነገ ነው። ፈጣሪ አንተን የሚያስደስትህ ነገር ሊሰጥህ ምንም እጥረት የለበትም። አንተ ብቻ በሆነውም ባለህም በሚሆነውም በሁሉም ተደሰት። ውስጥህ የሚያሳምምህን ሳይሆን የሚያስደስትህን እይ። ውስጥህ የሚያሳዝንህን ሳይሆን የሚያዝናናህን እይ።

ውስጤ ያለችውን ትንሽዬ ደስታ አስተውዬ ባየሁ ጊዜ ግን የፈጣሪን መልካምነትና ቸርነት አያለሁ። የፈጣሪን ደግነትና ቅንነት አስተውላለው። ከምንም በላይ የፈጣሪን ፍቅር አያለሁ። በየቀኑ በየሰአቱ በየደቂቃው ከስምንት ቢሊዮን የዓለም ሰው ሁሉ እኔንም አለመርሳቱ ይደንቀኛል። ውስጤ በፈጣሪ የተቀመጠችውም ትንሽዬ የደስታ ቅባትም በአካሌ ውስጥ ካሉትና በላዬ ላይ ከተፈጠሩት አሉታዊ ነገሮች ሁሉ ትልቃለች።

💡ውስጤ ያለችው ሚጢጢዬ የደስታ ፍንጣቂ ካጋጠሙኝ የሂወት መሰናክሎች ሁሉ ትገዝፍብኛለች። ያኔ ላለመሳቅ ምክንያት አጣለሁ። ከውስጤ የተፈጠረው ደስታ በፊቴ ላይ ይደገማል። መጀመሪያ ውስጤ ይስቃል በመቀጠል ጥርሴ። ከዛ ደሞ የኔ ደስታ ከኔ አልፎ በዙሪያዬ ያሉት ላይ ይጋባና እነሱም ይስቃሉ።

የእውነት ፈጣሪ እንዴት ድንቅ ነው። በሱ ላይ እምነታችንን በጣልን ጊዜ ልባችንን በደስታ ፊታችንን በፈገግታ ይሞላዋል! በእውነት የፈጣሪን ጥበበኝነት መመስከር ከፈለጋችሁ በምንም አይነት ሁኔታ ውስጥ ብትሆኑም ውስጠ ውስጣችሁን ተመልከቱ። ያኔ የምታገኙት የደስታ ጨረር ከከበቧችሁ ችግሮች ሁሉ ይበልጡባችኋል። ያኔ ከልባችሁ ትስቃላችሁ።

📍የበለጠ የፈጣሪን የእውቀት ጥግ ደሞ የምታዩት በምንምና በየትኛውም ጊዜ ለእያንዳንዳችን እደግመዋለሁ ለእያንዳንዳችን የሚሆን ደስታ ሰቶናል! እሱ ጋ ስስት የለም። እሱ ጋ ማዳላት የለም። የተወሰኑትን አስደስቶ የተወሰኑትን የሚያስከፋ ሚዛናዊ ያልሆነ አምላክ አይደለም። ውስጣችንን በደንብ ማየት ስንጀምር በገንዘብ ልንገዛው የማንችለውን ደስታ እናገኛለን። ይህም ደስታ ሳቅን ይፈጥርልናል። ጥርሳችንም ከልብ በመነጨ ደስታ ፈገግ ይላል።

💡ዛሬ ይህንን በውስጣችን ያለውን ደስታ የምናይበትና ፊታችንን በሳቅ የምንሞላበት ቀን ነው። አስተውለን ወደ ውስጥ እንይና ውስጣችን ያለውን ደስታ በፊታችን ላይ እንዲንጸባረቅ እንፍቀድለት!ውስጣችንን ስናይና ፈጣሪ ውስጣችን ያስቀመጠውን ድንቅ ስጦታ ስናስተውል ፤ያኔ አለመሳቅ ይከብደናል። አለመደሰት ታሪክ ይሆናል። ከፈገግታችሁ ጀርባ ያሉትን ብዙ ችግሮች መከራዎችና ማጣቶችን ሳይሆን ትንሿን ጥሩ ተአምር እዩ፤ያኔ ትንሿ ብዙ ትሆናለች። ከውስጥ የተጫረችው ሚጢጢዬም የደስታ ፍንጣቂ ከናንተ አልፋ ለዓለም ሁሉ የምትበቃ ትሆናለች።

🔑 ከውስጥህ ያለው ብዙ ነው። ከውስጥሽ ያለው ድንቅ ነው። ፈጣሪንም ለሰጣችሁ ሁሉ አመስግኑ! እውነቴን ነው ውስጠ ውስጣችሁ ያለውን ስታስተውሉ (ማየት ብቻ አይደለም ማየት ወስጥ ማስተዋል ካልተጨመረበት ትርጉም የለውም) ያኔ ባላችሁ ሁሉ ትገረማላችሁ።

ብሩክ የሺጥላ

ውብ አሁን❤️

@Ethiohumanity
@Ethiohumanity

@EthiohumanityBot
💡የተለያየ ድርሻ መያዛችን ሕይወትን የተሟላች ያደርጋታል፡፡ ሰዎች እንደ እኛ ካላሰቡ የተሳሳቱ ፣እንደ እኛ ካልተናገሩ ቋንቋ ያበላሹ ፣እንደ እኛ ካልኖሩ የሞቱ እንደ እኛ ካልሰሩ ሥራ የፈቱ አይደሉም ሌሎች አስፈላጊያችን የሚሆኑት እኛ የማንችለውን ሲያውቁና ሲያደርጉ ነው፡፡

📍ሁሉም ሰው ዶክተር ቢሆን ያለገበሬ ምን ይመገባል?? ዶክተሩ በእውቀቱ ተመክቶ ገበሬውን አንተ አታስፈልገኘም ቢለው ይሞኛል እንጂ ምን ይበላል? የላይኛው ከታችኛው የግድ የሚፈላለግበትን ጥምረት ተፈጥሮ ሰጥታናለች ፣ እኛም የድርሻችንን ተሰጦ ተቀብለናል፣ ስለዚህ አንዱ አንዱን አታስፈልገኘም ሊለውና ሕይወትን ብቻውን ሊመራ አይቻለውም፡፡ ትልቁ የኑሮ የኑሮ ሚስጢር " እኔ ለአንተ ፣ አንተ ለእኔ" የሚል ነው፡፡

🔷የጥቁሮች መብት ታጋይ  የነበረው ማርቲን ሉተር ኪንግ፡-  አላባማ እያለሁ ጫማዩን የሚጠርግልኝ አንድ ሊስትሮ ነበር፡፡ይህን ሊስትሮ ስመለከት ወደ አእምሮዬ የሚመጣ ነገር ቢኖር የቱንም ያህል ጫማዬን ብጠርገው እንደእርሱ አድርጌ ላሳምረው አለመቻሌ ነው፡፡ ስለዚህም ይህ ልጅ በጫማ ማሳመር የዶክትሬት ዲግሪ አለው ብዬ ተቀበልኩ፡፡ ከኔም የተሻለ ስለሆነ አከበርኩት" ብሏል፡፡

💡የትኛውም እውቀታችን አዋቂ የሚያሰኘን ላላወቁት በምናደርገው መንገድ ብቻ ነው፡፡ ምክንያቱም እውነተኛ እውቀት የአገልጋይነት እንጂ የጌትነት መንፈስ የለውምና፡፡ የእኛ እውቀት አስፈላጊ የሚሆነው የማያውቁ ስላሉ ነው፡፡ ሁሉም ቢያውቅ እውቀታቸው አለማወቅ ይሆናል ስለዚህ የማያውቁትን አክብረን ማገልገል ይኖርብናል፡፡

🔷የትኛውም ሀብታችን ባለጠጋ የሚያሰኘን በችግር ለሚያቃስቱት ባፈሰስነው ልክ ነው፡፡ ራሱን የቻለ ባለጠጋ አይባልም፡፡ለሌሎች የተረፈ ግን ባለጠጋ ይባላል፡፡ስኬታችን የሚለካው ራሳችንን በረዳንበት መጠን ሳይሆን በሌሎች በተረፍንበት መጠን ነው፡፡

♦️ዛሬ ኑሮአችንንና ሕይወታችንን እንዲገዛው የፈቀድንለት ነገር ቢኖር ንቀት ነው፣ ሌሎች እንዲያከብሩን እንፈልጋለን ፣ እኛ ግን ሌሎችን መናቅ እንሻለን፡፡ ሌሎችን መናቅ በአዋጅ የተፈቀደልን ሥልጣን ይመስለናል፡፡ ሌሎችን በንቀት ዝቅ ካላደረግን የተስተካከልናቸው አይመስለንም፡፡

💡ስለዚህ የበላይነት ስሜታችን የበታችነት መንፈስ የወለደብን ነው፡፡ የምንኖረው ለመስጠት ብቻ ሳይሆን ለመቀበልም ነውና ሌሎችን...ማክበር ደግሞም ፈጣሪ የምንሰጠውን አስታቅፎ ወደ ዓለም ልኮናልና አደራችንን ማድረስ ይገባናል፡፡

በቤታችን ፣ በሥራ ቦታችን ፣ በአገልግሎታችን እየሰራን ያለን እኛ ብቻ መስሎ ከተሰማን ሌሎች የሠሩት አይታየንም፡፡ ሌሎችን መውደድ ያቅተናል፡፡ ሥራችንም ከጥቅሙ ኩራቱ እየገነነ ይመጣል፡፡ በሌሎች ላይም እምነት እያጣንም የርክክብን ሥርዓት እናፈርሳለን፡፡ ራሳችን አልሚ ሌሎችን አጥፊ ሆነው እየታዩን ነቃፊ ብቻ እንሆናለን፡፡

🔷የዓለማችን ትልቁ የኢኮኖሚ አቅም ፣የሰላም መሰረት ግብረ ገብነት ወይም የሞራል ሕግ ነው፡፡ የሥነምግባር መሰረቱ ሃይማኖት ነውና ሃይማኖትን መጥላት ተገቢ አይደለም፡፡ብዙ ባለ ራዕዯች ነን የሚሉ ሃይማኖትን በቀና መንፈስ አያዩትም፡፡ሃይማኖት ግን የልምድ ሳይሆን የተፈጥሮ መሻት ነው፡፡ መስራት ፣ መማር ፣ መልፋት ፣ መትጋት ብቻውን በቂ አይደለም ሃይማኖት ያስፈልጋል፡፡

♦️ዓለም ድፍርስ ውሃ ናት፡፡ ስለዚህ የጠራ ማንነትን አታሳይህም፡፡ እንደውም እውነትን የምትሸፍን የሽንገላ አዙሪት ውስጥ በመሆኗ ምንም ያልበራለትን የብርሃናት አለቃ፣ አጥፊውን አልሚ ፣ ሰነፉን የትጉሃን አለቃ እያለች ትሾማለች፡፡  የኑሮአችን ባህልም ግለኝነት ባጠቃው "አኔ ለእኔ " በቻ በሚል ራስ ወዳድነት መንፈስ የተከበበ ነው፡፡ ሰዎች መንፈሳዊ መፅሐፍትን የሚጠሉት እውነት ስላልሆነ ሳይሆን ኃጢአጣቸውን ስለሚነግራቸው ነው፡፡ ዛሬ ድረስ የሰው ልጆች ይህን ሀቅ አልተረዱትም አሁንም ሌላውን እንጂ ራሳቸውን ዞር ብለው ማየት አልቻሉም፡፡

🔷ስለዚህ የኛ ድርሻ ቆም ብሎ ማሰብ ነው። ቆም ብሎ ማሰብ ይጠቅማል፣ ቀጥሎ መመልከት ከዚያም መጠየቅ በመጨረሻም መጓዝ ነው፡፡ ካልቆምን መመልከት ፣ ካልተመለከትን ማስተዋል ፣ ካላስተዋልን መጠየቅ ፣ ካልጠየቅንም መጓዝ አንችልም፡፡ መቆም ለቀጣዩ ጊዜ ያዘጋጃል ፣ ለቀጣዩ ጉዞም ኃይል ይሰጣል ፡፡

♦️በክፉ ጎዳና የሚጓዝ መቆም ያስፈልገዋል ፡፡ የመጣበትንና የሚሔድበትን የሚያየው በመቆም ብቻ ነው፡፡ በመቆም በፀጥታ ውስጥ ሆኖ ራስን መገምገም ፣ ከዚያም መመልከት ቀጥሎም መጠየቅ በመጨረሻም ዕረፍት ወዳለበት የራስ ደሴት መጓዝ፡፡

             ውብ ቅዳሜ❤️

@Ethiohumanity
@Ethiohumanity

@EthiohumanityBot
📍ወዳጄ ሆይ

ሥር የሰደዱ ዛፎች ነፋስን ይቋቋማሉ ፣ ወደ ታች የጠለቁ መሠረቶች ብዙ ፎቅ ይሸከማሉ ። ሰውም በሳል ሲሆን በፈተና ይጸናል ፣ ፈተናና ነፋስ ያልፋሉና ። ነፋሱ ዘንበል ቢያደርግህም እንዲሰብርህ መፍቀድ የለብህም ። ብዙ ጫናዎችን ለመሸከም እውቀትና ማስተዋልን ገንዘብ አድርግ ። አንተም እንደዛፉ ስር ስደድ ጠንካራነት እውቀት አለው ፣ በጥበብ ይናገራል ፤ ተግባር አለው ። ጠንካራነት ስሜት ሳይሆን ተግባር ፣ ፉከራ ሳይሆን ድርጊት ነው ። ጠንካራነት ሞራልም ምግባርም ነው።

📍ወዳጄ ሆይ

ፊት የልብ አደባባይነውና ሁሉን ቅሬታህን ፊትህ ላይ አታስነብብ፡፡ ጠላቶችህ ፊትህን እንጂ ልብህን እንዲያዩ አትፍቀድ፡፡ ለስድባቸው ስድብን አትመልስ ጆሮ ሰጥቼ ሰምቻችኀለሁ ማለት ነውና፡፡ ለአሳማሚዎችህ በቸኛው ማለፊያ ታምሞ አለመጠበቅ ነው ። ታመህ ካልጠበቀቻው ጆሮ ሰትጠህ ዝቅ ካላልክላቸው የሚያሳምምህ የለምና፡፡ ከራስህ ጋር ሳትመክር ከሰው ጋር አትመካከር፡፡ ለአንድ ሀሳብ የሶስት ቀን እድሜ ስጠው፡፡ ባዕድ ባለበት ስለቤትህ አታውራ፡፡  ለግቢህ አጥር ፣ለቤትህ በር፣ለህይወትህ ሚስጥር ይኑርህ፡፡ የተሻልክ ሳይሆን የበለጥክ ሁን፡፡

📍ወዳጄ ሆይ

መሬትህ በሚሸከመው መጠን ቤትህን ሥራ ፣ ወዳጅህ በሚችለው መጠን ምሥጢር ንገረው ፣ ተማሪህ ባደገበት መጠን መግበው ። የሌላው የሆነችውን ሴት ላንተ አትመኝ ። ያንን ጥላ ስትመጣ አንተን ጥላህ መሄድ እንደምትችል እያስተማርካት ነው ። አንቺም የሌላውን ባለትዳር አትመኚ ።

📍ወዳጄ ሆይ

ብትታመም በአገርህ ትታመማለህ ። አገርህ የታመመች ከሆነች ግን ዓለም ዝግ ይሆንብሃል ። ተሰደህም ለመከበር አገር ያስፈልግሃል ። ከሰላም የበለጠ ሀብት ፣ ከማስተዋል የበለጠ ሥልጣኔ ፣ ከፍቅር የበለጠ ደስታ የለም ። ያለ ፈጣሪ እየተስፋፉ ያሉ ሰዎች እየጠበቡ ነው ። ልብስ ጸድቶ ልብ ከቆሸሸ የመንፈስ ነጻነት ገና አልመጣም ። የድሮ ሰው ልቡ ንጹሕ ፣ ልብሱ አዳፋ ነበር ። የዛሬ ልጅ ልብሱ ንጹሕ ፣ ልቡ ሸርታታ ነው።

📍ወዳጄ ሆይ

የሰብዊነት ሥራ ለሰው ሁሉ የሚደረግ የደግነት ስራ ነው፣ ደግ ለመሆን ጥግ አትያዝ ። ከሥርህ ያለው አንተ የማትችለውን የሚችልልህ ነውና አክብረው ። ቆጥረህ ከሰጠህ ስጦታህ ይረክሳል ። ደብቀህ ከሰጠህ ስጦታህ ሲወራ ይኖራል ። ከፍ ስትል ልታይ ካልክ ሁሉም ሰው ስትወድቅ ያይሃል ። በከፈትክለት መጠን ጠላት ይገባል ። ሰይጣን አስገድዶ ሳይሆን አዘናግቶ የሚገድል ጠላት ነው ።

💡እናም ወዳጄ

የታወከ ሌሊት ሲገጥምህ በሰላም ስላደርክባቸው ሌሊቶች አለማመስገንህን አስብ ። ቀኑ መብትህ ሳይሆን ስጦታህ ነውና አመስግንበት ። እሰይ ነጋ ማለት ሲገባህ ደሞ ነጋ አትበል ።ሲያነጋልህ ምንም ክፈያ ላላስከፈለህ ጌታ የማለዳ ምስጋና ለማቅረብ አትዘግይ ። ወጥቶ የመግባት ዋጋው ትልቅ ነውና የምሽት ጸሎትህንም አታስታጉል ። እያጣጣርክ ስለ ጤና ከመጸለይ በጤናህ ፈጣሪህን አመስግን ።

ውብ ጊዜ❤️

@Ethiohumanity
@Ethiohumanity

@EthiohumanityBot
💡ስሙኒ ይቀራል

📍ከአንድ ሰው በራፍ ላይ ቁጭ ብሎ ድንች የሚሸጥ ምሲኪን ሰው ነበረ። የቤቱ ባለቤት ሁሌም ወደ ውጪ ሲወጣ ይህንን ምስኪን ሰው ይመለከተው ነበረ። ቀኑን ሙሉ ብርድና ጸሀይ እየተፈራረቀበት ኑሮን ለማሸነፍ መድከሙ ስላሳዘነው በአቅሙ ሊረዳው ወሰነ።

💡ነጋዴው አንዷን ድንች በ50 ሳንቲም ነበር የሚቸረችረው። ታዲያ ይህ ሰው ምስኪኑን ነጋዴ ለመርዳት በማሰብ በየቀኑ የአንድ ድንች ዋጋ እየሰጠው ለመሄድ ወሰነ። በየቀኑ 50 ሳንቲሙን እየሰጠው በአንጻሩ ምንም ድንች ሳይቀበል ይሄዳል። ከብዙ ጊዜ በኋላ ይህ ሰው እንደለመደው 50 ሳንቲሙን አኑሮለት ጉዞውን ቀጠለ።

ድንገት ከኋላው “ጌታዬ” የሚል ጥሪ ይሰማል። ዞር ብሎ ሲመለከት ምስኪኑ ነጋዴ ነበር በሩጫ የደረሰበትና የጠራው።

ሰውየው በፈገግታ “ከስንት ጊዜ በኋላ ለምን በቀን በቀን 50 ሳንቲም በነጻ እየሰጠሁ እንደማልፍ ልጠይቀኝ ነው ያስቆምከኝ?” አለው

ነጋዴው ግን እያለከለከ “አይደለም ኸረ” ሲል መለሰ። ይሄኔ ሰውየው ግራ ገብቶት

“እና ለምን አስቆምከኝ?” ቢለው

“የድንች ዋጋ 75 መግባቱን ልነግርዎት ነው፤ እናም ስሙኒ ይጎድላል” አለው አሉ።

💡ይህንን ታሪክ የሰማሁኝ ቀን በጣም አስቆኝ ነበር። መለስ ብዬ ሳስበው ግን ከቀልድነቱ በላይ የሰው ልጅን የአልጠግብ ባይነትና ያለማመስገንን ባህሪ የሚያንጸባርቅ መስሎ ታየኝ። ሰዎች አመስጋኝ ፍጡሮች ነን ብዬ አላምንም። ልክ እንደዚህ ምስኪን ነጋዴ ነጻ በሚሰጠን ነገር ላይ እንኳን እንደራደራለን። የእኛ ባልሆነው ሀብት እንሟገታለን። በቸርነት በተሰጠን ነገር ሁሉ ይበልጥ እንጠይቃለን። ሃምሳ ሳንቲም ለምን በነጻ ተሰጠኝ ሳይሆን ለምን ስሙኒ ጎደለ የሚል አመለካከት ስላለን እኮ ነው አብዛኛዎቻችን ባለን ነገር መደሰት የሚያቅተን።

📍ብዙ ጊዜ ከፈጣሪ ጋርም ሆነ በየእለት ኑሮዋችን በነገሮች ላይ የምንደራደረው ልክ እንደዚህ ምስኪን ነጋዴ ነው። በነጻ የሚሰጠንን 50 ሳንቲም ሳይሆን የኑሮዋችንን ዋጋ እራሳችን ተምነን ቀሪው ጎደለ ብለን እንሟገታለን። ስዎች የሚሰጡንን ነጻ ፍቅር፤ ነጻ ክብር፤ ነጻ እምነት ዋጋ የማንሰጠው ቀሪውን ስሙኒ ስለምናስብ ነው።እኛ በባህሪያችን ነጻ የሆነን ነገር ዋጋ አንሰጠውም፣ የሚያስደንቀው ግን የሰው ልጅ በምንም ያህል ገንዘብ ሊገዛቸው የማይችላቸው ሀብቶቹ በሙሉ በነጻ የሚያገኛቸው ናቸው።

💡በ50 ሳንቲሙ ያልተደሰተና ያላመሰገነ ሰው ስሙኒ ቢጨመርለት ምን ዋጋ አለው? በየቀኑ የሚቸረን 50 ሳንቲም ከበቂ በላይ ነው፤ አንዳንዴ ስሙኒው ይቀራል ብለን ሰጪውን ባናስቀይም መልካም ነበር፤ ነገር ግን ሰው ነን!!! ብዙ ጊዜ ደስታችንን የሚነጥቀን የ “ስሙኒ ይቀራል” አይነት አመለካከታችን ነው። የተሰጠንስ 50 ሳንቲም? የተሰጠን ነጻ ፍቅር፤ ነጻ ክብር፤ ነጻ እምነት፤ ነጻ ጤንነት፤ ነጻ ተስፋ? ከምንም በላይ ነጻ ህይወትስ?

ሚስጥረ አደራው

ውብ አሁን❤️

@Ethiohumanity
@Ethiohumanity

@EthiohumanityBot
💚ከትሕትና የበለጠ መልካም ነገር የለም። የደካማነት መገለጫ አይደለም ፣ ትህትና የትንሽነት ምልክት አይምሰልህ ፣ የዋህነት ደካማነት ሳይሆን የለስስት የመኖር ችሎታ ነው፣ ደግነት የመልካም ሰው የህይወት መምርያ ነው። ትህትና ዝቅ ላሉት የምናሳየው ፍቅርና ክብር ነው፡፡ ፍሬ ያለው ዛፍ ዘንበል ይላል ቀና የሚሉት ፍሬ የሌላቸው ናቸው፡፡ትህትና የልብ ነው፡፡

አየህ አንተ ባታስበውም አንተ የምታስፈልጋቸው ብዙ ሰዎች አሉ ፣ ያንተ መኖር የሚያኖራቸው አያሌ ሰዎች አሉ ። ህይወትም ትርጉሟ የሚጨምረው ለሌሎች መኖር ስንጀምር ነው፣ ምንም የለኘም ምንም መስጠት አልችልም አትበል ያለህን ካሰብከው ብዙ ነገር ማድረግ ትችላለህ፡፡

💛"ሰው ሁሉ በልቡ ያለውን ይሰጣል።"
በውስጥህ ያለውን ነው የምትሰጠው ፣ ሁሌም ደግ ሁን። ቸር ለመሆን ሃብት እስክታገኝ አትጠብቅ። አንዳንዶች ካንተ የሚፈልጉት ፈገግታህን ነው ፤ አንዳንዶች ሰላምታህን ፤ አንዳንዶች ጊዜህን ፤ አንዳንዶች ሃሳብህን ፤ አንዳንዶች ድጋፍህን ፤ አንዳንዶች ጓደኝነትህን ሊሆን ይችላል ።

❤️ሁላችንም ለሌላው የምናካፍለው ብዙ ነገሮች አሉን ፈገግታ እና ደስታችን እንኳን የምናውቀውን ሰው ቀረቶ የመንገደኛውን ሰው ቀን ብሩህ የማድረግ ሃይል አላቸው። ሀብታም ሁን ወይም ደሀ ደግነትህን በዛ ሚዛን አትመዝነው! ዋናው የሚያስፈልግህ ሀብታም የሆነ  ልብ ብቻ ነው"!

              ውብ አዳር ❤️

@EthioHumanity
@EthioHumanity

@EthioHumanitybot
2024/06/24 13:26:42
Back to Top
HTML Embed Code: