Telegram Web Link
+++ በእርሱ ቊስል እኛ ተፈወስን +++

    ‹‹ጲላጦስም የካህናት አለቆችንና መኳንንትን ሕዝቡንም በአንድነት ጠርቶ እንዲህ አላቸው ፡- ሕዝቡን ያጣምማል ብላችሁ ይህንን ሰው ወደ እኔ አመጣችሁት  ፤ እነሆም በፊታችሁ መርምሬ ከምትከሱበት ነገር አንድ በደል ስንኳ በዚህ ሰው አላገኘሁበትም፡፡ ሄሮድስም ደግሞ ምንም አላገኘም ፤ ወደ እኛ መልሶታልና ፤ እነሆም ለሞት የሚያደርሰው ምንም አላደረገም፡፡ እንግዲያስ ቀጥቼ እፈታዋለሁ አላቸው›› (ሉቃ. ፳፫፥፲፬‐፲፮)

    ጲላጦስ የጌታችንን ንጹሕ መሆን ካወቀ በኋላ ‹ቀጥቼ እፈታዋለሁ› አለ፡፡ ንጹሕ በመሆኑ ምክንያት የተቀጣ ከጌታችን በቀር ማን አለ? ጲላጦስ አይሁድን ደስ ለማሰኘት ስለፈለገ ያን ሁሉ ጥያቄና መልስና ሕጋዊውን የፍርድ ሒደት ማስፈጸም ትቶ በንጹሑ ጌታ ላይ ግርፋት እንዲወርድበት ፈረደ፡፡

    ነቢዩ ኢሳይያስ ‹‹በውርደቱ ፍርዱ ተወገደ›› ብሎ እንደተናገረው ትንቢት ጲላጦስ በእርጋታ ጀምሮት የነበረውን ሕጋዊ የምርመራና የፍርድ ሒደት አሽቀንጥሮ ጥሎ (አስወግዶ) ከሕግ ውጪ በዚያች ቀን በአይሁድ እጅ የተዋረደውን ጌታ ያለ ፍትሕ እንዲገረፍ ወሰነበት፡፡ (ሐዋ. ፰፥፴፫)

    ጲላጦስ ‹‹ኢየሱስን ይዞ ገረፈው›› (ዮሐ. ፲፱፥፩) የጲላጦስ አሳብ ‹በመሰቀሉ ፈንታ ግርፋት ቢገረፍ ሕይወቱን ካዳንኩለት ቢቆስል ምንም አይደለም› የሚል ነበር፡፡ አይሁድም የግርፋቱን ጽናት አይተው ይሙት ማለታቸው እንደሚቀር ተስፋ አድርጎ ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት ከትናንት ምሽት ጀምሮ ታስሮ ሲንገላታ ያመሸውን ፣ በሐናና ቀያፋ ግቢ ውስጥ ሲደበደብና በጡጫ ሲመታ ያደረውን ጌታ በምሕረት የለሾቹ የሮም ወታደሮች እጅ እንዲገረፍ አሳልፎ ሠጠው፡፡

    የሮማውያን ግርፋት እንደ አይሁድ ግርፋት በጅራፍ ብቻ አይደለም፡፡ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊው አውሳብዮስ ዘቂሣርያ እንደገለጠው ጅራፉ በቆዳ ከተሠራ በኋላ በላዩ ላይ ስለታማ የሆኑ የብረት ኳሶች ፣ ሾለው የተሳሉ የአጥንት ስብርባሪዎች ይደረጉበታል፡፡ በዚህ አሰቃቂ የግርፋት መሣሪያና በጨካኞቹ ወታደሮች እጅ ወድቀው ሥቃዩን መቋቋም ተስኖአቸው የሞቱም ብዙዎች ናቸው፡፡ 

    በጅራፉ ላይ የተሠሩት የብረት ኳሶችና የአጥንት ስብርባሪዎች በሚገረፈው ሰውነት ላይ ሲያርፉ ሥጋውን እየነጩ የሚነሡ ስለሆኑ ጅራፉ በሰውነት ላይ ማረፉ ብቻ ሳይሆን ከሰውነት ላይ የሚነሣበትም ቅጽበት እጅግ ለመግለጽ የሚከብድ ሥቃይ የሚያደርስ ነው፡፡ የግርፋቱ መጠን በጨመረ ቁጥር የደም ሥሮችና አጥንቶች እስከሚታዩ ድረስ የሚጎዳ ፣ የጎድን አጥንቶችን መሰባበር ፣ ከፍተኛ የሆነ ውጪያዊና ውስጣዊ የደም መፍሰስ ፣ የሳንባ መጎዳት የሚያስከትል አሰቃቂ ሒደት ነው፡፡  

    በዚያች ቀን ጌታችንን ለመግረፍ የተመደቡት ወታደሮች እስራኤልን በብርሃን ዓምድ በሌሊት የመራቸውን አምላክ ፣ ሙሴና አሮንን በደመና ዓምድ ያነጋገራቸውን አምላክ በድንጋይ ዓምድ ላይ ለመግረፍ ዕርቃኑን አሰሩት፡፡ የካህናት አለቆችን ደስ ለማሰኘት ሲሉም በሙሉ ኃይላቸው በታላቅ ጭካኔ እጅግ ብዙ ግርፋትን አዘነቡበት፡፡ አንድ ገጣሚ እንዳለው በሙሴ አድሮ የፈጣሪን ክብር ለማየት የለመነው የሰው ልጅ ፈጣሪ በጊዜው ‹ጀርባዬን ታያለህ› ብሎ የገባለትን ቃል ቢፈጽምለትና ጀርባውን ቢያሳየው ግርፋትን አዘነበበት፡፡ (ዘጸ. ፴፫፥፳፫) በእርግጥም ቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ‹‹ከጲላጦስ ግርፋትን ይቀበልበት ዘንድ ጀርባን ፈጠረ›› እንዳለው አምላክ ሰው የሆነውና ጀርባን ለራሱ ያዘጋጀው ስለ ሁላችን ኃጢአትን ግርፋትን ሊቀበልበት ነበር፡፡

    የሮማውያን ግርፋት ቅዱስ ጳውሎስ እንደተገረፈው እንደ አይሁድ ግርፋት በመጠን ተወስኖ ‹አንድ ሲጎድል አርባ ግርፋት አምስት ጊዜ ገረፉኝ› እያለ የተገረፈው ሰው በሕይወት ተርፎ እያስታወሰ የሚናገረው ዓይነት ግርፋት አይደለም፡፡ (፪ቆሮ. ፲፩፥፳፬)
    ቤተ ክርስቲያናችን የጌታችን ግርፋት ስድስት ሺህ ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ጊዜ እንደሆነ ስታስተምር አምስት ሺህ ነው ፣ አራት ሺህ ነው የሚሉም አሉ፡፡ ይህን አሰቃቂ ግርፋት በሺህ ለሚቆጠር ጊዜ መገረፉን ግን ሁሉም ሊቃውንትና የታሪክ ሰዎች ተስማምተውበታል፡፡ ጌታችን እጅግ መገረፉን የሚያሳየን መስቀሉን ባሸከሙት ጊዜ በየሥፍራው እስኪወድቅ ድረስ አቅም ማጣቱ ነው፡፡

    የጌታን ግርፋቱንስ መቁጠር ቢቻልም እንኳን ሥቃዩን ግን እንዴት ልንቆጥረው እንችላለን? ቤተ ክርስቲያናችን ከሥጋው አልፎ አጥንቶቹ እስከሚታዩ ድረስ ስለ ተገረፈው አምላክ በዕለተ ዓርብ የምታነበውና የምታዜመው ራሱ ክርስቶስ አስቀድሞ በነቢዩ ዳዊት አድሮ ስለሕማሙ የተናገረው የትንቢት ቃል  የሥቃዩ መጠን ጥቂትም ቢሆን ለማሰብ ያግዘናል፡-

‹‹እንደ ውኃ ፈሰስሁ … አጥንቶቼም ሁሉ ተለያዩ ፤
ልቤ እንደ ሰም ሆነ  …. በአንጀቴም መካከል ቀለጠ…
አጥንቶቼ ሁሉ ተቈጠሩ …  እነርሱም አዩኝ ተመለከቱኝም …
አጥንቶቼ ተነዋወጡ››
                            (መዝ. ፳፪፥፲፬፣፲፯፤፴፩፥፲)

    ቅዳሴያችን እንዲህ ይላል ‹‹የወልድን መከራውን የሚናገር ምን ዓይነት አፍ ነው? ምን ዓይነት ከንፈር ነው? ምን ዓይነት አንደበት ነው? የፍቅር ጌታ ሕማማቱ በተነገረ ጊዜ ልብ ይለያል ፤ ሕሊናም ይመታል ፤ ነፍስም ትንቀጠቀጣለች ፤ ሥጋም ይደክማል›› በእውነትም የጌታችንን ሥቃይ ለመግለጽ ምንም ዓይነት ቋንቋ ፣ ምንም ያህል ቅኔ አቅም አይኖረውም፡፡

    ቅዱስ ኤፍሬምም :-
     ‹‹በክርስቶስ የተወደዳችሁ ሆይ ኑ! ወዲህ ቅረቡ ፤ በዚች ዕለት በዳዊት ከተማ የሆነውን አብረን እንይ! በተስፋው ቃል ሲጠበቁ የነበሩት የተመረጡት የአብርሃም ዘሮች ዛሬ ምን እንዳደረጉ እንመልከት! ጌታ ሆይ ረዥሙን ሥቃይህን ማን ሊገልጸው ይችላል?›› ይላል፡፡

    ይህ ሁሉ የሆነው ስለ እኛ ኃጢአት ነበር፡፡ ኦሪት የሚገረፍ ሰው ‹‹የግርፋቱም ቊጥር እንደ ኃጢአቱ መጠን ይሁን›› ትላለች፡፡ (ዘዳ.፳፭፥፪) ጌታችን ማንም ስለ ኃጢአቱ ሊወቅሰው የማይችል ንጹሕ ቢሆንም ‹‹እግዚአብሔር የሁላችንን በደል በእርሱ ላይ አኖረ›› ስለተባለ ግርፋቱም በተሸከመው የእኛ ኃጢአት መጠን ሆነ፡፡

    ‹‹እርሱ ስለመተላለፋችን ቈሰለ ፣ ስለ በደላችንም ደቀቀ ፤ የደኅንነታችንም ተግሣፅ በእርሱ ላይ ነበረ›› በአጋንንት እጅ ልትገረፍ የጸጋ ልብስዋን አውልቃ ዕርቃንዋን በሲኦል የወደቀች ነፍሳችንን ነጻ ያወጣት ዘንድ እርሱ በጨካኝ ወታደሮች እጅ ዕርቃኑን ተገረፈ፡፡

    ‹‹እኛን ከሚገባን ግርፋት ያድነን ዘንድ ኢየሱስ የማይገባውን ግርፋት ተገረፈ›› ‹‹የተገረፈባቸውም አለንጋና ገመድ በደም ታለሉ (ተነከሩ) ፤ ከግርፋቱ ጽናት የተነሣ ሥጋው ሁሉ አለቀ››  ሐዋርያው ጴጥሮስ ‹‹በመገረፉ ቊስል ተፈወሳችሁ›› በማለት እንደተናገረ ‹‹በእርሱም ቊስል እኛ ተፈወስን›› (፩ጴጥ. ፪፥፳፬፤ኢሳ. ፶፫፥፭) 

("ሕማማት" ከተሰኘው የዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ ባለ 528 ገጽ መጽሐፍ ጥቂት ገጾች ተወስዶ ለመድኃኔ ዓለም ለበዓለ ስቅለቱ የዘነጋነውን መከራውን ለማስታወስ የተለጠፈ)
@Egizhaberanidinew
@Egizhaberanidinew
@Egizhaberanidinew
+  በርባን ይፈታልን +

ሕዝቡ ‹በርባን ይፈታልን! ክርስቶስ ግን ይሰቀል!› ማለታቸውን ስንሰማ መቼም ሁላችንም ማዘናችንና ‹ምን ዓይነት ክፉዎች ናቸው?!› ብለን መውቀሳችን አይቀርም፡፡ ወዳጄ ሆይ! እባክህን እስቲ አይሁድንና ጲላጦስ ለአፍታ እንተዋቸው! አንተ ብትሆን ኖሮ ከጌታና ከበርባን ማናቸውን ትፈታለህ? የእስክንድርያው ትምህርት ቤት ዲን የነበረው ሊቅ ‹‹በሥጋው ክፉ ነገርን የሚሠራ ሁሉ በርባንን ፈትቶ ክርስቶስን አሰረው ፤ መልካም ነገርን የሚያደርግ ደግሞ ክርስቶስን ፈትቶ በርባንን አስሮታል›› ይላል፡፡

ወዳጄ ሆይ! አንተ በሰውነትህ ላይ ፈትተህ የለቀቅከው ማንን ነው? በርባንን ነው ወይንስ ጌታን ነው? በርባንን ፈትተኸው ከሆነ ዛሬውኑ በንስሓ ተመልሰህ ፈጣሪህን በሰውነትህ ውስጥ አክብረው፡፡ ‹በርባንን የፈታሁት እኮ ወድጄ አይደለም! ሁኔታዎች አስገድደውኝ ነው› ብለህ እንደ ጲላጦስ ለራስህ ይቅርታ ማድረግና እጅህን መታጠብ አይበጅህም፡፡ ይልቅስ አሁኑኑ ጌታህን ፈትተህ በርባንን የተባለ ኃጢአትን ስቀለው! ያን ጊዜ የክርስቶስ መሆንህ ይታወቃል፡፡ ‹‹የክርስቶስ ኢየሱስ የሆኑቱ ሥጋን ከክፉ መሻቱና ምኞቱ ጋር ሰቀሉ›› ተብሎ ተጽፎአልና፡፡ (ገላ. ፭፥፳፬)  

ሕዝቡ ‹በርባን ይፈታ› ብለው ቢጮኹም ሁሉም ለበርባን ፍቅር አላቸው ማለት አይደለም፡፡ ሊቃነ ካህናቱ ባያባብሏቸው ኖሮ በዚያች ዕለት ሊያስፈቱት የሚፈልጉት ሌላ እስረኛ ዘመድ ያላቸውም ሰዎች መኖራቸው አይቀሬ ነው፡፡ ሆኖም ሊቃነ ካህናቱ ለጌታችን ካላቸው ጥላቻ የተነሣ ሕዝቡን ተለማምጠው በርባን እንዲፈታ አስደረጉ፡፡ ዛሬ በርባንን አግኝተን ‹በርባን ሆይ ማን ነው ያስፈታህ?› ብለን ብንጠይቀው ምናልባትም ‹የሰው መውደድ ይሥጥ ማለት ነው! የሚወደኝ ሕዝብ ነዋ ጮኾ ያስፈታኝ!› ማለቱ የማይቀር ነው፡፡ ሆኖም ሊቃነ ካህናቱና ተከታዮቻቸው ግን ‹በርባን ይፈታ› ብለው የጮኹት ለበርባን ፍቅር ኖሯቸው ሳይሆን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ በነበራቸው ጥላቻ ምክንያት ነው፡፡ ስለዚህ በርባንን ከሞት ፍርድ አድኖ ያስፈታው ሕዝቡ ሳይሆን ጌታችን ነበር፡፡

ጌታችን በዚያች ዕለት የበርባንን ሞት ወስዶ የእርሱን ሕይወት ለበርባን ሠጠው ፤ የበርባንን ሰንሰለት አስፈትቶ እርሱ ታሰረ ፤ ከበርባን ጓደኞች ጋር በርባን ሊሰቀል በነበረበት ቦታም ተሰቀለ፡፡ ወዳጄ ሆይ! ልብ ብለህ ከተረዳኸው በርባን እኮ አንተው ነህ! ለበርባን ከተደረገለት ለአንተ ያልተደረገ ነገር ካለ እስቲ ንገረኝ! እንደ በርባን ክርስቶስ ሞትህን ወስዶ ሕይወቱን ፣ እስራትህን ወስዶ ነጻነትን አልሠጠህምን?
ይህንን ያደረገውም ለአንተ ብቻ ሳይሆን ለአዳም ልጅ ሁሉ ነው ፡- ‹‹የእስረኛው በርባን (ወልደ አባ) መፈታቱ አምላካዊ ምሥጢርን የሚያስታውስ ነው፡፡ በኃጢአቱ ምክንያት በሲኦል ውስጥ ታሥሮ የነበረው አዳምን በአዳኙ መሰቀል ምክንያት መድኃኒት አግኝቶ ነጻ መውጣቱን ያስታውሳል›› / ‹‹እስመ ተፈትሕዎቱ ለወልደ አባ ሙቁሕ ያዜክር ምሥጢራተ አምላካዊ ያሌቡ ግዕዛነ አዳም ዘኮነ ሙቁሐ ውስተ ሲኦል በእንተ ኃጢአቱ ወረከበ መድኃኒተ በስቅለተ መድኅን›› እንዲል፡፡ 

በዚያች የዕለተ ዓርብ ረፋድ ላይ ያስፈታውን የማያውቀው ይህ ወንበዴ ሰንሰለቱ ተፈትቶ ወደ ቤቱ ሲሔድ ጌታችን ግን ለመከራና ለመስቀል ተሠጠ፡፡ እውነቱንስ ለመናገር እኛ ክርስቲያኖች በርባን በመፈታቱ ላይ ላዩን ብናዝንም ውስጥ ውስጡን ግን ደስ ብሎናል!

‹‹…በርባን ቢሰቀል ኢየሱስ ቀርቶ
ምን ይጠቅመናል ሽፍታ ሞቶ
እንኳን ኢየሱስን ሰቀሉት
የሞቱን መድኃኒት …››
ብለው መሪጌታ ፍቅሩ ሣህሉ በበገናቸው ጨርሰውታል፡፡

(ሕማማት ከሚለው መጽሐፍ ለመድኃኔ ዓለም የስቅለቱ መታሰቢያ የተወሰደ)
ቀዳም ሥዑር (የተሻረች ቅዳሜ)

#ቀዳም_ሥዑር ይባላል፡-
በዚች ዕለች ከድሮው በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል የተሻረችው ቅዳሜ ትባላለች፡፡ የማትጾመዋ ቅዳሜ ስለምትጾም ስዑር /የተሻረች/ ተብላለች በዓል መሻርን አይመለከትም በቀዳም ሥዑር ሌሊት ሥርዓቱ የሚጀመረው በመኀልየ ሰሎሞን ምንባብ ነው፡፡ ማኀሌቱም እዝሉ እየተቃኘ እየተመጠነ፣ እየተዘመመ እየተመረገደ እየተጸፋ ያድራል፡፡ ጥዋት አቡን መዋሥዕት ውዳሴ ማርያም ዜማ ተደርሶ ወለመልአከ ሕይወትሰ ሰቀልዎ በሚለው ሰላም ይጠናቀቃል፡፡በዚህ ዕለት ልብሰ ተክህኖ የለበሱ ካህናትና ዲያቆናት ቄጤማ ተሸክመው ቃጭል ሲያቃጨሉ መታየታቸው ዕለተ ትንሣኤውን ለሚናፍቅ ምእመን ትልቅ ብስራት ነው፡፡

#ለምለም_ቅዳሜ ይባላል፡-
ካህናቱ ለምእመናን ለምለም ቀጤማ የሚያድሉበት ዕለት ስለሆነ በዚህ ተሰይሟል፡፡ ቀጤማውንም ምእመናን እስከ ትንሣኤ ሌሊት በራሳቸው ላይ ያስሩታል፡፡ በቀዳም ስዑር ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ቃጭል /ቃለዓዋዲ/ እየመቱ ገብረ ሰላመ በመስቀሉ ትንሣኤሁ አግሃደ የሚለውን ያሬዳዊ ዜማ በመዘመር፤ ጌታ በመስቀሉ ሰላምን እንደሰጠን እና ትንሣኤውንም እንደገለጠልን በማብሰር፤ ቄጤማውን ለምእመናን ይሰጣሉ፡፡ ምእመናኑም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውል ገጸ በረከት ያቀርባሉ፡፡ ቄጤማውንም በራሳቸው ያስራሉ፡፡ ይህም አይሁድ ጌታችንን እያሰቃዩ ሊሰቅሉት ባሉ ጊዜ የእሾህ አክሊል ጭንቅላቱ ላይ ያሠሩበትን ድርጊት የሚያስታውስ ነው፡፡

(የቀጤማው አመጣጥና ምስጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ምድር በማየ አይኅ /በጥፋት ውኃ/ በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሰረችው ቀጤማ ይዛ በመግባት ነው፡፡ ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች የኃጢአት ውኃ ጐደለ፣ የኃጢአት ውኃ ጠፋ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነጻነት ተሰበከ ታወጀ በማለት ካህናት ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበሥሩበታል፡፡)

#ቅዱስ_ቅዳሜ ይባላል፡-
ቅዱስ ቅዳሜ መባሉ ቅዱስ የሆነ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ በዚህ ቀን ከሥራው ሁሉ ያረፈበት ነው፡፡ በዘመነ ሐዲስ ደግሞ የማዳን ሥራውን ሁሉ ፈጽሞ በሥጋው በመቃብር ሲያርፍ፣ በነፍሱ ሲዖልን በርብሮ ባዶዋን አስቀርቷታል፡፡ በዚያ ለነበሩት ነፍሳትም የዘለዓለም ዕረፍትን ያወረሰበት ዕለት ስለሆነ ከሌሎቹ ዕለታት የተለየ ዕለት ለማለት ቅዱስ ቅዳሜ ተብሏል፡፡

ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ልጆች👇
                •➢ ሼር // SHARE

    
ሕያውን ከሙታን መካከል ስለ ምን ትፈልጋላችሁ? ተነሥቶአል እንጂ በዚኽ የለም (ሉቃ 24፡5) እንኳን አደረሳቹ መልካም የትንሣኤ በዓል ይሁንልን !!!
ጎንችሬ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ልጆች በአክራሪ እስልምና ተከታዬ እንዲህ የሚገደሉት
2024/10/04 23:17:55
Back to Top
HTML Embed Code: